es
Feedback
የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

Ir al canal en Telegram

ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።

Mostrar más
2 641
Suscriptores
+324 horas
+177 días
+5630 días
Archivo de publicaciones
🔴#ስንክሳር ሐምሌ_10 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሐምሌ ዐሥር በዚህች ቀን #አቡነ_ሳሙኤል_ዘደብረ_ወገግ ልደታቸው ነው፣ ናትናኤል የተባለው #ቅዱስ_ስምዖን_ቀለዮጳ በሰማዕትነት አረፈ፣ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_ከላድያኖስ አረፈ፣ #ቅዱስ_አባት_ብስንዳ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_ሳሙኤል_ዘደብረ_ወገግ ሐምሌ ዐሥር በዚህች ቀን አቡነ ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ ልደታቸው ነው። ጻድቁ አቡነ ሳሙኤል እንድርያስና አርሶንያ ከሚባሉ የበቁ ደጋግ አባትና እናታቸው የተወለዱት በሸዋ ሀገረ ስብከት ቀድሞ ጽላልሽ ዛሬ ቡልጋ በሚባለው አውራጃ ነው፡፡ የወላጆቻቸው በጎ ምግባርና ሃይማኖት ቅዱስ ተክለሃይማኖትን ከደብረ ሊባኖስ አነሣስቶ በቤታቸው ሄደው እንዲስተናገዱ አድርጓል፡፡ ልጅ ስላልነበራቸው ያዝኑ ነበርና አቡነ ተክለሃይማኖትም በጸጋ እግዚአብሔር ተገልጾላቸው ‹‹እግዚአብሔር ጣዖታትን የሚሰብር፣ አጋንንትን በጸሎቱ የሚያርቅ፣ ሕዝብን ከኃጢአት በሽታ የሚያድን፣ ፈጣሪውን የሚያስደስት ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ›› ብለው ትንቢት ነግረዋቸዋል፡፡ በትንቢቱም መሠረት አቡነ ሳሙኤል ሐምሌ 10 ቀን 1248 ዓ.ም ሲወለዱ መልካቸው በአራት ልዩ ልዩ ሕብረ መልክ እየተለዋወጠ አንድ ጊዜ እንደ በረዶ፣ አንድ ጊዜ እንደ እሳት፣ አንድ ጊዜ እንደ ልምላሜና ቢጫ ሆነው ታይተዋል፡፡ አቡነ ተክለሃይማኖትም በአባቱ እንድሪያስ በኩል የሥጋ ዘመዱ ሲሆኑ የመንፈስ ቅዱስም አባት ሆኑትና በ40 ቀን ክርስትና አንስተው ስመ ክርስትናውን ‹‹ሳሙኤል›› አሉት፡፡ ትርጓሜውም ‹‹እግዚአብሔር ጸለቴን ሰማኝ›› ማለት ነው፡፡ ከሕፃንነትም ጀምረው በምግባር በሃይማኖት ኮትኩተው አሳድገው ለዲቁና አብቅተው በኋላም አመንኩሰውታል፡፡ ‹‹ደብረ ወገግ›› የሚለው ስያሜ የተገኘው ከመላእክት ነው፡፡ ድርሳነ ዑራኤል በሰፊው እንደሚያትተው ቅዱስ ዑራኤል የጌታችንን ደም በብርሃን ጽዋ ተቀብሎ ዓለምን እየረጨ ሲቀድሳት የያዘውን ጽዋ በደብረ አስቦ ቆሞ ሳለ ነው ጨልጦ ያንጠፈጠፈው፡፡ ያንጊዜም ደብረ አስቦን የብርሃን ውጋጋን ሲያጥለቀልቀው መላእክትም ‹‹ቦታውን ደብረ ወገግ›› (የብርሃን ተራራ) ብለው ሰይመውታል፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም ‹‹ወደፊት ፈጣሪውን የሚያገለግል ታላቅ ጻድቅ ይወጣባታልና ይህችን ቦታ ባርካት›› ብሎ ቅዱስ ዑራኤልን በነገረው መሠረት ባርኳት እንዳረገ ድርሳነ ዑራኤል ላይ በሰፊው ተጽፏል፡፡ በቦታው ላይ ብዙ ጊዜ የብርሃን ምሰሶ ተተክሎ መታየቱን የበቁ ገዳማውያን ብቻ ሳይሆኑ በከተማ ያሉና ለመሳለም ወደ ቦታው የሄዱ ደገኛ ሰዎችም በዐይናቸው ያዩትን ይናገራሉ፡፡ በገዳሙ ዙሪያ እጅግ በጣም ብዙ ስውራን ቅዱሳን እንዳሉ በግልጽ ይታወቃል፡፡ ንጉሥ ዓምደ ጽዮን በክፉዎች ምክር የአባቱን ሚስት እንጀራ እናቱን በማግባቱ ምክንያት አቡነ ፊሊጶስ ጋር ሆነው ያወገዙትን የቅዱስ ተክለሃይማኖትን ወገኖች በየአውራጃው በተናቸው፡፡ አቡነ ፊሊጶስንም ደሙ በምድር ላይ እስከሚንጣለል ድረስ ገርፈው ወደነበረበት ቤቱ ወሰዱት፤ ፊሊጶስም በሚሄድበት ቦታ ላይ ሳይደርስ በመንገድ ሞተ፡፡ እንድርያስ፣ አኖሬዎስና ተክለ ጽዮን ሁላቸው ከተከታዮቻቸው ጋር በሰማዕትነት አርፈው እነስድስተይ በምትባል ምድር ተቀበሩ፡፡ ጳጳሱን አቡነ ያዕቆብንም ደሙ በምድር ላይ እንደውኃ እስኪወርድ ድረስ ገርፈው ወደ ሀገሩ እንዲሰደደ አደረጉት፡፡ ከዚያም በኋላ ሃይማኖቱ የቀና ደግ ጻድቅ ንጉሥ ዳዊት በነገሠ ጊዜ አባታችን ሳሙኤል ዘወገግን አገኘውና ‹‹መማጸኛ እንዲሆነኝ በእንድርያስ መቃብር ላይ ቤተክርስቲያን ሥራልኝ›› ብሎ ለመነውና የሩፋኤልን ቤተ ክርስቲያን ሠራለት፡፡ የእንድርያስንም አጽም ከመቅደሱ ስር አኖረው፡፡ ንጉሡም በዚያ በእንደግብጦን አውራጃ ሁሉ ላይ ፓትርያርክ አድርጎ ሾመው፡፡ በእነስድስታይ አገር ላሉ ሰዎችም ሁሉ አባት ሆናቸውና የመንፈስ ቅዱስ ልጁንም ታዲዮስን መምህርና አባት አድርጎ ሾመላቸውና ጽላልሽ ሄዶ እናቱን ይዞ ጽጋጋ ምድረ ወገግ ወስዶ አመነኮሳት፡፡ አቡነ ሳሙኤል ወደ ምድረ ርስቱ ደብረ ወገግ እየሄደ በዚያ ያሉ ልጆቹን እያጽናና ወደ እንደግብጦን አውራጃም እየተመለሰ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን እያደረገ፣ ወንጌልን እያስተማረ፣ ጣዖት አምላኪዎችን ወደ ክርስትና እየቀየረ፣ አጋንንትንና መመለኪያ ቦታዎቻቸውን እያጠፋ፣ አብያተ ክርስቲያናትን እያነጸ በብዙ ተጋድሎ ኖረ፡፡ በቅዱስ ገድሉ ውስጥ በጣም አስገራሚ በሆነ መልኩ እጅግ ብዙ ታሪኮች ተጠቅሰዋል፡፡ እነዚህም ታሪኮች ውስጥ አቡነ ሳሙኤል በሀገራችን በጣም ብዙ ጣዖታትንና መመለኪያ ቤቶቻቸውን እያጠፉ፣ በሰዎች (በጠንቋዮች) ላይ፣ በዛፍና በባሕር ውስጥ አድሮ ይመለኩ የነበሩ ሰይጣናት አጋንንትን በሚያመልኳቸው ሰዎች ፊት እያጋለጡና እያዋረዱ ሰዎቹን አስተምረው አጥምቀው ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር እየመለሷቸው ቤተክርስቲያንም በመሥራት ሐዋርያትን መሰሉ፡፡ ሰይጣን አድሮባቸው የነበሩ ጠንቋዮች ይጠቀሙባቸው የነበሩ ዕቃዎችን ጻድቁ እየባረኩና እየቀደሱ ለቤተክርስቲያን መሥሪያና መጠቀሚያነት ያውሉት ነበር፡፡ ይህም ገና ሳይወለዱ በአቡነ ተክለሃይማኖት ትንቢት ተነግሮላቸው ነበር፡፡ አቡነ ተክለሃይማኖት ‹‹ጣዖታትን የሚሰብር፣ አጋንንትን በጸሎቱ የሚያርቅ፣ ሕዝብን ከኃጢአት በሽታ የሚያድን፣ ፈጣሪውን የሚያስደስት ደግ ልጅ ይሆናል›› ብሎው ትንቢት እንደተናገሩላቸው አቡነ ሳሙኤል በሰዎች፣ በባሕርና በዛፍ ላይ እያደሩ ይመለኩ የነበሩ በጣም ብዙ አጋንንትን አጠፏቸው፡፡ ጠንቋዮችንም በውስጣቸው ካደረባቸው ሰይጣን እያላቀቁ የእግዚአብሔር አገልጋይ ያደርጓቸውና ያመነኩሷቸው ነበር፡፡ ጻድቁ አባታችን አባ ሳሙኤል ወንጌልን ዞረው በማስተማር ሐዋርያትን መሰሉ፣ ከዓላውያን ጋር ለመዋጋት ሰውነታቸውን ለሞት በመስጠት ሰማዕታትን መሰሉ፣ በጾም በጸሎት በስግደት በተጋድሎ ቅዱሳን ጻድቃንን መሰሉ፣ ይህን ኃላፊና ጠፊ ዓለም ንቀው በመተው ባሕታውያንን መሰሉ፣ በደልንና ኃጢአትን በማስተሠረይ ካህናትን መሰሉ፣ በጽሕናና በቅድስና መላእክትን መሰሉ እንደዚሁም ሌሎች ብዙ አስደናቂ ተአምራትንም በማድረግ ይታወቃሉ፡፡ በትእምርተ መስቀል አድርገው እንደሙሴ ባሕርን ለሁለት ከፍለዋል፣ እንደ ኢያሱ በጸሎታቸው ፀሐይን አቁመዋል፡፡ አቡነ ሳሙኤል ተጋድሎአቸውን ፈጽመው ከጌታችን ታላቅ ቃኪዳን ተቀብለው ጥቅምት ሃያ ዘጠኝ በሰላም ዐርፈዋል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ናትናኤል_ሐዋርያ (ቀናተኛው ስምዖን) በዚህች ቀን ናትናኤል የተባለው ቅዱስ ሐዋርያ ስምዖን ቀለዮጳ በሰማዕትነት አረፈ፡፡ ይህንንም ሐዋርያ አይሁድ የጌታችንን ወንድም ያዕቆብን ከገደሉት በኋላ ለኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ አድርገው ሐዋርያት ሾሙት። እርሱም ክብር ይግባውና ስለ ጌታችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ አስተምሮ ከአይሁድ ብዙዎችን ጌታችንን ወደማመን መለሳቸው ተአምራትንም አድርጎአልና በሽተኞችንም አድኗልና።  ንጉሡ እንድርያስም ሴቶችን ከባሎቻቸው እንደሚለይ ንጽሕናቸውንም እንዲጠብቁ እንደሚአዝዛቸው ስለ እርሱ ሰማ ወደርሱም አስቀርቦ ጽኑ ሥቃይን አሠቃየው ማሠቃየቱንም በሰለቸ ጊዜ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ ከእርሱም ጋር ቴዎና የምትባል አንዲት ድንግል ተገደለች። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ከላድያኖስ_ሊቀ_ዻዻሳት በዚህችም ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ዘጠነኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ ከላድያኖስ አረፈ።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ፱ ኤጲስ ቆጶሳትን ሾመች። ሐምሌ ፳፱ ቀን ፳፻፲፭ ዓ/ም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ለዘጠኝ አህጉረ ስብከት የተመረጡት ፱ ቆሞሳት ዛሬ ሐምሌ ፱ ቀን ፳፻፲፭ ዓ/ም በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም በተፈጸመ ሥርዓት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት እና በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት አንብሮተ እድ በኤጲስ ቆጶስነት ተሹመዋል። ከሌሊቱ ፱ ስዓት ጀምሮ በተከናወነው ሥርዓተ ሢመት ላይ የተለያዩ የሃይማኖት መሪዎች።፣ ግብዣ የተደረገላቸው የክብር እንግዶች፣ ከየአህጉረ ስብከቱ የመጡ ሊቃውንት፣ የሥራ ኃላፊዎች እና ምእመናን ተገኝተዋል። በዚህም መሠረት የሚከተሉት አባቶች በቅድስት ቤተክርስቲያን የተሰጣቸውን ሥያሜ ይዘው ለተጠቀሱት አህጉረ ስብከት ተመድበዋል። ፩-  ቆሞስ አባ ክንፈገብርኤል ተክለማርያም ብፁዕ አቡነ ገሪማ ተብለው ተሠይመው ጌዴኦ አማሮና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ፪-  ቆሞስ አባ ሣህለማርያም ቶላ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል ተብለው ተሠይመው ለምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ፫-  ቆሞስ አባ ስብሐትለአብ ኃይለማርያም ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ተብለው ተሠይመው ዳውሮና ኮንታ ሀገረ ስብከት ፬-  ቆሞስ አባ አምደሚካኤል ኃይሌ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ተብለው ተሠይመው ምሥራቅ ወለጋ ሀገረ ስብከት ፭-  ቆሞስ አባ ኃይለማርያም ጌታቸው ብፁዕ አቡነ በርተሎሜዎስም ተብለው ተሠይመው በድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ፮- ቆሞስ አባ ጥላሁን ወርቁ ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም ተብለው ተሠይመው በቡኖ በደሌ ሀገረ ስብከት ፯-  ቆሞስ አባ ዘተክለሃይማኖት ገብሬ ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ ተብለው ተሠይመው በሆሮ ጉድሩ ሀገረ ስብከት ፰-  ቆሞስ አባ እስጢፋኖስ ገብሬ ብፁዕ አቡነ ዳንኤል ተብለው ተሠይመው በምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት ፱-  ቆሞስ አባ ወልደገብርኤል አበበ ብፁዕ አቡነ ኒቆዲሞስ ተብለው ተሠይመው በምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ተመድበዋል። ምንጭ:- ኢኦተቤ ሕዝብ ግንኙነት ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው። https://t.me/finotebirhan12 የዩቲዩብ ቻናላችን https://youtube.com/@finotebirhan12

ከዚህም በኋላ ቅዱሱን በአሠሩት ጊዜ ከሴትዮዋ እጅ ምላሱን ተቀብሎ በሆዱ ላይ አኖራት ወዲያውኑም ምላሱ ተዘርግታ ወደ አፉ ገባች አንዲት ነጭ ርግብም መጥታ በቅዱሱ ላይ ዞረች ሁለተኛም ሶሪት ዎፍ መጥታ በላዩ ተቀመጠች እሊህ ሁለቱ መኳንንትም አይተው አደነቁ። ሉክዮስም ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመነ ያን ጊዜም መኰንኑ ድግናንዮስ ተቆጥቶ ከቅዱስ ታኦድሮስ ኋላ ይከተሉ የነበሩ ሦስት ሴቶችን ገደላቸው።  ከዚህም በኋላ ቅዱስ ታኦድሮስ ነፍሱን በሰጠ ጊዜ ርግቧና ሶሪት ዎፍ በርረው ሔዱ ድግናንዮስም አደነቀ ሉክዮስም የክርስቲያን ሃይማኖት የቀናች እንደሆነች አስረዳው ክብር ይግባውና በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ አመነ።  ከዚህም በኋላ ሁለቱ መኰንኖች ከቆሮንቶስ አገር በመርከብ እስከ ቆጵሮስ ሔዱ በዚያም ክርስቲያኖችን ሲአሠቃያቸው ሌላውን መኰንን አገኙ ሉክዮስም ከድግናንዮስ ተሠውሮ በመኰንኑ ፊት ቆመ የጣዖታቱንም መንበር ገለበጠ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ መኰንኑም ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበለ። ድግናንዮስም ሥጋውን ወስዶ ገንዞ ቀበረው።  ከዚህም በኋላ ድግናንዮስ በመኰንኑ ፊት ቁሞ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ ይህንንም በሰይፍ ራሱን ቆርጠው የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ኅልያን_ገዳማዊ  በዚህችም ቀን መስተጋድል አባ ኅልያን አረፈ። የዚህ ቅዱስ የአባቱ ስም ዲስጣ የእናቱ ስም ካልሞና ነው የአገሩም ስም ዐይነ ፀሐይ ይባላል። እርሱም ቀድሞ በወጣትነቱ ጊዜ የወርቅና የብር አንጥረኛ ነበር በሥራውም የተመሰገነ ነው።  በአንዲት ቀንም ከዐረብ አገልጋዮች አንዲት ሴት መጥታ ለጆሮዎቿ ጉትቻ እንዲሠራላት ለመነችው ከሠራላትም በኋላ የሠራበትን ዋጋ ከእርሷ ፈለገ። በፊቱም ራሷን ዘንበል አድርጋ ወንዶች ከሴቶች የሚሹትን ብትሻ እነሆኝ አለሁ ሌላ ገንዘብ ግን የለኝም አለችው። ይህንም በሰማ ጊዜም አንቺ የጨለማው አበጋዝ ልጅ ከእኔ ራቂ ፊትሽንም አታሳይኝ አላት።  ከዚህም በኋላ ሞትና ፍርድ መኖሩን ለነፍሱ እያሳሰባት በማደሪያው ውስጥ ጥቂት ቆየ። ተነሥቶም ለድኆችና ለችግረኞች ገንዘቡን መጸወተ ከገንዘቡም ከፍሎ ለእናቱ ሰጥቷት ተሰናበታት። ለሦስት ቀን የሚበቃውንም ስንቅ ይዞ ወደ ገዳም ሔደ እግዚአብሔርም የልቡናውን ንጽሕና ስለ አየ መራው የራቀውን ቦታ ወደ እርሱ አቀረበለት ወደ ኤርትራ ባሕር ዳርቻም በአንዲት ቀን ደረሰ።  ቆሞ ሳለም ነጭ ልብስ የለበሱና እንደ ፀሐይ የሚያበራ መስቀልን የተመረኰዙ ሦስት ሰዎች ተገለጡለት አነቁትና ከእሳቸው ጋራ ወሰዱት ወደ አትክልት ቦታም በደረሱ ጊዜ በትርና የዕንቁ መስቀል ሰጡት። በዚያም በአንድነት ጸለዩና ሰገዱ ከሰገደበትም ራሱን ቀና ባደረገ ጊዜ ከእርሳቸው ያገኘው አልነበረም በመለየቱም አዘነ አለቀሰም።  ከዚህም በኋላ ከአትክልቱ ቦታ ቅጠል እየበላ ውኃም ከርሷ እየጠጣ ኑሮውን በብሕትውና አደረገ። ወደ ቦታዎችና ወደ ዋሻዎች ለመሔድ የፈለገ እንደሆነም በትረ መስቀሉ ታበራለት ነበር። የረዘመውንም መንገድ ትጠቀልልለት ነበር ልብሱም ከእነዚያ ዛፎች ቅጠል ነበር።  የተረገመ ሰይጣንም ተጋድሎውን በአየ ጊዜ ሰው ተመስሎ ወደ ክፉዎች ሰዎች ሔደ እንዲህም ብሎ ነገራቸው በእገሌ በረሀ የተሠወረ ገንዘብ አለ የሚጠብቀውን ከያዛችሁት ታገኛላችሁ ወደዚያ ወንዝ ማዶም መርቶ አደረሳቸው በደረሱም ጊዜ መሻገሪያ መንገድ አጡ። እጅግም ተጠምተው ነበርና ውኃውን እያዩ ወደ ውኃው መድረስ ተሳናቸው።  ሁለተኛም በሚያስፈራ ዘንዶ ተመስሎ ቅዱስ ኅልያንን ውኃ ሲጠማቸው አንተ ለባልንጀሮችህ እንዴት አትራራም እንዴትስ ውኃ አታጠጣቸውም አለው በዚህ የሚይዙት መስሎት ነበርና። ለቅዱስ ኅልያንም በአውሬ አንደበት እግዚአብሔር የዘለፈው መስሎት ውኃ ቀዳላቸው ያጠጣቸውም ዘንድ ተሻገረ። እነርሱም ድኃነቱን አይተው ራሩለት ልብስ ሊሰጡትም ወደዱ እርሱ ግን አልተቀበላቸውም ወደ በዓቱም ተመለሰ።  ሰይጣንም ተንኰሉ በከሸፈበት ጊዜ በደጋጎች መነኰሳት ተመሰለ ሊአስቱትም ወደርሱ ሔዱ በመስቀል ምልክትም በማተበ ጊዜ አፍረው ተበተኑ ። የዕረፍቱም ሰዓት በቀረበ ጊዜ ቀድሞ ተገልጸውለት የነበሩ እነዚያ ሦስት ሰዎች መጥተው ገድሉን ጻፉ ባረፈ ጊዜም ቀበሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሐምሌ_9 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሐምሌ ዘጠኝ በዚህች እለት #ለአቡነ_እስትንፋሰ_ክርስቶስ ጌታችን ቃልኪዳኑን የሰጠበት ዕለት ነው፣ የአምስቱ አህጉር ኤጲስቆጶስ #ቅዱስ_ቴዎድሮስ በሰማዕትነት አረፈ፣ #ቅዱስ_ታውድሮስ በሰማዕትነት አረፈ፣ መስተጋድል #አባ_ኅልያን አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_እስትንፋሰ_ክርስቶስ ሐምሌ ዘጠኝ በዚህች እለት ለአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ጌታችን ቃልኪዳኑን የሰጠበት ዕለት ነው፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ አባታቸው መልአከ ምክሩ እናቱ ወለተ ማርያም ይባላሉ፡፡ የተወለዱበት ልዩ ቦታው ወሎ ክፍለ ሀገር ዳውንት ነው፡፡ በተወለዱ ዕለት ተነሥተው በእግራቸው ቆመው ሦስት ጊዜ ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ብለው ፈጣሪያቸውን አመስግነዋል፡፡ የስማቸው ትርጓሜ የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ እስትንፋስ አንድም የክርስቶስ እስትንፋስ ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል እየጠበቃቸውና በመንገዳቸው ሁሉ እየመራቸው ነው ያደጉት፡፡ መንፈስ ቅዱስ ልቡናቸውን ብሩህ አድርጎላቸው በ5 ዓመታቸው የቅዱሳት መጻሕፍት ቃላትን፣ ብሉያትንና ሐዲሳትን፣ድርሳናትንም ጠንቅቀው ዐውቀዋል፡፡ በተወለዱ በ14 ዓመታቸው ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ደብረ ሐይቅ ገዳም ሄደው ከባሕር ዳር ቆመው የሙሴን ጸሎት ወደ እግዚአብሔር በጸለዩ ጊዜ የታዘዘ መልአክ መጥቶ ባሕሩን አሻግሯቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተዋል፡፡ ለ3 ዓመታት ያህል በኃይቅ ገዳም ለመነኮሳት እንጨት በመልቀምና ውሃን በመቅዳት ለአባቶች መነኮሳት ምግብ የሚሆናቸው ዓሣ ከባህር ውስጥ በማውጣት አገልግለዋል፡፡ አባታችን እስትንፋሰ ክርስቶስ 40 መዓልትና 40 ሌሊት ከጾሙ በኋላ ምንም እህል ሳይቀምሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ ለሙሴ በደብረ ሲና እንደሰጠው ለአባታችንም ወደ እርሳቸው መጥቶ ዓሥሩን ቃላተ ኦሪትና ስድስቱን ቃላተ ወንጌል በውስጣቸው የተጻፈባቸው ሁለት ጽላቶችን ሰጥቷቸዋል፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ከሠሩ በኋላ ዕለቱን ስንዴ ዘርተው፣ ወይን ተክለው፣ ጽድን ወይራንና ግራርን ተክለው በአንዲት ቀን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ዕለቱን አድርሰዋል፡፡ ስንዴውን ለመሥዋዕት ወይኑን ለቍርባን በተአምራት አድርሰዋል፡፡ አባታችን በጸሎት ላይ እንዳሉ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተልኮ መጥቶ አባታችንን በደመና ጭኖ ወስዶ ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ፊት አቆማቸው፡፡ ጌታንም በቅዱሳኑ ሁሉ እንዲባረኩ ካደረጋቸው በኋላ መልአኩን "ወደ ተወለድኩባትና ወደ ኖርኩባት ቦታ ወደ ኢየሩሳሌም አድርሰው" ብሎት ኢየሩሳሌምን አሳልሞ ሀገራችን መልሶ አምጥቷቸዋል። አባታችን ሁሉንም የኢትዮጵያን ቅዱሳት ገዳማትን ተዘዋውሮ ሲጎበኙ በሕይወተ ሥጋ የሌሉት የየገዳማቱ ቅዱሳን ሁሉ በአካል ይገለጡላቸው ነበር፡፡ ጎጃም ውስጥ እያስተማሩ፣ እያጠመቁ፣ የታመሙትን እየፈወሱ፣ የዕውራንን ዐይን እያበሩና ሙታንን እያሥነሱ ብዙ ካገለገሉ በኋላ ለዘጠኝ ዓመታት በባሕር ውስጥ ገብተው ቁልቁል ተዘቅዝቀው ለኢትዮጵያ ጸልየው የምሕረት ቃልኪዳን በዚህች ዕለት ተቀብለዋል፡፡ ከዘጠኝ ዓመት በኋላ ጌታችን መጥቶ "ከመነኮሳት ሁሉ ብልጫ ያለህ ወዳጄ ሆይ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ምሬልሃለሁ ከዚህች ባሕር ውጣ" በማለት በሞት የሚያርፉበትን ቦታ ነግሯቸዋል፡፡ ጻድቁ ወደ ደብረ አሰጋጅ በሚሄዱበት ጊዜ ጸሐይ ልትገባ ስትል "በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አውግዤሻለሁ ለመስፍን ኢያሱ በገባኦን እንደቆምሽ አሁንም ቀጥ ብለሽ ቁሚ" ብለው ገዝተው ፀሐይን አቁመዋል፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስም ደብረ አሰጋጅ ሲደርሱ ፀሐይ አፍ አውጥታ "አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ እገባ ዘንድ ፍታኝ" ስትላቸው "እግዚአብሔር ይፍታሽ" ባሏት ጊዜ ጠልቃለች፡፡ ጻድቁ ሌላው በእጅጉ የሚታወቁበት አንድ ትልቅ ቃል ኪዳን አላቸው፡፡ በአምላክ ልቡና የሚገኝ፣ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ልቡና የሚገኝ፣ በቅዱስ ሚካኤልና በቅዱስ ገብርኤል ልቡና የሚገኝ እንደ መልክአ መድኃኔዓለም ያለች እጅግ አስገራሚ ጸሎት አለቻቸው፤ እርሷን ጸሎት በጸለዩ ጊዜ እልፍ ነፍሳትን ከሲኦል ያወጣሉ፡፡ ጸሎቷም የመድኃኔዓለምን የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች እያንዳንዱ የሰውነት ክፍሎቹ የተቀበሉትን ጸዋትዎ መከራዎች ሁሉ ታዘክራለች፡፡ በእያንዳንዱ ክፍልም የጸሎት ማሳረጊያ አቡነ ዘበሰማያት ይደግማሉ፡፡ ንስሓ የገባ ኃጢአተኛ ሰው እንኳን ቢሆን ይህችን የአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስን ጸሎት በጸለየ ጊዜ ሺህ ነፍሳትን ከሲኦል እንደሚያወጣ ጌታችን በማይታበል ቃሉ ለአባታችን ነግሯቸዋል፡፡ እያንዳንዱን የመድኃኔዓለምን የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች መከራዎቹን የምታዘክረውን ይህቺን በአምላክ ልቡና ያለች ግሩም የሆነች ጸሎት ነፍሳትን ከሲኦል አታወጣም ብሎ የሚጠራጠር ቢኖር መንግስተ ሰማያትን አያያትም፡፡ (ይህንን የአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስን ጸሎት የምናገኘው ከገድላቸው ላይ ነው፡፡) ጻድቁ ታኅሣሥ 8 ቀን ተወልው ሚያዝያ 9 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ቴዎድሮስ_ሰማዕት (ዘሐምስቱ አሕጉር)  ሐምሌ ዘጠኝ በዚህች ቀን የአምስቱ አህጉር ኤጲስቆጶስ ቅዱስ ቴዎድሮስ በሰማዕትነት አረፈ። ዲዮቅልጥያኖስም በካደና ጣዖትን በአመለከ ጊዜ ምእመናንን ያሠቃዩአቸው ዘንድ መኳንንቱን ወደ ሀገሮች ሁሉ ላከ። ለጣዖትም እንዲሰግዱ ያስገድዷቸው ነበር።  ስሙ ፍላጦስ የሚባል አንድ መኰንንም ወደ አፍራቅያ አገር መጣ። በዚህም ቅዱስ ለክርስቲያን ወገን መምህር እንደ ሆነ ነገር ሠሩበት መኰንኑም ወደርሱ አስቀርቦ ለአማልክት እንዲሠዋ አዘዘው።  ቅዱሱም እንዲህ ብሎ መለሰለት ሰማይና ምድርን የፈጠረ አምላክን ትተን ጣዖት ማምለክ አይግባንም። መኰንኑም በውኑ አርጤምስንና አጵሎንን አርዳሚስንም ሌሎች አማልክትንም ያይላቸዋልን ሌላ ነውን አንተ ይምትናገርለት አምላክ ካለ እነዚህስ አማልክት አይደሉምን አለው። ቅዱስ ቴዎድሮስም መልሶ አዎን አማልክት አይደሉም ክብር ይግባውና ከአንድ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር አምላክ የለም እርሱም ለፍጥረቶች ሁሉ ፈጣሪያቸው ነው አለው።  መኰንኑም ኃይለ ቃል ስለመመለሱ ተቆጥቶ አርባ ቀን በግርፋትና በስቅላት በእሥራትና በመንኰራኲራት እንዲአሠቃዩት አዘዘ። እርሱ ግን ትእዛዙን አልሰማም ከሥቃዩም የተነሣ አልፈራም። ከዚህም በኋላ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ። በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጀ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ታውድሮስ_ሰማዕት  በዚህችም ቀን ከቆጵሮስ አገር ቅዱስ ታኦድሮስ በሰማዕትነት አረፈ፡፡ ከእርሱም ጋራ ሦስት ሴቶችና ያሠቃዩት የነበሩ ሁለቱ መኳንንት ሉክያኖስና ድግናንዮስ አረፉ።  ይህም እንዲህ ነው ይህን ቅዱስ ወደእነዚህ መኰንኖች በከሰሱት ጊዜ እርሱ ክርስቲያንና የቆጵሮስ ኤጲስቆጶስ እንደሆነ ሰምተው ወደ እነርሱ አቀረቡት ስለሃይማኖቱም ጠየቁት። እርሱም ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ታመነ በበትሮችም እየደበደቡና እየገረፉ ቀጡት እርሱም እየዳኸ ሒዶ ጣዖቱን ረገጠው ከመንበሩም ላይ ገልብጦ ጣለው። እሊህ ሁለቱ መኳንንትም ተቆጥተው ጽኑ ሥቃይን አሠቃዩት ሥጋውንም በማቅ ጨርቅ ጨውና ኮምጣጣ ነክረው ፋቁት እርሱም ጣዖታቱን ይረግም ነበረ። ሁለተኛም ምላሱን ቆረጡት። ያን ጊዜም በዚያ ከነበሩ ሴቶች አንዲቱ ምላሱን አንሥታ ወሰደች።

አዲስ ለሚሾሙት ኤጲስ ቆጶሳት የጸሎተ አስኬማ ሥነ ሥርዓት ተከናወነ። በነገው ዕለት  ሐምሌ ፱ ቀን ፳፻፲፭ ዓ/ም ሢመተ ኤጲስቆጶስነት ለሚፈጸምላቸው ፱ ቆሞሳት የጸሎተ አስኬማ ሥርዓት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት መሪነት ብፁፅ አቡነ ጴጥሮስ (ዶ/ር) የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የኒዩወርክ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ አብርሃም የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የባህርዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ክቡር ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኮንን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት የመምሪያ ኃላፊዎች ጥሪ የተደረገላቸው የክብር እንግዶችና በርካታ ቁጥር ያላቸው ምእመናን በተገኙበት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ተከናወነ። በሥርዓተ ቤተክርስቲያን በተቀመጠው መሠረት አዲስ ለሚሾሙ ኤጲስቆጶሳት በሲመቱ ዋዜማ የሚፈጸመው ጸሎተ አስኬማ የደረሰላቸው ዘጠኝ ቆሞሳት ሰኔ ፳፱ቀን ፳፻፲፭ ዓ/ም በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተመረጡና በነገው ዕለት ሥርዓትተ ሢመተ ኤጲስ ቆጶስና ተፈጽሞላቸው በዘጠኝ አህጉረ ስብከት የሚመደቡ ናቸው። በዛሬው ዕለት በተፈጸመው ጸሎተ አስኬማ  ለሥርዓቱ የተሠራው ጸሎት በቅዱስነታቸው መሪነት ከደረሰ በኋላ ቡራኬ የተሰጠበትን ቅናተ ዮሐንስ ቅዱስነታቸው ለተሿሚ ቆሞሳት አስታጥቀዋል። ሥርዓቱ ከደረሰ በኋላ  በቅዱስነታቸው ቃለ ምዕዳንና ጸሎት ተጠናቋል። ምንጭ: ኢኦተቤ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ

በዚያን ጊዜም እሊህ ቅዱሳን ስለዚህ ስለ ኃላፊው ዓለም ፍጻሜና በመንግሥተ ሰማያት ስላለው ዘለዓለማዊ የተድላ ደስታ ኑሮ አሰቡ።ከዚህም በኋላ ተስማምተው ወደ እስክንድርያ ከተማ ሔዱ በመኰንኑም ፊት ቁመው ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ መኰንኑም ከእሳት እንዲጨምሩአቸውና ከላም ቆዳ በተሠራ ጅራፍ ደማቸው እስኪፈስ ድረስ እንዲገርፉአቸው አዘዘ። ዳግመኛም ስለታምና ረጃጅም በሆኑ ችንካሮች ሥጋቸውን ቸንክረው ከታች እሳትን አነደዱባቸው ጌታችንም መልአኩን ልኮ ከእሳቱ አዳናቸው። እንደገናም በታላቅ ዛፍ ላይ ዘቅዝቀው ይሰቅሏቸው ዘንድ አዘዘ። ከአፍንጫቸውና ከአፋቸው ብዙ ደም ወረደ ጌታችን ፈጣሪያችንም ከመላእክቱ ጋራ ወርዶ አዳናቸው መኰንኑም በፊቱ በቆሙ ጊዜ ከጽናታቸው የተነሣ እጅግ አደነቀ። ከዚህም በኋላ ወደ ሀገረ ፈርማ ላካቸው መኰንኑም ለአማልክት ዕጣን አጢሱ አላቸው እምቢ በአሉትም ጊዜ ከኮምጣጤና ከሙጫ ጋራ ጨው ደባልቆ አፍልቶ በአፋቸውና በአፍንጫቸው ጨመረ እነርሱም ይህን ሁሉ ሥቃይ ታገሡ። ከዚህም በኋላ በብረት አልጋ ላይ አስተኝተው ከታች እሳትን አነደዱባቸው የእጆቻቸውንና የእግሮቻቸውንም ጥፍሮች አወለቁ በብረት በትሮችም አጽንተው መቷቸው። በዚያን ጊዜም የመኰንኑ ሚስት ሞተች እርሱም ደንግጦ ይቅር እንዲሉት ሚስቱንም እንዲአስነሡለት ቅዱሳኑን ለመናቸው። እነርሱም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመኑት ያን ጊዜም ተነሣች መኰንኑም ከሕዝቡ ሁሉ ጋራ በጌታችን አመነ ቅዱሳኑንም ወደ ሀገራቸው ይሔዱ ዘንድ ለቀቃቸው። ወደ ሀገራቸው ወደ ገምኑዲም በደረሱ ጊዜ የቀረ ገንዘባቸውን ለድኆችና ለችግረኞች ሰጡ የቅዱስ አንያኖስንም ሥጋ ስሙ ሰረባሞን ለሚባል አንድ ጻድቅ ሰው አደራ አስጠበቁት እንደቀድሞውም በፊቱ መብራትን እንዲአበራ አዘዙት። ከዚህም በኋላ በርሙን ወደሚባል አገር ሔደው በመኰንኑ ፊት ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። መኰንኑም እንዲገርፉአቸውና እንዲጐትቱአቸው አዘዘ ደማቸውም እንደ ውኃ ፈሰሰ ደንቆሮና ዲዳ የሆነች ሴትም መጥታ ከቅዱሳኑ ደም ወስዳ አፏንና ጆሮዎቿን ልቧንም ቀባች ወዲያውኑም ድና ተናገረች ሰማችም። መኰንኑ ግን አሠራቸው ከዚህም በኋላ እነርሱን ማሠቃየት በሰለቸው ጊዜ ራሶቻቸውን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘና ቆረጡአቸው። የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበሉ። በዚያም ከገምኑዲ አገር ሰረባሞንና ሌሎች ሰዎችም ነበሩ በበፍታና በከበሩ ልብሶች ገነዙአቸው መዓዛው ጣፋጭ በሆነ ሽቱም ቀቡአቸው ወደ አገራቸው ወደ ገምኑዲም ወሰዱአቸው። ከገምኑዲም ከተማ ውጭ በደረሱ ጊዜ ሥጋቸው የተጫነበትን ሠረገላ የሚስቡ እንስሶች ቆሙ። ሥጋችን በውስጡ ይኖር ዘንድ እግዚአብሔር የመረጠው ቦታ ይህ ነው የሚል ቃልን ከሰማይ ሰሙ በዚያም አኖሩአቸው። ከዚህም በኋላ ቤተ ክርስቲያን ሠሩላቸው ሥጋቸውንም ከቅዱስ አንያኖስ ሥጋ ጋር በውስጥዋ አኖሩ በገምኑዲ አገርም ድንቆችንና ተአምራቶችን እያሳዩ እስከ ዛሬ ድረስ አሉ። ለእኒህ ቅዱሳንም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስማቸውን ለሚጠራ መታሰቢያቸውንም እንደችሎታው ለሚያደርግ ኃጢአቱ ይሠረይለታል ሥቃይንም ከቶ አያይም ብሎ መከራ በሚቀበሉበት ጊዜ ቃል ኪዳን ሰጣቸው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አባ_በላኒ በዚህችም ቀን ከግብጽ ደቡብ አካ በሚባል አውራጃ ባራ በምትባል መንደር ይኖር የነበረ ቅዱስ ሰማዕት አባ በላኒ አረፈ። ይህም ቅዱስ ቄስ ነበር። የምእመናንን መከራቸውን የሰማዕታትንም መገደላቸውን በሰማ ጊዜ ገንዘቡን ሁሉ ለድኆችና ለችግረኞች ሰጥቶ ወደ እንዴናው ከተማ ሔደ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም በመኰንኑ ፊት ታመነ መኰንኑም ጽኑ የሆነ ሥቃይን ብዙ ቀን አሠቃየው ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ የሰማዕትነት አክሊልንም  ተቀዳጀ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ቢማ_ሰማዕት በዚህችም ዕለት ከላይኛው ግብጽ ከብህንሳ ከተማ አባ ቢማ በሰማዕትነት ሞተ። ይህም ሰው ባለጸጋና በጎ የሚሠራ ድኆችንም የሚወድ በሀገርም ላይ የተሾመ ነበር። በአንዲት ዕለትም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በራእይ ፊቱ ከፀሐይ ብርሃን እጅግ እየበራ አየው እንዲህም አለው ሰላም ለአንተ ይሁን ወደ መኰንኑም ሒደህ በስሜ ታመን። እኔ የክብር አክሊልን አዘጋጅቼልሃለሁና። ከእንቅልፉም በነቃ ጊዜ ተነሥቶ ገንዘቡን ለድኆችና ለችግረኞች ሰጠ። ከዚህም በኋላ ጸሎት አድርጎ ከቤቱ ወጣ  ሉቅያኖስ ወደሚባል መኰንንም ሒዶ በፊቱ ቁሞ ክብር ይግባውና  በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ። መኰንኑም በአየው ጊዜ ሹም እንደሆነ አውቆ ከእርሱ ንዋየ ቅድሳትን ፈለገ ዳግመኛም ለአማልክት እንዲሠዋ ፈለገ ቅዱሱም እንዲህ ብሎ መለሰለት ስለ ንዋየ ቅድሳት ከእኔ ልትሻ አይገባህም የረከሱ አማልክትንም ስለማምለክ ትእዛዝህን አልሰማም እኔ ሰማይንና ምድርን በውስጣቸው ያለውን ሁሉ የፈጠረ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን አመልከዋለሁና። መኰንኑም ይህን በሰማ ጊዜ ተቆጥቶ ምላሱን ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ ጌታችንም እንደ ቀድሞው ምላሱን መለሰለት።  ከዚህ በኋላ  በማበራያ ውስጥ አበራዩት በብረት ዐልጋ ላይም ቸንክረው በበታቹ እሳትን አነደዱ እግዚአብሔርም አዳነው ያለ ጉዳትም አስነሣው። ከዚህ በኋላ ወደ እስክንድርያ ከተማ ላከው ክብር ይግባውና ጌታችንም ተገልጾለት አጽናናው ከዚህም በኋላ በወህኒ ቤት ጨመሩት በዚያም ተአምራትን አደረገ። ጋኔን ያደረባት የአቅፋሃስ ሀገር ሰው የዮልያኖስ  እኅት ነበረች ቅዱስ ቢማም  ያንን ጋኔን ከእርሷ ላይ አወጣውና አሳደደው ዜናውም በሀገሩ ውስጥ በተሰማ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ብዙዎች አመኑ። መኰንኑም በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ በየአይነቱ በሆነ ሥቃይም  አሠቃየው በመንኰራኵርም የእጆቹንና የእግሮቹን ጥፍሮች አወለቁ በእሳት  በአጋሉት በብረት ሰንሰለትም አሥረው ጐተቱት። በውሽባ ቤት ማንደጃ ውስጥም ጣሉት ከዚህም ጌታችን አዳነው። ከዚህም በኋላ በአንገቱ ታላቅ ደንጊያ አንጠልጥለው በባሕር ውስጥ ጣሉት አሁንም ጌታችን አዳነው። ሁለተኛም ከእሳት ጨመሩት። ከዚህም ጌታችን አዳነው በእሳቱም መካከል እየጸለየ ቆመ። መኰንኑም ማሠቃየቱን በሰለቸ ጊዜ ወደ ላይኛው ግብጽ ሰደደው በዚያም ያሠቃዩት ጀመሩ ዘቅዝቀውም ሰቀሉት ከዚህም በኋላ በብረት ምጣድ ውስጥ ጨምረዉ በላዩ እሳትን አነደዱበት ጌታችንም ተገለጠለትና ከእሳቱ አዳነው። ከዚህም በኋላ ጌታችን ስሙን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ገድሉን ለሚጽፍ በስሙም ምጽዋት ለሚያደርግ  ሁሉ የዘለላም ሕይወትን ያድለው ዘንድ ቃል ኪዳንን ሰጠው። መኰንኑም ከማሠቃየቱ የተነሣ በደከመ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንደ አዘዘ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማይ ተቀበለ። የአቅፋሃስ ከተማ ሹም የሆነ የዮልዮስ ባሮችም ሥጋውን አንሥተው ወደ ሀገሩ ወሰዱት እስከ ስደቱ ዘመን ፍጻሜ ድረስም በመልካም ቦታ አኖሩት። ከዚህም በኋላ መልካም የሆነች ቤተ ክርስቲያንንና ገዳምን ሠሩለት ሥጋውንም በውስጧ አኖሩ ከእርሱም ታላላቅ ድንቆችና ተአምራት ተገለጡ  በሽተኞችም ሁሉ ይፈወሱ ነበርና። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው። https://t.me/finotebirhan12

በዚህችም ቀን አባ ኪሮስ የቀበረው የንጉሥ ልጅ ድኃ የነበረው አባ ሚሳኤል አረፈ። ዜናውም እንዲህ ነው። አባ ኪሮስ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ወደ ሳት ገዳም ሔደ። ከዚያም ደርሶ ቤተ ክርስቲያኒቱን ተሳለማት በዚያም አምላክን የወለደች የእመቤታችን የድንግል ማርያምን ሥዕል አየ። ከዐይኖቹም ዕንባ እያፈሰሰ እመቤቴ ሆይ አስቢኝ አላት ሥዕሊቱም ኪሮስ ሆይ መምጣትህ መልካም ነው ከዚህም አትለፍ የአባትህን ዐፅም ትጠብቅ ዘንድ ወደ ማደሪያህ ተመለስ እንጂ አለችው። አባ ኪሮስም ይህን ሰምቶ ከሥዕሏ ፊት ሰባት መቶ ሰግደትን ሰገደ። በዕብራይስጥም ቋንቋ እንግዳ ነህና በቃህ በምሕረት መዝገብም ተመዝግቦልሃል የሚለውን ቃል ሰማ። ከዚያም በአለፈ ጊዜ መነኰሳቱ መልኩ የተዋበ ሁለመናውም ያማረ እንደሆነ ተመለከቱ። እርስ በርሳቸውም እንዲህ ተባባሉ ይህ መነኵሴ ከመንግሥት ከተማ ከግብጽ አገር የመጣ ነው ሰውነቱ በጾምና በጸሎት አልጠወለገምና። እጅግም ነቀፉት አልተቀበሉትም።ነገር ግን ወደ ሌላ ወደሚንቁት ቦታ ሰደዱት። በዚያም መስፈርስ በሚባል ሕማም ለብዙ ጊዜ የታመመና በምድር ላይ የተጣለ ድኃ ሰውን አገኘ። በራስጌውም የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን በግርጌው ቅዱስ ገብርኤልን በቀኙም ሩፋኤልን በግራውም ሰዳካኤልን አየ። እነርሱም በክንፋቸው ጋርደውት ነበር ከሰውም ያለርሱ ያያቸው አልነበረም። በገዳዩች ፊት ሞትን የማይፈራ ጐበዝ እንዴት ነህ ብለው ሰላምታ ሰጡት። አባ ኪሮስም አደነቀ በልዕልና ነዋሪዎች ሆይ ከዚህ ለምን ተቀመጣችሁ አላቸው የህን ድኃ እንድንጠብቀው ከእግዚአብሔር ታዘናል አሉት አባ ኪሮስም እስከ መቼ ነው አላቸው። ከዚህ ድካም እስከሚአሳርፈው ድረስ ነው አሉት። ከዚህም በኋላ ወደ ታመመው ደኃ ተመልሶ በዚህ ቦታ ከኖርህ ምን ያህል ዘመን ነው አለው በሽተኛውም ሰላሳ አምስት ዓመት ነው አለው ሁለተኛም ከታመምክ ስንት ዓመት ነው አለው ሃያ ዓመት ነው ብሎ መለሰ።  አበ ምኔቱና የገዳሙ መነኰሳት ይጐበኙሃልን ብሎ ጠየቀው በሽተኛውም አባቴ ሆይ የለም አይጐበኙኝም ፊታቸውን ከአየሁ ዓሥራ አምስት ዓመት ይሆናል ብሎ መለሰ። አባ ኪሮስም ና ንገረኝ አባትህ ማነው እናትህስ ማናት አለው በሽተኛውም እንዲህ ብሎ መለሰ አባቴ የኬልቄዶን ንጉሥ እናቴም የራሕራሕ ንጉሥ ልጅ ናት። አባቴ ኪሮስ ሆይ እውነት እልሃለሁ በአባቴ ቤት ያሉ ሰዎች ወርቁንና ብሩን ቀጭኑንም ልብስ በእግሮቻቸው ይረግጡአቸዋል። አባ ኪሮስም ወደዚች ገዳም ማን አደረሰህ አለው ድውዩም እንዳንተ ያሉ ሁለት ሰዎች ወደ አባቴ ቤት መጥተው በዚያ አደሩ። እኩለ ሌሊትም ሲሆን ፊቱ ብሩህ የሆነ ሰውም ወደኔ መጣ ሚሳኤል ብሎ ጠርቶ ሲነጋ ተነሥተህ ከእነዚህ ቅዱሳን ጋራ ሒድ አለኝ በእንዲህ ያለ ሥራ ወጥቼ ወደዚህ ቦታ ደረስሁ ምንም በጎ ሥራ ሳልሠራም እንደ እነርሱ ሆንሁ። አባ ኪሮስም እኔ አጽናናሃለሁና ወንድሜ ሆይ ስማ ስሙ በብኑዳ የሚባል አንድ እጅግ ድኃ የሆነ በበረሃ የሚኖር መነኵሴ ነበረ። የበጎ ሥራ ጠላት ሰይጣን ወደርሱ መጥቶ አሳተው እግዚአብሔርም ሥጋውን ለአንበሳና  ለሰማይ ወፎች ሰጠ እርሱም በወገን የከበረ ከሮም ንገሥ በታች የሚገዛ የኬፋዝ ንጉሥ ልጅ ነበረ። ሁለተኛም እነግርሃለሁ የሮሜ ንጉሥ ልጅ የሆነ አንድ ድኃ ነበረ። እርሱም ከበትር ብቻ በቀር ከአባቱ ቤት ምንም ሳይዝ በቀስታ ወጣ ያንንም ሰው እኔ እጅግ አውቀዋለሁ። ከገዳም ወደ ገዳም ከተራራም ወደ ተራራ ይዞር ነበር ሞቱንም አላስተዋልኩም ሕይወቱንም  አላወቅሁም። ዳግመኛም አንድ የንጉሥ ልጅ ድኃ ነበረ። እርሱም በሰንበታት እነጂ በሌላ ቀን ምንም ሳይቀምስ ማቅ ለብሶ በቀንና በሌሊት ለጸሎት ይተጋ ነበር። በእንዲህ ያለ ሥራም ኑሮ አረፈ የብርሃን መላእክትም ነፍሱን ወስደው በመንግሥተ ሰማያት አኖሯት። አሁንም ወንድሜ የምነግርህን ስማ። የፈጣሪህ የእግዚአብሔርን ተግሣጽ አታድንቅ የወደደውን ይገሥጻልና ያም በሽተኛ ድኃ መነኰስ እውነት ነው ለእኔ ይገባኛል ሰለ ኃጢአቴም ይህን ተቀበልሁ ብሎ መለሰ። ይህንንም ብሎ ዝም አለ። በዚያች ሰዓትም ያን በሽተኛ በሞት ያሰናብተው ዘንድ አባ ኪሮስ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ።  ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በድንገት መጣ። እልፍ አእላፋት መላእክትም በዙሪያው ሆነው ከእርሱ ጋር ነበሩ ለጻድቃን ሞገሳቸውና ንጉሣቸው የሆነ አምላካችንን እናመስግነው ለችግረኞችም ተስፋ የሆነ አምላካችንን እናመስግነው  እያሉ ይዘምሩ ነበር። በዚህ ዓለም በገድል የደከሙ በእርሱ ደስ ይላቸዋል። አባ ኪሮስም በአየ ጊዜ በምድር ላይ ሰግዶ ጌታዬ ፈጣሪዬ ሆይ ወደዚህ ምን አመጣህ አለ ጌታችንም ስለ ጠራኸኝ መጣሁ አለው።  አባ ኪሮስም ይህ ሰው ፃዕር በዝቶበታልና ያርፍ ዘንድ አሰናብተው አለው። ጌታችንም  ምን ያህል እንደምወድህ የመላእክት ሠራዊት ያዩና ያውቁ ዘንድ ይቺን የገነት ተክል አበባ  ከእጄ ወስደህ በዚህ በሽተኛ በፊቱ ላይ ጣል አለው። አባ ኪሮስም ያንን የገነት ተክል አበባ ከጌታችን እጅ ተቀብሎ በበሽተኛው ፊት ላይ አኖረ ያን ጊዜም ነፍሱ ያለ ፃዕር በፍጥነት ወጣች መድኃኒታችንም ተቀብሎ ሳማት ከእርሱም ጋር በብርሃን ሠረገላ ውስጥ አስቀመጣት አውጥቶም በሰማያዊ ክብር አኖራት። አባ ኪሮስም እያደነቀ አለቀሰ ከዚህም በኋላ ወደ አበምኔቱ ሔዶ እነሆ ያ ድኃ ስለ አረፈ መቃብር ቆፍረው ይቀበሩት ዘንድ ከመነኰሳቱ እዘዝ አለው አበ ምኔቱም ምን ግዴታ አለብኝ አለው አባ ኪሮስም ትኩር ብሎ ተመለከተውና ይህ የሰይጣን ሥራ እንጂ የሰው ሥራ አይደለም አለው። ሰለ አስጨነቀውም ሰባት መነኰሳትን አዘዘለት እነርሱም ማዕጠንታቸውን ይዘው ተነሡ አባ ኪሮስም የሚአጥኑት አሉና የረከሱ ማዕጠንቶቻችሁን አስወግዱ።  በቦታቸውም ተዉአቸው ነገር ግን ቅበሩት ብሎ አማላቸው። ያን ጊዜም አራቱ የመላእክት አለቆች ሥጋውን በከርቤና በሚዓ አጠኑ መዓዛውም ያንን  በዓት መላው እነዚህ መነኰሳትም የሚያሸተን ምንድነው ይህ መነኰስ ሥራይን ያውቅ ይሆን ተባባሉ። ከዚህም በኋላ ሥጋውን ወስደው በዚያው ገዳም በእንግዳ መቃብር ቀበሩት ከመቃብሩም ጥሩ ውኃ ፈልቆ ለበሽተኞች ፈውስ ሆነ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱሳን_አቤሮንና_አቶም በዚህችም ቀን ዳግመኛ ከእስክንድርያ ከተማና ከገምኑዲ የሆኑ ቅዱሳን አቤሮንና አቶም በሰማዕትነት ሞቱ።  የእሊህም ቅዱሳን ወላጆቻቸው እግዚአብሔርን የሚፈሩ ምእመናን ነበሩ። ብዙ ምጽዋትንም ይሰጡ ነበር። የአባታቸውም ስም ዮሐንስ የእናታቸው ማርያም ነበር። አባታቸው በአረፈ ጊዜ የአቤሮን ዕድሜ ሠላሳ የአቶምም ዕድሜ ሃያ ሰባት ዓመት ነበረ። በቤተ ክርስቲያን አገልግሎትም የተፀመዱ ነበሩ የሚራሩም ነበሩ መጻተኞችንም በፍቅር ይቀበሏቸው ነበር በትሩፋት ሁሉና በበጎ ሥራ ፍጹማን ነበሩ። ፈርማ በሚባል አገር ብዙ ሰዎች በሰማዕትነት በሞቱ ጊዜ እሊህ ቅዱሳን ገንዘባቸውን ይዘው ለንግድ ወደ ፈርማ ሔዱ። የንጉሥ ጭፍሮችንም አገኟቸው ከእርሳቸውም ጋራ የሰማዕቱ የቅዱስ አንያኖስ ሥጋ ነበረ ለጭፍሮችም ብዙ ገንዘብ ሰጥተው ከጭፍሮች እጅ ወደ ቤታቸው ወሰዱት ከከበረ ደንጊያ በተሠራ ሣጥን ውስጥም አኖሩት በፊቱም ሁል ጊዜ የሚበራ መብራትን አኖሩ። ከሥጋውም ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶች ተገለጡ።

በዚህችም ዕለት በምዕራባዊ በረሀ የሚኖር ታላቅና ክቡር አባት የሆነው የአባ ኪሮስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ። ይህም ቅዱስ የታላቁ ንጉሥ ቴዎዶስዮስ ወንድሙ ነበር በከተማ ውስጥ የሚሠራውን ዐመፅ በአየ ጊዜ ገንዘቡን ሁሉ ትቶ ከሀገሩ ወጣ። ጌታቸንም መርቶ ወደዚች ምዕራባዊት በረሀ አደረሰው በውስጧም ብዙ ዘመናት ብቻውን ኖረ ከሰው ማንም አላየውም በዚህ ሁሉ ዘመን የዱር አራዊትም ቢሆኑ። በአስቄጥስም ገዳም ስሙ አባ ባውማ የሚባል አንድ ቄስ ነበረ እርሱም የንጉሥ ዘይኑን ልጅ ቅድስት ኢላርያን ሥጋዋን የገነዘ ነው። እርሱም እንዲህ አለ በቤተ ክርስቲያን ወስጥ እያለሁ አባ ባውማ ሆይ ተነሥ ወደ በረሀው ውስጥ ገብተህ ወደ ፀሐይ መግቢያ ሒድ ከቅዱሳን ሁሉ አብዝቶ ፈቃዴን የፈጸመውን የአንድ ገዳማዊ ሥጋ ትገንዝ ዘንድ የሚለኝን ቃል ከሰማይ ሰማሁ። ያን ጊዜም ደስ ብሎኝ ተነሣሁ በበረሀውም ውስጥ ሦስት ቀን ተጉዤ ከአንድ ገዳማዊ በዓት ደርሼ ደጁን አንኳኳሁ አንድ ሽማግሌ ገዳማዊም ከፈተልኝና እርስ በርሳችን ሰላምታ ተለዋወጥን በዚች በረሀ ሌላ ገዳማዊ አለን ብዬ ጠየቅሁት አዎን አለኝ። ሁለተኛም ስምህ ማነው አባቴ ሆይ በዚችስ በረሀ ውስጥ ምን ያህል ጊዜ ኖርክ አልሁት ስሜ ስምዖን ነው በዚች በረሀ የኖርኩትም ሰባ ዓመታት ነው አለኝ። ከእርሱ ዘንድም ወጥቼ  ሦስት ቀን ተጓዝኩ ሁለተኛም ስሙ ባሞን የሚባል ገዳማዊ አገኘሁ ሰላምታም ሰጠሁትና በዚች በረሀ ሌላ ገዳማዊ አለን አልሁት አዎን አለ አለኝ። አራት ቀንም ተጓዝኩ  ወደ አባ ኪሮስ በዓት ደረስኩ ቅዱስ አባት ሆይ ባርከኝ እያልኩ ደጁን አንኳኳሁ አባ ባውማ ሆይ መምጣትህ መልካም ነው ብሎ ከውስጥ ተናገረኝ። እግዚአብሔር ያከበረህ ሰው በሰላም በፍቅር ወደእኔ ግባ አለኝ ያን ጊዜ ገብቼ ከእርሱ ተባረክሁ በፊቱም የእግዚአብሔርን ጸጋ ክብር አየሁ የራሱ ጠጉርና ጽሕሙ እንደ በረድ የነጣ ነበር። ከዚህም በኋላ ተቀመጥሁ በብብቻውም አቀፈኝ እንዲህም አለኝ እነሆ ይችን ሰዓት እየጠበቅኋት በዚች በዓት ሃምሳ ሰባት ዓመት ኖርኩ ይህንንም ሲል ጥቂት ታመመና ተኛ እየደነገጠ ያቺን ሌሊት አደረ ሲነጋም በበዓቱ ውስጥ ታላቅ ብርሃን በራ ብርሃናዊ ሰውም ገባ በእጁም የብርሃን መስቀል አለ በአባ ኪሮስ አጠገብም ተቀምጦ ሳመዉ ባረከውም አጽናናው ሰላምን ፍቅርን አንድነትን አደረገለት ከእርሱም ተሠወረ እኔም ፈራሁ እንዲህ የሚበራ ይህን ክብር የተጐናጸፈ ይህ ማነው አልሁት። እርሱም ልጄ ሆይ ይህ የእግዚአብሔር ልጅ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ልማዱ ስለ ሆነ ሁልጊዜ ይመጣል ያጽናናኛልም አለኝ።  በቀዳሚት ሰንበት ዕለትም ዘጠኝ ሰዓት በሆነ ጊዜ እስከ ሰማይ የሚደርስ ታላቅ ጩኸትን ሰማሁ ከጩኸታቸውም ኃይል የተነሣ ምድር ተናወጸች። እኔም ይህ የምሰማው ጩኸት ምንድነው ብዬ ጠየቅሁት እርሱም ልጄ ሆይ ይህ በሲኦል የሚኖሩ የኃጥአን ጩኸት ነው ስለ ቅድስት ትንሣኤው የእሑድ ፀሐይ እስክትጠልቅ ድረስ እግዚአብሔር ያሳርፋቸዋልና ስለዚህም እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል አለኝ። በዚችም ዕለት ሐምሌ ሰባት ቀን ቅዱስ አባ ኪሮስ ጩኾ አለቀሰ ዛሬ በግብጽ አገር ታላቅ ምሰሶ ወደቀ ይኸውም የገዳማውያን አለቃ ቅዱስ አባ ሲኖዳ ነው አለ። ከዚህም በኋላ ከደዌው ጽናት የተነሣ እሑድ ሌሊት እጅግ ደነገጠ በበዓቱም ውስጥ እነሆ ታላቅ ብርሃን በራ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ገብቶ በአባ ኪሮስ ራስ አጠገብ ተቀመጠ። አባ ኪሮስም መድኃኒታችንን ጌታዬ ሆይ ይህን ሰው ባርከው አለው መድኃኒታችንም የመረጥሁህ አባ ባውማ ሆይ ጽና አትፍራም ሰላሜ በረከቴም ከአንተ ጋራ ይኑር። አሁንም ታማኝ አገልጋዬ የሆነ የዚህን የቅዱስ ኪሮስን ያየኸውንና የሰማኸውን ወደፊትም ዳግመኛ የምታየውንና የምትሰማውን ገድሉን ጻፍ አለኝ። ከዚህም በኋላ መድኃኒታችን አባ ኪሮስን እንዲህ አለው እነሆ አንተ ትሞታለህና አትዘን ሞትህ ሞት አይደለም የዘላለም ሕይወት ነው እንጂ። የገድልህን መጽሐፍ የሚጽፈውን ወይም የሚያነበውን የሚሰማውንም ሁሉ በምድርም መታሰቢያህን የሚያደርገውን ሁሉ በደብረ ጽዮን በሚደረገው የሽህ ዓመት በዓል ምሳ ከእኔ ጋር ይቀመጥ ዘንድ አደርገዋለሁ ከቅዱሳኖቼም ጋራ እቆጥረዋለሁ። የኃጢአቱንም መጽሐፍ ቀድጄ ስሙን በሕይወት መጽሐፍ እጽፋለሁ። ለመሥዋዕት የሚገባውንም ዕጣኑንና ወይኑን መብራቱንም መባ አድርጎ ለሚሰጥም በስምህም ለድኆችና ለችግረኞች ምጽዋትን ለሚያደርግ ዓይን ያላየውን ጆሮም ያልሰማውን በሰው ልቡናም ያልታሰበውን በጎ ዋጋ እኔ እጥፍ ድርብ አድርጌ እሰጠዋለሁ። በበኵር ቤተ ክርስቲያንም ሥጋዬንና ደሜን አቀብላቸዋለሁ በዚህም ዓለም ቤታቸውን እባርካለሁ። ልጆቻቸውን አሳድጋለሁ ከበጎ ነገር ሁሉ ምንም ምን አያጡም። አሁንም ከዚህ ዓለም ድካም ወደ ዕረፍት የዘላለም ተድላ ደስታ ወዳለበት ወደ ብርሃን ቦታ እወስድህ ዘንድ ጊዜው ደረሰ መድኃኒታችንም ይህን ሲናገር እነሆ ነቢዩና ዘማሪው ዳዊት መጣ መሰንቆውም ከእርሱ ጋራ ነበረች። ይቺ ዕለት በእርሷ ፈጽሞ ሐሤት እናደርግ ዘንድ እግዚአብሔር የሠራት ናት እያለ አመሰገነባት። መድኃኒታችንም አባ ኪሮስን እነሆ ዘማሪው ዳዊት መጥቷልና ይዘምርልህ ዘንድ የምትሻውን ንገር አለው። ዳዊትም ቅዱስ አባ ኪሮስን በየትኛው አውታር እንድዘምርልህ ትሻለህ ደግሞስ በየትኛው ዜማ በየትኛው ስልት በመጀመሪያው ነውን ወይስ በሁለተኛው ወይስ በሦስተኛው አለው። ቅዱስ አባ ኪሮስም በዐሥሩም አውታር በየስልታቸውና በየዜማቸው ልሰማ እሻለሁ አለ። ያን ጊዜ ዳዊት መሰንቆውን አዘጋጅቶ የጻድቅ ሞቱ በእግዚአብሔር ፊት የከበረ ነው አለ ዳግመኛም ጐለመስሁ አረጀሁም የሚወድቅ ጻድቅን አላየሁም አለ። ዳዊትም ድምፁን አሣምሮ ዘመረ መሰንቆውንም በስልት መታት። ያን ጊዜም የቅዱስ አባ ኪሮስ ነፍሱ ወጣች መድኃኒታችንም ተቀብሎ ሳማት ለመላእክት አለቃ ለሚካኤልም ሰጣት። እኔ አባ ባውማም የቅዱስ አባ ኪሮስን ሥጋውን ቀበርኩ ከበዓቱም በወጣሁ ጊዜ በረሀው በሰማይ ሠራዊት ተመልቶ አየሁ መድኃኒታችንም የቅዱስ አባ ኪሮስ ሥጋው ባለበት በዓት ላይ መስቀሉን አኑሮ ዘጋት። ከዚህም በኋላ መድኃኒታችን ለኔ ሰላምታ ሰጥቶኝ መላእክትና የመላእክት አለቆች በፊቱ እያመሰገኑና እየዘመሩ በታላቅ ክብር ዐረገ። የቅዱስ አባ ኪሮስን ነፍስ ከመድኃኒታችን ጋራ እንደዚህ አሳረጓት። እርሷም በተሰጣት ክብር ደስ እያላት ዐረገች። እኔም አባ ባውማ በዚያ ቦታ ብቻዬን ቀረሁ ተመልሼም ወደ አባ አሞን በዓት ደረስሁ። ከዚያም የሦስት ቀን መንገድ ተጉዤ ወደ አባ ስምዖን በዓት ደረስሁ። ከዚያም ሦስት ቀን ተጉዤ ወደ ቦታዬ ወደ አስቄጥስ ገዳም ደረስሁ። ለመነኰሳቱም ሁሉ ያየሁትንና የሰማሁትን ሁሉ የቅዱስ አባ ኪሮስን ገድሉን ስለ አባ ሲኖዳም ዕረፍት ትንቢት እንደ ተናገረ ነገርኋቸው። መነኰሳቱም ሰምተው እጅግ አደነቁ የተመሰገነ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት። እኔ አባ ባውማም የቅዱስ አባ ኪሮስን ገድሉን ጽፌ ለሚያነበውና ለሚሰማው ሁሉ መጽናኛ ይሆን ዘንድ ወደ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉና ወደ ገዳማትም ላክሁ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ሚሳኤል_ነዳይ

ስንክሳር ዘተዋሕዶ: #ሐምሌ_8 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሐምሌ ስምንት በዚች ቀን በጎ ስም አጠራር ያለው የዓለም ሁሉ ኮከብ የሆነው #ቅዱስ_አባት_አባ_ብሶይ አረፈ፣ታላቅና ክቡር አባት የሆነው #የአባ_ኪሮስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ፣ አባ ኪሮስ የቀበረው የንጉሥ ልጅ ድኃ የነበረው #አባ_ሚሳኤል አረፈ፣ #ቅዱሳን_አቤሮንና_አቶም በሰማዕትነት ሞቱ፣ ቅዱስ ሰማዕት #አባ_በላኒ አረፈ፣ #አባ_ቢማ በሰማዕትነት ሞተ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አባ_ብሶይ ሐምሌ ስምንት በዚች ቀን በጎ ስም አጠራር ያለው የአባ መቃርስ ገዳምና የዓለም ሁሉ ኮከብ የሆነው ቅዱስ አባት አባ ብሶይ አረፈ። ይህም ቅዱስ ከግብጽ አገር ስሟ ሰነስ ከምትባል አገር ነበር ሰባት ወንድሞችም ነበሩት እናቱም የእግዚአብሔር መልአክ እግዚአብሔር ያገለግለኝ ዘንድ ከሰባቱ ልጆችሽ አንዱን ስጪኝ ብሎሻል እያለ እንደሚያነጋግራት ራዕይን አየች። እርሷም ጌታዬ ሆይ የወደድከውን ውሰድ ሁሉም ገንዘቦቹ ናቸውና አለችው። መልአኩም እጁን ዘርግቶ የብሶይን ራስ ይዞ ለእግዚአብሔር መልካም ሥራ የሚሠራ ይህ ልጅ ነው አለ። ይህ ብሶይ የከሳና ሥጋው የኮሰሰ ነበርና እናቱ ለዚያ መልአክ ጌታዬ ሆይ እግዚአብሔርን የሚያገለግል ከእነዚህ አንዱን ጠንካራውን ውሰድ አለችው። መልአኩም እግዚአብሔር የመረጠው ይህ ነው አላት። ከዚህም በኋላ ከእርሷ ተሠወረ። በአደገም ጊዜ የምንኵስና ልብስ ሊለብስ ወደደ። ወደ አስቄጥስም ገዳም ሔደ በአባ ባይሞይ ዘንድም መነኰሰ እርሱም አባ ዮሐንስ ሐፂርን ያመነኰሰ ነው። ከዚህም በኋላ እጅግ ጽኑ የሆነ ተጋድሎን መጋደል ጀመረ ምንም ምን ሳይቀምስ አርባ ቀን እስከ መጨረሻው ሦስት ጊዜ ጾመ። በቀንና በሌሊት በጾምና በጸሎት እየተጋ ቅዱሳት መጻሕፍትን አዘውትሮ በማንበብ በመጻሕፍት ቃል ነፍሱን ያረካት ነበር። የእግዚአብሔርን ቃል እጅግ ይወድ ነበርና ከማር ከስኳርም እጅግ ይጥመው ነበርና በውኃ ዳርም እንዳለች ተክል ሆነ። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ያየው ዘንድ የተገባው ሆኖ ነበር ጌታችንም ብዙ ጊዜ ይገለጽለት ነበር። ከእርሱም ጋራ ይነጋገር ነበር። እርሱም እግሩን አጥቦ እጣቢውን ይጠጣው ነበር። በአንዲት ቀንም የመድኃኒታችንን እግሮቹን አጥቦ ግማሹን ጠጥቶ ግማሹን ለደቀ መዝሙሩ እንዲጠጣ ተወለት። ረድኡም በመጣ ጊዜ ልጄ ሆይ ተነሥና በኵስኵስቱ ውስጥ ካለው ውኃ ጠጣ አለው ረድኡም በልቡ በመቅጃው ውስጥ ካለው ከጥሩው ውኃ ለምን አይሰጠኝም አለ። ይህንም ብሎ ቸለል አለ። መምህሩ እንዳዘዘውም አልጠጣም ሁለተኛም ልጄ ሆይ ተነሥና ከኵስኵስቱ ያለውን ያንን ውኃ ጠጣ አለው። ግድ ጠጣ ባለውም ጊዜ ተነስቶ ወደኵስኵስቱ ሔደ። ነገር ግን ውኃ አላገኘም አባ ብሶይም የጌታችንን እግር እንዳጠበና ግማሹን ጠጥቶ ግማሹን እንዲጠጣ ለእርሱ እንደተወለት አስረዳው። በነገረውም ጊዜ እጅግ አዘነ ፍጹም ድንጋፄም ደነገጠ። አባ ብሶይም ረድኡን ራሱን እብድ አስመስሎ ወደሚኖር ወደ አንድ ጻድቅ ሰው ዘንድ ላከው እርሱም አረጋግቶ ወደ አባቱ ወደ አባ ብሶይ መለሰው። ድንጋጤውም ባልተወው ጊዜ ወደዚያ ጻድቅ ሰው ዳግመኛ ላከው በሔደም ጊዜ ሙቶ አገኘው አባ ብሶይም ለረድኡ ይህን በትሬን በላዩ አኑርና ተነሥተህ እንድታነጋግረኝ አባቴ አዞሃል በለው አለው ሔዶም የአባ ብሶይን በትር በዚያ ጻድቅ በድን ላይ አኖረ ወዲያውኑም ተነሥቶ ስማ ለአባትህም ታዘዝ ታዛዥ ብትሆን ይህ ድንጋጤ ባላገኘህም ነበር አለው ይህንንም ብሎ ተመልሶ ተኛ። በአንዲት ቀንም ከቅዱስ አባ ብሶይ ደቀ መዛሙርት አንዱ መጣ ወደ እርሱም ከመግባቱ በፊት ከሰው ጋራ ሲነጋገር ሰማው በገባ ጊዜም ከሰው ማንንም አላገኘም አባቴ ሆይ ከአንተ ጋራ ሲነጋገር የነበረ ማን ነው ብሎ ጠየቀው አባ ብሶይም እንዲህ ብሎ መለሰለት ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ወደኔ መጥቶ ይህ ታላቅ ክብር ለመነኰሳት እንዳላቸው አውቄ ቢሆን ኖሮ መንግሥቴን ትቼ መነኰስ በሆንኩ ነበር አለኝ እኔም ምን ጐደለብህ የጣዖትን አምልኮ አስወግደህ የቀናች ሃይማኖትን ሥልጣን አጽንተሃልና አልሁት። እርሱም መልሶ እንዲህ አለኝ እግዚአብሔር ይመስገን ክብርንስ እጅግ አብዝቶ ሰጥቶኛል ነገር ግን የመነኰሳትን ክብር ያህል አይሆንም እነርሱ በእሳት ክንፎች እየበረሩ ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት ሲገቡ አይቻቸዋለሁና አለኝ። እኔም እንዲህ አልሁት የእግዚአብሔር ፍርድ በእውነት ትክክል ነው ለእናንተ ቤቶች፣ ሚስቶችና ልጆች፣ ሀብትና ለዓለም የተዘጋጀው ሁሉ አሉአችሁ በእነርሱም ትጽናናላችሁ። መነኰሳት ግን ከዚህ ከተድላ ዓለም የተለዩና በሕይወታቸው ዘመን ሁሉ ችግረኞች ናቸው ስለዚህም ይህን ታላቅ ክብር እግዚአብሔር ሰጣቸው አልሁት። በአንዲት ዕለትም እግዚአብሔር አባ ብሶይን እንዲህ ብሎ ተናገረው ይህን ገዳም እንደርግቦች ማደሪያ አደርገዋለሁ። በውስጡም መነኰሳትን እመላለሁ። ቅዱስ አባ ብሶይም ጌታዬ ፈጣሪዬ ሆይ የበዙ ከሆነ ምግባቸውን ከወዴት ያገኛሉ አለው። ክብር ይግባውና ጌታችንም እኔ አስብላቸዋለሁ ምንም ምን እንዲአጡ አልተዋቸውም አለው። በሀገረ እንዴናው ስለሚኖር ስለ አንድ ገዳማዊ ሽማግሌ ተነገረ በትምህርቱ አምነው ወደ ርሱ ብዙ ሕዝቦች ተሰበሰቡ እርሱ መንፈስ ቅዱስ የለም ብሎ ተሳስቶ ነበርና። ብዙዎችም ተከትለውት ነበርና ቅዱስ አባ ብሶይም ይህን ነገር ሰምቶ ስለዚያ ገዳማዊ እጅግ አዘነ መስሚያውንም ሦስት ጆሮዎች አድርጎ ወደ ገዳመ እንዴናው ሔደ ከዚያ ገዳማዊ ሽማግሌ ጋራ ተገናኘ ብዙ ሕዝቦችንም በእርሱ ዘንድ አገኛቸው ሁሉም ለቅዱስ አባ ብሶይ ሰላምታ ሰጡት። መስሚያ ስለአደረጋቸው ስለ ሦስቱ ጆሮዎችም ጠየቁት እንዲህም አላቸው። ለእኔ ልዩ ሦስት አካላት አሉኝ ሥራዬ ሁሉ በእነርሱ አምሳል ነው በውኑ መንፈስ ቅዱስ አለን አሉት። ከብሉይና ከሐዲስ መጻሕፍትም ይተረጒምላቸው ጀመረ። ከሦስቱ አካላት አንዱ መንፈስ ቅዱስ እንደ ሆነ በመለኮትም አንድ እንደ ሆነ አብራራላቸው። ሁሉም ከስሕተት ተመልሰው ንስሓ ገቡ። ወደ ቀናች ሃይማኖትም ተመለሱ። ለአባ ብሶይም የዋህ ረድእ ነበረው የእጅ ሥራውንም ሊሸጥ በሔደ ጊዜ ከአሕዛብ ወገን አንድ ሰው አገኘ። ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የፅርፈት ቃልን እስከሚናገር ድረስ ከዕውነት መንገድ አሳሳተው። በተመለሰ ጊዜም በክርስትና ጥምቀት ያገኘው የልጅነት ክብር ከእርሱ እንደተለየው አባ ብሶይ ተመልክቶ ልጄ ሆይ በአንተ ላይ የደረሰው ምንድነው አለው። እርሱም ያ ሽማግሌ እንዳሳተው ነገረው አባ ብሶይም ስለርሱ ሰባት ቀን ሲጸልይ ሰነበተ በፍጻሜውም በክርስትና ጥምቀት የተሰጠው የመንፈስ ቅዱስ ልጅነት በርግብ አምሳል በላዩ ወርዶ በውስጡ ሲያድር አየ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም አመሰገነው። ረድኡንም እንዲጠነቀቅና የቀናች ሃይማኖቱን እንዲያጸና ልዩ ከሆነ ሰውም ጋር ስለ ሃይማኖት እንዳይነጋገር አዘዘው። የበርበር ሰዎችም ወደ አስቄጥስ ገዳም በመጡ ጊዜ ወደ እንዴናው ገዳም ሔዶ በዚያ ተቀመጠ ከዚህም በኋላ አረፈ። የመከራውም ወራት ጸጥ ባለ ጊዜ የቅዱስ አባ ብሶይን ሥጋ ከቅዱስ አባ ቡላ ሥጋ ጋር በአንድነት ወደ አስቄጥስ ገዳም አመጡ። ከሥጋውም ብዙዎች ድንቆችና ተአምራቶች ተገለጡ ዘመኑ አምሳ ሰባት ነበር። በአስቄጥስም ገዳም እየተጋደለ ሀያ ሰባት ዓመት ኖረ። በእንዴናው ገዳም ዐሥር ዓመት ኖረ ከመመንኰሱም በፊት በዓለም ውስጥ ሃያ ዓመት ተቀመጠ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_ኪሮስ_ጻድቅ

በዚችም ቀን የሮሜ ከተማ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አግናጥዮስ በሰማዕትነት ሞተ፡፡ እርሱም ከቅዱስ ጴጥሮስ በኋላ በከሀዲው ንጉሥ በጠራብያኖስ ዘመን ሆነ። ይህም ንጉሥ ስለ አባት አግናጥዮስ የጣዖት አምልኮን እንደሚአቃልል ሕዝቡንም ሁሉ እንደሚያስተምር ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደ ማመን እንደሚያስገባቸው በሰማ ጊዜ ወደ እርሱ አስቀርቦ ለአማልክት መሥዋዕት አቅርብ አለው ቅዱሱም እኔ ለረከሱ ጣዖታት አልሠዋም ብሎ መለሰለት። ንጉሡም ብዙ ቃል ኪዳኖችን በመግባት አባበለው በአልተቀበለውም ጊዜ ለአንበሳ ሰጠው ያን ጊዜም ቅዱስ አግናጥዮስ በቀናች ሃይማኖት እንዲጸኑ ሕዝቡን አዘዛቸው። ከዚህም በኋላ አንዱ አንበሳ ቀርቦ አንገቱን ያዘው ያን ጊዜም ክብር ይግባውና በጌታችን እጅ ነፍሱን ሰጠ። ከዚህ በኋላ ያ አንበሳ ወደ ሥጋው አልቀረበም ምእመናንም መጥተው ሥጋውን ወሰዱ በመልካም ቦታም አኖሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው። https://t.me/finotebirhan12 የዩቲዩብ ቻናላችን https://youtube.com/@finotebirhan12

ነው፡፡ የጻፈው በ1409 ዓ.ም እድሜው 52 በደረሰ ጊዜ ሲሆን በወቅቱም የዚህ መጽሐፍ ቅጅ በነጋድያን እጅ እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ ሄዶ ነበር፡፡ ዐፄ ይስሐቅ ለአባ ጊዮርጊስ ‹‹ምድረ ሰዎን›› የተባለውን የጳጳሳት መቀመጫ የነበረውን ሀገር በርስትነት ሰጥቶት ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ በምድረ ሰዎን ንጉሥ ይስሐቅ ክረምቱን ያሳልፍበት በነበረው ቦታ ላይ ቤተ ክርስቲያን ሠራ፡፡ በዚያም በማስተማርና በጾም በጸሎት ይተጋ ነበር፡፡ በጋሥጫ እያለ ዐፄ ይስሐቅ አስጠራው፡፡ በዚያ ጊዜ ንጉሡ የመናገሻ ማርያምን ቤተ ክርስቲያን አሠርቶ ስለነበር እንዲባርክለት ፈልጎ ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ ምንም እንኳን በዚያ ጊዜ ታሞ የተኛም ቢሆን ወደ ንጉሡ ተጓዘ፡፡ እዚያ ሲደርስ በጣም ተዳክሞ ነበር፡፡ ሥርዓቱን ለመፈጸምም አቅም አልነበረውም፡፡ ስለዚህም ንጉሥ ይስሐቅ በአልጋ ተሸክመውት እንዲዞሩና ቤተ ክርስቲያኗን እንዲባርካት አድርጓል፡፡ ቡራኬውን ከፈጸመ በኋላ ደቀ መዝሙሮቹን ሰብስቦ ‹‹ከሞትኩ አባቴ በጸሎተ ሚካኤል መከራ ወደ ተቀበለባትና እኔም ቤተ ክርስቲያን ወዳነፅኩባት ቦታ ወስዳችሁ ቅበሩኝ›› ሲል አዘዛቸው፡፡ ለደቀ መዛሙርቱ በቀናች ሃይማኖት እንዲጸኑ የመጨረሻ የስንብት ትምህርቱን አስተማራቸው፡፡ እነርሱም በአልጋ ተሸክመውት ወደ ጋሥጫ እያመሩ ሳለ በመንገድ ላይ ሐምሌ 7 ቀን 1417 ዓ.ም በ60 ዓመቱ ዐረፈ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ሲኖዳ ሐምሌ ሰባት በዚች ቀን ቅዱስ አባት የባሕታውያን አለቃ የሆነ መስተጋድል አባ ሲኖዳ አረፈ፡፡ ይህም ቅዱስ በግብጽና በአክሚም አውራጃ ስሟ ስንላል ከምትባል ሀገር ከላይኛው ግብጽ ነበር። ስለእርሱም የመላእክት አምሳል የሆነ አባ ሐርስዮስ ትንቢት ተናገረለት። እርሱም ስለ ገዳም አገልግሎት ከመነኰሳት ጋር ሲሔድ የዚህን የቅዱስ ሲኖዳን እናት ውኃ ለመቅዳት ወጥታ አገኛት። ወደርሷ ሒዶ ሦስት ጊዜ ራሷን ሳማትና እንዲህ አላት ዜናው በዓለሙ ሁሉ የሚሰማ የስሙ መዓዛ ከሽቱ የሚጥም የሆነ የሆድሽን ፍሬ እግዚአብሔር ይባርክ። እነዚያ መነኰሳትም በአዩት ጊዜ አድንቀው አባታችን አንተ የሴት ፊት ማየት ከቶ አትሻም ነበር ዛሬ ግን ከሴት ጋራ ትነጋገራለህ አሉት። ልጆቼ ሆይ ሕያው እግዚአብሔርን የእግዚአብሔርን ምሕረት ተስፋ የሚያደርግ ዓለሙ ሁሉ የሚጣፍጥበት ከዚች ሴት የሚወጣ የጨው ቅንጣት አለ አላቸው። አንድ በገድል የጸና ጻድቅ ሰው መነኰስ ነበረ እርሱም መልሶ አባ ሐርስዮስን እንዲህ አለው እግዚአብሔር ሕያው ነው አንተ ራሷን ትስም ዘንድ ወደዚያች ሴት በቀረብክ ጊዜ በእጁ የእሳት ሰይፍ የያዘ የእግዚአብሔርን መልአክ በዙሪያዋ አየሁት። ራሷንም በሳምካት ጊዜ ክብር ይግባውና የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ወዳጁ ሆይ ሰላምታ ይገባሃል ሲልህ ደግሞም ከዚች ሴት የሚወለደው የተመረጡ ቅዱሳንን ሁሉ ልባቸውን ደስ ያሰኛል ወልደ እግዚአብሔርም ከርሱ ጋር ብዙ ጊዜ ይነጋገር ነበር ሲል ሰማሁት አለ። በግንቦት ሰባት ቀን ይህ ቅዱስ አባ ሲኖዳ ተወለደ በአደገም ጊዜ አባቱ በጎች ስለነበሩት ለልጁ ለሲኖዳ እንዲጠብቃቸው ሰጠው ይህ ሲኖዳም ምሳውን ለእረኞች ሰጥቶ እስከ ማታ ድረስ ይጾም ነበር። በሌሊትም ከውኃ ዐዘቅት ውስጥ ወርዶ በዚያ ቁሞ እስቲነጋ ድረስ ሲጸልይ ያድር ነበር። በክረምትም ሆነ በቊር ሰዓት እንዲሁ ያደርግ ነበር። አባቱም የሲኖዳ እናት ወንድም ወደ ሆነው ወደ አባ አብጎል እጁን በላዩ ጭኖ ይባርከው ዘንድ ወሰደው። አባ አብጎልም በአየው ጊዜ የሕፃኑን እጅ አንሥቶ በራሱ ላይ አድርጎ ሲኖዳ ሆይ ባርከኝ ለብዙ ሕዝብ ታላቅ አባት ትሆን ዘንድ የሚገባህ ሁነሃልና አለው። አባቱም በአባ አብጎል ዘንድ ተወው። ከዕለታትም በአንዲቱ ቀን አባ አብጎል እንዲህ የሚል ቃል ከሰማይ ሰማ እነሆ ሲኖዳ ለዓለሙ ሁሉ አርሲመትሪዳ የባሕታውያን አለቃ ሁኖ ተሾመ። ይህም ሲኖዳ ለዓለሙ ሁሉ ብርሃን እስከሚሆን በበጎ አምልኮ ያለ ማቋረጥ በጾምና በጸሎት በስግደትና በመትጋት ታላቅ ተጋድሎ መጋደልን ጀመረ። ከዚህም በኋላ በአንዲት ቀን ለአባ አብጎል የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለትና የኤልያስን አስኬማ የሠለስቱ ደቂቅን ቆብና የመጥምቁ ዮሐንስን ቅናት አመጣለት። እንዲህም አለው እንድትጸልይና የምንኵስና ልብስ ለሲኖዳ እንድታለብሰው እግዚአብሔር አዝዞሃል። ያን ጊዜም አባ አብጎል ተነሥቶ ጸለየ የምንኵስና ልብስንም አለበሰው። ከዚህም በኋላ ተጋድሎውን አበዛ። ለመነኰሳት፣ ለመኳንንት፣ ለሕዝባውያንና ለሴቶች ለሰዎች ሁሉ መመሪያ የሚሆን ሥራትን ሠራ። በኤፌሶንም የሁለት መቶ ኤጲስቆጶሳት ጉባኤ ስለ ከሀዲው ንስጥሮስ በተደረገ ጊዜ ከማኅበሩ አባት ከሊቀ ጳጳሳት ቄርሎስ ጋራ ወደ ጉባኤው ሔደ ንስጥሮስም ከክህደቱ ባልተመለሰ ጊዜ አውግዘው ለይተው አሳደዱት። ከዚህ በኋላም ወደ ሀገራቸው በመመለሻቸው ጊዜ መርከበኞች ከሊቀ ጳጳሳቱ ጋራ አትሳፈርም ብለው አባ ሲኖዳን ከለከሉት እርሱም ወደ እግዚአብሔር በጸሎት ማለደ። ወዲያውኑም ደመና መጥታ ተሸከመችውና አባ ቄርሎስ በመርከቡ ውስጥ እያለ በበላዩ በአንጻሩ አደረሰችው። አባቴ ሆይ ሰላም ለአንተ ከአንተ ጋራ ላሉትም ይሁን ብሎ ሰላምታ አቀረበ። በመርከብ ያሉት ሁሉም ላንተም ሰላም ይሁን በጸሎትህም አትርሳን አሉት። እጅግም አደነቁ ለሚፈሩት ይህን ይህል ጸጋ የሚሰጥ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት። ወደ ገዳሙም ደርሶ ከልጆቹ መነኰሳት ጋራ የመንፈቀ ሌሊትን ጸሎት አደረገ። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ብዙ ጊዜ ወደርሱ እየመጣ ያነጋግረው ነበር። እርሱም የመድኃኒታችንን እግሩን ያጥበው ነበር እጣቢውንም ይጠጣ ነበር ጌታችንም ብዙ ምሥጢራትን ገለጠለት ትንቢቶችንም ተናገረ። ከዚህም በኋላ ፈጽሞ በአረጀ ጊዜ ሐምሌ ሰባት ቀን ተኛ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መጥቶ እያረጋጋው በእርሱ ዘንድ ተቀመጠ። ብፁዕ አባ ሲኖዳም ጌታችንን እንዲህ አለው ጌታዬ ፈጣሪዬ ልዩ ሦስትነትህንና ጌትነትህን ስለሚነቅፉ ከሀድያን ወደ ጉባኤው እሔድ ዘንድ እንዲጠሩኝ ሊቀ ጳጳሳቱ ወደ እኔ ልኳልና እንደቀድሞው ታጸናኛለህን። ጌታችንም በጸጋና በጥዑም ቃል እንዲህ ብሎ መለሰለት ወዳጄ ሲኖዳ ሆይ ሌላ ዕድሜ ትሻለህን። እነሆ ዕድሜህ ሁሉ መቶ ሃያ ዓመት ከሁለት ወር ሁኖሃል ዕድሜህ ዘጠኝ ዓመት ሲሆን አስኬማን ለበስኽ ከዚያ በኋላ መቶ ዐሥራ አንድ ዓመት ከሁለት ወር ኖርኽ አሁንስ ድካምህ ይብቃህ ይህንንም ብሎ ጌታችን በክብር ዐረገ። በዚያንም ጊዜም የቅዱሳን አንድነት ማኅበር ወደርሱ መጡ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ዳግመኛ አየው ልጆቹንም ክብር ይግባውና ለጌታዬ ለኢየሱስ ክርስቶስ እሰግድ ዘንድ አንሱኝ አላቸው አንሥተውትም ሰገደለት። ከዚህም በኋላ ዳግመኛ እንዲህ አላቸው ወደ እግዚአብሔር አደራ አስጠብቅኋችሁ ነፍሴም ከዚህ ከደካማው ሥጋዬ የምትለይበት ጊዜ ደርሷል እኔም ለአባታችሁ ለዊዳ እንድትታዘዙ አዝዛችኋለሁ ከእኔ በኋላ ጠባቂያችሁ እርሱ ነውና አላቸው። ለልጆቹም ይህን በተናገረ ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመረጥሁህ ሲኖዳ ሆይ ብፁዕ ነህ ቸርነቴም ይደረግልሃል በሕይወትህ ዘመን ሁሉ አንተ የምወደውን ሥራ ሠርተሃልና እንግዲህ ወደ ዘለዓለም ተድላ ታርፍ ዘንድ ወደእኔ ና አለው። ያን ጊዜም ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አግናጥዮስ

መኳንንቱም እጅግ ተደሰቱ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ሌላው ያጋጠመው ክርክር ቢቱ ከተባለው ሰው ጋር ያደረገው ክርክር ነበር፡፡ ቢቱ ‹‹በምጽዓት ጊዜ የሚመጣው ወልድ ብቻውን እንጂ አብና መንፈስ ቅዱስ አይመጡም›› የሚል ኑፋቄ ማስተማር ጀምሮ ነበር፡፡ ቢቱ ከዚህ ኑፋቄው በተጨማሪ የጥንቆላ ሥራም ይሠራ ነበር፡፡ ቢቱ በጥንቆላ ሥራው የተነሣ በቤተ መንግሥቱ ተቀባይነት የነበረው ሰው ነበረ፡፡ ይህን መሰሉን ተግባር አጥብቆ የተዋጋው ዘርዐ ያዕቆብ እስኪመጣ ድረስ ነገሥታቱ ምንም ክርስቲያኖች ቢሆኑ በዚህ መሰሉ ስንኩል ሕፀፅ ይዋጡ ነበር፡፡ ቢቱና አባ ጊዮርጊስ ወደ ንጉሥ ዳዊት ቀርበው በጉዳዩ ላይ መነጋገር እንደሚፈልጉ ገለጡ፡፡ ዐፄ ዳዊትም ጳጳሱና ሊቃውንቱ ባሉበት እንዲነጋገሩ ስለወሰነ ጳጳሱ እንዲመጡ አዘዘ፡፡ በዚህ ጊዜ ተንኮለኛው ቢቱ ከአባ ጊዮርጊስ ጋር ከተከራከረ እንደሚሸነፍ ስላወቀ ‹‹ንጉሡ የአባቶቻችንን ሃይማኖት ክዷልና አትምጣ›› የሚል ደብዳቤ በአባ ጊዮርጊስ ስም ጽፎ ጳጳሱን ሊጠሩ በሄዱት መልእክተኞች እጅ ላከ፡፡ ወድያውም ለዐፄ ዳዊት ይህንን ነገር አሳበቀ፡፡ ዐፄ ዳዊትም ፈጣን መልእክተኞች ልኮ የፊተኞቹ መልእክተኞች እንዲመለሱ አደረገና ደብዳቤው ተነበበ፡፡ የቢቱ ተንኮል ያልገባው ንጉሥ ዳዊት ይህን ደብዳቤ ሲመለከት አባ ጊዮርጊስን በደም እስኪነከር ድረስ እንዲደበደብ አድርጎ ወደ እስር ቤት አስገባው፡፡ ዐፄ ዳዊት እስኪሞትና ልጁ ቴዎድሮስ እስኪነግሥ ድረስም በዚያ ቆየ፡፡ ቢቱ ግን በመልአክ ተቀስፎ ሞተ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ግን በወኅኒ ቤት እያለ የከበሩ ቅዱሳን ሐዋርያት ጴጥሮስና ጳውሎስ እየመጡ ያጽናኑት ነበር፡፡ ‹‹ውዳሴ ሐዋርያት›› የተሰኘውንና ከሐምሌ 5 ጀምሮ በ12ቱም ወራት የሚመሰገኑበት የሐዋርያትን ምስጋና የያዘውን መጽሐፍ ያዘጋጀው በወኅኒ ቤት ሆኖ ጴጥሮስና ጳውሎስ ከጎበኙት ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡ አንድ ጊዜ አባ ጊዮርጊስ በእስር ላይ ሳሉ ንጉሡ ዐፄ ዳዊት መሞታቸው ተሰማ፡፡ ሰዎችም ወደ አባታችን መጥተው ‹‹ያሳሰረህ ንጉሥ ሞቷል›› በማለት ነገሩት፡፡ ይህንንም ተቻኩለው የነገሩት ያሰረው ንጉሥ መሞቱን ሲሰማ ይደሰታል ብለው ነበር፡፡ ነገር ግን አባ ጊዮርጊስ በታላቅ ሀዘን ውስጥ ሆኖ የሰጣቸው መልስ ‹‹አይ ንጉሡ ባይሞት እኔም እንደታሰርኩ ብቀር ይሻል ነበር፡፡ ንጉሡ ዐፄ ዳዊትኮ እኔን ባይወደኝ የአምላክን እናት እመቤታችንን ይወዳት ነበር›› አላቸው፡፡ ዐፄ ቴዎድሮስ አባ ጊዮርጊስን ከወኅኒ ቤት አውጥቶት በጥንቱ ቦታ አስቀመጠው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ግን የቤተ መንግሥትን ነገር ለመሸሽ ስለ ፈለገ በጋሥጫ ከመቀመጥ ይልቅ ርቆ ጥንት ወደ ነበረበት ወደ ዳሞት በመሄድ ማስተማር ጀመረ፡፡ ወደ ዳሞት ሲሄድ እግረ መንገዱን ወደ ደብረ ሊባኖስ ገብቶ የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን መቃብር ተሳልሟል፡፡ በዚያ ጊዜ የደብረ ሊባኖሱ አበ ምኔት እጨጌ ዮሐንስ ከማ ነበሩ፡፡ እርሳቸውም ሰባተኛው የደብረ ሊባኖስ እጨጌ ነበሩ፡፡ አባ ጊዮርጊስን በዕውቀቱ የሚቀኑበት፣ በችሎታው የሚመቀኙት ሰዎች ነገር ሠርተው ከንጉሥ ቴዎድሮስ ጋር ስላጣሉት እልም ካለ በረሃ እንዲጋዝ ተደረገ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ከግዞት የወጣው ዐፄ ቴዎድሮስ ሲሞት ነበር፡፡ የአባ ጊዮርጊስ ሌላው ተማሪ የነበረው ዐፄ ይስሐቅ በ1399 ዓ.ም መንግሥቱን ሲይዝ አባ ጊዮርጊስን ከግዞት አውጥቶ ወደ ጋሥጫ መለሰው፡፡ በዚያ ጊዜ አባ ጊዮርጊስ እድሜው 42 ዓመት ሲሆን በስደትና በጤንነት መታወክ የተነሣ ከባድ ጉዳት ደርሶበት ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ብዙውን ጊዜውን በጾም፣ በጸሎትና በድርሰት ያውለው ነበር፡፡ አንድ ቀን ቴዎድሮስ የተባለ መስፍን፣ ዳግመኛም የጦሩ አዛዥ የሚሆን፣ አባ ጊዮርጊስን ስለ ርትዕት ሃይማኖት በጠየቀው ጊዜ አባ ጊዮርጊስም ‹‹ፍካሬ ሃይማኖት›› የተባለውን መጽሐፍ ደርሶ ሰጠው፡፡ ንጉሡና የምሥጢር ሊቃውንት የሆኑ ካህናት ይህንን በተመለከቱና ባነበቡ ጊዜ ‹‹በእውነት ዮሐንስ አፈወርቅና አፈ በረከት የሆነው ቄርሎስ በዘመናችን ተነሥተዋል፡፡ ኢትዮጵያም ቍስጥንጥንያን መስላለች፣ ከእስክንድርያም በላይ ከፍ ከፍ ብላለች›› ብለው አደነቁ፡፡ ይህም ፍካሬ ሃይማኖት የተሰኘው ድንቅ ድርሰቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የምታምነውንና የምታወግዘውን በግልጽና በዝርዝር የጻፈበት መጽሐፍ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ በፍካሬ ሃይማኖት ድርሰቱ ላይ የዘረዘራቸው የመናፍቃን ስሞችንና ክህደታቸውን ስንምለከት በዘመኑ የነበሩ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ስለ ዓለም ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያላቸውን ዕውቀት በግልጽ ያሳየናል፡፡ አባ ጊዮርጊስ መከራ ያልተለየው አባት በመሆኑ አሁንም በቤተ መንግሥት የነበሩ ሰዎች የእርሱን መከበርና መወደድ አይፈልጉትም ነበር፡፡ በተለይም ‹‹ፍካሬ ሃይማኖት›› የተሰኘውን መጽሐፍ በመጻፉ በዚህም ዝናው የበለጠ ስለተነገረ እነርሱ በሁሉም ዘንድ መከበሩን አልወደዱትም ነበር፡፡ ስለዚህም ነገር ሠርተው ከዐፄ ይስሐቅ ጋር አሁንም አጣሉት፡፡ ዐፄ ይስሐቅ አባ ጊዮርጊስን አሳስሮ ውኃ ወደማይገኝበት ዓለታማ ቦታ አጋዘው፡፡ በዚያም በመከራ ለብዙ ጊዜ ኖረ፡፡ በዚያ እያለ ዘወትር በጸሎት አብዝቶ ይተጋ ነበር፡፡ እግዚአብሔርም ዐፄ ይስሐቅ ወደ ልቡናው እንዲመለስ አደረገ፡፡ ንጉሡ በአባ ጊዮርጊስ ላይ የፈጸመው ነገር ሁሉ ስለፀፀተው አገልጋዮቹን ጠርቶ አባ ጊዮርጊስን እንዲያመጡት አዘዘ፡፡ ነገር ግን እነዚያ ተንኮል ሠሪዎች የአባ ጊዮርጊስ መምጣት ተንኮላቸውን ስለሚያጋልጠው ‹‹አባ ጊዮርጊስ ሞቷል›› ብለው አስወሩ፡፡ ይህንን ሲሰማ ዐፄ ይስሐቅ ፈጽሞ አዘነ፡፡ አባ ጊዮርጊስም ሞቷል እየተባለ መወራቱን ከደቀ መዝሙሩ ስለ ሰማ በሕይወት የመኖሩን ዜና ጽፎ ለዐፄ ይስሐቅ እንዲያደርስለት መልእክቱን በአውሎ ንፋስ አሳስሮ ላከለት፡፡ አውሎ ንፋሱ ለአባ ጊዮርጊስ በመታዘዝ ደብዳቤውን ተሸክሞ በመሄድ ዐፄ ይስሐቅ በድንኳን ተቀምጦ በነበረ ጊዜ ጉልበቱ ላይ አስቀመጠው፡፡ ንጉሡ ምትሐት የተሠራበት ስለመሰለው ደነገጠና መኳንንቱንና ሕዝቡን ሰብስቦ ጉዳዩን ገለጠ፡፡ ወዲያውም ነፋሱ ያመጣለትን መልእክት እሳት አስነድዶ ከዚያ ውስጥ ቢጥለው ሊቃጠል አልቻለም፡፡ ወደ ውኃም ቢጨምረው አልጠፋም፡፡ በዚህ ተደንቆ ወረቀቱን ከፍቶ አነበበው፡፡ ደብዳቤው ከአባ ጊዮርጊስ የተላከ መሆኑን ሲያውቅ ዐፄ ይስሐቅ ደነገጠ፡፡ እነዚያን መልእክተኞች ይዞ ወደ ወኅኒ ከጨመራቸው በኋላ አባ ጊዮርጊስን ከግዞት ያወጡት ዘንድ ላከ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ወደ ቤተ መንግሥቱ ሲመጣ ንጉሡ በደስታ ተቀብሎ ማረኝ ብሎ ለመነው፡፡ አባ ጊዮርጊስም ይቅር አለው፡፡ ከዚህም በኋላ ደብዳቤውን በማን እጅ እንደ ላከው ጠየቀው፡፡ አባ ጊዮርጊስም ደብዳቤውን በሰው ሳይሆን በእግዚአብሔር ፈቃድ በነፋስ እንደ ላከው አስረዳው፡፡ ከግዞት ከተመለሰ በኋላ እመቤታችን ተገልጣለት መከራው ሁሉ እንደ ሐዋርያት መሆኑን ገለጠችለት፡፡ አእምሮውን ብሩህ፣ ልቡናውን ትጉኅ የሚያደርግ እጅግ ብዙ ምሥጢርም ነገረችው፡፡ ተሰናብታው ከሄደች በኋላ ‹‹እጅግ ብዙ መብራት አቅርቡ አምስት ፈጣን ጸሐፊዎችንም አምጡ›› ብሎ አዘዘ፡፡ ከዚህም በኋላ እርሱ እየነገራቸው እነርሱ እየጻፉ እረፍት ሳያደርጉ ሦስት ቀን ሙሉ አጽፎ ‹‹መጽሐፈ ምሥጢር›› የተሰኘውን መጽሐፍ ፈጸመ፡፡ አምስቱ ጸሐፍትም የየድርሻቸውን አጠናቅቀው በአንድ አደረጉት፡፡ አባ ጊዮርጊስም ይህን ተመልክቶ በእጅጉ አደነቀ፡፡ ‹‹እኔ የዚህን መጽሐፍ ቃል አልተናገርኩም፤ መንፈስ ቅዱስ በእኔ አፍ ተናገረ እንጂ›› ሲል በወቅቱ መስክሯል፡፡ የመጽሐፉንም ስም ‹‹መጽሐፈ ምሥጢር›› ብሎ የሰየመው ራሱ

ነበር፡፡ ጊዮርጊስም ባየ ጊዜ ወደ መሬት ወደቀ፡፡ እንደ በድንም ሆነ፡፡ እመቤታችንም አነሣችውና ‹‹ሳትጠይቀኝ መጽሐፌን ትጽፍ ዘንድ ለምን ደፈርህ?›› አለችው፡፡ ‹‹እኔ ወድጄህ ከእናትህስ ማኅፀን መርጬህ ለጴጥሮስ፣ ለጳውሎስና ለዮሐንስ አደራ ሰጥቼህ የለምን?›› አለችው፡፡ አባ ጊዮርጊስም ‹‹እመቤቴ ሆይ ይቅር በይኝ፣ ደስ የሚያሰኝሽ መስሎኝ ይህን ባለማወቅ ሠርቼዋለሁና›› አላት፡፡ እመቤታችንም ‹‹ወዳጄ ሆይ ይቅር ብየሃለሁ›› አለችው፡፡ ‹‹ልትጽፈው የወደድኸው መጽሐፍም እነሆ በእጄ አለ፣ ከአሁን በኋላ የተወደደ ልጄ በአንደበትህ ሊገልጸው ወዷል፡፡ ነገር ግን ከአርያም ከሰማይ ኀይልን እስክትለብስ ድረስ አትቸኩል፡፡›› ይህንም ብላው ከእርሱ ተሰወረች፡፡ ያን ጊዜም ልቡ እንደ ፀሐይ በራ፣ የመለኮትም ባሕር በኅሊናው አበራ፡፡ በመንፈስ ቅዱስም መስተዋትነት የተሰወረውን ሁሉ አየ፡፡ የመጀመርያው ድርሰቱ አርጋኖን የተሰኘውና በቅኔ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የሚያመሰግነው መጽሐፉ ነው፡፡ እግዚአብሔርን በሚወድ በንጉሥ ዳዊት ዘመንም አርጋኖን መጽሐፍን ይደርስና ይጽፍ ጀመረ፡፡ በሦስትም ስሞች ጠራው እነዚህም አርጋኖና ውዳሴ፣ መሰንቆ መዝሙር፣ ዕንዚራ ስብሐት ናቸው፡፡ ስለ መጽሐፉም ጣፋጭነት ንጉሡ ዐፄ ዳዊት ድርሰቱን በጣም ከመውደዱ የተነሣ በወርቅ ቀለም አጻፈው፡፡ ወርቁን የሚያንጸባርቅበት ድንጋይ (ዕንቊ) ባጣ ጊዜ እመቤታችን ማርያም በሌሊት ራእይ ዘማት በሚባል አገር እንዳለ ለጊዮርጊስ ነገረችው ኅብሩንም አሳየችው፡፡ አባታችን ጊዮርጊስም ከደረስኳቸውና ከተናገርኋቸው ድርሳናት ሁሉ አርጋኖን ውዳሴ ይጣፍጣል ይበልጣል አለ፡፡ ‹‹እንደዚሁም በፈጣሪው ቸርነት በእመቤታችን ረድኤት ብዙ ድርሳናትንና የጸሎት መጻሕፍትን ደረሰ፡፡ የእሊህም ድርሳናት ስማቸውና ቁጥራቸው በሊቃውንት ዘንድ የታወቀ ነው፡፡ እሊህም ውዳሴ መስቀል፣ መጽሐፈ ብርሃን፣ መጽሐፈ ሰዓታት የመዓልትና የሌሊት፣ መጻሕፍተ ቅዳሴያት ናቸው፡፡ ጸሎተ ፈትቶ (የፍታቴ ጸሎት) የሐዋርያት ማኅሌት፣ መልክአ ቊርባን፣ እንዚራ ስብሐት፣ አርጋኖን ውዳሴ፣ ፍካሬ ሃይማኖት፣ ውዳሴ ሐዋርያት፣ ኖኅተ ብርሃን ይኸውም ከመጽሐፈ አርጋኖን ጋር አብሮ የታተመው ነው፡፡ ፍካሬ ሃይማኖት፣ መጽሐፈ ምስጢር፣ ሕይወታ ለማርያም፣ ተአምኆ ቅዱሳን፣ ጸሎት ዘቤት ውስተቤት፣ ውዳሴ ስብሐት፣ ሰላምታ፣ ጸሎተ ማዕድ፣ ቅዳሴ እግዚእ ካልእ፣ መዝሙረ ድንግልና የመሳሰለው ነው፡፡›› ቅዱስ ገድሉ እንደሚናገረው የአባ ጊዮርጊስ ‹‹ድርሳናት ስማቸውና ቁጥራቸው በሊቃውንት ዘንድ የታወቀ ነው›› ብሎ ከጀመረ በኋላ በቁጥር የተወሰኑትን ድርሰቶቹን ብቻ ጠቅሶ መጨረሻ ላይ ‹‹… እና የመሳሰለው ነው›› ብሎ ይደመድመዋል፡፡ ሊቀ ብርሃናት መርቆሬዎስ አረጋ ደግሞ የአባ ጊዮርጊስ ድርሰቶች ከ12 ሺህ በላይ ቢሆኑም ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እየሰጡ ያሉት በጣም ጥቂቶቹ ብቻ መሆናቸውን በቅዱሳን ታሪክ መጽሐፋቸው ላይ ጠቅሰውታል፡፡ ሌሎች ሊቃውንት አባቶቻችንም የአባ ጊዮርጊስን ድርሰቶች ከግምት ባለፈ ሁኔታ በቁጥር ወስኖ ለማስቀመጥ አስቸጋሪ መሆኑን ይገልጣሉ፡፡ ይኸውም ወደፊት ራሱን የቻለ በቂና ብዙ ጥናት ማድረግ ሳያስፈልገን እንደማይቀር አመላካች ነው፡፡ የመጀመርያውን ድርሰቱን አርጋኖንን እመቤታችን አብዝታ ስለወደደችለት ዚማት በሚባለው ሀገር በነበረ ጊዜ ‹‹ከድርሰቶችህ ሁሉ እንደ አርጋኖን የምወደው የለም›› ብላዋለች፡፡ ከዚህ በኋላ የደረሰው ድርሰት ውዳሴ መስቀል ይባላል፡፡ ቀጥሎም መጽሐፈ ስብሐት ዘመዓልት ወዘሌሊት የተባለውን ወይም እርሱ ራሱ መጽሐፈ ብርሃን ብሎ የሰየመውን መጽሐፍ አዘጋጅቷል፡፡ መጽሐፉም የእግዚአብሔርን የምስጋናውን መንገድ ያበራል፣ አብርቶ ያመለክታልና፣ ልዑላነ ብርሃን የሆኑትን የማኅበረ ቅዱሳንንና የትጉኃንን የምስጋናቸውን መንገድ ያመለክታልና፣ የእመቤታችንንም የምስጋናዋን ጣዕም ይገልጣልና መጽሐፉ «መጽሐፈ ብርሃን» ተባለ፡፡ በዘመኑ በነበረው ልማድ ካህናቱ ቍርባን በሚያቀብሉ ጊዜ ሕዝቡ ወደ ካህናቱ መጥተው ሲቀበሉ ንግሥቲቱ ግን ካለችበት ድረስ ካህናቱ ሄደው ነበር የሚያቆርቧት፡፡ አባ ጊዮርጊስ ግን ‹‹ይህ ቁርባን ንጉሠ ነገሥት ነውና ንግሥቲቱ ወደዚህ መጥታ ልትቀበል ይገባታል እንጂ እኛ መሄድ የለብንም›› ሲል ተቃወመ፡፡ ይህ ነገር ንግሥቲቱንና አባ ጊዮርጊስን ስላጋጫቸው ዐፄ ዳዊት ችግሩን ለመፍታት አባ ጊዮርጊስን ወደ ሀገረ ዳሞት ንቡረ እድነት ሾሞ ላከው፡፡ ከዚህ በኋላ አባ ጊዮርጊስ ዋናው ትኩረቱ በድርሰቱ ላይ በማድረግ ወደ ጳጳሱ ወደ አቡነ በርተሎሜዎስ ዘንድ በመሄድ የቅዳሴ ድርሰት ለመድረስ እንዲፈቀድለት ጠይቆ ሲፈቀድለት የቅዳሴ ድርሰት ማዘጋጀት ጀመረ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ነገረ ሃይማኖትን ጠንቅቆ የተረዳና የሚያስረዳ ስለነበር በዘመኑ የተነሡ የሃይማኖት ክርክሮች ሁሉ እርሱ ከሌለ አይሳኩም ነበር፡፡ በዚያ ጊዜ በሸዋ በይፋት ራሳቸውን ቤተ እስራኤል እያሉ የሚጠሩ አይሁድ ነበሩ፡፡ ከአቡነ ዜና ማርቆስ ጀምሮ ብዙ መምህራን ወደነዚህ ሕዝቦች እየተሠማሩ ወንጌልን አስተምረዋል፡፡ አቡነ ዜና ማርቆስ ወደ ክርስትና ለተመለሱት ቤተ እስራኤላውያን በእመቤታችን፣ በቅዱስ ሚካኤል፣ በአባ ኖብና በሰማዕቱ በጊጋር ስም አራት አብያተ ክርስቲያናትን አሠርተው ነበር፡፡ ይህ ሁሉ ቢሆንም ቤተ እስራኤላውያኑ ሙሉ በሙሉ ወደ ክርስትና አልተመለሱም ነበር፡፡ ከእነዚህ አይሁድ መካከል አንዱ ከክርስቲያኖች ጋር በነገረ ሃይማኖት ለመከራከር ጥሪ አቀረበ፡፡ ‹‹ክርስቲያኖች ከረቱኝ ወደነርሱ ሃይማኖት እገባለሁ እኔ ከረታኋቸውም ወደኔ ሃይማኖት ይገባሉ›› ሲል ነገሩን ጥብቅ አደረገው፡፡ ዐፄ ዳዊት ይህን ጉዳይ ሲሰማ በጣም ስለ ተናደደ ሊቃነ ካህናቱን፣ ንቡራነ እዱንና የመጻሕፍት ዐዋቂዎችን ሁሉ ከየሀገሩ እንዲሰባሰቡ አዘዘ፡፡ ነገር ግን በዚህ ጊዜ አባ ጊዮርጊስ ታሞ አልጋ ላይ ነበር፡፡ አይሁዳዊው በአንድ ወገን መምህራኑ በአንድ ወገን ሆነው ክርክሩን ጀመሩ፡፡ የመጀመርያው እድል የተሰጠው ለአይሁዳዊው በመሆኑ ቀጥሎ ያለውን ጥያቄ አቀረበ፡- ‹‹እናንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነው የምትሉት ይሄ ክርስቶስ እውነት የእግዚአብሔር ልጅ ከሆነ፣ ወደ ቢታንያ በመጣ ጊዜ አልዓዛር የተቀበረበትን ቦታ ሳያውቅ ቀርቶ ‹አልዓዛርን የት ቀበራችሁት?› ብሎ እንደ ጠየቀ በወንጌላችሁ ተጽፏል፡፡ ለዚህ መልስ ስጡኝ፣ እኔንም ከመጽሐፈ ኦሪቴ ጠቅሳችሁ ጠይቁኝ?›› ሲል የመከራከርያ ነጥቡን አቀረበ፡፡ ሊቃውንቱም በዚህ ጊዜ ታሞ አልጋ ላይ የነበረውን አባ ጊዮርጊስን እንዲመጣላቸው ፈልገው ‹‹እንዲህ ያለው ነገር ያለ እርሱ አይሆንምና አባ ጊዮርጊስ ይምጣ›› ሲሉ ለዐፄ ዳዊት ጥያቄ አቀረቡ፡፡ አባ ጊዮርጊስም በአልጋ ላይ እያለ እንዲመጣ ተደርጎ በአልጋ ላይ ሆኖ በጉባኤው ላይ ተገኘ፡፡ ጉባኤተኞቹ የቀረበውን ጥያቄ በነገሩት ጊዜ አባ ጊዮርጊስ የሰጠውን መልስ እንዲህ የሚል ነው፡- ‹‹እኔ ግን በወንጌል ሳይሆን በኦሪት እከራከርሃለሁ፡፡ የምኩራብ መጻሕፍት ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን የታወቁ ናቸውና፡፡ ምኩራብ ዘራች ቤተ ክርስቲያንም አጨደችው፤ ምኩራብ ፈተለችው ቤተ ክርስቲያን ለበሰችው፤ አዳምን በገነት ሳለ አዳም ሆይ ወዴት ነህ? ብሎ የጠየቀው ማነው? አብርሃምንስ ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት? ብሎ የጠየቀው ማነው? እስቲ መልስልኝ? ሰይጣንንስ ከወዴት መጣህ? ብሎ የጠየቀው ማነው? እግዚአብሔር አብ አይደለምን?›› እያሉ የጥያቄ ዓይነት ባሽጎደጎዱለት ጊዜ አይሁዳዊው መልስ አጥቶ ዝም አለ፡፡ መልስ በማጣቱም አፈረ፡፡ ንጉሡ፣ ሊቃውንቱና

የእግዚአብሔር ሥራና ጌትነቱ በእርሱ ላይ ይገለጥ ዘንድ ነው እንጂ፡፡ ጸጋ ያለመከራ አይሰጥምና ያለመፈተንም ማብዛት አይቻልም፡፡ ጌታችንን ዕውር ሆኖ ስለተወለደው ሕፃን ደቀ መዛሙርቱ በጠየቁት ጊዜ ‹‹ይህ ሕፃን ዕዉር ሆኖ የተወለደው በማን ኃጢአት ነው? በራሱ ነውን ወይስ በወላጆቹ?›› አሉት፡፡ ጌታችንም ‹‹እርሱም አልበደለም፣ ወላጆቹም አልበደሉም፣ የእግዚአብሔር ሥራ በእርሱ ላይ ይገለጥ ዘንድ ነው እንጂ›› አላቸው፡፡ ዮሐ 9፡1፡፡ ሐዋርያትም መንፈስ ቅዱስ እስኪወርድላቸው ድረስ በትንሽ ዕውቀት ነበሩ፡፡ ‹‹በመጻሕፍት ያለውን ገና ዐላወቁምና›› ተብሎ እንደተጻፈ እንዲሁ አባ ጊዮርጊስም ዕውቀት ስለ ተሰወረውና ጓደኞቹ በትምህርት ሲቀድሙት ባየ ጊዜ እጅግ አዘነ፡፡ ስለዚህም በጾምና በጸሎት ወደ እግዚአብሔር መጮኽ ጀመረ፡፡ ሁልጊዜም በሥዕለ ማርያም ሥር እየተንበረከከ ጥበብን እንዲሰጠው ወደ እግዚአብሔር አብዝቶ በመለመን እንባንም በማፍሰስ ይጸልይ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ እመቤታችን ተገለጠችለትና አረጋጋችው፡፡ ዳግመኛም እንደምትመጣ ቀን ቀጥራው ከእርሱ ተሰወረች፡፡ በሰጠችውም ቀጠሮ መሠረት በነሐሴ 21ኛው ቀን እመቤታችን ሚካኤልና ገብርኤል በቀኝና በግራ ሆነው ኪሩቤልንና ሱራፌልን አስከትላ ተገለጠችለትና «አይዞህ ዕውቀት የተሰወረብህ ትምህርት ስለማይገባህ ሳይሆን የእግዚአብሔር ድንቅ ሥራ እንዲገለጥ ነው» አለችው፡፡ ‹‹የመረጥሁህ የልጄ ወዳጅ ጊዮርጊስ ብላ በስሙ ጠራችው፡፡ ከዕውቀት ወንዝ የመጣና ከጥበብ ምንጭ የተገኘ ከመለኮት ባሕር የተቀዳ ይህን ንጹሕ ጽዋ ንሣ ጠጣ›› በማለት ጽዋዓ ልቡናን አጠጣችው፡፡ ይኸውም ጽዋዕ ልቦና በዮሴፍ ቤት በጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት የጠጡት መንፈሳዊና ሰማያዊ መጠጥ ነው፤ በበዓለ ሃምሳ ከጠጡት ያልተለየ ነው፡፡ ይኸውም የሚናገር እሳት፣ የሚያድን እሳት፣ መለኮታዊ እሳት ነው፡፡ ከዚህም በኋላ አባ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያንን ያስጌጠበት የመጻሕፍትን ምስጢራት፣ የማኅሌትንና የድርሳናትን ቃል፣ ምስጋናዎችንም ሁሉ እመቤታችን ገለጠችለት፡፡ እመቤታችን ማርያም ለብፁዕ ጊዮርጊስ ጽዋውን ካጠጣችው በኋላ ያን ጊዜ አምስት የምሥጢር ቃላትን አስተማረችው፡፡ የኅሊናን ዓይኖች ያበራሉና የልቡናንም ጆሮዎች ይከፍታሉና፡፡ ከዚህ በኋላ ከእርሱ ተሰወረች፤ ከማይተኙ ከትጉሃን መላእክትም ጋር ወደ ሰማይ ዐረገች፡፡ የአምስቱ የምሥጢር ቃላት ትርጉምም ዕውቀትን የተመሉ መንፈሳውያን አባቶቻችን እንደ ነገሩን ከእመቤታችን ማርያም እጅ በተሰጠው በመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ትምህርት ሳይማር በአንድ ቀን የዳዊትን መዝሙር ማጥናት ነው፡፡ መዝሙረ ዳዊትን ግን ዕብራውያን በአምስቱ የስሜት ሕዋሳት ቁጥር ለአምስት ከፍለውታል፡፡ እነዚህም መስማት፣ ማየት፣ ማሽተት መቅመስና፣ መዳሰስ ናቸው፡፡ የመጀመሪያው ክፍል መጨረሻው 40ኛው መዝሙር ነው፤ የሁለተኛው ክፍል መጨረሻው 71ኛው መዝሙር ነው፡፡ ሦስተኛው ክፍል መጨረሻው 88ኛው መዝሙር ነው፤ አራተኛው ክፍል መጨረሻው 105ኛው መዝሙር ነው፡፡ አምስተኛው ክፍል መጨረሻው 150ኛው ነው፡፡ የእነዚህም ክፍላት መጨረሻ ለይኩን ለይኩን ባለ ጊዜ ይታወቃል፡፡ አባ ጊዮርጊስም የእነዚህን ምስጢር በልቡ ጠበቃቸው፡፡ አምስቱንም ቃላት በልቡ መዝገብነት ሰወራቸው፤ ሊገልጣቸው እግዚአብሔር አልፈቀደላትምና በተረዳ ነገር ግን መዝሙረ ዳዊት ነው፡፡ የገነትን ፍሬዎች ሁሉ የሰበሰበ መዝሙረ ዳዊት የገነት አምሳል ነውና አጋንንትን ያሳድዳል መላእክትንም ያቀርባል፡፡ እመቤታችንም ከእርሱ ተለይታ ካረገች በኋላ ከዚያችም ሰዓት ጀምሮ የልቡ ዓይን ተከፈተለት፡፡ ኅሊናውም በመንፈስ ቅዱስ ክንፎች ተመሰጠ፡፡ ወደ አብም ደረሰ፤ በዚያም ኢየሱስን በአባቱ ቀኝ ተቀምጦ ጰራቅሊጦስንም በአንድ አኗኗር አገኘው፡፡ ከዚህ በኋላ በሐይቅ እስጢፋኖስ የዜማ የቅኔና የመጻሕፍትን ትርጓሜ ትምህርቱን በሚገባ ተምሮ አጠናቀቀ፡፡ በዕውቀቱም ቀድሞ የሚያውቁት ሁሉ ይደነቁበት ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ የያሬድን ዜማ ከአቡነ ሳሙኤል ተማረ፡፡ በዚያ ዘመን በዐፄ ዳዊት አማካይነት በሰሜን ኢትዮጵያ የያሬድ ድጓ ዋና ማዕከል በሆነው በደብረ ነጎድጓድ ተሾሞ ያስተምር ነበር፡፡ የማስተማር ሥራውን የጀመረው በዚያው በሐይቅ እስጢፋኖስ ነበር፡፡ ከሐይቅ በኋላ በዚያ ዘመን ሸግላ በመባል ትጠራ ወደ ነበረችው ወደ ትውልድ ሀገሩ ወደ ጋሥጫ ተጓዘ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ወደ ሸግላ ሲመጣ አባቱ በጣም አርጅቶና መንኩሶ ነበር፡፡ ስለዚህም በአባቱ እግር ተተክቶ በቤተ መንግሥቱ ያለችውን ሥዕል ቤት እንዲያገለግል ወደዚያው አስገቡት፡፡ በቤተ መንግሥቱም የንጉሡን ልጆች ከማስተማሩም በላይ በቤተ መንግሥቱ ዙርያ ከነበሩት ሊቃውንት መካከል አባ ጊዮርጊስ አንዱ ነበር፡፡ በአንድ ወቅት ግብፃዊው ጳጳስ አቡነ በርተሎሜዎስ “ሥላሴን አንድ ገጽ” ብለው ያምናሉ ተብለው በተከሰሱ ጊዜ ነገሩን እንዲያጣሩ ከተመረጡት ከቄስ ሐፄ ተከሥተ ብርሃንና ከሐይቁ መምህር ከዐቃቤ ሰዓት ዮሴፍ ጋር አብሮ ተልኮ ነበር፡፡ እነዚህ ሦስት አበው ጳጳሱን ካነጋገሩ በኋላ ክሱ ውሸት መሆኑን በማረጋገጥ ስለ ምሥጢረ ሥላሴ የሚገልጠውን የጳጳሱን እምነት በጽሑፍ ይዘው መጡ፡፡ በቤተ መንግሥቱ በነበረ ጊዜ የንጉሡን ልጆች ይስሐቅን፣ ቴዎድሮስን፣ እንድርያስን፣ ሀብተ ኢየሱስን፣ ሕዝቅያስን፣ ኢዮስያስን፣ ዘርዐ ያዕቆብንና ሴት ልጁን እሌኒን በምግባርና በሃይማኖት ቀርጿቸዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል ዘርዐ ያዕቆብ በድርሰቱ ሲመስለው ቴዎድሮስ ደግሞ በሕይወት መስሎታል፡፡ ዐፄ ዳዊት የአባ ጊዮርጊስን ሊቅነትና መልካም ሥነ ምግባር በሚገባ ስላወቀ በጋብቻ ሊዛመደው ወዶ ስለነበር ልጁን እንዲያገባ ዘወትር ይጠይቀው ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ ግን በድንግልና ጸንቶ ለመኖር እንደሚፈልግ ከመግለጽ አልተቆጠበም፡፡ የዐፄ ዳዊት ጥያቄ ስለበዛበት ወደ አቡነ በርተሎሜዎስ ሄዶ ቅስናን ከተቀበለ በኋላ ወዲያው መነኮሰ፡፡ ከመነኮሰ በኋላ ወደ ሸግላ በመምጣት ለነገሥታትና በቤተ መንግሥቱ ለነበሩ ካህናት እንዲሁም በቤተ መንግሥቱ ለነበሩ ታላላቆች፣ ለንቡራነ እድና ለመኳንንት፣ ለመሳፍንትና በቤተ መንግሥቱ ለነበሩ ባለሟሎች ሁሉ መምህር ሆነ፡፡ አባ ጊዮርጊስ በሸግላ በነበረ ጊዜ በወባ በሽታ ታምሞ ሊሞት ደርሶ ነበር፡፡ ታምሞ በነበረ ጊዜ አንድ ሌሊት የከበሩ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ተገልጠውለት ‹‹ከእኛ ጋር ትኖር ዘንድ ልንወስድህ መጣን›› አሉት፡፡ እርሱም ‹‹የድርሰት ሥራዬን ሳልሠራና እግዚአብሔርንም አብዝቼ ሳላመሰግነው አሁን አትውሰዱኝ›› ሲል ለመናቸው፡፡ እነርሱም ልመናውን ተቀብለውት ከሕመሙ ፈውሰውት ሄዱ፡፡ ለዚህም ነው ከበሽታው እንደ ተፈወሰ ወድያው የድርሰት ሥራውን የጀመረው፡፡ የመጀመርያ መጽሐፉን ጽፎ እንደ ጨረሰ ጠፍቶበት ነበር፡፡ በማግሥቱ በዚያው ላይ ሊጨምር በወደደ ጊዜ የተጻፈበት ጥራዝ ቀለሙ ጠፍቶ ነጭ ሆኖ አገኘው፡፡ ስለዚህም የተሰረቀ መስሎት ልቡ አዘነ፡፡ የተስተካከሉ ጥራዞችንም በቈጠረ ጊዜ ደኅና ሁነው አገኛቸው ሁለተኛም በድጋሚ ጻፈ፡፡ በማግሥቱም እንደ መጀመሪያው ነጭ ሁኖ አገኘው እስከ ሦስትና ዐራት ቀንም እየተደጋገመ እንዲሁ ሆነ፡፡ ከዚህ በኋላ አባታችን ወደ እመቤታችን ይጸልይ ጀመረ፡፡ ‹‹ይህ የሆነ በኃጢአቴ ነውን? ወይስ አይደለም? ግለጭልኝ›› አላት፡፡ አንድ ቀንም በሌሊት እኩሌታ ወደ ቤተ ክርስቲያን ለጸሎት ሲሄድ እመቤታችን በድንገት በማይነገር ክብር ለጊዮርጊስ ተገለጠችለት፡፡ ከእርሷም ጋር የቅዱሳን ማኅበር ሁሉ ነበሩ፡፡ በእጇም ከፀሐይና ጨረቃ የበለጠ የሚያበራ መጽሐፍን ይዛ

ስንክሳር ዘተዋሕዶ: #ሐምሌ_7 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሐምሌ ሰባት በዚች ቀን #ሥሉስ_ቅዱስ በአብርሃም ቤት የተገለጡበት ነው፣ ኢትዮጵያዊው ሊቅ #ቅዱስ_የአባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ ልደቱና ዕረፍቱ ነው፣ ቅዱስ አባት የባሕታውያን አለቃ የሆነ መስተጋድል #አባ_ሲኖዳ አረፈ፣ የሮሜ ከተማ ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_አግናጥዮስ በሰማዕትነት ሞተ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅድስት_ሥላሴ ሐምሌ ሰባት በዚች ቀን ሥሉስ ቅዱስ በአብርሃም ቤት የተገለጡበት ነው፡፡ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ በስም በአካል በግብር ሦስትነት በባሕርይ በሕልውናና በፈቃድ አንድነት የጸኑ ናቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ተገኙ፣ በዚህ ጊዜ ያልፋሉ አይባሉም መጀመሪያም መጨረሻም እነርሱ ናቸውና፡፡ ርሕሩሐን ናቸውና በእናት ሥርዓት ‹‹ቅድስት ሥላሴ›› እንላቸዋለን፡፡ የሚጠላቸው (የማያምንባቸውን) አይጠሉም፡፡ የሚወዳቸውን ግን እጽፍ ድርብ ይወዱታል፣ በቤቱም መጥተው ያድራሉ፡፡ ከፍጥረታት ወገን ከእመቤታችን ቀጥሎ የአብርሃምን ያህል በሥላሴ ዘንድ የተወደደ ፍጡር የለም፡፡ አባታችን ቅዱስ አብርሃም የደግነት ሁሉ አባት ነውና በኬብሮን በመምሬ ዛፍ ሥር ሥላሴን ተቀብሎ አስተናግዷል፡፡ አባታችን አብርሃም በ99 ዓመቱ እናታችን ሣራ በ89 ዓመቷ ሥላሴን በድንኳናቸው አስተናገዱ፡፡ አብርሃም እግራቸውን አጠበ፡፡ በጀርባውም አዘላቸው፡፡ ምሳቸውንም አቀረበላቸው፡፡ እነርሱም እንደሚበሉ ሆኑለት፡፡ በዚያው ዕለትም የይስሃቅን መወለድ አበሠሩት፡፡ አብርሃም ከደግነቱና እንግዳ ከመውደዱ የተነሣ በተመሳቀለ ጎዳና ላይ ድንኳን ሠርቶ የወጣ የመረደውን፣ የመጣ የሄደውን ሁሉ እየተቀበለ እግዚአብሔርን እያገለገለ የሚኖር ጻድቅ ነበር፡፡ ለዚህም ነው አብርሃም በወይራ ግራር (በመምሬ) ዛፍ ሥር ተቀምጦ ሳለ እግዚአብሔር አንድነቱን ሦስትነቱን የገለጠለት፡፡ ዘፍ 18፡1-25፣ ሮሜ 4፡-3፡፡ ቀትር ሰዓት ላይ በድንኳኑ ደጅ ተቀምጦ እንግዳ ሲጠብቅ እግዚአብሔር ታየው ተነጋገረው፡፡ አንገቱን ቀና አድርጎ ዐይኑን አራምዶ በተመለከተ ጊዜ እነሆ ሦስት ሰዎች ከበላዩ ባለ ተራራ ላይ ቆመው አያቸው፣ ወደ እርሱም ሲወርዱ አይቶ ፈጥኖ ሄዶ ከሰግደላቸው በኋላ ‹‹አቤቱ በፊትህስ ሞገስ አግኝቼ እንደሆነ ባሪያህን አትለፈኝ ብዬ እለምናለሁ፤ ጥቂት ውኃ ይምጣላችሁ እግራችሁን ታጠቡ…›› እያለ በትሕትና በመጋበዝ ወደ ድንኳኑ አስገብቶ በሚገባ ጋበዛቸው፡፡ ‹‹በፊትህስ ሞገስ አግኝቼ›› ብሎ አንድነታቸውን፣ ‹‹ጥቂት ውኃ ይምጣላችሁ እግራችሁን ታጠቡ›› ብሎ የሦስትነታቸውን ምስጢር ገልጾአል፡፡ ያች ሥላሴ የገቡባት የአብርሃም ድንኳን የእመቤታችን ምሳሌ ናት፡፡ ሥላሴ ወደ አብርሃም ድንኳን እንደገቡ ሁሉ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያምም አብ ለአጽንዖ፣ መንፈስ ቅዱስ ለአንጽሖ፣ ወልድ በተለየ አካሉ ሥጋዋን ለመዋሐድ የማደራቸው ምሳሌ በመሆኑ አማናዊቷ የሥላሴ ማደሪያ የአብርሃም ድንኳን እመቤታችን ናት፡፡ ሉቃ 1፡35፡፡ እግዚአብሔርም አብርሃምን የዛሬ ዓመት ልጅ እንደሚወልድ ነግሮት በዓመቱ ይስሐቅን ወልዷል፡፡ ሁለቱ ሰዎች ከአብርሃም ድንኳን ወጥተው ወደ ሰዶም ወደ ገሞራ ሄዱ፣ አብርሃምም ይሸኛቸው ዘንድ አብሯቸው ሄደ፡፡ የሄዱትም ሁለቱ ሰዎች አብና መንፈስ ቅዱስ ናቸው፡፡ ነገር ግን አንዱ ወልድ በአብርሃም ቤት ቀርቷል ይኸውም ከቤተ አብርሃም ሰው እንደሚሆን ለማጠየቅ ነው፡፡ አብርሃምም ተመልሶ በእግዚአብሔር ፊት ቆመ፡፡ እግዚአብሔርም የሚሠራውን ሁሉ ከአብርሃም አይሠውርም ነበርና የሰዶምን የገሞራን ጥፋት ነገረው፡፡ አብርሃምም ይቅር እንዲላቸው አብዝቶ ለመነላቸው፡፡ ሥሉስ ቅዱስን የአብርሃሙ ሥላሴን በምግባር በሃይማኖት ሆነን እናገለግል ዘንድ የቅዱሳኑ ጸሎት ይርዳን! ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ በዚህች ዕለት ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ልደቱና ዕረፍቱ ነው፡፡ አባቱ ሕዝበ ጽዮን ዘትግራይ እናቱ አምኃ ጽዮን ዘወለቃ ይባላሉ፡፡ ስለሆነም ሀገሩ ትግራይና ወሎ ቦረና ነው፡፡ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ በመባል የሚታወቀው ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በድርሰቱ ከቅዱስ ያሬድ ቀጥሎ ስሙ የሚነሣ ታላቅ መመኪያችን የሆነ ጻድቅ አባታችን ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ከመናኝ ጻድቅነቱ በተጨማሪ በመላእክትም ዘንድ የተመሰከረለት ታላቅ ፈላስፋና ደራሲም ነው፡፡ በድርሰቱ ላይ ስለ ሰማይ፣ ስለ መብረቅ፣ ስለ ደመና፣ ስለ ዝናብ አፈጣጠር፣ ስለ አራቱ ዓለማትና ስለ ሰባቱ ሰማያት… በእነዚህና በመሳሰሉት በመንፈሳዊው በሚገባና እጅግ በሚያስደንቅ መንገድ ተፈላስፎባቸዋል፡፡ ጻድቁ ድርሰቶቹን እርሱ ካለበት ወደ ሌላ ቦታ ለመላክ ንፋስ ይታዘዝለት ነበር፡፡ ስለ ጾምና ስለ በዓላት የደረሰውን ድርሰቱን ለሸዋው ንጉሥ ደብዳቤ ጽፎ በነፋስ ጭኖ ልኮለታል፡፡ አስደናቂ ገደሙ ወሎ ቦረና ውስጥ ይገኛል፡፡ ጋስጫ በድሮ ስሟ ደብረ ባሕርይ ትባላለች፡፡ በአጠገቡም ራሱ አባ ጊዮርጊስ የፈለፈላቸው ብዙ ዋሻዎች አሉ፡፡ ከአባ ጽጌ ድንግል ጋር ለመገናኘት እንዲያመቻቸው ብለው የሠሩት ድልድይ ‹‹የእግዜር ድልድይ›› ይባላል፡፡ በእግር 5 ሰዓት የሚያስኬድ መንገድ ነው፡፡ የአባ ጊዮርጊስ ጋሥጫ ገዳም የአውሬ ሰጋጅና ባሕታዊ ያለበት አስደናቂ ገዳም ነው፡፡ በየዓመቱ የስቅለት ዕለት ቁመቱ 60 ክንድ የሆነ ዘንዶ ከመቅደሱ ወጥቶ ግብረ ሕመማት ከሚነበብበት ከአትሮንሱ ሥር ሆኖ ተጠምጥሞ እራሱን ቀና አድርጎ ሲሰግድ ውሎ ካህኑ ሲያሰናብት ማታ ተመልሶ ወደ መቅደሱ ይገባል፡፡ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ የተሰኘውን የዚህን ድንቅ አባታችንን ዜና ሕየወቱን በደንብ መመልከቱ ተገቢና አስፈላጊ ነው፡፡ የተወለደው በ1357 ዓ.ም በወሎ ክፍለ ሀገር በቦረና ወረዳ ሰግላ በተሰኘች ቦታ ነው፡፡ የተወለደው በቅዱስ ዑራኤል አብሳሪነት ነው፡፡ ወላጆቹ አስቀድሞ ልጅ አልነበራቸውምና በስለት ነው ያገኙት፡፡ አባ ጊዮርጊስ በመጀመርያ እናቱ ፈሪሐ እግዚአብሔርን እያስተማረች በጥበብና በዕውቀት አሳደገችው፡፡ ቀጥሎም የመጀመርያውን የቤተ ክርስቲያን ትምህርት የተማረው ከአባቱ ነበር፡፡ ሊቅ የነበረው አባቱ ካስተማረው በኋላ በ1341 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ ከመጡትና እስከ ዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ጳጳስ የነበሩት ከአቡነ ሰላማ መተርጕም ዘንድ ወስዶ ዲቁና አሹሞታል፡፡ ዲቁና ከተቀበለ በኋላ ለትምህርት ወደ ሐይቅ እስጢፋኖስ ወሰደው፡፡ አባ ጊዮርጊስ በሐይቅ እስጢፋኖስ ትምህርት አልገባው ብሎ ለሰባት ዓመታት ተቀምጦ ነበር፡፡ አብረውት የሚማሩት ተማሪዎች ‹‹ይህ ትምህርት የማይገባው ስለ ምንድን ነው? በእርሱ ኃጢአት ነው ወይስ በወላጆቹ?›› ይሉት ነበር፡፡ በዚያ ጊዜ የሐይቁ መምህር የነበረው ዐቃቤ ሰዓት ሠረቀ ብርሃን ለአባቱ ‹‹ልጅህ ትምህርት አይገባውምና የቤተ መንግሥት ነገር አስተምረው›› ብሎ መለሰው፡፡ አባቱ ሕዝበ ጽዮን ግን ‹‹አንድ ጊዜ ለእግዚአብሔር ሰጥቼዋለሁ፤ እዚያው ገዳሙን ያገልግል›› ብሎ እንደ ገና ወደ ሐይቅ ላከው፡፡ አባ ጊየርጊስ ከቀለም ትምህርቱ ይልቅ በሥራ እየደከመ የገዳሙን አባቶች ይረዳ ጀመር፡፡ በገዳሙ እንጨት ይሰብር ውኃ ይቀዳ ይልቁንም ደግሞ አብዝቶ እህል በመፍጨት ያገለግል ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ እህል ይፈጭበት የነበረውን የድንጋይ ወፍጮና ንፍሮ ይቀቅልበት የነበረው የድንጋይ ትልቅ ማሰሮ አሁንም ድረስ በሐይቅ ገዳም በክብር ተጠብቀው ይገኛሉ፡፡ ጊዮርጊስ ግን ትምህርቱን ለመረዳት የዘገየ ሆነ፣የእግዚአብሔር ቃልም አልገባውም ነበር፡፡ ይህም ስለ ኃጢአቱ አይደለም፡፡