fa
Feedback
ያሬድ ዘርአ-ቡሩክ ▪️መጋቤ ምስጢር

ያሬድ ዘርአ-ቡሩክ ▪️መጋቤ ምስጢር

رفتن به کانال در Telegram

ኦ አሐውየ እለ አፈቅረክሙ ጸልዩ ዲበ ድካምየ ከመ ይዕቀበኒ እግዚእ በዐቢይ ሣህሉ በሃይማኖት ርትዕት እስከ ፍጽሜ ደሓሪት እስትንፋስ። ወዝንቱ ውእቱ ባሕቲቱ ተስፋየ። ወስብሐት ለአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ለዓለመ ዓለም አሜን። ሃይ. አበ. ዘቴዎዶስ. ፹፫፡፵፬ https://t.me/joinchat/SWWiqKcuci79Brh9

نمایش بیشتر
2 105
مشترکین
-124 ساعت
-97 روز
-1030 روز
آرشیو پست ها
ዛሬ ማታ በዚህ https://t.me/kineyared የቅኔ ዘረፋ ይኖረናል። ሰዓት 2:30

ደብረ ዘይት.pdf4.51 KB

ክርስቶስ ዳግም ስለ መምጣቱ የተናገራቸው ፲፬ ምልክቶች ሰፊ ጊዜ ሰጥተው ሊያነቡት የሚገባ አስተማሪ ጽሑፍ ከላይ ያለውን Pdf አንድ ጊዜ ጠቅ አድርገው ከፍተው ያንብቡ!

...የቀጠለ ክፍል ፬ “ደዌ ዘለግሕደተ ክብረ እግዚአብሔር” “ደዌ ዘለግሕደተ ክብረ እግዚአብሔር” ከኃጢአት ጋር የሚያያይዝ አንድም ምክንያት የሌለው ሲሆን እግዚአብሔር ክብርን ሲሻና የአምላክነቱን ሥራ በመግለጥ በራሱ፣ አልያም በቅዱሳን/ት አማካኝነት የማዳኑን ሥራ ለማሳየት ሲፈልግ ብቻ አልፎ አልፎ የሚከሠት በሽታ ነው። የበሽታውም ዓይነት በተለያየ መልኩ ሊከሠት የሚችልና የየራሱ የሆነ የሕመም ስሜት ያለው  ሲሆን ለሞት ሊዳርግም ላይዳርግም የሚችል በሽታ ነው። “ደዌ ዘለግሕደተ ክብረ እግዚአብሔር” ማለትም ቀጥታ ዐማርኛዊ ፍቺው ‹‹ለእግዚአብሔር ክብር መገለጥ የሚሆን በሽታ›› ማለት ነው። የዚህ በሽታ ክሥተትንም ከቅዱስ መጽሐፍ እንደሚከተለው በጥልቀት እንመለከታለን፦ ፩. #አልዓዛርን እስከ ሞት ድረስ ያደረሰ በሽታ፦ “የማርያምና የእኅቷ ማርታ መንደር በሚሆን በቢታንያ ስሙ አልዓዛር የሚባል የታመመ አንድ ሰው ነበር። . . . እኅቶቹም ‹‹ጌታችን ሆይ! እነሆ የምትወደው ታሟል›› ብለው ወደ ጌታችን ኢየሱስ ላኩ። ጌታችን ኢየሱስም ሰምቶ እንዲህ አለ፦ ‹‹ይህ ደዌ በእርሱ የእግዚአብሔር ልጅ ይከብር ዘንድ ስለ እግዚአብሔር ክብር ነው እንጂ ለሞት አይደለም›› . . . ጌታችን ኢየሱስም ወደ ቢታንያ ሄደ፤ ከዚያም በደረሰ ጊዜ ከተቀበረ አራት ቀን ሆኖት አገኘው። . . . ይህንም ብሎ በታላቅ ቃል ጮኸና ‹‹አልዓዛር አልዓዛር ና! ወደ ውጭ ውጣ!›› አለ . . . ሞቶ የነበረውም እንደ ተገነዘ እጁና እግሩንም እንደ ታሰረ፥ ፊቱም በሰበን እንደ ተጠቀለለ ወጣ፤ ጌታችን ኢየሱስም እንግዲህስ ‹‹ፍቱትና ተዉት ይሂድ!›› አላቸው።" ዮሐ. 11፡1-44። ፪. #ዕውር ሆኖ የተወለደው ሰው፦ “ከዚያም ሲያልፍም ዕውር ሆኖ የተወለደውን ሰው አየ። ደቀ መዛሙርቱም ‹‹መምህር ሆይ! ይህ ሰው ዕውር ሆኖ የተወለደው በማን ኀጢአት ነው? በራሱ ነውን? ወይስ በወላጆቹ?›› ብለው ጠየቁት። ጌታችን ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፦ ‹‹የእግዚአብሔር ሥራ ሊገለጥበት ነው እንጂ እርሱ አልበደለም፤ ወላጆቹም አልበደሉም።” ዮሐ. 9፡1-3። ፫. #የስራጵታይቱ ሴት ወንድ ልጇን ለሞት ያበቃው ከባድ በሽታ፦ "እርሷም ኤልያስን የእግዚአብሔር ሰው ሆይ! ከአንተ ጋር ምን አለኝ? ኃጢአቴንስ ታሳስብ ዘንድ፥ ልጄንስ ትገድል ዘንድ ወደ እኔ መጥተሃልን? አለችው . . . እግዚአብሔርም የኤልያስን ቃል ሰማ፤ የብላቴናው ነፍስ ወደ እርሱ ተመለሰች፤ እርሱም ዳነ።" 1ኛ ነገ. 17፡17-24። ፬. #የሱናማዊቷ ሴት ወንድ ልጇን ለሞት ያበቃው የራስ ምታት በሽታ፦ “አባቱንም ‹‹ራሴን ራሴን›› አለው። እርሱም ሎሌውን ተሸክመህ ወደ እናቱ ውሰደው አለው። አንሥቶም ወደ እናቱ ወሰደው፤ በጕልበቷም ላይ እስከ ቀትር ድረስ ተቀመጠ፥ ሞተም . . . ኤልሳዕም ወደ ቤት በገባ ጊዜ እነሆ፥ ሕፃኑ ሞቶ በአልጋው ላይ ተጋድሞ ነበር። ኤልሣዕም ወደ ቤት ገብቶ በሩን በሁለቱ ላይ ዘጋ፥ ወደ እግዚአብሔርም ጸለየ። መጥቶም በሕፃኑ ላይ ተኛ፤ አፉንም በአፉ፥ ዐይኖቹንም በዐይኖቹ፥ እጆቹንም በእጆቹ ላይ አድርጎ ተጋደመበት፤ የሕፃኑም ሰውነት ሞቀ። ተመልሶም በቤቱ ውስጥ አንድ ጊዜ ወዲህና ወዲያ ተመላለሰ፤ ደግሞም ወጥቶ ሰባት ጊዜ በሕፃኑ ላይ ተጋደመ፤ ከዚያም በኋላ ሕፃኑ ዐይኖቹን ከፈተ . . .” 2ኛ ነገ. 4፡17-37። ፭. #ዶርቃስ የተባለችውን ደግ ሴት ለሞት ያበቃ በሽታ፦ “በኢዮጴም ሀገር ‹‹ጣቢታ›› የሚሏት አንዲት ደቀ መዝሙር ነበረች፤ በትርጓሜውም ‹‹ዶርቃስ›› ይሏታል፤ ፌቆ ማለት ነው፤ እርሷም ብዙ ደጋግ ሥራ ትሠራ ነበር፤ ምጽዋትም ትሰጥ ነበር፤ ያን ጊዜም ታማ ሞተችና በድኗን አጥበው በሰገነት አስተኟት . . . ጴጥሮስም ሁሉን ካስወጣ በኋላ ተንበርክኮ ጸለየ፥ ወደ በድኗም መለስ ብሎ ‹‹ጣቢታ ሆይ! ተነሽ!›› አላት። እርሷም ዐይኖቿን ገለጠች። ያን ጊዜም ጴጥሮስን ዐየችው። ቀና ብላም ተቀመጠች። እጁንም ለእርሷ ሰጥቶ አስነሣት፤ ቅዱሳንንና ባልቴቶችንም ጠርቶ እርሷን አድኖ ሰጣቸው።” ሐዋ. 9፡36-37። ፮. #ልምሾ ሆኖ የተወለደው ሰው፦ “ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ እግሩ ሽባ ሆኖ የተወለደ አንድ ሰው ነበረ፤ ወደ መቅደስም ከሚገቡት ምጽዋት ይለምን ዘንድ፥ ሁልጊዜ እየ ተሸከሙ መልካም በሚሏት በመቅደስ ደጃፍ ያስቀምጡት ነበር . . . ጴጥሮስም ከዮሐንስ ጋር ትኵር ብሎ ተመለከተውና ‹‹ወደ እኛ ተመልከት!›› አለው፤ ወደ እነርሱም ተመለከተ፤ . . . በቀኝ እጁ ይዞም አስነሣው፤ ያን ጊዜም እግሩና ቍርጭምጭምቱ ጸና ፤ ዘሎም ቆመ ፤ እየ ሮጠና እየ ተራመደም ሄደ። እግዚአብሔርንም እያመሰገነ ከእነርሱ ጋር ወደ መቅደስ ገባ።” ሐዋ. 3፡1-10። ይህ በሽታ ከላይ ባየነው መሠረት እግዚአብሔር ክብሩን ለመግለጽ እስከ ፈለገበት ቀን ብቻ የሚቈይ በሽታ ሆኖ ከተወሰኑ ጊዜያት በኋላ ላይመለስ ላንዴና ለመጨረሻ የሚወገድ በሽታ ነው። ለሞት ቢያበቃም ከሞት በኋላ ተመልሶ በአካለ ሥጋ መዳን የሚቻልበት መንገድ አለው። ስለ ሆነም  ወደ ፊት ጊዜው ባልታወቀ የሚፈወሱበት ዕለት እንዳለ በመገንዘብ እግዚአብሔር የማዳን ሥራውን በመሥራት ድንቅ ተአምር በርስዎ ሕይወት እስከሚገልጥበት ዕለት ድረስ ተስፋ ባለመቍረጥ በሕገጋተ እግዚአብሔር ተጠብቆ መቈየት ግድ ይላል።

…የቀጠለ ክፍል ፫. #ደዌ_ዘንጽሕ ይህ በሽታ ቅዱሳን/ት ከመንፈሳዊ ተጋድሏቸው፣ ከጾማቸውና ከዘወትር ጸሎታቸው ብዛት የተነሣ የሚመጣ በሽታ ሲሆን የሕመሙ ስሜት እንደ በሽታው ዓይነት ሊለያይ ይችላል። ይህ በሽታ ቅዱሳን/ት መንፈሳዊ ተጋድሏቸውን ከጀመሩበት ዕለት ማግሥት ጀምሮ በመዋዕለ ተጋድሏቸው ሁሉ አብሯቸው ሊጓዝ ይችላል። በዚህም በሽታ ያለፉ ቅዱሳን አባቶቻችንን እንመለከታለን፦ ፩. ቅዱስ #ጢሞቴዎስ፦ “ወኢትስተይ ማየ ዕራቆ ኅዳጠ ወይነ ቶስሕ በእንተ ሕማመ ከብድከ ወበእንተ ደዌከ ዘዘልፍ - ስለ ሆድህ በሽታና ስለ ዘወትር ደዌህ ጥቂት ወይን ጨምር እንጂ ውኃ ብቻ አትጠጣ።” ፩ ጢሞ. ፭፡፳፫። ፪. ቅዱስ #ያዕቆብ፦ “ከአራቱ የጠራቢው ዮሴፍ ልጆች መካከል የመጨረሻው ልጅ የሆነ፥ የጌታ ወንድም ተብሎ የሚጠራው፥ የኢየሩሳሌም ሊቀ ጳጳስ ሆኖ የተሾመው ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ በጾምና በጸሎት ተወስኖ አብዝቶ ከመቆሙ የተነሣ ከዚህ ዓለም በአካለ ሥጋ በሞት እስኪለይ ድረስ እግሮቹ #ዐብጠው እጅግ ይታመም ነበር። አዘውትሮም ይሰግድ ስለ ነበረ ግንባሩ የግመል ጕልበት ይመስል ነበር። ገድለ ሐዋርያት፤ ድርሳነ ዮሐንስ አፈ ወርቅ። ፫. #ቅዱሳን_ባሕታውያን፦ “…ወዔሉ በሠቅ ወበሐሜለት ወበዘብድወ ጠሊ፤ ተጸነሱ፤ ተመንደቡ፤ #ሐሙ፤ ርኅቡ፤ ጸምኡ። እሉ እሙንቱ ዘኢይደልዎሙ ዓለም፤ ወዔሉ ውስተ ገዳም፤ ወውስተ አድባር ወበዓታት ወግበበ ምድር = ማቅን ለብሰው፣ መጠምጠሚያቸውን ጠምጥመው፣ የፍየልን ሌጦ ለብሰው ተቸገሩ፤ #ታመሙ፤ ተራቡ፤ ተጠሙ፤ ዓለም ያልተገባቸው እነዚህ ናቸው። በየዱሩ፣ በየተራራዎችም፣ በየዋሻዎችም በየምድር ፍርኩታ ዞሩ”። ዕብ. 11፡36-38። ሲል ቅዱስ ጳውሎስ የመሰከረላቸው በየገዳሙ ስለ ጽድቅ ብለው በፈቃዳቸው የሚታመሙ አባቶቻችንና እናቶቻችን ጥቂት የሚባሉ አይደሉም። በመሆኑም ደዌ የነበረባቸውን ብዙዎቹን ሰዎች በልብሱ ቍራጭ ሲያድን የነበረው ቅዱስ ጳውሎስ በሆድ ሕመም ይሠቃይ ለነበረው ደቀ መዝሙሩ ጢሞቴዎስ የላከለት የልብሱን ቍራጭ ሳይሆን “በሌሎችም ኃጢአት አትተባበር፤ ራስህን በንጽሕና ጠብቅ፤ ስለ ሆድህና ስለ #በሽታህ ብዛት ጥቂት የወይን ጠጅ ጠጣ እንጂ፥ ወደ ፊት ውኃ ብቻ አትጠጣ።” በማለት ጊዜያዊ መፍትሔ ሊሆን የሚችልን ምክር ነበር የነገረው። 1ኛ ጢሞ. 5፡22-23 ፡፡ ስለ ሆነም ይሄ በሽታ ከጠነከረ መንፈሳዊ ተጋድሎ ሊመጣ የሚችል እንደ መሆኑ መጠን ጽድቅን በማይጋፋ መልኩ ጊዜያዊ መፍትሔዎችን መጠቀሙ አይከፋም። ፬. #ደዌ_ዘዕሴት “ደዌ ዘዕሴት” በመጀመሪያ በነበረው በጎ ስጦታ ላይ ዕጥፍ ድርብ በጎ ዋጋን የሚያሰጥና በክብር ላይ የክብር መጐናጸፊያን የሚያጐናጽፍ በሽታ ነው። ይህም በሽታ ከሰዎች ኃጢአት፣ ከበደልም ሆነ ከጥፋት ሁሉ የሚያያዝ የኃጢአት ውጤት አይደለም። ይህ በሽታ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ሊሽርም ይችላል። እስከ ወዲያኛው እስከ ሥጋዊ ሞትም ዐብሮ ሊቈይ ይችላል። የበሽታውም ስሜት “የተወሰነ ከፊል የሰውነት ክፍል፣ አሊያም ሙሉ የሰውነት ክፍል ቍስል፣ ዕብጠትና ወዘተርፈ… የውስጥም የውጭም የሕዋስን ክፍል የሚያጠቃ በሽታ ሊሆን ይችላል። ይህንም በሽታ ተቋቍመው ያለፉ ሰዎችን እንደ ምሳሌ እንመልከት፦ ፩. #ኢዮብ፦ “ሰይጣንም ከእግዚአብሔር ፊት ወጣ፥ ኢዮብንም ከእግሩ ጫማ ጀምሮ እስከ አናቱ ድረስ #በክፉ-ቍስል መታው።” ኢዮ. 2፡7። ኢዮብ የታመመው አምላኩ እግዚአብርሔርን በድሎ፥ ኃጢአት ሠርቶ ሳይሆን ሰይጣን ባቀረበው ፈተና ነበር። ኢዮብም በበሽታው ጽናት ዘመድ፥ አዝማድ፣ የቅርብ ወገን፣ ጎረቤት ተለይተውት ከራሱ ጸጕር እስከ እግሩ ጥፍር ድረስ መላ ሰውነቱ ሁሉ ቈስሎ ተልቶ፥ እየ ተቈራረጠ በዐመድ ላይ ተኝቶ ራሱ ታማሚ፥ ራሱ አስታማሚ ሆኖ ለዘመናት የእግዚአብሔርን ምሕረት ደጅ ይጠና ነበር። ደግሞም የዓሥሩ ልጆቹ መሞትና የቤቱ ንብረት ሁሉ ውድመት ለኢዮብ ሌላኛው ሕመሙ ነበረ። ነገር ግን ኢዮብ ይህን ሁሉ ፈተና በትዕግሥት ተሸክሞ እግዚአብሔርን አጥብቆ ከመለመን በቀር በእግዚአብሔር ላይ በክፉ አፉን እንኳን አልከፈተም። ለብዙ ዘመናት ደጅ ከጸና በኋላም እግዚአብሔርም ደረሰለት፤ ፈወሰውም። በተጨመረለት ዕድሜም በሞቱት ልጆቹ ልክ ዓሥር ልጆችን እንዲወልድ አደረገው፤ ከቀድሞውም ሀብቱ ይልቅ ሁለት ዕጥፍ አድርጎ ሀብት ሰጠው። ከድኅነቱ በኋላም ኢዮብ ይባል የነበረው ስሙ ኢዮባብ ተብሏል፡፡ ኢዮ. 1፡1-22፣ 2፡1-9፤ 42፡10-17፤ ተግ. ዘዮሐ. አፈ. ወር. ፳። ፪. #አልዓዛር፦  ይህ አልዓዛር የተባለው ሰው ምንም የሌለው ምስኪን ድሃ ሰው ነበረ፥ የበሽታውም ዓይነት ልክ እንደ ኢዮብ የቍስል ደዌ ነበረ። አልዓዛርም በሕመሙ ጊዜ ጧሪ፥ አስታማሚ ስላልነበረው ነዌ በተባለ ንፉግ ባለጠጋ ቤት ጥግ ሆኖ ፍርፋሪን ለመብላት ይመኝ ነበር። ውሾችም የደረቀውን ቍስሉን እየላሱ ሲያስታምሙት ንፉጉ ባለጠጋ ነዌ ግን ከማዕዱ የሚወድቀውን ፍርፋሪውን እንኳን አልሰጠውም። አልዓዛርም በሥጋ ከሚሠቃይበት #በሽታው በተጨማሪ ረኃብ ተደራርቦበት በበሽታው የሕመም ስሜትና በረኃብ ምክያት ከዚህ ዓለም በአካለ ሥጋ በሞት ተለይቷል። ሆኖም ግን ይህ የእግዚአብሔር ሰው አልዓዛር በዚሁ ከባድ ቍስል ተይዞ፥ በዚያውም ላይ የሥጋ ረኃብ ተደራርቦበት በአካለ ሥጋ እስኪሞት ድረስ እግዚአብሔርን ከማመስገን አንደበቱን አልገታም። ሉቃ. 16፡19-31። በልዩ ልዩ የበሽታ ሕመም/ሥቃይ ውስጥ ያላችሁ ወገኖች ሆይ! በልዩ ልዩ በሽታ ምክንያት የምትታመሙት መታመም እግዚአብሔር  የትዕግሥታችሁን ውጤት አይቶ በኋላ ላይ ዕጥፍ ድርብ የሆነ፥ በሕመማችሁ ጊዜ የመታገሣችሁን ዋጋ ሊሰጣችሁ ዐስቦ የኢዮብ በሽታ ዓይነት በሽታ እንደ ሆነ ማን ያውቃል? በመሆኑም በተለያዩ የበሽታ ዓይነቶች በምንታመምበት ጊዜ እንደ ኢዮብ ኢዮባውያን ሆነን በትዕግሥት የእግዚአብሔርን የምሕረት እጅ ደጅ መጽናት እንጂ ክፉ ቃልን ማሰማትና ማማረር ተገቢ አይደለም። ማማረርም ከማማረር አልፎ ይበልጥ ራስን ከመጕዳት በቀር የሚያመጣው ለውጥ የለም። ይልቁንም “ወንድሞች ሆይ! የመከራና የትዕግሥት ምሳሌ የሆኑትን በጌታም ስም የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሩትን ነቢያትን ተመልከቱ፤ እነሆ የታገሡትን ብፁዓን እንላቸዋለን፤ የኢዮብን ትዕግሥት ሰምታችኋል፤ እግዚአብሔርም የፈጸመለትን አይታችኋል፤ የእግዚአብሔር ቸርነቱ ብዙ ነውና፤ ይቅር ባይም ነውና።” በተባለው አምላካዊ ቃል መሠረት መፍትሔ ሊሆን የሚችለውን፥ በመንፈሳዊ ጕዞ የታጀበ ትዕግሥትን ገንዘብ ማድረግ ነው። ያዕ. 5፡10-11፤ ራእ. 2፡19። “አሁንስ ተስፋዬ ማን ነው? እግዚአብሔር አይደለምን? ትዕግሥቴም ከአንተ ዘንድ ነው። ከኃጢአቴ ሁሉ አድነኝ፥ ለሰነፎችም ስድብ አታድርገኝ። አንተ ሠርተኸኛልና ዝም አልሁ፤ አፌንም አልከፈትሁም። መቅሠፍትህን ከእኔ አርቅ! ከእጅህ ብርታት የተነሣ አልቄአለሁና። በተግሣጽህ ስለ ኃጢአቱ ሰውን ዘለፍኸው፥ ነፍሱም እንደ ሸረሪት ድር ታልቃለች፤ በእውነት ሰው ሁሉ ከንቱ ነው። አቤቱ! ጸሎቴን ስማ! ጩኸቴንም አድምጥ! ልቅሶዬንም ቸል አትበለኝ! ፤ እኔ በምድር ላይ መጻተኛ ነኝና፥ እንደ አባቶችም እንግዳ ነኝና። ወደማልመለስበት ሳልሄድ ዐርፍ ዘንድ ተወኝ!” እያሉ ዘወትር መጸለይም ይገባል፡፡ መዝ. 38፡7-13፡፡ በመቀጠልም ክፍል ፬ የመጨረሻ ይቀጥላል... ጦማሪ፦ መጋቤ ምስጢር ያሬድ  ዘርአ-ቡሩክ ዩቲዩብ👇 https://www.youtube.com/@Yared-Zeraburuk ቴሌግራም ቻናል https://t.me/yaredzer

• በተቅዋመ ብርሃን ብርሃነ እምከመ የኀቱ ሊቀ ካህናት አሮን ገፋዔ ገፋዒ ዮርማሮዴቅ፥ • እምነ መቅደስ አውፅአ ጸናጽለ ወርቅ ረቂቅ፥ • ከመ ይቁም መዝሙረ ምሳሌ ኢሳይያስ ሊቅ፥ • እስመ ይትራድእዎ ቀዊሞሙ በቤተ ከበሮ ሳሙኤል ወሙሴ በዐምደ ወርቅ። • ማኅሌትሂ ተነብይ እምቅድመ ይኅልቅ፥ • ሕዝቅኤል መዘምር ዖደ በምሥራቅ፥ • ብሂሎ ሚልክያስ ይቀጽበኒ በጽድቅ፥ • አምጣነ ፈቀደ ልቡናሁ በቤተ ልሔም ከመ ይርፍቅ። መወድስ ቅኔ ዘመምህር ገብረ ጊዮርጊስ ገብረ እግዚእ - ዘእስቴ መካነ ኢየሱስ - ዘአኵስም ጽዮን

“በምድር ላይ ረኃብ፥ ወይም ቸነፈር፥ ወይም ዋግ፥ ወይም አረማሞ፥ ወይም አንበጣ፥ ወይም ኩ ኵብኩባ ቢሆን፥ የሕዝብህም ጠላት የሀገሩን ቀበሌዎች ከብቦ ቢያስጨንቃቸው፥ መቅሠፍትና ደዌ ሁሉ ቢሆን፥ ማናቸውም ሰው የልቡን ሕመም ዐውቆ ጸሎትና ልመና ቢጸልይ፥ እጆቹንም ወደዚህ ቤት ቢዘረጋ በማደሪያህ በሰማይ ስማ፥ ይቅርም በል፤ አንተ ብቻ የሰውን ልጆች ሁሉ ልብ ታውቃለህና ልቡን ለምታውቀው ሰው ሁሉ እንደ መንገዱ ሁሉ መጠን ክፈለውና ስጠው!” (1ኛ ነገ. 8፡37-40) ብሎ ጠቢቡ ሰሎሞን በመቅደሱ ዐደባባይ ተንበርክኮ ሲጸልይ እንደ ተናገረም በሰዎች ምልአተ-ኃጢአት ምክንያት ከመጣው ከደዌ ዘመቅሠፍት ለመዳን በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ተገኝቶ፥ እደ ልቡናን ዘርግቶ ፍጹም ጸሎትን በፍጹም ሕሊና ማቅረብ ነው። ወዳጄ ሆይ! ቅዱስ መጽሐፍ “ሕዝቤ ሆይ! ና! ወደ ቤትህም ግባ!፥ ደጅህን በኋላህ ዝጋ! ቍጣ መቅሠፍት እስኪያልፍ ድረስ ጥቂት ጊዜ ተሸሸግ!” ይልሃል። ኢሳ. 26፡20-21። “ወደ ቤትህ ግባ!” ሲልህም በድንጋይ፣ በብሎኬት፣ በብረትና በሲሚንቶ አልያም በጭቃና በዕንጨት የተሠራውን፥ ዛሬ አልያም ነገ ጥለኸው የምታልፈውን ምድራዊ ቤትህን እየ ጠቈመህ እንዳልሆነ ልብ በል! ይልቁንም ከኰበለልክበት የኃጢአት ዓለም የዘለዓለም ቤትህ ምሳሌ ወደ ሆነችው፣ የመንፈስ ቅዱስን ልጅነት ወደ ተቀበልክባት፣ ቅዱስ ሥጋው ወደሚፈተትባት፥ ክቡር ደሙ ወደሚሰጥባት፣ ወደ እናትህ፣ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በንስሓ ተመልሰህ ግባ! ሲልህ ነው። አንድም፦ ‹‹ደጅህን በኋላህ ዝጋ!›› ሲልህ የዚያች ምድራዊት ቤትህ በር እየ ጠቈመ ‹‹እጅህንና እግርህን ዐጣጥፈህ ተኛ!›› ያለህ አይምሰልህ! ይልቁንም የእግዚአብሔርን ሕገጋት እስከ ዛሬ ድረስ የሻርክበትን፣ ያፈረስክበትን፣ የጣስክበትን የኃጢአት በር በንሥሓ ዐጥር ዐጥረህ የክርስቶስን ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም በመቀበል መዝጊያ ዝጋ!  ሲልህ ነው። አንድም፦ “ቍጣ እስኪያልፍ ድረስ ጥቂት ጊዜ ተሸሸግ!” ቢልህ በበደልህ ምክንያት የመጣው ቍጣ እስኪመለስ ድረስ በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደትና በሱባዔ ቈይ! ሲልህ ነው። በኃጢአትህም ምክንያት ከመጣብህ ከደዌ ዘመቅሠፍት ትድን ዘንድ ካንተ ልመና በተጨማሪ ወደ እግዚአብሔር የሚማልድልህና የሚለምንልህ ከቅዱሳን መካከል እንደ ሙሴ ያለ ራሱን ስላንተ አሳልፎ የሚሰጥ፥ በእግዚአብሔር ፊትም ለምልጃ የሚቆም ቅዱስ አማላጅ ያስፈልግሃል። ዘፀ. 32፡31-33። ስለ ሆነም ወዳጄ ሆይ!  ያንተ በንስሓ መመለስና ጸሎት እንዳለ ሆኖ ከእግዚአብሔር ጋር ሊያስታርቅህና ምሕረት ሊያሰጥህ በሚችል በአካለ ሥጋም በአካለ ነፍስም ባሉ የቅዱሳን ምልጃና ጸሎት ያለ መጠራጠር ታመን! በመቀጠልም ክፍል ፫ ይቀጥላል… ጦማሪ፦ መጋቤ ምስጢር ያሬድ  ዘርአ-ቡሩክ ●➖●➖●➖● ቅኔን በቴሌግራም ለመማር👇 https://t.me/kineyared ቴሌግራም ቻናል https://t.me/yaredzer ዩቲዩብ👇 https://www.youtube.com/@Yared-Zeraburuk ፌስቡክ https://www.facebook.com/share/1Gw4Rx8hAC/

…የቀጠለ ክፍል ፪. #ደዌ_ዘመቅሠፍት ደዌ ዘመቅሠፍት ሰዎች የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ባለመጠበቅ በሚያደርጉት ኃጢአት የሚመጣ በሽታ ነው። ይህም በሽታ አብዛኛውን ጊዜ ጊዜ ሳይሰጥ በዓጭር ጊዜ ለሞት የሚዳርግ በሽታ (A deadly disease) ሲሆን ለተወሰነ ጊዜም እያሠቃየ መቈየት የሚችል ዐደገኛ የሆነ የሕመም ስሜት ሊኖረው ይችላል። ደዌ ዘመቅሠፍት በሰውነት/ሕዋስ ላይ ስሜት ካለው በሽታ ባሻገር፥ ስሜት አልባ በሆነ በሌላ መንገድም ሊከሠት ይችላል። ለምሳሌም በግብጻውያን ላይ የወረደው ዓሥር መቅሠፍት ከዓሥረኛው በቀር ዘጠኙ መቅሠፍታት ቀጥታ ከሰው ውስጣዊ ሰውነት ጋር የሚያያዝ ስሜት ያለው በሽታ አልነበራቸውም። በተዘዋዋሪ ግን ሰውን የሚጐዱ ነበሩ። በግብጻውያን ላይ የወረዱት ዐሥሩ መቅሠፍታትም፦ 1ኛ. የውኃ ወደ ደም መለወጥ መቅሰፍት ዘፀ. 7፡14-25፤ 2ኛ. የጓጕንቸር/ዕንቍራሪት መቅሠፍት ዘፀ. 8፡1-15፤ 3ኛ. የቅማል መቅሠፍት ዘፀ. 8፡16-19፤ 4ኛ. የተናካሽ ዝንብ መቅሠፍት ዘፀ. 8፡20-32፤ 5ኛ. የእንስሳት ዕልቂት መቅሠፍት ዘፀ. 9፡1-7፤ 6ኛ. የሻህኝ መቅሠፍት ዘፀ. 9፡8-12፣ 7ኛ. የበረዶ መቅሠፍት ዘፀ. 9፡13-35፤ 8ኛ. የአንበጣ መንጋ መቅሠፍት ዘፀ. 10፡21-29፤ 9ኛ. የጨለማ መቅሠፍት ዘፀ. 10፡21-29፣ 10ኛ. የሞተ በኵር መቅረፍት ዘፀ. 12፡29-36 ናቸው። በተጨማሪም የዐሥራ አንደኛው የስጥመተ ባሕር መቅሠፍትንም ልብ ይላሉ። ዘፀ. 14፡26-28። ደዌ ዘመቅሠፍት ብዛት ያላቸውን ዐመፀኞች በዓጭር ጊዜ አንድ ላይ ሊያጠፋና ሊገድል የሚችል በሽታ ነው። የደዌ ዘመቅሠፍት መንሥኤውም  “በዚህ መጽሐፍ የተጻፉትን የዚህን ሕግ ቃሎች ሁሉ ታደርግ ዘንድ ባትጠብቅ፥ ይህንንም አምላክህ እግዚአብሔር የተባለውን የተመሰገነውንና የተፈራውን ስም ባትፈራ፥ እግዚአብሔር #መቅሠፍትህን፥ የዘርህንም መቅሠፍት፥ ብዙ ዘመንም የሚኖረውን ታላቅ መቅሠፍት፥ ብዙ ዘመን የሚኖረውንም ክፉ ደዌ ያደርግብሃል፤ የፈራኸውንም የግብጽ ደዌ ሁሉ እንደ ገና ያመጣብሃል፥ ይጣበቅብህማል፤ ደግሞም ይህ ሕግ ባለበት መጽሐፍ ውስጥ ያልተጻፈውን ደዌ ሁሉ መቅሠፍትም ሁሉ እስክትጠፋ ድረስ እግዚአብሔር ያመጣብሃል፤ የአምላካችሁን የእግዚአብሔርን ቃል አልሰማችሁምና ከብዛታችሁ የተነሣ እንደ ሰማይ ከዋክብት የነበረው ቊጥራችሁ ጥቂት ሆኖ ይቀራል።” ተብሎ እንደ ተገለጠው በቅዱሳት መጻሕፍት ሕገጋትና ትእዛዛት አለመመራት ነው። ዘዳ. 28፡58-62። በመሆኑም የደዌ ዘመቅሠፍት ዋና መንሥኤው በቅዱስ መጽሐፍ የተነገረውን የእግዚአብሔርን ቃል አለመጠበቅና በኃጢአት በቅቶ የኃጢአትን ጽዋ እስከ አፉ ድረስ መሙላት ነው። ከላይ እንደ ተጠቀሰውም ደዌ ዘመቅሠፍት የሚመጣባቸውና የሚከሠትባቸው መንገዶች ብዙ ናቸው። ከብዙዎቹም ጥቂቶቹን ብቻ እንደ መጽሐፍ ቅዱስ ገለጻ የሚቀጥሉትን የመቅሠፍት ዓይነቶችን መመልከት ይቻላል፦ ውስን ጊዜ ሰጥቶ የሚገድል የማይድን የአንጀት በሽታ፣ የማይድን ስብራትና መድኃኒት አልባ የቍስል በሽታ፣ ለሞት የሚዳርግ የልብ በሽታ፣ ለሞት የሚያበቃ ሰዓታዊ/ዕለታዊ ቸነፈር/ወረርሽኝ፣ ተልቶ መሞት፣ በክፉ መንፈስ ርኩስ መሠቃየት… በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡ 2ኛ ዜና. 21፡1-20፤ ኤር. 30፡11-15፤  ዘዳ. 28፡27፤ 1ኛ ሳሙ. 25፡37-38፤ ዘኍ. 16፡49፤ 1ኛ ዜና. 21፡14፤ ሐዋ. 12፡23፤ 1ኛ ሳሙ. 16፡14-23 ከላይ ከተጠቀሱ የመቅሠፍት ደዌያትም ባሻገር በኃጢአት ምክንያት የሚከሠቱና ወዲያውኑ ለሞት የሚዳርጉ የመቅሠፍት ዓይነቶችን መመልከት ይቻላል፦ ቅጽበታዊ በሆነ መቅሠፍት መሞት፣ በምድር መደርመስ ምክንያት መሞት፣ በእባብ ተነድፎ ተሠቃይቶ መሞት፣ በውሻ ተበልቶ መሞት፣ ድንገት በአንበሳ ተሰብሮ መሞት፣ ድንገት ወድቆ መሞት፣ በጦርነት ሜዳ በጠላት እጅ መሞት፣ በንፍር/ትኩስ/የፈላ ውኃ ተቀቅሎ መሞት፣ በእሳት ተቃጥሎ መሞት፣ በባሕር ውስጥ ሰጥሞ መሞት፣ እንዲሁ ወዲያው ከመ ቅጽበት መሞት፣ ከሰው ተፈጥሮ ወደ ጨው ሐውልት/ድንጋይ መለወጥ፣ በሰይፍ፣ በረኃብና በቸነፈር መሞት…፡፡ ዘኍ. 26፡60-61፤ መዝ. 104/105፡16-17፤ ዘኍ. 14፡37፤  ዘፍ. 38፡7፤ 1ኛ ዜና. 13፡9-11፤ ዘኍ. 21፡6፣ 2ኛ ነገ. 9፡10-36፣ 1ኛ ነገ. 13፡21፡24፤ 1ኛ ነገ. 21፡35-36፣ 1ኛ ሳሙ. 3፡12-14፣ 4፡18፣ 1ኛ ሳሙ. 2፡12፣ 22፤ 4፡11፣ ዘፍ. 7፡11-23፣ ዘፍ. 19፡24-26፣ ሐዋ. 3፡13-10፣ ዘፀ. 14፡28፣ ዘፍ. 19፡26፣ ሕዝ. 6፡12፣  ኤር. 14፡12። በሰዎች የኃጢአት ምላት ምክንት ሊመጣ ከሚችል ደዌ ዘመቅሠፍት ራስንና ወገንን ለማትረፍ “የእግዚአብሔርም ቍጣ እንዳይነድባችሁ፥ ዝናብም እንዳይዘንብ ምድሪቱም ፍሬዋን እንዳትሰጥ ሰማይን እንዳይዘጋባችሁ፤ እግዚአብሔርም ከሚሰጣችሁ ከመልካሚቱ ምድር ፈጥናችሁ እንዳትጠፉ ተጠንቀቁ!" እንደ ተባለ አስቀድሞ የኃጢአትን ሸክም አራግፎ በንስሓ ወኔ የጽቅን ዝናር ታጥቆ ቅዱሱን የእግዚአብሔርን ቃል ሾተል አጥብቆ መያዝ ነው። ዘዳ. 11፡17። ስለ ሆነም “በበደል ላይ በደል እየ ጨመራችሁ ለምን ትቀሠፋላችሁ? ራስ ሁሉ ለሕመም፥ ልብም ሁሉ ለሐዘን ሆኗል፤ ከእግር ጫማ አንሥቶ እስከ ራስ ድረስ ጤና የለውም፤ ቍስልና ዕበጥ፥ የሚመግልም ነው፤ አልፈረጠም፥ አልተጠገነምም፥ በዘይትም አልለዘበም።" (ኢሳ. 1፡5-6) እንደ ተባለ ከደዌ ዘመቅሠፍት ራስንና ሌላውን ለማዳን "ኑ! ወደ እግዚአብሔር እንመለስ፤ እርሱ ሰብሮናልና፥ እርሱ ይፈውሰናል፤ እርሱ መትቶናል፥ እርሱም ይጠግነናል።” (ሆሴ. 6፡1) በሚለው የንስሓ ጥሪ መሠረት በፍጹም ልቡና ወደ እግዚአብሔር ተመልሶ አብዝቶ ከልብ ማልቀስና በሠሩት የኃጢአት ሥራ ከልብ እየ ተጸጸቱ ከእግዚአብሔር ዘንድ ምሕረትን መሻት ነው። "እግዚአብሔርም ያጠፋት ዘንድ ወደ ኢየሩሳሌም መልአክን ሰደደ፤ ሊያጠፋትም በቀረበ ጊዜ ዳዊት ዐይኖቹን አነሣ፤ የእግዚአብሔር መልአክ በምድርና በሰማይ መካከል ቆሞ፥ የተመዘዘም ሰይፍ በእጁ ሆኖ ወደ ኢየሩሳሌም ተዘርግቶ አየ፤ ዳዊትም ሽማግሌዎችም ማቅ ለብሰው በግምባራቸው ተደፉ፤ እግዚአብሔር አይቶ ስለ ክፉው ነገር ተጸጸተ፥ የሚያጠፋውንም መልአክ <በቃህ! አሁን እጅህን መልስ!> አለው። የእግዚአብሔርም መልአክ በኢያቡሳዊው በኦርና ዐውድማ አጠገብ ቆሞ ነበር።" (1ኛ ዜና. 21፡15-16) ተብሎ እንደ በመጽሐፍ እንደ ተገሐጠውም የዳዊትንና የሽማግሌዎቹን ፈለግ በመከተል የኃጢአትን ራስ ዝቅ አድርጎ በጌታ ፊት እግረ ልቡናን መስበር ነው። በንጹሕ ልቡና ከተመለሱም “ከሰይፍና ከረኃብ ከቸነፈርም ጥቂቶች ሰዎችን ከእነርሱ አስቀራለሁ፤ እኔም እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ያውቃሉ።” (ሕዝ. 12፡16) ሲል ምናልባት ብዙዎች በጅምላ በሞተ - ኃጢአት ሲያልቁ በጽድቃቸው ከሚቀሩ ጥቂቶቹ መካከል እርስዎ ሊሆኑ ይችላሉ።

✅ የምትጾሙ ሰዎች ይሄን ብታነቡት መልካም ነው👇 ✅ ሙሉ መጽሐፉን ደግሞ ገዝታችሁ ብታነቡት ብዙ ታተርፉበታላችሁ! ለበለጠ መንፈሳዊ መረጃ👇 https://t.me/yaredzer
+1
✅ የምትጾሙ ሰዎች ይሄን ብታነቡት መልካም ነው👇 ✅ ሙሉ መጽሐፉን ደግሞ ገዝታችሁ ብታነቡት ብዙ ታተርፉበታላችሁ! ለበለጠ መንፈሳዊ መረጃ👇 https://t.me/yaredzer

ምናልባትም ካንተ ሕይወት ጋር ሊመሳሰል ይችል ይሆናልና እስኪ የሚከተለውን ኀይለ ቃል በማስተዋል አንብበው!፦ “ከኢያሪኮም በወጣ ጊዜ ደቀመዛሙርቱ ከእርሱ ጋር ነበሩ፤ ብዙ ሰውም ነበረ፤ የጤሜዎስ ልጅ በርጤሜዎስም በመንገድ ዳር ተቀምጦ ይለምን ነበር፤ የናዝሬቱ ኢየሱስ እንደ ሆነም ሰምቶ ‹‹የዳዊት ልጅ ኢየሱስ ሆይ! ማረኝ!›› ብሎ ጮኸ፤ ብዙዎችም ዝም እንዲል ገሠጹት፤ እርሱ ግን ድምፁን ከፍ አደረገና ‹የዳዊት ልጅ ሆይ! ማረኝ!› አለ፤ ጌታችን ኢየሱስም ቆመና ‹ጥሩት› አለ፤ እነርሱም ዕውሩን ጠሩት፤ ‹በርታና ተነሥ መምህር ይጠራሃል›፤ እርሱም  ተነሥቶ ልብሱን ትቶ ወደ ጌታችን ኢየሱስ መጣ፤ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ ‹ምን ላደርግልህ? ትሻለህ?› አለው፤ ዕውሩም ‹መምህር ሆይ! እንዳይ ነው› አለው፤ ጌታችን ኢየሱስም ‹ሂድ! እምነትህ አዳነችህ› አለው፤ ወዲያውም አየ፤ በመንገድም ተከተለው።” ማር. 10፡46-52። አየህ? ወዳጄ! የሰዎችን ተቃራኒ ሐሳብ ሳትሰማ አብዝተህ መጮህ ትርጉም አለው። ውጤትንም ያስገኝልሃል። ስለዚህ እልሃለሁ አብዝተህ አብዝተህ ከልብህ ጩህ! አብዝተህ የምትጮኸውን ጩኸት እግዚአብሔር የሚሰማ ከሆነ ጩኸትህ ስለሚያስከፋቸው ሰዎች አትጨነቅ! እስኪጠራህ ድረስ ዝም ብለህ በጸሎት ጩህ! ወዳጄ! ሆይ! የበሽታህን ስሜት ለአፍታ ቻል አድርገውና እስኪ ይህን ጥቅስ ልብ ብለህ አንብበው! “ልጄ ሆይ! የጌታን ቅጣት አታቃልል! በሚገሥጽህም ጊዜ አትድከም! ጌታ የሚወደውን ይቀጣዋልና፥ የሚቀበለውንም ልጅ ሁሉ ይገርፈዋል… ለመቀጣት ታገሡ! እግዚአብሔር እንደ ልጆች ያደርግላችኋልና፤ አባቱ የማይቀጣው ልጅ ማን ነው?... ቅጣት ሁሉ ለጊዜው የሚያሳዝን እንጂ ደስ የሚያሰኝ አይመስልም፥ ዳሩ ግን በኋላ ለለመዱት የሰላምን ፍሬ እርሱም ጽድቅን ያፈራላቸዋል።” ዕብ. 12፡5-11። ጌታ የቀጣህ ለራሱ ሊያደርግህ ወዶህ እንጂ ጠልቶህ አይደለም። በመቀጠልም “እኔ የምወዳቸውን ሁሉ እገሥጻቸዋለሁ፤ እቀጣቸውማለሁ፤ እንግዲህ ቅና፤ ንስሓም ግባ።” ራእ. 3፡19 ይልሃል። ወገኖቼ ሆይ! በየትኛውም ስፍራ የትኛውንም የጽድቅ ሥራ ብንሠራም ኃጢአት የለብንም ከኃጢአትም ነጻ ነን ልንል አይገባም። ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌምም “ወኢይትከሀል የሀሉ ሰብእ እንበለ ሓጢአት ወፈድፋደሰ እንተ ትከውን እምሕሊና እስመ ሕሊናሁ ለሰብእ ይትወላወል እምጊዜ ልደቱ እስከ ዕለተ ሞቱ = ሰውም ያለ ኃጢአት ሊኖር አይችልም፤ ይልቁንም ከሐልዮ ኃጢአት የሚነጻ የለም፤ የሰው ሕሊና ከተወለደበት ቀን ጀምሮ እስከሚሞትበት ቀን ድረስ ሲወጣ ሲወርድ ይኖራልና።” ብሏል። ሃይ. አበ. ፶፪፡፲፰። ይልቁንም “የልጁም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻናል፤ ኃጢአት የለብንም ብንል ራሳችንን እናስታለን፥ እውነትም በእኛ ውስጥ የለም፤ ኃጢአታችንን ብንናዘዝ ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን ከዐመፃም ሁሉ ሊያነጻን የታመነ ጻድቅ ነው።” በማለት ቅዱስ ዮሐንስ እንዳስተማረን ራሳችንን ለካህን በማሳየት የዕለት ተዕለት ኃጢአታችንን እንናዘዝ። 1ኛ ዮሐ. 1፡7-9። ከደዌ ሥጋና ከደዌ ነፍስ የሚያነጻን የኢየሱስ ክርስቶስንም ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም በንጽሕና እንቀበል። የኃጢአት ውጤት ከሆነ “ከደዌ ዘኃጢአትም” እንገላገል። “ከደዌ ነፍስም” ነፍሳችንን እንታደግ! “ኃጢአተኛውም ከሠራው ኃጢአት ቢመለስ ፍርድንና ቅን ነገርንም ቢያደርግ ነፍሱን ይጠብቃል፤ ዐስቦ ከሠራው በደል ሁሉ ተመልሷልና ፈጽሞ በሕይወት ይኖራል እንጂ አይሞትም።” ሕዝ. (18፡27-28) የሚለውንም ቃል በመገንዘብ “ንስሓ ግቡ ኃጢአትም ዕንቅፋት እንዳይሆንባችሁ ከኀጢአታችሁ ሁሉ ተመለሱ!” (ሕዝ. 18፡30) የሚለውን ቃል ብንተገብርና ብንፈጽም “እኔ ‹ጤናህን እመልስልሃለሁ ቍስልህንም እፈውሳለሁ› ይላል እግዚአብሔር” የሚል መልስ ከቸሩ አባታችን ከእግዚአብሔር ዘንድ አሁኑኑ እናገኛለን። ኤር. 30፡17። #ድኅረ_ድኅነት በእግዚአብሔር ቸርነት በአንድም በሌላም ምክንያት ከዳኑና ከተፈወሱ በኋላ ሠላሳ ስምንት ዓመት ሙሉ ሽባ ለነበረው ሰው “እነሆ ድነሃል፤ ነገር ግን ከዚህ የሚከፋ እንዳያገኝህ ዳግመኛ እንዳትበድል ተጠንቀቅ” (ዮሐ. 5፡14) ተብሎ ምክር እንደ ተሰጠው ወደ መጀመሪያው በሽታ ላለመለስና ከዚያም በባሰ በሽታ ላለመያዝ “ተፈውሻለሁ/ድኛለሁ” ተብሎ ከቤተ ክርስቲያን አለመራቅ፣ መጻሕፍተ እግዚአብሔርን አዘውትሮ ማንበብ፣ በጾምና በጸሎት መወሰን፣ ሳያውቁም ዐውቀውም ሲያጠፉና ሲበድሉ ወዲያውኑ ንሥሓ መግባት ዋና ዋናዎቹ ቀደምት መንፈሳውያን ተግባራት ናቸው። ይልቁንም ሃይማኖትን ከምግባር ጋር እንደ ሰምና እንደ ፈትል አድርጎ አጽንቶ መያዝ ነው። ባለዎትም ጸጋ ዘወትር እገዚአብሔርን ማገልገል ግድ ይልዎታል። ቅዱስ መጽሐፍም “ከክፉዎች መናፍስትና ከደዌም ተፈውሰው የነበሩ አንዳንድ ሴቶች፤ እነርሱም ሰባት አጋንንት የወጡላት መግደላዊት የምትባል ማርያም፥ የሄሮድስ አዛዥ የኩዛ ሚስት ዮሐናም፥ ሶስናም ብዙዎች ሌሎችም ሆነው በገንዘባቸው ያገለግሉት ነበር።” ይላል። ሉቃ. 8፡2-3። እንደ እግዚአብሔር ቃል መመራት ካልቻሉ ግን ከመጀመሪያው የባሰና የከፋ ያውም ከመጀመሪያው በሽታዎ ሰባት ዕጥፍ የሆነ በሽታ ይመጣብዎታል። ይህም ለማስፈራራት ሳይሆን “እምከመ ወፅአ መንፈስ ርኩስ እም ሰብእ የዐውድ በድወ ኀበ አልቦ ማይ እንዘ የኀሥሥ ዕረፍተ ወየኀጥእ፤ ወእምዝ ይብል እገብእ እንከሰ ውስተ ቤትየ እምኀበ ወፃእኩ እምኔሁ፤ ወመጺኦ ይረክቦ ዕሩቀ ወኵስቱረ ወምሩገ፤ ወእምዝ የሐውር ወያመጽእ ምስሌሁ ሰብዓተ ካልኣነ መናፍስተ እለ የአክዩ እምኔሁ፤ ወበዊኦሙ የኀድሩ ውስቴቱ ወይከውን ደኃሪቱ ለውእቱ ብእሲ ዘየአኪ እም ቀዳሚቱ = ርኩስ መንፈስ ከሰው በወጣ ጊዜ ዕረፍትን እየ ፈለገ ውኃ በሌለበት ቦታ ያልፋል፤ አያገኝምም፤ በዚያን ጊዜም ወደ ወጣሁበት ቤቴ እመለሳለሁ ይላል፤ ቢመጣም ባዶ ሆኖ ተጠርጎና አጊጦ ያገኘዋል፤ ከዚያ በኋላም ይሄድና ከእርሱ ይልቅ የከፉትን ሰባት ሌሎች አጋንንትን ከእርሱ ጋር ይወስዳል፤ በዚያም አብረው ይኖራሉ፤ ለዚያም ሰው ከፊተኛው ሕመሙ ይልቅ የኋለኛው በሽታ ይብስበታል።” ብሎ ጌታችን የተናገረው ቃል የማይታበል ነው። ማቴ. 12፡43-45። በመቀጠልም ክፍል ፪ ይቀጥላል… ጦማሪ፦ መጋቤ ምስጢር ያሬድ  ዘርአ-ቡሩክ የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቃውንት ጉባኤ ዋና ሰብሳቢ

“ትፈቅድኑ ትሕየው - ከበሽታህ ልትድን ትወዳለህን?” ዮሐ. ፭፡፮ ✅ ክፍል ፩  ➖  በሽታ ምንድን ነው?  ➖ “በሽታ” የሚለው ቃል አስገኝ ግስ የሌለው ዐማርኛዊ ነባር ቃል ሲሆን በግእዝ ቋንቋ “ደዌ፣ ሕማም፣ ዝልጋሴ፣  አዴዴርማን፣ መስፈርስ…” የሚል ስም ይሰጠዋል። በሽታ ሕይወት ባለው ፍጡር ሁሉ ሊከሠት የሚችልና በሥሩ ቸነፈርን፣ ወረርሽኝን፣ የትኛውንም ቀላልና ከባድ የሕመም ስሜት ያካተተ፣ ልዩ ልዩ መጠሪያ ስም ያላቸው የበሽታ ዓይነቶች ጥቅል የሕመም ስሜት ውጤት መጠሪያ ስም ነው። ➖ በሽታ ምንጩ ከምንድን ነው? ➖ በሽታ የመጀመሪያው ሰው አዳም በፈጸመው ኃጢአት አማካኝነት ኃጢአትን ተከትሎ የመጣ፥ የኃጢአት ውጤት ነው። ዘፍ. 3፡16-19። በሽታ እንደ ሊቃውንት የአንድምታ ሐተታ “ደዌ ዘኃጢአት፣ ደዌ ዘመቅሠፍት፣ ደዌ ዘንጽሕና ደዌ ዘዕሴት” ተብሎ በአራት ይከፈላል። ዮሐ. 5፡14። ደዌ ማለትም “በቁሙ ደዌ፣ በሽታ፣ ሕመም፣ የቈየ፣ የዘገየ፣ ዐብሮ የሚኖር፣ ወይም ዐልፎ ኻያጅ” ማለት መሆኑን ተርጓምያን ገልጸዋል። ከላይ የተጠቀሱት አራቱ የደዌ ዓይነቶችንም ከዚህ በታች በዝርዝር እንመለከታቸዋለን፦ ፩. #ደዌ_ዘኃጢአት “ደዌ ዘኃጢአት” ሰዎች የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በመሻር በሚያደርጉት ኃጢአት ምክንያት የሚመጣ የኃጢአት ውጤት የሆነ በሽታ ነው። ይህም በሽታ በሥሩ የተለያየ የሕመም ስሜት ያለው ሲሆን ከኃጢአት ተመልሰው ንስሓ ካልተቀበሉበት አእምሮን ከማሳጣት ጀምሮ እስከ ሞት ድረስ ሊያደርስ የሚችል የሥጋም የነፍስም የከፋ ሕመም ስሜት ያለው በሽታ ነው። የዚህ የደዌ ዘኃጢአት መንሥኤው የእግዚአብሔርን ቃል አለመስማትና ሊጠበቁ የታዘዙትን ትእዛዛቱን፣ ሕገጋቱንና ሥርዐቱን ሁሉ አለመጠበቅና አለመተግበር ነው። ዘዳ. 28፡15-35። እንደ መጽሐፍ ቅዱስ ገለጻ ደዌ ዘኃጢአት በሥሩ ካቀፋቸው የበሽታ ዓይነቶችም በከፊል፦ ለብዙ ጊዜ የሚቈይ የአልጋ ቁራኛ/ሽባ የሚያደርግ በሽታ፣ የለምጽ በሽታ፣ ዐይንን ጋርዶ የሚያሳውር ቅጽበታዊ የዐይን በሽታ፣ የዕባጭ በሽታ፣ ዲዳ የሚያደርግ በሽታ፣ የእጅ መስለል በሽታ፣ ለሞት የሚያበቃ ሙሉ ሰውነትን ሽባ የሚያደርግ ዐደገኛ በሽታ… መጥቀስ ይቻላል። ዮሐ. 5፡5-9፣ 14፤ ሐዋ. 9፡33-35፤ ኢዮ. 33፡19፤ ዘኍ. 12፡1-15፤ 2ኛ ነገ. 5፡20-27፤ ማቴ. 8፡2-4፤ ሉቃ. 17፡12-14፤ ሐዋ. 13፡6-11፤ 2 ነገ. 20፡1-7፤ ሉቃ. 1፡5-23፤ 1ኛ ነገ. 13፡4-6፤ 2ኛ ነገ. 1፡2-17። ከላይ ከተጠቀሱ ደዌያት ባሻገርም በኃጢአት ምክንያት ሊከሠቱ የሚችሉ ሌሎች የኃጢአት ውጤቶች፦ ለጠላት እጅ ተላልፎ መሰጠት፣ በጠላት እጅ መማረክ፣ ከሰው-ሰውኛ ተፈጥሮ ወደ እንስሳ ተፈጥሮ መለወጥ ሊኖር ይችላል። ሕዝ. 39፡23፤ 2ኛ ነገ. 24፡18-19፤ ኤር. 21፡7፤ ዳን. 4፡33። በዚህ ሰሞን ታሪኩ የሚተረክለት መፃጕዕም በደዌ ዘኃጢአት የተጠቃ ኃጢአተኛ ሰው ነበር። በኃጢአቱ ምክንያት የታመመ ኃጢአተኛ ሰው የነበረ መሆኑን ለመረዳትም “ከዚህ የሚብስ እንዳያገኝህ ዳግመኛ አትበድል!” ብሎ ያስጠነቀቀውን የጌታን ቃል ማስታወስ ነው፡፡ የዚህ ሰው ስም በበሽታውም ምክንያት ጠፍቷል። መፃጕዕ በሽታውን ተከትሎ የመጣ የበሽታው ስም ነው። ይህ ሰው በደዌ ዳ፥ በአልጋ ቍራኛ ተይዞ ለሠላሳ ስምንት ዓመት ሙሉ ድኅነትን ሲሻ የኖረ ሰው ነው። በበሽታውም ምክንያት ቤተሰቦቹን ጨምሮ ሰው የራቀውና የናቀው፥ ሰው አልባ ሰው ነበር፡፡ እንዲያም ሆኖ ይህ ሰው የጽድቅን ሥራ መሥራቱ የሚገልጽ የመጽሐፍ ክፍል የለም፡፡ ይህ ሰው ውጫዊ ሰውነቱ መፃጕዕ እንደ ሆነ ሁሉ ልቡም መፃጕዕ ነበር።  ጌታ “ለማንም አትንገር!” ብሎ ያዘዘውን ትእዛዝ ሽሮ በዐደባባይ አውጥቶ መናገሩም የልቡን መፃጕዕነት  ያረጋግጥልናል፡፡ ከሁሉም የሚከፋ የልብ መፃጕዕነት ነው፡፡ ይህም በሽታ በቀላሉ የሚፈወስ አይደለም፡፡ ሰፊ ጊዜን፣ እምነትን፣ ምግባርንና ንስሓን ይጠይቃል፡፡ #ከደዌ_ዘኃጢአት ለመዳን ምን ማድረግ ይቻላል? ማንኛውም በደዌ ዘኃጢአት የተያዘ ሰው ሳይዘገይ ራሱን ለካህን በማሳየት ከኃጢአት በመንጻት የሻረውን የእግዚአብሔርን ቃል መልሶ በመጠበቅ "ከእናንተ የታመመ ሰው ቢኖር በቤተ ክርስቲያን ያሉ ቀሳውስትን ይጥራና ይጸልዩለት፤ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም የተጸለየበትንም ዘይት ይቅቡት፤ የሃይማኖት ጸሎትም ድውዩን ይፈውሰዋል፤ እግዚአብሔርም ያስነሣዋል፤ ኃጢአትንም ሠርቶ እንደ ሆነ ይሰረይለታል።” የሚለውንም ቅዱስ ቃል ተግባራዊ ማድረግ ነው። ያዕ. 5፡14። “አምላካችሁ እግዚአብሔር ቸርና መሓሪ ነውና፥ ወደ እርሱም ብትመለሱ ፊቱን ከእናንተ አያዞርምና” ተብሎ እንደ ተጻፈም እግዚአብሔር የሚያየው የትናንቱን ነውር ሳይሆን የዛሬውን ከልብ ወደ ርሱ መመለስን ነው። 2ኛ ዜና. 30፡9። በሕመማችንም ጊዜ “እግዚአብሔር በደዌው አልጋ ሳለ ይረዳዋል፤ መኝታውን ሁሉ በበሽታው ጊዜ ያነጥፍለታል።” (መዝ. 41፡3) እንዲልም ጥሎ የማይጥል፣ ክዶ የማይከዳ፣ እንደ ሰው ልጅ ፍጹም ቂመኛ ያይደለ፣ በንስሓ እንባ ለጠየቁት ሁሉ ፊቱን የማያዞር፣ የምሕረት ፊቱን የሚያሳይ፣ ኃጢአትን ሁሉ የሚደመስስ፣ ነውርን ሁሉ የማይቈጥር፣ እንደ ሰው ልጅ የትናንትናን ስሕተት ሒሳብ የማያወራርድ ብቸኛ ርኅሩኅ ይቅር ባይ አባት ነው። ወገኔ ሆይ! በሽታ የሆነብህ የገዛ ኃጢአትህ እንደ ሆነ አምነህ የምትታመመውም ለቅጣት እንደ ሆነና ከስሕተትህ እንድትታረም መሆኑን ልብ በል! “አድንህ ዘንድ ከአንተ ጋር ነኝ ይላል እግዚአብሔር አንተን ፈጽሜ አላጠፋህም፤ በመጠን እቀጣሃለሁ፥ ያለ ቅጣትም ከቶ አልተውህም።” ተብሏልና። ኤር. 30፡11። አየህ? ወዳጄ! ኃጢአትህ ተራራን ያህል ገዝፎ ሳለ የተቀጣኸው ግን በመጠን ነው። በመጠነኛውም ቅጣት እቀጣሃለሁ እንጂ በጭራሽ አልተውህም ይልሃል፤ ፈጽሜ አላጠፋህም እያለም ያጽናናሃል። ኃጢአትህ ዐይሎ ፈጽሞ ቢያጠፋህስ ኖሮ ምን ታመጣ ነበር? እርግጠኛ ነኝ መልስህ ምንም ነው። በሰው ክንድ የምትታመን ወዳጄ ሆይ “ሰው የለኝም” ብለህ ተስፋ አትቍረጥ ፤ በዘመድና አዝማድ ክንድ መታመንህንም ትተህ በእግዚአብሔር ክንድ ታመን፤ በቃሉም ታመን፤ የእግዚአብሔርም ክንድ የማይዝል ክንድ ነው፤ ከወደቅህበትም ያነሣሃል። መዝሙረኛው ዳዊትም “እግዚአብሔር በቃሎቹ የታመነ ነው፤ በሥራውም ሁሉ ጻድቅ ነው፤ እግዚአብሔር የተፍገመገሙትን ሁሉ ይደግፋቸዋል፤ የወደቁትንም ያነሣቸዋል።” ይላል። መዝ. 144፡14። በላይህ ጤነኛ፥ በሕሊናህ መፃጕዕ የሆንክ ወዳጄ ሆይ ካለብህ የሥጋና የነፍስ ደዌ ልትድን ትወዳለህን? መልስህ አዎን ከሆነ እንግዲያውስ ክፋትን፣ ተንኰልን፣ አድመኝነትን፣ ዘረኝነትን፣ ጎጠኝነትን፣ መለያየትን፣ ሐሜትን፣ ውሸትን፣ ዝሙትን... ተው!። የሠራኸውንም ነውር እያሰብህ በንስሓ ወደ እግዚአብሔር ተመለስ። ይህን ያደረግህ የሆነ እንደ ሆነ ፍጹም ድኅነትን ታገኛለህ። ለዘመናት ከተጣበክህበት የኃጢአት አልጋ ላይም ወርደህ በፍጹም ደስታ ወደ ቤትህ ትመለሳለህ። ወዳጄ ሆይ! ከበሽታህ ጽናት የተነሣ "አልድንም" ብለህ በጭራሽ ተስፋ አትቍረጥ! በራስህም ላይ የምትወስነው ክፉ ነገር አይኑር። ነገር ግን ለመዳን አብዝተህ ወደ እግዚአብሔር ጩህ። ሰዎችም የበሽታህን ጽናት እያዩ ተስፋ ሲያስቈርጡህ በጭራሽ አትስማቸው።

በምሥራቅ ኢትዮጵያ የሚገኘው ታላቁና አንጋፋው የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ጽሕፈት ቤት ኦርቶዶክሳዊ ትምህርተ ሃይማኖትንና ያሬዳዊ ዜማን ወደ ተመልካቾችና አንባብያን እያደረሰ ይገኛል። ገጹን Follow ያ
+1
በምሥራቅ ኢትዮጵያ የሚገኘው ታላቁና አንጋፋው የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ጽሕፈት ቤት ኦርቶዶክሳዊ ትምህርተ ሃይማኖትንና ያሬዳዊ ዜማን ወደ ተመልካቾችና አንባብያን እያደረሰ ይገኛል። ገጹን Follow ያላደረጋችሁ ውድ ኦርቶዶክሳውያን Follow እያደረጋችሁ ለሌላው ደግሞ  Share በማድረግ ተደራሽ ብታደርጉ ብዙዎችን በወንጌል ቃል ትጠቅማላችሁ። በቅርቡም የሚከፈተውን YouTube እናስታዋውቃችኋለን። ገጽ👇 https://www.facebook.com/share/18SnUcUxZC/ https://www.facebook.com/share/1BwUATG9bC/

የቀጠለ ክፍል ፪. አንድም ቤትም፥ መቅደስም፥ ምኵራብም የተባለው የኛ ሰውነት ነው። አንድም የኛ ሕሊናና ልቡና ነው። ላሞቹና በጎቹም ክፋት፣ ተንኰል፣ ስርቆት፣ ሐሰት፣ ጥላቻ፣ መካሰስ፣ መወነጃጀል፣ መለያየት፣ መገዳደል... ናቸው። ገንዘብ የተባለውም በቁሙ ለብዙዎች ክሕደትና ሞት ምክንያት የሆነው ቁስ ገንዘብ ነው። ወንበዴዎችና ዘራፊዎች የተባሉትም እነዚህን ሁሉ ለሰው ልጆች የሚቸረችሩና  የሚያከፋፍሉ አጋን*ንትቀ ናቸው። የኛም ሥጋ/ሰውነት ቤተ መቅደስነቱ ለእግዚአብሔር ነው። ይህም አማናዊ መቅደስ እግዚአብሔር ቀድሞ በአርአያውና በአምሳሉ ያነጸው፥ በእግዚአብሔር መልክ የተሠራ፥ የማንም የፍጡር እጅ ያልተጠበበበት ሕያው መቅደስ ነበር። ነገር ግን በጠላት ዲያ*ብሎስ ሴራ በተሠራ በሰባት ዐመቱ ድንገት ፈርሶ ለ5500 ዘመናት የአጋ*ንንት ማደሪያ ባድማ፥ ዑና ስፍራ ሆኖ ቈይቷል። በኋላም ሕያው ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ በቀራንዮ ሕያው ደሙን አፍሶ፥ ባፈሰሰው ደሙ ያደፈውን፥ መቅደስ የተባለውን ሰው ዐጥቦ፥ በወርቀ ደሙ ዋጅቶ የራሱ ቤተ መቅደስ አድርጎታል። ቅዱስ ጳውሎስም "ሥጋችሁ ከእግዚአብሔር የተቀበላችሁት በእናንተ የሚኖረው የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንደ ሆነ አታውቁምን? በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም፤ ስለዚህ በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ።" ያለው ለዚህ ነው። ፩ኛ ቆሮ. ፮፡፲፱-፳። ይህን ጽሑፍ በእምነት የምታነቡ ወንድሞችና እኅቶች ሁላችንም በሕያው የክርስቶስ ደም የተዋጀን ሕያዋን አብያተ መቅደስ ነን። ኀጢአታችንን ሳይመለከት በሕያው ደሙ የዋጀንም ስሙ፦ አልፋና ኦሜጋ፥ ቀዳማዊና ደሓራዊ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ይባላል። መቅደሰ እግዚአብሔር የሆነውንም ሰው የሚያፈርስ ከመቅሱ ባለቤት ከእግዚአብሔር ዘንድ ፍርድ ይጠብቀዋል። መቅደሱንም በኀጢአት ያሳደፈና ያረከሰ የዘለዓለም ውርደት ይከተለዋል። ሐዋርያውም "ኢተአምሩኑ ከመ ታቦቱ ለእግዚአብሔር አንትሙ፤ ወመንፈሰ እግዚአብሔር ሕዱር ላዕሌክሙ፤ ወዘሰ አማሰነ ቤተ እግዚአብሔር ሎቱኒ ያማስኖ እግዚአብሔር ወቤቱሰ ለእግዚአብሔር አንትሙ ውእቱ ወቅዱሳን አንትሙ፤ ወኢታርኵሱ ቤቶ ለእግዚአብሔር = =  የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንደ ሆናችሁ፥ የእግዚአብሔርም መንፈስ እንዲኖርባችሁ አታውቁምን? ማንም የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ቢያፈርስ እግዚአብሔር እርሱን ያፈርሰዋል፤ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ቅዱስ ነውና፥ ያውም እናንተ ናችሁ።" ይለናል። 1ኛ ቆሮ. ፫፡፲፮-፲፯። ስለሆነም ውድ አንባብያን በቃሉ ታንጸን የእግዚአብሔር አብያተ መቅደስ ለመሆን በእግዚአብሔር ሕግና ትእዛዝ መኖር ግድ ይለናል። መድኅነ ዐለም ክርስቶስም የርሱ ቤተ መቅደስ መሆናችን የሚረጋገጠው እንደ ቃሉ መኖር ስንችል ብቻ መሆኑን ሲያስገነዝበን "ዘያፈቅረኒ ይዕቀብ ቃልየ ወያፈቅሮ አቡየ ወእመ ቦ ዘዐቀበ ቃልየ አነ ወአቡየ ንመጽእ ኀቤሁ ወንገብር ምዕራፈ ውስቴቱ = የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል፥ ወደ እርሱም እንመጣለን በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን።" በማለት  አረጋግጦልናል። ዮሐ. 14:23። 👉አንባብያን ሆይ! አይሁድ ይገበያዩበት እንደ ነበረው መቅደስ ኀጢአትን ከአጋ*ንንት ጋር የምንገበያይበት የሰውነት መቅደስ እንዳይኖረን መቅደሰ እግዚአብሔር የሆነውን ሰውነታችንን ለጸሎት፣ ለጾም፣ ለምስጋና፣ ለስግደት፣ ለንስሓና ለአምልኮተ ክርስቶስ አገልግሎት መስጫ ልናውለው ይገባል። ጦማሪ፦ መጋቤ ምስጢር ያሬድ ዘርአ-ቡሩክ የቅኔና የመጻሕፍት ትርጓሜ መምህር

"ህየ ብንያም ወሬዛ በኀይሉ።" መዝ. ፷፯፡፳፯ (68፡27)
"ህየ ብንያም ወሬዛ በኀይሉ።" መዝ. ፷፯፡፳፯ (68፡27)

"ቤትየሰ ቤተ ጸሎት ይሰመይ ለአሕዛብ = ቤቴ ለሰዎች ሁሉ የሚሆን የጸሎት ቤት ይባላል።” ኢሳ. ፶፮፡፯ ምኵራብ - ቤተ መቅደስክፍል ፩ በይሁዳ ከተማ በኢየሩሳሌም አንድ መቅደስ ብቻ የነበረ ሲሆን ናቡከደነጾር ሰሎሞን የሠራውን ቤተ መቅደስ አፍርሶ ሕዝቡን ወደ ባቢሎን ካፈለሰበት ዘመን ጀምሮ ግን አይሁድ በሚገኙባቸው ሥፍራዎች ሁሉ ለጸሎት፣ ለምስጋናና ለትምህርት የሚሆን  ምኵራብ መሥራት ተጀምሯል። ከባቢሎን መልስ በኋላም በይሁዳና በእስራኤል ምድር ይበልጥ የምኵራብ መሠራት ቀጥሏል። ነገር ግን ለጸሎት፣ ለምስጋናና ለትምህርት ካልሆነ በቀር መሥዋዕት የሚቀርብበትና የሚሠዋበት አልነበረም። ምኵራብ ማለትም አዳራሽ/ቤት ማለት ነው። በምኵራብም አይሁዳውያን ሁሉ በመደበኛነት ቅዳሜ ቀን  ይሰባሰቡ ነበር። ዘወትርም በየዕለቱ የሚገኙ ነበሩ። ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስም "ዕለት ዕለት በምኵራብ ያስተምር ነበር፡፡" ተብሎ እንደ ተጻፈ ዕለት ዕለት በምኵራብ ተገኝቶ  አይሁድን ያስተምራቸው ነበር። ሉቃ. ፲፱፡፵፯። መጽሐፍ ቅዱስም አልፎ አልፎ በነዘሩባቤል፣ በነነህምያ፣ በኋላም በንጉሥ ሄሮድስ ዕድሳት የተደረገለትን የሰሎሞንን ቤተ መቅደስ "ምኵራብ" እያለ ይጠራዋል። ኢየሱስ ክርስቶስም በኢየሩሳሌም ወዳለው ቤተ መቅደስ መግባቱ ቅዱስ ማቴዎስ በጻፈው ወንጌል "ወቦአ እግዚእ ኢየሱስ ቤተ #መቅደስ ወሰደደ ኵሎ እለ ይሠይጡ ወይሣየጡ በቤተ #መቅደስ፤ ወገፍትዐ ማእዳቲሆሙ ለመወልጣን ወመናብርቲሆሙ ለእለ ይሠይጡ አርጋበ። = ጌታ ኢየሱስም ወደ መቅደስ ገባና በመቅደስ የሚሸጡትንና የሚገዙትን ሁሉ አስወጣ፥ የገንዘብ ለዋጮች ገበታዎችንና የርግቦች ሻጮች ወንበሮችንም ገለበጠ።" ተብሎ  ተረጋግጧል። ማቴ. ፳፩፡፲፪። ቅዱስ ማርቆስ የጻፈው ወንጌል ግን "ወበጽሐ ኢየሩሳሌም ወቦአ ቤተ #መቅደስ ወአኀዘ ይስድድ እለ ይሠይጡ ወይሣየጡ #በምኵራብ። = ወደ ኢየሩሳሌምም ደረሰ፤ ወደ ቤተ መቅደስም ገብቶ በቤተ መቅደስ የሚሸጡትንና የሚገዙትን ያወጣ ጀመር።" በማለት ወደ መቅደስ ገብቶ በምኵራብ ያሉትን አስወጣ ይላል። ይህም ቤተ መቅደሱን ምኵራብ ሲለው ነው። ማር. ፲፩፡፲፭። ቅዱስ ሉቃስ በጻፈው ወንጌል ደግሞ በተመሳሳይ "ወቦአ #ምኵራበ ወሰደደ ኵሎሙ እለ ይሠይጡ ወይሣየጡ በቤተ #መቅደስ = ወደ ምኵራብም ገብቶ በመቅደስ የሚሸጡትን የሚገዙትንም ሁሉ ያስወጣ ጀመር።" በማለት ወደ ምኵራብ ገብቶ በመቅደስ ያሉትን አስወጣ ይላል። ይህም ምኵራቡን ቤተ መቅደስ ሲለው ነው። ሉቃ. ፲፱፡፵፭። ቅዱስ ዮሐንስ በጻፈው ወንጌል ደግሞ "ወቀርበ በዓለ ፋሲካሆሙ ለአይሁድ ወዐርገ እግዚእ ኢየሱስ ኢየሩሳሌም፤ ወረከበ #በምኵራብ እለ ይሠይጡ ወይሣየጡ አልሕምተ ወአባግዐ ወአርጋበ ወመወልጣነ እንዘ ይነብሩ። = የአይሁድ ፋሲካም ቀርቦ ነበር፥ ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ፤ #በምኵራብም በሬዎችንና በጎችን ርግቦችንም የሚሸጡትን ገንዘብ ለዋጮችንም ተቀምጠው አገኘ።" ተብሎ ተጽፏል። መተርጕማንም ምኵራብ የሚለውን ቤተ መቅደስ ብለው ተርጕመውታል። ዮሐ. ፪፡፲፫-፲፬። ከላይ ወንጌላውያኑ ቤተ መቅደሱን ምኵራብ፥ ምኵራቡን ቤተ መቅደስ እያሉ መጥራታቸውን ተመልክተናል። በመሆኑም በአራቱ ወንጌላውያን እንደ ተዘገበው ኢየሱስ ክርስቶስ በይሁዳ ከተማ በኢየሩሳሌም ወዳለው ቤተ መቅደስ ገብቶ ነጋዴዎችንና ለዋጮችን የገሠጸው ሁለት ጊዜ ሲሆን አንደኛው  በዮሐንስ ወንጌል እንደ ተገለጠው በ፴፩ ዓ/ም ነው። ዮሐ. ፪፡፲፫-፲፯። ሁለተኛው ደግሞ በሦስቱ ወንጌላውያን እንደ ተገለጠው በ፴፬ ዓ/ም መጋቢት ፳፪  ቅዳሜ ቀን ነው። ማቴ. ፳፩፡፲፪-፲፫፤ ማር. ፲፩፡፲፭-፲፰፤ ሉቃ. ፲፱፡፵፭፡-፵፱። ቅዱስ ያሬድም በቀዳሚት ሰንበት የተከናወነውን ታሪክ በዕለተ እሑድ እንዲነገርና እንዲሰበክ አድርጓል። ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ ከአብና ከመንፈስ ጋር በዕሪና ወደሚመለክበት ቤተ መቅደስ ሲገባ አይሁድን ሲጸልዩ፣ ሲያመሰግኑ፣ ሲያመልኩ፣ ስለ ሓጢአታቸው እየወደቁና እየተነሡ ሲያነቡና ሲያለቅሱ  አላገኛቸውም። ይልቁንም ተቀምጠው በሬዎችን፣ በጎችንና ርግቦችን ሲሸጡና ገንዘብ ሲለውጡ አግኝቷቸዋል። የገመድ ጅራፍንም አበጅቶ በጎችንና በሬዎችን ከመቅደስ አስወጥቷቸዋል። ገበታዎቻቸውንም አፍርሶባቸዋል። የለዋጮችንም ገንዘብ በትኖባቸዋል። የርግብ ሻጮችንም ወንበር ገለባብጦ ርግቦቻችሁን ከዚህ አንሡ፥ አስወጡ ብሏቸዋል። ቤተ መቅደሱም የጸሎት ቤት እንጂ የንግድ ቤት እንዳይደለ በተግሣጽ አስገንዝቧቸዋል። ይልቁንም ሌቦችና ወንበዴዎች የሚገበያዩበት ገበያ አለመሆኑን ገልጦ ነግሯቸዋል። አይሁድ ቤተ መቅደሱን ሓጢአታቸውን በንስሓ ሊያራግፉበት ሲገባ እንስሳትንና አዕዋፋትን የሚያራግፉበት ገበያ አድርገውት ነበር።  የዝማሬ ድምፅም ሊያሰሙበት ሲገባ የእንስሳትና የአዕዋፋትን ድምፅ ያስተጋቡበት ነበር። የጽድቅ ልምምድን ሊለዋወጡበት ሲገባቸውም ጠገራ ብር ይለዋወጡበት ነበር። አይሁድ ቤተ መቅደሱን ሌቦችና ወንበዴዎችን ሰብስበው ሊመክሩበትና ሊገሥጹበት ሲገባ በሌቦችና በወንበዴዎች ተሰርቀውና ተዘርፈው የመጡትን  በጎችንና በሬዎችን ይገበያዩበት ነበር። ይህም ድርጊት ክርስቶስን ያስቈጣ እጅግ የአይሁድ ነውራቸው ነበር። ዮሐ. ፪፡፲፫-፲፯። እግዚአብሔር ወልድ ቤተ መቅደሱ ላልተገባ አገልግሎት መስጫ ሲውል ተቈጥቷል። እግዚአብሔርም ዓለማት ሁሉ ገንዘቦቹ ቢሆኑም ለወዳጆቹ ምሕረትን የሚያድልበትና የሚገለጥበት፣ የተነሳሕያንን ዕንባና ጸሎት የሚያብስበት፣ ንስሓቸውንም የሚቀበልበት፣ እርሱን ለማመስገን በተመረጡ ሰዎች ዘንድ የሚመሰገንበትና የሚመለክበት፣ ከስፍራዎች ሁሉ የተለየ ልዩ የጸሎትና የምስጋና ስፍራ ቤት ደግሞ አለው። ቤቱም ሰዎች ሁሉ እርሱን አምነው እርሱን ለሚያመልኩ እንዲሁ የተገባ ነው። ይህ ቤት ሰዎች በመልካቸው፣ በድኽነታቸው፣ በቋንቋቸው፣ በጎሳቸው፣ በጎጣቸውና በጾታቸው የማይገለሉበት፣ እኩል ከሌላው ጋር በጋራ የሚስተናገዱበት፣ በዓለም ካሉ ቤቶች ይልቅ እጅግ ሰላምንና ፍቅርን የተሞላ ሰላማዊ የሰላም ቤት ነው። ቤቱም ቤተ እግዚአብሔር ይባላል። ቤተ ክርስቲያንም ይሰኛል። እግዚብሔርም ከሌሎች ቤቶች የተለየ የራሱ የግሉ ቤቱ መሆኑን ሲገልጥ #ቤቴ ይለዋል። መዝሙረኛው ዳዊትም ይህ ቤት እግዘብሔር ያደረበት ከሌሎቹ ስፍራዎች ሁሉ የተለየ ቅዱስ የቅድስና ስፍራ መሆኑን ሲገልጥ "ደብር ዘሠምሮ እግዚአብሔር የኀድር ውስቴቱ እስመ የኀድሮ እግዚአብሔር ለዝሉፉ። = እግዚአብሔር ይህን ተራራ ያድርበት ዘንድ ወደደው፤ በእውነት እግዚአብሔር ለዘለዓለም ያድርበታል።" በማለት በመንፈስ ቅዱስ ተነድቶ መስክሯል። መዝ. ፷፯፡፲፮። ክርስቶስም በራሱ ሰዎች ሁሉ ለጸሎት፣ ለምስጋናና ለአምልኮ ዘወትር ሊሰባሰቡበት የሚገባ መሆኑን ሲያስገነዝብ "ቤትየሰ ቤተ ጸሎት ይሰመይ ለአሕዛብ = #ቤቴ ለሰዎች ሁሉ የጸሎት ቤት ይባላል።” ብሏል። ኢሳ. ፶፮፡፯ ይህም ቤት የተመሠረተው በክርስቶስ ደም ሲሆን መሠረቱና ጕልላቱ ክርስቶስ ነው። የሰላም አምላክ ክርስቶስም ብቻ ይመለክበታል። ከክርስቶስ ጋር የሚመለክ ደባል አምላክም ኖሮበት አያውቅም፤ የለምም፤ አይኖርምም። ይህ ቤት አንድነትና ኅብረት፣ መስማማትና መግባባት፣ ፍቅርና ሰላም ለዓለም ይታወጁበታል። በዓለም ላይ ስላለው ሰው ስለ ሆነው ሁሉና ስለ ዓለም መሪዎች ድኅነትና በጎነትም ዘወትር ይጸለይበታል።  በዚህ ቅዱስ ስፍራ ውስጥም ጥላቻ፣ መለያየት፣ መወነጃጀል፣ መካሰስ፣ መገዳደል ወንበር የላቸውም። ክፍል ፪  ይቀጥላል...

፩.፩.ግእዝ ጉባኤ ቃና • እስኩ ቅረቡ ዘአልብክሙ ኵነኔ፥ • እስመ ለሕይወት ተሦዐ መሥዋዕተ መድሓኒት ቅኔ። ፩.፪. ግእዝ ጉባኤ ቃና • ልቡ ለጾም መርድአ ድካም ዐንበዘ፥ • እስመ በአርብዓ ዓመት መልክዐ ኢየሱስ አሐዘ። ፪.፩. ዕዝል ጉባኤ ቃና • ከሃሊ ከሃሊ ተትሒተኪ ግብረ እዴኪ ወዐሊ፥ • ከሃሊ ከሐዲ ትርጓሜ ዘይቤለኪ ታቅልሊ። ፪.፪.ዕዝል ጉባኤ ቃና • ለጸዊመ ጾም አክኒጦስ አርዳኢሁ ምሳሌያተ ጽድቅ ኵሉ፥ • ሥጋ ኢነሥአ ፈጣሪ ወኢተዋሐደ ይብሉ። (ሃይ. አበ. ፳፱) ፫. ዘአምላኪየ • ለኵሉ ዕሩየ በረከትየ ትሩፍ፥ • ዘይብል መድሐኔ ዓለም ብእሲ ገዚፍ፥ • ሥጋሁ ያቀድም ወቃሉ ዘኢየሐልፍ እምአፍ። ፬. ሚ በዝሑ • መቤዛዌ ሱቱኤል ጾም መቤዛዌ ሙሴ ምልክዓም መቤዛዌ ራጉኤል መቤዛዊ፥ • ተኖላዌ አዳም አዳም ተኖላዌ አቤል ተኖላዊ፥ • መድሕን መድሕን መድሕን መድሕን ዘበደዌ ሥጋ ይደዊ። ፭. ዋይዜማ • ቴዎዳስ ጸናጽል ውስተ ቤቴል ግብጽ ኀበ ኀበ ያተሉ ሰብአ፥ • ተንሥአ በአዕብዮ ርእሱ ወፍጡነ ጠፍአ፥ • ወይሁዳኒ ከበሮ ምስለ እሊኣሁ ተንሥአ፥ • ባሕቱ፦ ግብተ ሞተ ወመሬተ ገብአ፥ • ወበዜማ ገሊላ ተኀጥአ። (ግብ. ፭፡፴፮-፴፯) ፮. መስኮት ዋይዜማ • መሓዛተ ሱቱኤል እለ ሐሙ እንተ ሐሙ ሐም ጽድቀ ተባሕትዎ ታሕማ፥ • እንተ ሐመ፦ እመ ወልድ አዕረፈት በብዝሐ ጻማ፥ • ለባሕቲታ ንስቲተ ሐሚማ። ፯. ሐፂር ዋይዜማ • አዋልድ ምግባራተ ጽድቅ ዘቆማ ዘቆማ፥ • ወራዙተ ሙሴ ዘቆሙ ሱባዔያተ ጽድቅ ተሠይማ። • (አዋልድ ምግባራተ ጽድቅ ዘቆማ ዘቆማ) ፰. ሥላሴ • ኵልነ ንትዌለጥ ከመ ቅጽበተ ዐይን በደሓሪ እስመ ከመ ትካት ተሰብከ ነገሩ በኢሳይያስ ስብሐት፥ • ተውሕጠ ዘተሐየለነ መናፍቅ ሞት፥ (ኢሳ. ፳፭፡፰፤ ፩ ቆሮ. ፲፭፡፶፩-፶፮) • ወነዋ ተሰጥመ ተሰጥሞ ውስተ ባሕረ ጽድቅ ሙአት፥ • ወበብርተ ጳውሎስ ሃይማኖት፥ • ቀኖቱ ለሞት በትረ ሓጢአት፥ • ተቀጥቀጠ ወነግሠ ሕይወት። ፱. ዘይእዜ • ኤራቅሊስ መጥሊጎን ሄሬኔዎስ ፊልክስ ቆዝሞስ አክርስቶዶሎስ ከዐወ፥ • ማየ ድያድርስ ወትዮድርስ እምሐቢብ ምክረ ናጣሊስ ለበወ ለበወ፥ • በዐይነ ቡራኬ ብሩህ ደቂቀ ወአበወ፥ • ወልታ ብርሃናት አርክቦስ አመ ተወልተወ፥ • ርእዮ ይሬኢ ባሕረ ቆሮንቶስ ተወርወ። • (ወልታ ብርሃናት አርክቦስ አመ ተወልተወ፥) ፲. ሣህልከ • ድንቃዌ ወይንየ በተኳንኖ፥ • ፍሬሁ ኢየሀብ እመ ፈጸመ ዘመኖ፥ • ከመ ይትሐብለይዎ ነኪራን ለልየ በማዕፀደ ቅኔ እነሥት ጸቈኖ። (ኢሳ. ፭፡፭) ፲፩. ሐፂር ሣህልከ • ሕየው ለነ ዘለዓለም፥ • ምስጢረ ቅኔ ሕያው እስመ ዲበ ኵሉ ሥዩም። • (ሕየው ለነ ዘለዓለም።) ፲፪. መወድስ • ይቤ ዳዊት ጸናጽለ ወርቅ ለነገር ላዕሌየ አርእስተ ዚኣሆሙ የሐውሱ፥ (መዝ. ፻፰፡፳፭) • አብትረ ማኅሌት ረቂቅ ጽሉኣንየ ዘብእሱ፥ • ወመልዕልተ ዕፅ ተሰቂሎ አኪጦፌል ማኅሌተ ሱራፊ ተሐንቀ በርእሱ፤ (፪ ሳሙ. ፲፯፡፳፫) • በምክረ ኵሲ ወርሐ ጸዊም ሶበ ተወለጠት ምክሩ አምጣነ ተጽዕረት ነፍሱ። • ይቤሎሂ ጾመ እግዚእ እግዚአ ነቢይ ኢያሱ፥ • ለአካዝ በትረ ወርቅ እንተ ልብሰ ወርቅ ዲበ ሕዋሱ፥ • ተዐቀብኬ ወአርምም እንዘ ውስተ መቅደስ ታንሶሱ፥ • ወኢትፍራሕ እምክልኤቱ ትንታጋተ ዕፀው ዘይጠይሱ። (ኢሳ. ፯፡፫-፬) ፲፫. ኵልክሙ መወድስ • በብሂለ ላዕል ወታሕት እምድሕረ ፈጸመ መዋዕሊሁ ማኅሌተ ብዙሐ ዘአበሰ፥ • ጸናጽለ ወርቅ ሓጥእ ሓጣውኢሁ ደምሰሰ፤ • አኮኑ እምቅድመ ሞቱ ገዳመ ሐዊሮ በገዳም መንኰሰ፥ • ወውእቱሰ በትረ ማሕሌት ወልዱ ዘበኵር ርስተ ወላዲሁ ወረሰ፥ • ሕዳጠሂ ይዘርእ እንዘ የሐፍስ ሐፊሰ፥ • ገራሕቶ ምስጢረ ቅኔ ድሕረ አቀምጠወ ወሐረሰ፥ (ኢሳ. ፳፰፡፳፭) • ቃላተ መጻሕፍት ከሙነ ወአለንሰ፥ • ሥርናየ ወሰገመ ጉባኤ ቃና ወመወድሰ፥ • ፍሡሐ ይዕርር ወያስተጋብእ ሐዲሰ። • (ሥርናየ ወሰገመ ጉባኤ ቃና ወመወድሰ፥) ፲፬. ሐፂር ኵልክሙ መወድስ • ኵሎ አሚረ ከመ ንጸውዕ ስመከ፥ • ቅኔ ያሬድ እግዚአብሔር ሚጠነ ኀቤከ። (መዝ. ፸፱፡፫) ✅ ተዘረፈ፦ በያሬድ ዘርአ-ቡሩክ ✅ የካቲት ፲፰/፳፻፲፰ ዓ/ም https://t.me/kineyared

Repost from N/a
፩.፩.ግእዝ ጉባኤ ቃና • እስኩ ቅረቡ ዘአልብክሙ ኵነኔ፥ • እስመ ለሕይወት ተሦዐ መሥዋዕተ መድሓኒት ቅኔ። ፩.፪. ግእዝ ጉባኤ ቃና • ልቡ ለጾም መርድአ ድካም ዐንበዘ፥ • እስመ በአርብዓ ዓመት መልክዐ ኢየሱስ አሐዘ። ፪.፩. ዕዝል ጉባኤ ቃና • ከሃሊ ከሃሊ ተትሒተኪ ግብረ እዴኪ ወዐሊ፥ • ከሃሊ ከሓዲ ትርጓሜ ዘይቤለኪ ታቅልሊ። ፪.፪.ዕዝል ጉባኤ ቃና • ለጸዊመ ጾም አክኒጦስ አርዳኢሁ ምሳሌያተ ጽድቅ ኵሉ፥ • ሥጋ ኢነሥአ ፈጣሪ ወኢተዋሐደ ይብሉ። (ሃይ. አበ. ፳፱) ፫. ዘአምላኪየ • ለኵሉ ዕሩየ በረከትየ ትሩፍ፥ • ዘይብል መድሐኔ ዓለም ብእሲ ገዚፍ፥ • ሥጋሁ ያቀድም ወቃሉ ዘኢየሐልፍ እምአፍ። ፬. ሚ በዝሑ • መቤዛዌ ሱቱኤል ጾም መቤዛዌ ሙሴ ምልክዓም መቤዛዌ ራጉኤል መቤዛዊ፥ • ተኖላዌ አዳም አዳም ተኖላዌ አቤል ተኖላዊ፥ • መድሕን መድሕን መድሕን መድሕን ዘበደዌ ሥጋ ይደዊ። ፭. ዋይዜማ • ቴዎዳስ ጸናጽል ውስተ ቤቴል ግብጽ ኀበ ኀበ ያተሉ ሰብአ፥ • ተንሥአ በአዕብዮ ርእሱ ወፍጡነ ጠፍአ፥ • ወይሁዳኒ ከበሮ ምስለ እሊኣሁ ተንሥአ፥ • ባሕቱ፦ ግብተ ሞተ ወመሬተ ገብአ፥ • ወበዜማ ገሊላ ተኀጥአ። (ግብ. ፭፡፴፮-፴፯) ፮. መስኮት ዋይዜማ • መሓዛተ ሱቱኤል እለ ሐሙ እንተ ሐሙ ሐም ጽድቀ ተባሕትዎ ታሕማ፥ • እንተ ሐመ፦ እመ ወልድ አዕረፈት በብዝሐ ጻማ፥ • ለባሕቲታ ንስቲተ ሐሚማ። ፯. ሐፂር ዋይዜማ • አዋልድ ምግባራተ ጽድቅ ዘቆማ ዘቆማ፥ • ወራዙተ ሙሴ ዘቆሙ ሱባዔያተ ጽድቅ ተሠይማ። • (አዋልድ ምግባራተ ጽድቅ ዘቆማ ዘቆማ) ፰. ሥላሴ • ኵልነ ንትዌለጥ ከመ ቅጽበተ ዐይን በደሓሪ እስመ ከመ ትካት ተሰብከ ነገሩ በኢሳይያስ ስብሐት፥ • ተውሕጠ ዘተሐየለነ መናፍቅ ሞት፥  (ኢሳ. ፳፭፡፰፤ ፩ ቆሮ. ፲፭፡፶፩-፶፮) • ወነዋ ተሰጥመ ተሰጥሞ ውስተ ባሕረ ጽድቅ ሙአት፥ • ወበብርተ ጳውሎስ ሃይማኖት፥ • ቀኖቱ ለሞት በትረ ሓጢአት፥ • ተቀጥቀጠ ወነግሠ ሕይወት። ፱. ዘይእዜ • ኤራቅሊስ መጥሊጎን ሄሬኔዎስ ፊልክስ ቆዝሞስ አክርስቶዶሎስ ከዐወ፥ • ማየ ድያድርስ ወትዮድርስ እምሐቢብ ምክረ ናጣሊስ ለበወ ለበወ፥ • በዐይነ ቡራኬ ብሩህ ደቂቀ ወአበወ፥ • ወልታ ብርሃናት አርክቦስ አመ ተወልተወ፥ • ርእዮ ይሬኢ ባሕረ ቆሮንቶስ ተወርወ። • (ወልታ ብርሃናት አርክቦስ አመ ተወልተወ፥) ፲. ሣህልከ • ድንቃዌ ወይንየ በተኳንኖ፥ • ፍሬሁ ኢየሀብ እመ ፈጸመ ዘመኖ፥ • ከመ ይትሐብለይዎ ነኪራን ለልየ በማዕፀደ ቅኔ እነሥት ጸቈኖ። (ኢሳ. ፭፡፭) ፲፩. ሐፂር ሣህልከ • ሕየው ለነ ዘለዓለም፥ • ምስጢረ ቅኔ ሕያው እስመ ዲበ ኵሉ ሥዩም። • (ሕየው ለነ ዘለዓለም።) ፲፪. መወድስ • ይቤ ዳዊት ጸናጽለ ወርቅ ለነገር ላዕሌየ  አርእስተ ዚኣሆሙ የሐውሱ፥ (መዝ. ፻፰፡፳፭) • አብትረ ማኅሌት ረቂቅ ጽሉኣንየ ዘብእሱ፥ • ወመልዕልተ ዕፅ ተሰቂሎ አኪጦፌል ማኅሌተ ሱራፊ ተሐንቀ በርእሱ፤ (፪ ሳሙ. ፲፯፡፳፫) • በምክረ ኵሲ ወርሐ ጸዊም ሶበ ተወለጠት ምክሩ አምጣነ ተጽዕረት ነፍሱ። • ይቤሎሂ ጾመ እግዚእ እግዚአ ነቢይ ኢያሱ፥ • ለአካዝ በትረ ወርቅ እንተ ልብሰ ወርቅ ዲበ ሕዋሱ፥ • ተዐቀብኬ ወአርምም እንዘ ውስተ መቅደስ ታንሶሱ፥ • ወኢትፍራሕ እምክልኤቱ ትንታጋተ ዕፀው ዘይጠይሱ። (ኢሳ. ፯፡፫-፬) ፲፫. ኵልክሙ መወድስ • በብሂለ ላዕል ወታሕት እምድሕረ ፈጸመ መዋዕሊሁ ማሕሌተ ብዙሐ ዘአበሰ፥ • ጸናጽለ ወርቅ ሓጥእ ሓጣውኢሁ ደምሰሰ፤ • አኮኑ እምቅድመ ሞቱ ገዳመ ሐዊሮ በገዳም መንኰሰ፥ • ወውእቱሰ በትረ ማሕሌት ወልዱ ዘበኵር ርስተ ወላዲሁ ወረሰ፥ • ሕዳጠሂ ይዘርእ እንዘ የሐፍስ ሐፊሰ፥ • ገራሕቶ ምስጢረ ቅኔ ድሕረ አቀምጠወ ወሐረሰ፥ (ኢሳ. ፳፰፡፳፭) • ቃላተ መጻሕፍት ከሙነ ወአለንሰ፥ • ሥርናየ ወሰገመ ጉባኤ ቃና ወመወድሰ፥ • ፍሡሐ ይዕርር ወያስተጋብእ ሐዲሰ። • (ሥርናየ ወሰገመ ጉባኤ ቃና ወመወድሰ፥) ፲፬. ሐፂር ኵልክሙ መወድስ • ኵሎ አሚረ ከመ ንጸውዕ ስመከ፥ • ቅኔ ያሬድ እግዚአብሔር ሚጠነ ኀቤከ። (መዝ. ፸፱፡፫) ✅ ተዘረፈ፦ በያሬድ ዘርአ-ቡሩክ https://t.me/kineyared