የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት / His Holiness Patriarch Office
رفتن به کانال در Telegram
نمایش بیشتر
1 678
مشترکین
-124 ساعت
-47 روز
-1430 روز
آرشیو پست ها
የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ ፕሮግራሞች ያስተማራቸውን ደቀመዛሙርት በብፁዕ ወቅዲስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ አስመረቀ።
(ሰኔ 27 ቀን 2018 ዓ/ም )
የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ በሁለተኛ እና በመጀመሪያ ድግሪ ፣ በዲፕሎማ እና በካህናት ሴሚናር መርሐ ግብር በዲፕሎማ ያስተማራቸውን ደቀ መዛሙርት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ፣ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራአስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር አህጉረ ስብከት ሊቀጳጳስ፣
፣ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣የከፍተኛው ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዝጀንት ክብርት አበባ አለበል እና ጥሪ የተደረገላቸው ዕንግዶች በተገኙበት አስመርቋል።
በመርሐ ግብሩ መሠረት ጸሎተ ወንጌልና ጸሎተ ኪዳን በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ደርሷል።
በዩኒቨርሲቲው ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ዶክተር ሪፖርት የቀረበ ሲሆን ብፁዕነታቸው ባቀረቡት ሪፖርት ከእግዚአብሔር ቤት መረቅናችሁ የሚለውን የመጽሐፍ ቃል አብራርተዋል።
የደቀመዛሙርቱን ተልእኮ አስመልክተው በገለጹት ሐሳብ የክርስቶስ ወንጌል አምባሳደሮች ናችሁ ፣በጥበብ ተመሩ፣ተግታችሁ ሥሩ፣ግራ በገባው ዘመን ለሀገራችሁና ለሕዝባችሁ ቅድሚያ ስጡ፣ተስፋ ሳትቆርጡ ተግታችሁ ሥሩ፣ከመከራ በኋላ ደስታ እንዳለ አስቡ፣ የመከራን ዝናብ ታግሣችሁ ሰማያዊ ዘር ዝሩ በማለት ለተመራቂ ደቀመዛሙርቱ መመሪያ ሰጥተዋል፣
ብፁዕነታቸው አክለው እንደገለጹት የኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃን ይታይባችሁ፣ በትምህርት ቆይታችሁ አውቀናል ስትሉ አለማወቅን እንደተማራችሁ እወቁ፣ በችግረኛው ዓለም ችግርን የምትፈቱ እንጂ ችግርን የምትፈጥሩ እንዳትሆኑ የሚል አደራ ብፁዕነታቸው ለተመራቂ ደቀመዛሙርት አስተላልፈዋል።
በዩኒቨርሲቲው ሥርዓተ አስተምህሮ መሠረት ትምህርታቸውን በማጠናቀቅ ለምረቃ የበቁ ደቀ መዛሙርት
በሁለተኛ ዲግሪ 70 በመጀመሪያ ድግሪ 80 በካህናት ዲፕሎማ 39 የማታ የመጀመሪያ ድግሪ 160 በርቀት የመጀመሪያ ድግሪ 206 በድምሩ 555 ደቀ መዛሙርትን ዩኒቨርሲቲው አስመርቋል።
በምረቃ መርሐ ግብሩ መሠረት በተመራቂ ደቀመዛሙርት
"እለ ቅኑታን ኃቔሆሙ በጽድቅ" የሚል ያሬዳዊ ወረብ የተወረበ ሲሆን በቅኔ ምሑራን ቅኔም ቀርበዋል።
ከተመራቂ ደቀ መዛሙርት ዝማሬ በማያያዝ ፕሮፌሰር አባ ኃለ ገብርኤል ግርማ የዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ምክትል ፕሬዚዳንት ባቀረቡት ሪፖርት የመማር ማስተማሩ ሂደት ተጨማሪ ስኬት አስመዝግቧል።እርሱም የመማሪያ መጽሔት ኅትመት ነው ብለዋል። ዩኒቨርሲቲው እያደገ መምጣቱንም አብሥረዋል።
ለተገኘው ስኬት ፕሮፌሰር አባ ኃይለ ገብርኤል የዩኒቨርሲቲውን መምህራን አመስግነዋል።
ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ያጠናቀቁ መሆናቸውን በሪፖርታቸው በይፋ አብሥረዋል።
ለብፁዕነታቸውም ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ስጦታ ተበርክቶላቸዋል። በብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የብዙኃን መገናኛ ቴሌቭዥን ድርጅት ሊቀ ጳጳስ ለብፁዕ ዶክተር አቡነ ፊልጶስ ተጨማሪ ስጦታ አበርክተዋል ።
በመቀጠልም ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገቡ ተመራቂ ደቀ መዛሙርት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
በትምህርታቸው በጣም ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገቡ ተመራቂዎች በቅዱስነታቸው የዋንጫ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
የዩኒቨርሲቲው መምህር የክቡር ረዳት ፕሮፌሰር መኮንን ወርቅነህ የትምህርት ዝግጅትና አገልግሎት ታሪክ በንባብ የቀረበ ሲሆን የዕውቅና ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
ሌሎችም የዩኒቨርሲቲው የረጅም ጊዜ አገልግሎት የሰጡ ነባር ሠራተኞች የዕውቅና ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
ተመራቂ ደቀመዛሙርት ቀጣዩ አገልግሎታቸውን በአንቀጸ ሃይማኖት የተደነገገውን ዶግማ፣ቀኖና እና ትውፊት ጠብቀው ለማገልገል ቃለ መሐላ ፈጽመዋል።
ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ለተመራቂ ደቀመዛሙርት እና ለመርሐ ግብሩ ታደሚዎች ትምህርተ ወንጌል የሰጡ ሲሆን ብፁዕነታቸው ባስተላለፉት የወንጌል መልእክት ቤተ ክርስቲያን ዕድለኛ መሆንዋን፣በአባቶች ፈንታ ልጆች መወለዳቸውን፣ልጆች የአባቶችን ኃላፊነት መረከባቸውን፣ነገር ግን በአሁኑ ጊዜ በአባቶቻቸው የሚተኩ ልጆች እየጠፉ መሆኑን፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ በሰጠው ትምህርት አባቶቻቸው ነቢያት መከራ መቀበላቸውን፣ሐዋርያትም በጨለማውና ባልጫው ዓለም ቀጣይ መከራ እየተቀበሉ ብርሃን መሆናቸውን፣
ተመራቂ ደቀ መዛሙርትም ለጨለመውና ላልጫው ዓለም ብርሃን መሆን የሚገባቸው መሆኑን አብራርተው ገልጸዋል።
ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ በዶክትሬት ድግሪ በመመረቃቸው የእንኳን ደስ አለዎት የመልካም ምኞት መልእክት አስተላልፈዋል።
በመጨረሻም ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ቃለ ምዕዳንና አባታዊ ትምህርት የሰጡ ሲሆን ቅዱስነታቸው ባስተላለፉት አባታዊ ትምህርት ተመራቂ ደቀ መዛሙርት በተማሩት ትምህርት ተግተው እንዲያስተምሩ አባታዊ መመሪያ ሰጥተዋል።
ቅዱስነታቸው በመልእክታቸው አክለው እንደገለጹት ሰው አዋቂ ሆኖ መፈጠሩን፣ በልዩ አፈጣጠር የተፈጠረ ሰው ክብሩን ጥሎ እንደ እንስሳ ማሰብ የማይገባው መሆኑን፣ሰው ክብሩን ካወቀ እንደ እንስሳ የማያስብ መሆኑን፣ትናንት ተማሪ የነበራችሁ ዛሬ መምህራን በመሆን ሰው ፈጣሪውን እንዲአምንና ክብሩን እንዲጠብቅ ሓላፊነታችሁን ልትወጡ ይገባል በማለት የአደራ መልእክት በማስተላለፍ መርሐ ግብሩን በጸሎት አጠናቀዋል።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ የራሺያ ቤተክርስቲያን ልኡካንን በጽ/ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ፣
(ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ም)
ልኡካኑ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት እና ከብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ፣ የራያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንዲሁም ከብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ጋር ሰፊ ውይይት አድርገዋል ።
ከልኡካኑ መካከል የሞስኮ ፓትርያርክ የውጭ አብያተ ክርስቲያናት ግንኙነት መምሪያ ሊቀመንበር የሆኑት የቮሎኮላምስክ ሜትሮፖሊታን አንቶኒ የራሺያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጋር ያላትን መንፈሳዊ አና ታሪካዊ ግንኙነት አንስተው በቀጣይም የጋራ ሥራዎች እንዳሏቸው ገልጸዋል ።
አያይዘውም በሩሲያ የቲዎሎጂ አካዳሚዎች ከፍተኛ ትምህርታቸውን ለመከታተል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አባቶች ወደ ራሺያ ማቅናታቸው በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ለማጠናከር መቻሉን ገልጸዋል።
ብፁዕ አቡነ ፊሊጶስ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ፣የደቡብ ኦሞ እና አሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ በበኩላቸው የራሺያ ቤተክርስቲያን እና የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ያለፉበት መንገድ ተመሣሣይነት ያለው መሆኑን አንስተው በበርካታ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመሥራት መወያየታቸውን ተናግረዋል ።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በአርሲ ሀገረ ስብከት በቤተ ክርስቲያናችን እና በኦርቶዶክሳውያን ላይ የደረሰውን ጥቃት በማስመልከት አባታዊ መልእክት አስተላለፉ።
ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
ቅዱስነታቸው ያስተላለፉት አባታዊ የኀዘን መልእክት እንደሚከተለው ነው፦
መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡
‹‹ወረሰዩ አብድንቲሆሙ ለአግብርቲከ መብልዐ ለአዕዋፈ ሰማይ፣ ወሥጋሆሙኒ ለጻድቃኒከ ለአራዊተ ገዳም፦ የአገልጋዮችህንም በድኖች ለሰማይ ወፎች መብል አደረጉ፥ የቅዱሳንህንም ሥጋ ለምድር አራዊት።››
(መዝሙረ ዳዊት ፸፰፥፪)
በአርሲ ሀገረ ስብከት በአሰኮ፣ በሽርካ፣ በሆንቆሎ፣ በዋቤ እና በሙኔሳ ወረዳዎች በመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችንና በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ላይ ስለደረሰው አሰቃቂ ጥቃት የሰማነው በተሰበረ ልብ ነው።
የእምነት ነፃነት ተደፍሮ መቶ ዓመታት ያስቆጠረው የጠላታ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በተቃጠለበት፣ እንዲሁም የካራ ኩፍቴና መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን በተዘረፈበት በዚህ ክፉ ቀን፤ በርካታ ምእመናን በግፍ መሰዋታቸውና በመቶዎች የሚቆጠሩ ወገኖቻችን ከቀዬአቸው መፈናቀላቸው ቤተ ክርስቲያናችንን በእጅጉ ያሳዘነ ክስተት ነው።
የሰላም፣ የፍቅርና የታሪክ ማህደር የሆነችው ቤተ ክርስቲያን በምድራዊ መከራ ውስጥ ያሉትን ምእመናን በምታጽናናበት በዚህ ወቅት ራሷ በፈተና ውስጥ ሆና ከመቸገሯም በላይ በአርሲ ምድር በተደጋጋሚ የሚስተዋለው በደልና ግፍ በሁላችንም ልቡና ውስጥ "እስከ መቼ?" የሚል የቁጭት እና የኀዘን ጥያቄን ፈጥሯል።
በመሆኑም ይህ መከራ እያበቃ ሳይሆን እየሰፋ በመምጣቱ የዜጎችን ደኅንነት የመጠበቅና ሰላምን የማስፈን አደራ የተጣለባችሁ የጸጥታ አካላትና በየመዋቅሩ ያላችሁ ሓላፊዎች ከምንም በላይ ታሪክ የሚጠይቃችሁ በሥልጣን ዘመናችሁ ለዜጎች ደኅንነት በምትከፍሉት ዋጋ ነውና ይህንን የጥቃት ሰንሰለት በማስቆምና ወንጀለኞችን ለሕግ በማቅረብ ከታሪክ ባለዕዳነት ትድኑ ዘንድ በቤተ ክርስቲያናችን ስም አበክረን እናሳስባለን።
በየአካባቢው የምትገኙ ምእመናንና መላው ኢትዮጵያውያንም በወንድማማችነት መንፈስ ተጋግዛችሁ፣ የተፈናቀሉ ወገኖችን በመደገፍና በጸሎት ከቤተክርስቲያናችን ጎን እንድትሆኑ ጥሪያችንን እናቀርባለን።
በመጨረሻም ቤተ ክርስቲያናችን ለሰላም፣ ለይቅርታና ለሰው ልጆች ክብር ሁል ጊዜ የምትቆም መሆኑን በመግለጽ ይህንን የኀዘን ሰዓት አምላካችን በምሕረቱ ያሳልፍልን፣ የሞቱትን ነፍሶቻቸውን በመንግሥቱ ይቀበልልን፣ የተጎዱትንም በቸርነቱ ያጽናናልን በማለት አባታዊ የኀዘን መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን።
እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
አሜን።
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
__________
#የቅዱስ_ፓትርያርኩ_ሓዋርያዊ_አገልግሎቶች እና ወቅታዊ የሆኑ ጉዳዮችን_ለማግኘት:-
ከታች ያለውን link #share, Like & #follow ያድርጉ
👇👇👇👇
1.ድረ-ገጽ:- eotcp.org
2. ቴሌግራም:- https://t.me/EOTCPatriarichate
3 ፌስቡክ ;- https://www.facebook.com/EotcpatriarchateOffice?mibextid=ZbWKwL
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ በቫቲካን በቅድስት መንበር የምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ክፍል ኃላፉ ብፁዕ ካሪዲናል ክላውዲዮ ጉጀሮቲን በቢሮአቸው ተቀብለው አነጋገሩ።
ዛሬ ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በቫቲካን በቅድስት መንበር የምሥራቅ ክርስቲያናት ክፍል ኃላፉ ብፁዕ ካሪዲናል ክላውዲዮ ጉጀሮቲን በቢሮአቸው ተቀብለው አነጋገሩ፡፡
ቅዱስነታቸው ልዑካኑን “ወደ ኢትዮጵያ ለጉብኝት እንኳን ደህና መጣችሁ፣ ወደ መንበረ ፓትርያርክ ለመጎብኘት ስለመጣችሁ ደስ ብሎናል፤ መልካም የጉብኝት ወቅት ያድርግላችሁ” በማለት መልካም ምኞታቸውን ለልዑካኑ ገልጸዋል፡፡
ብፁዕ ካሪዲናል ክላውዲዮ ጉጀሮቲም እንደተናገሩት “በመጀመሪያ መልእክቴ በፖፕ ሊዮ የተላከ የፍቅር መልእክት ለማድረስ ነው፡፡ ወደዚህች ምስጠራዊ ሀገር፣ የብዙ ሰማዕታት፣ መነኮሳት፣ የብዙ መንፈሳውያን ሀገር ወደ ሆነችው ኢትዮጵያ የመጣሁት” ሲሉ ደስታቸውን ገልጸዋል፡፡ ካርዲናል ክላውዲዮ አያይዘውም “በዓለማችን በክርስቲያኖች ላይ እየተላለፈ ያለው ጥላቻ እየጨመረ መጥቷል፤ በዚህ ጉዳይ በቫቲካን ያለንም ሐሳብ ውስጥ ገብተናል፤ ክርስቲኖችን ለመታደግ በአንድነት አብረን መሥራት አለብን” ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በመጨረሻም ቅዱስነታቸው እንደተናገሩት “ሁላችንም በችግር ውስጥ ነው ያለነው፤ በዚህ ወቅት በኅብረት መሥራት፣ መነጋገር አስፈላጊም፣ ወቅታዊም ጉዳይ ነው፡፡ እኛ ክርስቲያኖች ያለን መሣሪያ ጸሎትና ምህላ ብቻ ነው፡፡” ሲሉ አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ግቢ ውስጥ የተገነባውን የአብነት ትምህርት ቤት ባርከው ሥራ አስጀመሩ።
በቅዱስነታቸው ቡራኬ የተመረቀው ይህ የአብነት ትምህርት ቤት ክቡር ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም ከባለቤታቸው ክብርት ወ/ሮ ኢትዮጵያ ጥላሁን ጋር ከ133 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ አድርገው ያስገነቡት ነው።
በዚሁ የምርቃት መርሐ ግብር ከቅዱስ አባታችን በተጨማሪ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፤ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ ሀድያና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ሌሎችም ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ተገኝተዋል።
በተጨማሪም ሊቀ ሥልጣናት ቆሞስ አባ ሲራክ አድማሱ የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል አስተዳዳሪ ፣ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ፣ ካህናት አባቶች ፣ በአብነት ትምህርት ቤቱ ግንባታ ላይ የተሳተፉ መሐንዲሶች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
ቅዱስነታቸው በምርቃቱ ላይ ቃለ ምእዳንና ቡራኬ ሲሰጡ "ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም የአብነት ትምህርት ቤት መገንባታቸው የቅድስት ቤተክርስቲያንን መሠረት የሚያጸና ሊቃውንትን ፣ ካህናትን ሊአስገኝ የሚችል ከሁሉም የበለጠ ለቅድስት ቤተክርስቲያን የሚጠቅም በጎ ተግባር ነው" ብለዋል።
ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን ኦርቶዶክሳዊያን ባለፀጋዎች ልክ እንደ ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም እግዚአብሔር ባርኮ የሰጣቸውን ሀብት ለትውልድ በሚጠቅም ዘመን ተሻጋሪ ሥራ ላይ አውለው በረከት እንዲያገኙም አባታዊ ጥሪ አቅርበዋል።
በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የተመረቀውን የአብነት ያስገነቡት ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም ባስተላለፉት መልእክት ደግሞ "በሕይወቴ የሚያስደስተኝ ቤተክርስቲያን ሲተከል የአብነት ትምህርት ቤትም አብሮ ሲሠራ ነው" ተብለዋል ።
ቢትወደድ ባሕሩ አክለውም በዚህ ታሪካዊ ካቴድራል ግቢ ውስጥ የአብነት ትምህርት ቤት ያስገነቡት "የአሁኑ ትውልድ ጥንታዊውን የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ትምህርት በተመቻቸ መልኩ እንዲማር" ስለሚፈልጉ መሆኑንም ጠቁመዋል።
ዛሬ ግንቦት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ለመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የአብነት ትምህርት ቤት ሠርተው ያስረከቡት ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም ከባለቤታቸው ክብርት ወ/ሮ ኢትዮጵያ ጥላሁን ጋር ከዚህን ቀደም በልዩ ልዩ የአገራችን ክፍሎች በርካታ አብያተ ክርስቲያናትንና የአብነት ትምህርት ቤቶችን ማሳነጻቸው ይታወቃል።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከ፣ የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ።
ግንቦት 16 ቀን 2018 ዓ.ም
በዕለቱ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ፤ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፤ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊ የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፤ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መገናኛ ብዙኀን ድርጅት የበላይ ሓላፊ የሰሜንና ምሥራቅ አፍሪካ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስን ጨምሮ ሌሎችም ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ተገኝተዋል።
በተጨማሪ የሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የሥራ ሓላፊዎች ፤ አገልጋይ ካህናትና ፤ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ፣ ዘማሪያንና በርካታ ምእመናን ቅዳሴ ቤቱ ሲከበር የበረከቱ ተካፋይ ሁነዋል።
በዚሁ መርሐ ግብር ታቦተ ሕጉ ከመንበሩ ወጥቶ ምእመናንን የባረከ ሲሆን በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እና በሰንበት ትምህርት ቤት ዘማርያን ሕንጻ ቤተክርስቲያኑ ቅዱስ ፓትርያርኩን ጨምሮ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ቡራኬ ለምርቃት መብቃቱንና የቅዳሴ ቤቱ መከበሩን የሚያዘክር ያሬዳዊ ጥዑመ ዜማ ቀርቧል።
ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መገናኛ ብዙኀን ድርጅት የበላይ ሐላፊ የሰሜንና ምሥራቅ አፍሪካ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት ትምህርት ደግሞ በአዲሱ ሕንጻ ቤተክርስቲያን "ቅዳሴው በሊቃነ ጳጳሳት ተቀድሶበታል ፣ሕፃናት አረጋዊያንም ቆርበውበታል ፣ከዚህ የበለጠ ደስታ ምንም ነገር የለም ፣ እንኳን ደስ ያላችሁ" ብለዋል።
ብፁዕነታቸው አክለውም ይህ ሕንጻ ቤተክርስቲያን እንዲጠናቀቅ መመሪያ ሰጥተው ግንቦት 16 ቀን 2018 ዓ.ም ቅዳሴ ቤቱ እንዲከበር ላደረጉት ለብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና ሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ምስጋና ይገባቸዋል ሲሉም ተደምጠዋል።
ከዚህ በመቀጠል የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ግንባታ ለፍፃሜው እንዲበቃ ገንዘባቸውን ፣ እውቀታቸውንና ጊዜያቸውን በበጎ ፈቃደኝነት የሰጡ እንዲሁም በአስተባባሪነት ፣ በልዩ ልዩ የሥራ ድርሻዎችና ሓላፊነቶች የጎላ ድርሻ የነበራቸው ሁሉ ከቅዱስ አባታችን ሽልማት ወስደዋል።
በመጨረሻም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሰጡት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ "እግዚአብሔር አምላክ ይህንን ሕንጻ ቤተክርስቲያን ለማነፅ አነሳስቶ ስላስፈፀማችሁ እንኳን ደስ ያላችሁ" ብለዋል።
ቅዱስ አባታችን ለለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን ምእመናን "ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተላለፈ ለብዙ ዘመናት መገልገያ የሚሆናችሁን እግዚአብሔርን የምታመሰግኑበት ፣ የምትቆርቡበትን ሕንፃ ቤተክርስቲያን ነው የገነባችሁትና እንኳን ደስ ያላችሁ" ሲሉም አክለዋል።
ቅዱስነታቸው "ከዛሬ ጀምሮ ይህንን አዲስ ሕንጻ ቤተክርስቲያን ካቴድራል ብለነዋል" ያሉ ሲሆን ቤተክርስቲያኑ በስያሜው ልክ መሆን ስለሚገባው ትምህርት ቤትና ሌሎችንም ከዚህ የበለጠ ልማት ሊሰራበት እንደሚገባ አመላክተዋል።
ከ100 ሚሊየን ብር በላይ ፈሰስ ተደርጎበት ለምርቃት የበቃው የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ጥር 29 ቀን 2002 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ ዶክተር አቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚደንት፣ የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት ለሰላም የክብር ፕሬዚደንት፣ የዓለም የሰላም አምባሳደር የመሰረት ድንጋይ ተቀምጦለት ግንባታው መጀመሩ ይታወቃል።
اکنون در دسترس! پژوهش تلگرام ۲۰۲۵ — مهمترین بینشهای سال 
