አድልዎ አታድርጉ
ያዕ 2:1-7
ያዕቆብ በምዕራፍ አንድ መጨረሻ ላይ ስለ ንጹህና ነውር ስለ ሌለው አምልኮ እየተናገረ ወላጅ የሌላቸውን ልጆችና ባልቴቶችን በችግራቸው መርዳት አስፈላጊ ስለ መሆኑ አስተምሯል ይሁን እንጂ ሰወችን ከመርዳት በፊት ስለ ሰው የተስተካከለ እይታ ሊኖር ይገባል ። ጳውሎስ ሰውን በክርስቶስ አውቃለሁ እንዳለ ከሁሉ በፊት ክርስቶስ ሰውን እንዴት እንደሚያየውና በክርስቶስም ማን እንዳደረገው መረዳት ያስፈልጋል ። እነዚህ ቅዱሳን በየስፍራው ተበታትነው በፈተና ውስጥ እያለፉ የሚገኙ ናቸው ይሁን እንጂ በመከራ ማለፍ በራሱ ቅድስናን አያመጣም ነገር ግን እውነትን መማርና ማወቅ አርነትንና ቅድስና እንዲገለጥ ያደርጋል ። ሰውን በቀለሙ ፣ በውጫዊ ልብሱ ፣ በገንዘቡ ፣ በብሄሩ ፣ በእውቀቱ ፣ በስልጣኑ ወዘተ ... ማሰብ በመጀመሪያ ኃጢአት ነው ሲቀጥልም ይህ የዓለም እይታ እንጂ የክርስቶስ አይደለም ። ይህ የክርስቶስን አካል ምንነትን በሚገባ አለመረዳት የፈጠረው ቀውስ ሰወች በክርስቶስ ሆነው በቀለማቸው መሰባሰብን ፣ በብሄራቸውና በቋንቋቸው ህብረት ማድረግን እንደ መልካም ነገር እንዲቆጥሩት አድርጓል እንዲህ ዓይነቱ አስተሳሰብ ግን የክርስቶስን አካል አይወክልም ። ችግሩ በቀለምና በቋንቋ መሰባሰብ ሳይሆን የተሰባጠረ ህዝብ ባለበት ለሌላው ስፍራ / room / ሳይኖረን ሲቀር ነው ። መጽሐፍ ቅዱስ በተለይ አዲስ ኪዳንን የጻፉት የአይሁድ ክርስቲያኖች ናቸው ይሁን እንጃ የጻፉት በራሳቸው ቋንቋ ሳይሆን በግሪክ ቋንቋ ነበር ምክንያቱም በዚያ ዘመን ሰወች በጋራ የሚናገሩት የነበረው የግሪክ ቋንቋ ስለ ነበር ነው ። ይህ ማለት በየቋንቋው መጻፉ ትክክል አይደለም ማለት ሳይሆን ሀልጊዜ የጋራ በሆነ ጉዳይ ላይ ትኩረት ማድረግ ጠቃሚ መሆኑን ለማሳየት ነው ።
1. የክርስቶስን መርህ አትጣሱ
“ ወንድሞቼ ሆይ ፥ በክብር ጌታ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ያለውን እምነት ለሰው ፊት በማድላት አትያዙ ” ያዕ 2፥1
ኢየሱስ አድልዎ የለበትም ለሰው ልጆች ካለው ፍቅር የተነሳ ለሰው ሁሉ በመስቀል ላይ ዋጋ ከፍሎአል ። እኛ እያንዳዳችን በክርስቶስ ወንድማማቾች ነን ስለዚህ ነው ያዕቆብ ወንድሞች ሆይ የሚለው ጳውሎስ ሲናገር " ... እናንተ ከቅዱሳን ጋር የአንድ አገር ዜጋ ፣ የእግዚአብሔርም ቤተ ሰብ አባል ናችሁ እንጂ ፣ ከእንግዲህ ወዲህ መጻተኞችና እንግዶች አይደላችሁም " ኤፌ 2:19 ይላል ። በክርስቶስ አድልዎ የለም ። ስለዚህ ይህንን መርህ ልንከተል ይገባል እንጂ አድልዎ በማድረግ የክርስቶስን የፍቅር ህግና መርህ መጣል አይገባንም ። በክርስቶስ የሆነው ምንም የሌለው ወንድም ከማንም ይልቅ በእምነት ባለጠጋ በመሆኑ በክርስቶስ ጸጋ ከክርስቶስ ጋር በአብ ቀኝ መቀመጡን መዘንጋት አይገባም ። ምንም ጊዜ ከሚታየው ነገር ይልቅ የማይታየው ይበልጣል ያዕቆብ ስለዚህ ዓለም ቁስ ሲናገር " ... እንደ ሣር አበባ ይረግፋልና ። ፀሓይ በነዲድ ሙቀቷ ወጥታ ሣሩን ታጠወልጋለችና ፤ አበባው ይረግፋል ፤ ውበቱም ይጠፋል " ያዕ 1:10
2. ለሰወች መሰናከል አትሁኑ
" የጌጥ ልብስም የለበሰውን ተመልክታችሁ ፦ አንተስ በዚህ በመልካም ስፍራ ተቀመጥ ብትሉት ፥ ድሀውንም ፦ አንተስ ወደዚያ ቁም ወይም ከእግሬ መረገጫ በታች ተቀመጥ ብትሉት ፥ ራሳችሁን መለያየታችሁ አይደለምን ? ክፉ አሳብ ያላቸውም ዳኞች መሆናችሁ አይደለምን ? " ያዕ 2:3,4
በቤተክርስቲያን በክርስቶስ ያመኑ ሰወች ህብረት ስትሆን እንደ ማግኔት ሰውን ሁሉ ከየአቅጣጫው ወደዚህ ማዕከል የሚስበው የክርስቶስ ፍቅር ነው ። ክርስቶስ የሰው ልጆች ሁሉ ነው ። እኛም በዚሁ የፍቅር መንፈስ ወደ ህብረታች የሚመጡትን ሁሉ ለመቀበል የተዘጋጀን ካልሆንንና በተለያየ አስተሳሰብ ልዩነትን የምንፈጥር ከሆን ሰወችን እናሰናክላለን እኛም ከእግዚአብሔር ጋር ያለን ህብረት ጥያቄ ውስጥ እንዲወድቅ እናደርጋለን “ እግዚአብሔርን እወደዋለሁ” እያለ ወንድሙን ቢጠላ ፣ እርሱ ሐሰተኛ ነው ፤ ያየውን ወንድሙን የማይወድ ያላየውን እግዚአብሔርን መውደድ አይችልም ' 1ኛ ዮሐ 4:20 ሰውን በውጫዊ ልብስ ስንመዝን የኛን ግብዝነት ከማሳየቱ ሌላ በማንነቱ ክቡር የሆነውን የሰው ልጅ ልቡን እንሰብራለን ። ሰይጣን ይህንን እንደመሳሪያ በመጠቀም ሰወች ከክርስቶስ ማለትም ከህይወት እንዲወጡ በማድረገ ይጠቀምበታል ። ሰወችን መርጠን ሰላም ስንል ሰወችን እናሰናክላለን ፣ እንጎዳቸዋለን ፣ ክርስቶስ ግን ከነ ቆሻሻችን ጠርቶ አጠበን " በቃሉ አማካይነት በውሃ አጥቦ በማንጻት እንድትቀደስ ፣ እንዲሁም ጒድፍ ወይም የፊት መጨማደድ ወይም አንዳች እንከን ሳይገኝባት ቅድስትና ነውር አልባ የሆነች ክብርት ቤተ ክርስቲያን አድርጎ ለራሱ ሊያቀርባት ነው " ኤፌ 5:26-27
3. የዓለምን መንገድ አትከተሉ
" እናንተ ግን ድሆችን አዋረዳችሁ ። ባለ ጠጎቹ የሚያስጨንቁአችሁ አይደሉምን ? ወደ ፍርድ ቤትም የሚጎትቱአችሁ እነርሱ አይደሉምን ? የተጠራችሁበትን መልካሙን ስም የሚሰድቡ እነርሱ አይደሉምን ? " ያዕ 2:6,7
ዓለም ሰወችን የምትመዝነው በውጫዊ ነገር ነው ፣ ዓለም ሽር ጉድ የምትለው ለክፉዎች ፣ ለሌቦች ፣ ለሚያስጨንቁ ፣ በላያቸው ለሚሰለጥኑ ፣ ኃጢአትን ለሚጨልጡ ወዘተ ... ነው ። እኛ ግን የዓለምን መንገድ እንዳንከተል ታዘናል " መልካም ፣ ደስ የሚያሰኝና ፍጹም የሆነውን የእግዚአብሔር ፈቃድ ምን እንደሆነ ፈትናችሁ ታውቁ ዘንድ በአእምሮአችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ " ሮሜ 12:2 ጌታ ኢየሱስ ስለዚህ ዓለም ሰወች ሲናገር " ... የአሕዛብ አለቆች ተብለው የሚታሰቡት እንደሚገዟቸው ፤ ሹሞቻቸውም በእነርሱ ላይ ሥልጣናቸውን እንደሚያሳዩ ታውቃላችሁ ፤ በእናንተ ዘንድ ግን እንዲህ አይደለም ፤ ከመካከላችሁ ታላቅ መሆን የሚፈልግ ሁሉ አገልጋይ ይሁን ” ማር 10:42-43
ምንጭ ወዊ ምንተሰኖት