805
مشترکین
اطلاعاتی وجود ندارد24 ساعت
اطلاعاتی وجود ندارد7 روز
-130 روز
آرشیو پست ها
#2ኛ_ቀን_የፀሎት_ርዕስ
🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥
ሰው ከእግዚአብሔር የተሰጠውን ማንነት ተረድቶ እንዲኖር በእግዚአብሔር ክብር ውስጥ እንዲኖር ሁላችንም ቃሉን እያሰላሰልነው እንፀልያለን።
ዘፍጥረት 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²⁶ እግዚአብሔርም አለ፦ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር፤ የባሕር ዓሦችንና የሰማይ ወፎችን፥ እንስሳትንና ምድርን ሁሉ፥ በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ይግዙ።
²⁷ እግዚአብሔርም ሰውን በመልኩ ፈጠረ፤ በእግዚአብሔር መልክ ፈጠረው፤ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው።
²⁸ እግዚአብሔርም ባረካቸው፥ እንዲህም አላቸው፦ ብዙ፥ ተባዙ፥ ምድርንም ሙሉአት፥ ግዙአትም፤ የባሕርን ዓሦችና የሰማይን ወፎች በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ግዙአቸው።
#እንፀልያለን
ሰላም ውድ የካርዝማቲክ ቤተሰቦች በክረምት በሞጆ ሱባኤ ሴንተር ለምናደርገው ልዩ ሱባኤ የምንችል ሁሉ ከወዲሁ በፆም በፀሎት እንድንተባበር አደራ እንላለን። ለሚቀጥሉት 21 ቀናት የፀሎት ርዕሶቻችንን በእግዚአብሔር ፊት እናቀርባለን።
#1ኛ_ቀን_ሰኞ_የፀሎት_ርዕስ
🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥🔥
እግዚአብሔርን ባለማወቅ ምክንያት ሕይወታቸው ተመሰቃቅሎ በተለያየ ችግር ውስጥ ላሉ እህት ወንድሞቻችን እግዚአብሔርን ማወቅ እንዲሆንላቸው አልፎም በዚህ ሱባኤ እንዲሳተፉ እንፀልያለን።
ቆላስይስ 2
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
² ልባቸው እንዲጸናና፥ በፍቅርም ተባብረው በማስተዋል ወደሚገኝበት ወደ መረዳት ባለ ጠግነት ሁሉ እንዲደርሱ የእግዚአብሔርንም ምሥጢር እርሱንም ክርስቶስን እንዲያውቁ እጋደላለሁ፤
³ የተሰወረ የጥበብና የእውቀት መዝገብ ሁሉ በእርሱ ነውና።
ጥበብ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ
በክቡር አባ ጴጥሮስ በርጋ
በዮሐንስ ወንጌል ም. 4 ቁ 10 ላይ እንደ ተጠቀሰው መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ስጦታ ነው፡፡ እሱ እራሱ መንፈስ ቅዱስ ልባቸውን ከፍተው ለሚቀበሉት መንፈሳዊ ስጦታዎችን ያድላል፡፡ ከእነዚህም ስጦታዎቹ መሃከል አንዱ ስለሆነው ስለ ጥበብ፤ በራሱ በመንፈስ ቅዱስ እገዛ ተደግፈን እናስተነትናለን፡፡ ይህ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ የሆነው ጥበብ የእግዚአብሔርን ፈቃድ በሕይወታችን፣ በአገልግሎታችን በተሰማራንበት ቦታ ሁሉ እንድንገነዘብ የሚያደርገን ውስጣዊ ብርሃን ነው፡፡
ጥበብ ከሰው ዕውቀትና ልምድ ያልሆነ የመጀመሪያው የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ነው፡፡ ይህ ጥበብ በ1ኛው መጻፈ ነገስት 3፤9 ላይ ሰለሞን የእሥራኤል ንጉስ ተደርጎ በተሾመበት ዕለት እግዚአብሔር እንዲሰጠው የጠየቀው ስጦታ ነው፡፡ ስሆነም እንደ መጽሐፍ ቅዱስ አገላለጽ ጥበብ፤ ሁሉንም ነገሮች በእግዚአብሔር አይን መመልከት የመቻል ጸጋ ነው፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ የሆነው ጥበብ፤ ዓለምን፣ ሁኔታዎችን፣ ችግሮችን፣ ፈተናዎችን፣ ስኬትም ሆነ ሽንፈትን፤ የምንገኝበት ሁኔታ ሁሉ በእግዚአብሔር እሳቤ ውስጥ የመመልከት ችሎታ ነው፡፡ ጥበብ እኛ ነገሮችን በእግዚአብሔር ዓይን የማየት ብስለት እስክናዳብር ድረስ መንፈስ ቅዱስ በእኛ ውስጥ በቀጣይነት የሚያከናውነው ሥራ ነው፡፡ ይህን ዓይነት ጥበብ የምናገኘው ደግሞ ከራሱ ከእግዚያብሔር ጋር ካለን ግንኙነት ነው፡፡ እንደ ልጆች ሆነን ከእግዚያብሔር አባት ጋር ከምናደርገው ጉዞ ይመነጫል፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር የልጅነት ትሥሥር ሲኖረን፤ መንፈስ ቅዱስ እራሱ ይህንን የጥበብ ስጦታ ይሰጠናል፡፡ ከአምላክ ጋር ባለን ግንኙነት መንፈስ ቅዱስ ቀስ በቀስ ልባችንን፣ አስተሳሰባችንን ይቀይራል፤ እኛን ለእግዚአብሔር ፈቃድ ያዘጋጀናል፤ ፈቃዱንም የመረዳት ጥበብ ያጎናጽፈናል፡፡
ስሆነም እኛን እንደ ክርስቲያን ጥበበኞች የሚያደርገን መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ለሁሉም ነገር መልስ አለን፤ ሁሉንም ነገር እናውቃለን ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን ስለ እግዚአብሔር በማወቅ እንበለጽጋለን፤ እግዚአብሔር እንዴት እንደሚሰራ እንገነዘባለን፣ በመንፈስ ቅዱስ ጥበብ ስንመራ፤ በዙሪያችን የሚሆነው ነገር ከእግዚአብሔር መሆኑንና አለመሆኑን ይንለያለን፤ የምናደርጋቸው ውሳኔዎች፣ የምንከተለው መንገድ፣ በየዕለቱ የምንመርጠው ምርጫ ከእግዚአብሔር ፈቃድ አኳያ ስለመሆኑን እናስተውላለን፡፡ እንደ ክርስቲን እንዲህ አይነቱ ጥበብ በልባችን ካለ፤ ከውጭ በምናያቸው ነገሮች ሳንደናገጥና ተስፋ ሳንቆርጥ ለሚቀርቡን ሁሉ የሕይወትን ጣዕም ልንሰጥ እንችላለን፡፡
ንጉስ ሰለሞን እንዳደረገው በመሪነት፣ በአገልግሎት ዘርፍ፣ በቤተሰብ አስተዳዳሪነት እና በተለያዩ የሕይወት ስምሪቶች ውስጥ ስንገኝ፤ በዚህ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ በሆነው ጥበብ ስንመራ መልካም ነው፤ የእግዚአብሔርንም ፈቃድ የማወቅ አቅማችን ይጎለብታል፡፡ ይህ ጥበብ ምርጫዎቻችንን፣ ውሳኔዎቻችንን መንገዳችንን ሲመራ እናያለን፡፡ ይህ ጥበብ ሁሉንም ነገሮች በእግዚአብሔር ዓይን እንደ እግዚአብሔር ሐሳብ ማስኬድ እድንችል ያደርገናል፡፡
እንደ ክርስቲያንና በእግዚአብሔር መንፈስ ጥበብ እንደ ተሞላ ሰው፤ በማህበረሰባችን፣ በሥራ ቦታችን በተለያዩ የሕይወት ዘርፍ ውስጥ ስንገኝ መንገዳችንን አቅንተን፤ መንገድ የምንጠቁም፤ ይህ ከእግዚአብሔር ነው፤ ያ ደግሞ ከእግዚአብሔር አይደለም የምንል፣ የጊዜውን ሁኔታ መለየት የምንችል መሆን ይጠብቅብናል፡፡ በተሰማራንበት ሁሉ በዚህ ጥበብ መመራት ስንችል፤ የእግዚአብሔር ሰላምና ዕርቅ በመሃከላችን ይሰፍናል፡፡ ንጉስ ሰለሞን ለእግዚአብሔር ‹‹ሕዝብህን ለመምራት ካንተ የሆነው ጥበብ ያስፈልግኛል›› ሲል፤ የሕዝቡን፤ በአስተሳሰብ፣ በማንነትና በፍላጎት የተለያየ መሆንና ያን ሕዝብ ደግሞ ወደ አንድነት ለማምጣት የፍቅር፣ የዕርቅ መንፈስ እንደሚያስፈልገው ስላመነ ነው፡፡ ዛሬ እያንዳንዳችን በተሰማራንበት ቦታ ሁሉ ብናስተውል፤ የሚያስፈልገን ይህን የሰላምና የዕርቅ መንፈስ ነው፡፡ እያንዳንዳችን ለዚህ የሰላምና የዕርቅ ግንባታ ጉዞ ላይ መንፈስ ቅዱስ በሚሰጠን የጥበብ ስጦታ አማካኝነት አስተዋጾ እንድናደርግ እንጠራለን፡፡
ይህን ጥበብ ስንከተል፤ እግዚአብሔር በሕይወታችን ይናገራል፡፡ ሁለነገራችን የእግዚአብሔርን መገኘት ይናገራል፤ ያከብራልም፡፡ ይህ እኛ ልንፈጥረው የምንችለው ነገር ሳይሆን እግዚአብሔር ለመንፈስ ቅዱስ ክፍትና ታዛዥ ለሆኑት የሚያበረክተው ሥጦታ ነው፡፡ እኛ ውስጥ መንፈስ ቅዱስ አለ፤ የማዳመጥም ሆነ ያለማዳመጥ ነጻነት አለን፡፡ ብናዳምጠው ይህን የጥበብ መንገድ ያስተምረናል፤ ይህም በእግዚአብሔር ዓይን የማየት፣ በእግዚአብሔር ጆሮ የማዳመጥ እና በእግዚአብሔር ልብ የማፍቀር እንዲሁም በእግዚአብሔር ፍርድ ነገሮችን የመፍረድ አቅም እንዲኖረን ያደርጋል፡፡ ከጠየቅነውና ለመቀበልም ዝግጁዎች ከሆንን ፤ መንፈስ ቅዱስ የሚለግሰን የጥበብ ስጦታ ይህ ነው፡፡
በዚህ ጥበብ ብቻ ተመርተን፤ ማህበረሰብን፣ ቤተሰብን፣ ቤተክርስቲያንን መገንባት እንችላልን፡፡ መንፈስ ቅዱስ ይህን የጥበብ ጸጋ እንዲለግሰን እንለምን፡፡ አሜን፡፡
ምዝገባ ተጀምሯል
#ሕይወት_በመንፈስ_ቅዱስ_ሰሚናር
ዘወትር እሁድ 5:30 እሰከ 7:00
ቦታ ጎተራ ዶንቦስኮ ቤተ ፀሎት
መንፈሳዊነታችንን በእግዚአብሔር ቃል የምናሳድግበት ሕይወታችን በመንፈስ ቅዱስ እንዲመራ የሚረዳን ልዩ ሴሚናር።
0910056879
በመንፈስ የምትቃጠሉ ሁኑ
ክቡር አባ ተስፋዬ ቢሻሞ
“ለሥራ ከመትጋት አትለግሙ፤ በመንፈስ የምትቃጠሉ ሁኑ፤ ለጌታ ተገዙ፤”
— ሮሜ 12፥11
ከየትኛውም ዘመን ይልቅ በዚህ ዘመን እውነተኛ የመንፈስ ቅዱስ ልምምድ ያስፈልጋል። ብዙ ማስመሰል በበዛበት ዘመን ውስጥ እውነተኛውን የመንፈስ ቅዱስ ማንነት የሚገልጡ አገልጋዮች ያስፈልጉናል።
መንፈስ ቅዱስ እኛ የወደድነውን የፈለግነውን የሚያደርግ ሳይሆን እርሱ የወደደውን የሚያደርግ ታማኝ አምላክ ነው። ስለዚህ እኛም መንፈስ ቅዱስ የወደደውን እንዲሰራብን ልንፈቅድ ያስፈልጋል።
በዚህ ዘመን የራሳችንን ሀሳብ የመናገር ትልቅ ችግር አለብን የቀድሞዎቹ ሐዋርያት ግን የእግዚአብሔርን እንጂ የራሳቸውን ሀሳብ አይገልጹም አይናገሩም ነበር። የእነርሱ ክብር ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲከብር ማየት ስለነበር በየዕለት ሕይወታቸው ክርስቶስን በንግግራቸው በተግባራቸው ይገልፁት ነበር።
የተቀደሰ እሳት ከውጭ የሚመጣ ሳይሆን በጥምቀት ከመንፈስ ቅዱስ የተቀበልነው በውስጣችን የተቀመጠ እሳት ነው። ይህ ቅዱስ እሳት ማንነትን የሚገልጥ ነው። ይህን ማንነት (ሰውነት) ሁልግዜ በየዕለቱ ቅዱስና ሕያው መስዋዕት አድርገን ልናቀርብ ይገባል። ይህ በእሳት የተነካ ማንነት ከላይ የሆነ ደስታ ያለው በአእምሮ መታደስ የሚያመጣ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ተረድተን እንድንኖር የሚያደርግ አስደሳች ሕይወት ነው።
ሰው የሚመስለው በውስጡ የተሞላውን ብቻ ነው። መንፈስ ቅዱስን ተሞልተን በታደስ አእምሮ የምንኖር ከሆነ ዓለምን መምሰል አንችልም። ስለዚህ በመንፈስ ተሞሉ እንደሚል ዕለት ዕለት በመንፈሰ ለመሞላት ማንነታችንን በእግዚአብሔር ፊት ልናቀርብ ይገባል።መንፈስ ቅዱስ ሲገለገልብን ብቻ ነው ደካማው ብርቱ ሞኙ ጠቢብ ሰነፉ ብርቱ ፈሪው ደፋር መሆን የሚችለው። እኛ መሞት ከቻልን መንፈስ ቅዱስ በእኛ ሕያው ሆኖ ይገለጣል።
መንፈስ ቅዱስ እንዲሰራብን ከፈቀድን ለብዙዎች መባረክ መለወጥ መዳን ምክንያት እንሆናለን። አስቴር እግዚአብሔርን ስላከበርች 120 ሀገራት ለሚገኙ አይሁዳውያን ለመዳን ምክንያት ሆነች። ዛሬም የኛ ኑሮ ለሌሎች በረከት እንዲሆን እግዚአብሔርን የሚያስከብር ሕይወት ለመኖር ልንፈቅድ ይገባል።
ኢየሱስ እግዚአብሔር አብን ይገልጥ እንደነበር የመንፈስ ቅዱስ ዋና አላማ ጌታን ማክበርና መግለጥ ነው። መንፈስ ቅዱስ በእኛም አልፎ ጌታ እንዲገለጥ ይፈልጋል። ጌታን የሚያከብርና ጌታን የሚገልጥ መንፈስና ሕይወት የየዕለት መሻታችንን ሊሆን ይገባል።
ሰማያዊ አገልግሎት በምድር ማገልገል የምንፈልግ ከሆነ የመንፈስ ቅዱስ እሳት ሊነካን ያስፈልጋል። የመንፈስ ቅዱስ እሳት አገልጋይን ሲነካው ያበስለዋል ፣ ያጠራዋል ፣ ያዘጋጀዋል ያበራዋል ፣ በጥበብ ይገልጠዋል። ስለዚህ ከአገልግሎት በፊት በእሳት ልንነካ ያስፈልጋል ያለበለዚያ ፍሬ የሌለው በራስ የሆነ የልምምድ ውጤት የሆነ ከንቱ አገልግሎት ነው የሚሆንብን።
የመንፈስ ቅዱስ እሳት ሲነካን የእሳቱ ባህሪ ነው በእኛ ላይ የሚሆነው ብረት እሳት ውስጥ ሲገባ የእሳቱን አይነት ይሆናል እንዲቀልጥም ከተፈለገ ይቀልጣል። እንጨትም እንደዛው ፍም አመድ ነው የሚሆነው። ስለዚህ እኛም የመንፈስ ቅዱስ እሳት እንደነካን የሚታወቀው መንፈስ ቅዱስ የሚሰጠንን የክርስቶስ ባህሪ በሕይወታችን ሲገለጥና ሲታይ ብቻ ነው። መንፈስ ቅዱስ በሕይወታችን ሲሰራ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ ፍቅር ደስታ ሰላም በጎነት.... ዕለት ዕለት በሕይወታችን የሚገለጥ ሕይወት ይኖረናል። መንፈስ ቅዱስን እንረዳው እንወቀው የመንፈስ ቅዱስ እሳት እንዲነካን ራሳችንን መስዋዕት አድርገን እናቅርብ። ጣፋጭና ደስ የሚለው የክርስትና ሕይወት ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ያለ ሕብረት ነው።
በዓመት አንድ ግዜ የሚገኝ ልዩ እድል ህያው የሆነውን ጌታ ፊት እያዩ ከጌታ ጋር እየተወያዪ ጌታን እያመለኩ ጌታን እያዳመጡ የሚያሳልፉት ልዩ ለሊት ለመንፈስ ቅዱስ ስጦታ መቀበል የሚያዘጋጅ ሊያመልጠን የማይገባ ልዩ ለሊት።
የቅዱስ ቁርባን ስግደት
አምልኮ (ዝማሬ)
እርማችንን የምናቃጥልበት
ምኞታችንን ፅፈን በጌታ ፊት ምናቀርብበት
በልዩ ልዩ ርዕስ የምንፀልይበት
ስለሀገር
ስለቤተሰብ
ስለ አገልጋዮች ስለመሪዎች
ስለ ወጣቶች
ስለ በሽተኞች
ከምንም በላይ እግዚአብሔርን በምስጋና ከፍ የምናደርግበት ልዩ ደስ የሚል የምንባረክበት ልዩ ምሽት።
አርብ ሰኔ 3 በጎተራ ዶንቦስኮ ቤተ ፀሎት
ከምሽት 3 ሰዓት እስከ ንጋት 12:00 ሰዓት
ኑና አብረን እንባረክ።
የዛሬው የአራተኛ ቀን የኖቬና ፀሎት ፕሮግራማችን በመደበኛ ሰአታችን 9:00 ሰአት ላይ የምንጀምር ይሆናል።
የሶስተኛ ቀን የኖቬና ትምህርት
ክቡር አባ እስራኤል ጎይቶም
ርዕስ በእግዚአብሔር የማዳን ስራ ውስጥ የመንፈስ ቅዱስ ሚና
በዚህ ዘመን ኢየሱስ ቢመጣ የት ይሆን የሚያሰማራን እኛስ ግን እርሱ በወደደው ለመሰማራት ዝግጁ ነን? እንግዲያውስ የኢየሱስን ሚና ይዞ መንፈስ ቅዱስ አብሮን ይኖራል። ልንሰማው ልንታዘዘው ዝግጁ ከሆንን ወደ መልካም ሕይወት ሊያሰማራን ይጠራናል።
“ስለዚህ ማንም በእግዚአብሔር መንፈስ ሲናገር፦ ኢየሱስ የተረገመ ነው የሚል እንደሌለ፥ በመንፈስ ቅዱስም ካልሆነ በቀር፦ ኢየሱስ ጌታ ነው ሊል አንድ እንኳ እንዳይችል አስታውቃችኋለሁ።”
— 1ኛ ቆሮንቶስ 12፥3
ማንም ሰው ኢየሱስ ጌታ ነው ሊል ይችላል ነገር ግን በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ የሚናገር ሰው በመገለጥና በልዩነት ይናገራል።
ኢየሱስን በሙላት የሚገልጠው ስለእርሱ አንብቦ ያወቀው ሰው አይደለም ብዙ ፈላስፎች ስለ ኢየሱስ የሚያውቁትን ተናግረዋል። በአዳኝነቱ ባያምኑበትም። ሐዋርያት ግን ከመንፈስ ቅዱስ መገለጥን ነው ያገኙት ስለ ኢየሱስ አዳኝነት ለዓለም አደረሱ ይህ ነው የመንፈስ ቅዱስ ውጤት።
የእግዚአብሔር መንፈስ በሙላት ያለው ሰው በፅድቅ ሕይወት ለመኖር የሚያስችል አቅም ስላገኘ በሰማያዊ ነገር ላይ ትኩረቱን ያደርጋል። ስጋዊ የሆነ ሰው ሙሉ ትኩረቱ ምድራዊ ነገር ላይ ይሆናል።
የኀጢአት ክፍቱን የእግዚአብሔርን የፍቅር ጥሪ እንድንተው ማድረጉ ነው። እግዚአብሔር ወደ ፍቅሩን ሲጋብዘን ኃጢአት ከፍቅሩ ያሸሸናል።
ሰው የእግዚአብሔርን ፈቃድ አውቆ ማድረግ የሚችለው በመንፈስ ቅዱስ ሲሞላና ሲመራ ብቻ ነው። በሌላ ነገር የተሞላ ሰው የእግዚአብሔርን ፈቃድ ማወቅ አይችልም።
መንፈስ ቅዱስ የሌለበት አንድነት የትም አያደርስም። ዓለም አንድ ለመሆን ብትሞክርም ያለ መንፈስ ቅዱስ እርዳታ የማይሆን ድካም ነው።
በዘፍጥረት ምዕራፍ 11 ያለው የባቢሎን ታሪክ በአንድ ቋንቋ ይናገሩ የነበሩ በአንድ ላይ ተሰባስበው እግዚአብሔርን ለማውረድ የተደረገ ጥረት ቋንቋቸው ተደባልቆ መግባባት አቃታቸው። ሐዋርያት ምዕራፍ 2 ላይ ደግሞ በተለያየ ቋንቋ የሚናገር ከተለያዩ አገራት የመጡ ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ኃይል እንዲግባቡ ሆነዋል። መንፈስ ቅዱስ የአንድነት መንፈስ ነው።
ሰው ሙሉ የሚሆነው መንፈስ ነፍስ እና ስጋው ነው። (1ተሰ 5:23) እነዚህ ፈፅመው እንዲጠበቁ ታዘናል። እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በመንፈስ ቅዱስ ተሞልታ ይህን ዝማሬ አቅርባለች። ሉቃስ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁴⁶ ማርያምም እንዲህ አለች፦
⁴⁷ ነፍሴ ጌታን ታከብረዋለች፥ መንፈሴም በአምላኬ በመድኃኒቴ ሐሴት ታደርጋለች፤
እኛም ሕይወታችን በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ መኖር ከቻልን እኛም መንፈሳችን ሀሴት እያደረገ መኖር እንችላለን። የክርስትና ጣፍጭ ሕይወት በመንፈስ ቅዱስ የሚገኝ ምሪት ነው።
ይህ ትምህርት የተቀረፀ ሲሆን ትምህርቱ ሲለቀቅ አደራ ሰምታችሁ እንድትባረኩበት እንላለን። ይሄ ለቅምሻ ነው።
የዛሬውን የሶስተኛ ቀን የኖቬና ትምህርት በክቡር አባ እስራኤል ጎይቶም የተሰጠ ሲሆን በቅርቡ በካቶሊክ ቲቪ ወይም ደግሞ በ YouTube ቻናል የሚተላለፍ ይሆናል። ተባረኩ መልካም አዳር።
የሁለተኛ ቀን የኖቬና ትምህርት
በክቡር አባ ፍስሐ ታፈሰ
ርዕስ በመንፈስ ቅዱስ አምናለሁ
ሩጫ በሆነው ዓለም ውስጥ እንደ ማርያም ከእግሩ ስር መገኘት ትልቅ የሆነ በረከት ያለው ሕይወት እንደሆነና ለዚህ ሕይወት ጊዜውን ሰጥቶ ለፀሎትና ቃሉን ለመስማት መገኘት ዋጋው ልዩ መሆኑን በስብከታቸው መጀመሪያ ላይ ገልፀዋል።
በተቀበልነው በመንፈስ ቅዱስ ኃይል በዚህ ዓለም ስንኖር በሚያጋጥሙን የትኛውም የስጋ ፈተናዎች በትህትና ዝቅ በማለት አሸንፈን መኖር እንችላለን።
እግዚአብሔር በእሳት የሚገለጥ አምላክ ነው። በኤልያስ መስዋዕት ላይ በእሳት ተገለጠ እንዲሁም በኮሬብ ተራራ ለሙሴ በእሳት ተገለጠ እስራኤላውያን ቀን በደመና ለሊት በእሳት ዓምድ ይመራቸው እንደነበረ ለእኛም እንዲሁ መንፈስ ቅዱስ ነገሮቻችንን በእሳቱ እያጠራ በመልካም ሕይወት እየመራ ያኖረናል።
መንፈስ ቅዱስ እምነታችንን በተግባር እንድንገልፀው ኃይል ይሰጠናል። እምነትና ተግባር የተያያዙ የሕይወት ክፍሎች ናቸው አንዱን ከአንዱ ለይቶ መኖር አይቻልም። ለዚህ ነው ሐዋርያው ያዕቆብ ስራ የሌለው እምነት በራሱ የሞተ ነው የሚለን። ስለዚህ እምነታችን በተግባር የሚገለጥ መሆን አለበት ይህ ደግሞ ለሌሎች ሻማ ሆነን እየቀለጥን የምናበራ መሆን አለብን።
መንፈስ ቅዱስ የተቀበልነው አፍነን ልንቀመጥ አይገባም እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ ኤልሳቤጥ ለጉብኝት እንደሄደች እኛም የተቀበልነውን መንፈስ ቅዱስ ወደ ሌሎች ይዘን ልንወጣ ይገባል።
ቅዱስ አጉስጢኖስ ሙሉ ፍቅር ካለህ ሁሉን አድርግ ፍቅር ሕግ የለውም እንዳለ እኛም ፍቅርን በሙላት ይዘን ልንወጣ ወደሌሎች ልንደርስ ይገባል።
ኤርሚያስ ሲጠራ መጀመሪያ ያለ መቻል ነበር ውስጡ የሚሰማው ነገር ግን በእሳቱ አንደበቱ ከተዳሰሰ በኋላ እግዚአብሔርን ለመላክ ዝግጁ ሆነ እኛም በመንፈስ ቅዱስ እሳት ስንነካ የክርስቶስ መልዕክተኛ ለመሆን አቅም እናገኛለን።
መንፈስ ቅዱስ ከራሳችን ወጥተን በበሰለ እና በተረጋጋ ሕይወት በቤተክርስቲያን ውስጥ ስንኖር አስደሳች የሆነ መንፈሳዊ ሕይወት ይኖረናል።
በመንፈስ ቅዱስ ስንመራ የፅናትና የቆረጠ ሕይወት ስለሚኖረን በሕይወት ለመኖር ብቻ ሳይሆን ስለ ጌታ ለመሞትም የቆረጠ ሕይወት ይኖረናል በደስታ ሕይወታቸውን ለሞት የሰጡ በዙሪያችን እንደደመና የሆኑ ብዙ ምስክሮች አሉ። እነዚህ ሰማዕታት የመንፈስ ቅዱስ ኃይል የበዛላቸው ነበሩ። የጌታ ስለሆንን ብቻ ነገሮች አልጋ በአልጋ ይሆኑልናል ማለት አይደለም። ችግርም ቢኖር በመንፈስ ቅዱስ ኃይል እና ብርታት የምናልፈው ይሆናል።
የፍቅር ሰው ሆነን በጥበብ የአገልግሎት መንፈስ መያዝ አለብን ከሚጠሉን ከማይቀበሉን ጋር መጋጨት የለብንም በፍቅር በሰላም በጥበብ ለመኖር መትጋት አለብን። መንፈስ ቅዱስ ደግሞ ኃይል ይሰጠናል።
የመጀመሪያ ቀን የኖቬና ፕሮግራም መንፈስ ቅዱስ በልዩ ሁኔታ ባርኮናል ነገም ይቀጥላል። ሁላችሁም የበረከቱ ተካፍይ እንድትሆኑ ተጋብዛችኋል።
