. 🔥 አባ ጳኩሚስ ❤
ግንቦት 14 የአንድነት ማኅበርን የመሠረተ፣ በአባ መቃርስ እጅ ከመነኮሰ በኋላ እነ አረጋዊን ያመነኮሰውና ገዳማዊ ኑሮንና ምንኩስናን ያስፋፋው ወንድና ሴት መነኮሳትም ፊት ለፊት እንዳይተያዩ ብሎ ሕግ የሠራ ታላቁ አባት አባ ጳኩሚስ ዐረፈ፡፡
እርሱም በአዳም መቃብር ላይ 60 ዓመት ቆሞ የጸለየ ሲሆን በአንዲት ሴት ላይ አድረው የነበሩትን 100 አጋንንት በጸሎት ወደ እርሱ እንዲገለበጡና በእርሱ ላይ እንዲያድሩ አድርጎ በጾም ጸሎት ስግደት ያቃጠላቸው ነው፡፡
አባ ጳኩሚስ ግብፅ ውስጥ ኤስና በምትባል መንደር ከአረማውያን ቤተሰቦች በ290 ዓ.ም ተወለደ፡፡ በቆስጠንጢኖስ ዘመነ መንግሥት ለውትድርናም ተመልምሎ አገልግሎት ሰጥቷል፡፡ በውትድርናው ዘመን የክርስቲያኖችን ቆራጥነት፣ ደግነትና ርኀራኄ በማየቱ ልቡ ስለተነካ ግዳጁን ፈጽሞ ሲመለስ በ313 ዓ.ም የክርስትናን እምነት ጠንቅቆ በመማር አምኖ ተጠመቀ፡፡ የአባ ጳኩሚስ ልቡና የቅዱስ እንጦንስ ደቀ መዝሙር በነበረው በአባ ጴላጦንስ ኑሮ ስለተማረከ ወደ በረሃ ወርዶ የብሕትውናን ኑሮና ሥርዓት ሲማር ከቆየ በኋላ በ320 ዓ.ም በዓባይ ወንዝ አጠገብ ታቤኒስ ከተባለው ቦታ የራሱን ገዳም መሠረተ፡፡ ይኽም ታላቅ አባት ከአባ ጰላሞን ዘንድ መንኩሶ ሲያገለግለው ኖረ፡፡ የምንኩስናንም ሥራ እየሠራ ብዙ ዘመናት ኖረ፡፡
ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ተገልጦለት እንደ አባቶቻችን ሐዋርያት የአንድነትን ማኅበር ለመሥራት መነኮሳትን እንዲሰበስብ አዘዘው፡፡ በታዘዘውም መሠረት ብዙዎች መነኮሳትን ሰብስቦ በየቦታው ብዙ ገዳማትን ገደመላቸው፡፡
ርዕሰ መነኮሳት የሆኑት አቡነ እንጦንስ በእግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ ምንኩስናን ከሊቀ መልአኩ ከቅዱስ ሚካኤል እጅ ተቀበሉ፡፡ እንጦንስም ታላቁ መቃርስን አመነኮሷቸው፤ ታላቁ መቃርስም ጳኩሚስን አመነኮሷቸው፤ አባ ጳኩሚስም አባ ቴዎድሮስ አመነኮሷቸው፤ አባ ቴዎድሮስም አቡነ አረጋዊን አመነኮሷቸው፡፡ አቡነ አረጋዊ ክርስቶስ ቤዛነን፣ ክርስቶስ ቤዛነ መስቀል ሞዐን፣ መስቀል ሞዐ ዮሐኒን፣ ዮሐኒ ኢየሱስ ሞዐንና ተክለ ሃይማኖትን (በቆብና በአስኬማ)፣ ኢየሱስ ሞዐ ተክለ ሃይማኖትን (በቅናትና በቀሚስ)፣ ተክለ ሃይማኖት ኢየሱስ ሞዐን (በቆብና በአስኬማ) ወልደዋል፡፡ አባ ጳኩሚስ መጀመሪያ ወደ ምንኩስናው ዓለም የመጣው በታላቁ አባ ጰላሞን አማካኝነት ነው፡፡ ለተወሰነ ጊዜም መንፈሳዊ አባቱን እየረዳ ሕይወተ መነኮሳትን አጥንቷል፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወቱና በተጋድሎ እየበረታና እየደረጀ ሲሄድ ከአባ ጰላሞን ተለይቶ ማሕበር መሥርቶ ለመኖር አምላኩን ጠይቆ ፈቃድ በማግኘቱ በሕግ የሚመራ የመጀመሪያውን ገዳም መሥርቷል፡፡
ቅዱስ አባ ጳኩሚስ ጸሎቱ አጋንንትን ከአካባቢው አያስቀርባቸውም ነበር፡፡ አካሉ አልቆ በአጥንቶቹ እስኪቆም ድረስ በጾም በጸሎት ይጋደል ነበር፡፡ ዓርብ ዓርብ የጌታችንን ሕማማት እያሰበ ከእንባ ጋር ይሰግዳል፡፡ እንባውና ላበቱ ከፊቱ እየወረደ አካባቢው ጭቃ ይሆን ነበር፡፡ ጌታችንም መስቀል ተሸክሞ ይታየው ነበር፡፡ ከዕለታትም በአንደኛው ቀን አባ ጳኩሚስ እንደወትሮው ሲሰግድ ወዙ ወርዶ መሬቱን ጭቃ አደረገው፣ ወዲያው ጌታችን ተገለጸለትና ጳኩሚስ ‹‹አንተን አገኝ ብዬ እንዲህ እደክማለሁ›› አለው፡፡ ጌታችንም ‹‹እኔም እንጂ ላንተ ብዬ እንዲህ ሆኜ ተሰቅያለሁ›› ብሎ በዕለተ ዓርብ እንደተሰቀለ ሆኖ ጐኑን እንደተወጋ ደሙ እንደፈሰሰ ሆኖ ታይቶታል፡፡
ከዕለታት በአንደኛው ቀን አባ ጳኩሚስ በበረሃ ሳለ መልአክ መጥቶ በነሐስ የተጻፈ ሕግ ሰጠው፤ እርሱም በዚህ የመጀመሪያውን ሥርዓተ መነኮሳትን አዘጋጅቷዋል፡፡ ከዚህም ባለፈ በርካታ ሥራዎችን ሠርቷል፡፡ ቅዱስ ዻኩሚስ ጫማ ሳይጫማ እሾህን ሳይሰቀቅ ይረግጥም ነበር፡፡ አባታችን ቅዱስ ጳኩሚስ ከርሕራሔው የተነሣ አጋንንት ያደሩባቸውን ሰዎች ሲያገኝ በቀጥታ ከመፈወስ ይልቅ ደዌውን ርኩሳን መናፍስቱንም ወደ እርሱ እንዲገለበጡ ያደርግ ነበር፡፡ ከዚያም በጾም በጸሎትና በስግደት መድረሻ ያሳጣቸዋል፡፡ ያንጊዜ በግዳቸው እየጮሁ ሲወጡ አባ ጳኩሚስ ‹‹ምነው ትንሽ ቆዩ እንጂ›› እያለ ይቀጣጠብባቸዋል፡፡ አንድ ዕለት ቅዱስ አባ ጳኩሚስ አንዲት ሴት ብዙ አጋንንት ሰፍረውባት ስትሠቃይ አየና ‹‹አቤቱ ጌታዬ ሆይ! ይህን ሁሉ እንዴት ትችለዋለች?›› ብሎ በእርሷ ላይ ያለውን የአጋንንት መንጋ ወደ እርሱ እንዲገለበጥ ፈጣሪውን በጸሎት ጠየቀ፡፡ በዚያም ጊዜ በአንድ ቀፎ ውስጥ ያሉ ንቦች ወደ ሌላ ቀፎ እንደሚገለበጡ እነዚያ በሴትዮዋ ላይ አድረው የነበሩ አጋንንት በሙሉ ከዚያች ሴትዮ ወጥተው በአባ ጳጉሚስ ላይ ሰፈሩ፡፡ እርሱም ማቅ ለብሶ አመድ ነስንሶ በሥግደት በጾምና በጸሎት አሠቃያቸው፡፡ አጋንንቱም የአባ ጳኩሚስን ትሩፋትና ተጋድሎ መቋቋም ስላልቻሉ አጋንንቱ ‹‹እንሂድ እንጂ እንግዲህማ ከዚህ ምን እናደርጋለን›› ሲሉ ሰማቸው፡፡ ቅዱስ ጳኩሚስም ‹‹ለምን አትቆዩም ሰው እንዲህ ካለ ኃጥእ ወዳጁ ቤትኮ ጥቂት ጊዜ ያርፋል›› ቢላቸው ‹‹እኛስ ከገነት ካስወጣነው ከአዳም በቀር እንዲህ ያለ ሰው አላየንም፣ ትሩፋቱ አቃጠለን ሊያስቀምጠን አልቻለም›› ብለው መስክረውለት ወጥተው ሄዱ፡፡
አባ ጳኩሚስን ስለ ክብሩ መልአክ ነጥቆ ወስዶ ገነትንና ሲኦልን አሳይቶ በኋላ ወደ ምድር መልሶታል፡፡ ከዚህም በኋላ ጻድቁ በዙሪያው ለተሰበሰቡት መነኰሳት የአንድነት ኑሮ ሕግ አወጣላቸው፡፡ ምንኩስና በእግዚአብሔር ፈቃድ በአባ እንጦንስ ቢመሠረትም ሕይወቱን በማስፋፋት ደረጃ የቅዱስ ጳኩሚስን ያህል የደከመና የተሳካለት ግን የለም፡፡ በአባ እንጦንስ የተጀመረውን የመነኰሳትን የማኅበር ኑሮ አባ ጳኩሚስ በተጠናከረ መልኩ ሥርዓት አውጥቶ የበለጠ ከማስፋፋቱም በተጨማሪ ዘጠኝ የወንዶችና ሁለት የሴቶች ገዳማት መሥርቷል፡፡ አባ ጳኩሚስ ያወጣው የመነኰሳት የአኗኗር ሕግ ዋናው ቅጂ ሲጠፋ ወደ ላቲን የተተረጐመው ግን እስከዛሬ ድረስ ይገኛል፡፡ ከሕግጋቱ መካከል፡- መነኮሳት ጠዋትና ማታ በማኅበር እንዲጸልዩ፣ በኅብረት በአንድነት እንዲሠሩ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን አዘውትረው እንዲመለከቱ፣ መነኮሳት ሹመት እንዳይሾሙ ከልክሏል፣ መነኮሳት የቁም ጽሕፈት እንዲማሩ፣ ገቢና ወጫቸው አንድ ላይ እንዲሆን፣ በአንድነት እንዲመገቡ፣ አንድ ዓይነት ልብስ እንዲኖራቸው፣ ንጽሕናቸውን ጠብቀው እንዲኖሩ፣ ከገዳማቸው በፍጹም እንዳይወጡ ከልክሏል፣ የመጀመሪያውን ሥርዓተ መነኮሳት አዘጋጅቷል፣ መነኮሳት ደግነት፣ ፍቅርና ታዛዥነት እንዲኖራቸው የሚሉትና የመሳሰሉት ናቸው፡፡
ሐዋርያው ቅዱስ አትናቴዎስ ወደ ላዕላይ ግብጽ በወጣ ጊዜ ይህን አባት ጳኩሚስን ቅስና ሊሾመው ወደደ፡፡ ከእርሱም ሸሸ፡፡ እጅግ የከበረ አትናቴዎስም ልጆቹን ‹‹‹የማይናወጽ ቤትን የሠራህ ቅዱስ ሆይ! ከከንቱ ውዳሴ የራቅህ አንተ ብፁዕ ነህ፣ ልጆችህም ብፁዓን ናቸው› ብሎሃል በሉት አባታችሁን›› አላቸው፡፡
ይኽም ቅዱስ አባት አንድ ጊዜ ሲኦልን ያዩ ዘንድ ወደዱ፡፡ እነሆም የእግዚአብሔር መልአክ ነጥቆ ወስዶ በገነት የጻድቃንን ማደሪያ እንዲሁም በሲኦል የሥቃይን ቦታዎች ሁሉ አሳያቸው፡፡