HAILE GEBRIEL - በማለዳ ንቁ
Ir al canal en Telegram
❤️ ቅዱሳን አባቶች እንዲህ ይላሉ **ጸጋ ያለምስጋና አያድግም ይላሉ** እግዚአብሔር ሆይ ስለሆነልኝ፣ ክፉውንም ከእኔና ከቤተሰቦቼ ስላራክልኝ 👏 አመሰግንሃለሁ ❤️ 👇👇👇 http://www.youtube.com/@haileG2239
Mostrar más2 277
Suscriptores
-124 horas
+107 días
+3530 días
Archivo de publicaciones
«ወደ ቤተክርስቲያን መጥተህ ታከም»
❖ በክርስትና ጸንተህ መኖር አለመኖርህን ለማረጋገጥ የሚከተሉትን ጥያቄዎች ራስህን ጠይቅ
፩. ጠዋትና ማታ በቋሚነት ትጸልያለህ?
፪. ሳታቋርጥ በቤተክርስቲያን የጋራ ጸሎት ትሳተፋለህ?
፫. በመምህረ ንስሐ በመመራት በቅዱስ ቍርባንና በሌሎች የቤተክርስቲያን ምሥጢራት ትሳተፋለህ?
፬. በቤተክርስቲያን ግጻዌ መሠረት ትጾማለህ? በተሠራው ቀኖና መሠረት በዓላትን ታከብራለህ? በአጥቢያ አገልግሎት ትታዘዛለህ?
፭. ኃጢአተኛነትህን አምነህ ራስህን በመርመር ለጸሎት በቆምክበትም ሆነ በሁሉ ቦታ የአምላክን ምሕረት ትጠይቃለህ? በሌሎች ከመፍረድ ራስህን ታቅባለህ?
፮. ዘመኑ ካመጣው ወከባ፣ አልጠግብ ባይነት፣ ያጡትን እያሰቡ ባገኙት አለመደሰት ከኢአማንያን የሚለይህ የተረጋጋ ሕይወት አለህ?
፯. በእጅህ ላይ ባለውና እግዚአበሔርን በሚያስደስተው ሥራ ታተኩራለህ ወይንስ በማይጨበጠውና ምኞታዊ በሆነ አሳብ ትዳክራለህ?
፰. በቃለ እግዚአብሔር በመመራት በቅዱሳን ምሳሌነት ራስን መግራትና መግዛት ላይ ታተኩራለህ ወይስ ፍተወታትን እያዳመጥህ ራስህን በማርካት ትጠመዳለህ?
፱. ሌሎችን በመርዳት ትደሰታለህ ወይስ በራስ ወዳድነት ሮጠህ አሸናፊ ለመሆን ትፈልጋለህ?
፲. ከሌሎች በመማር እምነትህን ታጸናለህ፣ የግብረ ሠናይና መልካም ሥነ ምግባር አርአያ ትሆናለህ? ሌሎችን ለመርዳት ትሳተፋለህ ወይስ ከዓለማውያን ጋር ጊዜህን በጭፈራና በዋዛ ፈዛዛ ታሳልፋለህ?
፲፩. መጽሐፍ ቅዱስን፣ ስንክሳርና ገድላትን ለማንበብ ቋሚ ጊዜ አለህ ወይስ በማይጠቅም መረጃ ብቻ ትጠመዳለህ?
፲፪. ከዘረኝነት ደዌ አምልጠህ የሰው ልጅን ሁሉ እኩል የምትወድበት ልብ አለህ ወይንስ ከአራዊት በከፋ ጭካኔ በጎራ ተሰልፈው ከሚናከሱት ጋር ሆነህ ራስህን ትወጋለህ?
፲፫. የሕግ ሁሉ ፍጻሜ ሰውንና እግዚአብሔርን መውደድ መሆኑን ተረድተሃል? ወይስ ለአንተ የሚስማማህን የግል እምነት ፈጥረህ ከአንዲት ቤተክርስቲያን ተለይተሃል?
፲፬. ፍቅርን፣ ተስፋን፣ እምነትን መያዝ አለመያዝህን ራስህን ትጠይቃለህ? ተስፋ ቢስነት፣ ኑፋቄና ክህደት ወርሶህ በቍሳዊ ሀብት የምትተማመን ከሆንህ ፈጥነህ ወደ ቤተክርስቲያን ተመልሰህ ታከም::
#Subscribe #Like #Share
👇👇👇👇
www.youtube.com/@haileG2239
www.youtube.com/@pagumentube
ውዶች መዝሙር ተጋበዙልኝ! ሰላም እንዴት ናችሁ ሁሉ ሰላም ነው። ጾሙ ጸሎቱ ስግደቱ እንዴት ይዟችኋል። አሁንም እንበርታ እግዚአብሔር አምላካችን ሀገራችንን ሰላም ያድርግልን! 🙏🙏🙏
«የምታዳምጡ ብቻ አትሁኑ!»
◈ ተወዳጆች ሆይ የምታደምጡ ብቻ አትኹኑ፤ ያስተማርኳችሁን ትምህርት ለሌሎችም በማስተላለፍ መምህራን ትኾኑ ዘንድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረ፦ “አንዱ ሌላውን ያንጸው” (1ኛ ተሰ 5፥11) ዳግመኛም “በፍርሐትና በመንቀጥቀጥም የራሳችኁን መዳን ፈጽሙ” ብሎ እንደ ተናገረው በስሕተት ጐዳና ያሉትን ታድኑ ዘንድ መረባችሁን ጣሉ ብዬ እማፀናችኋለሁ። (ፊልጵ 2፥12)
◈ ይህን ስታደርጉ ቤተክርስቲያን ከመቼውም ጊዜ በላይ ትሰፋለች፤ እኛም ይህን ዐይተን እጅግ ደስ እንሰኝባችኋለን፤ እናንተም ለወንድሞቻችሁ፣ ለእኅቶቻችሁ ባሳያችሁት ፍቅር በሰማያት ዘንድ ታላቅ ማዕረግና ክብር ታገኛላችሁ። እንደምታውቁት የእግዚአብሔር ፈቃድ እያንዳንዱ ክርስቲያን ስለ ራሱ መዳን ብቻ እንዲያስብ አይደለም፤ ወንድሙንም እንዲያንጽ ነው እንጂ፤ ሲያንጸውም በቃል ብቻ አይደለም፤ በተግባርም ጭምር እንጂ፤ የእግዚአብሔር ፈቃዱ እያንዳንዳችን በአኗኗራችን ክርስቶስን መስለን ታምነን እንድንኖርና ፍጥረት ኹሉ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንዲገቡ ማድረግ ነው፡፡
◈ ይኸውም ሰዎች ከምንናገረው በላይ የምንኖረውን ስለሚያምኑና ስለሚማርካቸው ነው፤ ብዙውን ጊዜ በተዋቡ ቃላት ስለ ይቅርታ ብንናገር ነገር ግን በሕይወታችን እጅግ ቂመኞችና ይቅርታን የሚቀበል ልብ የሌለን ከኾነ ቃላችንና ሕይወታችን ስላልተስማማላቸው ሰዎች የምንለውን ነገር አያምኑንም፡፡ የምንናገረውንና የምናስተምረውን የምንኖረው ከኾነ ግን ያምኑናል፤ እውነቱን ለመቀበልም አይቸገሩም፤ በቃል መነገሩ፣ በልብ መታሰቡ፣ በቅዱሳት መጻሕፍት መዘገቡ ከፍ ከፍ ይበልና ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንዲህ ያለውን ክርስቲያን እንዲህ ሲል አመስግኖታል። “የሚያደርግም የሚያስተምርም እርሱ ንዑድ ክቡር ነው። (ማቴ 5፥19)
◈ እንግዲህ ጌታችን ሲያስተምር በተግባር የሚሰጠውን ትምህርት በቃል ከሚሰጠው ትምህርት ይልቅ እንዳስቀደመው ታስተውላላችሁን? አያችሁ! ከተግባራችን በኋላ ቃላችን ባይከተል እንኳን ሰዎችን ወደ እውነት (ኢየሱስ) ለማምጣት በቂ ነው፡፡ የቅድስና ሕይወት ለፈለገውና ለመረጠው ሁሉ ይቻላል፤ አሁን ካለንበት ደረጃ ከፍ ብለን የእግዚአብሔር ጸጋ በየልባችን እንዲሠራ እግዚአብሔር ፈቃዱ ነው፤ የእግዚአብሔር መንፈስ ነፍስን ወደ እግዚአብሔር በመምራት ልዩ ሀብቶችን በመስጠትና በረድኤት ከክርስቲያኖች ጋር ይሠራል።
◈ ቅዱሳን የሠሩት የእግዚአብሔር መንፈስ በውስጣቸው የሠራውን ነው፤ ታሪካቸውን ስታስብ በሕይወታቸው ውስጥ እግዚአብሔር እንዴት እንደሠራና በእነርሱ እንደተመሠገነ አስተውለሃል? የእነዚህ ሁሉ የጀግንነት ሥራዎቻቸው ምክንያትስ ገብቶሃል? በሚሠሩት ሥራ ሁሉ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ጠንካራ ሕብረት እንደነበራቸው አትረዳም? (2ቆሮ 13፥14)
አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ
#Subscribe #Like #Share
👇👇👇👇
www.youtube.com/@haileG2239
www.youtube.com/@pagumentube
«በሰይጣን አናስወስደው!»
◈ እግዚአብሔር በፍጥረት ጊዜ ለሁላችንም ከሰጠን መሠረታዊ ነገሮች ውስጥ አንዱ ነጻ ነት ነው። በዚህ ስጦታ አማካኝነት ሰጪውን እግዚአብሔርን ምን ያህል ቸር እንደ ኾነ እናጣጥምበታለን። በተለይ በሐዲስ ኪዳን ያገኘነውን ነጻነት በተመለከተ ዮስጢኖስ እንዲህ ይላል “በእውነታው አንድ ነጻነት ብቻ ነው ያለው። ይኸውም ከኃጢአት፣ ከክፋትና ከዲያብሎስ ነጻ ያደረገን የክርስቶስ ቅዱስ ነጻነት ነው። በዚህ ከእግዚአብሔር ጋር እንገናኛለን። ሌሎች ነጻነቶች በሙሉ እውነት የሚመስሉ፣ የተሳሳቱ፣ በእርግጥም በአጠቃላይ ባርነቶች ናቸው" (St. Justin Popovich, Ascetical and
Theological Chapters, II.36) አንድ ሰው ከእግዚአብሔር ተለይቶ የወደደውን ለማድረግ በመፈለጉና አንዳንዴም ተሳክቶለት በማድረጉ ምክንያት የተሰጠውን ስጦታ ተጠቅሟል ማለት አይደለም። ነጻነታችንን መልካም የኾነውን ለመምረጥ ብቻ የማንጠቀም ከኾነ እንጎዳበታለን። እግዚአብሔር ነጻነትን የሰጠን ከልባችን እርሱን ፈልገን እንድናመልከው ስለሚፈልግ ነው። ክርስቲያን ማለት ክርስቶስን የሚመርጥና ፈቃዱን በማድረግ ደስ የሚሰኝ ማለት ነው። ከእውነተኛው ነጻነት እውነተኛ ደስታ ይመነጫል፤ ይህ ደስታ ደግሞ የእኛ ብቻ ሳይኾን የሰማይ መላእክትም ደስታ ነው።
◈ ፍጹም የኾነውን ነጻነት የምናገኘው በፍቅረ እግዚአብሔርና በፍቅረ ቢጽ ውስጥ ነው። ፍቅር የሌለው ሰው ነጻነት የለውም። እግዚአብሔርንና ሰውን የምንወድ ከኾነ ፍጹሙን ነጻነት ገንዘብ አድርገናል ማለት ነው። በዚህ ውስጥ ደግሞ ፍጹም የኾነ እኩልነት አለ። ስሎዋን እንዲህ ይላል “ሁሉም ሰው ንጉሥ፣ አባት፣ አለቃ መኾን አይችልም። ነገር ግን በማንኛውም የሥልጣን ደረጃ ውስጥ ኾኖ እግዚአብሔርን መውደድና ማስደሰት ይችላል፤ ይህ ብቻ ጠቃሚ ነውና። ማንም እግዚአብሔርን በምድር ላይ አብልጦ ቢወድ፣ በእግዚአብሔር መንግሥት በታላቅ ክብር ይኾናል።" (St. Silouan the Athonite, Writings, VI.23)። እንግዲህ በእውነተኛው ነጻነት ውስጥ መኖር ማለት እግዚአብሔርን በማፍቀርና በማስደሰት መኖር ማለት ነው። በነጻነት ውስጥ አለን ማለት በዚህ መልካም ነገር ውስጥ አለን ማለት ነው።
◈ ተወዳጆች ሆይ! ይህን ቅዱሱን ነጻነት ክፉ ምኞታችን አላጠፋብንምን? የዚህ ዓለም ኃላፊ ነገሮች እጅግ በጣም ደስ የሚያሰኙን ራሳችንን ለኃጢአት ባርያ በማድረጋችን ምክንያት ከቅዱሱ ነጻነች ስለ ራቅን መኾኑን መዘንጋት የለብንም። ሐሳባችን ከመልካምነት ሲወጣ አእምሯችን ለአጋንንት ባርያ ወደ መኾን መውረዱን እናስተውል! ቶሎ ብለንም ውስጣችንን እንመርምር፥ ስለ ፍቅር ብሎ ፈጥሮን በፍቅሩ የሚያኖረንን አምላክ የሰጠንን ነጻነት ፍሬ በማፍራት እናስደስተው! ለዚህ ዓለም ማንኛውም ኃላፊ ነገር ውስጣችንን ባርያ በማድረግ ነጻነታችንን አናበላሽ። እስከ ዛሬ ድረስ የፈጸምናቸው ክፉ ሥራዎች እጅግ መብዛታቸውን አስበን ፈጣሪያችንን በአንብዓ ንስሓ ማረን እንበለው።
◈ ቅዱስ ማርቆስ “መንፈሳዊ ሕይወትን የሚኖር ትሑት ሰው፥ ቅዱሳት መጻሕፍትን በሚያነብበት ጊዜ፥ ሁሉንም ነገር ከራሱ ሕይወት ጋር ያገናኛል እንጂ ከሌሎች አይደለም።" ይላል። (St. Mark the Ascetic, Sermon, 1.6)። ስለዚህ ነጻነትን ጠብቆና ቀድሶ ለመኖርን የራስን ሕይወት መመርመር ያስፈልጋል። የራሳችንን ሕይወት ሳንቀድስ ስለ ሌላው ብቻ በማወራት የምንኖር ከኾነ በአጋንንት ወጥመድ ውስጥ መጠመዳችንን ልብ እንበል! ለዚህም ነው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ “ብርሃን የሌላቸው ቀጥ ብለው መሄድ እንደማይችሉ የቅዱሳት መጻሕፍትን ጨረር ያላዩ በጨለማ ስለሚጓዙ ኃጢአትን ይሠራሉ።" (St. John Chrysostom, Conversations on the Epistle to the Romans, 0.1)። በመኾኑም ነጻነታችንን በቅዱሳት መጻሕፍት መመሪያ ውስጥ እናድርገው።
◈ በራሳችን ምድራዊ ፍላጎት ምክንያት እግዚአብሔር የሰጠንን ልዩ ስጦታ በሰይጣን አናስወስደው! እግዚአብሔር በቸርነቱ ይጠብቀን፥ በብዙ የኃጢአት ዱላ ተደብድቦ የደነዘዘውን ልቡናችንን ይፈውስል፤ የሐሳቡንም ብርሃን በልባችን ያብራልን፤ በፈቃዳችን ከታሠርንበትን የኃጢአት ባሪነት በቸርነቱ ያላቅቀን፤ ቅዱስ ቃሉንም ወደ መረዳትና በገቢራዊ ሕይወት ወደ መኖር ልዕልና ያሣርገን አሜን።
#Subscribe #Like #Share
👇👇👇👇
www.youtube.com/@haileG2239
www.youtube.com/@pagumentube
መዝሙር ተጋበዙልኝ ውዶች! ጾሙ ጸሎቱ እንዴት ነው? በያላችሁበት ሰላሜ እግዚአብሔር ከሁላችሁ ጋር ይሁን። በርቱ፣ ጠንክሩ!
«አለአግባብ አትጠቀሙ»
◈ ብዙ ጊዜ ጉዳቶች የሚመጡብን ለነገሮች ባለን የተሳሳተ አጠቃቀም ምክንያትነት ነው። ነገሮችን ሥርዓታቸውን ጠብቀን ለመጠቀም፥ አስቀድመን አጠቃቀማቸውን ማወቅና መረዳት አለብን። አጠቃቀሙን የማናውቀውን ነገር ኹሉ ዝም ብለን መጠቀም የለብንም። ካልኾነ የመለየት ብቃት ስለማይኖረን እንደ ሕፃናት እሳት ውስጥ እጃችንን ልንሰድ እንችላለን፥ ጉዳቱም የሚገባን ስንቃጠል ይኾናል ማለት ነው። እግዚአብሔር ለአዳም በገነት ዕፅ በለሰን የሰጠው፥ ለበጎ ነበር፥ አዳምም በበጎ በተጠቀመበት ጊዜ ከእግዚአብሔር ጋር የነበረው አንድነት ጽንቶለታል። ኾኖም ዕፀ በለስን አዛብቶ ሲጠቀም ግን፥ የእግዚአብሔር ሕልውናና ከእርሱም ጋር ያለውን አንድነት ይረዳበት የነበረውን አንድም አዳም ራሱ የራሱን ፍጡርነት የፈጣሪውን አምላክነት ያይበት የነበረውን ዕፅ የጥፋቱ ምክንያት አደረገው። አለአግባብ በመጠቀም ከእግዚአብሔር ጋር የነበረውን ተግባቦት አፈረሰበት።
◈ ብዙዎቻን እያደረግን ያለነው ልክ እንደ አዳም ነው። እግዚአብሔር ለበጎ የሰጠንን ነገር ኹሉ ገልብጠን የጥፋት አድርገን እንጠቀማለን። ሰውነታችን በራሳችን የፈጠርነት ማንነት አይደለም፤ ይልቅስ ከፈጣሪያችን ያገኘነው ሀብታችን ነው እንጂ። ገዢነታችን፣ ነጻነታችን፣ ዕውቀታችን በተፈጥሮ የተሰጡን በጎ ስጦታዎች ናቸው። እኛ ግን እነዚህን ገልብጠን በመጠቀም ሰውነትን ጎጂ አስመስለን ሳልነው፤ እግዚአብሔር የሚነግሥበትን ሰውነት በፈቃዳችን ጥመት ምክንያት ተጎዳንበት። ገዢነታችንን አለአግባብ በመጠቀም የተለያዩ ነገሮች ተገዢ ኾንን፥ ነጻነታችንንም በፈቃዳችን ጥመት ምክንያት የርግማን ምንጭ አደረግነው፤ ዕውቀታችንንም አለአግባብ በመጠቀም ድንቍርና አደረግነው። ስለዚህም በጽኑ የሕይወት ጉዳት ውስጥ ጠልቀን ገብተን እንኳን ጉዳት ውስጥ መኾናችን እስኪረሳን ድረስ ታመምን። አለአግባብ መጠቀም ምን ያህል ጥፋት እያመጣብን ይኾን? እግዚአብሔር ቋንቋን እንግባባበት ዘንድ ቢሰጠን እኛ ግን ገልብጠን የልዩነት አድርገን ተጠቀምነው፥ ሕይወትንም ቢሰጠን እንደ ግብፁ ፈርኦን የድንዳኔ አደረግነው። ይህ ድርጊታችን አያሳዝነንምን? ስለ ምንድን ነው ውስጣችን ለመንፈሳዊነት ስሜት እንዳይኖረው የኾነው?
◈ ማክሲመስ መስካሪው "ምግብ ክፉ አይደለም፤ ነገር ግን ኾዳምነት እንጂ። መጽነስ ክፉ አይደለም፤ ነገር ግን ዝሙት እንጂ። ገንዘብ ክፉ አይደለም፤ ነገር ግን ስግብግብነት እንጂ። ክብር ክፉ አይደለም፤ ነገር ግን ከንቱ ውዳሴ እንጂ። በእርግጥ ህልው ኾነው በሚኖሩ ነገሮች ክፋት የለባቸውም፤ ነገር ግን አለአግባብ በኾነ አጠቃቀም እንጂ።" ይላል። (Maximus the Confessor, Chapters on Love, 3.4)። ይህ ማለት የሰው አስተሳሰብና ለነገሮች ያለው አተያይ ወይም አጠቃቀም ዋና ጉዳይ ነው። ከላይ የተዘረዘሩት ነገሮች ሰውን አስገድደው የመጉዳት ኃይል የላቸውም፤ ሊኖራቸውም አይችልም። ሕሊናችንን ለእነዚህ ነገሮች ባርያ አድርገን እስካላስገዛን ድረስ በራሳቸው አይጎዱንም። እንግዲያውስ ሰውነታችንን የእግዚአብሔር መቅደስ አድርገን የራሳችንን አእምሮ በንጹሕ የወንጌል ትምህርት አጽር ቅጽር ውስጥ እንዲኖር እናሠልጥነው፥ የተሰጡንን ነገሮች በአግባቡ ወደ መጠቀም እንመለስ።
◈ በዚህ ዓለም ያሉ የኃጢአት መንገዶች ለጊዜው ጣዕም ያለቸው ሊመስለንና፥ የተፈጠርንለትን ዓላማ ሊያስረሱንና ውስጣችንን ሊስቡን ይችላሉ፥ ኾኖም እኛ እግዚአብሔር በሰጠን አእምሮ ራሳችንን ልንጠብቅ ይገባናል። በእርጋታና በአስተውሎት ነገሮችን ኹሉ ሥርዓት ባለው መንገድ መጠቀምና የጠላታችን የዲያብሎስን ወጥመድ መስበር አለብን። አለአግባብ ለኾኑ ነገሮች ዕድል አንስጥ፥ በትንሽዬ ቀዳዳ የክፉው መንፈስ ሐሳብ ወደ ውስጣችን ጥልቅ ከገባ ጠማማውን ቀና፥ እውነቱንም ውሸት አድርጎ እያሳየ የሕሊና ረብሽ ሊያመጣብን ይችላል። ስለዚህም በአግባቡ ብቻ ለመኖር ወስነን ወደ መኖር እንምጣ፥ እግዚአብሔር ይርዳን አሜን።
#Subscribe #Like #Share
👇👇👇👇
www.youtube.com/@haileG2239
www.youtube.com/@pagumentube
ኢየሱስ ሕሙይ በእንቲአነ፥ ኢየሱስ ሙቁሕ፤ እንተ ዐቀሙከ ውስተ አውደ ፍትሕ፤ ጊዜ ኮነ ጎሐ ጽባሕ፥ ሰብሐት ለከ።
የጎህ ንጋት በሆነ ጊዜ በፍርድ አደባባይ የአቆሙህ፤ ስለእኛ የታሰርክ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ምሥጋና ይገባሀል።
#Subscribe #Like #Share
👇👇👇👇
www.youtube.com/@haileG2239
www.youtube.com/@pagumentube
«የሰው ልጅ ለመዳን ምን ያስፈልጉታል?»
፩ኛ. ማመን
የሰው ልጅ፣ ከዂሉ አስቀድሞ የዓለም መደኀኒት ክርስቶስ ሕግን እንደ ሠራለት አምኖ መመለስ ያስፈልገዋል፡፡ “ለሰው ዂሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም (ወደ ሰው) የመጣው ነው፡፡ በዓለም ነበረ፤ ዓለሙም በእርሱ ኾነ፤ ዓለሙ ግን አላወቀውም፡፡ ወደ ወገኖቹ መጣ፤ ወገኖቹ ግን አልተቀበሉትም፡፡ ለተቀበሉት ዂሉ ግን በስሙ ለሚያምኑ የእግዚአብሔር ልጆች እንዲኾኑ ሥልጣንን ሰጣቸው፡፡ እነርሱም ከእግዚእሔር ተወለዱ …፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዮሐ. ፩፥፱)፡፡ ቀደም ሲል የነበረው ድኅነት ለተቀበሉትም ላልተቀበሉትም የተደረገ፤ ላመኑትም ላላመኑት የተፈጸመ ድኅነት ነው፡፡ አሁን ግን ላመኑ እንጂ ላላመኑ የሚሰጥ ድኅነት የለም፡፡
፪. መጠመቅ
“ያመነ የተጠመቀ ይድናል” (ማር. ፲፮፥፲፮) ተብሎ በቅዱስ ወንጌል እንደ ተነገረው ለመዳን እምነት ያስፈልጋል፤ ከእምነት ቀጥሎ መጠመቅ ያሻል፤ ይህን ካሣ ተፈጽሞ የተሠራውን ሕግ መፈጸም ግዴታ ነው፡፡ ለመዳን ማመን ብቻ አይበቃም፡፡ እምነትማ አጋንንትም አላቸው፡፡ ዕለት ዕለት የሚድኑበት፣ የሚጨመሩበት መንገዱ እምነትና ጥምቀት ነው፡፡ የቅዱሳን ሐዋርያት ተግባርም ይህ ነበር፡፡ ሕይወትን ድኅነትን መስበክ፤ ያመነውን ማጥመቅ፤ የድኅነቱ ተሳታፊ ማድረግ ወደ ድኅነቱ ማስገባት፤ የሕይወትን ቃል ለዂሉ መመስከር ነው፡፡ ዓላማው ለማሳመን፣ ለማጥመቅ፣ ለማዳን ነው፡፡ ለመዳን አምኖ መጠመቅ የግድ አስፈላጊ መኾኑን በሐዋርያት ሥራ የተመዘገበው የጃንደረባው ታሪክ ያስረዳናል (ሐዋ. ፰፥፴፭-፴፯)፡፡
ማመን ብቻውን ስለማያድን ጃንደረባው ‹‹አምናለሁ›› ብሎ ከማመን አልፎ ሃይማኖቱን መስክሯል፤ ፊልጶስም ‹‹ድነሃል፤ ሒድ›› አላለውም፤ አጠመቀው እንጂ፡፡ ስለዚህ ከእምነት ቀጥሎ መጠመቅ ለድኅነት ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ ስለዚህ ነው ዓለምን ለማዳን የመጣው አምላካችን ሐዋርያትን ወደ ዓለም ዂሉ የላከው (ማቴ. ፳፰፥፲፱)፡፡ ተልዕኮውም በቃ ‹‹አድኛቸዋለሁ›› አይደለም፤ እንዲያምኑ፣ እንዲጠመቁ፣ ትእዛዙን እንዲጠብቁ፣ ደቀ መዛሙርት እንዲኾኑ ነው፡፡ ድኅነት የሚገኘው በዚህ መንገድ ነው፡፡ በማውራት ብቻ ‹‹ድኛለሁ›› ብሎ ተዘልሎ በመቀመጥ አይደለም፡፡ “… እነዚህ ሰዎች የልዑል እግዚአብሔር አገልጋዮች ናቸው፤ የሕይወትንም መንገድ ያስተምሯችኋል …” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሐዋ. ፮፥፲፯)፡፡
ቅዱሳት መጻሕፍት የመዳንን መንገድ የሚነግሩን እንድናየው አይደለም፤ እንድንጓዝበት ነው እንጂ፡፡ “… ‹ጌቶቼ፥ እድን ዘንድ ምን ላድርግ?› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እመን፤ አንተ እና ቤተሰቦችህ ትድናላችሁ› አሉት፡፡ የእግዚአብሔርንም ቃል ለእርሱና በቤቱ ላሉት ዂሉ ነገሩአቸው … በዚያው ጊዜ ከቤተ ሰቡ ዂሉ ጋር ተጠመቀ፤” (ሐዋ. ፲፮፥፴-፴፬)፡፡ ከዚህ ላይ ‹‹ድናችኋል›› ሳይኾን ‹‹ትድናላችሁ›› የሚለውን ቃል ልብ ይሏል፡፡ “ዳግመኛ ከውኃ እና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም” እንዳለ (ዮሐ. ፫፥፭)፡፡ ስለዚህ ሰው አምኖ ይጠመቃል፤ ከእግዚአብሔርም ይወለዳል፤ በዚህ ድኅነትን ገንዘብ ያደርጋል፡፡ ከእግዚአብሔር ካልተወለደ በፍጹም ሊድን አይችልም፡፡ መዳን ማለት የእግዚአብሔርን መንግሥት ወርሶ ስሙን ቀድሶ መኖር ነው፡፡ ስለዚህ የሕይወት እና የድኅነት ወንጌል ለዓለሙ ዂሉ ይሰበካል፤ ዂሉም ይድን ዘንድ (ማር. ፲፮፥፰)፡፡
፫. ሥጋውን መብላት ደሙን መጠጣት
ሰው ካመነ ከተጠመቀ በኋላ ማድረግ ያለበት ቅዱስ ሥጋውን መብላት፣ ክቡር ደሙን መጠጣት ነው፡፡ ሥጋ ወደሙ ሕይወት የሚገኝበት የእምነት እና የጥምቀት ማተሚያ መደምደሚያ ነው፡፡ እምነት መሠረት፤ ጥምቀት መሰረት የሚጸናበት ከእግዚአብሔር የምንወለድበት፤ ሥጋው እና ደሙ ማረጋገጫ ነው፡፡ ያመነ በጥምቀት ይወለዳል፤ የተወለደ ደግሞ የሚያድግበት ምግብ ያስፈልገዋል፡፡ ምግቡም ሥጋውና ደሙ ነው፡፡ ይህን በልቶ ጠጥቶ የሚኖር የእግዚአብሔር ልጅ፣ የእግዚአብሔር የመንግሥቱ ወራሽ፣ የስሙ ቀዳሽ ይኾናል፡፡
“የሰው ልጅ ለሚሰጣችሁ ለዘለዓለም ሕይወት ለሚኖር መብል ሥሩ እንጂ ለሚጠፋው መብል አይደለም፤ ይህን እግዚአብሔር አብ አትሞታልና … የእግዚአብሔር እንጀራ ከሰማይ የሚወርድ፤ ለዓለም ሕይወትን የሚሰጥ ነውና …” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዮሐ. ፮፥፳፯-፶፬፤ ሮሜ. ፭፥፱፤ ኤፌ. ፩፥፯፤ ፩ኛ ዮሐ. ፩፥፯)፡፡ ስለዚህ አምነን ተጠምቀን ሥርየት የተገኘበትን እና የሚገኝበትን ሥጋውን መብላት ያፈልጋል፡፡ በሃይማኖት ከብረን፣ በጥምቀት ተወልደን፣ በሥጋው በደሙ ታትመን ድኅነትን ገንዘብ እናደርጋለን፡፡
፬. መልካም መሥራት (ዐቂበ ሕግ)
ያመነ፣ የተጠመቀ፣ ሥጋውን የበላ፣ ደሙን የጠጣ ዂሉ በመልካም ሥራ መኖር አለበት፡፡ መልካም ሥራ የሌለው እምነት፣ ጥምቀት፣ ቊርባን ብቻውን አያድንም፤ ያመነ የተጠመቀ ሰው ፈጣሪውን በሃይማኖት መከተል በግብር መምሰል አለበት፡፡ “መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ፤” (ማቴ. ፭፥፲፮)፡፡ የሰው ልጅ ከላይ የተዘረዘሩ ተግባራትን ከፈጸመ እንንደየሥራው መጠን ዋጋውን እንደሚቀበል ቅዱሳት መጽሐፍት ምስክሮች ናቸው፡፡ “እነሆ በቶሎ እመጣለሁ፤ ለእያንዳንዱ እንደየሥራው መጠን እከፍለው ዘንድ ዋጋዬ ከእኔ ጋር ነው፤” (ራእ. ፳፪፥፲፪፤ ያዕ. ፪፥፳፮)፡፡
አምላካችን ለፍርድ ሲመጣ የሚጠይቀው ሃይማኖት ብቻ ሳይኾን ሥራ መኾኑን መዘንጋት ሞኝነት ነው፡፡ “… ብራብ አላበላችሁኝም፤ ብጠማ አላጠጣችሁኝም፤ ብታረዝ አላለበሳችሁኝም …” እንዳለ ጌታችን (ማቴ. ፳፭፥፴፭-፵፭)፡፡ ስለዚህ ለድኅነቱ ተግባር አስፈላጊ ነው፡፡ ከተግባር ጋር ዐቂበ ሕግ (ሕግ መጠበቅ) ተገቢ ነው፡፡ “የዘለዓለም ሕይወትን አገኝ ዘንድ ምን ላድርግ?” ብሎ ለጠየቀው ጐልማሳ ጌታችን የሰጠው ምላሽም “… ትእዛዛትን ጠብቅ” የሚል ነው (ማቴ. ፲፱፥፲፮-፲፯)፡፡ የዘለዓለም ሕይወትን ለመውረስ እግዚአብሔር በቸርነቱ የሚቀበለው መልካም ሥራ ወሳኝ ጉዳይ ነውና፡፡
፭. መጽናት
ለመዳን ከማመን፣ ከመጠመቅ፣ ሥጋውን ከመብላት፣ ደሙን ከመጠጣት በተጨማሪ በዚሁ ጸንቶ መኖር ያስፈልጋል፡፡ ገብተው የወጡ፤ አምነው የካዱ ዂሉ ድኅነት የላቸውም፡፡ “በዂሉም ዘንድ ስለ ስሜ የተጠላችሁ ትኾናላችሁ፤ እስከ መጨረሻ የሚጸና ግን እርሱ ይድናል፤” (ማቴ. ፲፥፳፪፤ ፳፬፥፲፫፤ ማር. ፲፫፥፲፫)፡፡ “እኛም የምንደፍርበትን የምንመካበትን ተስፋ እስከ መጨረሻው አጽንተን ብንጠብቅ ቤቱ ነን … የመጀመሪያ እምነታችንን እስከ መጨረሻው አጽንተን ብንጠብቅ የክርስቶስ ተካፋዮች ኾነናል …” (ዕብ. ፫፥፮-፲፬)፡፡ “እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ኹን፤ የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ፤” (ራእ. ፪፥፲)፡፡
“ድል ለነሣውና እስከ መጨረሻ ሥራዬን ለጠበቀው እኔ ደግሞ ከአባቴ እንደ ተቀበልኩ በአሕዛብ ላይ ሥልጣን እሰጠዋለሁ፡፡ በብረት በትር ይገዛቸዋል፤ እንደ ሸክላ ይቀጠቅጣቸዋል፤” (ራእ. ፪፥፳፮)፡፡ የሰው ልጅ የሚድነው በእምነት፣ በጥምቀት፣ በሥጋው በደሙ፣ በመልካም ሥራ ጸንቶ ሲኖር ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ጸንተን እንድኖር እና መንግሥቱን እድንወርስ፤ ስሙን እንድንቀድስ አምላካችን በቸርነቱ ይርዳን፡፡ እንግዲህ ዂላችሁም ወደ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በመመለስ (በመምጣት) ድኅነታችሁን በመፈጸም የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ የተዘጋጃችሁ ኹኑ መልእክታችን ነው፡፡
#Subscribe #Like #Share
👇
ኦ ማሪያም!
በእንተዝ ናፍቅረኪ ወናአብየኪ፤
እስመ ወለድኪ ለነ መብልዓ ጽድቅ፤
ዘበአማን ውስቴ ሕይወት ዘበአማን፤
ማሪያም ሆይ ስለዚህ እንወድሻለን፤
ከፍ ከፍም እናደርግሻለን፥ እውነተኛ የጽድቅ መብልንና፤
እውነተኛ የይወት መጠጥን ወልደሽልናልና።
#Subscribe #Like #Share
👇👇👇👇
www.youtube.com/@haileG2239
www.youtube.com/@pagumentube
«ተስፋ መቍረጥ»
◈ ዮሐንስ ዘሰዋስው ስለ ቀቢጸ ተስፋ ሲያስረዳ፦ "ቀቢጸ ተስፋ የመቀባጠር አንዱ ቅርንጫፍ፣ የእርሱም የበኲር ልጅ ናት። ... ቀቢጸ ተስፋ የነፍስ ልምሾነት (መሰልሰል)፣ የአእምሮ መዛል (መድከም)፣ ተጋድሎን ቸል ማለት፣ ብፅዓትን (ቃል ኪዳንን) መጥላት ነው። ... እግዚአብሔርንም ምሕረት የለሽና ሰዎችን የሚጠላ እንደ ኾነ አድርጋ ትከሳለች። መዝሙራትን ለመዘመር የምትዝል፣ ለጸሎት የምትደክም፣ ለአገልግሎት እንደ ብረት የጸናች (ግትር የኾነች)፣ ለተግባረ እድ የምትተጋ፣ ለመታዘዝ ኹኔታ (ብቃት) ቸልተኛ ናት።" ይላል። (ሳሙኤል ፍቃዱ (ሐተታና ትርጒም)፣ ምዕራግና ድርሳን፣ 2011 ዓ.ም፣ ገጽ 173)። ከዚህ ትርጒም ተነሥተን ተስፋ መቍረጥ ለመንፈሳዊ አገልግሎት ያለንን ስልቹነት፣ ወይም ጥላቻ የሚያመለክት ነው ማለት እንችላለን። ልበ አምላክ ዳዊት "ሰነፍ በልቡ እግዚአብሔር የለም ይላል" እንዳለ በንዝኅላልነታችን ምክንያት እግዚአብሔር የለም ብለን እስከ ማመን የምንደርስበት ክፉ አኗኗር በቀቢጸ ተስፋ ኾኖ መኖር ነው። ተስፋ የሚቈርጥ ሰው ስኬት ላይ መድረስ አይችልም። ሕይወቱን በበጎ ጎዳና መምራት አይኾንለትም። ምክንያቱም ማንኛውም ነገር ጥረትንና ተጋድሎን ይሻልና። አንዴ ወደሚፈልገው መንገድ እየሄደ ውድቀት ካገጠመው ኹሉም ነገር ወዲያ ጨለማ መስሎ ይታየዋል።
◈ በዋናነት ብዙ ሰዎች በተስፋ መቍረጣቸው ምክንያት ራሳቸውን ለማጥፋት ይወስናሉ። ተስፋ መቍረጥ የእግዚአብሔርን ምሕረት የመርሳትና ይሁዳን የመምሰል ሕይወት ነው። ተስፋ የሚቈርጥ ሰው ከዚህ ሐሳቡ ለመውጣት ሲል ወደ ሱስ ይጓዛል። በጽኑ ሱስ ሲያዝ ደግሞ የበለጠ የሕይወትን ጣዕም እያጣ ይሄዳል፤ ኋላም ራስን ማጥፋትን እንደ ቀላል ነገር አድርጎ ሊመለከት ይችላል። ቅዱስ ይስሐቅ ዘሶርያ "በመሰናክልህ ምክንያት ተስፋ አትቍረጥ። ይኸውም ኃጢአትህን በማሰብ አትጸጸት ማለቴ ሳይኾን፥ ነገር ግን የማይድኑ አድርገህ አታስብ ማለቴ ነው።" በማለት የገለጸው ብዙውን ጊዜ ተስፋ መቁረጥ ከኃጢአቴ አልነጻም፣ መዳን አልችልም ብሎ ከማሰብ የሚመጣ ስለ ኾነ ነው። The Ascetical Homilies of St. Isaac the Syrian, Homily 64, “On Prayer, Prostrations, Tears, Reading, Silence, and Hymnody”። ወንድሜ ሆይ! ምንም ዓይነት መሰናክል ሊገጥምህ ይችላል፤ ነገር ግን ከልብህ ተጸጽተህ ንስሓ ከገባህ የሚድን መኾኑን አትዘንጋው። ከማንኛውም ውድቀትህ በላይ እግዚአብሔር የሚያዝንብህ አይምረኝም ብለህ ማመን ስትጀምር ነው። ንስሓ ከተገባበት የማይድን ምንም ዓይነት አደገኛ የኃጢአት በሽታ የለምና። የደማስቆው ጴጥሮስ "ነፍስን የሚገድለውን ተስፋ መቍረጥን፥ ጽኑ ተአጋሲነት ይገድለዋል።" በማለት ያስረዳል። St. Peter of Damaskos, “Book II: Twenty-Four Discourses,” V Patient Endurance, The Philokalia: The Complete Text (Vol. 3)። እንግዲህ ይህ የሊቁ አገላለጽ በአንድ በኩል ተስፋ መቍረጥ ነፍስን የሚገድል መርዝ መኾኑን የሚጠቁም ሲኾን፥ በሌላ በኩል በትዕግሥት ሊነቀል የሚችል መኾኑን ያስረዳል። ስለዚህ ተስፋ መቍረጥ ትዕግሥትን በማጣት የሚበቅል ክፉ አረም መኾኑን በዚህ እናስተውላለን።
◈ ዮሐንስ ዘካርፓቶስ እንዲህ ይላል "ፈርዖን ፈርቶ እንዲህ አለ፦ "ፈርዖንም ሙሴንና አሮንን በፍጥነት ጠራ፦ አምላካችሁን እግዚአብሔርን እናንተንም በደልሁ፥ አኹን እንግዲህ በዚህ ጊዜ ብቻ ኃጢአቴን ይቅር በሉኝ፥ ይህንም ሞት ብቻ ከእኔ ያነሣልኝ ዘንድ አምላካችሁን እግዚአብሔርን ለምኑ፣ አላቸው። ሙሴም ከፈርዖን ፊት ወጣ ወደ እግዚአብሔር ለመነ።" ፈርዖንም ተሰማለት። በተመሳሳይ ኹኔታ አጋንንትም ጌታችንን ወደ ገደል እንዳይከታቸው ለመኑ፥ ጥያቄያቸው ተመለሰላቸው። ሉቃ 8፡31። እንግዲያው አንድ ክርስቲያን ከመንፈሳዊ ሞት ይወጣ ዘንድ ቢለምን ምን ያህል የበለጠ ይሰማለት ይኾን?" በማለት በምንም መንገድ ተስፋ ወደ መቍረጥ መሄድ እንደ ሌለብን ነው።(St. John of Karpathos, For the Encouragement of the Monks in India who had Written to Him: One Hundred Texts (69)። ያን ጨካኙን ፈርዖንን የሰማ አምላክ አንተን እንዴት አይሰማህም? በመስቀል ላይ የሚሰቅሉትን እኒያን አይሁድን የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው ብሎ የምሕረት ድምፁን ያሰማ እርሱ አይምረኝም ብለህ ስለምን ትጨነቃለህ? ይልቅስ ኃጢአትህን አምነህ ይቅር ይልህ ዘንድ ወደ ፈጣሬ ዓለማት ወደ ኾነው ጌታ በአንብዓ ንስሓ ብትቀርብ አይሻልህምን? ተስፋ ስንቈርጥ ሁሉንም ነገር አጥርተን ማየት አንችልም። ልክ በጨለማ ውስጥ ያለ ሰው በብርሃን አለመኖር ምክንያት ከፊት ለፊቱ ያሉ ነገሮችን አጥርቶ ማየት እንደ ማይችል፥ ተስፋ በመቍረጥ ጨለማ ውስጥ ያለም ሰውም እንዲሁ አጥርቶ ማየት አይችልም።
#Subscribe #Like #Share
👇👇👇👇
www.youtube.com/@haileG2239
www.youtube.com/@pagumentube
የክፉ ትንቢት መፈጸሚያ ሰነፍ ትውልድ ሆነናል ያሳዛናል!
****
በኦሮሚያ ክልል ዶዶላ ከተማ የለመድነው እና ብዙም የማንደነግጠው የኦርቶዶክሳውያን ግድያ ተፈጽሟል።
ይህቺ ከተማ ከእዚህ ቀደም ጅዋር መሐመድ ተከበብኩኝ አዋጅ ተከትሎ የሞት ጽዋ ከቀመሱ የኦሮሚያ ከተሞች መሃል ናት።
ዛሬም የሞት አባጃግሬው የሆነው ገዳይ ስብስብ የኦርቶዶክሳውያን እልፍኝ ጎብኝቷል። አገልጋዮችን ከእነ ሙሉ ቤተሰቦቻቸው ረሽነዋል።
እንግዲህ አሁን ላይ ኦርቶዶክስ ሆነህ ብትጠቃ የሚያተርፍህ ምድራዊ እረኛም ሆነ ስርዓት የለም።
እንኳን ሊያተርፍህ መሞትህ አሳስቦት የሚያዝንልህ ኖላዊም ሆነ መንግስት አይገኝም።
እንዲህ ዘወትር እያለቃቀሱ "ነፍስ ይማር " እያሉ የሞት ጽዋው ወደ እራስ እስኪመጣ ማላዘን ሆኗል ሥራችን !!!
የክፉ ትንቢት መፈጸሚያ ሰነፍ ትውልድ ሆነናል።
እግዚአብሔር ይለመነንን !!!
#Subscribe #Like #Share
👇👇👇👇
www.youtube.com/@haileG2239
www.youtube.com/@pagumentube
«ግብዝነት»
ግብዝ ሰው (አስመሳይ ሰው) በድብቅ እግዚአብሔር የለም ብሎ የሚያምን ነው፤ እግዚአብሔር አለ ብሎ የሚያምን ቢኾን ኖሮ፣ እርሱን ፊት ለፊት ለማታለል ባልደፈረ ነበር። በሕይወታችን አስመሳይነትን ለብሰን የምንኖር ከኾነ አኗኗራችን ድራማ ይኾንብናል። የሚኾነውና እንዲኾን የምንፈልገው እርስ በእርሱ ይምታታብናል። መልካም መባል እጅግ የምንፈልግና በሰዎች ዘንድም እንደዛ እንድንባል የሚያደርጉ ነገሮችን በማስመሰል የምንተውን፡ ከእውነተኛ የመልካምነት ሕይወት ግን ፈጽሞ ራቅ ያልን ጥቂት ሰዎች አይደለንም።
ግብዝነት ተግባራዊ የኾነ የመጠራጠር ሕይወት ነው። እግዚአብሔርን በአንደበታችን ላንክደው እንችላለን፣ በሕይወታችን ውስጥ ሰዎች እርሱን የምናመልክ አድርገው እንዲያስቡ አድርገን ልንተውን እንችላለን፡ በድብቅ ወይም በስውር በውስጣችን ያለው ግን ድፍረትና ትዕቢት፡ ራስን ማክበር ስለ ኾነ እግዚአብሔር ከሚፈቅደው ውጪ ኾነን እንገኛለን። የዚህ ኹሉ መነሻው ከእውነት መንገድ መውጣትና እውነትን በተግባራዊ የሕይወት ክፍላችን ውስጥ መግፋታችን ነው። ለዚህም ነው ሕይወታችን ከጥፍጥና ይልቅ ምሬት እንዲስማማው ያደረግነው።
መልካም የኾነው እርሱ በአርአያውና በአምሳሉ ፈጠረን እኛ ግን በፈቃዳችን ጥመት ምክንያት ሌላ አርአያን ተላበስን። ውስጣችንን በዚህ ዓለም ፍቅር አሰከርናት፥ የእግዚአብሔር የኾነውን በጎ ነገር ከተግባራዊ ሕይወታችን አራቅነው፥ ራሳችን ላይ በክፉ ዝንባሌያችን ምክንያት የዝሙትን እሳት አነደድን። ራሳችንም ባነደድነው የዝሙት እሳት ተቃጠልን፣ ረከስን፣ ቆሸሽንም፤ ኾኖም በሰዎች ዘንድ ንጹሕ አድርገን ራሳችንን በማሳየት ጻድቅ ተሰኘን፥ ይህ በእጅጉ አስገራሚ ነው።
ግብዝነታችን ከማደጉ የተነሣም፥ ግብዝ መኾናችንም ተረሳን፥ ውስጣችን በከንቱ ውዳሴ፥ በዚህ ዓለም ክብር ገነነች። ሰዎችን ከሰዎች አበላለጥን፥ ፍትሐዊነትን ከአእምሮችን በግብዝነታችን ብሩሽ አጠብናት፥ ፍትሕ ርትዕ የምትመስል ሌላ አዲስ ነገር አበጃጀን። ስለዚህም የማንሰማ፥ የማናስተውል፥ አፍቅሮተ ሰብእ የሌለን፥ በራስ ወዳድነት ጽናት የታጠርን፥ ከእግዚአብሔር ይልቅ ለዓለም የተመቸን፥ በውስጣችን ፈጽሞ የረከስን፥ ወደ እውነተኛ ሕይወት የመመለስ ፍላጎትና ወኔያችን የሞተብን ስንት ነን? እጅግ ብዙ! እግዚአብሔር በቸርነቱ ዓይነ ልቡናችንን ያብራል።
መፍትሔውም ወደ እውነት ለመመለስ ኹል ጊዜ ሳያቋርጡ መትጋት ነው። እውነት የምትሽሞደሞድ አይደለችም፥ በግል ስሜት የምትሠራም አይደለችም፥ ይልቅስ ከእግዚአብሔር ጋር ባለን አንድነት የምትረዳ ልዩ ሀብት ናት። ጌታ ራሱ "እኔ መንገድ እውነትና ሕይወት ነኝ" እንዳለ፥ እርሱ ባሳየን የአርአያነት ተግባራዊ የኾነ የእርስ በእርስ ፍቅር መንገድነት፥ እውነት የኾነውን የእርሱን ቃል አክብረን፥ ወደ ሕይወት መግባት አለብን። መንገዱን ካላገኘን እውነትን ሕይወትንም ማግኘት አንችልም። ስለዚህ ከግብዝነት ለመውጣት ስለ እውነት በእውነት መኖር መጀመር አለብን። በእውነተኛ የሕይወት ጎዳና ውስጥ እውነተኛ ፍቅር እና እውነተኛ ጣዕም ያለው ሕይወት አለና። ቆም ብለን አኗኗራችንን እንመርምር፥ የገፋናትን እውነት እንመልሳት፥ የጠላናትን አንድነት እንፈልጋት፥ ይህን ጊዜ የምናመልከው አምላክ ከግብዝነት እሳት ያድነናል።
#Subscribe #Like #Share
👇👇👇👇
www.youtube.com/@haileG2239
www.youtube.com/@pagumentube
«ትሑት ነፍስ ምስጉን ናት። ጌታ ይወዳታልና። እመ አምላክ ከኹሉም የምትበልጥ ትሕት ናት፤ ስለዚህም በምድር ላይ የሰው ልጆች በሙሉ ያመሰግኗታል፥ ሰማያውያን ኃይላትም ያገለግሏታል። ጌታ የተመሰገነች እናቱን ለእኛ ጠባቂና ረዳት አድርጎ ሰጠን።" (St. Silouan the Athonite, Writings III.14) በእርግጥ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የትሕትና ትምህርት ቤት ናት። ለእርሷ ያለን ፍቅር የሚገለጠውም እርሷ የምትወደውን ትሕትና ገንዘብ ስናደርገው ነው። ትሕትናን ገንዘብ ለማድረግ በየዕለቱ እስካልተጋን ድረስ ደርሶ የሚገኝ ጸጋ አይደለም። በእመቤታችን ዕለት ከእርሷ ጋር መኾናችን አንዱ የሚረጋገጠው ትሕትና ያለን እንደ ኾነ ነው። በትዕቢት እየተቃጠልን ሺህ ጊዜ ለእመቤታችን ፍቅር አለን፤ ማርያም ማርያም ብንል ምን ጥቅም አለው? ዋናው ጉዳይ ለራሳችን በፈቃዳችን ጥመት ያለበስነውን ትዕቢት ክፉ መኾኑን አምነን በማውገዝ ወደ ትሕትና ለመድረስ እንትጋ እንጂ!»
#Subscribe #Like #Share
👇👇👇👇
www.youtube.com/@haileG2239
www.youtube.com/@pagumentube
«የሰይጣን ወጥመድ»
◈ አባ ኔቅጣስ ስለ ኹለት ወንድሞች የሚከተለውን ተናግረዋል። አንድ ጊዜ ኹለት መነኮሳት በአንድነት ለመኖር ወሰኑ። አንደኛው በልቡ "ወንድሜ የሚፈልገውን ኹሉ አደርግለታለሁኝ" ሲል ቃል ገባ። ሌላኛውም "የወንድሜን ፈቃድ እፈጽምለታለሁ" ሲል በልቡ ወሰነ። በዚህ ውሳኔያቸው ለብዙ ዘመናት በለጋሥነት ኖሩ። በዚህ ፍቅራቸው የቀና ሰይጣን ሊለያያቸው ተነሣ። በበኣታቸው በር ላይ ቆመና ለአንደኛው ርግብ ለሌላኛው ቍራ መስሎ ታያቸው። በዚህ ጊዜ አንደኛው መነኩሴ "ርግቧን አየሃት?" ሲለው ሌላኛው ደግሞ "ርግብ አይደለችም ቍራ ነት" ሲል መለሰ። "ርግብ ናት"፣ "ቍራ ነው" ክርክር ጀመሩ። ክርክሩ ወደ ጭቅጭቅ፣ ጭቅጭቁ ወደ ድብድብ አመራና ደም በደም እስኪ ኾኑ ድረስ ተደባደቡ። በመጨረሻም ተለያዩ። ከሦስት ቀናት በኋላ ወደ ልባቸው ተመልሰው ኹለቱም ተፀፀቱ። ይቅርታም ተጠያየቁ። ኹለቱም በተለያየ መልክ አንድ ዓይነት ነገር ማየታቸውንና ልዩነታቸው የመጣው ከነገሩ ሳይኾን ከዲያብሎስ መኾኑን ተረዱ። እስከ ዕለተ ሞታቸውም ድረስ አብረው ያለ ፀብ ኖሩ። (ዳንኤል ክብረት (ዲ/ን፣ አርተር)፣ በበረሓው ጉያ ውስጥ፣ ሦስተኛ ዕትም 2004 ዓ.ም፣ ገጽ 57-58)።
◈ ብዙ ጊዜ መንፈሳዊ ሕይወታችን ምስቅልቅል የሚልብን በእንዲህ ዓይነት ስውር የሰይጣን ወጥመድ ነው። አንድን ነገር በእርጋታ ከመመርመር ይልቅ ያየነውን ብቻ መሠረት አድርገን ወደ ተሳሳተ ውሳኔ የምንገባው እና የእግዚአብሔርን መግቦት የምንጠራጠር ብዙ ሰዎች አለን። ከሌሎች ጋር በፍቅር ለመኖር የወሰነውን ውሳኔ ድንገት በአንዲት ተራ ምክንያት የምናፈርስ መኾኑን እናስተውል። የገጠመንን ነገር በልቡናችን ከገባነው ቃል ኪዳን ጋር እያስተያየን በትዕግሥት ልንጸናና ረጋ ልንል ሲገባን በጥድፊና ተቃራኒ መልስ እየመለስን ወደ ጥልና ፀብ የምንገባ ልንጠነቀቅ ይገባናል። እግዚአብሔር ዓይነ ልቡናችንን ያብራልን።
◈ በሌላ በኩል ደግሞ አንድን ነገር በተለያየ መንገድ ለተለያዩ ሰዎች በማሳየት ሰይጣን ምን ያህል ፀብና ጥልን የሚፈጥር ክፉ ጠላት መኾኑን ልብ ማለት እንችላለን። ክፉው ጠላት ሰይጣን እኛን ለመጣል ያን ያህል የሚዋጋ ከኾን እኛስ እርሱን ለመግጠም ምን ያህል ሠልጥነን ይኾን? ይህን ኹላችንም ለየራሳችን እንጠይቅ። በክርስትና ሕይወት በጣም የዛልን፣ በእምነታችን ላይ ጥርጣሬ የመጣብን፣ በሃይማኖታዊ ጉዳይ ለዘብተኛ ወደ መኾን እየሄድን ያለን በሙሉ ለአንድ አፍታ ቆም ብለን እናስብ። ጠላት ምን ያህል የጥፋት ጉድጉድ እየቆፈረልን እንደ ኾነም ልብ በማለት ንቁ ተዋጋጊ እንኹን። ሊዋጋው እና ሊያጠፋው ብዙ ኃይል ታጥቆ የሚመጣን ጠላት እያየ ባዶ እጁን ቍጭ ብሎ የሚጠብቅ ተዋጋ ይኖራልን? ቢኖሩ እንኳን ለማሸነፍ ያሰበ ሳይኾን አስቀድሞ በስንፍና ራሱን አሸንፎ ጠላትም ሲመጣ እጁን ሰጥቶ ባርያ ሊኾንለት ያቀደ ብቻ ነው ሊኾን የሚችለው። ወይም ሕይወቱን የጠላና ለበለጠ ሥቃይና መከራ ራሱን በፈቃዱ አሳልፎ ለመስጠት የፈቀደ ሞኝና ሰነፍ ነው ሊኾን የሚችለው። ይህ ደግሞ በራስ ላይ ራስን ጠላት እንደ ማድረግ ነው። ስለዚህ በጥንቃቄ እንኑር።
◈ ሰይጣን በተለያየ መልክ እየተገለጠ ወደ ልዩነትና ፀብ የሚወስድ መኾኑን ልብ ከማለት ጋር እኔ የማየው ብቻ ነው ትክክል ከማለት በፊት ጸሎት ማድረግ ወደ እግዚአብሔር መጮህ ያስፈልጋል። ብዙ ጊዜ ልዩነት እየመሰሉን የምንጣላባቸው ነገሮች ልክ እንዲሁ ናቸው። ወደ ልዩነት፣ ፀብና ክርክር፣ አለፍ ሲልም ወደ ጭቅጭቅ እና ድብድብ ድረስ የሚያደርሰን ለነገሮች ያለን የተቃረነ አረዳድ ነው። ኹላችንም ማንኛውንም ነገር በጸሎትና እግዚአብሔርን በመጠየቅ ብናደርገው እጅጉን ጠቃሚ ነው። ተቃራኒ የሚመስለን ነገር ኹሉ የጠላታችን የዲያብሎስ ወጥመድ መኾኑን እንረዳለን። የእኔ ብቻ ትክክል ነው፣ ያንተ ትክክል አይደለም እያሉ የሌሎችን ሐሳብም ኾነ ንግግር ለማድመጥ ፈቃደኛ አለመኾን ወደ ጭቅጭቅና ከዚያም አልፎ ደም እስከ ማፋሰስ ድብድብ የሚያደርስ መኾኑን ልብ ይሏል። እንዲህ ዓይነት የልዩነትና የፀብ ፈተና በገዳም እንኳን የማይቀር መኾኑን ኹል ጊዜ ልብ እንበል።
◈ ኹለቱ መነኮሳት ለጊዜው ባይረዱትም ዃላ ወደየልቡናቸው ሲመለሱ ያጣላቸው ሰይጣን እንደ ኾነ ተረድተው፡ ይቅር ተባብለው፡ አንዴ አለያይቷቸው ደም ያፋሰሳቸውን ጠላት እስከ ሞታቸው ድረስ ተዋግተው ድል አድርገውት እነርሱ በፍቅር በአንድነት ምድራዊ ሕይወታቸውን አጠናቀዋል። እንግዲያውስ እኛም እንደነርሱ ወደየ ልቡናችን ተመልሰን የተጣላን ይቅር ብንባባልና ወደ ልዩነት እና ፀብ የመራን ሰይጣን መኾኑን ተረድተን በፍቅርና ክርስቲያናዊ በኾነ አንድነት ብንኖር አሸናፊ መኾናችን በዚያ ይታወቃል። እግዚአብሔር ለኹላችንም ንጹሕ ልቡና አድሎ በፍቅር በአንድነት የምንኖርበትን ኃይል ያድለን።
#Subscribe #Like #Share
👇👇👇👇
www.youtube.com/@haileG2239
www.youtube.com/@pagumentube
ከመ የዋህ በግዕ፤ ወከመ ላሕም መግዝዕ መሥዋዕተ መድኃኒት ትኩን፤ ለቤዝዎ ስብእ ዘኃለፍከ ዐፀደ ግፍዕ፤ ስብሐት ለከ።
እንደ የዋህ በግ እና እንደ ተግዛ ላም፤
ሰውን ሁሉ ለማዳን መሥዋዕት ትሆን፤ ዘንድ በግፍ ቦታ ያለፍክ፤ ጌታ ሆይ ምሥጋና ይገባሀል።
#Subscribe #Like #Share
👇👇👇👇
www.youtube.com/@haileG2239
www.youtube.com/@pagumentube
