es
Feedback
Sinksar tube(ስንክሳር)

Sinksar tube(ስንክሳር)

Ir al canal en Telegram

እኔ ቅዱስ ነኛና ቅዱሳን ሁኑ 1ጴጥ 1:15

Mostrar más
El país no está especificadoLa categoría no está especificada
2 500
Suscriptores
-1024 horas
+1137 días
+42130 días
Archivo de publicaciones
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን ሰኔ 15-ታላቁ ሰማዕት ማር ቅዱስ ሚናስ ታላላቅ ተአምራት ያደረገበት ዕለት ነው፡፡ ዳግመኛም በዚኽች ዕለት መርዩጥ በሚባል አገር ቤተ ክርስቲያኑ የከበረችበት ዕለት (ቅዳሴ ቤቱ) ነው፡፡ የቅዱስ ሚናስ አባቱ አውዶክስዮስ ሲሆን ሀሩም አናቅዮስ ይባላል፡፡ እርሱም ሀገረ ገዥነት ተሹሞ ሳለ ወንድሙ ቀንቶበት በሐሰት ነገር በመሥራት ከንጉሡ ጋር አጣላው፡፡ ንጉሡም አፍራቅያ ወደምትባል ሌላ ሀገር ልኮት በዚያ ገዥ አድርጎ ሾመው፡፡ አውዶክስዮስ ፈሪሃ እግዚአብሔር ያደረበት ደግ ሰው ስለነበር በአፍራቅያ የሚገኙ ሕዝቦችም ደስ አላቸው፡፡ የአውዶክስዮስም ልጅ አልነበረውና ሚስቱ ወደ እመቤታችን ቤተ ክርስቲያን እየሄደች እመቤታችንን ትለምናት ነበር፡፡ አንድ ቀን ጸሎቷን ስትጨርስ ከእመቤታችን ሥዕሏ ድምፅ ወጣና አነጋገረቻት፡፡ ልጅ እንደምትወልድና ስሙንም ሚናስ እንደምትለው ነገረቻት፡፡ ሚናስም ተወለደና ወላጆቹ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያስተማሩ አሳደጉት፡፡ በ12 ዓመቱ አባቱ ዐረፈ፣ ከ3 ዓመት በኋላ እናቱም ዐረፈችና ሚናስ ብቻውን ቀረ፡፡ መኳንንቱም አባቱን በጣም ከመውደዳቸው የተነሣ ሚናስን በአባቱ ፈንታ መስፍንነት ሹሙት፡፡ እግዚአብሔርንም መንግሥትንም በትጋትና በቅንነት እያገለገለ እያለ ከሃዲው ዲዮቅልጥያኖስ ነገሠና ክርስቲያኖችን ማረድ ጀመረ፡፡ ቅዱስ ሚናስም ይህን ሲሰማ ሹመቱን ትቶ ወደ ገዳም ገባና በመንፈሳዊ ተጋድሎ ብቻ እየተጋደለ ብዙ ዘመን ኖረ፡፡ አንድ ቀን ሰማይ ተከፍቶ ሰማዕታት የብርሃን አክሊል ሲቀዳጁ አየ፡፡ በዚህም ጊዜ ወደ ከተማው ተመለሰና የጌታችን የመድኃታችን የኢየሱስ ክርስቶስን እውነተኛ አምላክነት መመስከር ጀመረ፡፡ መኰንኑም የመንግሥት ወገን መሆኑን ዐውቆ በማባበል ብዙ ለመነው፡፡ ‹‹የንጉሡን ትእዘዝ አትተላለፍ›› እያለ ቢለምነው ቅዱስ ሚናስ ግን አልሰማ አለው፡፡ ከዚህም በኋላ ልዩ ልዩ በሆኑ ሥቃዮች ያሠቃየው ጀመር፡፡ ማሠቃየቱም በሰለቸው ጊዜ አንገቱን በሰይፍ እንዲቆርጡት አዘዘና ቅዱስ ሚናስ ኅዳር 15 ቀን ተሰይፎ ሰማዕትነቱን በድል ፈጸመ፡፡ በእርሱም ምክንያት ብዙዎች በክርስቶስ አምነው ሰማዕት ሆኑ፡፡ የቅዱስ ሚናስንም ሥጋ እሳት አንድደው በዚያ ጨመሩት፡፡ ነገር ግን እሳቱ አልነካውም፡፡ ክርስቲያኖችም ሥጋውን ወስደው የመከራ ዘመን እስኪያልፍ ደብቀው በክብር አኖሩት፡፡ የመርዩጥ አገር ሰዎች ወደ አምስት አገሮች ሲጓዙ የቅዱስ ሚናስን ሥጋ ረዳት ይሆናቸው ዘንድ በመንገድም እንዲጠብቃቸው አብረው ወሰዱት፡፡ በባሕርም ላይ በመርከብ ውስጥ ሳሉ ፊታቸው እንደ ከይሲ አንገታቸው እንደ ግመል አንገት ያሉ አውሬዎች ከባሕር ወጡና የቅዱስ ሚናስን ሥጋ ይልሱት ዘንድ አንገታቸውን ዘረጉ፡፡ ነገር ግን ከቅዱስ ሚናስን ሥጋ ውስጥ እሳት ወጥታ እነዚያን አራዊት አቃጥላ ገደለቻቸው፡፡ ሰዎቹም ይህን አይተው እጅግ ተደሰቱ፡፡ ወደ እስክንድርያ አገር ደርሰው ሥራቸውን ፈጽመው ወደ አገራቸው በሚመለሱ ጊዜ የቅዱስ ሚናስን ሥጋ ይዘው ሊመለሱ ወደው በግመል ላይ ጫኑት፡፡ ነገር ግን ግመሏ አልንቀሳቀስ አለች፡፡ ሁለተኛም በሌላ ግመል ቢጭኑትም አሁንም አልንቀሳቀስ አለች፡፡ አብዝተውም ቢደበድቧት እምቢ አለች፡፡ አሁንም ሌላ ሦስተኛ ግመል ቢሞክሩ እርሷም እምቢ አለች፡፡ ከዚያም ‹‹ይህ ቦታ እግዚአብሔር የፈቀደለት ቦታ ነው›› ብለው ቦታውን አዘጋጅተው በዚያ ቀብረውት ሄዱ፡፡ ማር ሚናስ ሰማዕትነቱን ፈጽሞ ካረፈ በኋላ ቅዱስ ሥጋው ተሰውሮ ለብዙ ዘመን ኖረ፡፡ ከዚህም በኋላ ለምእመናን ጥቅም ቅዱስ ሥጋው የሚገለጥበት ጊዜ ሲደርስ በእግዚአብሔር ፈቃድ በአንድ በግ ጠባቂ እረኛ አማካኝነት ያለበት ታወቀ፡፡ ይኸውም አንድ የታመመች በግ የቅዱስ ሚናስን ሥጋ ተደብቆ በሚኖርበት ኮረብታ አካባቢ ባለው ውኃ ውስጥ ገብታ ስትወጣ ዳነች፡፡ እረኛውም መዳኗን አይቶ ሌሎች የታመሙ በጎቹንም በውኃው ውስጥ እየከተተ ሲሞክራቸው ፍጹም ጤነኛ ሆኑለት፡፡ ቦታውም የታወቀ ሆነና ምክንያቱ ምን እንደሆነ ሳይታወቅ ሁሉም እየመጣ በውኃው እየተጠመቁና አፈሩን በውኃው እየለወሱ እየተቀቡ ይፈወሱበት ጀመር፡፡ ወሬውም እስከ ሮሙ ንጉሥ ድረስ ደረሰ፡፡ ንጉሡም የታመመች ሴት ልጅ ነበርችውና ወደ እረኛው ዘንድ ላካትና እርሷም ፍጹም ተፈወሰች፡፡ የንጉሡም ልጅ ይህ ፈውስ የሚደረግበት ነገር ምን እንደሆነ ታውቅ ዘንድ ወደደች፡፡ ቅዱስ ሚናስም በሕልሟ ተገለጠላትና ቅዱስ ሥጋውን አስቆፍራ እንድታወጣ እግዚአብሔር ያዘዛት መሆኑን ነገራት፡፡ እንደታዘዘችውን ቅዱስ ሥጋውን አስወጥታ ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያን አሠራችለት፡፡ ንጉሡም በቦታው ላይ ታላቅ ከተማ እንዲሠራ አዘዘና ከተማ ሆነች፣ ስሟንም መርዩጥ አሏት፡፡ እግዚአብሔርም በቅዱስ ሚናስ ሥጋ እስከዛሬ ድረስ እጅግ አስገራሚ ተአምራት እያደረገ ይገኛል፡፡ ለመናገር የሚከብዱ እጅግ ብዙ ተአምራት ይሠራሉ፡፡ ይህችም ቤተ ክርስቲያን የከበረችበት ዕለት ሰኔ 15 ነው፡፡ ዳግመኛም ይኸች ዕለት ታላላቅ ተአምራት ያደረገባት ዕለት ናት፡፡ የሰማዕቱ የቅዱስ ሚናስ ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣ በጸሎቱ ይማረን፡፡

💠የንስሐ ◇የሽብሻቦ ◇ወረብ ◇የቅዱሳን እንዲሁም የመላእክት መዝሙር የምትፈልጉ ከሆነ አሁኑኑ JOIN በሉት ይሄ ቻናል ምርጥ ምርጥ መዝሙሮችን በጥራትና በፍጥነት ያሳያል። 𝐉𝐨𝐢𝐧👇👇👇 h
💠የንስሐ ◇የሽብሻቦ ◇ወረብ ◇የቅዱሳን እንዲሁም የመላእክት መዝሙር የምትፈልጉ ከሆነ አሁኑኑ JOIN  በሉት  ይሄ ቻናል ምርጥ ምርጥ መዝሙሮችን በጥራትና በፍጥነት ያሳያል። 𝐉𝐨𝐢𝐧👇👇👇 https://t.me/addlist/sZA2UFcsVPplMjI0

✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞✞✞
✞ ✞ እንኩዋን ለአራቱ ቅዱሳን አበው ሰማዕታት ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞ ✞
=> #4ቱ_ቅዱሳን አበው የዘመነ ሰማዕታት ፍሬዎች ሲሆኑ ስማቸው #አባ_አክራ : #አባ_ዮሐንስ : #አባ_አብጥልማ እና #አባ_ፊልዾስ ይባላሉ:: ከመከራ ዘመን በፊት (ማለትም በቀደመ ሕይወታቸው) ካህናትና ሃብታሞች ነበሩ:: ሀብቱ ግን በሥራ ብቻ የተገኘ ነው:: +ታዲያ ቅዱሳኑ በያሉበት ሆነው በሀብታቸው እንግዳ እየተቀበሉ: ድሆችን እያበሉ: በክህነታቸው ደግሞ እያስተማሩና እየናዘዙ ትጉሃን ስለ ነበሩ በሰውም ሆነ በእግዚአብሔር ዘንድ ሞገስ ነበራቸው:: በእንዲህ ያለ ግብር ሳሉ ዘመነ ሰማዕታት አሐዱ አለ:: "ክርስቶስን ካዱ: ለጣዖት ስገዱ" እያሉ መኩዋንንቱና ነገሥታቱ ሕዝበ ክርስቲያኑን ያሰቃዩ ገቡ:: +በዚህ ጊዜ 4ቱ ቅዱሳን አንድ ነገር መከሩ:: በየእሥር ቤቱ የተጣሉ ክርስቲያኖችን ለማገልገል ቆረጡ:: እግረ መንገዳቸውን እያስተማሩ እሥረኞችን ያጽናኑ ገቡ:: የራበውን ያበላሉ: የተሰበረውን ይጠግናሉ: በቁስሉም ላይ መድኃኒትን ያደርጉ ነበር:: የመከራው ዘመን ግን እየረዘመ: ግፉም ከልክ እያለፈ መጣ:: +በዚህ ጊዜ 4ቱ ቅዱሳን ትልቁንና የመጨረሻውን ውሳኔ አስተላለፉ:: ከሰማዕታት ወገን ይቆጠሩ ዘንድ መርጠዋልና: ክርስቶስን በሞቱ ይመስሉት ዘንድ ሽተዋልና: የሩጫቸው መጨረሻ ሰማዕትነት እንዲሆን መረጡ:: +አራቱም ያላቸውን ንብረት ሁሉ ሰብስበው ለነዳያን አካፈሉ:: በትከሻቸው ካለች አጽፍ በቀር ስባሪ ገንዘብ ከሃብታቸው አላስቀሩም:: ከዚያ ጉዞ ወደ ምስክርነት አደባባይ (ዐውደ ስምዕ) አደረጉ:: +በዙፋኑ የተቀመጠው የመኮንኑ ግርማ: መሬት ላይ የፈሰሰው የወገኖቻቸው ደም: የሠራዊቱ ድንፋታ ቅዱሳኑን አላስፈራቸውም:: በይፋ "ክርስቲያን ነን" ሲሉ ተናገሩ:: በዘመኑ እንዲሕ ብሎ መናገር አንገት የሚያስቆርጥ ትልቅ ድፍረት ነበር:: +መኮንኑም ከበጐ ሃይማኖታቸው ይለያቸው ዘንድ በእሳት አቃጠላቸው:: እግዚአብሔር አዳናቸው:: በቀስትም: በስለትም: በብረትም ለቀናት አሰቃያቸው:: ቅዱሳኑ ግን አምላካቸውን አምነው ሁሉን በአኮቴት ተቀበሉ:: በመጨረሻ ግን በዚሕች ዕለት የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው ተገድለዋል:: ስለ ምጽዋታቸው: በጎ አገልግሎታቸውና ሰማዕትነታቸው ጻድቅ: ፈራጅ ከሆነ ፈጣሪ አክሊልን ተቀብለዋል:: =>የበረከት አምላክ ከወዳጆቹ ጸጋ ክብርን ያድለን:: =>ሰኔ 14 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት= 1.ቅዱሳን አበው ሰማዕታት (አባ አክራ: አባ ዮሐንስ: አባ አብጥልማ: አባ ፊልዾስ) =>ወርሐዊ በዓላት 1.አቡነ አረጋዊ (ዘሚካኤል) 2.ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ መርዓዊ 3.ቅዱስ ፊልዾስ ሐዋርያ 4.ቅዱስ ሙሴ (የእግዚአብሔር ሰው) 5.አባ ስምዖን ገዳማዊ 6.አባ ዮሐንስ ጻድቅ 7.እናታችን ቅድስት ነሣሒት =>+"+ እግዚአብሔር ቅዱሳንን ስላገለገላችሁ: እስከ አሁንም ስለምታገለግሏቸው ያደረጋችሁትን ሥራ: ለስሙም ያሳያችሁትን ፍቅር ይረሳ ዘንድ ዓመጸኛ አይደለምና:: በእምነትና በትእግስትም የተስፋውን ቃል የሚወርሱትን እንድትመስሉ እንጂ ዳተኞች እንዳትሆኑ ተስፋ እስኪሞላ ድረስ እያንዳንዳችሁ ያን ትጋት እስከ መጨረሻ እንድታሳዩ እንመኛለን::+"+ (ዕብ. 6:10-13) <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>> 🔵TELEGRAM 🔴 YOUTUBE

††† እንኳን ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል እና ለጻድቁ አባ ዮሐንስ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፣ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት ††† ††† ቅዱስ ገብርኤል :- ¤በራማ ከሚኖሩ ሊቃናት አንዱ:: ¤አርባብ በሚባሉ አሥር ነገዶች ላይ አለቅነትን የተሾመ:: ¤የስሙ ትርጓሜ "እግዚእ ወገብር" (ጌታና አገልጋይ) አንድም "አምላክ ወሰብእ" (የአምላክ ሰው መሆን) ማለት የሆነ:: ¤በመጀመሪያዋ የፍጥረት ቀን ዘጠና ዘጠኙን ነገደ መላእክት ያረጋጋ:: ¤ብርሃናውያን መላእክትን የሚመራ:: ¤በብሉይም ሆነ በሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት አብሣሪነቱ በስፋት የተነገረለት:: ¤በተለይ ደግሞ የወልደ እግዚአብሔርን ሰው የመሆን ዜና ይሸከም ዘንድ ያደለው:: ¤ከድንግል ማርያም ጎን በፍጹም የማይርቅ:: ¤በፈጣን ተራዳኢነቱ ብዙ ቅዱሳንን ያገለገለ ታላቅ ቀናዒ መልአክ ነው:: በዚሕች ዕለት እግዚአብሔር ቅዱስ ገብርኤልን ወደ ባቢሎን ልኮታል:: ሊቀ መላእክት ነቢዩ ዳንኤልን ከአናብስቱ ጥርስ እንዳዳነው መጽሐፍ ነግሮናል:: ይልቁኑ ታላቁ ነቢይ ዳንኤል የተማረኩ ወገኖቹን መመለስ እያሰበ በሃዘን ሲጸልይ በዚሕ ቀን ቅዱስ ገብርኤል ወርዶ ዳስሶታል:: ባርኮታል:: አጽናንቶታል:: ለዳንኤል በዋነኛነትም ሦስት ምሥጢራትን ገልጾለታል:- 1.የቤተ እሥራኤልን ከሰባ ዘመን በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም መመለስ:: 2.የክርስቶስን ሰው መሆንና መሞት:: 3.የሐሳዌ መሲሕን በመጨረሻ ዘመን መምጣት ነግሮታል:: ስለዚህም እኛ ቅዱስ ገብርኤልን እንድናከብረው : በጸሎትም እንድንጠራው አባቶቻችን አዝዘውናል:: ††† አባ ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም ††† ††† ጻድቁ ሃገራቸው መካከለኛው ምሥራቅ አካባቢ ሲሆን የታላቁ ሊቅ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ባልንጀራ ናቸው:: ከሕፃንነታቸው ጀምሮ በክርስትና አድገው : ቅዱሳት መጻሕፍትን ተምረው ወደ ገዳም መንነዋል:: ከታላቁ ኮከበ ገዳም አባ ኢላርዮን ሥርዓተ መነኮሳትን አጥንተው አባ ኤስድሮስን በረድዕነት አገልግለዋል:: ከብዙ ዓመታት ትሕርምትና ገዳማዊ ሕይወት በኋላ የቅድስት ሃገር ኢየሩሳሌም ጳጳስ ሆነው ተሹመዋል:: በጵጵስናቸው ዘመን አንድ ከባድ ስሕተት ሠርተው ነበር:: እርሱም ለቤተ ክርስቲያንና ለነዳያን ከምእመናን የተሠበሠበውን ገንዘብ ለግል ጉዳያቸው አውለው ልብሳቸውና ቤታቸው ወርቅ በወርቅ ሆኖ ነበር:: ፈጣሪ ግን ይሕንን ብክነት ከእርሳቸው ያርቅ ዘንድ ቅዱስ ኤጲፋንዮስን ላከው:: እርሱም በምክንያት ከቆጵሮስ ኢየሩሳሌም ገባ:: ጓደኛ ናቸውና አሳምኖ የወርቅ ንብረቶቹን ሁሉ ወሰደ:: ለነዳያንም ሰጣቸው:: አባ ዮሐንስ ሊቁን "እቃየን ካልመለስክ" ብለው ቢይዙት ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ጸልዮ ዐይናቸው እንዲታወር አደረገ:: አንዳንዴ የታወረ ልብ የሚገለጠው እንዲሕ ነውና:: በደቂቃዎች ልዩነት ዐይነ ስውር የሆኑት አባ ዮሐንስ አለቀሱ:: ሊቁንም "ራራልኝ : አማልደኝ?" አሉት:: እርሱም ጸልዮ አንድ ዐይናቸውን ብቻ አበራላቸው:: "ለምን?" አሉት:: "ተግሳጽ ነው" አላቸው:: ከዚያች ቀን በኋላ አባ ዮሐንስ ወደ ልቡናቸው ተመለሱ:: ቤታቸውን ገዳም አደረጉት:: በሚደነቅ ቅድስና : ፍቅርና ሐዋርያዊ አገልግሎት ምዕመናንን አገልግለው በዚሕች ቀን በመልካም ሽምግልና ዐርፈዋል:: ††† የሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ረድኤት : የአባ ዮሐንስ በረከት አይለየን:: ††† ሰኔ 13 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት (ወደ ዳንኤል የወረደበት) 2.አባ ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም 3.አባታችን ቃይናን (ከአዳም አራተኛ ትውልድ) 4.አባ ማትያን ጻድቅ ††† ወርኀዊ በዓላት 1.እግዚአብሔር አብ 2.ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላእክት 3.ዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት 4.ቅዱስ አስከናፍር 5.አሥራ ሦስቱ ግኁሳን አባቶች 6.ቅዱስ አርሳንዮስ ጠቢብ ገዳማዊ 7.አቡነ ዘርዐ ቡሩክ ††† " . . . በአምላኬም በእግዚአብሔር ፊት ስለ ተቀደሰው ስለ አምላኬ ተራራ ስለምን: ገናም በጸሎት ስናገር አስቀድሜ በራእይ አይቼው የነበረው ሰው ገብርኤል እነሆ እየበረረ መጣ:: በማታም መሥዋዕት ጊዜ ዳሰሰኝ:: አስተማረኝም: ተናገረኝም:: እንዲህም አለ:- "ዳንኤል ሆይ! ጥበብንና ማስተዋልን እሰጥህ ዘንድ አሁን መጥቻለሁ::" ††† (ዳን. ፱፥፳-፳፪) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

ወንድሞቹም ከሔዱበት ሲመለሱ ጥሪተ እግዚእን ስላጡት እያዘኑ ሳለ የገዳሙ አንድ መነኵሴ ሕፃኑ ወደ ገዳም እንደገባና ከታላቅ ወንድሙ ጋር እንደተገናኘ ነገሯቸው። ወንድሞቹም ወደ ገዳሙ ገብተው አበ ምኔቱን አባ ተወልደ መድኅንን አግኝተው ተባረኩ። አበ ምኔቱም ከወንድሞቻቸው ጋር አገናኛቸውና እያለቀሱ ተሳሳሙ። ከዚያም ወንድሞቹ ወጥተው ወደ ማሳቸው ሲሔዱ ሕፃኑ ጥሪተ እግዚእ ግን በገዳም ቀረ። በዚያም መመንኰስ እንደሚፈልግ ሲናገር መነኰሳቱ ‹‹ልጄ ሆይ! ይህ ለአንተ ይከብድሃል ምንኵስና ለትልልቆች ነው የሚገባው፣ ትዕግሥት አድርግ…›› ሲሉት እርሱም ‹‹…ለእኔ የሚሻለኝን ዐውቃለሁ›› ብሎ መለሰ። እነርሱም በመልሱ ተገርመው አመነኰሱትና ማትያስ የሚል ስም ሰጡት። ከዚኸም በኋላ አቡነ ማትያስ ቅዱሳት መጻሕፍትን ተምረው በጾም በጸሎት ተወስነው ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን እየተቀበሉ ማገልገል ጀመሩ። በዚኸም ጊዜ ሰይጣን በሥጋቸው ፈተናቸው። እርሳቸውም ወደ ቤተ ክርስቲያን ሔደው ‹‹ኦ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ነፍሴን ተቀበላት፣ ግደለኝ፤ እንዴት ከተወለድኹ ጀምሮ እስከዛሬ ፍጹም የማላውቀው መጥፎ ሀሳብ ከሚመጣብኝ ሞት ይሻለኛል፣ ግደለኝ.. እያሉ ሲጸልዩ የክብር ባለቤት ጌታችን በአካል ተገልጦላቸው በመለኮታዊ እጆቹ ዳስሶ ፈጽሞ አዳናቸው። ከዕለታት በአንደኛው ቀን አቡነ ማትያስ ከአንድ መነኵሴ ጋር ለገዳሙ ማኅበር ምግብ ለማዘጋጀት ወደ በረሓ እንደደረሱ የሚጠጡት ውኃ ሲያጡ አባታችን ማትያስ ጸሎት ካደረሱ በኋላ በበትራቸው መሬትን ባርከው እንደ ሊቀ ነቢያትሙሴ ውኃ አፈለቁ። እነርሱም የማኅበሩን ምግብ ይዘው ሲመለሱ በመንገድ ላይ ሽፍቶች አግኝተዋቸው ምግቡን ወሰዱባቸው፤ አባታችንም ጸሎት ቢያደርጉ ወዲያው እነዚያ ሽፍቶች ታመው ወደቁ። ከዚያም ሽፍቶቹ ‹‹እናንት የአምላክ ሰዎች ሆይ! እባካችሁ ይቅር በሉን፣ የወሰድንባችሁንም እንኩ ውሰዱ፣ እኛንም እርዱን…›› እያሉ ለመኗቸው። አባታችንም ምራቃቸውን እንትፍ ብለው በትእምርተ መስቀል አማትበው በእርሱ ዳበሷቸውና ሽፍቶቹ ዳኑ። ዳግመኛም በአንደኛው ቀን መነኰሳቱ ሁሉም ሥራ ጨርሰው ተኝተው ሳለ አቡነ ማትያስ ግን ደከመኝ ሳይሉ መቶ ሃምሳውንም መዝሙረ ዳዊት ሲደግሙ አደሩ እግዚአብሔርም መላእክቱን ልኮ አንድ ፈረስ ሰጣቸው። አባታችንም በዚህ ተደስተው ለኹለተኛ ጊዜ መቶ ሃምሳውን መዝሙረ ዳዊት ሲደግሞ አሁንም ለኹለተኛ ጊዜ ፈረስ ተላከላቸው። ከእርሳቸውም ጋር የነበሩት መነኰሳት ምን እንደተፈጠረ ሳያውቁ ተኝተው አደሩ። አቡነ ማትያስን መላእክት ወደ ሰማያት አውጥተዋቸው በገነት ተድላ ያሉ ጻድቃንን አሳይተው ዳግመኛም የኀጥአንን ፍዳና መከራ አሳዩዋቸው። አባታችንም የኀጥአንን መከራ አይተው አዝነው ደንግጠው አለቀሱ። በዚኸም ጊዜ ‹‹የተመረጥህ ማትያስ ሆይ! አትፍራ፣ እነዚህ ሕጌን የማያከብሩ ትእዛዜን ያፈረሱ ናቸው፣ በተድላ ገነት ያየኻቸውም ጻድቃን ናቸው›› የሚል ቃል አጽናናቸው። ከዚኸም በኋላ አባታችን ወደ ምድር ተመልሰው በመጡ ጊዜ አበ ምኔቱ አባ ተወልደ ምድኅን ዐርፈው በእርሳቸው መንበር አባ ፊቅጦር ተተኩ፤ ከአባ ፊቅጦርም በኋላ አስቀድሞ በተነገረው ትንቢት መሠረት አቡነ ማትያስን መርጠው ለመሾም ተስማሙ ነገር ግን አባታችን ማትያስ ሹመቱን እምቢ ሲሉ እጅና እግራቸውን አሥረው በግድ አበ ምኔት አድርገው ሾሟቸው። አቡነ ማትያስም ወደ ሰማያት ወጥተው የጻድቃንን ደስታና የኀጥአንን ፍዳ መከራ ከተመለከቱና ወደምድር ተመልሰው ከመጡ በኋላ መነኰሳቱን ሁሉ ሰብስበው ሕግንና ሥርዓትን ተግብረው ይኖሩ ዘንድ ስለነገሯቸው ከእነርሱ ውስጥ አንዳንድ ክፉዎች ወደ ንጉሡ ዘንድ ሔደው በብዙ ነገር በሐሰት ከሰሷቸው። ንጉሡም የተነገረው ሁሉ እውነት መስሎት አባታችንን ከሥልጣን አወረዳቸውና አሳደዳቸው። አቡነ ማትያስም ከገዳሙ ወጥተው ሲሔዱ ‹‹ከአንተ ከአባታችን አንለይም ብለው 230 መነኰሳት አብረዋቸው ሔዱ። ከዚኽም በኋላ ‹‹ትኹል ጎዳዕ፣ ጨዓት፣ ቃቕብዳ፣ ኣቄታብ፣ ወኪ፣ ምድረ ባሕር›› ወደተባሉ የተለያዩ | ቦታዎች ሔደው በተጋድሎ ኖሩ። በየበረሓውም ሲጓዙ ልጆቻቸው ውኃ ሲጠማቸው አባታችን መሬትን ባርከው ውኃ አፍልቀው አጠጧቸው። አባታችንም በምድረ ባሕር ሣሉ እህል ሳይቀምሱ በአንዲት ዋሻ ለኹለት ሳምንት ከቆዩ በኋላ በዚኸች ቦታ ላይ በሞት ማረፍ ፈለጉ፣ ነገር ግን እግዚአብሔር መልአኩን ልኮ ‹ለአንተ የምትሆን ምድር አዘጋጅቼልሃለሁና ወደልጆችህ ተመለስ›› አላቸው። አባታችን ዳግመኛም ከልጆቻቸው ጋር ሆነው ወደ ዓንደቕ ከዚያም ወደ ዒላ ሔደው ለ66 ቀናት ከቆዩ በኋላ ደብረ ብርሃን ደረሱ። አባታችንም ይኸችን ቦታ ‹‹እግዚአብሔር የሰጠን ገዳማችን ናት›› አሉ። ቦታዋንም ደብረ በረከት ብለው ሰየሟት። የዕረፍታቸውም ጊዜ ሲደርስ ልጆቻቸውን ሰብስበው በቃለ እግዚአብሔር አጽናንተው ‹‹በሥጋ ብለያችሁም በመንፈስ ግን ከመካከላችሁ አልለያችሁምና አትፍሩ እኔ ከእናንተ ጋር ነኝ፣ የአቡነ ኤዎስጣቴዎስንና የአቡነ አብሳዲን ሥርዓት ጠብቁ…›› ብለው ከመከሯቸው በኋላ በእርሳቸው ቦታ ዮሐንስን ሾመውላቸው ከጌታችን ታላቅ የምሕረት ቃልኪዳን ከተቀበሉ በኋላ ሰኔ 13 ቀን በሰላም ዐረፉ። አቡነ ማትያስም ካረፉ በኋላ ለልጆቻቸው በአካለ ነፍስ እየተገለጡ አጽናንተዋቸዋል ። ከማረፋቸውም በፊት አስቀድመው .....ከእናንተ ውስጥ የሚማረኩ አሉ፣ ነገር ግን እኔ አድናችኋለሁ›› ብለዋቸው ስለነበር ትንቢታቸው ደርሶ ኹለቱ መነኰሳት ተማረኩ ነገር ግን በአባታችን ጸሎት ወደ ገዳማቸው ተመለሱ። ዳግመኛም ከመነኰሳቱ ውስጥ ሰባቱን ዐረማውያን ማረኳቸው፣ ንብረታቸውንም ወስደው ኹለቱን ገድለው፣ አምስቱን በባሕር ውስጥ ጣሏቸው፤ በዚኸም ጊዜ አባታችን ማትያስ በአካለ ነፍስ መጥተው ‹‹ልጆቼ አይዟችሁ፣ እኔ ከእናንተ ጋር ነኝና አወጣችኋለሁ፣ ባሕሩንም በእሳት አቃጥለዋለሁ›› ብለው ካወጧቸው በኋላ ባሕሩን በእሳት አቃጥለውታል። የአቡነ ማትያስ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን። (ምንጭ በእንተ ቅዱሳን ኅሩያን መጽሐፍ) ✞ ✞ ✞

ቅዱስ ሚካኤል - መልአከ ምክሩ *** በቅዱሳት መጻሕፍት እግዚአብሔር ከቅዱሳን ጋር ስለሚያደርገው የምክር ጉባኤ ተጽፏል። ይህ መለኮታዊ ምክር ( the devine council) እግዚአብሔር ስለሚያደርገው እና ስለፍርዱ ከተመረጡ ቅዱሳን ጋር የሚያደርገው ነው። ይህን የሚያደርገውም ከቅዱሳንም መርጦ ላከበራቸው ያለውን ክብር ያሳይ ዘንድ ከሥልጣኑ በጸጋ እያሳተፋቸው እንጂ ከእግዚአብሔር ፍርድ እና ምክር የሚጎድል ኖሮ እነርሱ ሊሞሉለት አይደለም። የመጀመሪያው ይህን የተመረጡ ቅዱሳን ምክር የሚያሳይ ጥቅስ መዝ. 81/82 ነው፦ “እግዚአብሔር በአማልክት ማኅበር ቆመ፥ በአማልክትም መካከል ይፈርዳል።" ሌላኛው ደግሞ "እግዚአብሔርን በሰማይ የሚተካከለው ማን ነው? ከአማልክትስ ልጆች እግዚአብሔርን ማን ይመስለዋል? በቅዱሳን ምክር እግዚአብሔር ክቡር ነው፤ በዙሪያው ባሉት ሁሉ ላይ ታላቅና ግሩም ነው፤" የሚለው ነው። (መዝ. 89፥6-7) *** ቅዱስ ሚካኤል መልአከ ምክሩ የሚባል የመላእክት አለቃ ሆኖ የዚህ መለኮታዊ ምክር አካል ስለሆነ ነው። 'ተሾመ' የሚለው ቃል ይህን መመረጥ ይገልጣል። ከሌሎች መላእክት በተለየ በዙፋን ላይ ተቀምጦ መሳሉም ለዚሁ ነው። ድንግል ማርያምም የዚህ ማኅበር አካል ነች። ቀድሞ የክርስቶስ ምሳሌ የሆነው ሰሎሞን ለእናቱ ያለውን ክብር ይገልጥ በጎኑ ዙፋን አስቀምጦ ያማክራት ነበር። (1ኛ ነገ. 2፥19) ዳዊትም "ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች" ብሎ ተናግሮላታል። (መዝ. 44/45፥9) ሐዋርያትም እንዲሁ ናቸው፤ ጌታ በ12ቱ የእሥራኤል ነገዶች ላይ ሲፈርዱ በዙፋን እንደሚቀመጡ መናገሩ የመለኮታዊው ምክር አካላት እንዳደረጋቸው ያሳያልና። (ማቴ. 19፥28) ይህንም ነቢዩ ዳንኤል ቀድሞ ተናግሮታል፦ “ዙፋኖችም እስኪዘረጉ ድረስ አየሁ፥ በዘመናት የሸመገለውም ተቀመጠ፤ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ፥ የራሱም ጠጕር እንደ ጥሩ ጥጥ ነበረ፤ ዙፋኑም የእሳት ነበልባል ነበረ፥ መንኰራኵሮቹም የሚነድድ እሳት ነበሩ።” (ዳን. 7፥9) ነቢዩ 'ዙፋኖች' ያለው እግዚአብሔር ብዙ ዙፋኖች ኑረውት ሳይሆን የተመረጡ ቅዱሳን የሚሳተፉበትን ከእግዚአብሔር ፍርድ ሲወጣ ቀድመው የሚያውቁ እና በባለሟልነት የሚማልዱ የቅዱሳን ጉባኤ ክብራቸውን ለማመልከት ነው። *** በዚህ ሁሉ ታላቁ መልአክ ሚካኤል አለ! ኦ ሚካኤል ኦ ሚካኤል! ከእግዚአብሔር የተሰጠህ ክብር ታላቅ ነው። ለጎስቋሎች ባሮችህ ለምንልን። አሜን።

††† ✝✝✝🌹እንኳን ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል እና ለቅዱሳኑ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፣አደረሰን። ††† †††✝✝✝ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††✝✝✝ ††† በዚህች ቀን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤልን ጨምሮ ቅዱስ ላሊበላ: ቅድስት አፎምያና ቅዱስ ባሕራን ቀሲስ ይከበራሉ:: ††† ✝ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት †††✝ ††† ቅዱስ ሚካኤል በጥንተ ተፈጥሮ በኢዮር: ኃይላት በተባሉት ነገደ መላእክት ተሹሞ ነበር:: ሳጥናኤል በካደ ጊዜ እግዚአብሔር ባወቀ: አንድም በትሕትናውና ደግነቱ በ99ኙ ነገደ መላእክት ላይ ሁሉ ተሹሟል:: ከፍጥረት ወገን ከእመቤታችን ቀጥሎ የቅዱስ ሚካኤልን ያሕል ክብርና ርሕሩሕ የለም:: በምልጃውም: በረዳትነቱም የታወቀ መልአክ ነው:: መጽሐፍ "መልአከ ምክሩ ለእግዚአብሔር" ይለዋል:: "ወስሙ መስተሣሕልም" ይለዋል:: ቂም የሌለው: ለምሕረት የሚፋጠን: ደግ መልአክ ነውና:: በብሉይ ኪዳን በመከራ ለነበሩ ቅዱሳን ሁሉ ሞገስ: ረዳትና አዳኝ ቢሆናቸው "መጋቤ ብሉይ" ተሰኝቷል:: እሥራኤልን 40 ዘመን በበርሃ መርቷል: መግቧልም:: ቅዱስ መጽሐፍ ስለ እርሱ ብዙ ይላል:: (ዘፍ. 48:16, ኢያ. 5:13, መሳ. 13:17, ዳን. 10:21, 12:1, መዝ. 33:7, ራዕይ. 12:7) ደስ የሚለው ደግሞ ርሕሩሑ መልአክ ከእመቤታችን ጋር ልዩ ፍቅር አለው:: ከእናቷ ማሕጸን ጀምሮ እስከ ዛሬ እነሆ አብሯት አለ:: ደስ ብሎት ይታዘዛታል:: ማማለድ ሲፈልግም "እመቤቴ ሆይ! ቅደሚ" ይላታል:: ወደ እሳት መጋረጃ አብረው ገብተው ለዓለም ምሕረትን: በረከትን ያወርዳሉ:: ቅዱስ ሚካኤልን በዚሕች ዕለት ስለ እነዚህ ነገሮች እናከብረዋለን:- 1.በመላእክት ሁሉ ላይ አለቃ ሆኖ መሾሙን 2.ቅዳሴ ቤቱን (ግብፅ ውስጥ) 3.ቅድስት አፎምያን መርዳቱን 4.ቅዱስ ባሕራንን መጎብኘቱን 5.ቅዱስ ላሊበላን ወደ ሰማያት ማሳረጉን 6.ለፍጥረታት ሁሉ ምሕረት የሚጠይቅበት ዕለት ነውና:: ††† ሊቀ መላእክት በክንፈ ረድኤቱ ከክፉ ሁሉ ይጠብቀን:: ††† ✝✝ቅዱስ ላል ይበላ ንጉሥ †††✝✝ ††† በ12ኛው መቶ ክ/ዘመን መጨረሻ ላይ በሃገራችን የነገሠው ቅዱስ ላሊበላ:- ¤በብሥራተ መልአክ ተወልዷል ¤ቅዱሳት መጻሕፍትን ገና በልጅነቱ አጥንቷል ¤የንጉሥ ዘር ቢሆንም በጾምና ጸሎት: በትሕርምት አድጓል ¤በወንድሙ ቢገረፍም ቂም አልነበረውም ¤ስለ ወዳጆቹ ፍቅር መርዝ ጠጥቷል ¤በዙፋን ላይ የኢትዮዽያ ንጉሥ ሆኖ ቢቀመጥም እርሱስ አኗኗሩ ገዳማዊ ነበር ¤ከተባረከች ሚስቱ ቅድስት መስቀል ክብራ ጋር አንዲት ማዕድ ብቻ በቀን ይቀምሱ ነበር:: ለዛውም ለምለሙን ለነዳያን ሰጥተው እነርሱ የሚበሉት የእንጀራውን ቅርፍት (ጠርዝ) ብቻ ነበር:: በአካለ ሥጋ ወደ ሰማያት ተነጥቆ ብዙ ምሥጢራትን አይቷል ¤በምሳሌውም ሃገረ ሮሃን (ላስታን) ገንብቷል ¤ዛሬም ድረስ ምስጢር የሆኑት ፍልፍል አብያተ መቃድስ የእጆቹ ሥራዎች ናቸው:: ሥራውን ከፈጸመ በኋላ መንግሥቱን ለቅዱስ ነአኩቶ ለአብ አውርሶ: በመንኖ ጥሪትና በቅድስና ኑሮ በዚሕች ቀን አርፏል:: ጌታችን ስምህን ያከበረ: ዝክርህን የዘከረ: ከቤትህ ያደረውን: ከርስተ መንግስተ ሰማያት አካፍለዋለሁ ሲል ቃል ኪዳን ገብቶለታል:: ††† በረከቱን: ክብሩን ያድለን:: ††† ቅድስት አፎምያ ††† ከቅዱስ አስተራኒቆስ ጋር በተቀደሰ ትዳር የኖረች ¤ምጽዋትን ያዘወተረች ¤በፍቅረ ቅዱሳን የጸናች ¤ንጽሕናዋን ጠብቃ ሰይጣንን ያሳፈረች ደግ እናት ናት:: ዛሬ የቅዱስ ሚካኤልን ስዕል ታቅፋ: በትእምርተ መስቀልም አማትባ አርፋለች: ቅዱሱ መልአክም ወደ ገነት አሳርጓታል:: ††† ✝✝ቅዱስ ባሕራን ቀሲስ †††✝✝ የደጋግ ክርስቲያኖች ግን የድሆች ልጅ: ¤በሕጻንነቱ በግፍ ወደ ባሕር የተጣለ: ¤በእግዚአብሔር ጥበብ አድጎ የግፈኛውን ንብረት የወረሰ: ¤በመልካም ትዳር በቅስና ያገለገለ: ¤ምጽዋትን ያዘወተረ: አብያተ ክርስቲያናትን ያሳነጸ ደግ ክርስቲያን ነው:: ¤በዚህች ቀን አርፎ ቅዱስ ሚካኤል ወዳጁ በዕረፍተ ገነት አኑሮታል:: ††† አምላካችን እግዚአብሔር ከቅዱሳኑ በረከት ይክፈለን:: አሜን:: ††† ††† ሰኔ 12 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት 2.ቅዱስ ላሊበላ ጻድቅ (ንጉሠ ኢትዮዽያ) 3.ቅድስት አፎምያና ባለቤቷ ቅዱስ አስተራኒቆስ 4.ቅዱስ ባሕራን ቀሲስ 5.ቅዱስ እለ እስክንድሮስ ሊቅ 6.አባ ዮስጦስ ሊቀ ዻዻሳት (የሐዋርያው ቅዱስ ማርቆስ ደቀ መዝሙር) 7.አባ ቄርሎስ ሊቀ ዻዻሳት ††† ወርሐዊ በዓላት 1.ቅዱስ ማቴዎስ ሐዋርያ 2.ቅዱስ ድሜጥሮስ 3.ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ 4.ቅዱስ ቴዎድሮስ ምሥራቃዊ (ሰማዕት) 5.ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ 6.አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ ††† "በሰማይም ሰልፍ ሆነ:: ሚካኤልና መላእክቱ ዘንዶውን ተዋጉ:: ዘንዶውም ከመላእክቱ ጋር ተዋጋ:: አልቻላቸውምም:: ከዚያም ወዲያ በሰማይ ሥፍራ አልተገኘላቸውም:: ዓለሙንም ሁሉ የሚያስተው ዲያብሎስና ሰይጣን የሚባለው ታላቁ ዘንዶ እርሱም የቀደመው እባብ ወደ ምድር ተጣለ::" ††† (ራዕይ. 12:7) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††