የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት / His Holiness Patriarch Office
Ir al canal en Telegram
Mostrar más
1 686
Suscriptores
-124 horas
-47 días
-2230 días
Archivo de publicaciones
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ የራሺያ ቤተክርስቲያን ልኡካንን በጽ/ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ፣
(ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ም)
ልኡካኑ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት እና ከብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ፣ የራያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንዲሁም ከብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ጋር ሰፊ ውይይት አድርገዋል ።
ከልኡካኑ መካከል የሞስኮ ፓትርያርክ የውጭ አብያተ ክርስቲያናት ግንኙነት መምሪያ ሊቀመንበር የሆኑት የቮሎኮላምስክ ሜትሮፖሊታን አንቶኒ የራሺያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጋር ያላትን መንፈሳዊ አና ታሪካዊ ግንኙነት አንስተው በቀጣይም የጋራ ሥራዎች እንዳሏቸው ገልጸዋል ።
አያይዘውም በሩሲያ የቲዎሎጂ አካዳሚዎች ከፍተኛ ትምህርታቸውን ለመከታተል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አባቶች ወደ ራሺያ ማቅናታቸው በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ለማጠናከር መቻሉን ገልጸዋል።
ብፁዕ አቡነ ፊሊጶስ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ፣የደቡብ ኦሞ እና አሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ በበኩላቸው የራሺያ ቤተክርስቲያን እና የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ያለፉበት መንገድ ተመሣሣይነት ያለው መሆኑን አንስተው በበርካታ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመሥራት መወያየታቸውን ተናግረዋል ።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በአርሲ ሀገረ ስብከት በቤተ ክርስቲያናችን እና በኦርቶዶክሳውያን ላይ የደረሰውን ጥቃት በማስመልከት አባታዊ መልእክት አስተላለፉ።
ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
ቅዱስነታቸው ያስተላለፉት አባታዊ የኀዘን መልእክት እንደሚከተለው ነው፦
መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡
‹‹ወረሰዩ አብድንቲሆሙ ለአግብርቲከ መብልዐ ለአዕዋፈ ሰማይ፣ ወሥጋሆሙኒ ለጻድቃኒከ ለአራዊተ ገዳም፦ የአገልጋዮችህንም በድኖች ለሰማይ ወፎች መብል አደረጉ፥ የቅዱሳንህንም ሥጋ ለምድር አራዊት።››
(መዝሙረ ዳዊት ፸፰፥፪)
በአርሲ ሀገረ ስብከት በአሰኮ፣ በሽርካ፣ በሆንቆሎ፣ በዋቤ እና በሙኔሳ ወረዳዎች በመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችንና በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ላይ ስለደረሰው አሰቃቂ ጥቃት የሰማነው በተሰበረ ልብ ነው።
የእምነት ነፃነት ተደፍሮ መቶ ዓመታት ያስቆጠረው የጠላታ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በተቃጠለበት፣ እንዲሁም የካራ ኩፍቴና መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን በተዘረፈበት በዚህ ክፉ ቀን፤ በርካታ ምእመናን በግፍ መሰዋታቸውና በመቶዎች የሚቆጠሩ ወገኖቻችን ከቀዬአቸው መፈናቀላቸው ቤተ ክርስቲያናችንን በእጅጉ ያሳዘነ ክስተት ነው።
የሰላም፣ የፍቅርና የታሪክ ማህደር የሆነችው ቤተ ክርስቲያን በምድራዊ መከራ ውስጥ ያሉትን ምእመናን በምታጽናናበት በዚህ ወቅት ራሷ በፈተና ውስጥ ሆና ከመቸገሯም በላይ በአርሲ ምድር በተደጋጋሚ የሚስተዋለው በደልና ግፍ በሁላችንም ልቡና ውስጥ "እስከ መቼ?" የሚል የቁጭት እና የኀዘን ጥያቄን ፈጥሯል።
በመሆኑም ይህ መከራ እያበቃ ሳይሆን እየሰፋ በመምጣቱ የዜጎችን ደኅንነት የመጠበቅና ሰላምን የማስፈን አደራ የተጣለባችሁ የጸጥታ አካላትና በየመዋቅሩ ያላችሁ ሓላፊዎች ከምንም በላይ ታሪክ የሚጠይቃችሁ በሥልጣን ዘመናችሁ ለዜጎች ደኅንነት በምትከፍሉት ዋጋ ነውና ይህንን የጥቃት ሰንሰለት በማስቆምና ወንጀለኞችን ለሕግ በማቅረብ ከታሪክ ባለዕዳነት ትድኑ ዘንድ በቤተ ክርስቲያናችን ስም አበክረን እናሳስባለን።
በየአካባቢው የምትገኙ ምእመናንና መላው ኢትዮጵያውያንም በወንድማማችነት መንፈስ ተጋግዛችሁ፣ የተፈናቀሉ ወገኖችን በመደገፍና በጸሎት ከቤተክርስቲያናችን ጎን እንድትሆኑ ጥሪያችንን እናቀርባለን።
በመጨረሻም ቤተ ክርስቲያናችን ለሰላም፣ ለይቅርታና ለሰው ልጆች ክብር ሁል ጊዜ የምትቆም መሆኑን በመግለጽ ይህንን የኀዘን ሰዓት አምላካችን በምሕረቱ ያሳልፍልን፣ የሞቱትን ነፍሶቻቸውን በመንግሥቱ ይቀበልልን፣ የተጎዱትንም በቸርነቱ ያጽናናልን በማለት አባታዊ የኀዘን መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን።
እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
አሜን።
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
__________
#የቅዱስ_ፓትርያርኩ_ሓዋርያዊ_አገልግሎቶች እና ወቅታዊ የሆኑ ጉዳዮችን_ለማግኘት:-
ከታች ያለውን link #share, Like & #follow ያድርጉ
👇👇👇👇
1.ድረ-ገጽ:- eotcp.org
2. ቴሌግራም:- https://t.me/EOTCPatriarichate
3 ፌስቡክ ;- https://www.facebook.com/EotcpatriarchateOffice?mibextid=ZbWKwL
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ በቫቲካን በቅድስት መንበር የምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ክፍል ኃላፉ ብፁዕ ካሪዲናል ክላውዲዮ ጉጀሮቲን በቢሮአቸው ተቀብለው አነጋገሩ።
ዛሬ ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በቫቲካን በቅድስት መንበር የምሥራቅ ክርስቲያናት ክፍል ኃላፉ ብፁዕ ካሪዲናል ክላውዲዮ ጉጀሮቲን በቢሮአቸው ተቀብለው አነጋገሩ፡፡
ቅዱስነታቸው ልዑካኑን “ወደ ኢትዮጵያ ለጉብኝት እንኳን ደህና መጣችሁ፣ ወደ መንበረ ፓትርያርክ ለመጎብኘት ስለመጣችሁ ደስ ብሎናል፤ መልካም የጉብኝት ወቅት ያድርግላችሁ” በማለት መልካም ምኞታቸውን ለልዑካኑ ገልጸዋል፡፡
ብፁዕ ካሪዲናል ክላውዲዮ ጉጀሮቲም እንደተናገሩት “በመጀመሪያ መልእክቴ በፖፕ ሊዮ የተላከ የፍቅር መልእክት ለማድረስ ነው፡፡ ወደዚህች ምስጠራዊ ሀገር፣ የብዙ ሰማዕታት፣ መነኮሳት፣ የብዙ መንፈሳውያን ሀገር ወደ ሆነችው ኢትዮጵያ የመጣሁት” ሲሉ ደስታቸውን ገልጸዋል፡፡ ካርዲናል ክላውዲዮ አያይዘውም “በዓለማችን በክርስቲያኖች ላይ እየተላለፈ ያለው ጥላቻ እየጨመረ መጥቷል፤ በዚህ ጉዳይ በቫቲካን ያለንም ሐሳብ ውስጥ ገብተናል፤ ክርስቲኖችን ለመታደግ በአንድነት አብረን መሥራት አለብን” ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በመጨረሻም ቅዱስነታቸው እንደተናገሩት “ሁላችንም በችግር ውስጥ ነው ያለነው፤ በዚህ ወቅት በኅብረት መሥራት፣ መነጋገር አስፈላጊም፣ ወቅታዊም ጉዳይ ነው፡፡ እኛ ክርስቲያኖች ያለን መሣሪያ ጸሎትና ምህላ ብቻ ነው፡፡” ሲሉ አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ግቢ ውስጥ የተገነባውን የአብነት ትምህርት ቤት ባርከው ሥራ አስጀመሩ።
በቅዱስነታቸው ቡራኬ የተመረቀው ይህ የአብነት ትምህርት ቤት ክቡር ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም ከባለቤታቸው ክብርት ወ/ሮ ኢትዮጵያ ጥላሁን ጋር ከ133 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ አድርገው ያስገነቡት ነው።
በዚሁ የምርቃት መርሐ ግብር ከቅዱስ አባታችን በተጨማሪ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፤ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ ሀድያና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ሌሎችም ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ተገኝተዋል።
በተጨማሪም ሊቀ ሥልጣናት ቆሞስ አባ ሲራክ አድማሱ የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል አስተዳዳሪ ፣ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ፣ ካህናት አባቶች ፣ በአብነት ትምህርት ቤቱ ግንባታ ላይ የተሳተፉ መሐንዲሶች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
ቅዱስነታቸው በምርቃቱ ላይ ቃለ ምእዳንና ቡራኬ ሲሰጡ "ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም የአብነት ትምህርት ቤት መገንባታቸው የቅድስት ቤተክርስቲያንን መሠረት የሚያጸና ሊቃውንትን ፣ ካህናትን ሊአስገኝ የሚችል ከሁሉም የበለጠ ለቅድስት ቤተክርስቲያን የሚጠቅም በጎ ተግባር ነው" ብለዋል።
ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን ኦርቶዶክሳዊያን ባለፀጋዎች ልክ እንደ ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም እግዚአብሔር ባርኮ የሰጣቸውን ሀብት ለትውልድ በሚጠቅም ዘመን ተሻጋሪ ሥራ ላይ አውለው በረከት እንዲያገኙም አባታዊ ጥሪ አቅርበዋል።
በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የተመረቀውን የአብነት ያስገነቡት ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም ባስተላለፉት መልእክት ደግሞ "በሕይወቴ የሚያስደስተኝ ቤተክርስቲያን ሲተከል የአብነት ትምህርት ቤትም አብሮ ሲሠራ ነው" ተብለዋል ።
ቢትወደድ ባሕሩ አክለውም በዚህ ታሪካዊ ካቴድራል ግቢ ውስጥ የአብነት ትምህርት ቤት ያስገነቡት "የአሁኑ ትውልድ ጥንታዊውን የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ትምህርት በተመቻቸ መልኩ እንዲማር" ስለሚፈልጉ መሆኑንም ጠቁመዋል።
ዛሬ ግንቦት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ለመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የአብነት ትምህርት ቤት ሠርተው ያስረከቡት ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም ከባለቤታቸው ክብርት ወ/ሮ ኢትዮጵያ ጥላሁን ጋር ከዚህን ቀደም በልዩ ልዩ የአገራችን ክፍሎች በርካታ አብያተ ክርስቲያናትንና የአብነት ትምህርት ቤቶችን ማሳነጻቸው ይታወቃል።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከ፣ የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ።
ግንቦት 16 ቀን 2018 ዓ.ም
በዕለቱ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ፤ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፤ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊ የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፤ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መገናኛ ብዙኀን ድርጅት የበላይ ሓላፊ የሰሜንና ምሥራቅ አፍሪካ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስን ጨምሮ ሌሎችም ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ተገኝተዋል።
በተጨማሪ የሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የሥራ ሓላፊዎች ፤ አገልጋይ ካህናትና ፤ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ፣ ዘማሪያንና በርካታ ምእመናን ቅዳሴ ቤቱ ሲከበር የበረከቱ ተካፋይ ሁነዋል።
በዚሁ መርሐ ግብር ታቦተ ሕጉ ከመንበሩ ወጥቶ ምእመናንን የባረከ ሲሆን በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እና በሰንበት ትምህርት ቤት ዘማርያን ሕንጻ ቤተክርስቲያኑ ቅዱስ ፓትርያርኩን ጨምሮ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ቡራኬ ለምርቃት መብቃቱንና የቅዳሴ ቤቱ መከበሩን የሚያዘክር ያሬዳዊ ጥዑመ ዜማ ቀርቧል።
ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መገናኛ ብዙኀን ድርጅት የበላይ ሐላፊ የሰሜንና ምሥራቅ አፍሪካ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት ትምህርት ደግሞ በአዲሱ ሕንጻ ቤተክርስቲያን "ቅዳሴው በሊቃነ ጳጳሳት ተቀድሶበታል ፣ሕፃናት አረጋዊያንም ቆርበውበታል ፣ከዚህ የበለጠ ደስታ ምንም ነገር የለም ፣ እንኳን ደስ ያላችሁ" ብለዋል።
ብፁዕነታቸው አክለውም ይህ ሕንጻ ቤተክርስቲያን እንዲጠናቀቅ መመሪያ ሰጥተው ግንቦት 16 ቀን 2018 ዓ.ም ቅዳሴ ቤቱ እንዲከበር ላደረጉት ለብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና ሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ምስጋና ይገባቸዋል ሲሉም ተደምጠዋል።
ከዚህ በመቀጠል የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ግንባታ ለፍፃሜው እንዲበቃ ገንዘባቸውን ፣ እውቀታቸውንና ጊዜያቸውን በበጎ ፈቃደኝነት የሰጡ እንዲሁም በአስተባባሪነት ፣ በልዩ ልዩ የሥራ ድርሻዎችና ሓላፊነቶች የጎላ ድርሻ የነበራቸው ሁሉ ከቅዱስ አባታችን ሽልማት ወስደዋል።
በመጨረሻም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሰጡት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ "እግዚአብሔር አምላክ ይህንን ሕንጻ ቤተክርስቲያን ለማነፅ አነሳስቶ ስላስፈፀማችሁ እንኳን ደስ ያላችሁ" ብለዋል።
ቅዱስ አባታችን ለለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን ምእመናን "ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተላለፈ ለብዙ ዘመናት መገልገያ የሚሆናችሁን እግዚአብሔርን የምታመሰግኑበት ፣ የምትቆርቡበትን ሕንፃ ቤተክርስቲያን ነው የገነባችሁትና እንኳን ደስ ያላችሁ" ሲሉም አክለዋል።
ቅዱስነታቸው "ከዛሬ ጀምሮ ይህንን አዲስ ሕንጻ ቤተክርስቲያን ካቴድራል ብለነዋል" ያሉ ሲሆን ቤተክርስቲያኑ በስያሜው ልክ መሆን ስለሚገባው ትምህርት ቤትና ሌሎችንም ከዚህ የበለጠ ልማት ሊሰራበት እንደሚገባ አመላክተዋል።
ከ100 ሚሊየን ብር በላይ ፈሰስ ተደርጎበት ለምርቃት የበቃው የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ጥር 29 ቀን 2002 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ ዶክተር አቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚደንት፣ የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት ለሰላም የክብር ፕሬዚደንት፣ የዓለም የሰላም አምባሳደር የመሰረት ድንጋይ ተቀምጦለት ግንባታው መጀመሩ ይታወቃል።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ።
ግንቦት 4 ቀን 2018 ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
ቅዱስነታቸው ያስተላለፉት አባታዊ መልእክት እንደሚከተለው ነው፦
መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡
‹‹ተዘከሩ መቁሓነ ዘከመ ተሞቃሕክሙ ምስሌሆሙ ወእለ ተሣቀዩ ከመ ዘሀለውክሙ በሥጋክሙ፡-
ከእነርሱ ጋር አብራችኋቸው እንደታሰራችሁ ሆናችሁ እስረኞችን ዐስቡ፤ መከራ የጸናባቸውንም በሥጋችሁ ከእነርሱ ጋር እንዳላችሁ ሆናችሁ ዐስቡ››
(ዕብ. 13፡3)
እውነተኛ እምነትም ሆነ ጤናማ አመለካከት የሚመዘነው መከራ ስለሚቀበሉ ሰዎች ሰምቶና አይቶ በዝምታ ባለማለፍ፤ ይልቁንም በእነርሱ ሕመም ውስጥ ራስን በማስገባት በሚሰማው ጥልቅ ኀዘን እና በሚደረገው ድጋፍ ነው፡፡ ይልቁንም በዚች ዓለም የምንኖር ለችግርና ለመከራ ቅርብ እንደመሆናችን የታሰሩትን መጎብኘት፣ የተገፉትን ማጽናናት፣ በስደት ምድር ላይ ሆነው በሞት ፍርድ የሚጨነቁትን ወገኖች ስቃይም እንደራሳችን ስቃይ በመቁጠር ስለእነርሱ ድምፅ መሆንና ማዘን ስንችል በሰማያዊው መንግሥት የማይጠፋ የጽድቅ ዋጋን እናከማቻለን፡፡
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን!
እረኛ በበረት ውስጥ ያለችው አንዲት በግ ስትጠፋ ወይም ለአደጋ ስትጋለጥ ዝም ብሎ እንደማያይ ሁሉ፣ በሳዑዲ ዓረቢያ ምድር በሞት ጥላ ሥር ሆነው ‹‹የፍትሕ ያለህ›› እያሉ የሚጮኹ፤ በጭንቀት ቀናትን የሚቆጥሩና ድምፅ የሌላቸው ኢትዮጵያውያን ልጆቻችን የተሻለ ኑሮ እናገኛለን ብለው በተሰደዱበት ሀገር ሕይወታቸው በጅምላ ሊቀጠፍ እንደሆነ መረጃውን ከልዩ ልዩ መገናኛ ብዙኃን የተገነዘብን በመሆኑ የዲፕሎማሲ ግንኙነት ጠቀሜታው የሰው ልጆችን ሕይወት ለመጠበቅ ነውና የኢትዮጵያ መንግሥት በከፍተኛ ደረጃ ከሚገኙ ከሳዑዲ ባለሥልጣናት ጋር በመነጋገር በግፍ የተፈረደባቸው ልጆቻችን የሞት ፍርድ እንዲነሳላቸውና ወደ ሀገራቸው የሚመለሱበት መንገድ ይመቻች ዘንድ የተጀመሩ ሥራዎች ልዩ ትኩረት እንዲሰጥባቸው፤ ወገኖቻችንም በቋንቋ እጥረትና በሕግ አማካሪ እጦት ለሞት እንዳይዳረጉ ከአደራ ጭምር እናሳስባለን ፡፡
እግዚአብሔር አምላክ ለሰው ልጅ የሰጠው ታላቅ ስጦታ ሕይወት ነው፤ "አትግደል" የሚለው ሕግም በማንኛውም ምድርና ቋንቋ የሚሠራ ሲሆን ፍርድ ያለ ምሕረት ከሆነ አምላካዊ ቁጣን ይጋብዛልና የሳዑዲ ባለሥልጣናት የሁለቱን ሀገራት የቆየ ታሪክና ወዳጅነት አስበው፣ በሞት ፍርድ ጥላ ሥር ላሉት ወገኖቻችን ምሕረትን እንዲያደርጉ፣ ቅጣቱንም ወደ እስራት እንዲቀይሩ በአባታዊ ርኅራኄ እንጠይቃለን ፡፡
ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችም በማያውቁት ቋንቋ እንዲሁም ባልተረዱት የሕግ ሂደት ሞት የተፈረደባቸውን ወገኖች ስቃይ ተመልክተው የፍትሕ መዛባትን እንዲቃወሙና የንጹሐንን ነፍስ እንዲታደጉ ጥሪያችንን እናቀርባለን።
በመጨረሻም፣ ማንኛውም በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረ ሰው ሕይወቱ ሊጠፋ አይገባምና ኦርቶዶክሳውያን ልጆቻችን የክርስትናችን አንዱ መገለጫ የአንደኛው ወገን ሕመምን በጋራ መካፈል እንደሆነ ተረድታችሁ ወደ ፈጣሪያችን በጸሎት እንድትማጸኑ፤ መላው ኢትዮጵያውያንም ለመፍትሔው የበኩላችሁን ጥረት እንድታደርጉ ስንል አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን።
እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
አሜን።
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
ግንቦት 4 ቀን 2018 ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ የግንቦት ርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የመክፈቻ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ።
መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
በስመ ኣብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ኣሓዱ ኣምላክ ኣሜን!
ብፁዕ ኣቡነ ሳዊሮስ
የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ስራ ኣስኪያጅ፤
ብፁዕ ኣቡነ ዲዮስቆሮስ
የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ፤
ብፁዕ ኣቡነ ሕርያቆስ
የኣዲስ ኣበባ ሃገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣
ብፁዓን ኣበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ ኣባላት፣
በኣጠቃላይ በዚህ ዓመታዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልኣተ ጉባኤ የተገኛችሁ በሙሉ፦
ማሕየዊት በምትሆን ሞቱ ሰማያውያንና ምድራውያንን ያስታረቀ፣ በቅድስት ትንሣኤውም የሙታንን ሕይወት በተስፋ ያለመለመ ጌታችን፣ ኣምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ እንኳን ለዓመታዊው የረክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልኣተ ጉባኤ ኣደረሰን ኣደረሳችሁ!
“እስመ ተዋለጠ እግዚአብሔር ዓለመ በክርስቶስ ኣናኅስዮ ኃጢኣቶሙ ወኢነጺሮ ጌጋዮሙ፤ ወረሰየ ላዕሌነ ቃለ ሥምረቱ፤ ወወሃበነ መልእክተ ሣህሉ፡- እግዚአብሔር በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከራሱ ጋር ያስታርቅ ነበርና በደላቸውን ኣይቈጥርባቸውም ነበር፤ በእኛም የማስታረቅ ቃል ኣኖረ” (2ቆሮ. 5፥19)።
የእግዚአብሔርም ልጅ፣ የሰውም ልጅ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም በሰብእነት ሲገለጽ ግልጽ የሆነ ዓላማና ግብ እንደነበረው ቅዱስ መጽሓፍ ይነግረናል፤ እሱም በሰማይም፣ በምድርም ያሉትን በሙሉ ማስታረቅ፣ ማገናኘትና ኣንድ ማድረግ ነበረ፤
ጌታችን ይህንን ሲያደርግ ሰማያውያኑንና ምድራውያኑን የለያየው ምክንያት በማስወገድ ነው፤ የመለያየቱ ምክንያት ክፉ ኅሊና ኣምጦ የወለደው በደልና እሱን ተከትሎ የተከሠተው ኃጢኣት ነበረ፤ በኃጢኣት ምክንያት የገባው ሞት ደግሞ የቅጣቱ ማሳያ ፍርድ ነበረ።
የመጀመሪያዎቹ ሰዎች በፈጸሙት ስሕተት መነሻነት ምድርንና ምድራውያንን ለከባድ ቅጣትና መርገም የዳረገው ይህ መለያየት ለሰማያውያኑም ተርፎኣል፤
ምክንያቱም መለያየቱ በእግዚአብሔርና በሰው፣ በመላእክትና በሰው፣ በሰውና በሰው፣ በነፍስና በሥጋ ጭምር የጥል ግድግዳን ገንብቶ እስከ ክርስቶስ ዕለተ ስቅለት መዝለቁን በቅዱስ መጽሓፍ የምናውቀው ስለሆነ ማለት ነው።
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ ኣባላት!
ቀዳማዊና ዘላለማዊ የሆነው ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ሰብእናችንን ተዋሕዶ በዚህ ዓለም የተገለጸው ሰማያውያንንና ምድራውያንን የለያየው የጥል ግድግዳን ለማፈራረስ ነው፤
ለመለያየት ምክንያት የሆነችውን ኃጢኣት በሰውነቱ በመቅጣት የሕግን ትእዛዝ ከፈጸመ በኋላ የዕርቁን ተግባር በወሳኝ መልኩ ኣከናውኖታል፤
በክርስቶስ ቤዛነት የሆነው ይህ ዕርቅ በእግዚአብሔር ዘንድ እጅግ የተወደደ ነበረና እሱ ራሱ በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከራሱ ጋር ኣስታረቀ፤
ለዚህም ነው ተበዳይ እሱ፣ ቤዛዊ መሥዋዕት ሆኖ የቀረበው እሱ፣ ኣስታራቂ እሱ፣ ታራቂ እሱ ሆኖ የምናገኘው፤ ለሱ የሚሳነው ነገር የለምና ለኛ ግር የሚል ቢመስልም ለሱ ቀላል ነበረ።
በዚህ የዕርቅ ተግባር ሰውና እግዚአብሔር፣ ሰውና መላእክት፣ ሰውና ሰው፣ ነፍስና ሥጋ ታርቀው በይፋ ተገናኙ፤ በኅብረትና በኣንድነትም መኖር ቻሉ፤ በቀኙ ለተሰቀለው ሽፍታ “ዛሬውኑ ከኔ ጋር በገነት ትኖራለህ” የሚለው ቃለ ምሕረትና “ኣባት ሆይ፥ ነፍሴን በእጅህ ኣደራ እሰጣለሁ” የሚለው ቃለ ኣማሕፅኖ የዕርቁ፣ የግንኙነቱና የኣንድነቱ ማሳያ ኣስረጅ ናቸው።
ስቅለተ ክርስቶስ ነፍሶቻችን ወደ ግዞት ቤት ሳይሆን ወደ ገነት እንዲገቡ፣ የሚቀበላቸውም ራሱ እግዚአብሔር እንዲሆን ያስቻለ ታላቅ መለኮታዊ ፍጻሜ ነው፤
እኛ “ክርስቶስ መድኃኒታችን ነው፤ ኣድኖናል” ብለን በልበ ሙሉነት የምንመሰክረው፣ እሱም “ሰላሜን ሰጠኋችሁ” ብሎ የሚያረጋጋን በመሰቀሉ ይህንን ውጤት ስላስገኘልን ነው።
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ ኣባላት!
የድኅነታችንና የሰላማችን መሠረት የሆኑትን የክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ለዓለም ማኅበረ ሰብ የማብሰርና የማሥረጽ ተግባር የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቍጥር ኣንድ ተልእኮ ነው፤
ነገረ ሞቱና ነገረ ትንሣኤው በኣስተውሎት፣ በጥልቀትና በተመሥጦ ስናስተምር በውስጡ የምናገኘው የዕርቅ፣ የሰላምና የኣንድነት ምስጢር ነው፤
እንደ እውነቱ ከሆነ እኛ የክርስቶስ መልእክተኞች እንደ ቃሉ ራሳችንን ክደን በሚጠበቀው መጠን ተልእኮኣችንን መወጣት ብንችል ኖሮ፣ ኣሁን በዓለማችን የተፈጠረው መለያየትና ግጭት ኣይኖርም ነበር፤
ችግሩን ሙሉ በሙሉ ማስቀረት ባንችልም በእጅጉ መቀነስና ዓቅሙን ማዳከም እንችል ነበር፤ ነገር ግን ተልእኮኣችንን በኣግባቡ ኣለመወጣት ኣንድ ነገር ሆኖ የዓለሙ መሳሪያ ሆነን መገኘታችን “በዕንቅርት ላይ…” ሆኖ ይስተዋላል።
ይሁንና ኣሁንም ሕዝቡን ወደ ኣንድነት፣ ወደ ፍቅር፣ ወደ ሰላም፣ ወደ ዘላቂ የጋራ ጥቅምና ወደ ፈሪሐ እግዚአብሔር ማምጣት የጉባኤያችን ዓቢይ ተግባር ሊሆን ይገባል፤ እነዚህ ካሉ የምናጣውም ሆነ የሚያመልጠን የለምና ነው፤
ሃገርን በኃላፊነት ተረክባችሁ በላዕላዊ፣ በማእከላዊና በታሕታዊ መዋቅር የምትገኙ፣ እንደዚሁም ኣማራጭ ሓሳብ ኣለን ብላችሁ የምትንቀሳቀሱ ልኂቃነ ሃገር ፣ ሁላችሁም እግዚአብሔርን ከሚያውቅ፣ ከሚያመልክና ከሚፈራ ሕዝብ የተገኛችሁ ናችሁና በልባችሁ እግዚአብሔርን ፍሩ፤ ድምፁንም ስሙ፤ የሱ ገንዘብ በሆኑ ፍጡራንም ኣትጨክኑ፤ ሰውን መያዝ የሚቻለው ኅሊናን በመርታት እንጂ በሌላ ኣይደለምና፣
የሕዝቡን ፍላጎትና የልብ ትርታ በሚገባ ኣዳምጡ፤ ሕዝቡ የሚፈልገው በኣንድነትና በእኩልነት መኖር፣ በሰላም ወጥቶ መግባት፣ ፍትሕን ማስፈን፣ ለኑሮው የሚበቃ ምጣኔ ሃብትን ማግኘት፣ የእምነት ነጻነትና እኩልነት መረጋገጥ የመሳሰሉት ናቸው።
ሕዝቡ እነዚህ ከተሟሉለት ተደመጠ ማለት ነው፤ ከተደመጠ ደግሞ እሱም በበኩሉ ያደምጣል፤ ይከተላልም፤
ስለሆነም ለሁሉም ልጆቻችንና ወገኖቻችን የምናስተላልፈው ወቅታዊ ጥሪ ሁሉንም ችግሮቻችን በሰላምና በሰላም ብቻ ለመፍታት ተባበሩ የሚል ነው፤ ከዚህ ውጭ የሚደረገው ኣማራጭ ሁሉ ለዘላቂ ሰላማችን ኣይበጅም እንላለን።
በመጨረሻም፦
በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት ከበዓለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ ኣምስተኛው ቀን የሚካሄደው ዓመታዊው የረክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልኣተ ጉባኤ በዛሬው ዕለት የተጀመረ መሆኑን ለሕዝበ ክርስቲያኑና ለመላው ኢትዮጵያውያን እናበስራለን!!!
እግዚአብሔር ጉባኤያችንን ይባርክ!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
ወስብሓት ለእግዚአብሔር፤
አሜን!!!
አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ
ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘኣኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤
ሚያዝያ 28 ቀን 2018 ዓ.ም
ኣዲስ ኣበባ - ኢትዮጵያ
¡Ya disponible! Investigación de Telegram 2025 — los principales insights del año 
