የህፃናት ጉልበት ብዝበዛ
***
በሰዎች የመነገድ ድርጊት ህገ-ወጥ የሰዎች ዝውውርን ለመነገድና ለብዝበዛ አላማ በማከናወን በአለም አቀፍ ደረጃ በሰው ልጆች የመኖር ህልውና ላይ ከፍተኛ አደጋን የጋረጠ ተግባር ነው፡፡ በሰዎች መነገድ በሀገር ውስጥ ወይም ከሀገር ውጪ ሰዎችን በማዘዋወር ሊፈፀም ይችላል፡፡ ይህ ተግባር በተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ላይ በተለያየ መንገድ እና ምክንያት ሊፈፀም የሚችል ሲሆን ለድርጊቱ በብዛት ተጋላጭ ከሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ውስጥ ሴቶች እና ህፃናት ይገኙበታል፡፡
የተባበሩት መንግስታት የህፃናት መብቶች ስምምነት አንቀፅ 1 ህፃን ማለት ማንኛውም ዕድሜው ከ18 ዓመት በታች የሆነ ሰው ማለት ነው ይላል። የሀገራችንን ህጎች ስንመለከትም በተሻሻለው የፌደራል የቤተሰብ ቤተሰብ ህግ አንቀፅ 215 መሰረት ህፃን በማለት ትርጉም ባይሰጥም ለአካለ መጠን ያልደረሰ ሰው ፆታ ሳይለይ ማንኛውም እድሜው 18 ዓመት ያልሞላው ልጅ ማለት እንደሆነ ያመለክታል። በተጨማሪም በሰው የመነገድና ሰውን በህገ-ወጥ መንገድ ድንበር የማሻገር ወንጀልን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በወጣው አዋጅ ቁጥር 1178/12 አንቀፅ 2(10) መሰረት ህፃን ማለት ዕድሜው ከ18 ዓመት በታች የሆነ ማንኛውም ሰው ነው፡፡
ህፃናት በሀገር ውስጥ እንዲሁም ከሀገር ውጪ በሰዎች የመነገድ ድርጊት በመጋለጥ ለከፍተኛ ጉዳት ሲዳረጉ ይስተዋላል፡፡ ህፃናትን በሰዎች የመነገድ ድርጊት ተጋላጭ የሚያደርጓቸው የተለያዩ ምክንያች ያሉ ሲሆን እድሜያቸው ውሳኔ የመወሰን አቅማቸው ላይ ከሚፈጥረው ተፅዕኖ በተጓዳኝ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች እንደ ዋና መንስኤ ሊወሰዱ ይችላሉ፡፡ በሰዎች የመነገድ ድርጊት የተዳረጉ ህፃናት ከሚደርሱባቸው ጉዳቶች መካከል የጉልበት ብዝበዛ ዋንኛው ነው፡፡ ይህም ህፃናትን ለከፋ የአካል እና የስነ-ልቦና ጉዳት ይዳርጋቸዋል፡፡
በአለም አቀፍ ስምምነቶች፣ አህጉራዊ ስምምነቶች እንዲሁም በአገራችን የህግ ማዕቀፍ የህፃናት መብቶች መከበር እንዳለባቸው የተደነገገ ቢሆንም የህግ ድንጋጌዎችን በሚጥስ መልኩ ህፃናት ተጎጂ ሆነው እናገኛለን፡፡ በመሆኑም በህፃናት የመነገድ ድርጊትና የህፃናት ጉልበት ብዝበዛ ምክንያት በህጻናት ላይ የሚደርሱ ጉዳቶችን ለመከላከል፣ ለመቆጣጠር እንዲሁም ጉዳት አድራሾችን ለመቅጣት የተለያዩ አለም አቀፍ ስምምነቶች እና ህጎች በስራ ላይ ውለዋል፡፡
ይህ የንቃተ ህግ ትምህርታዊ ፅሑፍ በሁለት ክፍል የቀረበ ሲሆን የመጀመሪያው ክፍል ምንነት በአጠቃላይ፣ ህፃናትን ለሰዎች የመነገድ ድርጊትና ጉልበት ብዝበዛ ተጋላጭ የሚያደርጓቸው መንስኤዎች እና የህፃናት ጉልበት ብዝበዛ አይነቶችና የሚያስከትሉት ጉዳት እንመለከታለን፡፡ በክፍል ሁለት በህፃናት የመነገድ ድርጊትና የህፃናት ጉልበት ብዝበዛ በኢትዮጵያ ህጎች ያለው ሽፋን ይዳሰሳል፡፡
• በሰዎች የመነገድ ድርጊት ምንነት በአጠቃላይ
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት በሰዎች የመነገድ ድርጊት በተለይም በሴቶችና ሕጻናት የመነገድ ድርጊት ለመከላከል፣ ለመቆጣጠርና ወንጀል ፈጻሚዎችን ለመቅጣት በወጣው እና ሀገራችን ባፀደቀችው ፕሮቶኮል አንቀፅ 3 መሰረት በሰዎች የመነገድ ድርጊት የሚከተለውን ትርጉም ይዞ እናገኘዋለን፡፡
"በሰዎች የመነገድ ድርጊት ማለት ብዝበዛን አላማ በማድረግ ዛቻን፣ ሀይልን ወይም ሌላ የማስገደጃ ዘዴ በመጠቀም፣ በማገት፣ በመጥለፍ፣ በተንኮል፣ በማታለል ወይም የተስፋ ቃል በመስጠት፣ ሥልጣንን አላግባብ በመጠቀም፣ የሰዎችን ለጥቃት ተጋላጭነት በመጠቀም ወይም ስለሌላው ኃላፊነት ያለበትን ሰው ፈቃድ ለማግኘት መደለያ ወይም ጥቅም በመስጠት ወይም በመቀበል ሰዎችን መመልመል፣ ማጓጓዝ፣ ማዘዋወር፣ ማስጠለል ወይም መቀበል ሲሆን የብዝበዛ ተግባር ቢያንስ በሌሎች ሰዎች ዝሙት አዳሪነት መጠቀም ወይም ሌላ ማንኛውም አይነት ወሲባዊ ብዝበዛን፤ የጉልበት ብዝበዛ፣ የግዳጅ ሥራ ወይም አገልጋይነት፤ ባርነት ወይም ባርነት መሰል ተግባር፤ የሰው ልጅን አካል ማውጣት ወይም መውሰድን ያካትታል፡፡" ስለሆነም እነዚህ ድርጊቶች እድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች በሆኑ ህፃናት ላይ የተፈፀሙ እንደሆነ በህፃናት የመነገድ ድርጊት ይሆናል ማለት ነው፡፡
በዚህ መግለጫ ውስጥ ሶስት መሰረታዊ ፍሬ ነገሮች ማለትም ተግባር (The Act, What is done)፣ አደራረግ/ዘዴ (The Means, How it is done) እና አላማ (The Purpose, Why it is done) መሟላት ያለባቸው መሆኑን መገንዘብ ይቻላል። በተጨማሪም ከብዝበዛ ተግባራት ውስጥ የጉልበት ብዝበዛ በፕሮቶኮሉ የተካተተ በመሆኑ የህፃናት ጉልበት ብዝበዛ በዚሁ የሚሸፈን መሆኑን እንገነዘባለን፡፡ በመሆኑም በሰዎች የመነገድ ድርጊት እና የጉልበት ብዝበዛ የማይነጣጠሉ ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ እርግጥ የብዝበዛው አይነት እንደ ተጎጂው አይነት የሚለያይ ቢሆንም ማለትም በሴቶች ላይ የሚደረገው ብዝበዛ እና በወንዶች ወይም በህፃናት ላይ የሚደረገው ብዝበዛ ሊለያይ ቢችልም ድርጊቱ ግን በሰው ልጆች ሰብዓዊ መብት ላይ ጉዳትን ማስከተሉ አጠያያቂ አይደለም፡፡
በፕሮቶኮሉ እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ፍሬ ነገሮች መቀመጣቸው አንድ ድርጊት በሰዎች የመነገድ ድርጊት ውስጥ ይወድቃል ወይስ አይወድቅም የሚለውን ለመወሰን የአለም ሀገራት ወጥነት ያለው እና ስምምነት የተደረሰበት (consistency and consensus) መለኪያ እንዲጠቀሙ የሚያደርጋቸው ሲሆን ይህንም በህጎቻቸው ውስጥ እንዲያካትቱ ይረዳቸዋል፡፡ የፕሮቶኮሉ አንቀፅ 5 በፕሮቶኮሉ አንቀፅ 3 ስር የተቀመጡትን ድርጊቶች ሀገራት በህጎቻቸው ውስጥ በወንጀል የሚያስቀጡ ተግባራት እንደሆኑ (criminalized in domestic legislation) መደንገግ እንዳለባቸው ያስቀምጣል፡፡ ይህንንም ሲያደርጉ ከሀገራቸው ነባራዊ ሁኔታ ጋር በሚስማማ መልኩ መሆን አለበት፡፡ ምክንያቱም ለተግባራዊነቱ ጠቀሜታ ስለሚኖረው ነው፡፡
በሌላ በኩል ከሰዎች የመነገድ ድርጊት ጋር የሚነሳው ጉዳይ የፍቃድ ወይም የስምምነት (consent) ጉዳይ ነው፡፡ በፕሮቶኮሉ አንቀፅ 3/ለ/ ስር እንደተደነገገው ለመነገድ ድርጊት ስምምነቱ የተገኘው በዛቻ፣ በሀይል፣ በተንኮል፣ በማታለል ወይም የተስፋ ቃል በመስጠት፣ ሥልጣንን አላግባብ በመጠቀም፣ የሰዎችን ለጥቃት ተጋላጭነት በመጠቀም ወይም ሌሎች የተከለከሉ መንገዶችን በመጠቀም ከሆነ ተገጂው ተስማምቷል ወይም ፍቃዱን ሰጥቷል ለማለት አይቻልም፡፡ ስለሆነም የበሰዎች የመነገድ ድርጊት ፈፃሚዎች የተጎጂውን ፍቃደኝነት ከህግ ተጠያቂነት ለማምለጥ እንደመከላከያ ሊያነሱት አይችሉም፡፡ ህፃናትን በተመለከተ ደግሞ ከላይ የተጠቀሱት መንገዶች (The Means) ተግባራዊ ባይደረጉም በህፃናት የመነገድ ድርጊት ከተከናወነ የወንጀል ድርጊቱ ተፈፀመ ማለት ይቻላል፡፡
በሁለቱም ጊዜ ማለትም አዋቂዎች ፍቃዳቸውን በተለያዩ ተፅዕኖ ውስጥ ሲሰጡ እንዲሁም ህፃናት በተፅዕኖም ይሁን ያለተዕፅኖ በሰዎች የመነገድ ድርጊት ሲጋለጡ ስምምነታቸውን ሰጥተዋል ማለት አይቻልም፡፡ ምክንያቱም የሰው ልጅ በምንም አይነት ሁኔታ ለብዝበዛ ነፃ ፍቃዱን ይሰጣል ተብሎ አይታሰብም፡፡ በዚህ ጊዜ የአዋቂዎች ፍቃድ ተገቢ ባልሆነ መንገድ እንደተገኘ፣ ህፃናት ደግሞ ተጋላጭ (vulnerable) በመሆናቸው ፍቃድ መስጠት እንደማይችሉ መገንዘብ ይቻላል፡፡