የኒቂያ ጉባኤ
በአሏህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ እጅግ በጣም አዛኝ በሆነው፡፡
112፥3 «አልወለደም አልተወለደምም»፡፡ لَمْ يَلِدْ وَلَمْ يُولَدْ
ጥንት ላይ የነበሩ ነቢያት እንዲሁ ኢየሱስ እና ሐዋርያት አሓዳዊያን"Unitarian" የነበሩ ሲሆን ከሐዋርያት ኅልፈት በኃላ የተነሱ የቤተክርስቲያን አበው ደግሞ በሂደት "ክልዔታውያን"Binitarian" ነበሩ። ከክልዔታውያን አበው መካከል ጠርጡሊያኖስ"Tertullian" ስለ ወልድ ሲናገር እንዲህ ይለናል፦
"አብ አጠቃላይ ባሕርይ ነው፥ ነገር ግን ወልድ የአጠቃላዩ መገኘት እና ክፍል ነው"
(Against Praxeas (Tertullian), Chapter 9).
አንድ ሰው ሰውነቱ ከራሱ ጋር ኖሮ ኖሮ ልክ ሲወልድ አባት እንደሚባለው አንድ አምላክ አምላክነቱ ከራሱ ጋር ኖሮ ኖሮ ልክ ሲወልድ አብ ተባለ የሚል ትምህርት ያስተማረው ጠርጡሊያኖስ ዘካርቴጅ ነው፦
"ምክንያቱም አምላክ እንዲሁ አብ ነው፥ እንዲሁ ደግሞ እርሱ ፈራጅ ነው። ሁልጊዜም አምላክ በሆነው መሠረት ላይ ብቻ እርሱ ግን ሁልጊዜ አብ እና ፈራጅ አልነበረም፥ ከወልድ በፊት አብ ሊሆን አይችልም፤ እንዲሁ ከኃጢአት በፊት ፈራጅ ሊሆን አይችልም። ነገር ግን በእርሱ ዘንድ ኃጢአት ባልነበረበት እና እንዲሁ ወልድ ባልነበረበት ወቅት ጊዜ ነበር፥ የመጀመሪያው ጌታ ፈራጅ ሆኖ እና የኃለኛ አብ ሆኖ መመሥረት ነበር። በዚህ መንገድ እርሱ ጌታ ሊሆን ከነበረባቸው ነገሮች በፊት ጌታ አልነበረም፥ ነገር ግን እርሱ ግን ወደፊት በሆነ ጊዜ ብቻ ጌታ ሊሆን ነበር። ልክ እንደዚሁ እርሱ በወልድ አብ እንደ ሆነ በኃጢአትም ፈራጅ ሆነ።
Against Hermogenes (Tertullian) chapter 3
ተመልከቱ! አብ ያለ አባትነት ከፍጥረት በፊት ወልድን እስከሚወልድበት ጊዜ ብቻውን በአምላክነት ነበር የሚለው እሳቤ የጠርጡሊያኖስ እሳቤ ነው፦
"ከፍጥረት በፊት እስከ ወልድ ውልደት ነበረ፥ ከሁሉ ነገር በፊት አምላክ ብቻውን ነበረ"።
Against Praxeas (Tertullian) Chapter 5.
በዚህ ወቅት የትርጓሜ ትምህርት ቤት"School of Thought" በእስክንድሪያ እና በአንጾኪያ ነበር፥ የእስክንድሪያን ትምህርት ቤት በአፍላጦን"Plato" ፍልስፍና ሰርጎገብ መሠረት ያረገ ሲሆን የአንጾኪያው ትምህርት ቤት ደግሞ በአሪስጣጣሊስ"Aristotle" ፍልስፍና መሠረት ያረገ ነው። በእስክንድሪያ ትምህርት ቤት ይማር የነበረው አትናቴዎስ ዘእስክንድሪያ "ከአምላክ አምላክ ተወለደ" የሚል አቋም ሲኖረው በአንጾኪያ ትምህርት ቤት ይማር የነበረው አርዮስ ዘሊቢያ "ከአምላክ አምላክ ተፈጠረ" የሚል አቋም ነበረው፥ አርዮስ ዘሊቢያ ስለ አቋሙ እንዲህ ይለናል፦
"አብ ወልድን ከወለደው የተወለደው መጀመሪያ ነበረው፥ ከዚህም ክስተት የተነሳ ልጁ ያልነበረበት ጊዜ እንደ ነበረ ግልጥ ነው። ስለዚህም እርሱ [ወልድ] ምንነቱ ካለመኖር እንደ ነበረው ነው"።
(Socrates of Constantinople, Church History, Book I, Ch. 5.)
በሁለቱ ውዝግብ የመጀመሪያው ዓለም ዓቀፍ ሲኖዶስ በኒቂያ ተካሄደ፥ "ሲኖዶስ" σύνοδος ማለት "ጉባኤ" "ስብሰባ"council" ማለት ነው። ኒቂያ፣ ቆስጠንጢኒያ፣ ኤፌሶን እና ኬልቄዶን በጥንት ጊዜ ቱርክ ውስጥ የሚገኙ ከተሞች ናቸው። በ325 ድኅረ ልደት በንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ሊቀ መንበርነት የኒቂያ ጉባኤ ላይ 318 ኤጲጵ ቆጶሳት ከመላው ዓለም ተሰብስበው "ሆሙኡሲዮስ" እና "ሆሞኡሲዮስ" የሚባሉ ክርክሮችን ለመታደም መጡ፥ "ሆሙኡሲዮስ" ὅμοιοιούσιος የአርዮስ አቋም ሲሆን "ሆሞኡሲዮስ" ὁμόιοιούσιος ደግሞ የአትናቴዎስ አቋም ነው።
"ኡሲያ" οὐσία የሚለው ቃል "ኤይሚ" εἰμί ማለትም "ነኝ" ከሚል አያያዥ ግሥ የተገኘ ሲሆን "ህላዌ" "ሃልዎት" "ኑባሬ" የሚል ትርጉም አለው፥ "ሆሙስ" ὅμοιος ማለት "የተለያየ" ማለት ሲሆን "ሆሞስ" ὁμός ማለት ደግሞ "ተመሳሳይ" ማለት ነው።
፨አርዮስ፦ "ወልድ ፍጡር ነው፥ አንዱ አምላክ አብ እና ኢየሱስ "ሆሙኡሲዮስ" ὅμοιοιούσιος ማለትም "የተለያየ ህላዌ" እንጂ ተመሳሳይ አይደለም" በማለት ኢየሱስ "ሆሙኡሲዮን ቶ ፓትሪ" ὅμοούσιον τῷ Πατρί ማለት "ከአብ ጋር የተለያየ ህላዌ ነው" የሚል አቋም ነበረው።
፨አትናቴዎስ፦ "ወልድ ፍጡር አይደለም፥ አንዱ አምላክ አብ እና ኢየሱስ "ሆሞኡሲዮስ" ὁμόιοιούσιος ማለትም "ተመሳሳይ ህላዌ" እንጂ የተለያየ አይደለም" በማለት ኢየሱስ "ሆሞኡሲዮን ቶ ፓትሪ" ὁμόούσιον τῷ Πατρί ማለት "ከአብ ጋር ተመሳሳይ ህላዌ ነው" የሚል አቋም ነበረው።