fa
Feedback
ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

رفتن به کانال در Telegram

ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።

نمایش بیشتر
636
مشترکین
اطلاعاتی وجود ندارد24 ساعت
-47 روز
-1230 روز
آرشیو پست ها
የእነዚህን ምስጢር በልቡ ጠበቃቸው፡፡ አምስቱንም ቃላት በልቡ መዝገብነት ሰወራቸው፤ ሊገልጣቸው እግዚአብሔር አልፈቀደላትምና በተረዳ ነገር ግን መዝሙረ ዳዊት ነው፡፡ የገነትን ፍሬዎች ሁሉ የሰበሰበ መዝሙረ ዳዊት የገነት አምሳል ነውና አጋንንትን ያሳድዳል መላእክትንም ያቀርባል፡፡ እመቤታችንም ከእርሱ ተለይታ ካረገች በኋላ ከዚያችም ሰዓት ጀምሮ የልቡ ዓይን ተከፈተለት፡፡ ኅሊናውም በመንፈስ ቅዱስ ክንፎች ተመሰጠ፡፡ ወደ አብም ደረሰ፤ በዚያም ኢየሱስን በአባቱ ቀኝ ተቀምጦ ጰራቅሊጦስንም በአንድ አኗኗር አገኘው፡፡ 🌹 ከዚህ በኋላ በሐይቅ እስጢፋኖስ የዜማ የቅኔና የመጻሕፍትን ትርጓሜ ትምህርቱን በሚገባ ተምሮ አጠናቀቀ፡፡ በዕውቀቱም ቀድሞ የሚያውቁት ሁሉ ይደነቁበት ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ የያሬድን ዜማ ከአቡነ ሳሙኤል ተማረ፡፡ በዚያ ዘመን በዐፄ ዳዊት አማካይነት በሰሜን ኢትዮጵያ የያሬድ ድጓ ዋና ማዕከል በሆነው በደብረ ነጎድጓድ ተሾሞ ያስተምር ነበር፡፡ የማስተማር ሥራውን የጀመረው በዚያው በሐይቅ እስጢፋኖስ ነበር፡፡ 🌹 ከሐይቅ በኋላ በዚያ ዘመን ሸግላ በመባል ትጠራ ወደ ነበረችው ወደ ትውልድ ሀገሩ ወደ ጋሥጫ ተጓዘ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ወደ ሸግላ ሲመጣ አባቱ በጣም አርጅቶና መንኲሶ ነበር፡፡ ስለዚህም በአባቱ እግር ተተክቶ በቤተ መንግሥቱ ያለችውን ሥዕል ቤት እንዲያገለግል ወደዚያው አስገቡት፡፡ በቤተ መንግሥቱም የንጉሡን ልጆች ከማስተማሩም በላይ በቤተ መንግሥቱ ዙርያ ከነበሩት ሊቃውንት መካከል አባ ጊዮርጊስ አንዱ ነበር፡፡ በአንድ ወቅት ግብፃዊው ጳጳስ አቡነ በርተሎሜዎስ "ሥላሴን አንድ ገጽ" ብለው ያምናሉ ተብለው በተከሰሱ ጊዜ ነገሩን እንዲያጣሩ ከተመረጡት ከቄስ ዐፄ ተከሥተ ብርሃንና ከሐይቁ መምህር ከዐቃቤ ሰዓት ዮሴፍ ጋር አብሮ ተልኮ ነበር፡፡ እነዚህ ሦስት አበው ጳጳሱን ካነጋገሩ በኋላ ክሱ ውሸት መሆኑን በማረጋገጥ ስለ ምሥጢረ ሥላሴ የሚገልጠውን የጳጳሱን እምነት በጽሑፍ ይዘው መጡ፡፡ 🌹 በቤተ መንግሥቱ በነበረ ጊዜ የንጉሡን ልጆች ይስሐቅን፣ ቴዎድሮስን፣ እንድርያስን፣ ሀብተ ኢየሱስን፣ ሕዝቅያስን፣ ኢዮስያስን፣ ዘርዐ ያዕቆብንና ሴት ልጁን እሌኒን በምግባርና በሃይማኖት ቀርጿቸዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል ዘርዐ ያዕቆብ በድርሰቱ ሲመስለው ቴዎድሮስ ደግሞ በሕይወት መስሎታል፡፡ ዐፄ ዳዊት የአባ ጊዮርጊስን ሊቅነትና መልካም ሥነ ምግባር በሚገባ ስላወቀ በጋብቻ ሊዛመደው ወዶ ስለነበር ልጁን እንዲያገባ ዘወትር ይጠይቀው ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ ግን በድንግልና ጸንቶ ለመኖር እንደሚፈልግ ከመግለጽ አልተቆጠበም፡፡ የዐፄ ዳዊት ጥያቄ ስለበዛበት ወደ አቡነ በርተሎሜዎስ ሄዶ ቅስናን ከተቀበለ በኋላ ወዲያው መነኰሰ፡፡ 🌹 ከመነኰሰ በኋላ ወደ ሸግላ በመምጣት ለነገሥታትና በቤተ መንግሥቱ ለነበሩ ካህናት እንዲሁም በቤተ መንግሥቱ ለነበሩ ታላላቆች፣ ለንቡራነ እድና ለመኳንንት፣ ለመሳፍንትና በቤተ መንግሥቱ ለነበሩ ባለሟሎች ሁሉ መምህር ሆነ፡፡ 🌹 አባ ጊዮርጊስ በሸግላ በነበረ ጊዜ በወባ በሽታ ታምሞ ሊሞት ደርሶ ነበር፡፡ ታምሞ በነበረ ጊዜ አንድ ሌሊት የከበሩ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ተገልጠውለት "ከእኛ ጋር ትኖር ዘንድ ልንወስድህ መጣን" አሉት፡፡ እርሱም "የድርሰት ሥራዬን ሳልሠራና እግዚአብሔርንም አብዝቼ ሳላመሰግነው አሁን አትውሰዱኝ" ሲል ለመናቸው፡፡ እነርሱም ልመናውን ተቀብለውት ከሕመሙ ፈውሰውት ሄዱ፡፡ ለዚህም ነው ከበሽታው እንደ ተፈወሰ ወድያው የድርሰት ሥራውን የጀመረው፡፡ የመጀመርያ መጽሐፉን ጽፎ እንደ ጨረሰ ጠፍቶበት ነበር፡፡ በማግሥቱ በዚያው ላይ ሊጨምር በወደደ ጊዜ የተጻፈበት ጥራዝ ቀለሙ ጠፍቶ ነጭ ሆኖ አገኘው፡፡ ስለዚህም የተሰረቀ መስሎት ልቡ አዘነ፡፡ የተስተካከሉ ጥራዞችንም በቈጠረ ጊዜ ደኅና ሁነው አገኛቸው ሁለተኛም በድጋሚ ጻፈ፡፡ በማግሥቱም እንደ መጀመሪያው ነጭ ሁኖ አገኘው እስከ ሦስትና ዐራት ቀንም እየተደጋገመ እንዲሁ ሆነ፡፡ 🌹 ከዚህ በኋላ አባታችን ወደ እመቤታችን ይጸልይ ጀመረ፡፡ "ይህ የሆነ በኃጢአቴ ነውን? ወይስ አይደለም? ግለጭልኝ" አላት፡፡ አንድ ቀንም በሌሊት እኩሌታ ወደ ቤተ ክርስቲያን ለጸሎት ሲሄድ እመቤታችን በድንገት በማይነገር ክብር ለጊዮርጊስ ተገለጠችለት፡፡ ከእርሷም ጋር የቅዱሳን ማኅበር ሁሉ ነበሩ፡፡ በእጇም ከፀሐይና ጨረቃ የበለጠ የሚያበራ መጽሐፍን ይዛ ነበር፡፡ ጊዮርጊስም ባየ ጊዜ ወደ መሬት ወደቀ፡፡ እንደ በድንም ሆነ፡፡ እመቤታችንም አነሣችውና "ሳትጠይቀኝ መጽሐፌን ትጽፍ ዘንድ ለምን ደፈርህ?" አለችው፡፡ "እኔ ወድጄህ ከእናትህስ ማኅፀን መርጬህ ለጴጥሮስ፣ ለጳውሎስና ለዮሐንስ አደራ ሰጥቼህ የለምን?" አለችው፡፡ አባ ጊዮርጊስም "እመቤቴ ሆይ ይቅር በይኝ፣ ደስ የሚያሰኝሽ መስሎኝ ይህን ባለማወቅ ሠርቼዋለሁና" አላት፡፡ እመቤታችንም "ወዳጄ ሆይ ይቅር ብየሃለሁ" አለችው፡፡ "ልትጽፈው የወደድኸው መጽሐፍም እነሆ በእጄ አለ፣ ከአሁን በኋላ የተወደደ ልጄ በአንደበትህ ሊገልጸው ወዷል፡፡ ነገር ግን ከአርያም ከሰማይ ኀይልን እስክትለብስ ድረስ አትቸኩል"፡፡ ይህንም ብላው ከእርሱ ተሰወረች፡፡ ያን ጊዜም ልቡ እንደ ፀሐይ በራ፣ የመለኮትም ባሕር በኅሊናው አበራ፡፡ በመንፈስ ቅዱስም መስተዋትነት የተሰወረውን ሁሉ አየ፡፡ 🌹 የመጀመርያው ድርሰቱ አርጋኖን የተሰኘውና በቅኔ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የሚያመሰግነው መጽሐፉ ነው፡፡ እግዚአብሔርን በሚወድ በንጉሥ ዳዊት ዘመንም አርጋኖን መጽሐፍን ይደርስና ይጽፍ ጀመረ፡፡ በሦስትም ስሞች ጠራው እነዚህም አርጋኖና ውዳሴ፣ መሰንቆ መዝሙር፣ ዕንዚራ ስብሐት ናቸው፡፡ ስለ መጽሐፉም ጣፋጭነት ንጉሡ ዐፄ ዳዊት ድርሰቱን በጣም ከመውደዱ የተነሣ በወርቅ ቀለም አጻፈው፡፡ ወርቁን የሚያንጸባርቅበት ድንጋይ (ዕንቊ) ባጣ ጊዜ እመቤታችን ማርያም በሌሊት ራእይ ዘማት በሚባል አገር እንዳለ ለጊዮርጊስ ነገረችው ኅብሩንም አሳየችው፡፡ አባታችን ጊዮርጊስም ከደረስኳቸውና ከተናገርኋቸው ድርሳናት ሁሉ አርጋኖን ውዳሴ ይጣፍጣል ይበልጣል አለ፡፡ 🌹 እንደዚሁም በፈጣሪው ቸርነት በእመቤታችን ረድኤት ብዙ ድርሳናትንና የጸሎት መጻሕፍትን ደረሰ፡፡ የእሊህም ድርሳናት ስማቸውና ቁጥራቸው በሊቃውንት ዘንድ የታወቀ ነው፡፡ እሊህም ውዳሴ መስቀል፣ መጽሐፈ ብርሃን፣ መጽሐፈ ሰዓታት የመዓልትና የሌሊት፣ መጻሕፍተ ቅዳሴያት ናቸው፡፡ ጸሎተ ፈትቶ (የፍታቴ ጸሎት) የሐዋርያት ማኅሌት፣ መልክአ ቊርባን፣ እንዚራ ስብሐት፣ አርጋኖን ውዳሴ፣ ፍካሬ ሃይማኖት፣ ውዳሴ ሐዋርያት፣ ኖኅተ ብርሃን ይኸውም ከመጽሐፈ አርጋኖን ጋር አብሮ የታተመው ነው፡፡ ፍካሬ ሃይማኖት፣ መጽሐፈ ምስጢር፣ ሕይወታ ለማርያም፣ ተአምኆ ቅዱሳን፣ ጸሎት ዘቤት ውስተቤት፣ ውዳሴ ስብሐት፣ ሰላምታ፣ ጸሎተ ማዕድ፣ ቅዳሴ እግዚእ ካልእ፣ መዝሙረ ድንግልና የመሳሰለው ነው፡፡ ቅዱስ ገድሉ እንደሚናገረው የአባ ጊዮርጊስ "ድርሳናት ስማቸውና ቁጥራቸው በሊቃውንት ዘንድ የታወቀ ነው" ብሎ ከጀመረ በኋላ በቁጥር የተወሰኑትን ድርሰቶቹን ብቻ ጠቅሶ መጨረሻ ላይ "… እና የመሳሰለው ነው" ብሎ ይደመድመዋል፡፡ ሊቀ ብርሃናት መርቆሬዎስ አረጋ ደግሞ የአባ ጊዮርጊስ ድርሰቶች ከ12 ሺህ በላይ ቢሆኑም ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እየሰጡ ያሉት በጣም ጥቂቶቹ ብቻ መሆናቸውን በቅዱሳን ታሪክ መጽሐፋቸው ላይ ጠቅሰውታል፡፡ ሌሎች ሊቃውንት አባቶቻችንም የአባ ጊዮርጊስን ድርሰቶች ከግምት ባለፈ ሁኔታ በቁጥር ወስኖ ለማስቀመጥ አስቸጋሪ መሆኑን ይገልጣሉ፡፡ ይኸውም

🌹 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹            🌹 #ጥቅምት ፫ (3) ቀን። 🌹 እንኳን #ለታላቁ_ሊቅ_ከመጽሐፈ_ሰዓታት ውጭ እጅግ ብዙ ድርሰቶችን ለደረሰ ፈላስፋም ጻድቅም ደራሲም መናኝ ባሕታዊም ለሆነ ድርሰቶቹንም ለቅዱሳን በነፋስ ጭኖ ይልክላቸው ለነበረ ለቤተ ክርስቲያናችን ታላቅ ኩራት ለሆነ #ለኢትዮጵያዊው_ቄርሎስ ለአባታችን #አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ_ለጽንሰት በዓል በሰላም አደረሰን።                                                   ✝ ✝ ✝ 🌹 #ታላቁ_ሊቅ_ኢትዮጵያዊው_ቄርሎስ_አባ_ጊዮርጊስ ዘጋስጫ፦ አባቱ ሕዝበ ጽዮን ዘትግራይ እናቱ አምኃ ጽዮን ዘወለቃ ይባላሉ፡፡ ስለሆነም ሀገሩ ትግራይና ወሎ ቦረና ነው፡፡ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ በመባል የሚታወቀው ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በድርሰቱ ከቅዱስ ያሬድ ቀጥሎ ስሙ የሚነሣ ታላቅ መመኪያችን የሆነ ጻድቅ አባታችን ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ከመናኝ ጻድቅነቱ በተጨማሪ በመላእክትም ዘንድ የተመሰከረለት ታላቅ ፈላስፋና ደራሲም ነው፡፡ በድርሰቱ ላይ ስለ ሰማይ፣ ስለ መብረቅ፣ ስለ ደመና፣ ስለ ዝናብ አፈጣጠር፣ ስለ አራቱ ዓለማትና ስለ ሰባቱ ሰማያት… በእነዚህና በመሳሰሉት በመንፈሳዊው በሚገባና እጅግ በሚያስደንቅ መንገድ ተፈላስፎባቸዋል፡፡ 🌹 ጻድቁ ድርሰቶቹን እርሱ ካለበት ወደ ሌላ ቦታ ለመላክ ንፋስ ይታዘዝለት ነበር፡፡ ስለ ጾምና ስለ በዓላት የደረሰውን ድርሰቱን ለሸዋው ንጉሥ ደብዳቤ ጽፎ በነፋስ ጭኖ ልኮለታል፡፡ አስደናቂ ገደሙ ወሎ ቦረና ውስጥ ይገኛል፡፡ ጋስጫ በድሮ ስሟ ደብረ ባሕርይ ትባላለች፡፡ በአጠገቡም ራሱ አባ ጊዮርጊስ የፈለፈላቸው ብዙ ዋሻዎች አሉ፡፡ ከአባ ጽጌ ድንግል ጋር ለመገናኘት እንዲያመቻቸው ብለው የሠሩት ድልድይ "የእግዜር ድልድይ" ይባላል፡፡ በእግር 5 ሰዓት የሚያስኬድ መንገድ ነው፡፡ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ገዳም የአውሬ ሰጋጅና ባሕታዊ ያለበት አስደናቂ ገዳም ነው፡፡ በየዓመቱ የስቅለት ዕለት ቁመቱ 60 ክንድ የሆነ ዘንዶ ከመቅደሱ ወጥቶ ግብረ ሕመማት ከሚነበብበት ከአትሮንሱ ሥር ሆኖ ተጠምጥሞ እራሱን ቀና አድርጎ ሲሰግድ ውሎ ካህኑ ሲያሰናብት ማታ ተመልሶ ወደ መቅደሱ ይገባል፡፡ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ የተሰኘውን የዚህን ድንቅ አባታችንን ዜና ሕየወቱን በደንብ መመልከቱ ተገቢና አስፈላጊ ነው፡፡ ✝ የተወለደው በ1357 ዓ.ም በወሎ ክፍለ ሀገር በቦረና ወረዳ ሰግላ በተሰኘች ቦታ ነው፡፡ የተወለደው በቅዱስ ዑራኤል አብሳሪነት ጥምቀት 3 ቀን ተጸንሰው ሐምሌ 7 ቀን ተወለዱ፡፡ ወላጆቹ አስቀድሞ ልጅ አልነበራቸውምና በስለት ነው ያገኙት፡፡ አባ ጊዮርጊስ በመጀመርያ እናቱ ፈሪሐ እግዚአብሔርን እያስተማረች በጥበብና በዕውቀት አሳደገችው፡፡ ቀጥሎም የመጀመርያውን የቤተ ክርስቲያን ትምህርት የተማረው ከአባቱ ነበር፡፡ ሊቅ የነበረው አባቱ ካስተማረው በኋላ በ 1341 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ ከመጡትና እስከ ዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ጳጳስ የነበሩት ከአቡነ ሰላማ መተርጕም ዘንድ ወስዶ ዲቁና አሹሞታል፡፡ 🌹 ዲቁና ከተቀበለ በኋላ ለትምህርት ወደ ሐይቅ እስጢፋኖስ ወሰደው፡፡ አባ ጊዮርጊስ በሐይቅ እስጢፋኖስ ትምህርት አልገባው ብሎ ለሰባት ዓመታት ተቀምጦ ነበር፡፡ አብረውት የሚማሩት ተማሪዎች "ይህ ትምህርት የማይገባው ስለ ምንድን ነው? በእርሱ ኃጢአት ነው ወይስ በወላጆቹ?" ይሉት ነበር፡፡ በዚያ ጊዜ የሐይቁ መምህር የነበረው ዐቃቤ ሰዓት ሠረቀ ብርሃን ለአባቱ "ልጅህ ትምህርት አይገባውምና የቤተ መንግሥት ነገር አስተምረው" ብሎ መለሰው፡፡ አባቱ ሕዝበ ጽዮን ግን "አንድ ጊዜ ለእግዚአብሔር ሰጥቼዋለሁ፤ እዚያው ገዳሙን ያገልግል" ብሎ እንደ ገና ወደ ሐይቅ ላከው፡፡ 🌹 አባ ጊዮርጊስ ከቀለም ትምህርቱ ይልቅ በሥራ እየደከመ የገዳሙን አባቶች ይረዳ ጀመር፡፡ በገዳሙ እንጨት ይሰብር ውኃ ይቀዳ ይልቁንም ደግሞ አብዝቶ እህል በመፍጨት ያገለግል ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ እህል ይፈጭበት የነበረውን የድንጋይ ወፍጮና ንፍሮ ይቀቅልበት የነበረው የድንጋይ ትልቅ ማሰሮ አሁንም ድረስ በሐይቅ ገዳም በክብር ተጠብቀው ይገኛሉ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ግን ትምህርቱን ለመረዳት የዘገየ ሆነ፣ የእግዚአብሔር ቃልም አልገባውም ነበር፡፡ ይህም ስለ ኃጢአቱ አይደለም፡፡ የእግዚአብሔር ሥራና ጌትነቱ በእርሱ ላይ ይገለጥ ዘንድ ነው እንጂ፡፡ ጸጋ ያለመከራ አይሰጥምና ያለመፈተንም ማብዛት አይቻልም፡፡ ጌታችንን ዕውር ሆኖ ስለተወለደው ሕፃን ደቀ መዛሙርቱ በጠየቁት ጊዜ "ይህ ሕፃን ዕዉር ሆኖ የተወለደው በማን ኃጢአት ነው? በራሱ ነውን ወይስ በወላጆቹ?" አሉት፡፡ ጌታችንም "እርሱም አልበደለም፣ ወላጆቹም አልበደሉም፣ የእግዚአብሔር ሥራ በእርሱ ላይ ይገለጥ ዘንድ ነው እንጂ" አላቸው፡፡ ዮሐ 9፡1፡፡ ሐዋርያትም መንፈስ ቅዱስ እስኪወርድላቸው ድረስ በትንሽ ዕውቀት ነበሩ፡፡ "በመጻሕፍት ያለውን ገና ዐላወቁምና" ተብሎ እንደተጻፈ እንዲሁ አባ ጊዮርጊስም ዕውቀት ስለ ተሰወረውና ጓደኞቹ በትምህርት ሲቀድሙት ባየ ጊዜ እጅግ አዘነ፡፡ ስለዚህም በጾምና በጸሎት ወደ እግዚአብሔር መጮኽ ጀመረ፡፡ 🌹 ሁልጊዜም በሥዕለ ማርያም ሥር እየተንበረከከ ጥበብን እንዲሰጠው ወደ እግዚአብሔር አብዝቶ በመለመን እንባንም በማፍሰስ ይጸልይ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ እመቤታችን ተገለጠችለትና አረጋጋችው፡፡ ዳግመኛም እንደምትመጣ ቀን ቀጥራው ከእርሱ ተሰወረች፡፡ በሰጠችውም ቀጠሮ መሠረት በነሐሴ 21 ኛው ቀን እመቤታችን ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል በቀኝና በግራ ሆነው ኪሩቤልንና ሱራፌልን አስከትላ ተገለጠችለትና "አይዞህ ዕውቀት የተሰወረብህ ትምህርት ስለማይገባህ ሳይሆን የእግዚአብሔር ድንቅ ሥራ እንዲገለጥ ነው" አለችው፡፡ "የመረጥሁህ የልጄ ወዳጅ ጊዮርጊስ ብላ በስሙ ጠራችው፡፡ ከዕውቀት ወንዝ የመጣና ከጥበብ ምንጭ የተገኘ ከመለኮት ባሕር የተቀዳ ይህን ንጹሕ ጽዋ ንሣ ጠጣ" በማለት ጽዋዓ ልቡናን አጠጣችው፡፡ 🌹 ይኸውም ጽዋዕ ልቦና በዮሴፍ ቤት በጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት የጠጡት መንፈሳዊና ሰማያዊ መጠጥ ነው፤ በበዓለ ሃምሳ ከጠጡት ያልተለየ ነው፡፡ ይኸውም የሚናገር እሳት፣ የሚያድን እሳት፣ መለኮታዊ እሳት ነው፡፡ ከዚህም በኋላ አባ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያንን ያስጌጠበት የመጻሕፍትን ምስጢራት፣ የማኅሌትንና የድርሳናትን ቃል፣ ምስጋናዎችንም ሁሉ እመቤታችን ገለጠችለት፡፡ 🌹 እመቤታችን ማርያም ለብፁዕ ጊዮርጊስ ጽዋውን ካጠጣችው በኋላ ያን ጊዜ አምስት የምሥጢር ቃላትን አስተማረችው፡፡ የኅሊናን ዓይኖች ያበራሉና የልቡናንም ጆሮዎች ይከፍታሉና፡፡ ከዚህ በኋላ ከእርሱ ተሰወረች፤ ከማይተኙ ከትጉሃን መላእክትም ጋር ወደ ሰማይ ዐረገች፡፡ የአምስቱ የምሥጢር ቃላት ትርጉምም ዕውቀትን የተመሉ መንፈሳውያን አባቶቻችን እንደ ነገሩን ከእመቤታችን ማርያም እጅ በተሰጠው በመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ትምህርት ሳይማር በአንድ ቀን የዳዊትን መዝሙር ማጥናት ነው፡፡ መዝሙረ ዳዊትን ግን ዕብራውያን በአምስቱ የስሜት ሕዋሳት ቁጥር ለአምስት ከፍለውታል፡፡ እነዚህም መስማት፣ ማየት፣ ማሽተት መቅመስና፣ መዳሰስ ናቸው፡፡ የመጀመሪያው ክፍል መጨረሻው 40ኛው መዝሙር ነው፤ የሁለተኛው ክፍል መጨረሻው 71ኛው መዝሙር ነው፡፡ ሦስተኛው ክፍል መጨረሻው 88ኛው መዝሙር ነው፤ አራተኛው ክፍል መጨረሻው 105ኛው መዝሙር ነው፡፡ አምስተኛው ክፍል መጨረሻው 150ኛው ነው፡፡ የእነዚህም ክፍላት መጨረሻ ለይኩን ለይኩን ባለ ጊዜ ይታወቃል፡፡ አባ ጊዮርጊስም

🌹 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹 🌹 #የተባረከ_የጥቅምት_ወር_የቀኑ_ሰዓት_ዐሥራ_አንድ ነው ከዚህም በኋላ ይቀንሳል።            🌹 #ጥቅምት ፩ (1) ቀን። 🌹 እንኳን #ከሮሜ_አገር_ለሆነች በገድል ተጠምዳ ለኖረች #በጨካኙ_ንጉሥ_በዳኬዎስ ወታደሮች እጅ ሰማዕትነት ለተቀበለች #ለቅድስት_አንስጣስያ ለዕረፍት በዓልና #ለአልዓዛር_እኅት_ለቅድስት_ማርያም ለመታሰቢያ በዓሏ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከኅርጣንና_ከድንግል_ቅድስት_ሶስና ከመታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                          ✝️ ✝️ ✝️ 🌹 #ሰማዕቷ_ቅድስት_አንስጣስያ፦ ይችም ቅድስት መስተጋድልት ከሮሜ አገር ናት ወላጆቿም ክርስቲያኖች ናቸው ጠቃሚ የሆነ ትምህርትን በማስተማር ክብር ባለው በመልካም ሥርዓት አሳደጓት። 🌹 በአደገችም ጊዜ ወላጆቿ ሊያጋቧት ፈለጉ እርሷ ግን ይህን ሥራ አልፈለገችም የምንኲስናን ልብስ መልበስ ፈለገች እንጂ፤ ከታናሽነቷም መንፈሳዊ ገድልን መረጠች። ስለዚህም በሥውር ሒዳ በሮሜ ካሉ ገዳማት ወደ አንዱ ገዳም ገባች ታናሽ ስትሆንም የምንኲስና ልብስን በመልበስ በጾም በጸሎት በረኃብ በጽምዕ በመጠመድ የዚህን ዓለም ሐሳብ ሁሉ ከልቡናዋ ቆርጣ በመተው በመጋደል ሥጋዋን አደከመች። 🌹 በቀኑ ርዝመትም ሁሉ የምትጾም ሆነች በየሁለት ቀኖችም ታከፍላለች በጌታችን ጾም ግን ያለ ሰንበታት ቀን የምትመገበው የለም። በሰንበታትም የምትመገበው ከቀትር ጸሎት በኋላ ነው። በነዚያም በምንኲስናዋ ወራት በእሳት ያበሰሉትን ወጥ አልቀመሰችም። 🌹 በገዳሟ አቅራቢያም ሌላ የደናግል ገደም አለ የዚያ ደብር በዓልም በደረሰ ጊዜ እመ ምኔቷ በዓሉን ለማክበር ይቺን ቅድስት አንስጣስያን ከእኅቶቿ ደናግል ጋር አስክትላት በአንድነት ተጓዙ። ሲጓዙም የንጉሥ ዳኬዎስን ወታደሮች አየቻቸው። ከእርሳቸውም ጋር የታሠሩ ክርስቲያኖች አሉ ወታደሮቹም አሥረው በቁጣ ይጎትቷቸው ነበር። ልቧም በሃይማኖቷ ፍቅር ነደደና ያን ጊዜ እንዲህ ብላ ዘለፈቻቸው "የእውነት ፈጣሪን የካዳችሁ ልባችሁ የደነዘዘ እግዚአብሔር በመልኩና በአምሳሉ በፈጠራቸውና ስለእነርሱም ነፍሱን ለሞት አሳልፎ በሰጠላቸው ላይ ለምን እንዲህ ትሠራላችሁ"። 🌹 ይህንንም በአለቻቸው ጊዜ ወታደሮች ተቆጡ ይዘውም ወደ መኰንኑ አቀረቧት እርሱም እንዲህ ብሎ ጠየቃት "በእውነት አንቺ የተሰቀለውን የምታመልኪው ክርስቲያን ነሽን?" እርሷም "ስለእኛ የተሰቀለውን ክብር ይግባውና እርሱን አመልከዋለሁ" ብላ መለሰችለት። 🌹 በዚያን ጊዜም ጽኑ ሥቃይን አሠቃያት በሥጋዋም እሳትን ጨመረ ከዚህም በኋላ ዘቅዝቆ ሰቀላት ከበታቿም አጤሱባት ከሃይማኖቷም ባልተናወጸች ጊዜ ራሷን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። በዚህ በታላቅ ሥቃይም ውስጥ ሳለች ራሷን በሰይፍ ቆረጧት። በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በበሰማቷ ቅድስት አንስጣስያ ጸሎቱ ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥቅምት 1 ስንክሳር።                            ✝️ ✝️ ✝️ 🌹 "#ሰላም_ለማርያም_ለአልዓዛር_እኅቱ። እንተ አንሥኦ #ክርስቶስ እምነ መቅበርቱ። በሀሊተ ብካይ ጊዜ ተቀበሎቶ ሎቱ። #ሶበሰ_እግዚእየ_ሀሎከ_በዝንቱ። እመኢትውህበ እኅየ ለሞቱ"። #ሊቀ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጥቅምት_1።                            ✝️ ✝️ ✝️ 🌹 #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ተዘከር እግዚኦ ከመ መሬት ንሕነ። ሰብእሰ ከመ ሣዕር መዋዕሊሁ። ወከመ ጽጌ ገዳም ከማሁ ይፈሪ"። መዝ 102፥14-15። የሚነበቡት መልክታት 1ኛ ቆሮ 7፥32-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 3፥1-5 እና የሐዋ ሥራ 17፥10-13። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 6፥25-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።          

🌹 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹            🌹 #መስከረም ፴ (30) ቀን። 🌹 እንኳን #የዘብዴዎስ_ልጆችን ለሐዋርያት #ቅዱስ_ዮሐንስና_ቅዱስ_ያዕቆብ ጌታችን #ለሐዋርያነት_ለጠሩበት_ቀን_ለመታሰቢያ_በዓል፣ ከውዳሴ ከንቱ ለመራቅ ሲል #እራሱን_እንደ_እብድ መስሎ ታላቅ ተጋድሎ #ለአባ_ሣሉሲ_ለዕረፍት በዓል፣ #የእስክንድርያ_ሊቀ_ጳጳሳት በሆነ በከበረና በተመሰገነ #በአባ_አትናቴዎስ_ላይ ክብር ይግባውና #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ_ላደረገው_ተአምር መታሰቢያ ቀን በዓልና #ለአቡነ_አሮን_ዘገሊላ ለመታሰቢያ በዓላቸው በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከአርማንያ ጳጳሳት #ከአቡነ_ጎርጎርዮስ ከመታሰቢያቸው፣ #ከአባ_ቡላ__ከማርዩ_ከብትሩስ፤ ከሰማዕቱም #ከቅዱስ_አስታሬስ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                   ✝ ✝ ✝ 🌹 #አባ_ሣሉሲ፦ ይህም ቅዱስ መስጋድል ሲሆን ራሱን እንደ እብድ አደረገ እርሱም በሥውር ይጸልያል ይጾማልም በሰው ፊት ግን ምንም ምን አይጸልይም አይጾምም በየጥዋቱ ሁሉ የሚመገበውን የሣር ፍሬ አድርጎ በሰው ፊት ያላምጣል በምሽት ጊዜ ግን ከውንድሞች መነኰሳት ጋር ምንም ምን አይቀምስም። አበ ምኔቱ አባ ይስሕቅና መነኰሳቱ ሁሉ ከሥራው የተነሣ ያደንቃሉ ይህንንም ልማዱን ሊአስጥሉት ይሻሉ ነገር ግን ልቡን እንዳያሳዝኑት ያስባሉ። 🌹 በአንዲትም ዕለት የገዳማቸው በዓል ሆነ አበ ምኔቱ አባ ይስሐቅም መነኰሳቱን እንዲህ አላቸው "ቅዱስ ቁርባንን ከመቀበሉ በፊት እህልን እንዳይቀምስ አባ ሣሉሲን ጠብቁት"። እነርሱም ጠበቁት የሚበላበትም ጊዜ ሲደርስ ከእነርሱ ሊለይ ወደደ መነኰሳቱም ከለከሉት እርሱም "በረኃብ እንዳልሞትና በእናንተ ላይ በደል እንዳይሆንባችሁ ልቀቁኝ ብሎ ጮኸባቸው"። ባልተውትም ጊዜ በዚያን ወቅት ቆቡን ከራሱ ላይ አውልቆ "እመቤቴ ማርያም ሆይ ከእሊህ መነኰሳት እጅ አድኝኝ" ብሎ የቤተ ክርስቲያኑን ግድግዳ በቆቡ መታበት ሕንፃውም ተሠንጥቆለት በዚያ ወጥቶ ሔደ የግድግዳውም ግምብ ተመልሶ እንደቀድሞው ሆነ። 🌹 የተሰበሰቡትም ይህን ድንቅ ተአምር በአዩ ጊዜ ሦስት መቶ ጊዜ ኪርያላይሶን እያሉ ጮኹ በዚያንም ጊዜ ያቺን ቆብ ወድቃ አገኙአት በታላቅም ክብር በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩዋት ድውያንንም በመፈወስ ከእርሷ ብዙ ተአምራት ተደረገ። ሊቀ ጳጳሳቱም በሰማ ጊዜ ከእርሷ ሊባረክ ወዶ ያቺን ቆብ ሊወስዳት ፈለገ በየጊዜውም ሲወስዳት ወደቦታዋ ወደዚያ ገዳም ትመለሳለች እንዲህም ሦስት ጊዜ ሆነ ከዚህም በኋላ መውሰዱን ተወ። 🌹 ከብዙ ወራትም በኋላ እንደ ዛሬው ሁሉ በዚች ቀን አባ ሣሉሲ በዚሁ ገዳም በዐረፈበት ቦታ ተገልጾ ተገኘ በክብርም ገንዘው ቀበሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ሣሉሲ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                             ✝ ✝ ✝ 🌹 #የእስክንድርያ_ሊቀ_ጳጳሳት በሆነ በከበረና በተመሰገነ #በአባ_አትናቴዎስ ላይ ክብር ይግባውና #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ_ያደረገው_ተአምር፦ ይህም ሁለተኛም ቈስጠንጢኖስ ወደ ረከሰች የአርዮስ ሃይማኖት በገባ ጊዜ የእስክንድርያውን ሊቀ ጳጳሳት አባ አትናቴዎስን አሳድዶ ከሀዲውን ጊዮርጊስን በእስክንድርያ መንበር ላይ ሾመው። የአርዮስንም ሃይማኖት እንዲአጠናክር የረከሰ የአርዮስን ሃይማኖት የማይቀበሉትን ግን ሁሉንም ይገድላቸው ዘንድ አዘዘው ብዙዎች ፈረሰኞች ጦረኞችን ለእርሱ ሰጥቶታልና። ስለዚህም ከእስክንድርያ ሰዎች ቁጥር የሌላቸውን ብዙዎች ምእመናንን ገደላቸው። 🌹 ቅዱስ አትናቴዎስም በተሰደደበት ስድስት ዓመት ኖረ። ከዚህም በኋላ የእግዚአብሔርን ልጅ የካደው ታናሹ ቈስጠንጢኖስ ወደአለበት ወደ ቊስጥንጥንያ ተነሥቶ ሔደ ንጉሡንም እንዲህ አለው "ወደ ተሾምሁበት መንበሬ ትመልሰኝ እንደሆነ መልሰኝ ይህ ካልሆነ የምስክርነት አክሊልን እንድቀበል ግደለኝ"። 🌹 ንጉሡም ይህን ነገር ከእርሱ በሰማ ጊዜ በታናሸ መርከብ አድርገው ያለ ቀዛፊና ያለ መብልና መጠጥ በባሕር ውስጥ እንዲተዉት አዘዘ ንጉሡም በስጥመት ወይም በረኃብና በጥም እንደሚሞትለት አስቦ ነበርና የቀናች ሃይማኖትንም ስለመለወጡ እንዳይዘልፈው ከእርሱ ያርፍ ዘንድ እንዲሁም ንጉሡ እንዳዘዘ በቅዱስ አትናቴዎስ ላይ አደረጉበት። ንጉሡም እንጀራና ውኃ ባይሰጠው ከሰማይ ለእርሱ የወረደ እንጀራ ስለርሱ የፈለቀ ውኃም አለው። የመርከብም ቀዛፊ ቢከለክለው እነሆ ዓለሙን ሁሉ በቃሉ የሚጠብቅ የሚመራ ከእርሱ ጋር ነበር። ስለዚህም ቅዱስ አትናቴዎስ በውስጧ የተቀመጠባት ያቺ መርከብ መላእክት እየቀዘፏት በጸጥታና በሰላም ተጓዘች በሦስተኛውም ቀን ከእስክንድርያ ወደብ ደረሰ። 🌹 የምእመናን ወገኖችም ደግ ጠባቂያቸው እንደ ደረሰ በሰሙ ጊዜ እጅግ ደስ አላቸው መብራቶችንም በመያዝ በምስጋና እየዘመሩ ሊቀበሉት ወጡ። እግዚአብሔርንም እያመሰገኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን አስገቡት። ከሀዲው ጊዮርጊስም ከወገኖቹ ጋር ወጥቶ ሔደ። 🌹 በዚያችም ቀን ቅዱስ አትናቴዎስ ለእግዚአብሔር ታላቅ በዓልን አከበረ የእስክንድርያም ሰዎች እስከ ዛሬ ድረስ ያከብሩ አታል። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም የቅዱስ አትናቴዎስም በረከቱ ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመስከረም 30 ስንክሳር።                                                  ✝ ✝ ✝ 🌹 "#ሰላም_ለክሙ_መምህራነ ዕበይ ወተድላ። #ዘደብረ_ማርያም_አብሳዲ_ወአሮን_ዘገሊላ። ትትኖለዉኒ ሥሙረ መንገለ ወፈርኩ ኵላ። ኢይንዐወኒ ዐርየ ከመ ይንዕዉ ገድላ። አንበሳ ርኁብ ወካይኡ ተኵላ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_30።                              ✝ ✝ ✝ 🌹 #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ናሁ ሠናይ ወናሁ አዳም። ሶበ ይሔልው አኃው ኅቡረ። ከመ ዕረፍት ዘይውኅዝ እምርእሱ እስከ ጽሕሙ"። መዝ 132፥1-2። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 9፥20-ፍ.ም፣ 1ኛ ዮሐ 1፥8-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 20፥28-3%። የሚነበበው ወንጌል ማር 1፥16-23። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም የአቡነ አቡሳዲ የዕረፍት በዓል፣ የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።