ru
Feedback
የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

Открыть в Telegram

ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።

Больше
2 640
Подписчики
+124 часа
+47 дней
+6130 день
Архив постов
🔴 ስንክሳር #የካቲት_9 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የካቲት ዘጠኝ በዚህች ዕለት #የአቡነ_እስትንፋሰ_ክርስቶስ የመነኮሱበት በዓል ነው፣ የከበረ በሶርያ አገር ላሉ መነኰሳት አባት የሆነ ታላቁ #አባ_በርሱማ አረፈ፣ የከበረ #ቅዱስ_ጳውሎስ_ሶርያዊ በሰማዕትነት ሞተ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_እስትፋሰ_ክርስቶስ የካቲት ዘጠኝ በዚህች ዕለት የአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ የመነኮሱበት በዓል ነው፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ አባታቸው መልአከ ምክሩ እናታቸው ወለተ ማርያም ይባላሉ፡፡ የተወለዱበት ልዩ ቦታው ወሎ ክፍለ ሀገር ዳውንት ነው፡፡ በተወለዱ ዕለት ተነሥተው በእግራቸው ቆመው ሦስት ጊዜ ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ብለው ፈጣሪያቸውን አመስግነዋል፡፡ የስማቸው ትርጓሜ የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ እስትንፋስ አንድም የክርስቶስ እስትንፋስ ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል እየጠበቃቸውና በመንገዳቸው ሁሉ እየመራቸው ነው ያደጉት፡፡ መንፈስ ቅዱስ ልቡናቸውን ብሩህ አድርጎላቸው በ5 ዓመታቸው የቅዱሳት መጻሕፍት ቃላትን፣ ብሉያትንና ሐዲሳትን፣ ድርሳናትንም ጠንቅቀው ዐውቀዋል፡፡ በተወለዱ በ14 ዓመታቸው ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ደብረ ሐይቅ ገዳም ሄደው ከባሕር ዳር ቆመው የሙሴን ጸሎት ወደ እግዚአብሔር በጸለዩ ጊዜ የታዘዘ መልአክ መጥቶ ባሕሩን አሻግሯቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተዋል፡፡ ለ3 ዓመታት ያህል በኃይቅ ገዳም ለመነኮሳት እንጨት በመልቀምና ውሃን በመቅዳት ለአባቶች መነኮሳት ምግብ የሚሆናቸው ዓሣ ከባህር ውስጥ በማውጣት አገልግለዋል፡፡ አባታችን እስትንፋሰ ክርስቶስ 40 መዓልትና 40 ሌሊት ከጾሙ በኋላ ምንም እህል ሳይቀምሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ ለሙሴ በደብረ ሲና እንደሰጠው ለአባታችንም ወደ እርሳቸው መጥቶ ዓሥሩን ቃላተ ኦሪትና ስድስቱን ቃላተ ወንጌል በውስጣቸው የተጻፈባቸው ሁለት ጽላቶችን ሰጥቷቸዋል፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ከሠሩ በኋላ ዕለቱን ስንዴ ዘርተው፣ ወይን ተክለው፣ ጽድን ወይራንና ግራርን ተክለው በአንዲት ቀን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ዕለቱን አድርሰዋል፡፡ ስንዴውን ለመሥዋዕት ወይኑን ለቍርባን በተአምራት አድርሰዋል፡፡ አባታችን በጸሎት ላይ እንዳሉ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተልኮ መጥቶ አባታችንን በደመና ጭኖ ወስዶ ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ፊት አቆማቸው፡፡ ጌታንም በቅዱሳኑ ሁሉ እንዲባረኩ ካደረጋቸው በኋላ መልአኩን ‹‹ወደ ተወለድኩባትና ወደ ኖርኩባት ቦታ ወደ ኢየሩሳሌም አድርሰው›› ብሎት ኢየሩሳሌምን አሳልሞ ሀገራችን መልሶ አምጥቷቸዋል፡፡ አባታችን ሁሉንም የኢትዮጵያን ቅዱሳት ገዳማትን ተዘዋውሮ ሲጎበኙ በሕይወተ ሥጋ የሌሉት የየገዳማቱ ቅዱሳን ሁሉ በአካል ይገለጡላቸው ነበር፡፡ ጎጃም ውስጥ እያስተማሩ፣ እያጠመቁ፣ የታመሙትን እየፈወሱ፣ የዕውራንን ዐይን እያበሩና ሙታንን እያሥነሱ ብዙ ካገለገሉ በኋላ ለዘጠኝ ዓመታት በባሕር ውስጥ ገብተው ቁልቁል ተዘቅዝቀው ለኢትዮጵያ ጸልየው የምሕረት ቃልኪዳን ተቀብለዋል፡፡ ከዘጠኝ ዓመት በኋላ ጌታችን መጥቶ ‹‹ከመነኮሳት ሁሉ ብልጫ ያለህ ወዳጄ ሆይ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ምሬልሃለሁ ከዚህች ባሕር ውጣ›› በማለት በሞት የሚያርፉበትን ቦታ ነግሯቸዋል፡፡ ጻድቁ ወደ ደብረ አሰጋጅ በሚሄዱበት ጊዜ ጸሐይ ልትገባ ስትል ‹‹በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አውግዤሻለሁ ለመስፍን ኢያሱ በገባኦን እንደቆምሽ አሁንም ቀጥ ብለሽ ቁሚ›› ብለው ገዝተው ፀሐይን አቁመዋል፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስም ደብረ አሰጋጅ ሲደርሱ ፀሐይ አፍ አውጥታ ‹‹አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ እገባ ዘንድ ፍታኝ›› ስትላቸው ‹‹እግዚአብሔር ይፍታሽ›› ባሏት ጊዜ ጠልቃለች፡፡ ጻድቁ ሌላው በእጅጉ የሚታወቁበት አንድ ትልቅ ቃል ኪዳን አላቸው፡፡ በአምላክ ልቡና የሚገኝ፣ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ልቡና የሚገኝ፣ በቅዱስ ሚካኤልና በቅዱስ ገብርኤል ልቡና የሚገኝ እንደ መልክአ መድኃኔዓለም ያለች እጅግ አስገራሚ ጸሎት አለቻቸው፤ እርሷን ጸሎት በጸለዩ ጊዜ እልፍ ነፍሳትን ከሲኦል ያወጣሉ፡፡ ጸሎቷም የመድኃኔዓለምን የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች እያንዳንዱ የሰውነት ክፍሎቹ የተቀበሉትን ጸዋትዎ መከራዎች ሁሉ ታዘክራለች፡፡ በእያንዳንዱ ክፍልም የጸሎት ማሳረጊያ አቡነ ዘበሰማያት ይደግማሉ፡፡ ንስሓ የገባ ኃጢአተኛ ሰው እንኳን ቢሆን ይህችን የአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስን ጸሎት በጸለየ ጊዜ ሺህ ነፍሳትን ከሲኦል እንደሚያወጣ ጌታችን በማይታበል ቃሉ ለአባታችን ነግሯቸዋል፡፡ እያንዳንዱን የመድኃኔዓለምን የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች መከራዎቹን የምታዘክረውን ይህቺን በአምላክ ልቡና ያለች ግሩም የሆነች ጸሎት ነፍሳትን ከሲኦል አታወጣም ብሎ የሚጠራጠር ቢኖር መንግስተ ሰማያትን አያያትም፡፡ ጻድቁ ታኅሣሥ 8 ቀን ተወልው ሚያዝያ 9 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል በዚህች ዕለትም የምንኩስናቸው በዓል ይከበራል፡፡ ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት እና #ከገድላት_አንደበት) https://t.me/finotebirhan12

🔴 ስንክሳር #የካቲት_8 የካቲት ስምንት በዚህች ዕለት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ከከበረ ልደቱ ከአርባ ቀኖች በኋላ ወደቤተ መቅደስ የገባበት ሆነ፣ የከበረች እመቤት #አመተ_ክርስቶስ አረፈች፣ ከአሴር ወገን የሆነች የፋኑኤል ልጅ #ነቢዪት_ሐና አረፈች፣ በትሩፋቱ ፍጹም የሆነ ታላቅ አረጋዊ የገዳመ ሲሐቱ #ቅዱስ_ኤልያስ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅድስት_አመተ_ክርስቶስ በዚህችም ቀን የከበረች እመቤት አመተ ክርስቶስ አረፈች ሁለቱም አገልጋዮቿ። ይችም ቅድስት ከቍስጥንጥንያ አገር ሰዎች ውስጥ ናት ከንጉሥ መሳፍንቶችም ባል ነበራት እርሱም በጐልማሳነቱ ሙቶ ዕድሜዋ ዐሥራ ሁለት ዓመት ሲሆናት ፈት አረጋት። ከጥቂትም ቀን በኋላ ከመንግሥት ታላላቆች ከሆኑት ውስጥ አንድ ሰው በኃይል ወስዶ ሊአገባት ፈለገ እርሷም ጽኑ ደዌ አለብኝ እስከምድን ጠብቀኝ አለችውና ከዚህ በኋላ ገንዘቧን ሁሉ ለድኆችና ለችግረኞች በተነች ወንዶችና ሴቶች ባሮቿን ነጻ አወጣች ሁለት ሴቶች ባሮቿንም ከእርሷ ጋር ይዛ ማንም ሳያያት በሌሊት ወጣች ከኰረብታ በታች ጥልቅ ከሆነ ቦታ ውስጥ ወዳለ ዋሻ ገብታ በዚያ ዐሥራ አንድ ዓመት ኖረች በየዕለቱም ከዕፀዋት ፍሬ አዕዋፍ እያመጡላት ከአገልጋዮቿ ጋር ትመገባለች። ከዚህም በኋላ በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ዘመን ከጸሐፊዎች አንዱ እንዲህ አለ ግብር እሰበስብ ዘንድ ወደ ምሥራቅ አቅጣጫ ሔድኩ ወደ አንድ ገዳምም ደረስኩ መነኰሳቱና አበ ምኔቱም ተቀበሉኝ እርስበርሳችንም እጅ ተነሣሥተን ተቀመጥን ከዚያ በየአይነቱ ፍሬ ያላቸው ዛፎች አሉ አዕዋፍም ቅርንጫፉን ከፍሬው ጋር እየቆረጡ ይበራሉ እነርሱ ራሳቸው አይበሉም። እኔም አይቼ አደነቅሁ መነኰሳቱንም ይህ ሥራ ምንድን ነው አልኳቸው እነርሱም እንዲህ ሲያደርጉ ዐሥራ አንድ ዓመት ነው የሚሆነውን ግን አናውቅም አሉኝ እኔስ በተራራ ውስጥ ለሚኖር መነኰሳት የሚወስዱ ይመስለኛል አልኳቸው። ይህንንም ስናገር ቊራ መጥቶ ቅርንጫፍን ቆርጦ ከፍሬው ጋር ይዞ በረረ ሥራውን አውቅ ዘንድ ከአበ ምኔቱ ጋር ተከተልኩት የሚገባበትንም አየን ወደዚያም ቦታ ደርሰን ደንጋይ ጣልን ክርስቲያኖች ከሆናችሁ አትግደሉን የሚል ቃልን ሰማን እናንተ ከወዴት ናችሁ አልናቸው እኛን ለማየት ከፈለጋችሁ ራቁታችንን ስለሆን ሦስት ልብሶችን ጣሉልን አሉን እኛም ልብሶችን ጣልንላቸውና ወደርሳቸው ጭንቅ በሆነች መንገድ ወረድን በደረስንም ጊዜ ተቀበሉን እርስበርሳችንም እጅ ተነሣሥተን አንዲቱ ከእኛ ጋር ተቀመጠች ሁለቱ ግን በፊቷ ቆሙ። አበ ምኔቱም እናቴና እመቤቴ ሆይ ከወዴት ነሽ ወደዚህስ አወጣጥሽ እንዴት ነው አላት እርሷም ሥራዋን ሁሉ ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው ነገረችው አበ ምኔቱም የምትፈቅጂ ከሆነ ከገዳም ምግብ እናምጣላችሁና ከእናንተ ጋር በአንድነት እንመገብ አላት። እርሷም ወደዚህ ከመጣን ቅዱስ ቁርባንን አልተቀበልንምና የክርስቶስን ሥጋና ደም አምጥቶ እንዲአቀብለን ቄስን እዘዝልን አለችው። አበ ምኔቱም ቄስን አዘዘላቸውና አቈረባቸው በማግሥቱም አመተ ክርስቶስ ረጅም ጸሎትን ጸለየችና አረፈች አገልጋዮቿም ተከታትለው አረፉ በዝማሬና በማኅሌት ገንዘው በክብር ቀበሩአቸው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት) https://t.me/finotebirhan12

እደምን አመሻችሁ ነገ የካቲት 8ጸሎቱ ይቀጥላል 11ሰአት ስለሚጀመር ቀደም ብለን እንገኝ ከጸሎቱ በኋላ ወረብ ጥናት ይኖራል ስለሆነ በጸሎቱ ሰአት ቀደም ብለን እንገኝ ሠላመ እግዚአብሔር አይለየን ፆሙን የበረከትእና የድኅነት ፆም ያድርግልን።

🔴 ስንክሳር #የካቲት_7 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የእስክንድርያ ሀገር አርባ ሦስተኛ ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት #ቅዱስ_እለእስክንድሮስ አረፈ፣ የእስክንድርያ አርባ አምስተኛ ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት #ቅዱስ_ቴዎድሮስ አረፈ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_እለ_እስክንድሮስ_ሊቀ_ዻዻሳት የካቲት ሰባት በዚህች ቀን የእስክንድርያ ሀገር ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት እለእስክንድሮስ አረፈ፡፡ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት አርባ ሦስተኛ ነው። ይህም አባት ታሮን በሚባል ገዳም መነኰሰ ትርጓሜውም የአባቶች ገዳም ማለት ነው በጌታችንም ፈቃድ በእስክንድርያ አገር ላይ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ እርሱ የተማረ አዋቂ ጻድቅ ሰው ነበረና። በሹመቱ ወራትም ብዙ መከራ ደረሰበት የግብጽ ንጉሥ ልጁን ሹሞ በመንግሥቱ ላይ አሠለጠነው እርሱም በአስቄጥስ በረሀ ያለውን የመነኰሳቱን ገዳማት አፈረሳቸው። ከክፋቱና ከክህደቱ ብዛት የተነሣ ከምስር በስተሰሜን ወዳለች ገዳም ገብቶ በዚያ አምላክን የወለደች የእመቤታችንን የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕሏን አየና ይች ምንድን ናት አለ እርሷም በሽልማት ሁሉ የተሸለመችና ያጌጠች ናት በልብሶቿም ላይ ያማረ የሐር ልብስ ነበረ ስዎችም የክርስቶስ እናት የሆነች የእመቤታችን የድንግል ማርያም ሥዕል ናት አሉት እርሱም ተሳድቦ የረከሰ ምራቁን በፊቷ ላይ ተፍቶ ደኅና ከሆንኩ ክርስቲያኖችን ፈጽሜ አጠፋቸዋለሁ አለ ዳግመኛም በክብር ባለቤት በጌታችን ክርስቶስ ላይ የስድብ ቃልን ተናገረ። ሌሊትም በሆነ ጊዜ የሚያስፈራና የሚያስደነግጥ ታላቅ ራእይን አየ በነጋም ጊዜ ለአባቱ እንዲህ ብሎ ነገረው ዛሬ በዚች ሌሊት ታላቅ መከራና ብዙ ቅጣት ደረሰብኝ ታላቅ ዙፋንንም አየሁ በላዩ የተቀመጠበት ሰው እጅግ የሚያስፈራ የሚያስደነግጥ ነው ፊቱም ከፀሐይ ይበራል የብዙ ብዙ የሆኑ ሠራዊት የጦር መሣሪያ ይዘው በዙሪያው ቁመው ነበር እኔና አንተም እሥረኞች ሁነን በኋላው ቁመን ነበር እኔም በዙፋን ላይ የተቀመጠው ማነው ብዬ ጠየቅሁ ትላንት አንተ የዘበትክበት የክርስቲያን ንጉሥ ክርስቶስ ይህ ነው አሉኝ ከዚህም በኋላ የጦር መሣሪያ ከተሸከሙት አንዱ ወደ እኔ መጥቶ ጐኔን በጦር ወጋኝ ጦሩንም ከጐኔ ውስጥ አላወጣውም። አባቱም ሰምቶ ደነገጠ እጅግም አዘነ ያ ልጁም ወዲያውኑ ታመመ አንደበቱም ተዘግቶ በክፉ አሟሟት ሞተ። ዳግመኛም ከአርባ ቀን በኋላ አባቱ ሞተ። በርሱም ፈንታ ሌላ ንጉሥ ተሾመ እርሱም ክርስቲያኖችን እጅግ አሠቃያቸው ይህንንም አባት ሊቀ ጳጳሳት እለእስክንድሮስን አብዝቶ አሠቃየው ከሕዝቡ ሦስት ሺህ የወርቅ ዲናር ለምኖ እስከ ሰጠው ድረስ ጌታችንም ይህን ንጉሥ ፈጥኖ አጠፋው። ከዚህም በኋላ አሁንም ሌላ ንጉሥ ተሾመ እርሱም ሊቀ ጳጳሳቱን ይዞ እንደ ቀድሞው ሦስት ሺህ የወርቅ ዲናር እንዲሰጠው ፈለገ እርሱም ከወገኖቼ እስከምለምን ታገሠኝ ብሎ ማለደው ንጉሡም ቀጠሮ ሰጠውና ይለምን ዘንድ ወደ ላይኛው ግብጽ ወጣ። በተራራ ላይ አንድ ገዳማዊ ሰው ነበር ከእርሱም ጋር ሁለት ደቀ መዛሙርት አሉ በተራራውም በአንድ ቦታ እንዲቆፍሩና እንዲጠርጉ አዘዛቸው ወርቅን የተመላ አምስት ማሰሮ አገኙ አንዱን ሸሽገው አራቱን ወደ ገዳማዊ መምህራቸው አመጡ እርሱም ይረዳበት ዘንድ እንዲስጡት ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ላካቸው። እነርሱ ግን እነዚያን የወርቅ ማሰሮዎች ይዘው ተመልሰው ወደ ዓለም ገቡ የምንኵስና ልብሳቸውንም ጥለው ሚስት አገቡ በዚያም ወርቅ ወንዶችና ሴቶች ባሮችን እንስሳትንም ገዙ። የዚያችም አገር አስተዳዳሪ ያዛቸው ገንዘብንም ከወዴት እንዳገኙ በመግረፍ መረመራቸው እነርሱም አምስት የወርቅ ማሰሮዎችን እንዳገኙ አመኑ መኰንኑም ለንጉሥ የጭፍራ አለቃ አሳልፎ ሰጣቸው እርሱም ወደ ንጉሥ አቀረባቸውና አምስት የወርቅ ማሰሮ እንዳገኙ አስረዳው ንጉሡም ጭፍሮቹን ልኮ የሊቀ ጳጳሳቱን ቤት በረበረ የአብያተ ክርስቲያናት ከሆነ ከንዋየ ቅድሳት ያገኘውን ሁሉ ወሰደ ሊቀ ጳጳሳቱንም አሠረውና ወርቅን የተመሉ አራቱን ማሰሮዎች ደግሞም ሦስቱን ሽህ የወርቅ ዲናር አምጣልኝ አለው እርሱም ከዚህ ከኃላፊው ዓለም ገንዘብ ምንም ምን የለኝም አለው ወደ ሕዝቡ ልኮ ሦስቱን ሽህ የወርቅ ዲናር አምጥተውለት እስከ ሰጠው ድረስ አልተወውም ይህንንም ክፉ ንጉሥ ጌታችን አጠፉው። ከዚህም በኋላ ከእርሱ የከፋ ሌላ ንጉሥ ተሾመ እርሱም የሐሰተኛውንና የርኵሱን ነቢይ ስም በከበረ መስቀል ፈንታ በእጆቻቸው ውስጥ እንዲአትሙ የክርስቲያንን ወገኖች አስገደዳቸው። ይችም ምልክት የመለኮትን ነገር የሚናገር ወንጌላዊ ዮሐንስ የተናገራት ትንቢት ናት ይህም ክፋ ንጉሥ ወደ ሀገሮች ሁሉ ይህን እንዲአደርጉ አዘዛቸው ሊቀ ጳጳሳቱንም እንዲሁ ያደርግ ዘንድ አዘዘው። ሊቀ ጳጳሳትም ይተወው ዘንድ ብዙ ለመነው አልተቀበለውም ዳግመኛም እስከ ሦስት ቀን ይታገሠው ዘንድ ለመነው ከዚህም በኋላ ደግሞ እንዳይጥለውና ወደዚህ ወደረከሰ ሥራ እንዳያስገባው ወደ እግዚአብሔር ፈጽሞ ማለደ ጌታችንም ልመናውን ተቀብሎ በጥቂት ደዌ ጐበኘው ወደ ቤቱ እስክንድርያ ይሔድ ዘንድ እንዲአዝዝለት ንጉሡን ለመነው። ንጉሡም ከለከለው ሰለ እጅ ኀትመት ምክንያት ለመፍጠር ሰለ መሰለው የእግዚአብሔርም መልአክ ተገለጠለትና ነገ ታርፋለህ አለው እርሱም አርድእቱን እግዚአብሔር ነገ ስለሚጐበኘኝ አርፋለሁና መርከብን አዘጋጁ አላቸው። አንዳለውም በማግሥቱ አረፈ ሥጋውንም በመርከብ ተሸክመው ወስደው ከአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሥጋ ጋር ቀበሩት። በዚህም አባት አለእስክንድሮስ ዘመን በግብጽ አገር ለሚኖሩ መለካውያን ስሙ አንስጣስዮስ የሚባል ሊቀ ጳጳሳት ነበራቸው ያዕቆባውያን ምእመናንን ይወዳቸዋል ስለዚህም ወገኖቹ መለካውያን ተጣሉት። እርሱም ነፍሱን ያድን ዘንድ አስቦ ወደዚህ አባት አለእስክንድሮስ መጥቶ ከሥልጣኑ በታች በመሆን የሚታዘዝ ሆነ እለእስክንድሮስም አንስጣስዮስን በእርሱ ፈንታ የሊቀ ጵጵስናውን ሥልጣን ይዞ መንጋውን ይመራ ዘንድ እርሱ ግን ከመነኰሳት እንዳንዱ ሁኖ በገዳም ይኖር ዘንድ እንዲተወው ለመነው። አባ አንስጣስዮስም አልወደደም እንዲህም አለ ይህን የምሻ ከሆነ አኔ እስከ ዛሬ ሊቀ ጳጳሳት አልነበርኩምን ላንተ ደቀ መዝሙርህ ሁኜ ላገለግልህ ወደድኩ እንጂ አለ። በመካከላቸው ከተደረገው ከብዙ ልመና ከብዙ ምልልስም በኋላ ኤጲስቆጶስ ይሆን ዘንድ አንስጣስዮስ ፈቀደ በአንዲትም ሀገር ላይ ኤጲስቆጶስነትን ሾመው። መንጋውንም እንደሚገባ በጎ አጠባበቅን ጠበቀ፡፡ አባት እለእስክንድሮስም በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበር የኖረው ሃያ አራት ዓመት ከስድስት ወር ነው እግዚአብሔርንም አገለገለው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት) https://t.me/finotebirhan12

🔴#እንኳን_ለጾመ_ነነዌ_በሰላም_አደረሳችሁ ======================= ጾመ ነነዌ የካቲት 7 ሰኞ ይጀመራል የዚህ ጾም ጊዜ ሦስት ( 3 ) ቀን ብቻ ነው ቀኖቹም በየዓመቱ ሰኞ ማክሰኞ ረቡዕ ናቸው። የነነዌ ጾም በቤተክርስቲያናችን የቀን አቆጣጠር ስሌት መሠረት ከፍ እና ዝቅ እያለ በየዓመቱ በጥርና በየካቲት ወር ይውላል። የቤተ ክርስቲያን አባቶች ይህን ጾም የወሰኑልን ልትጠፋ የነበረች ነነዌን በጾም ምክንያት እግዚአብሔር ይቅር ስላላት ይህን አምላካዊ ይቅርታውን ለዘለዓለም ለማሰብና ዛሬም በዚህ ዓለም ከነነዌ የከፋ ርኩሰትንና ኃጢአትን ስላለ የነነዌ ሕዝብ ይቅር ያልክ አምላክ ዛሬን ይቅር በለን ለማለት እንጾማለን። የነነዌ ህዝብን በምሕረቱ የጎበኘ ቸር አባታችን እግዚአብሔር ለሀገራችንም ለህዝባችንም ምሕረትና ቸርነቱን ያብዛልን ጾማችንን ጾመ ድኅነት፣ ጾመ ሥርየት፣ ሰይጣንን ድል መንሻ የኃጥአት መደምሰሻ ፣ መንግስተ ሰማያትን መውረሻ ያድርግልን #ወስብሐት_ለእግዚአብሔር #ፍኖተ_ብርሃን_ሰንበት_ት/ቤት https://t.me/finotebirhan12

#እንኳን_ለጾመ_ነነዌ_በሰላም_አደረሳችሁ ጾመ ነነዌ የካቲት 7 ሰኞ ይጀመራል #የዚህ ፆም ጊዜ ሶስት ( 3 ) ቀን ብቻ ነው ። ቀኖቹም በየዓመቱ ሰኞ ማክሰኞ ረቡዕ ናቸው ። የነነዌ ፆም በመባጃ ሐሙስ( አቆጣጠር ) ከፍ እና ዝቅ ስለሚል አንድ ጊዜ በጥር አንድ ጊዜ በየካቲት ይሆናል ። የቤተ ክርስቲያን አባቶች ይህን ፆም የወሰኑት ልትጠፋ የነበረች ነነዌን በፆም ምክንያት እግዚአብሔር ይቅር ስላላት ይህን አምላካዊ ይቅርታውን ለዘለዓለም ለማሰብና ዛሬም በዚህ ዓለም ከነነዌ የከፋ ርኩሰትንና ኃጢያትን ስላለ የነነዌ ሕዝብ ይቅር ያልክ አምላክ ዛሬን ይቅር በለን ለማለት ነው ። ++ የነነዌ ሰዎችም እግዚአብሔርን አመኑ ለፆም አዋጅ ነገሩ ከትልቁም ጀምሮ እስከ ትንሾቹም ማቅ ለበሱ ወሬውም ለነነዌ ንጉስ ደረሰ። እርሱም ከዙፋኑ ተነስቶ መጎናፀፊያውን አውልቆ ማቅንም ለበሰ። አመድ ላይም ተቀመጠ አዋጅንም አስነገረ። ++ በነነዌም ውስጥ የንጉሱንና የመኳንቱን ትእዛዝ አሳወጀ እንድህም አለ ሰዎችም እንስሶችም አንዳችም እንዳይቀምሱ አይሰማሩም ውኃንም አይጠጡ። ሰወችና እንስሳትም በማቅ ይከደኑ። ወደ እግዚአብሔርም በብርቱ ይጩሁ። ሰዎችም ሁሉ ከክፉ መንገዳቸውና በእጃቸው ካለው ግፍ ይመለሱ። እኛ እንዳንጠፋ እግዚአብሔር ተመልሶ ይፀፀት እንደሄነ ከፅኑ ቁጣውስ ይመለስ እንደሆነ ምን ያውቃል በማለትም አሳሳበ። ++ እግዚአብሔርም ከክፉ መንገዳቸውም እንደተመለሱ በስራቸውም አየ። እግዚአብሔር አምላክም ያደርግባቸው ዘንድ በተናገረው ክፉ ነገር ተፀፀቶ አላደረገውም ት ዮናስ ( ፫ ፤ ፭-፲ ) የነነዌ ህዝብን በምህረቱ የጎበኘ ቸር አባት ለሀገራችንም ለህዝባችንም ምህረትና ቸርነቱን ያብዛልን ፆሙን የበረከት ፆም ያድርግልን አሜን ፫ ለመንፈሳዊነት ቅድሚያ እንስጥና የእግዚአብሔርን ብድራት እንጠብቅ፡ እግዚአብሔር ጾማችንን ጾመ ድህነት ጾመ ስርየት ሰይጣንን ድል መንሻ ፣የኃጥያት መደምሰሻ ፣ መንግስተ ሰማያትን መውረሻ ያድርግልን ፆሙን የበረከት ፆም ያድርግልን #ወስብሐት ለእግዚአብሔር

🔴 ስንክሳር#የካቲት_6 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የካቲት ስድስት በዚህች ቀን ሊቀ ጳጳሳት የከበረ #አባት_ቅዱስ_አቡሊዲስ ሥጋው ከባሕር የወጣበት ነው፣ ጌታን ሽቱ ለቀባችው #ቅድስት_ማርያም_እንተ_ዕፍረት የዕረፍቷ መታሰቢያ ነው፣ የከበሩ #አቡቂርና_ዮሐንስ_ሦስት_ደናግልም_ከእናታቸው_ከአትናስያ ጋር በሰማዕትነት ሞቱ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅድስት_ማርያም_እንተ_ዕፍረት በዚህችም ቀን ጌታን ሽቱ ለቀባችው ማርያም የዕረፍቷ መታሰቢያ ነው። ይችም ቅድስት አስቀድማ ኑሮዋን በዝሙት ያሳለፈች ኃጢአተኛ ነበረች። እርሷም ጐልማሶችን ወደርሷ ትማርካቸው ዘንድ በየራሱ በሆነ ሽልማትና ጌጥ ትሸለም ነበር። በአንዲትም ዕለት እንደ ልማድዋ ተሸልማ አጊጣ ሽቱም ተቀብታ ፊቷን በመስታዋት ተመለከተች የጉንጯ ቅላትና ደም ግባቷ የዓይኗም ወገግታና ጥራት ማማሩን አይታ እያደነቀች አንድ ሰዓት ያህል ቆየች ከዚህም በኋላ በጎ ኀሳብ በላይዋ መጣ ሞትንና የዚህን ዓለም ማለፍ አሰበች። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስም ኃጢአተኞችን እንደሚቀበልና ኃጢኣትንም እንደሚአስተሰርይ ሰምታ ገንዘቧን ወስዳ የአልባስጥሮስን ሽቱ ገዝታ በስምዖን ዘለምጽ ቤት ለምሳ ተቀምጦ ሳለ ወደ ጌታችን ሔደች። ከእግሩ በታችም ሰግዳ ያንን ሽቱ ቀባችው እግሮቹን በዕንባዋ አጠበችውና በራስዋ ጠጉር ወለወለችው ጌታችንም የፍቅርዋን ጽናት አይቶ ኃጢኣቷን በደሏን ተወላት የመንግሥት ወንጌልም በሚሰበክበት ይህን ያደረገችውን እንዲአስቡ አዘዘ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት) https://t.me/finotebirhan12

🔴 ነገ ለባለ ትዳር አባላት በሙሉ የካቲት 6, 2014 ዓ.ም ከቀኑ 5:00 ጀምሮ የተዘጋጀ መርሐግብር
🔴 ነገ ለባለ ትዳር አባላት በሙሉ የካቲት 6, 2014 ዓ.ም ከቀኑ 5:00 ጀምሮ የተዘጋጀ መርሐግብር

🔴 ስንክሳር #የካቲት_5 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የካቲት አምስት በዚች ቀን የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት #ቅዱስ_አክርጵዮስ አረፈ፣ አባት ጴጥሮስ የተባለ #አባ_ብሶይ አረፈ፣ አስቀድሞ ራሱን ለኃጢአት አስገዝቶ የነበረ ጽኑዕ ተጋዳይ #አባ_ዕብሎይ አረፈ፣ ኢትዮጵያዊ የሆኑ ጻድቃን #አቡነ_አሞኒ የተወለዱበት ነው፡፡ =================== #አቡነ_አሞኒ በዚህችም እለት ኢትዮጵያዊ የሆኑ ጻድቃን አቡነ አሞኒ የተወለዱበት በዓልና ለልጃቸው አቡነ ዮሐኒም መታሰቢያቸው ነው፡፡ አባታችን የካቲት5 ቀን አክሱም ውስጥ ሲወለዱ ሰይጣናት የወላጆታቸውን ቤት ከበው በማየታቸው እንደተወለዱ በእጃቸው ቢያመለክቱ በአንድ ጊዜ 60 ሰይጣናት ተሸንፈው እንጢስ በነው ጠፍተዋል። አሞኒ ማለት አሸናፊ ማለት ነው። አባ አሞኒ የራስ ፀጉራቸው ልብስ መጎናጸፊያ ሆኖቸው የኖሩ ታላቅና ቀደምት አባት ናቸው። በደመና ተጭነው ኢየሩሳሌም ደብረ ዘይት ድረስ በመሄድ ከአባ ዕብሎይ ጋር ተገናኝተው ብዙ ምሥጢርን አውርተዋል። አባ ዮሐኒንያ ሳደጉት አስተምረው ያሳደጓቸው አባ አሞኒ ናቸው፡፡ የእናቱን ጡት ፈጽሞ ጠብቶ የማያውቀውን የመንፈስ ቅዱስ ልጃቸውን አባ ዮሐኒን እሳቸው እያጫወቱት የታዘዘ አሞራ በክንፎቹ እያለበሰው ቶራ (ሰሳ) እያጠባችው ነው ያደገው፡፡ አባ አሞኒ ልጃቸው አባ ዮሐኒ አድጎ 12 ዓመት ሲሆነው ከዚህም በኋላ ዲቁና ሊያሾሙትና አክሱም ጽዮን ወስደው ሊያስባርኩት ቤተ ካህናት ከተባለው ቦታ ይዘውት ሲሄዱ ልዩ ስሙ ሲሂታ ከሚባለው ቦታ ሲደርሱ ከወገባቸው በላይ እራቁታቸውን የሆኑ እንስራ የተሸከሙ ዐሥር ሴቶች አገኙ፡፡ አባ ዮሐኒም አባታቸውን "አባቴ እነዚህ ደረታቸው ላይ ቀንድ ያላቸው ጽጉራቸው የረዘመ ምንድን ናቸው? እንደ እኛ የሆኑ መስህታን የሚባሉት እነዚህ ናቸውን?" አሏቸው፡፡ አባ አሞኒም "አይደሉም ልጄ ዝም ብለህ ሂድ" አሏቸው፡፡ በኋላ ግን ትዝ ሲላቸው "በዱር እንስሳት ያሳደኩት ልጄ ወንድና ሴት ለይቶ ሲያውቅ በዚያው ሊሳሳት አይደልምን?" ብለው በማሰብ ዲቁናና ክህነቱ ይቅርበት ብለው ተመልሰው ወደ በዓታቸው ይዘውት ገቡ፡፡ ከዚህም በኋላ አባ አበይዶ ወደ አባ አሞኒ መጣና እሳቸውን ከአባ ዮሐኒ ጋር እያገለገሏቸው ተቀመጡ፡፡ ዮሐኒ እየጻፈ አበይዶ የሚጻፍበትን ቆዳ እያዘጋጁ ሦስቱም በአንድነት በተጋድሎ መቀመጥ ጀመሩ፡፡ አባ ዮሐኒ ሃያ ዓመት አባ አሞኒ ደግሞ አርባ ዓመት በሆናቸው ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለአባ አሞኒ ተገለጠላቸውና "አሞኒ ሆይ ከእንግዲህስ እግዚአብሔር ወደኔ ና ብሎሃል" አላቸው። እሳቸውም ልጆቻቸውን አባ ዮሐኒንና አባ አበይዶን ጠርተው "በሉ እንግዲህ እኔ ወደ እግዚአብሔር መሄዴ ነውና ጸልዩልኝ" አሏቸው፡፡ ከማረፋቸውም በፊት አባ ዮሐኒን ለብቻቸው ጠርተው "አንተ አባ ዮሐኒ ካሁን በፊት ሲሂታ ላይ ያየሃቸው ሴቶች ናቸው፣ አዳምንም ከገነት ያስወጡ ናቸው፡፡ ወደፊትም እንደ እነርሱ ያለ የደረሰብህ እንደሆነ ካለህበት ገደል ተወርውረህ ውደቅመ በባሕር ውስጥ ጥለቅ" ብለው ነግረዋቸው ዕለት ኅዳር5 ቀን በሰላም ዐረፉና ወደ ጠራቸው እግዚአብሔር ሄዱ፡፡ ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት እና #መዝገበ_ቅዱሳን) https://t.me/finotebirhan12

🔴 ለባለ ትዳር አባላት... እሑድ ለሚኖረን የባለትዳር ጉባኤ በእለቱ የንግድ ባንክ ሕንጻ ምርቃት ስለሚካሄድና መንገዶች ሊዘጉ ስለሚችሉ የጉባኤው ተሳታፊዎች በጊዜ አማራጭ መንገድ ተጠቅማችሁ በሰዓቱ
🔴 ለባለ ትዳር አባላት... እሑድ ለሚኖረን የባለትዳር ጉባኤ በእለቱ የንግድ ባንክ ሕንጻ ምርቃት ስለሚካሄድና መንገዶች ሊዘጉ ስለሚችሉ የጉባኤው ተሳታፊዎች በጊዜ አማራጭ መንገድ ተጠቅማችሁ በሰዓቱ እንድንገኝ ይሁን።

🔴 ስንክሳር#የካቲት_4 የካቲት አራት በዚህች ቀን ሉቃስ የሣላት ከጒንጯ ደም የሚፈስሳት ተአምር አድራጊዋ #የእመቤታችን_ሥዕል የምትታሰብበት በዓሏ ነው፣ ከሰባ ሁለቱ አርድእት አንዱ ሐዋርያ የከበረ #ቅዱስ_አጋቦስ በሰማዕትነት ሞተ፣ በምግባር ፍጹም የሆነ ተጋድሎውም የበዛ #አባ_ዘካርያስ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ተአምር_አድራጊዋ_የእመቤታችን_ሥዕል በዚህች ዕለት ሉቃስ የሣላት ከጒንጯ ደም የሚፈስሳት ተአምር አድራጊዋ የእመቤታችን ሥዕል የምትታሰብበት በዓሏ ነው። ይኸውም ከ829-842 ዓ.ም በቤዛንታይን የነገሠው ንጉሥ ቴዎፍሎስ በቅዱሳት ሥዕላት ላይ በክፋት ተነሳሥቶ ዐዋጅ በማወጁ ወታደሮቹ በርሱ ትእዛዝ በእያንዳንዱ ቤት እየዞሩ ቅዱሳት ሥዕላትን ለማጥፋት ፍተሻ ያደርጉ ነበር፤ በኒቅያ ከተማ አቅራቢያ አንዲት የተቀደሰች ሴት ነበረች፤ ቅዱስ ሉቃስ የሣላት የአምላክ እናት የቅድስት ድንግል ማርያም ውብ ሥዕሏን በቤቷ ውስጥ ደብቃ በማኖር በሥዕሏ ፊት መብራትን እያበራች ከልጇ እንድታማልዳት ትማፀን ነበር፡፡ የከሓዲው ንጉሥ ወታደሮቹም የአምላክ እናት ሥዕል በቤቷ እንዳለች በማወቃቸው ወደ ቤቷ በድንገት ዘልቀው ገቡ፤ ከመካላቸውም አንዱ ወታደር የእመቤታችንን ሥዕሏን በያዘው ጦር ጒንጯ ላይ ወጋት፡፡ ኾኖም ግን በእግዚአብሔር ድንቅ ሥራ ይኽ ክፉ ሥራው በተአምር ተተክቶ፤ ከተወጋው ከአምላክ እናት ፊት ላይ ደም ይፈስስ ጀመር፡፡ ይኽን ግሩምና ድንቅ ተአምር ባዩ ጊዜ ወታደሮቹ ደንግጠው ሸሽተዋል፤ ሴቲቱም ይኽነን ድንቅ ተአምር ባየች ጊዜ ሌሊቱን ሙሉ በሥዕሏ ፊት መብራትን አብርታ በአምላክ እናት በቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ፊት ስትጸልይ ዐደረች፤ በነጋታውም በእግዚአብሔር ፈቃድ ከጒንጮቿ ደም የፈሰሳትን የአምላክ እናት ሥዕሏን በባሕሩ ላይ እንድታስቀምጥ ታዘዘችና አስቀመጠቻት። ሥዕሏም በባሕሩ ላይ በመንሳፈፍ በማዕበሉ እየተነዳች ያለምንም መስጠምና መርጠብ ወደ ምዕራብ አቅጣጫ ጉዞዋን አድርጋ ወደ አቶስ ደረሰች፡፡ ጊዜያቶች ካለፉ በኋላ ከዕለታት በአንዳቸው ምሽት በአቶስ ተራራ የአይቬሮን ገዳም መነኮሳት የብርሃን ምሰሶ በባሕሩ ላይ ተተክሎ እንደ ፀሓይ ሲያበራ ተመለከቱ፡፡ ይኽም ተአምር ለተካታታይ ቀናቶች በመቀጠላቸው በዚያ የተቀደሰ ተራራ በምናኔ ያሉ አባቶች ኹሉ በአንድ ላይ ተሰባስበው በማድነቅ የብርሃን ምሰሶ ወደተተከለበት የአምላክ እናት ሥዕል በላዩ ላይ ወደ ተንሳፈፈበት ወደ ባሕሩ በመውረድ ወደ ሥዕሏ ለመጠጋት ቢሞክሩም ሥዕሏ ወደ ኋላዋ እየተመለሰች ሊያነሷት አልተቻላቸውም፡፡ በዚያው የአይቮሪዮን ገዳም ረድእ (የጉልበት አገልጋይ) ኾኖ የሚኖር አባ ገብርኤል የተባለው መነኩሴ ብቻ ሥዕሏን ከባሕር ውስጥ ማንሣት የሚችል እንደኾነ የአምላክ እናት ለመነኮሳቱ ገለጠችላቸው፤ በተመሳሳይም ለአባ ገብርኤል እመቤታችን ተገልጣለት “ወደ ባሕሩ ኺድ፤ ማዕበሉንም ሳትፈራ በባሕሩ ውስጥ በእምነት ተጓዝ፤ እናም ኹሉም ለዚኽ አንተ ላለኽበት ገዳም ያለችን ፍቅርና ርኅራኄ ምስክር እንዲኾኑ፤ ሥዕሌን ከባሕር አውጣ” በማለት ነገረችው፡፡ ከዚያም በአቶስ ተራራ ያሉት መናንያን ኹሉ አባ ገብርኤልን ይዘው ልብሰ ተክህኖ ለብሰው፣ እያመሰገኑ፤ በማዕጠንታቸው ዕጣን እያጠኑ የብርሃን ምሰሶ ወደተተከለበት የአምላክ እናት ሥዕል ወዳለበት ወደ ባሕሩ ኼዱ፤ አባ ገብርኤልም በደረቅ መሬት እንደሚጓዝ ያለምንም ፍርሃት ወደ ባሕሩ ውስጥ በመግባት በናፍቆት ኾኖ የአምላክ እናት የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕሏን በደረቱ ታቅፎ ተሳለማትና ወደ ባሕር ዳርቻ ይዟት ወጣ፤ እነርሱም በደስታ ኾነው እጅ ነሷት፡፡ ከዚያም ማግሰኞ በጠዋቱ ሥዕሏ ባረፈበት ቦታ ላይ በሚያመሰግኑበት ጊዜ ቀዝቃዛና ጣፋጭ ውሃ ከምድር ላይ ፈለቀላቸው፡፡ ከዚያም የእመቤታችንን ሥዕሏን በታላቅ ክብር በምስጋና ይዘው በመኼድ ወደ ቤተ መቅደስ አግብተው በመንበሩ ላይ አስቀመጧት፡፡ ነገር ግን በነጋታው መነኮሳቱ ወደ ቤተ መቅደስ ገብተው መብራት ሲያበሩ የእመቤታችን ሥዕሏን ባስቀመጡበት ቦታ አላገኟትም፤ ይልቁኑ በመግቢያው በር ባለው ግድግዳ ላይ ተሰቅላ አገኟት፤ እነርሱም መልሰው ቦታዋ ላይ ቢያኖሯትም ተመልሳ በገዳሙ መግቢያ ላይ ተሰቅላ ያገኟት ነበር፤ ከዚያም እመቤታችን ለአባ ገብርኤል ተገልጻለት “ለወንድሞች እንዲኽ ብለኽ ንገራቸው፤ ከዚኽ በኋላ ሥዕሌን ማግባት የለባቸውም፤ የእኔስ ፈቃድ በእናንተ ልጠበቅ ሳይኾን እኔን በምልጃዬ ጥላ በዚኽም ዓለም በወዲያኛውም ዓለም ልጋርዳችኊ እንጂ፤ ሥዕሌን በገዳሙ በምታዩበት ጊዜ ኹሉ የልጄ ምሕረትና ጸጋ ከእናንተ አይቋረጥም” አለችው፡፡ በዚህ ምክንያት ሥዕሏ በነገረ መለኮት ሊቃውንት "አቃቢተ ኆኅት" (ደጃፍን የምትጠብቅ) Panagia Portaitissa ("She who resides by the door" or "Keeper of the gate" ትባላለች። መነኮሳቱም ይኽነን ሰምተው በእጅጉ በመደሰት ለአምላክ እናት ለእመቤታችን ክብር በገዳሙ በር አጠገብ አነስ ያለች ቤተ ክርስቲያን ሠርተው ገባሪተ ተአምራት ወመንክራት (ድንቅ ተአምር አድራጊዋን) የአምላክ እናት የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕሏን ወደ ውስጥ አገቧት፤ የተቀደሰች የሥዕሏ መጠሪያም “የአይቬሮኗ የአምላክ እናት” (the Iviron Theotokos) ስትባል በግሪክ “ፓርታኢቲሳ” Παναγία Πορταΐτισσα; ትባላለች። ከዚያም በአይቬሮን ገዳም ያለችው የእመቤታችን ሥዕል ድንቅ ተአምር በዓለም ኹሉ ላይ ከተሰማ በኋላ በረከቷን ለማግኘት ክርስቲያኖች ወደዚያች ገዳም መኼድን ጀመሩ፤ ይኽ የተቀደሰ ሥዕሏና ታሪኳም ኢትዮጵያን ጨምሮ በዓለሙ ኹሉ ላይ ተሰማ፤ ዛሬም ምእመናን ይማፀኑበታል፡፡ ለአባ ገብርኤል የተለመነች እና በረከቷን እንዳሳደረችበት ዛሬም የምልጃዋ ጥላ በዚኽም ዓለም በወዲያኛውም ዓለም አይለየን። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት እና #መጋቤ_ሐዲስ_ሮዳስ) https://t.me/finotebirhan12

ከጥር እስከ ጥር.. የፊታችን እሁድ የካቲት 06, 2014 ዓ.ም ከ5:00 ሰዓት
ከጥር እስከ ጥር.. የፊታችን እሁድ የካቲት 06, 2014 ዓ.ም ከ5:00 ሰዓት

🔴 ስንክሳር#የካቲት_3 የካቲት ሦስት በዚችም ቀን #የቅዱስ_ኤፍሬም የሥጋው ፍልሰት ሆነ፣ ተጋዳይ የሆነ #መነኰስ_አባ_ያዕቆብ አረፈ፣ የባሕታውያን አለቃ ኑሮው የመላእክትን ኑሮ የሚመስል የከበረ #ቅዱስ_አባት_አባ_ዕብሎይ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ኤፍሬም_አፈ_በረከት የካቲት ሦስት በዚችም ቀን የሶርያዊ ቅዱስ ኤፍሬም የሥጋው ፍልሰት ሆነ። ይህም ቅዱስ ከዋክብትን ከሚያመልኩ ሰዎች ሀገር ነው አባቱም ክብር ይግባውና የክርስቶስን አምልኮት የሚጠላ የጣዖት ካህን ነበር። በዚያን ጊዜም የእግዚአብሔር ቸርነት ቀሰቀሰችውና አነሳሥታ የንጽቢን ጳጳስ ወደሆነው ወደ አባ ያዕቆብ ወሰደችው እርሱም የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው በእርሱም ዘንድ በጾምና በጸሎት ያለማቋረጥ እየተጋደለ ለብዙ ዘመናት ኖረ። የመንፈስ ቅዱስም ጸጋ አደረበት አሕዛብን ተከራክሮ ይረታቸው ነበር። ኒቅያ በሚባል ከተማ የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት አባቶች ኤጲስቆጶሳት ጉባኤ በተደረገ ጊዜ ይህ ቅዱስ ኤፍሬም ከመምህሩ ከአባ ያዕቆብ ጋራ ወደ ቅዱሳን ጉባኤው ሔደ። ከሀዲው አርዮስንም አውግዘው ከለዩት በኋላ ይህ ቅዱስ ኤፍሬም በዚያች ሌሊት ከምድር እስከ ሰማይ የሚደርስ የብርሃን ምሰሶ ተተክሎ አየ ከዚህ ራእይም የተነሣ አደነቀ ይገልጽለትም ዘንድ ወደ ጌታ ጸለየ ይህ የቂሣርያ ሊቀ ጳጳሳት ብፁዕ ባስልዮስ ነው የሚል ቃል ከሰማይ ወደርሱ መጣ። ቅዱስ ኤፍሬምም ያየው ዘንድ ወድዶ ወደ ቂሣርያ ሀገር ተጓዘ በደረሰም ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ በማእዘኑ በኩል ቆመ ቅዱስ ባስልዮስንም ወንጌልን ሊያነብ በወጣ ጊዜ ዋጋው ብዙ የሆነ ከወርቅ የተሠራ ልብሰ ተክህኖ ለብሶ አየው። ሦስት ምልክቶችንም እሰኪያይ ድረስ ተጠራጠረ ምልክቶችም እኒህ ናቸው ነጭ ርግብ መጥታ በራሱ ላይ አረፈች ሁለተኛም በልብሱ ላይ የሚያርፉ ተዋሐስያን ይቃጠሉና ይረግፉ ነበር። ሦስተኛም ከአፉ የእሳት ነበልባል ወጥቶ በምእመናን ላይ ያድር ነበር። ከዚህም በኋላ ቅዱስ ባስልዮስ ቅዱስ ኤፍሬምን በስሙ ጠራውና እርስ በርሳቸው ሰላምታ ተለዋወጡ። በአስተርጓሚ ይነጋገሩ ጀመሩ። የየራሳቸውንም ቋንቋ ይገልጽላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እንዲጸልይ ቅዱስ ኤፍሬም ቅዱስ ባስልዮስን ለመነው። በጸለየ ጊዜም ተገልጾላቸው ያለ አስተርጓሚ ተነጋገሩ። ከዚህ በኋላም ቅዱስ ኤፍሬምን ዲቁና ሾመው ከጥቂት ወራትም በኋላ ቅስና ሾመው ከእርሱም ብዙ ትሩፋቶች ተገለጡ በመንፈሳዊ ተጋድሎ ሁሉ ተጋደለ። አንዲት በወገን የከበረች ባለ ጸጋ ሴት ነበረች ራስዋንም ለካህን ለማስመርመር ታፍር ነበር ከታናሽነቷ ጀምራ የሠራችውን ኃጢአቷን ሁሉ ጽፋ ወደ ቅዱስ ባስልዮስ አመጣች። አባቴ ሆይ በዚህ ክርታስ ውስጥ ያሉት ኃጢአቶቼ ይደመሰሱ ዘንድ ተናገር ብላ ለመነችው እርሱም እንዳልሺው ይሁንልሽ አላት፡፡ እርሷም ክርታሱን በገለጠች ጊዜ ከአንዲት ኃጢአትዋ በቀር ኃጢአቷ ሁሉ ተደምስሶ አገኘች ያችም ኃጢአት አስጨናቂና ታላቅ ኃጢአት ነበረች። ባገኘቻትም ጊዜ ያቺን የቀረች ኃጢአቷን ያጠፋላት ዘንድ አልቅሳ ለመነችው እርሱም ወደ ቅዱስ ኤፍሬም ሒጂ እርሱ ይህችን የቀረች ኃጢአትሽን ያስተሠርይልሻል አላት። ወዲያውም ወደ ቅዱስ ኤፍሬም ሔዳ ከርሷ የሆነውን ሁሉ ነገረችው ። እርሱም እንዲህ አላት ፈጥነሽ ወደ ቅዱስ ባስልዮስ ሒጂ ግን ሙቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲወስዱት ታገኝዋለሽ ሳትጠራጠሪም ይህችን ክርታስ በላዩ ጣይ ይደመሰስልሻል። ያቺም ሴት ወደ ቅዱስ ባስልዮስ ተመለሰች ሙቶ ተሸክመው ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲወስዱትም አገኘችው ። ያንንም ክርታስ በአስክሬኑ ላይ ጣለችው ወዲያውኑም ተደመሰሰላት። ይህም ቅዱስ ኤፍሬም ብዙ ተአምራቶችን አድርጓል በዘመኑም ዲዳን የሚባል አንድ ከሀዲ ተነሣ ይህም አባት ኤፍሬም ተከራክሮ ረታው። እጅግም ብዙ የሆኑ ዐሥራ አራት ሽህ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሰ ከእርሳቸውም ውስጥ አምላክን የወለደች የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ውዳሴዋ ነው ። አቤቱ የጸጋህን ማዕበል ግታልኝ እስከሚል ድረስ ድርሳናትን ደርሶአል ። መልካም የሆነ ገድሉንም በፈጸመ ጊዜ ወደ ወደደው ወደ እግዚአብሔር ሔደ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት) https://t.me/finotebirhan12

🔴 "አርአዮ ለሙሴ" ሊታይ የሚገባ ድንቅ ወረብ #ሰብስክራይብ ያላደረጋችሁን የፌስቡክ ገጽ ተከታታዮቻችን youtube ገጻችንን ሰብስክራይብ, ሼርና Like በማድረግ አገልግሎታችንን ይደግፉ https://m.youtube.com/watch?v=rTv0ZQaIq5E

የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel) - Статистика и аналитика Telegram-канала @finotebirhan12