fa
Feedback
ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

رفتن به کانال در Telegram

ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።

نمایش بیشتر
638
مشترکین
اطلاعاتی وجود ندارد24 ساعت
-37 روز
-1130 روز
آرشیو پست ها
የብፁዕ አቡነ ማቴዎስ ወላጅ እናት እማሆይ አስካለ ማርያም ሥርዐተ ቀብር ተፈጸመ። ሚያዝያ ፳ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም የብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን  የመገናኛ ብዙኃን ሥርጭት አገልግሎት ድርጅት፣  የአፋን ኦሮሞ መገናኛ ብዙኃን ቴሌቪዥን ማሰራጫ ድርጅት  የበላይ ኃላፊ፣ የምሥራቅና ሰሜን አፍሪካ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ወላጅ እናት እማሆይ አስካለ ማርያም በዓለም ስማቸው ወይዘሮ አምሳለ ወርቅ ማሞ በ85 ዓመት ዕድሜያቸው ከዚህ ዓለም ድካም ዐርፈዋል። የሕይወት ታሪካቸው እንደሚያስረዳው እማሆይ አስካለ ማርያም (በቀድሞ ስማቸው ወይዘሮ አምሳለ ወርቅ ማሞ) ከአባታቸው አቶ ማሞ ወልደየስና ከእናታቸው ወሮ አጸደ በየነ በሰሜን ሸዋ ምንጃር ሸንኮራ ወረዳ ልዩ ስሙ መምህር አገር ቦሰቄ ቀበሌ በ፲፱፻፴፫ ዓ.ም ተወለዱ። እማሆይ አስካለ ማርያም (ወይዘሮ አምሳለ ወርቅ ማሞ) ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ በአካባቢያቸው ባለው ትምህርት ቤት ገብተው የመሠረተ ትምህርት ተምረዋል። እማሆይ አስካለ ማርያም (ወይዘሮ አምሳለ ወርቅ ማሞ) ዕድሜያቸው ለአቅመ ሔዋን ሲደርስ ቤተሰቦቻቸው ለአባ ክንፈ ሚካኤል (በቀድሞ ስማቸው አቶ ጌታነህ የኋላሸት) ጋር በ፲፱፻፵፰ ዓ.ም ጋብቻ መሠረቱ። በጋብቻ ሕይወታቸውም በፍጹም ፍቅርና መተሳሰብ በትዳር ሲኖሩ ስድስት ወንዶችና ሀለት ሴቶች ልጆችን ያፈሩና ልጆቻቸውንም በሃይማኖትም በሥነ ምግባርና በፍቅር፣  ያሳደጉ ደግ እናት ነበሩ። እማሆይ አስካለ ማርያም ከትዳር አጋራቸው ከአባ ክንፈ ሚካኤል (አቶ ጌታነህ የኋላሸት) ጋር በፍቅር በሚኖሩበት ወቅት ለ8 ልጆች እናት፣ ለ38  የልጅ ልጆች አያት፣ ለ20 ልጆች ቅድመ አያትና ለአራት ልጆች ቅም አያት በመሆን የልጅ ጸጋ የበዛላቸው ደግ  እናት ነበሩ። እማሆይ አስካለ ማርያም እጅግ ትሑትና ቅን ትንሽ ትልቅ ሳይሉ ሰውን የሚያከብሩ፣ ለተቸገረ የሚራሩ፣ እንግዳን አብልተው አጠጥተው የጠገበ የማይመስላቸው እትዬ፣ እማዬ እያለ ለሚጠራቸው ወዳጅ ዘመዶቻቸውና በአካባቢው ማኅበረሰብ ዘንድም የተወደዱ ስመ ጥር ደግ እናት ነበሩ። እማሆይ አስካለ ማርያር ማሞ ከትዳር አጋራቸው ከአባ ክንፈ ሚካኤል ዕረፍት በኋላ በጾም፣ በጸሎትና በትህርምት መኖርን በመውደዳቸው ብዛት የተነሣ የምግብ ፍላጎታቸውን በመግታት ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እወዳለሁ  እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ  የአምላካቸው ጥሪ ደርሶአቸው ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፳፻፲፰ ዓም በተወለዱ በ85 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም ድካም ዐርፈዋል። እማሆይ አስካለ ማርያም  ክቡር አስከሬናቸው በቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን በርካታ የገዳማትና አድባራት ሊቃውንት በተገኙበት በማኅሌትና  ጸሎተ ፍትሐት ተደርሶ የቅዳሴ ሥርዐት ከተፈጸመ በኋላ ሥርዐተ ቀብራቸው  ሚያዝያ ፳ ቀን ፳፻፲፰  ዓ.ም በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት በሉሜ ሞጆ ወረዳ ኤጀሬ ደብረ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እና ወዳጅ ዘመዶቻቸው በተገኙበት ተፈጽሟል። በሥርዐተ ቀብራቸው  ላይ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል የዋሽንግተን ዲሲና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባና ሀዲያ ሥልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት፣ የደቡብ ኦሞና አሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ዜናማርቆስ የቦረና ሊበን እና ምዕራብ አርሲ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ የወላይታ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዴኦ፣ አማሮ ቡርጂና ኮሬ ሀገረ ስብከት ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ የምሥራቅ ጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የጠቅላይ ቤተክህነት የመምሪያ ኃላፊዎች፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሥራ ኃላፊዎች የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎችና ሠራተኞች፣ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት የሥራ ሓላፊዎች፣ የሞጆ ሉሜ ወረዳ ቤተክህነት ሠራተኞች፣ የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ በርካታ የአዲስ አበባና የአካባቢው ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን፣ ካህናትና ዲያቆናት፣ ወዳጅ ዘመዶቻቸው ተገኝተዋል።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤         ❤ #ሚያዝያ ፳፩ (21) ቀን። ❤ እንኳን አምላክን ለወለደች #ለእመቤታችን_ለቅድስት_ድንግል_ማርያም ወራዊ በዓልዋ መታሰቢያ፣ ለከበረ አባት #ለአባ_ቡሩታዎስ ለዕረፍቱ በዓል  እግዚአብሔር አምላክ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከከበሩ #ከቅዱሳን_አካርክስ_ከቅሪይስና #ከይወራስ ከመታሰቢያቸው  ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                       ✝ ✝ ✝  ❤ በዚች ቀን አምላክን የወለደች #የእመቤታችን_የከበረች_ድንግል_ማርያም የበዓልዋ መታሰቢያ ነው። እርስዋ ወደ ተወዳጅ ልጅዋ ስለ ሰው ልጆች ትማልዳለችና ስሟን ለምንጠራ ለእኛ ኃጢአታችንንም ያስተሠርይልን ዘንድ ስለዚህም በየወሩ ሁሉ መታሰቢያዋን ልናደርግ ይገባል። ልመናዋ በረከቷ ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋራ ለዘላለሙ ይኑር አሜን።                            ✝ ✝ ✝  ❤ #የከበረ_አባት_አባ_ቡሩታዎስ፦ ይህም አባት የአቴና አገር የሆነ ከምሁራን ጥበበኞች አንዱ ነው እርሱም ደግሞ ደራስያን ከሆኑ ከአረጋውያን መምህራን ጋራ የተቆጠረ ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስንም ተገኝቶት ስለ ቀናች ሃይማኖት ተከራከረው። የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት የቀናች እንደሆነች ተረድቶ አመነ በሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እጅ ተጠምቆ የቤተ ክርስቲያንን ሕግና ሥርዓት ተማረ። ❤ ከዚህም በኋላ ቅዱስ ጳውሎስ በአቴና አገር ቅስና ሾመው። በታላቂቱ አገር በአቴና የመምህራን አለቃ ከሆነ ዘመደ ላሕም አብሮባ ከተባለ ከከበረ ዲዮናስዮስ ጋራ ተገናኘ። እርሱም የክብር ባለቤት ስለሆነ ጌታ ኢየሱስ ሃይማኖት ብዙ ገለጠለት ከውስጡ ሥውር የሆነበትንም ተረጐመለት እጅግም ዐዋቂ ሆነ። ❤ ይህም አባት አምላክን የወለደች እመቤታችን የከበረች ድንግል ማርያም በዐረፈችበት ቀን ደርሶ በሐዋርያት መካከልም ቆመ በደረሰው ማኅሌትና ዝማሬ ጣዕም ባለው በመሰንቆ በዜማ ድምጽም አጽናናቸው። ከአይሁድና ከአሕዛብም ብዙዎቹን መልሶ ወደ ክብር ባለቤት ወደ ጌታ ክርስቶስ እምነት አስገባቸው። በተሰጠችውም ጸጋ ነግዶ ታላቅ ትርፍ አስገኘ። ❤ ሐዋርያትም ኤጲስቆጶስነት ሊሾሙት በፈለጉ ጊዜ ጌቶቼ ይቅርታ አድርጉልኝ እኔ ለዚች ለከበረች ሹመት አልበቃሁምና የቅስናንም አገልግሎት ልፈጽም አልቻልኩምና ተውኝ ብሎ ማለዳቸው። በዕውቀቱና በሥራው ሰማያዊ ሀብትን ተቀብሎ ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔር ሚያዝያ21 ቀን ሔደ። የአባ ቡሩታዎስ በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።                                                                        ✝ ✝ ✝  ❤ "#ሰላም_ለብሩታዎስ_ዘዘመረ_ማዕከለ_ሐዋርያት ዘኤፍራታ። #በጺሖ_ለማርያም ጊዜ ዕረፍታ። ወአመ ፈቀዱ ይሢምዎ ዘኢጲስቆጶስ መዐረገ ፆታ። ኢይክል ይቤ ሢመታተ መንታ። እስመ ኢያብጻሕኩ ለቅስና ሠናየ መልእክታ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሚያዝያ_21።                         ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወትቀውም ንግሥት በየማንከ። በአልባሰ ወርቅ ዑጽፍት ወኊብርት። ስምዒ ወለትየ ወርእዪ ወአጽምዒ ዕዝነኪ"። መዝ 44፥9-10።  የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 1፥39፥57።                          ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር። ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን። በዘአዝፋረ ወርቅ ዑፅፍት ወኊብርት"። መዝ 44፥12-13። የሚነበበው መልዕክታት ኤፌ 5፥15-21፣ 1ኛ ጴጥ 2፥4-11 እና የሐዋ ሥራ 17፥30-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 17፥1-11። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም የበዓለ ሃምሳ ጊዜና በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ ከዚህም በኋላ እስከጎጃም ድረስ እየተዘዋወሩ ወንጌልን ሰበኩ፡፡ በርካታ አብያተ ክርስቲያናትንም አነጹ፡፡ እስከ ምድረ ቢዘን ድረስም ወረዱ፡፡ በዚህም ጊዜ ግራኝ አህመድ ተነሥቶ ክርስቲያኖችን በግፍ መግደል አብያተ ክርስቲያናትን ማቃጠል ጀመረ፡፡ አቡነ ዕንባቆም ለግራኝ በዐረብኛ ቋንቋ ደብዳቤ ጻፉለት፡፡ "ክርስቲያኖችን አትግደሉ ተብሎ በቁርአን ተጽፎ እያለ አንተ ግን ለምን ትገድላለህ? አብያተ ክርስቲያናትንስ ለምን ታቃጥላለህ?" ብለው ጻፉለት፡፡ ግራኝ አህመድም ደብዳቤአቸውን ካነበበ በኋላ "ከእንግዲህ ወዲህ ክርስቲያኖችን እንዳልገድል ቤተ ክርስቲያኖችንም እዳላቃጥል ከሚወጉኝ በቀር በክርስቲያን ላይ ክፉ እንዳልሠራ በአላህና ከሚስቶቹ በሦስቱ ጠለቅ ማልሁ" ብሎ ተናገረ፡፡ ለአቡነ ዕንባቆምም "የክርስቲያን ሃይማኖት ከቁርአን የሚለይበትን መንገድ ትገልጽልኛለህና መጥተህ እየኝ" ብሎ ልኮባቸው ነበር ነገር ግን አቡነ ዕንባቆም መንፈስ ቅዱስ ሳይፈቅድላቸው ቀርቶ ሳያገኙት ቀሩ፡፡  ❤ ዐፄ ልብነ ድንግል ሞቶ ልጁ ገላውዴዎስ ሲተካ አቡነ ዕንባቆምን ወደ እርሱ ይመጡ ዘንድ መልእክተኛ ላከባቸውና ሲመጡ "ስለ አህመድ ግራኝ ምን ባደረግ ይሻላል?" አላቸው፡፡ እርሳቸውም "የሥልጣንህ ሰይፍ ከአንገቱ ላይ ሆናለች፡፡ እኔም ወደ ጎጃም እሄዳለሁ፣ እከተልሃለሁ፣ በደንቢያ ላይም እንገናኛለን፡፡ ሐነፋውያን (የግራኝ ዘሮች) በእጅህ ይጠፋሉ፡፡ አንተም በመጨረሻ በእነርሱ እጅ በሰማዕትነት ታልፋለህ" ብለው ይመጣ ዘንድ ያለውን ሁሉ በትንቢት ነገሩት፡፡ በትንቢታቸውም መሠረት ዐፄ ገላውዴዎስ ግራኝን ካጠፋው በኋላ በሌላ ጊዜ የግራኝ ተከታይ ኢማም ኑር ገላውዴዎስን ገደለው፡፡ የንጉሡ እኅት ወለተ ጊዮርጊስም ወደ አቡነ ዕንባቆም መጥታ ያመነኲሳት ዘንድ ስለለመነችው ሥርዓተ ምንኲናን ፈጸመላት፡፡ ❤ ከገላውዴዎስ ቀጥሎ ዐፄ ሚናስ ሲነግስ አቡነ ዕንባቆምን መጥተው እንዲባርኩት ለመናቸው፡፡ እርሳቸውም ከባረኩት በኋላ ወደ ደብረ ሊባኖስ እንዲመለሱ ለመናቸው፡፡ እርሳቸውም እምቢ ቢሉትም ከብዙ ልመና በኋላ እሺ ብለውት ወደ ደብረ ሊባኖስ ሲሄዱ ልጆቻቸው በደስታ ተቀበሏቸው፡፡ እርሳቸውም እያስተማሩና መልካም አገልግሎታቸውን እየፈጸሙ አንድ ዓመት ከቆዩ በኋላ በ137 ዓመታቸው ሚያዝያ 21 ቀን 1553 ዓ.ም በሰላም ዐረፉ፡፡ በአባቶቻቸውም መቃር ተቀበሩ፡፡ ዐፄ ሠርፀ ድንግልም በ1580 ዓ.ም የአቡነ ዕንባቆምን ገድል አጻፈላቸው፡፡ ይህ ታሪካቸውም ከዚሁ ገድላቸው ላይ የተቀዳ መሆኑን የ1990 ዓ.ም የካቲት መጋቢት እትም ሐመር ትገልጻለች፡፡ ከአባታችን ዕጨጌ አባ ዕንባቆም እግዚአብሔር አምላክ ረድኤት በረከትን ያሳትፈን፣ በጸሎታቸው ይማረን። ምንጭ፦ ከገድላት አንደበት።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤         ❤ #ሚያዝያ ፳፩ (21) ቀን። ❤ እንኳን ታላቁ አባት በጎ ስም አጠራር ላላቸው የሐዋርያት አምሳል ሃይማኖትን ለሚሰብኩ፣ ከየመን ወደ ኢትዮጵያ  ከእስልምና እምነት ተመርጦ ክርስቲያ ሆነው #በአቡነ_ተክለ_ሃይማኖት ወንበር ለመሾም እስከተገባው ድረስ ለደረሱ #ለዕጨጌ_አባ_ዕንባቆም ለዕረፍቱ ነው በዐል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                          ✝ ✝ ✝  ❤ #አባ_ዕንባቆም_ዕጨጌ_ዘደብረ_ሊባኖስ፡- እርሳቸው በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ወንበር ለመሾም እስከተገባቸው ድረስ እግዚአብሔር ከእስልምና እምነት መርጦ ያመጣቸው ታላቅ ሐዋርያ ናቸው፡፡ የመናዊው እጨጌ ዕንባቆም በዐረብ ምድር በየመን የተወለዱ ሲሆን አስቀድመው እስላም ነበሩ በኋላ ግን መጻሕፍትን መርምረው ዕውነትን ፈልገው በማግኘት በጌታችን በክርስቶስ አምነው ተጠምቀው ከመነኰሱ በኋላ በደብረ ሊባኖስ በአቡተ ተክለ ሃይማኖት ወንበር ተሾመው እስከማገለግል የደረሱ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ ❤ አባ ዕንባቆም በ1416 ዓ.ም አካባቢ የመን ውስጥ ነው የተወለዱ፡፡ አባታቸው እስላም ሲሆን እናታቸው ግን አይሁዳዊት ነበረች፡፡ አባታቸው በሕጋቸው መሠረት ሁለት ሚስት አግብቶ ከአንደኛዋ 7 ልጆችን ሲወልድ ከአንዷ ደግሞ 2 ልጆችን ወልዷል፡፡ ከሁለቱ አንዱ አባ ዕንባቆም ነበር፡፡ እርሱም ቁርአንን እና ልዩ ልዩ ቋንቋዎችን በሚገባ እየተማረ አደገ፡፡ ለእስልምና ሃይማኖቱ ቀናተኛ የነበረው ዕንባቆም የክርስትና ስም ሲነሳበት አይወድም ነበር፡፡ 114ቱንም የቁርአን ምዕራፎች (ሱራዎች) በቃሉ ይዞ ቀን ከሌሊት ይጸልይባቸው ነበር፡፡ አንድ ቀን በቁርአን ላይ ስለመሞትና መነሣት የተጻፈውን ሲያነብ ኅሊናው ታወከ፡፡ ወዲያውም ወደ ቁርአን ሊቅ ዘንድ ሄዶ ትርጉሙን ጠየቀ፡፡ ነገር ግን የተሰጠው ምላሽ "ለምን አነበብከው?" የሚል ነበር፡፡ (በነገራችን ላይ ቁርአኑን ከዐረብኛ ቋንቋ ውጭ ወደ ሌሎች ቋንቋዎች መተርጎም እንደሌለበትና በእርሱ ላይ ስለተጻፉት ነገሮች ጥያቄ መጠየቅ ክልክል እንደሆነ ቁርአኑ ለራሱ ከለላ የሰጠ መሆኑ ይታወቃል፡፡)  ❤ ዕንባቆምም ለጥያቄው መልስ በማጣቱ ይልቁንም ስለጠየቀ በቁጣ ስለተገሠጸ በእስልምና ላይ የነበረው ፍጹም እምነት ወደ ጥርጣሬ ተቀየረ፡፡ በዚያም ዘመን የኢትዮጵያ ንጉሥና የአዳል ንጉሥ ጦርነት ገጥመው አዳሎች አሸነፉና ንጉሡ 51 የኢትዮጵያ ምርኮኞችን ለአባ ዕንባቆም አባት ላከለት፡፡ ምርኮኞቹም ዕንባቆም በሃይማኖት ምክንያት ከወገኖቹ ጋር አለመስማማቱን አይተው ወደ ኢትዮጵያ እንዲሄድ መከሩት፡፡ እርሱም አብሯቸው በመካ በኩል ዳህላክን አቋርጦ ከነጋዴዎች ጋር ወደ ኢትዮጵያ ወደብ ደረሰ፡፡  ❤ ዕንባቆምም መጀመሪያ ካገኘውና አብሮት ከመጣው ወሰንጌ ጋር በመርሐ ቤቴ ተቀመጠ፡፡ በዚያም ትምህርተ ሃይማኖትን መማር ጀመረ፡፡ በግእዝ ንባብ የጀመረውም ትምህርት ተአምረ ማርያም ላይ ሲደርስ የእመቤታችን ፍቅሯ ስላደረበት ወደ ክርስትናው ሃይማኖት ይበልጥ ተሳበ፡፡ የዕንባቆም የዘወትር ጸሎት "ወደ ዕውነተኛው ሃይማኖት ምራኝ" የሚል ሆነ፡፡ አንድ ቀንም በክረምት ወደ ዠማ ወንዝ ወርዶ ሳለ በአንድ ጎልማሳ የተመሰለ ቅዱስ ተገለጠለትና የውኃውን ሙላት በተአምራት አሻግሮ "በዚህች መንገድ ሂድ" ብሎ ካሳየው በኋላ ተሰወረው፡፡ ዕንባቆምም መንገዱን ይዞ ሲጓዝ ደገኛው አባ ጴጥሮስ ካለበት ገዳም ደረሰ፡፡ በገዳሙም ማረፊያ ሰጥተውት በዚያ ተቀመጠና ብዙ ቅዱሳት መጻሕፍትን ተማረ፡፡ ❤ ከዚህም በኋላ መጠመቅ እንደሚፈልግ ለአባ ጴጥሮስ ነገራቸውና አጥምቀው ስመ ጥቀቱን ዕንባቆም አሉት፡፡ ዳግመኛም በዚሁ ገዳም መነኰሰ፡፡ አባ ጴጥሮስም ከጳጳሱ ከአቡነ ማርቆስ በተገናኙ ጊዜ ስለ አባ ዕንባቆም ነገሯቸው፡፡ ጳጳሱም አባ ዕንባቆምን አስጠርተው በዐረብኛ ቋንቋ የተጻፈን ወንጌል እንዲያነብላቸው ሰጡት፡፡ እርሱም በድንብ አነበበላቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ዲቁና ሰጡትና በቤታቸው አስቀመጡት፡፡ በዚህም ጊዜ ለጳጳሱ የሶርያን፣ የቅብጥን፣ የዕብራይስጥንና የአርመንን ቋንቋዎች ከነጽሕፈታቸው አስተማራቸው፡፡ ጳጳሱም ቆይተው ቅስና ሾሙት፡፡ ❤ አባ ዕንባቆም አንዱን የካቶሊክ እምነት ተከታይ ተከራክሮ ሲያሳምነው ጳጳሱ ተመልክተው በዚህ ደስ ተሰኝተው ከአንግብጦን ወረዳዎች ጢቆ በምትባል አገር ላይ ሾመው ላኩት፡፡ እርሱም በዚያ በእመቤታችን ስም የተዋበች ቤተ ክርስቲያን ሠርቶ ስሟን ቤተልሔም አላት፡፡ ዜናውም በሁሉ ዘንድ መሰማት ጀመረ፡፡ የአባ ዕንባቆም የዘወትር ጸሎት መዝሙረ ዳዊት፣ መኃልየ ሰሎሞን፣ ወንጌለ ዮሐንስ፣ ውዳሴ ማርያምና አርጋኖን ነበሩ፡፡ የደብረ ሊባኖስ ገዳም መነኰሳት ራእይ ተገልጦላቸው አባ ዕንባቆምን "የደብረ ሊባኖስ አለቃ ትሆናለህ ነገር ግን መነኰሳቱ ከንጉሡ ጋር ያጣሉሃል" ብለው ነገሩት፡፡ እርሱም ከዚህ ሹመትና የሰይጣን ፈተና ሸሽቶ ወደ ምድረ ግብጦን ሄዶ የሐብላሽ በምትባል ገዳም ተቀመጠ፡፡ "አቤቱ የገዳም አስተዳዳሪ ከመሆን ጠብቀኝ" እያለ በመጸለይ በዚህች ገዳም 3 ዓመት ተቀመጠ፡፡ ነገር ግን የትሩፋቱ ዜና በእንደግብጦንና በዳሞት ተሰማ፡፡ ወደ ላሊበላም ተጉዞ ከዋልድባ መነኰሳት ጋር በመገናኘት ወደ ኢየሩሳሌም ለመሄድ ቁርጥ አሳብ አድርጎ ሳለ መነኰሳቱ "ይህ ሀሳብህ አይሰምርልህምና ወደ ደብርህ ተመለስ" ብለው መከሩት፡፡ እርሱ ግን ሳይመለስ ቅጻ ወደምትባል ሥፍራ ሄዶ በአንድ ገዳም ተቀምጦ የተለያዩ ተአምራትን እያደረገ ተቀምጦ ሳለ በደዌ ተያዘ፡፡ በቤተ ክርስቲያንም ሳለ የታዘዘ መልአክ ተገለጠለትና "ወደ ደብርህ ሂድ" አለውና ደብረ አንጎት አደረሰው፡፡ በዚያም አባ በትረ ማርያምን አገኛቸው፡፡ እርሳቸውም ወደ ደብሩ እንዲመለስ ስለመከሩት ወደ ደብረ ሊባኖስ ተጉዞ ከአባ ጴጥሮስ ጋር በድጋሚ ተገናኘ፡፡ እርሳቸውም "ከእንግዲህስ ወዲህ ወዲያ አትበል፣ የሞቴም ጊዜ ደርሷልና አንተ በመንበሬ ተተክተህ ትሾማለህ፡፡ እንደእኔም ለብዙዎች አባት ትሆናለህ ነገር ግን መነኮሳት በከንቱ ወንጅለውህ ንጉሡ ያሥርሃል፣ ትሰደዳለህም" ብለው ትንቢት ነገሩት፡፡  ❤ አባ ጴጥሮስም ባረፈ በ40ኛው ቀን መነኰሳቱ ተሰብስበው ዕጣ ቢጥሉ ለአባ ዕንባቆም ስለወጣ በእጨጌነት ሾሙት፡፡ ወዲያውም ሴቶችና ወንዶች መነኰሳትን በመልክ እንኳን እንዳይተያዩ በማድረግ እያስተማረ አገልግሎቱን ሲያከናውን ፈቃደ ሥጋቸውን ማሸነፍ የተሣናቸው መነኰሳት "ክብርህን ያሳንሳል፣ ስለአንተም አይጸልይም፣ እንዲያውም "ንጉሡ በአሳርና በመከራ ይሞታል" እያሉ ይናገራሉ" ብለው በሐሰት ለንጉሡ በመንገር አጣሏቸው፡፡ ክፉዎችም በወጠኑት ሴራ ጻድቁ በንጉሡ ፊት ለፍርድ ቀረቡና ብዙዎቹ "ይገደሉ" ብለው ፈረዱባቸው፡፡ ነገር ግን የዐፄ ልብነ ድንግል እንደራሴ "ከምንገድላቸው አስረን በግዞት ጉንጭ ወደሚባለው ቦታ እንውሰዳቸውና በዚያ ከሞቱ ይሙቱ" ብሎ ሌላ ሀሳብ አቀረበ፡፡ ንጉሡም በዚህ ተስማምተው አቡነ ዕንባቆምን እጅና እግራቸውን አስረው እየደበደቡ አጋዟቸው፡፡  አቡነ ዕንባቆምም በግዞት ሆነው ሳለ ውኃ ሳይቀምሱ አንድ ዓመት ተቀመጡ፡፡

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤              ❤ #ሚያዝያ 20 (፳) ቀን። ❤ እንኳን ደንደራ ከሚባል አገር ደግሞ እልበደራ ከሚባል አገር ለሆነ #ለቅዱስ_በብኑዳ ሰማዕትነት ለተቀበለት ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                            ✝ ✝ ✝ ❤ #ቅዱስ_በብኑዳ፦ ይህ ቅዱስ ለብቻው የሚኖር ዕውነተኛ ተጋዳይ ነው እግዚአብሔር መልአክም ተገልጦለት "የመቀደሻ ልብስ ለብሰህ ወርደህ ለመኰንኑ ተገለጥለት" አለው። በዚያን ጊዜ መኰንኑ አርያኖስ ከመርከብ ወርዶ ወደዚያች አገር ወደብ መድረሻው ጊዜ ነበር። ይህንንም ባሕታዊ ፈልጎት አላገኘውም ነበር። እነሆ ቅዱስ በብኑዳም በፈቃዱ መጥቶ ወደ መኰንኑ ሔዶ "በክብር ባለቤት በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ የማምን በግልጥ እኔ ክርስቲያን ነኝ" ብሎ በታላቅ ቃል ጮኸ። መኰንኑም ፈልጎ ያጣው የታወቀ ባሕታዊ መሆኑን በአወቀ ጊዜ እንዲአሠቃዩት በእግር ብረትም አሥረው ከጨለማ ቤት እንዲጥሉት አዘዘ። በዚያን ጊዜም ብርሃን ወጣ የእግዚአብሔር መልአክ ከሕማሙ ፈወሰው አበረታው አጽናናውም። ❤ በዚያችም አገር ስሙ ቄርሎስ የሚባል ምዕመን ሰው ነበር ከእርሱ ጋራም ሚስቱና ዐሥራ ሁለት ጐልማሶች ልጆቹ አሉ። እነዚህን ሁሉንም የከበረ በብኑዳ አስተማራቸው አጽናንቷቸውም ራሶቻቸውን ቆርጠዋቸው በሰማዕትነት ሙተው አክሊል ተቀበሉ። ❤ አርያኖስም ተቆጥቶ በቅዱሱ አንገት ከባድ ደንጊያ ሰቅለው ወደ ባሕር ይጥሉት ዘንድ አዘዘ በእግዚአብሔር ኃይልም ከድንጋዩ ጋራ ዋኘ። ደግሞ ከሰሎን ዛፍ ላይ ይሰቅሉት ዘንድ አዘዘ ያቺም ሰሌን ዐሥራ ሁለት ዘለላን አፍርታ ለመጪው ትውልድም መታሰቢያ ሆነች። ከዚህም በኋላ የከበረች ራሱን ቆረጡት የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበለ። የቅዱስ በብኑዳ በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ 20 ስንክሳር።                              ✝ ✝ ✝               ❤ "#ሰላም_ዕብል_ለበቡኑዳ_ሰማዕት። እንተ አግሀደ ብርሃነ በቤተ ጽልመት። ወአመ ሰቀልዎ ሎቱ መልዕልተ በቀልት። አውጽአት ፍሬ በይእቲ ሰዓት። እስከ ጉቡአን አንከሩ እምዛቲ ትእምርት"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርከ) #የሚያዝያ_20።                         ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #ዕለቱ_ምስባክ፦ "ወይርአዩ አሕዛብ በቅድመ አይንቲነ። በቀለ ደሞሙ ለአግብርቲከ ዘተክዕወ። ይባእ ቅድሜከ ገዓሮሙ ለሙቁሓን"። መዝ 78፥10-11። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ቆሮ 3፥7-12፣ ያዕ 3፥13-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 5፥38-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 25፥14-31። የሚቀደሰው ቅዳሴ ሠለስቱ ምዕት ወይም የቅዱስ ዲዮስቆሮ ቅዳሴ ነው። መልካም የበዓለ ሃምሳ ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን። ❤            ❤ #ሚያዝያ ፲፱ (19) ቀን። ❤ እንኳን #ለአርማንያ_ሰው_የፋርስ_ኤጲስቆጶስ ለከበረ #አባ_ስምዖንና ከእርሱም ጋራ #መቶ_ሃምሳ_ሰማዕታት ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #አባ_ስምዖንና_መቶ_ሃምሳ_ሰማዕታት፦ ይህ አባት የአርማንያ ሰው የፋርስ ኤጲስቆጶስ ነው። ❤ ይህም ቅዱስ ትከሻ ነቃይ የተባለ የሐርመዝ ልጅ ሳቦር ግዛት ውስጥ ይኖራል ይህም ሳቦር ሌላውን ንጉሥ ድል በሚያደርግ ጊዜ አሥሮ ትክሻውን ይመዝዘዋልና ትከሻ ነቃይ ተባለ። ይህም ከሀዲ ለጣዖት እንዲሰግዱ እያስገደደ ምዕመናንን በጽኑዕ ሥቃይ አሠቃያቸው። ❤ ይህም የከበረ አባ ስምዖን ለንጉሥ ሳቦር መልእክት ጽፎ ላከለት እንዲህ የሚል "የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከበረ ደሙ የዋጃቸው ከሰው ተገዢነት ድነዋል የክብር ባለቤት የክርስቶስ ተገዥ ናቸውና። ስለዚህ ተገዥ መሆን ከተሠራው ሕግ አብዝቶ መገበርም አይገባቸውም። የሕያው እግዚአብሔርን ሕግ ለለወጡ ከሀድያን አይገዙም። ስለ እርሳቸው ደሙን በአፈሰሰ በክብር ባለቤት በክርስቶስ ስም እንዲሞቱ እነርሱ ይመርጣሉ"። ንጉሥ ሳቦርም መልእክት በአነበበ ጊዜ በዚህ አባት ላይ እጅግ ተቆጣ በሁለት ሰንሰለትም አሥሮ በእሥር ቤት ጣለው በዚያም ሃይማኖታቸውን ክደው ሰማይን ያመለኩ እነርሱም በሌላ የታሠሩ ብዙ እሥረኞችን አገኘ። ይህ ቅዱስም ገሠጻቸው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምነው መሰገሩ ራሶቻቸውንም ቆረጡአቸውና የሕይወት አክሊል ተቀበሉ። ❤ ከዚህም በኋላ ይህን አባት ወደ ምስክርነት ሸንጎ አቀረቡት ከእርሱም ጋራ መቶ ሃምሳ ሰዎች አሉ እነርሱም አንገታቸውን እስከ ቆረጡአቸውና አክሊል እስከ ተቀበሉ ድረስ ያጽናናቸው ነበር። ከእርሳቸውም አንዱ ሰይፍን ከመፍራት የተነሣ ደንግጦ ሃይማኖቱን ሊክድ ወደደ በዚያ ከቆሙት አንዱ "አትደንግጥ የሰይፍ በትር ዓይንህን ከሸፈንክ ምንም አይደለም ጽና። ከሰማዕታት ጋራ ተቆጥረህ በክብር ባለቤት ክርስቶስ ጋራ ለዘላለም ነግሠህ ትኖራለህ" ብሎ አጽናናው። እንዲሁም አደረገ የሕይወት አክሊልንም ተቀበለ። ስሙ ባሴቅ የተባለ ያንን ያጥናናውን ሰው ከሰሱት ንጉሡም አስቀርቦ ምላሱን አስቆረጠው። ቆዳውንም አስገፈፈውና ነፍሱን አሳለፈ የድል አክሊልንም ተቀበለ። ❤ ከዚህም በኋላም የከበረ ስምዖንን ወደ እርሱ አቅርቦ "ለአማልክት ስገድ ያለዚያ በጽኑ ሥቃይ አሠቃይሃለሁ" አለው። ቅዱስም ትእዛዙን አልሰማም ሥቃዩንም አልፈራም ያን ጊዜም ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዝዞ ቆረጡት በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕታትን አክሊል ተቀበለ። በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ19 ስንክሳር።                            ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለስምዖን_ለአርማንያ_ሞገሳ። ወለሀገረ ፋርስ ኤጲስቆጶሳ። በዐውደ ኵነኔ ወስምዕ ትዕግሥተ ሕማም ዘለብሳ። ሰላም ሰላም ወ፻ ወ፶ሳ። እለ ነፍሳቲሆሙ ክብረ በሰማይ ወረሳ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሚያዝያ_19።                          ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦"እስመ አመርከነ እግዚኦ። ወፈተንከነ ከመ ይፈትንዎ ለብሩር። ወአባእከነ ውስተ መሥገርት"። መዝ 65፥10-11። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 8፥12-18፣ 1ኛ ዮሐ 4፥3-9 እና የሐዋ ሥራ 5፥33-36 የሚነበበው ወንጌል ማቴ10፥16-23። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይም የቅዱስ ባስልዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም  የበዐለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤ ❤ እንኳን #ለትንሣኤ_ሦስተኛ_ሳምንት_ለኤማሁስ_መንገደኞች መታሰቢያ ቀን እግዚአብሔር በሰላምና በጠረ አደረሰን።                           ✝ ✝ ✝ ❤ #የዚህ_ሳምንት_መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ በ፩ "#ወበእሑድ_ሰንበት_ጌሠት_ማርያም_ መግደላዊት በጽባሕ ኀበ መቃብር እንዘ ዓዲ ጽልመት ወረከበት ዕብነ ዕቱተ እምአፈ መቃብር ወበጽሐት ኀበ #ስምዖን_ጴጥሮስ ወኀበ ካልዕ ረድዕ #ዘያፈቅሮ_ኢየሱስ ወትቤሎሙ ነሥእዎ ለእግዚእየ እምውስተ መቃብር ወኢየአምር ኀበ ወሰድዎ እንዘ ይረውጹ ክልኤሆሙ ኅቡረ በድሮ ለጴጥሮስ ዝኩ ካልዕ ረድእ ዘያፈቅሮ ኢየሱስ"። ትርጉም፦ #በእሑድ_ሰንበትም_ማርያም_መግደላዊት ገና ጨለማ ሳለ ገሥግሣ ወደ መቃብር ደንጊያውንም ከመቃብሩ አፍ ተነሥቶ አገኘች ፈጥናም ወደ ስምዖን ጴጥሮስ ኢየሱስ ይወደው ወደ ነበረው ወደ ሁለተኛው ደቀ መዝሙር ደረሰች፤ ጌታዬን ከመቃብር የወሰዱበትን አላውቅም አለቻቸው #ቅዱስ_ጴጥሮስም ያ #ሁለተኛውም_ደቀ_መዝሙር ወጡና ወደ መቃብር ሄዱ ሁለቱም በአንድነት ሲሮጡ ያ ሌላው ደቀ መዝሙር #ቅዱስ+ጴጥሮስን_ቀድሞት ወደ መቃብር ደረሰ። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ይእዜ እትነሣእ ይቤ እግዚአብሔር። እሬሲ መድኀኒተ ወአግህድ ቦቱ። ቃለ እግዚአብሔር ቃል ንጹሕ"። መዝ 11፥5። የሚነበቡት መልእክታት 2ኛ ቆሮ 5፥11-ፍ.ም፣ 2ኛ ጴጥ 3፥14-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 21፥31-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 24፥13-33። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የበዓለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤         ❤ #ሚያዝያ ፲፰ (18) ቀን። ❤ እንኳን #ለቅዱስ_ሱስንዮስ አገልጋይ #ለቅዱስ_አውሳብዮስ ለዕረፍቱ በዓል፣ #ለአባ_ብሶይ_ወንድም_ለአባ_ጴጥሮስ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከበጠርሴስ _አገር ውስጥ መከራ ከተቀበሉ #ከከበሩ_ሰማዕታት ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                              ✝ ✝ ✝ ❤ #የቅዱስ_ሱስንዮስ_አገልጋይ_ቅዱስ_አውሳብዮስ፦ ከዲዮቅልጥያኖስ ቅዱስ ሱስንዮስን በሚያሠቃየው ጊዜ ንጉሥ ሆይ "ለሱስንዮስ አውሳብዮስ የሚባል አገልጋይ አለው እርሱም በፍጹም ልቡ እንደ ጌታው ክርስቶስን ያመልከዋል የአንተን አማልክት አያመልኩት" አሉት "አምጡት" አለ። ወደርሱም በቀረበ ጊዜ ስለ ሃይማኖቱ ጠየቀው እርሱም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  ታመነ። ንጉሡም ብዙ አባበለው አማልክቶቹን ማምለክ በመተዉም ገሠጸው ቅዱሱም የእውነተኛ አምላክ የእግዚአብሔር አምልኮ በመተዉ ንጉሡን መልሶ ገሠጸው። ስለዚህም ንጉሥ ቊጣን ጨምረ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። ይህም ቅዱስ ከጌታው ከሱስንዮስ ቀድሞ የሰማዕትነትነት አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። የቅዱስ አውሳቢዮስ  በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #የአባ_ብሶይ_ወንድም_አባ_ጴጥሮስ፦ የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም ሲድራቅ የእናቱ ስም ማርያም ነው። ይህንንም ቅዱስ በወለዱት ጊዜ ከርሳ የምትባል የእናቱ እኅት ወስዳ ከልጅዋ ጋራ አሳደገችው። ሰባት ዓመትም በሆናቸው ወደ መምህር ወሰደጀቻቸውና የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሕጉንም ተማሩ በጾም በጸሎትም ሲጋደሉ ኖሩ። የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤልም ተገለጠላቸው ስለ ክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ምስክር እንዲሆኑ ነገራቸው። ❤ ከጥቂት ወራትም በኋላ ሰይጣን ከዲዮቅልጥያኖስን አስቶት ለጣዖት በሰገደ ጊዜ እሊህን ቅዱሳን ክርስቲያኖች እንደሆኑ ነገር ሠሩባቸው። የእንዴናው ገዥ አርያኖስም ወደርሱ አስቀርቦ ለጣዖት እንዲሰግዱ ግድ አላቸው እምቢ በአሉትም ጊዜ ደማቸው እስኪፈስ ከባላ ላይ ሰቅለው እንዲገርፋቸው አዘዘ። ከጾምና ከስግደት የተነሣ ሥጋው ስለደከመ የሥቃዩ ሕማም ለአባ ጴጥሮስ ታወቀው ያን ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ከሕማሙ ፈወሰው። አርያኖስም አይቶ አባ ጴጥሮስ ወደ ምሥራቅ አገር ወስደው በዚያ ራሱን በሰይፍ  አዘዘ። ❤ አባ ብሶይም እንዲቆርጡት በእሥር ቤት እያለ መልአክ ነጥቆ ወደ ወንድሙ ወደ ጴጥሮስ አደረሰው። እርስበርሳቸውም ተቃቅፈው ተሳሳሙ በሰማያዊት ኢየሩሳሌምም እንዲሰበስባቸው ወደ ጌታችን ጸለዩ እነሆ ወደ እርሳቸውም ከሰማይ ቃል መጣ። እንዲህ የሚል "ተጋዳዮች ሆይ በሰማያት በብዙ ጉባኤ መካከል ትኖራላችሁና ሰላም ይሁንላችሁ ሥጋችሁም በምድር አይለያይም"። ከዚህም በኋላ መልአክ አባ ብሶይን ወደ እሥር ቤት መለሰው። ጭፍሮችም ኃይል ድል አድራጊ አባ ጴጥሮስ ራሱን ቆረጡ ሥጋውንም በዕንጨት ላይ ሰቀሉ። አባ ብሶይም በጭልታ ይሰደው ዘንድ የእሥር ቤት ጠባቂውን ለመነው ሒዶም የአባ ጴጥሮስን ሥጋ ዋጀው በሽቱ አድርጎ ገንዞም በሥውር ቦታ ቀበረው። የአባ ጴጥሮስ በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ18 ስንክሳር።                            ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለጴጥሮስ_ሠናይ_ላህይ_ወገጹ። በምግባረ ንዱቁ ወበሃይማኖት ሕኑጽ። ሶመ አመትሮ መኰንነ ግብጽ። ድኅረ ወድቀ መልዕልተ ምድር ርእሱ ቅሩጽ። ሥጋሁ ወዐለ ስቁለ በዕፅ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሚያዝያ_18።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤        ❤ #ሚያዝያ 18 (፲፰) ቀን። 🌹 እንኳን #ለታላቁ_አባት_ሰው_ቢረሳ_ቢረሳ_ምግቡን_አይረሳምና #ስብሐት_ብሎ_በእንተ (ስለ) አባ አቢብ  ብሎ በሚመገብ ጊዜ  ያሰበውን እምርልሃለሁ ብለው ታላቅ ቃል ኪዳንን መድኃኔዓለም ለሰጣቸው፤ የጌታችንን መከራ መስቀሉን በማሰብ #ራሳቸውን_ሰባት_ጊዜ_ለገደሉ ለታላቁና ክቡሩ ለሆኑ #አባ_አቢብ_ለተባሉት_ለመስተጋድል_አባ_ቡላ ራሱን አንድ መኰንን በሰይፍ በቆረጣቸው ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል ከሰማይ ወርዶ ከሙታን ለይቶ ላስነሳቸው ዓመታዊ ክብረ በዓል እግዚአብሔር በሰላምና በጤና አደረሰን።                            ✝ ✝ ✝ ❤ #አባ_ብላ (#አቡነ_አቢብ)፦ የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም አብርሃም የእናቱም ስም ሐሪክ ነው እነርሱም ከሮሜ አገር ሉፊ ከሚባል አውራጃ ናቸው በዘመናቸውም ከሀዲው ንጉሥ መክስምያኖስ በክርስቲያን ወገኖች ላይ መከራ ስለ አመጣ ስደት ሁኖ ነበርና እነርሱም በስደት ብዙ ዘመን ኖሩ። ❤ ልጅንም በአጡ ጊዜ የተባረከ ልጅን ይሰጣቸው ዘንድ በጾም በጸሎት ተወስነው ወደ እግዚአብሔር ለመኑ የእግዚአብሔር መልአክ በሕልም ተገለጠላቸውና ፍሬ የመላበትን ዘለላ ሰጣቸው። ይህም ቅዱስ በተፀነሰ ጊዜ በቤታቸው አጠገብ ታላቅ ዛፍ በቀለ በቅጠሉም ላይ በሮማይስጥ ቋንቋ "ቡላ የእግዚአብሔር አገልጋይ በጽዮንም አድሮ የሚኖር የያዕቆብ ፈጣሪ ያከበረው" የሚል ጽሑፍ ነበረበት። ❤ በተወለደም ጊዜ ክርስትና ሳያስነሡ ዓመት ሙሉ አኖሩት እመቤታችን ማርያምም ለሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ለሰለባስትርዮስ ተገልጣ ወደ አብርሃም ቤት ሒዶ ሕፃኑን እንዲአጠምቀው አዘዛችው እርሱም ሒዶ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው ስሙንም "ቡላ" ብሎ ሰየመው እናትና አባቱም ሳይነግሩት "ቡላ" ብሎ ስለሰየመው አደነቁ "ዕፁብ ዕፁብ" አሉ። ❤ ከዚህም በኋላ ሊቀ ጳጳሳቱ በጸለየ ጊዜ የቊርባን ኅብስትና ወይን የተመላ ጽዋ ከሰማይ ወረደ እርሱም ቀድሶ ሥጋውንና ደሙን ከሕፃኑ ጋር አቀበላቸው በዚያንም ጊዜ ሕፃኑ የአንድ ዓመት ልጅ ሲሆን "በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሆነ አብ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሆነ ወልድ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከአብ ከወልድ ጋር አንድ የሆነ መንፈስ ቅዱስ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው" ብሎ ተናገረ። ❤ ከጥቂት ዘመንም በኋላ አባትና እናቱ ኅዳር ሰባት ቀን ሙተው ሕፃኑ ብቻውን ቀረ። ሕፃኑም ዐሥር ዓመት በሆነው ጊዜ ለጣዖት መስገድን የሚያዝ ከሀዲ መኰንን መጣ ቅዱስ ቡላም በሰማ ጊዜ ወደ መኰንኑ ሒዶ የረከሱ አማልክቶቹን ረገመ መኰንኑም በአካል ታናሽነቱን አይቶ እጅግ አደነቀ በዚያንም ጊዜ በችንካር እንዲቸነክሩት ሥጋውንም እንዲሠነጥቁት ቆዳውንም ከዐጥንቱ እንዲገፋ እጆቹንና እግሮቹንም በመጋዝ እንዲቆርጡ ጀርባውንም እንዲገርፋ በሾተሎችና በጦሮች መካከል አድርገው በመንኰርኲር ውስጥ እንዲጨምሩት ዳግመኛም በመንገድ ላይ እንዲጐትቱት አዘዘ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም መጥቶ አዳነው ያለ ጉዳትም ጤነኛ አደረገው። ❤ ከዚህም በኋላ ወደ ሌላ መኰንን ሒዶ እርሱንና የረከሱ ጣዖቶቹን ረገመ መኰንኑም ተቆጥቶ #በሚያዝያ_ወር_18_ቀን ራሱን በሰይፍ ቆረጠው ቅዱስ ሚካኤል ከሰማይ ወርዶ ከሙታን ለይቶ አስነሣው ወደ አንድ ገዳምም ወስዶ የምንኲስና ልብስንና አስኬማን በመስቀልም ምልክት አለበሰው። እንዲህም አለው "ከቅዱሳን ጻድቃን አንድነት ትሆን ዘንድ እግዚአብሔር አዝዞሃል"። ያን ጊዜም ቅዱስ አባ ቡላ ከደረቅ ተራራ ላይ ወጣ ያለ ማቋረጥም በውስጧ እየተጋደለ ኖረ። የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መከራውንና ስቅለቱን በአሰበ ጊዜ ከረጅም ዕንጨት ላይ በመውጣት ራሱን ወደታች ሁል ጊዜ ይወረውር ነበር። ❤ በአንዲትም ቀን ከዛፍ ላይ በተወረወረ ጊዜ ሰይጣን ሊገድለው ስለ በረታበት ሞተ ያን ጊዜም ክብር ይግባውና መድኃኒታችን ከሞት አነሣውና እንዲህ አለው "ከእንዲህ ስምህ ቡላ አይሁን አቢብ ይባል እንጂ የብዙዎች አባት ትሆናለህና"። እርሱም የክርስቶስን ፍቅር እጅግ ጨመረ ፊቱንም እየጸፋ ሥጋውን በየጥቂቱ እየቆረጠ ጀርባውንም ሰባት መቶ ጊዜ እየገረፈ ኖረ ጌታችንም ይፈውሰው ነበር በየእሑድም ቀን ከቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያም እንደተወለደ በሌሎች ቀኖችም እንደተያዘና ከአይሁድ መከራ እንደ ተቀበለ ሁኖ ይገለጽለት ነበር። ስለዚህም ሳይበላ ሳይጠጣ አርባ ሁለት ዓመት ኖረ ዳግመኛም ናላው ፈስሶ እስቲአልቅ ዐሥራ ሁለት ወር በራሱ ተተክሎ ኖረ። ❤ በአንዲትም ቀን የጌታችንን መከራ በአሰበ ጊዜ ሰይፋን በአንጻሩ ተከለ ከዕንጨት ላይም ወጥቶ በላዩ ወድቆ ሞተ ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምም ከአእላፍ መላእክት ጋር መጥታ "የእኔና የልጄ ወዳጅ ሰላምታ ይድረስህ" አለችው። ከበድኑም ቃል ወጥቶ "የሰማይና የምድር ንግሥት እመቤቴ ሰላምታ ይገባሻል" አላት እርሷም በከበሩ እጆቿ ዳሥሣ ከሞት አስነሣችው። ❤ ዕድሜውንም ፈጽሞ ከዚህ ዓለም የሚወጣበት ጊዜ ሲደርስ ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ በእጁ ልዩ የሆኑ አክሊሎችን የሚያበሩ ልብሶችም ይዞ ተገለጠለት "ወዳጄ አቢብ ሆይ በማያልቅ ተድላ ደስታ ደስ አሰኝህ ዘንድ ወደእኔና ስምህን ለሚጠራ፣ መታሰቢያህን ለሚያደርግ እኔ ኃጢአቱን አስተሠርይለት ዘንድ በራሴ ማልኩልህ ወይም ለተራቆተ የሚያለብሰውን ለተራበም የሚያጠግበውን፣ ለተጠማ የሚያጠጣውን፣ የገድልህን መጽሐፍም የሚጽፈውን ወይም የሚያነበውንና የሚሰማውን፣ በጸሎትህም የሚታመኑትን ሁሉ እስከ ዐሥር ትውልድ እምራቸዋለሁ" ይህንም ብሎ አፋን ሳመው በደረቱም ላይ አድርጎ ወደአየር አወጣው የመላእክትንም ምስጋና በሰማች ጊዜ ነፍሱ ከሥጋው ጥቅምት 25 ቀን ተለየች ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ገባች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ አባት በአባ ብላ (አቡነ አቢብ) ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

❤ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።❤          ❤ #ሚያዝያ ፲፯ (17) ቀን። ❤ እንኳን #ለዘብዴዎስ_ልጅ ለወንጌላዊ #ቅዱስ_ዮሐንስ ወንድም ለሆነ፤ የእንስሳና የአራዊት የሰማይ ወፎችንም ቋንቋ ያውቅ ለነበረ ለሐዋርያው #ለቅዱስ_ያዕቆብ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል በሰላም አደረሰን።                           ✝ ✝ ✝      ❤ #ሐዋርያው_ቅዱስ_ያዕቆብ፦ ይህም ሐዋርያ በእስያ ውስጥ ከአስተማረ በኋላ ዕርቅ በተገኘባት በእውነተኛ አምላክ በጌታችን ወንጌል ሊያስተምራቸው ወደ ተበተኑ ወደ ዐሥራ ሁለቱ ነገድ ወጣ። እነርሱም አንድ አምላክን የሚአመልኩ አልነበሩም እየራሳቸው የመረጡትን የሚአስቷቸው ጣዖታትን ያመልኩ ነበረ እንጂ። ከቄሣር ሥልጣን በታች የተሾመ ኄሮድስም ሹመቱ በሚዳብር መንግሥቱ በሚያጽና ገንዘብ ብዙ ግብር እንዲገብሩ እጅ መንሻም እንዲአስገቡ አዘዘ። ❤ ቅዱስ ያዕቆብ ግን ወደእርሳቸው በደረሰ ጊዜ በአገራቸው ቋንቋ ሰበከላቸው የፍጥረትን ሁሉ ቋንቋ ማወቅን እግዚአብሔር ሰጥቶት ነበርና የሚያውቀው የሰው ቋንቋ ብቻ አልነበረም የእንስሳና የአራዊት የሰማይ ወፎችንም ቋንቋ ነበረ እንጂ። በውስጣቸው በሰበከም ጊዜ የከፋ ሥራቸውን ትተው በሕያው እግዚአብሔር በአንድ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወት በሆነ መንፈስ ቅዱስ ነፍሶቻቸው በእጁ ውስጥ በተያዙ በአንድ አምላክ እንዲያምኑ አዘዛቸው ። እርሱም በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ የሚመጣ ነው። ዳግመኛም በማይጠፋና በማይበላሽ በሰማያት ድልብ ይሆናቸው ዘንድ ከገንዘባቸው ለችግረኞችና ለድኆች እንዲመጸውቱ አዘዛቸው። ❤ ትምህርቱንም በሰሙ ጊዜ ከክፋ ሥራቸው ተመልሰው በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። ሐዋርያ ቅዱስ ያዕቆብም ትምህርቱን ፈጥነው ስለተቀበሉት እጅግ ወደዳቸው በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው በየአገራቸው ቤተ ክርስቲያን ሠራላቸው። ዳግመኛም ከእንስሶቻቸው ከሚዘሩአቸው እህሎችና ወይን አትክልቶች ፍሬዎች ለካህናትና ለድኆች ምግብ ሊሆን ለቤተ ክርሰቲያን የመጀመርያውን መባ እንዲሰጡ አዘዛቸው። ሕዝቡም በአንድ ቃል ያዘዝከንን ሁሉ እኛ እናደርጋለን አሉት። ከዚህ በኋላ ከእንስሳት መጀመሪያ የተወለደውን ከእህሉም ቀዳምያቱንና ዓሥራትን ለቤተ ክርስቲያን አመጡ። ❤ ኄሮድስም ቅዱስ ያዕቆብ ለቤተ ክርስቲያን መባ ይሰጡ ዘንድ እንዲሚያዝ በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ ጭፍራ ልኮ ወደርሱ አስመጣውና "ሕዝቡ ገንዘባቸውን ሁሉ ለድኆች ምጽዋትና ለቤተ ክርስቲያን መባ እንዲሰጡ የምታዝ አንተ ነህን" አለው። "አዎን እኔ ነኝ" አለው ያን ጊዜ ኄሮድስ ተቆጥቶ ራሱ በሰይፍ ሚያዝያ 17 ቀን አንገቱን መትቶ ቆረጠው። በኢየሩሳሌምም ሁከትና ሽብር ሆነ ደግሞ ከፋሲካ በዓል በኋላ ሊገድለው አስቦ የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ ወስዶ አሠረው የእግዚአብሔር መልአክም ኄሮድስን ቀሠፈው ተልቶ ተበላሽቶ ሞተ ልዑል አምላክን አላከበረውምና። ❤ የቅዱስ ያዕቆብን ሥጋ ግን ምዕመናን ወሰዱት ገንዘው በቤተ መቅደስ ውስጥ ቀበሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የሐዋርያው የቅዱስ ያዕቆብ በረከት ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ 17 ስንክሳር።                            ✝ ✝ ✝   ❤ "#ሰላም_ዕብል_ሐዋርያ_ፍንወ። አኅወ ወንጌላዊ #ዮሐንስ እንተ ይሄሉ ሕያው። አህጒራተ ይስብክ ጊዜ አንሶሰወ። ድምፀ አራዊት ወዘአዕዋፍ ንቃወ። በመንፈስ #ቅዱስያ_ዕቆብ ለበወ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) የሚያዝያ 17።                             ✝ ✝ ✝           ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ለእለ የዐቅቡ ሕጎ። ወይዜከሩ ትእዛዞ ከመ ይግበሩ። እግዚአብሔር አስተዳለወ መንበሮ በሰማያት"። መዝ 102፥18-19። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 20፥20-29።                          ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ሊተሰ ተሊወ እግዚአብሔር ይኄይሰኒ። ወትውክልትየኒ ላዕለ እግዚአብሔር። ከመ ዕንግር ኵሎ ስብሐቲሁ"። መዝ 72፥28። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 12፥1-12፣ ያዕ 1፥1-17 እና የሐዋ ሥራ 12፥1-12። የሚነበበው ወንጌል ማር 1፥19-23። የሚቀደሳው ቅዳሴ የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ ወይም የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ነው። መልካም የሐዋርያ የቅዱስ ያዕቆብ የዕረፍት በዐልና የበዐለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤        ❤ #ሚያዝያ ፲፮ (16) ቀን። ❤ እንኳን #ለወንጌላዊው_ቅዱስ_ዮሐንስ ረድኡ (አገልጋዩ) ለሆነ ለበአርማ አገር ኤጲስቆጶስ #ለቅዱስ_አንቲቦስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ #ከሰማዕት_ሳባ ከመታሰቢያው ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                            ✝ ✝ ✝ ❤ #ቅዱስ_አንቲቦስ፦ እርሱም የመለኮትን ነገር ለሚናገርና ለወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ረድኡ ነው። እርሱም ከአይሁድ ወገን በግዛቱ ውስጥ አንድ ሰው የሚታይ እስከ አልሆነ ድረስ አይሁድን ያጠፋቸውና ኢየሩሳሌምንም በአፈረሳት በአስባስያኖስ ልጅ በግማትያኖስ ዘመን ነበር። ከእስራኤል መንግሥት ትውልድ ያላቸውንም ብዙዎችን ገደላቸው ለመንግሥቱና ለራሱ ስለ ፈራ ነው። የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ አምላካቸውና ንጉሣቸው ድል አድራጊና እርሱም ወገኖቹ እንደሆኑ ክርስቲያኖች ይናገራሉና ስለዚህ ከአማንያን ብዙዎችን ገደለ። ❤ ወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስም ከእርሱ ሸሸ የዮሴፍ ልጅ በሮሜ ከተማ ታሥሮ ሳለ ወደ ኢየሩሳሌም ጭፍራ ልኮ የይሁዳን ተወላጆች ወደርሱ አስመጣቸው የክብር ባለቤት ስለሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ መንግሥት በጠየቃቸው ጊዜ ክርስቶስ ሰማያዊ ንጉሥና በሰማያት የሚኖር እንደሆነ በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ ለሁሉም እንደየሥራው ሊከፍለው ዳግመኛ ይመጣ ዘንድ እንዳለው አስረዱት። ይህንንም ሰምቶ እጅግ ፈራ ክርስቲያኖችንም ማሠቃየቱን ተዋቸው። ❤ ቅዱስ አንቲቦስ ግን የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስን ሊአስክደው ሽቶ ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃየው እርሱም በሥቃዩ ውስጥ በመታመን ጸና። ከዚህም በኋላ ከናስ በተሠራ በላም ፈጅ ጋን ውስጥ አድርገው ከበታቹ እሳትን አነደዱ እርሱም በውስጧ ሁኖ ስለከበረ ስሙ ምስክር ሊሆን ያደውን እግዚአብሔርን ፈጽሞ ያከብርና ያመሰግን ነበር። ❤ ከዚህም በኋላ ስሙን ለሚጠሩና መታሰቢያውን ለሚያደርጉ ከነፍስ ከሥጋ ደዌ ሁሉንም ይፈውሳቸው ዘንድ እግዚአብሔር ፈለገ።  ከዚህም በኋላ ከነሐስ በተሠራው በላም ፈጅ ውስጥ የምስክርነቱን ተጋድሎ ፈጽሞ ሚያዝያ 16 ቀን ነፍሱን ሰጠ። በድኑንም ሲጥሉት ምዕመናን አንሥተው በታላቅ ክብር ፈጽሞ እያመሰግኑ ወስደው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩት። ❤ እርሱም አስቀድሞ በግዞት ቤት ሳለ ከወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ ዘንድ የሚያጽናናውና የሚያአረጋጋው "ቸር ጠባቂ እረኛና ታማኝ አገልጋይ ካህን" የሚለው መልእክት ወደርሱ መጣ። እንዲህም ብሎ ሁለተኛ ነገረው "በሰማዕትነት እንደሚሞት አንተ በከበሩ ሐዋርያትና ከሰማዕነት ጋራ ተቆጥረሃል"። ❤ ደግሞ ከሥጋው ጣፋጭ የሽቱ ቅባት እንደሚፈስ ስለርሱ ተነገረ እርሱም መዓዛው እጅግ ጣፍጭ የሆነ በእምነት ለሚሻው ሁሉ እስከ ዛሬ ጠቃሚ የሆነ ነው። የቅዱስ አንቲቦስ በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።                            ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ዘገብረ ሰማየ ወምድር። ሰማየ ሰማያት ለእግዚአብሔር። ወምድርሰ ወሀበ ለእጓለ እምሕያው"። መዝ113፥23-24። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 15፥50-59፣ 3ኛ ዮሐ 3፥1-1-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 5፥34-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 15፥17-26። የሚቀደሰው ቅዳሴየ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይም የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ  ቅዳሴ ነው። የበዓለ ሃምሳ ሰሞኑንና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤        ❤ #ሚያዝያ ፲፭ (15) ቀን። ❤ እንኳን #ለመጥምቁ_መለኮት_ለሰማዕቱ #ለቅዱስ_ዮሐንስ ነፍሱ ከተቆረጠች ራሱ ጋራ በአየር ውስጥ #እየዞረች_ዐሥራ_አምስት_ዓመት ካስተማረች በኋላ ተለይታ ለወጣችበት መታሰቢያ በዓል፣ ከሰባ ሁለቱ አርድእት ለአንዱ #ለሐዋርያ_ቅዱስ_አጋቦስ ለመታሰቢያው በዓሉና ለከሀዲ ለዱድያኖስ ንጉሥ ሚስት ለከበረች #ቅድስት_እለእስክድርያ ሰማዕትነት ለተቀበለችበት ለዕረፍቷ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ የአገረ ሜራ ኤጲስቆጶስ በሆነ #በአባ_ ኒቆላዎስ ስም ለያዕቆባውያን ወገን በግብጽ አገር ያለች ቤተ ክርስቲያን ከከበረችበትና #ከአቡነ_አቢብ ከመታሰቢያቸው ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                            ✝ ✝ ✝ ❤ #ሐዋርያው_ቅዱስ_አጋቦስ፦ እርሱም በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ይታወሳል በሐዋርያው በቅዱስ ጳውሎስ ትንቢት እንደተናገረ ሁለተኛም በቀላውዴዎስ ቄሣር ዘመን ታላቅ ረኃብ እንደሚመጣ ተናገሮ ትንቢቱም ተፈጸሞ ረኃብ ቸነፈር መጥቶ ብዙዎች ሕዝቦችን አጠፋቸው። እነሆ ከገድሉ የቀረውን የካቲት አራት ቀን ጽፈናል። ከቅዱስ አጋቦስ በጸሎቱ የምትገኝ በረከቱ ከእኛ ጋራ ትኑር አሜን።                               ✝ ✝ ✝ ❤ #ቅድስት_እለእስክድርያ፦ ይችም ቅድስት ለከሀዲ ለዱድያኖስ ንጉሥ ሚስት ናት። ሰማዕነት የቀበለችበት ምክንያት ይኸውም ለጣዖቶቹ እንደሚሠዋ መስሎ ቅዱስ ጊዮርጊስ በዘበተበት ጊዜ ዝንጉዕ ዱድያኖስም ዕውነት መስሎት ራሱን ሊስም ተነሣ። ቅዱሱ ግን ለአማልክት ከመሠዋት አስቀድሞ አይሆንም ብሎ እንዳይስመው ከለከለው። ከዚህም በኋላም ዱድያኖስ ወደ ቤተ መንግሥቱ አዳራሽ ቅዱስ ጊዮርጊስን አስገባው በዚያም በንግሥት እለእስክድርያ ፊት የዳዊትን መዝሙር በማንበብ ጸለየ። በስማችም ጊዜ ይተረጒምላት ዘንድ ለመነችው ያን ጊዜም ተረጐመላት የክብር ባለቤት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ጌትነቱን ገለጠላት ትምህርቱም በልቡዋ አድሮ በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመነች። ❤ ከዚህ በኋላ ሲነጋ ለአማልክት ወደሚሠዋበት ቅዱስ ጊዮርጊስን ወሰዱት እርሱም የረከሱ አማልክትን ትውጣቸው ዘንድ ምድርን አዘዛት ምድርም ዋጠቻቸው። ንጉሥ ዱድያኖስም አፈረ እየአዘነና እየተከዘ ወደ ሚስቱ ወደ እለእስክድርያ ዘንድ ገባ። እርሷም "ክርስቲያኖችን አትጣላቸው አምላካቸው ጽኑዕና ኃያል ነው አላልኩህምን" አለችው። ይህንንም ሰምቶ በእርሷ ላይ ተቆጣ ያሠቃዩዋት ዘንድ ጡቶቿንም ሠንጥቀው ይሰቅሏት ዘንድ አዘዘ። የሰማዕትነትንም አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለች። እግዚአብሔር በጸሎቷ ይማረን ለዘላለሙ አሜን።                            ✝ ✝ ✝ ❤ በዚች ዕለት #የመጥምቁ_የቅዱስ_ዮሐንስ ነፍሱ ከተቆረጠች ራሱ ጋራ በአየር ውስጥ እየዞረች ዐሥራ አምስት ዓመት ካስተማረች በኋላ ተለይታ የወጣችበት ሆነ በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።                            ✝ ✝ ✝ ❤ በዚች ቀን የአገረ ሜራ ኤጲስቆጶስ በሆነ #በአባ_ኒቆላዎስ ስም ለያዕቆባውያን ወገን በግብጽ አገር ያለች ቤተ ክርስቲያን የከበረችበት መታሰቢያ ሆነ። ❤ ይህም ኒቆላዎስ ስለ ከሀዲው አርዮስ በኒቅያ ከተማ ከተሰበሰቡት ከሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ሃይማኖታቸው ከቀናች ኤጲስቆጶሳት አንዱ ነው። ይቺም በእስክንድርያ ምሥራቅ ያለች ቤተ ክርስቲያን በአባ ሲኖዳ ገድል የታወቀች ናት። ❤ ይህም ቅዱስ በተጋድሎው እጅግ ከፍ ከፍ አለ በዲዮቅልጥያኖስ መኳንንት ፊት እምነቱን በመግለጥና በመታመን ብዙ መከራና ሥቃይ ደረሰበት። ከሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት የከበሩ ሊቃውንት ጋራ በአንድነት ለመሰብሰብ እስቲደርስ እግዚአብሔር ጠብቆ አተረፈው። የዚህአባት ተአምራቶቹ የብዙና በአራቱ ማዕዘን የተገለጡ ናቸው በሰላም በፍቅር ዐረፈ። በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ 15 ስንክሳር።                             ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለዮሐንስ_እንተ_ዐብየ_ሞገሱ። እምትውልደ አንስት ኵሉ እለ ዘበሕግ ተፀነሱ። ወከመ ታውፊ ሰጊዶ ለልዑል ስብሐት ንግሡ። ለሠርቀ ወርኅ ቀዳማይ አመ ሠላስ ታሕማሱ። እምነ ሠራሪት ርእሱ ተፈልጠት መንፈሱ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሚያዝያ_15።                            ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እስመ አንተ ረዳእየ እግዚኦ። ውስተ እዴከ አመኃፅን ነፍስየ። ቤዝወኒ እግዚአብሔር እምላክ ጽድቀ። መዝ 30፥4። 2ኛ ቆሮ 2፥8-1-10 እና የሐዋ ሥራ 11፥27-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 14፥1-13። የሚቀደው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይም የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ ነው መልካም የበዓለ ሃምሳ ሰሞንና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።