ፍኖተ ወንጌል ሰንበት ት/ቤት
رفتن به کانال در Telegram
በአሰላ ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ካቴድራል ፍኖተ ወንጌል ሰንበት ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው። የቴሌግራም ቻናል:- @Finote_Wongel የቴሌግራም ግሩፕ:- @FinoteWongel27 የቲክቶክ ገፅ:- https://www.tiktok.com/@finotewongel27 Youtube:- https://www.youtube.com/@Finote_Wongel ©ፍኖተ ወንጌል ሰንበት ት/ቤት
نمایش بیشتر672
مشترکین
اطلاعاتی وجود ندارد24 ساعت
+37 روز
-130 روز
آرشیو پست ها
+ ልጇን የምትመስል እናት +
ላቲኖች "ጎርፍም ያለ እርከን፥ ምራቅም ያለ ከንፈር አይቆምም" ይላሉ። በዓይን የታያቸውን፥ በአእምሮ የታወቃቸውን፥ በልብ የተረዳቸውን እውነት ከሽነው ሲገልጹት ነው። በእርግጥም የተፈጥሮ ሥርዓት እንደ ሰንሰለት የተጋመደ ነው። የቆመ ገፊ ከሌለው እንዳይሄድ፥ የሄደ የሚገታው ከሌለ እንዳይቆም አድርጎ ያዘጋጀው መድኃኔዓለም ነው። ሰማይን እንደሰሌዳ የዘረጋ፥ ከዋክብትን በሰማይ ላይ የሚያንቦገቡግ እርሱ ክርስቶስ ነው። ፀሐይን በቀን፥ ጨረቃን በሌሊት ያሰለጠነ እርሱ አማኑኤል ነው። ውሃ ቁልቁል እንዲፈስ፥ እሣት ሽቅብ እንዲወጣ የቀመረው እርሱ እግዚአብሔር ነው። እግዚአብሔር የሥርዓት አምላክ ነው የምንለው እንዲህ ያሉ የተፈጥሮ ሕግጋትንም ተመስርተን መኾኑን ማስታወስ ይበጃል።
የእግዚአብሔር ጥበብ ግን ገደብ እንደሌላው ወንዝ፥ አድማስ እንደሌለውም ሰማይ ነው። አባቶቻችን "ሰማይን ያለ ባላ፥ ምድርን ያለ ካስማ" ያቆምክ እያሉ የሚለምኑት ይህንን ስለተረዱ ነው። እግዚአብሔር ተፈጥሮን አስገኘ እንጂ ተፈጥሮ እግዚአብሔርን ባለማስገኘቱ፥ መላው ፍጥረት ምክንያት ሳይሻ ፈጣሪውን ይታዘዛል። የእግዚአብሔር ትእዛዝ ሲኾን ውሃ ተፈጥሮውን ይረሳና፤ እንደ ኤርትራ ባሕር ቀጥ ይላል፥ እንደ ዮርዳኖስ ባሕር ይሸሻል፥ እንደ ገሊላ ባሕር የሚራመድበትን ይሸከማል። የክርስቶስ ትእዛዝ ሲኾን ፀሐይ በገባኦን እንደቆመች ዑደቷን ትገታለች፥ በስቅለት እንደኾነውም በቀትር ትጨልማለች። የሥላሴ ፈቃድ ሲኾን ለእስራኤላውያን እንደኾነው መና ከሰማይ ይወርዳል፥ ለሣራ እንደኾነው የደረቀ ማኅፀን በዘጠና ዓመት ይለመልማል፥ ለሶምሶን እንደተደረገው ማር ከአንበሳ ሬሳ ይቆረጣል፥ ለአላዛርም እንደኾነለት ሙት ተነስቶ ከመቃብር ሰተት ብሎ ይወጣል።
አንዱ የተፈጥሮ ሕግ በወላጅና በልጅ ያለ መመሳሰል ነው። በዘመናት ውስጥ "ልጅ አባቱን ይመስላል" ወይም "ልጅት እናቷን ትመስላለች" እየተባለ ተመጣ እንጂ፥ አባት ወይም እናት "ልጃቸውን ይመስላሉ" አይባልም። ልጇን የምትመስል እናት ማየት የምትሹ ከኾነ ግን እናታችን ድንግል ማርያምን ተመልከቱ! ከመነሻው በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እና በእናቱ በድንግል ማርያም መካከል የተፈጥሮ ሕግ እጁን ሊያስገባም አልፈቀደም፥ ይህ ከተፈጥሮም በላይ ነውና። እናቱን ሳይፈጥራት በሕሊናው አስቀድሞ ያሰባት ልጅ ከቶ ማን ነው? እናቱን ፈጥሮ በሕይወት አኑሮና ጠብቆ ከእርሷ የተወለደስ ልጅ በየት አለ? ከፈጠራት እናቱ ተወልዶ እየታዘዘ ያደገ ልጅስ ከወደ የት ይመጣል? ድንግልናዋ ሳይለወጥ የወለደች አንስት፥ በድንግልና ወልዳ ልጇን ያጠባች እናትስ ማን ትኾን? ልጇ እንደሞተ የሞተች እናት ብናገኝ፥ ልጇ ከሞት እንደተነሳ ከሞት የተነሳች እናት ከየት እናመጣ ይኾን?
እግዚአብሔር ለዘመናት እርሱን እንድንመስለው ሲነግረን ኖሯል። “እኔ ቅዱስ ነኝና፥ እናንተም ቅዱሳን ሁኑ” (ዘሌ 19፡2) የሚለው ትእዛዝ የቀደመ ነው። ጌታችንም በተራራው ስብከቱ ላይ “የሰማይ አባታችሁ ፍጹም እንደ ሆነ እናንተም ፍጹማን ሁኑ።” (ማቴ 5፡48) በማለት አጽንቶታል። ቅዱስ ጳውሎስም “እንግዲህ እንደ ተወደዱ ልጆች እግዚአብሔርን ምሰሉ” (ኤፌ 5፡1) እያለ መልሶ ያሳስበናል። ይህንን ጥሪ በምልዐት የተገበረች፥ ‘ምሰሉኝ’ ያለውን እግዚአብሔርን መስላ የተገኘች፥ በድንግል ማርያም ደረጃ አንዳች ሰው አይገኝም። የነፍስ መዳን አክሊሉ ‘ክርስቶስን መምሰል’ ወይም ‘ሱታፌ አምላክ’ ነው፤ ከእርሷ በላይ ልጇ ክርስቶስን የመሠለ፤ ከእርሷ በላይ ሱታፌ አምላክን ገንዘቡ ያደረገ ደግሞ ማንም የለም።
ቅዱስ ጳውሎስ “ሞቱንም በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን፡፡” (ሮሜ 6፡5) በማለት መስክሮ ነበር። እነሆ ሞቱን በሚመስል ሞት ከልጇ ጋር ተባብራ፥ ትንሣኤውን በሚመስል ታላቅ ትንሣኤ የተባበረች እናታቸን ድንግል ማርያም ዛሬ የትንሣኤዋ ዕለት ነውና - ደስ ይበለን! ደስ ይበለን! ደስ ይበለን!
✒ Fresenbet G.Y Adhanom
ዐረገች
ከሰማዮች ይልቅ ውብ ሰማይ ነበረች፣
የጨለማውን ሊቅ ድቅድቅ የሰበረች፣
እውነተኛ ፀሐይ ከርሷ ቢፈነጥቅ ብርሃን ያበሰረች።
እርሷ ያወጣችው አማናዊ ፀሐይ፣
እንዳገዘፈችው ኑሮ በምድር ላይ፣
ሞቶ ተነሣና ከፍ ብሎ ቢያርግ ቢሔድ ወደ ሰማይ፣
እርሷም ሞተችና ፀሐዩአን ልትፈልግ ተነሣች ወደ ላይ፣
ዐረገች ወደ ላይ ብርሃን ልጇን ልታይ።
©ዘሕሊና
"እግዚአብሔር ሆይ አትተወኝ በፊትህ መልካም የሚኾን ምንም ምግባር የለኝም። ነገር ግን ስለቸርነትህ ስትል መልካም ነገር እንዴት እንደምጀምር ግለጥልኝ"
ቅዱስ አርሳንዮስ
" ድንግል ሆይ ከምልጃሽ በቀር ሊጠብቀኝ የሚችል እንደሌለ አወኩኝ ያለ ማህጸንሽም ፍሬ ሊራራልኝ የሚችል እንደሌለ ይህንንም አውቄ ወደ አንቺ ተጠጋሁ በልጅሽም አመንኩ እርሱንም አመለኩ ቸርነቱንም ተስፋ አደረኩ "
አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ
#ጽንሰታ፡ ለእግዝእትነ፡ ማርያም
+++++++++++++++++++
እንኳን፡ አምላክን፡ ለወለደች፡ ለእመቤታችን፡ ቅድስት፡ ድንግል፡ ማርያም፡ ጽንሰት፡ ዓመታዊ፡በዓል፡ አደረሰን፣ አደረሳችኁ!
ጻድቅ፡ ሰው፡ የኾነ፡ ኢያቄም፡ እና፡ የከበረች፡ ሚስቱ፡ ሐና፡ ልጅ፡ ሳይወልዱ፡ ሸመገሉ። የከበረች፡ ሐና፡ መካን፡ ኹናለችና፤ በዚኽም፡ ኹልጊዜ፡ ያዝኑ፡ ነበር። የእሥራኤል፡ ልጆች፡ ልጅ፡ ያልወለዱትን፡ ከእግዚአብሔር፡ በረከትን፡ ያጡ፡ ናቸው፡ እያሉ፡ ያቃልሏቸው፡ ነበር።
እነርሱም፡ እግዚአብሔር፡ አምላክ፡ ልጅን፡ ይሰጣቸው፡ ዘንድ፡ ዘወትር፡ በጸሎት፡ ይለምኑ፡ ነበር። ከዚኽም፡ በኋላ፡ ወንድ፡ ልጅን፡ ወይም፡ ሴት፡ ልጅን፡ ቢወልዱ፡ ለእግዚአብሔር፡ ቤት፡ አገልጋይ፡ ሊያደርጉ፡ ስለትን፡ ተሳሉ።
አንድ፡ ቀንም፡ የከበረ፡ ኢያቄምም፡ በተራራ፡ ላይ፡ ሳለ፡ ሲጸልይ፡ እና፡ ሲማልድ፡ እነሆ፡ በላዩ፡ እንቅልፍ፡ እንቅልፍ፡ ብሎት፡ አሸለበ። ከእግዚአብሔር፡ ዘንድ፡ የተላከ፡ የመላእክት፡ አለቃ፡ ቅዱስ፡ ገብርኤል፡ ተገልጾ፡ "ሚስትኽ፡ ሐና፡ ትጸንሳለች፤ ዓለሙ፡ ኹሉ፡ ደስ፡ የሚሰኝባትን፣ የብዙዎችም፡ ዐይነ፡ ልቡናቸው፡በርሷ፡ የሚበራላቸውን፣ በርሷም፡ ድኅነት፡ የሚኾንባትን፡ ሴት፡ ልጅን፡ ትወልድልኻለች።" አለው።
ኢያቄምም፡ በነቃ፡ ጊዜ፡ ወደ፡ ቤቱ፡ ኼዶ፡ ለሚስቱ፡ ለቅድስት፡ ሐና፡ ነገራት። ርሷም፡ ያየችውን፡ ራዕይ፡ ነገረችው። እጅግም፡ ተገረሙ። ከዚኽም፡ በኋላ፡ ነሐሴ፡ ሰባት፡ ቀን፡ እመቤታችን፡ ቅድስት፡ ድንግል፡ ማርያም፡ ተጸነሰች።
+++++++++++++++++
የእመቤታችን፡ ቅድስት፡ ድንግል፡ ማርያም፡ ጸሎት፡ እና፡ ምልጃ፡ ቅድስት፡ ቤተ፡ ክርስቲያናችንን፣ ሀገራችን፡ ኢትዮጵያን፡ ይጠብቅልን!
✨✨✨🌿✨🌿✨🌿
"ምስጋናን የተመላች እርስዋን ከፍ ከፍ እናደርጋት ዘንድ እንዲህም እያልን እናመሰግናት ዘንድ ጸጋን የተሞላሽ ሆይ የደስታ መፍሰሻ ሆይ ዓይኖቻቸው ብዙዎች ከሆኑ ከኪሩቤል ክንፎቻቹው ስድስት ከሚሆኑ ከሱራፌል ይልቅ የሚበልጥ የመልክ ግርማ አለሽ ።
እግዚአብሔር አብ በሰማይ ሆኖ ምሥራቅንና ምዕራብን ሰሜንና ደቡብን ዳርቻዎችንም ሁሉ በእውነት ተመለከተ ተነፈሰ አሻተተም እንድ አንቺ ያለ አላገኘም ። የአንቺን መዓዛ ወደደ ደምግባትሽንም ወደደ ። የሚወደውን ልጁን ወደ አንቺ ሰደደ ። አንቺን የወደደ እግዚአብሔር አብ ቅዱስነው ፣ በመኀፀንሽ ያደረ ወልድ ዋህድም ቅዱስ ነው ፣ ያጸናሽም የጽድቅ መንፈስ ጰራቅሊጦስ ቅዱስ ነው ።
ምስጋናን የተመላሽ ድንግል ሆይ በማንና በማንስ ምሳሌ እንመስልሻለን ። አማኑኤል የማይተረጎም የሥጋን ልብስነት ከአንቺ የለበሳት መሣሪያ ነሽ ። "✨🌿ቅዳሴ ማርያም✨🌿 ✨✨✨🌿✨🌿✨🌿
"እውነተኛና ብልህ የሆነ ሰው አንድ ነገር ይፈልጋል ይኸውም ለእግዚአብሔር መታዘዝ ነው በዚህች ዓለም እያለ ነፍሱን ሥርዓት ያሲዛል። ስለ ሥጦታዎቹና ስለሚያጋጥሙ ነገር ሁሉ እግዚአብሔር ያመሰግናል።"
አባ እንጦንስ
🌴🌴🌴🌷🌷🌷🌴🌴🌴🌷🌷🌷🌴🌴🌴
📚#በእንተ_ፍልሰታ_ለማርያም#📚
#ቅዳሴ_ማርያም
#አባ_ሕርያቆስ_ስለ_እመቤታችን_ቅድስት_ድንግል_ማርያም
አንቲ ውእቱ ተስፋሁ ለአዳም አመ ይሰደድ እምገነት ።
አበው ቀደምት ያለውን ይተረትራል። አመ ተሰደ ሲል ነው። አመ ይትበሃሎ ለሰይጣን አመ ይወፅኡ እስራኤል እምግብጽ እንዲል። አዳም ከገነት በወጣ ጊዜ ተስፋው አንቺ ነሽ
ታሪክ
ይህስ እንደምን ነው ቢሉ ጌታ አዳምን ከአራቱ ባሕርያተ ሥጋ ከአምስተኛ ባሕርየ ነፍስ ፈጥሮ በልጅነት አክብሮ በገነት አኖረው ሰባቱን ዓመት በሕግ ጸንቶ አትብላ ያለውን ዕፀ በለስ ሳይበላ ጠብቆ ኖረ ከዚያ በኋላ አትብላ ያለውን ዕፀ በለስን በላ ሕጉንም አፈረሰ። እንግዲህ ወዲህ በዚህ ቦታ መኖር አይገባህም ብሎ ከገነት አስወጥቶ በገነት አንጻር በደብር ቅዱስ አኖረው ስለምን ቢሉ ኀዘን እንዲጸናበት። ወደ ቀደመ ቦታዬ!ይመልሰኝ ይሆን እያለ ተስፋ እንዳይቆርጽ ከዕለታት ባንዳቸው እግዚአብሔርን ያህል ጌታ ገነትን ያህል ቦታ ባንች ምክንያት አጣሁ ብሎ ፊት ነሣት ሴቶች ድንጉፆች ናቸውና ሸሽታ ሂዳለች መልአኩ መጥቶ አትታረቃትምን አለው እግዚአብሔርን ያህል ጌታ ገነትን ያህል ቦታ ያጣሁት በእሷ ምክንያት አይደለም አይሆንም አለው በእሷ ብታጣ መታረቂያህም እሷ ናትና ታረቃት አለው። ኢትከውነኒ ናዛዚተ እሷስ መታረቂያም አትሆነኝ አለው። ከዚህ በኋላ መላእክት ጊዜያት አስተምረውት ነበርና ሲጸልይ መልአክ መጥቶ አዳም ምን ይሆንሃል የመስተቀይምን ጸሎት እግዚአብሔር አይቀበለው አለው አንተ ሂደህ አምጣልኛ አለው። እንዳበረርሃት አንተ ሂደህ አምጣት እንጂ እኔ ምን ባይ ነኝ አለው። ከዚህ በኋላ ሂዶ አምጥቷታል። እሷም ከጫማው ወድቃ ማረኝ ብላለች። ከዚህ በኋላ አትለያት ብሎታል ይህ ዛሬ ለሴቶች አብነት ሁኗቸው ምንም ተርታ ሴት ብትሆን ወንድ ይማልዳታል እንጂ ሴት አትማልድም። ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር እንደተጣላን ይቀር ይሆን አለችው። እሱስ መሓሪ ነው ዳሩ ግን አንች አለሽና ምን ይሆናላ አላት ከእንግዲህስ ወዲህ ካንተ ፈቃድ አልወጣም አለችው ከዚያ በኋላ ሄደው ከባሕር ገብተው ይጸልዩ ጀመር። ብለህ ዓለም የሚድን በሩቅ ብእሲ መሥዋዕትነት አይደለም እንደ ቅዳሴ ሐዋርያት ተርክ ።
ትርፍ
እኔ ከሰማየ ሰማያት ወርጄ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ሲል። በኀሙስ ዕለት ወበመንፈቃ ለዕለት እትወለድ እምወለተ ወለትከ ብሎ ተስፋውን ነግሮታልና የአዳም ተስፋው አንች ነሽ አለ አዳም ማለት ሥግው እመሬት ዘተሰግወ እምድር ይህ ቀረህ የማይባል ፍጹም መልከ መልካም ፍጥረት ማለት ነው።
የዋህቱ ለአቤል ዘተቀትለ በዓመጻ። ይቆየን.....
🔱⚜🔱⚜🔱⚜🔱⚜🔱⚜🔱⚜🔱⚜
"ጾምህን በፍቅርና እርሱን ተስፋ በማድረግ በእምነት ካላደረግኸው አንተን ፈጽሞ ሊረዳህ አይችልም ።በጠብ ሆኖና በውስጡ ጠላትነትን አንግሥ የሚጾም ጻዋሚ እግዚአብሔር ይጠላዋል ከመዳንም ፈጽሞ የራቀ ነው።"
ቅዱስ ኤፍሬም
🌴🌴🌴🌷🌷🌷🌴🌴🌴🌷🌷🌷🌴🌴🌴
📚#በእንተ_ፍልሰታ_ለማርያም#📚
#ቅዳሴ_ማርያም
#አባ_ሕርያቆስ_ስለ_እመቤታችን_ቅድስት_ድንግል_ማርያም
ጐሥዐ ልብየ ቃለ ሠናየ ጐሥዐ ልብየ ቃለ ሠናየ ጐሥዐ ልብየ ቃለ ሠናየ። መጽሐፍ ምሥጢርን ከምሥጢር አያይዞ መናገር ልማዱ ነው። አባቷ ዳዊት ለንጉሠ ሰማይ ወምድር ለእግዚአብሔር ምሥጋና ላቅርብ ባለ ጊዜ ጐሥዐ ልብየ ቃለ ሠናየ ብሎ እንደተናገረ ከዚህም አባ ሕርያቆስም ለንግሥተ ሰማይ ወምድር ለእመቤታችን ምሥጋና ላቅርብ ባለ ጊዜ ጐሥዐ ልብየ ቃለ ሠናየ ብሎ ተናገረ ወአነ አየድዕ ማንሻ፡፡
አንድም በዳዊት አድሮ የተናገረ መንፈስ ቅዱስ በአባ ሕርያቆስም አድሮ ተናገረ፡፡ ልሕኵት ልቦናዬ በመንፈስ ቅዱስ እሳትነት ፈላ፤ ፈላና በጎ በጎ ነገርን አውጥቶ ተናገረ፡፡ ወትጕሥዖሙ ይእቲ ባሕር ለነጋድያን እንዲል ወአነ አየድዕ ማንሻ፡፡
አንድም ልሕኵት ልቦናዬ ስንቡል መንፈስ ቅዱስን ተቀብሎ በጎ በጎ ነገርን ገሣ፡፡ በሀገራቸው የበሉት የጠጡት ያልተስማማቸው እንደሆነ ዑድ ሰንደል የሚባል ሽቱ አለ ያን ተመግበው በጎ በጎ ነገር ገሣሁ እንዲሉ፡፡
ሦስት ጐሥዐ ተናገረ ወአነ አየድዕ ቅዳሴሃ ለማርያም፣ ወአነ አየድዕ ውዳሴሃ ለድንግል፣ ወአነ አየድዕ ዕበያቲሃ ለድንግል ብሎ የሚያመጣው ነውና ለዚያ አርእስት ነው፡፡ ይህስ ለራሱ አርእስት ነው ብሎ ሦስት ጊዜ መላልሶ መናገሩ የሦስትነት ቃሉ አንድ ዐይነት መሆኑ (ያለመለወጡ) የአንድነታቸው ምሳሌ::
አንድም እመቤታችን በዚህ ዓለም፣ በገነት፣ በመንግሥተ ሰማያት ትመሰገናለችና፡፡
አንድም በመንግሥተ ሰማያት ያሉ ጻድቃን የሚያመሰግኗት ስለሆነ አስቀድሞ መንግሥተ ሰማያት የገባ የለም ብሎ ኋላ መንግሥተ ሰማያት የሚገቡ ጻድቃ የሚያመሰግኗት ስለሆነ፤ አንድም በነገደ ሴም፣ በነገደ ካም፣ በነገደ ያፌት ትመሰገናለችና፡፡ አንድም በወጣንያን፣ በማዕከላውያን፣ በፍጹማን አንደበት ትመሰገናለችና፡፡ አንድም በመላእክት፣ በደቂቀ አዳም፣ በካልዕ ፍጥረት ትመሰገናለችና፡፡ አንድም የንጽሐ ሥጋ፣ የንጽሐ ነፍስ፣ የንጽሐ ልቦናዋ ምሳሌ ነው፡፡ እሱስ የተናገረው አንድ ጐሥዐ ነው ቅዱስ ያሬድ ለዜማ ማቅኛ ሦስት አድርጎ ተናግሮታል እንጂ፡፡
ወአነ አየድዕ ውዳሴሃ ለድንግል።
እኔስ የድንግልን ምሥጋና እናገራለሁ:: ሁለት ጐሥዐ ተናግሮ ነበርና ለዚያ አርእስት ይህስ ለራሱ አርእስት ነው ብሎ ኦ ድንግል አኮ ወራዙት ስፉጣን ዘናዘዙኪ አላ መላእክተ ሰማይ ሐወጹኪ መተብህለ ካህናት ወሊቀ ካህናት ብሎ የሚያመጣው ነውና ለዚያ አርእስት ነው᎓᎓
አኮ በአንኆ በቃለ ዝንጋዔ። ይቆየን....
🔱⚜🔱⚜🔱⚜🔱⚜🔱⚜🔱⚜🔱⚜
ወበትንሣኤሁ ቅድስት አግብዖ ለብእሲ ዳግመ ውስተ ገነት።ያልተካከለ ዳግመ ነው። ለመውጣታቸው መግባታቸውን ዳግመ አለ። አንድም የተስተካከለ ዳግመ ነው ቀድሞ ለመግባታቸው ኋላ መግባታቸውን ዳግመ አለ። በልዩ ትንሣኤው አዳምን ዳግመኛ ወደ ገነት መለሰው። በልዩ ትንሣኤው አለ ከነአልዓዛር ትንሣኤ ሲለይ። እሊያ አስነሺ ይሻሉ፤ እርሱ ግን በገዛ ሥልጣኑ ነውና። ወተንሣእኩ በሥልጣነ ባሕቲትየ እንዲል። አብ አንሥኦ፥ መንፈስ ቅዱስ አንሥኦ ቢል አንድ ነው ዕሪናቸውን መናገር ነው። አንድም የነአልዓዛር ትንሣኤ በብሉይ ሥጋ ነው፤ የእርሱ ግን በሐዲስ ሥጋ ነውና። የነአልዓዛር ትንሣኤ ሞትን ያስከትላል፤ የእርሱ ግን ሞትን አያስከትልምና። አንድም የነአልዓዛር ትንሣኤ ትንሣኤ ዘጉባኤን ይጠብቃል። የእርሱ ግን አይጠብቅም።
ሰአሊ ለነ ቅድስት።አዳምን ወደገነት ዳግመኛ ከመለሰ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጒት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አዕምሮውን ለብዎውን በልቦናችን ሳይብን አሳድሪብን።
ማርያም ንጽሕት ድንግል ወላዲተ አምላክ ማዕምንት።ይቆየን..... ✨✨✨🌹🌹🌹️️️️️️✨✨✨🌹🌹🌹️️️️️️✨✨✨🌹🌹🌹
✨✨✨🌹🌹🌹️️️️️️✨✨✨🌹🌹🌹️️️️️️✨✨✨🌹🌹🌹
ውዳሴሃ ለእግዝእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ ዘይትነበብ በዕለተ ዓርብ
ማርያም ድንግል ሙዳየ ዕፍረት ነቅዓ ፈልፈለ ማየ ሕይወት።ነቅዕ እና ፈልፈል አንድ ወገን እመቤታችን፤ ማየ ሕይወት ጌታ። አንድም ነቅዕ እመቤታችን፤ ፈልፈል ጌታ፤ ማየ ሕይወት ልጅነት ኅድጉኒ ሊተ ነቅዓ ማየ ሕይወት ወከረዩ አዘቅተ ዘኢይትረከብ ማዩ እንዲል።
ፍሬ ከርሳ አድኀነ ኩሉ ዓለመ።የማኅፀኗ ፍሬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰውን ሁሉ አድኗልና።
ወሠዓረ እምኔነ መርገመከእኛ መርገመ ሥጋን መርገመ ነፍስን አጠፋልን።
ወገብረ ሰላመ ማዕከሌነ በመስቀሉ።በመስቀሉ ኅሩይ ማዕከለ እግዚአብሔር ወሰብዕ እንዲል በመካከል ሆኖ አስታረቀን፤ ወገብረ ሰላመ በደመ መስቀሉ እንዲል።
"ፍትሕና ርትዕም ለሰው ልጅ መነፈግ የበለትም፤ ሰው በምድር ላይ ሰርቶ የመኖር መብቱ ሊከበርለት ይገባል፤ይህንን ማድረግ ማለት ለእግዚአብሔር መታዘዝ ማለት ነው።"
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ
የ2017 ዓ.ም የጾመ ፍልሰታ መግባትን አስመልክተው ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ.ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ቃለ ምእዳንና ቡራኬ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ኣሓዱ ኣምላክ ኣሜን፤
በሀገራችን በኢትዮጵያና በመላው ዓለም የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ፡-
የክብር ባለቤት እግዚአብሔር ኣምላካችን እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ ሰባት ዓ.ም የቅድስት ድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም ኣደረሳችሁ!
‹‹ታዓብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር፣ ነፍሴ እግዚአብሔርን እጅግ ታከብረዋለች›› (ሉቃ.፩÷፵፮)፤
ይህንን ዐረፍተ ነገር የተናገረችው ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ የሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፤ ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር ዓለምን ለማዳን በሰራው ስራ ሰውነታችንን ለመዋሓድ የመረጣት ምርጥ የፍጥረት ወገን ናት፤ፍጥረት ሁሉ በእግዚአብሔር ለእግዚአብሔር ተፈጥሮኣል፤የእግዚአብሔርም ነው፤ የቅድስት ድንግል ማርያም መመረጥም በእግዚአብሔር ለሰው የተደረገ ምርጫ ነው፤
የሰው መዳን ከጥንቱ ከጠዋቱ በእግዚአብሔር ልዩ ኣሰራር እንደሚከናወን በነቢያት የተገለጸ ነበረ፣‹‹ኣኮ በተንባል ወኣኮ በመልኣክ ኣላ ለሊሁ እግዚእ ይመጽእ ወያድኅነነ፤ በኣማላጅም ኣይደለም፤ በመልኣክም ኣይደለም እሱ ራሱ ጌታ መጥቶ ያድነናል እንጂ›› የሚለው የነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ ትንቢትም ይህንን ያስረዳል፤ ቃለ ትንቢቱ ድኅነታችን በጌታ ቤዛነት እንደሚከናወን ያረጋግጣል፤ይህም ሊሆን የቻለው ከፍጡራን ወገን በደሙ ቤዛነት ፍጡራንን የሚያድን ስለሌለ ነው፤
ከዚህ ኣንጻር የሰው መዳን በእግዚአብሔር ኣሰራር በደም ቤዛነት ከሆነ፣ በደሙ ቤዛነትም ዓለምን ማዳን የሚችል ከፍጡር ወገን ከሌለ፣ መዳናችን በእግዚአብሔርና በእግዚአብሔር እጅ ብቻ የተንጠለጠለ ነበረ፤ እግዚአብሔር በደሙ ቤዛ ሆኖ ዓለምን ለማዳን ደግሞ ደም ሊኖረው ይገባ ነበር፤ በመሆኑም እግዚአብሔር በክዋኔው ደም የሌለው ስለሆነ ለቤዛ ዓለም የሚፈስ ደምን ገንዘብ ማድረግ ነበረበት፤ይህንን ደም ለመዋሓድ ቅድስት ድንግል ማርያምን መረጠ፤ ለዚህ ብቁ እንድትሆንም በእስዋ ላይ ስራውን ሰራ፤በምርጫውም መሠረት ከቅድስት ድንግል ማርያም ደማዊ ሥጋንና ነፍስን ተዋሕዶ ለቤዛዊ መሥዋዕት መንገዱን ኣመቻቸ፤
ቅድስት ድንግል ማርያም በነገረ ድኅነት መሰላል ለመሆን በእግዚአብሔር የተመረጠች በመሆኗ ኣንቀጸ ኣድኅኖ ወይም የድኅነት በር ትባላለች፤ቅድስት ድንግል ማርያም ለዚህ ታላቅ ነገረ ድኅነት መመረጥዋ እጅግ ታላቅ ዕድል መሆኑን ስለተገነዘበች ‹‹ታላላቅ ስራዎችን ሰርቶልኛልና›› በማለት እግዚአብሔርን በመዝሙር ኣመስግናለች ኣክብራለችም፤
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!
የቅድስት ድንግል ማርያም የምስጋና እና የኣምልኮ መዝሙር የኛም መዝሙር ነው፤ እግዚአብሔር ለቅድስት ድንግል ማርያም ታላላቅ ስራዎችን እንደሰራ ለኛም ብዙ ታላላቅ ስራዎችን ሰርቶልናል፤ እየሰራልንም ነው፤ ለሰራልን ኣምላክም እንደ ቅድስት ድንግል ማርያም ታላቅ ክብርን መስጠት ይገባናል፤ ለእግዚአብሔር የምንሰጠው ክብርም በቃል ብቻ የሚገለጽ ሳይሆን በተግባር የሚታይ ሊሆን ይገባል፤ የድንግል ማርያም መንፈሳዊ ሕይወት በማስተዋል በትሕትና፣ በትዕግሥት በርኅራኄ በመታዘዝ በንጽህና በቅድስና በክብርና በበረከት የተሞላ እንደሆነ በቅዱስ መጽሓፍ ከተጻፈው ሥነ-ሕይወቷ መረዳት እንችላለን፤
ታድያ በእርሷ ክብርና ተማሕፅኖ የምንተማመን ልጆቿም የእሷን ያህል እንኳ ባንችል ወደእርስዋ የሚጠጋጋ መንፈሳዊ ሕይወት ሊኖረን ይገባል፤ ይህም የምናደርገው ለእግዚአብሔር ክብርና ለእኛ መዳን ሲባል ነው፤ እኛ እግዚአብሔርን ስናከብር እንከብራለን እንድንማለን፤ ለእግዚአብሔር ክብር የማንሰጥ ከሆነ ግን ውጤቱ መክበር ሳይሆን ሌላ ነው የሚሆነው፤
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!
እኛ በየጊዜው ጾምን እንድንጾም ያስፈለገበት ዋናው ምክንያት ፈቃደ ሥጋችንን በመግራት ለእግዚአብሔር ታዛዦች እንድንሆን ነው፤ ጾም የኃጢኣት መግቻ መሳሪያ በመሆኑ ‹‹ልጓመ ኃጢኣት›› ተብሎ ይታወቃል፤ በዚህም ሰውነታችንን ለግብረ ኃጢኣት ከሚያጋግሉ ምግቦች ኣርቀን በሰከነ መንፈስ እግዚአብሔርን እያሰብን ኃጢኣታችንንም እያስታወስን በንስሓ ወደ እርሱ ለመቅረብና ለሱ ለመታዘዝ እንጾማለን፤
የጾም ጥቅም ከጥንት ጀምሮ የታወቀ በእግዚአብሔርና በሰውም ተቀባይነት ያለው ነው፤ እግዚአብሔር ከመሥዋዕት ይልቅ መታዘዝን ይወዳልና በጾምና በጸሎት ለሱ ልንታዘዝ ይገባል፤ እግዚአብሔር በቅድስት ድንግል ማርያም ማሕፀን ሊያድር የቻለው ‹‹እንዳልኸኝ ይሁንልኝ›› ብላ ታዛዥነትዋን በገለጸች ጊዜ ነው፤ እኛም እንዳልከን ይሁንልን እያልን እንደእስዋ ታዛዥ መሆን አለብን፤
ዛሬ በዓለማችን ያለው መተረማመስ ለእግዚአብሔር ያለመታዘዝ ያመጣው ጣጣ እንደሆነ ማንም ኣይስተውም፤ መታዘዙ ቢኖር ኖሮ የሰው ልጅ ሰውን የሚያድን ብቻ እንጂ ሰውን የሚገድል መሳሪያ ኣያመርትም ነበር፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር ወንድምህን እንደራስህ ኣድርገህ ውደድ ኣለ እንጂ ግደል ብሎ ኣላዘዘምና ነው፤ኣሁንም በዚህ ባለንበት ዓለም በጣም ተባብሶ የሚገኘው የመጠፋፋት ዝንባሌ ለእግዚአብሔር በመታዘዝ በሰላምና በሰጥቶ መቀበል ካልተቋጨ ዳፋው ኣስከፊ መሆኑ ኣይቀርም ፤
ከዚህ አንጻር ዛሬም ለሰው ልጆች ሁሉ የምናስተላልፈው መልእክት ‹‹በፍቅር ከሆነ ትንሹም ለሁሉ ይበቃልና ያለውን በጋራ በመጠቀም በፍቅርና በሰላም እንኑር›› የሚል ነው፤ ‹‹ፍትሕና ርትዕም ለሰው ልጅ መነፈግ የበለትም፤ ሰው በምድር ላይ ሰርቶ የመኖር መብቱ ሊከበርለት ይገባል፤ይህንን ማድረግ ማለት ለእግዚአብሔር መታዘዝ ማለት ነው፤ስለሆነም ለእግዚአብሔር ክብርና ለራሳችን መዳን ስንል ለእርሱ በመታዘዝ በሕይወትና በሰላም እንኑር፡፡
በመጨረሻም፡-
በጾመ ማርያም ሱባዔ ስለሀገር ሰላምና ስለሕዝብ ደኅንነት በመጸለይ፣ በልዩ ልዩ ምክንያት በመከራ ላይ ወድቀው የሚገኙ ወገኖቻችንን በሚያስፈልጋቸው ሁሉ በመርዳት ሱባዔውን እንድናሳልፍ ኣባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም ለመላው ሕዝበ ክርስቲያን እናስተላልፋለን፤
መልካም የሱባዔ ወቅት ያድርግልን
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
ወስብሓት ለእግዚአብሔር ኣሜን!!
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣
ነሐሴ 1 ቀን 2017 ዓ.ም
ዋሽንግተን ዲሲ
✨✨✨🤲✨🤲✨🤲
እንኳን ለጾመ ፍልሰተ ሥጋሃ ለማርያም በሰላም አደረሳችሁ
ሰአሊ ለነ ቅድስት
(ሠዐሊ ለነ ቅድስት)" "ቅድስት ሆይ ለምኝልን" (ቅድስት ሆይ ሣይልን)ሰአለ ማለት ለመነ ፣ማለደ ፣ጠየቀ ማለት ሲሆን ሠዐለ ማለት ደግሞ ሣለ(ለሥዕል)፣ቀረፀ ማለት ነው። የመጀመሪያው ቅድሰት ሆይ ለምኝልን፣ ማልጅልን፣ ከፈጣሪያችን ምህረትንና ይቅርታን ጠይቀሽ አሰጭን ሲሆን ሁለተኛው ምሥጢር አእምሮ (ዕውቀት) ፣ ለብዎ( ማስተዋል) ጥበቡን በልቡናችን ሣይብን አሳድሪብን ማለት ነው።
"ቅድስት" ማለትም ንጽሕት፣ክብርት፣ፅንዕት፣ ልዩ ማለት ነው።✨ንጽሕት ተብላ ስትጠራ እንደሌሎቹ ፍጡራን ፣እነደሌሎች ሴቶች አይደለም፣ ሌሎች ሴቶች ከገቢር(ኃጢአት ከመሥራት) በነጹ ከነቢብ(በአንደበት ከመበደል) አይነጹም፣ ከነቢብ ቢነጹ ከኀልዮ(በሀሳብ ኃጢአት መስራት) አይነጹም እመቤታችን ግን በዘህ ንጽሕት ናትና " ዐቀባ ጰራቅሊጦስ እምከርሠ እማ ወኢረኲሰት በምንትኒ እምዘፈጠራ እምፅቡር ጽሩየ ገብራ ድንግል በኅሊናሃ ወድንግል በሥጋሃ" " ከእናቷ ማኅፀን ጀምሮ መንፈስ ቅዱስ ጠበቃት፣ከፈጠራት ጀምሮ በምንም በምን አላደፈችም፣ከአፈር ንጽሕት አደረጋት፣ እርሷም በሀሳቧና በሥጋዋ ድንግል ናት" እንዲል። መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም ይህንን መስክሯል ሉቃ 2:27፣ ኤልሳቤጥም እንዲሁ። ✨ክብርት ፦ ሌሎች እናቶች ነገሥታትን ፣ጳጳሳትን ካህናትን ......በመውለዳቸው ይከበራሉ እመቤታችን ግን አምላክ፣ንጉሠነገሥት፣ሊቀ ካህናት ..... ኢየሱስ ክርስቶስን ስለወለደች ክብሯ ልዩ ነው፣ ስለዚህም ክብርት ትባላለች። ✨ፅንዕት ፦ ማለት የፀናች ማለት ነው፣ሌሎች ሴቶች ቢፀኑ እስከ ጊዜ ተፈትሖ ማኅፀን ነው ከዛ በኋላ ፅናት የላቸውም እመቤታችን ግን ከመፅነሷ በፊት፣ ከፀነሰችም በኋላ፣ከመውለዷ በፊት ከወለደችም በኋላ ለዘለዓለም ፅንዕት ናት። ✨ልዩ ፦ እናትነትን ከድንግልና፣ድንግልናን ከእናትነት አስተባብራ ይዛ የተገኘች ብቸኛ ሴት ናት፣ የሥላሴን ዙፋን የተሸከመች፣ መላእክት በሰማይ እየራዱ እየተንቀጠቀጡ የሚያመሰግኑትን አምላክ እርሷ 9 ወር ከ5 ቀን በማህፀን ተሸክማዋለች፣አዝላዋለች፣አቅፋዋለች፣ እርሱንም ተሸክማ በግብፅ በረሃ ተንከራታለች፣ የእኛ የሕይወት ምግብ የሆነው እንጀራችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእርሷ በኩል አልፎ፣ ተጋግሮ፣በስሎና ጣፍጦ የመጣ ነው!!! ልዩ ናት!!!! በረከቷ አማላጅነቷ አይለየን፣ የልጅዋ ቸርነት ይጠብቀን!!!! ሀገራችንንም ሰላም ያድርግልን! 📝መጋቤ ሐዲስ ነቅዐጥበብ ከፍያለው ✨✨✨🤲✨🤲✨🤲
እግዚአብሔር አምላክ ከአንተ ጋር ነውና አትፍራ፥ አትደንግጥም፤ ለእግዚአብሔርም ቤት አገልግሎት የሚሆነው ሥራ ሁሉ እስኪፈጸም ድረስ እርሱ አይተውህም፥ አይጥልህምም።
1ኛ ዜና28÷20
🌴🌴🌴🌷🌷🌷🌴🌴🌴🌷🌷🌷🌴🌴🌴
#ጊዜ_ተሰዓቱ_ሰዓት_ዘዓርብ
ምቅናይ፡-
#ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለም ዓለም፣
#አማኑኤል አምላኪየ ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለም ዓለም፣
#ኦ እግዚእየ ኢየሱስ ክርስቶስ ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለም ዓለም፣
#ኃይልየ ወጸወንየ ውእቱ እግዚእየ እስመ ኮንከኒ ረዳእየ እብል በአኮቴት
አቡነ ዘበሰማያት.......... (በዜማ )
#ለአምላክ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለመ ዓለም፤
#ለሥሉስ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለመ ዓለም፤
#ለማሕየዊ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለመ ዓለም፤
#ለዕበዩ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለመ ዓለም፤
#ለዕዘዙ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለመ ዓለም፤
#ለመንግሥቱ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለመ ዓለም፤
#ለኢየሱስ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለመ ዓለም፤
#ለክርስቶስ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለመ ዓለም፤
#ለሕማሙ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለመ ዓለም፤
#ለመስቀሉ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ ለዓለመ ዓለም፤
#ለከ ይደሉ ኃይል፣
#ወለከ ይደሉ ስብሐት፣
#ወለከ ይደሉ አኰቴት፣
#ኦ እግዚእየ ኢየሱስ ክርስቶስ ለዓለመ ዓለም።
#ግብረ_ሕማማት
🔱⚜🔱⚜🔱⚜🔱⚜🔱⚜🔱⚜🔱⚜
"ወዳጄ ኾይ! መንፈሳዊ ተጋድሎን አትፍራ፥ ከእርሱም አትሽሽ፡፡ ተጋድሎ ከሌለ ምግባር ትሩፋትም የለምና፡፡ እምነትና ፍቅርም ካልተፈተኑ በእውን ከአንተ ጋር ስለ መኖራቸው እርግጠኛ መኾን አይቻልምና፡፡ እነዚኽ በርግጥ አንተ ገንዘብ አድርገኻቸው እንደኾነ የሚታወቀው መከራ ሲገጥምኽ ነውና፡፡ ስለዚኽ ተጋድሎን አትፍራ፥ ከእርሱም አትሽሽ፡፡"
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
