Mahtot Eshetie / ማኅቶት እሸቴ
Open in Telegram
መንፈሳዊ የቤተክርስቲያን አስተምህሮና ሙሉ የግእዝ ቋንቋ ሥልጠና ትምህርት ማስተማሪያ የቴሌግራም ገጽ። በመደበኛ መርሐ ግብር የግእዝ ቋንቋ ሥልጠናን መከታተል የምትሹ በኮሜንት መስጫው ጻፉልኝ።
Show more4 654
Subscribers
+5624 hours
+1677 days
+17430 days
Posts Archive
የሰኞ ውዳሴ ማርያም ማብራሪያ
#ክፍል_ሦስት
ከዘሀሎ - ብርሃን
♦️🔹♦️ ዘሀሎ
"ዘሀሎ ወይሄሉ ... የነበረው የሚኖረው የመጣው ዳግመኛም የሚመጣው ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ ያለመለወጥ ፍጹም ሰው ሆነ አንዱ ወልድ በሥራው ሁሉ አልተለየም የእግዚአብሔር ቃል መለኮት አንድ ነው እንጂ ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ:-
🔹🔸🔹 ነፍስ አልነሣም ፣ ምትሐት ፣ ኅድረት ፣ ተለወጠ የሚሉ መናፍቃን አሉና ለእነዚህ መልስ ይሰጣል።
🔈ነፍስ አልነሣም ማለት ሥጋን ብቻ ነስቶ ስለ ነፍስ ፈንታ መለኮቱ ሆነው ማለት ነው።
🔈ምትሐት ማለት ሰው አልሆነም ሥጋ አለበሰም መስሎ ተገለጸ እንጂ ማለት ነው።
🔈ኅድረት ማለት መለኮት በሥጋ አደረ አልተዋሐደም ማለት ነው። ልክ እንደ ዳዊትና ማኅደር።
🔈ተለወጠ ማለት ሰው በሆነ ጊዜ መለኮቱ ጠፋ ተለወጠ ማለት ነው።
✍️ ነፍስ አልነሣም ፣ ምትሐት ላሉት : ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው ወልድ ዋሕድ በሥራው ሁሉ ከእኛ አልተለየም። አንድ ግብር አንድ ባሕርይ ነው እንጂ። ይህም ማለት ሰው ሁኖ ከኃጢአት በቀር እንደ እኛ የሰውነትን ሥራ ሠርቷል ማለት ነው። ይህም ምትሐት አለመሆኑን ያሳያል ማለት ነው። እኛንም በሦስት ወገን ይመስለናል እሊህም ፤
1, የአብርሃም ልጅ የዳዊት ልጅ በመባል (ኃይለ ዘርዕ)።
2, አባ እማ ብሎ በመጥራት (ኃይለ ንባብ)።
3, በመብላት በመጠጣት (ኃይለ እንስሳ)
✍️ ኅድረት ላሉት :- ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው ወልድ ዋሕድ በሥራው ሁሉ ከነሣው ሥጋ አልተለየም። ይህ ማለት ሰው ከሆነ ጀምሮ የማሠራውን ሥራ ሁሉ በተዋሕዶ ይሠራዋል እንጂ መለኮት ከሥጋ ተለይቶ የሠራበት ጊዜ የለም ማለት ነው።
✍️ ተለወጠ ላሉት :- ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው ወልድ ዋሕድ ሰውም ቢሆን ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ አልተለየም። ይህ ማለት ምንም እንኳ ከአብ ከወልድ ተለይቶ ሰው ቢሆን ሥጋን ቢነሣ ሥጋን መልበሱ ግን ከመለኮት ከባሕርይ አንድነቱ አለየውም ማለት ነው።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ሰውም ቢሆን ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ካልተለየ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ተፈሥሒ ኦ ቤተልሔም
"ተፈሥሒ ኦ ቤተልሔም ሀገሮሙ ለነቢያት ... ፤ የነቢያት ሀገራቸው ቤተልሔም ሆይ ደስ ይበልሽ ሁለተኛው አዳም ክርስቶስ ባንቺ ዘንድ ተወልዷልና። የቀደመውን ሰው አዳምን ከምድር (ከሲዖል) ወደ ገነት ይመልሰው ዘንድ። አዳም ሆይ መሬት ነህና ወደ መሬት ትመለሳለህ ብሎ የፈረደበትንም የሞት ፍርድ ያጠፋለት ዘንድ ብዙ ኃጢአት ባለችበት የእግዚአብሔር ጸጋ ትበዛለች። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 እመቤታችንን ቤተልሔም አላት ቤተልሔም ማለት የእንጀራ ቤት ማለት ነው እሷም የሕይወት እንጀራ ክርስቶስን ወልዳለችና። የነቢያት ሀገራቸው ማለቱም ነቢያት ስለ እመቤታችን ትንቢት ስለተናገሩ ነው።
🔹🔸🔹 ክርስቶስ ሁለተኛው አዳም መባሉ አዳም ከኅቱም ምድር እንበለ ዘርዕ እንደ ተገኘ ጌታም ከኅቱም ማኅፀነ ድንግል እንበለ ዘርዕ ተገኝቷልና። #አንድም ፡ አዳም በኃጢአቱ ሰውን ሁሉ እንደ ጎዳው ጌታም በትሩፋቱ ሰውን ሁሉ ጠቅሞታልና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ዳግማይ አዳም ከሚባል ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ትትፌሣሕ
"ትትፌሣሕ ወትትሐሠይ ኵሉ ነፍስተ ሰብእ ... ፤ የሰው ሁሉ ሰውነት ፈጽሞ ደስ ይላታል በሰማይ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን በምድርም ሰላም ለሰውም እርሱ በሚፈቅደው እያሉ ጩኸው ንጉሥ ክርስቶስን ከመላእክት ጋራ ያመሰግኑታል የቀደመውን ርግማን አጥፍቷልና የጠላት ምክሩን አፈረሰበት ለአዳምና ለሔዋን የእዳ ደብዳቤያቸውን ቀደደላቸው በዳዊት ሀገር የተወለደ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዳምንና ሔዋንን ነፃ አደረጋቸው። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 በጌታ ልደት ሰውና መላእክት በአንድነት በደስታ አመስግነዋል ዘምረዋል።
"ድንገትም ብዙ የሰማይ ሠራዊት ከመልአኩ ጋር ነበሩ። እግዚአብሔርንም እያመሰገኑ። ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ አሉ።" ሉቃ 2÷13-14
ይህም በጌታ ልደት ሰውና መላእክት አንድ መሆናቸውን ያሳያል።
"ክርስቶስን በማመን ያመሰግኑት ዘንድ ሰውና መላእክት ዛሬ በልደት ቀን አንድ መንጋ ሆኑ" እንዳለ ቅዱስ ያሬድ በልደት ድጓ።
🔹🔸🔹 የጠላት ዲያብሎስ ምክሩን አፈረሰበት ማለት ፤ ዲያብሎስ አዳምና ሔዋንን ያሳታቸው በእባብ አካል ተሠውሮ ነው። ክርስቶስም በሰው አካል መለኮቱን ሠውሮ ድል አድርጎታልና።
"ሰይጣን በሽንገላው በእባብ ሥጋ በሠውሩ እንደ ሞትነ ሁሉ ፤ የእግዚአብሔር ቃል ዘመዳችን ከምትሆን ከእመቤታችን በመሠወሩ ድኅነታችን ሆነ።" መቅድመ ወንጌል
#አንድም ፡ የጸላኢ ዲያብሎስ ምክሩን አፈረሰበት ሥጋን በመቃብር ነፍስን በሲዖል ተቆራኝቼ እኖራለሁ ብሎ ነበር። የመከረባቸውን ሥጋና ነፍስ ጌታ ተዋሕዶ አድኖበታልና። ይህንንም የጌታን የማዳን መንገድ ድንቅ ነው ይሉታል መምህራን። ምክንያቱም ደካማ ሥጋን ለብሶ በደካማ ሥጋ ተገልጦ ነውና ድል ያደረገው።
"ኃያል መለኮት በእርሱ ዘንድ ደካማ የሆነውን ዲያብሎስን ድል ቢያደርገው ድንቅ አይደለም ፤ ድንቅነቱስ ደካማ ሥጋ በእርሱ ላይ የሰለጠነበትን ዲያብሎስን ድል ማድረጉ ነው እንጂ" እንዳለ። ይህ ማለት መለኮት ዲያብሎስን ድል ያደረገው በሥጋ ባሕርይ ራሱን ሠውሮ መሆኑን ለመናገር ነው።
🔹🔸🔹 የአዳምና የሔዋንን የእዳ ደብዳቤያቸውን አጠፋላቸው ይላል ዲያብሎስ የጨለማ መጋረጃ ጋርዶ ሥቃይ አበዛባቸው ፤ ሥቃይ እንዳቀልላችሁ የባርነት ስም ጽፋችሁ ስጡኝ አላቸው። ከዛ አዳም የዲያብሎስ ባሪያ ሔዋን የዲያብሎስ ባሪያ ብለው ጽፈው ሰጡት። ያንን በሁለት ዕብነ በረድ አድርጎ አንዱን በሲዖል አንዱን በዮርዳኖስ ጥሎት ነበር። ጌታ በዮርዳኖስ የተጣለውን ሲጠመቅ እንደ ሰውነቱ ተረግጦ እንደ አምላክነቱ አቅልጦ አጠፋላቸው። በሲዖል የተጣለውን ደግሞ በአካለ ነፍስ ወደ ሲዖል ሲወርድ አጠፋላቸው።
#አንድም : ጌታ በካህናት አድሮ የኛን የኃጢአት እዳ በየዕለቱ ማጥፋቱን መናገር ነው። ይኸውም እኩይ ፍልስጣ የሚባል ከሰይጣን ወገን አለ በየዕለቱ የምንሠራውን ኃጢአታችንን እየጻፈ ያዘክራል ቄሱ እግዚአብሔር ይፍታ ባለን ጊዜ ይፋቅልናልና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። አዳምንና ሔዋንን ነፃ ካደረጋቸው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ብርሃን
"ብርሃን ዘበአማን ዘያበርህ ለኵሉ ሰብእ ... ፤ በዚህ ዓለም ለሚኖሩ ሰዎች የምታበራ እውነተኛ ብርሃን ስለሰው ፍቅር ወደ ዓለም የመጣህ ፍጥረት ሁሉ በመምጣትህ ደስ አለው። አዳምን ከስህተት አድነኸዋልና ሔዋንንም ከሞት ጻዕረኝነት ነፃ አድርገኻታልና የምንወለድበትን መንፈስ ረቂቁን ልደት ሰጠኸን ከመላእክት ጋርም አመሰገንኽ። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ:-
🔹🔸🔹ሰው ፈጽሞ ደስ የሚሰኘው ለዘመናት በዲያብሎስ ባርነት ሲገዛ ከአምላኩ ተለይቶ ሞት ተፈርዶበት ያነ ፍርድ ተወግዶ ከሞት ድኖ የእግዚአብሔር ልጅ በመባሉ ነውና። ይህም የተገኘው እግዚአብሔር ሰውን በመውደዱ ልጁን ለሕማም ለሞት አሳልፎ በመስጠቱ ነው። ልጁን አሳልፎ በመስጠቱም በእርሱ ያመነ ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው ነው።
"በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።" (ዮሐ 3:16) እንዳለ።
🔹🔸🔹 ወልድ የአብ ክንዱ መባሉ ስለምን ነው ቢሉ ፤ የሰው ኃይሉ በክንዱ እንዲታወቅ የአብ ኃይሉም በወልድ ታውቋልና። #አንድም: ክንድ ከአካል ሳይለይ የወደቀውን እቃ አንሥቶ እንዲመለስ ወልድም ከአብ አንድነት ሳይለይ ሰው ሁኖ አዳምን አድኖ በአባቱ ዕሪና ተቀምጧልና። #አንድም: በክንድ የራቀውን ያቀርቡበታል የቀረበውን ያርቁበታል ፤ አብም በወልድ ጻድቃንን ኑ ወደ እኔ ብሎ ያቀርብበታል ፣ ኃጥኣንን ከእኔ ሂዱ ብሎ ያርቅበታል። ይህም የዕለተ ምጽአቱን መናገር ነው።
🔹🔸🔹ሰአሊ ለነ ቅድስት። የአብ ቀኝ እጁ ክንዱ ከተባለ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
➢➢ የቀጣይ ትምህርት
#ክፍል_ሦስት
የሰኞ ውዳሴ ማርያም
(ዘሀሎ - ብርሃን )
➜ ነሐሴ / 2 / 2018 ዓ.ም
©መ/ር ማኅቶት እሸቴ
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
የሰኞ ውዳሴ ማርያም ማብራሪያ
#ክፍል_ሁለት
ከፈቀደ - ተፈሣሕ
♦️🔹♦️ ፈቀደ
"ፈቀደ እግዚእ ያግእዞ ለአዳም ... ፤ ጌታ ልቡ የዘነና የተከዘ አዳምን ነፃ ያወጣውና ወደ ቀድሞ ቦታው ይመልሰው ዘንድ ወደደ። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 አዳም በድሎ ከገነት ከወጣ በኋላ እያዘነና እየተከዘ ነው የኖረ። ማዘኑም እንደ ቤተ ፈት በዚህ ጊዜ እበላ እጠጣ ተድላ ደስታ አደርግ ነበር እያለ አይደለም ፤ አትብላ ያለኝን በልቼ ከፈጣሪየ ትእዛዝ ወጣሁ እያለ ነው እንጂ።
"አዳም ስለ ኃጢአቱ ከማልቀስ በቀር ሌላ ሀሳብ አልነበረውም" እንዳለ መቅድመ ወንጌል።
🔹🔸🔹 አምስት ሺህ ከአምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም በግብርናተ ዲያብሎስ የነበረ ከዳምን ነፃ ያደርገው ዘንድ ወደ ቀደመ ቦታው ወደ ገነት ወደቀደመ ክብሩ የእግዚአብሔር ልጅነት ይመልሰው ዘንድ ጌታ ወደደ።
በዚህም ቀን እመቤታችን አባቷ አዳምን አስከትላው መጥታ ነበርና ቢያየው አነሳው።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። አምስት ሺህ ከአምስት መቶ ዘመን በግብርናተ ዲያብሎስ የነበረ አዳምን ነፃ ካደረገው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ሠረቀ
"ሠረቀ በሥጋ እም ድንግል ... ከድንግል ያለ ወንድ ዘር በሥጋ ተወለደና አዳነን። ከይሲ (ዲያብሎስ) ያሳታት ሔዋንን እግዚአብሔር ምጥሽንና ጻርሽን አበዛዋለሁ ብሎ ፈረደባት ፤ ሰውን ወደደና ነፃ አደረጋት። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ:-
🔹🔸🔹 ዘር ምክንያት ሳይሆነው ከድንግል በሥጋ ተወልዶ አዳነን አለ በመለኮቱ አትወልደውምና። "በሰውነቱ እንጂ በመለኮቱ የማርያም ልጅ አይደለም" እንዳለ ቴዎ ሃይ.አበ 82÷20
🔹🔸🔹ልደቱን በዘርዕ ያላደረገው እንበለ ዘርዕ ያደረገው ለምንድን ነው ቢሉ። ቀዳማዊ ልደቱን ለመግለጽ። ድኅረ ዓለም ከእመቤታችን ያለ አባት መወለዱ ቅድመ ዓለም ከአብ ያለ እናት መወለዱን ያስረዳልና።
"ልደት ቀዳማዊ ተአውቀ በደኃራዊ ልደት : የመጀመሪያው ልደት በሁለተኛው ልደት ታወቀ" እንዳለ ኤራቅሊስ። ሃይ.አበ ም : 49
ዳግመኛም በዘርዕ በሩካቤ ተወልዶ ቢሆን ዕሩቅ ብእሲ (አምላክ ያልሆነ ሰው ወይም ሰው ብቻ) ፣ የዮሴፍ ልጅ ባሉት ነበርና።
"እንደ ዕሩቅ ብእሲ በዘር በሩካቤ ተወልዶ ቢሆንስ ብዙ ሰዎች በተሳሳቱ ነበር ፤ አምላክ ሰው መሆኑንም ሐሰት በአደረጉት ነበር።" ጎር ሃይ.አበ 60÷19
🔹🔸🔹 ዳግመኛም መወለዱን ድንግል ካልሆነች (ተፈትሖ ካላት) ያላደረገው ፤ ድንግል ከሆነች (ተፈትሖ ከሌላት) ያደረገው ስለምን ነው ቢሉ ፤ ትንቢቱ ምሳሌው ሊፈጸም ነው።
#ትንቢት:- "እነሆ ድንግል በድንግልና ፀንሳ በድንግልና ትወልዳለች" ተብሎ ተነግሯል። ኢሳ 7:14
#ምሳሌ:-
➣አዳም ከኅቱም ምድር ተገኝቷል ፤ ጌታም በኅቱም ማኅፀን ለመወለዱ ምሳሌ። ዘፍ 1:27
➣ሔዋን ከኅቱም ጎን ተገኝታለች ፤ ጌታም በኅቱም ማኅፀን ለመወለዱ ምሳሌ። ዘፍ 2:21
➣ለይስሐቅ ቤዛ የሆነው በግ ከኅቱም ግንድ ተገኝቷል ፤ ቤዛ ዓለም ክርስቶስም በኅቱም ማኅፀን ለመወለዱ ምሳሌ። ዘፍ 22:13
➣የእስራኤል መጠማት ያስወገደ ውኃ ከኅቱም ዓለት ተገኝቷል ፤ የነፍሳትን መጠማት ያበረደ ማየ ሕይወት ጌታም በኅቱም ማኅፀን ለመወለዱ ምሳሌ። ዘጸ 17:1
➣የሶምሶምን መጠማት ያበረደ ውኃ ከኅቱም የአህያ መንጋጋ ተገኝቷል ፤ ጽምዓ ነፍሳትን ያበረደ ማየ ሕይወት (የሕይወት ውኃ) ጌታም በኅቱም ማኅፀን ለመወለዱ ምሳሌ። መሣ 15:19
በዚህም ስትወልደው ማኅተመ ድንግልናዋ እንዳልተለወጠ ፤ ሰው ሲሆን አምላክነቱ ላለመለወጡ ምሳሌ። #አንድም እሷ ድንግልም እናትም ስትባል መኖሯ ክርስቶስ አምላክም ሰውም ሲባል ለመኖሩ ምሳሌ ነው።
🔹🔸🔹 ሔዋን የስሕተት ምክንያት ናትና ከሲዖል አልወጣችም የሚሉ መናፍቃን ነበሩና ነፃ አወጣት አለ። አስከትላት መጥታ ነበርና አነሳት።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ሔዋንን ነፃ ካወጣት ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ኢየሱስ
"ኢየሱስ ክርስቶስ ቃል ዘተሰብአ ... ፤ ሰው የሆነና በእኛ ያደረ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ክብሩንም ለአባቱ አንድ እንደመሆኑ ክብር አየን። ይቅር ይለን ዘንድ ወደደ። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ:-
🔹🔸🔹ክርስቶስ የሚለው ስም የመለኮት ወይም የትስብእት ብቻ አይደለም ከሁለት አካል አንድ አካል ከሁለት ባሕርይ አንድ ባሕርይ ሲሆን የወጣለት ስም ነው እንጂ።
ሰው ሆነ በእኛ አደረ ማለቱ ፤ መናፍቃን ሰው ሆነ ያለውን ይዘው ተለወጠ እንዳይሉ አደረ አለ ፣ አደረ ያለውን ይዘው ኅድረት እንዳይሉ ሰው ሆነ አለ። ሥጋንም ነፍስንም እንደተዋሐደ ለማጠየቅ በእኛ አደረ አለ።
🔹🔸🔹ለአባቱ አንድ ልጅ እንደመሆኑ ክብሩን አየን ማለቱ ጌታ ሰው በሆነ ጊዜ የእግዚአብሔር ልጅ የመሆኑን ክብሩን አየን ማለት ሲሆን ፤ ይህም አብ ልጄ ብሎ ሲመሰክርለት ፣ እሱ አባቴ ሲል ፣ ሐዋርያት የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ሲሉት ፣ በደብረታቦር የመለኮቱን ክብር ሲገልጽ ፣ ሙት ሲያስነሣ ድውይ ሲፈውስ የእግዚአብሔር ልጅነት ክብሩን አየን ማለት ነው።
🔹🔸🔹ሰአሊ ለነ ቅድስት። ይቅር ይለን ዘንድ ከወደደ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ርእየ
"ርእየ ኢሳያስ ነቢይ በመንፈሰ ትንቢት ... ፤ ነቢዩ ኢሳያስ በመንፈስ ቅዱስ የአማኑኤልን ምሥጢር አየ። ስለዚህም ሕፃን ተወለደልን ወልድም ተሰጠልን ብሎ አሰምቶ ተናገረ። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳያስ እግዚአብሔር ገልጾለት ከጌታ በድንግልና ተፀንሶ በድንግልና ከድንግል ማርያም እንደሚወለድ ስሙም አማኑኤል እንደሚባል በትንቢት ተናገረ።
"እነሆ፥ ድንግል በድንግልና ትፀንሳለች፥ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፥ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች።" (ኢሳ 7:14)
ነቢዩ ትንቢት የተናገረለት ጌታም ሕፃን ሁኖ ለእኛ ተወለደልን ወልድም ስለ እኛ ለሕማም ለሞት ተሰጠልን።
አማኑኤል ማለትም ሰው የሆነ አምላክ ማለት ነው።
🔹🔸🔹ሰአሊ ለነ ቅድስት። ከአብ በመወለዱ ወልድ ከአንቺ በመወለዱ ሕፃን ከተባለ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ተፈሣሕ
"ተፈሣሕ ወተሐሠይ ኦ ዘመደ እጓለ እመሕያው ... ፤ ሰው ሆይ ፈጽሞ ደስ ይበልህ። እግዚአብሔር ዓለሙን ወዶታልና የሚያምንበት ሁሉ እስከ ዘላለም ፈጽሞ ይድን ዘንድ አንድ ልጁን አሳልፎ ሰጥቶታልና። ልዑል ክንዱን ሰደደልን። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
የውዳሴ ማርያም ማብራሪያ
#ክፍል_አንድ
የውዳሴ ማርያም መቅድም
#መግቢያ
🔹🔸🔹የእመቤታችንን ምስጋና የደረሰው ሶርያዊዩ ሊቅ ቅዱስ ኤፍሬም ነው። ቅዱስ ኤፍሬም
ቅዱስ ያዕቆብ ዘንጽቢንን ደቀመዝሙር ሲሆን በጉባኤ ኒቅያ አርዮስን ለማውገዝ አብሮ ሂዶ ነበር።
ከተመለሱ በኋላም በራዕይ በአምደ ብርሃን መልኩ ተገልጾለት ከቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ ጋር ተገናኝቷል።
🔹🔸🔹ይህ ቅዱስ ለእመቤታችን ልዩ ፍቅር ስለነበረው ምጽዋት ሲሰጥ ዘወትር በእመቤታችን ስም ብቻ ይሰጥ ነበር። እመቤታችንንም ከመውደዱ የተነሣ የእመቤቴ ምስጋናዋ በዝቶልኝ እንደ ልብስ ለብሸው እንደ ምግብ ተመግቤው እያለ ሲመኝ ይኖር ነበር።
የፈለጉትን መግለጽ ለእግዚአብሔር ልማዱ ስለሆነ ገልጾለት ከአሥራ አራት ሺህ ድርሰት በላይ ደርሷል። የጸጋህን ማዕበል ግታልኝ እስኪል ድረስ።
🔹🔸🔹ዘወትር የሚጸልየው ጸሎቱም ከሉቃስ ወንጌል "በስደስተኛው ወር ገብርኤል መልአክ ... ከድንግል ዘንድ ተላከ ..." የሚለውን እና "የእመቤታችን የማርያም ጸሎት (ጸሎተ እግዝእትነ ማርያም)" የሚለውን አውጥቶ በእድሜዋ ልክ 64 : 64 ጊዜ ይጸልይ ነበር።
🔹🔸🔹ከዕለታትም በአንድ ቀን የጧት ጸሎቱን አድርሶ ከሥራ ቦታው ተቀምጦ ሳለ ፤ እመቤታችን ትመጣለች ፣ የብርሃን ድንኳን ይተከላል ፣ የብርሃን ምንጣፍ ይነጠፋል ፣ የብርሃን ዙፋን ይዘጋጃል ከዛ ላይ ሁና "ሰላም ለከ ፍቁርየ ኤፍሬም ፣ ወዳጄ ኤፍሬም ሰላም ለአንተ ይሁን" ትለዋለች። እርሱም ታጥቆ እጅ ነስቶ ይቆማል።
"ወድሰኒ ፡ አመስግነኝ" ትለዋለች።
እርሱም "እፎ እክል ወድሶተኪ ዘኢይክሉ ወድሶተኪ ምድራውያን ወሰማያውያን ፤ ምድኣውያን ጻድቃን ሰማዕታት ሰማያውያን መላእክት አንቺን ማመስገን ያልተቻላቸው ለእኔ እንደምን ይቻለኛል" አላት።
#ማብራሪያ :- አሁን እንደዚህ ማለቱ ጻድቃን ሰማዕታት መላእክት የማያመሰግኗት ሁኖ ሳይሆን እንደ ክብሯ እንደ ቅድስናዋ መጠን ማመስገን አለመቻላቸውን መናገሩ ነው። እርሱም አይቻለኝም ማለቱ እንደ ክብርሽ እንደ ገናንነትሽ መጠን ማመስገን አይቻለኝም። አንቺ ከፍጡራን ሁሉ በላይ ነሽና አንቺን ፈጣሪ እንጂ ፍጡር አይበልጥሽምና ሲል ነው።
🔹እመቤታችንም "በከመ አለበወከ መንፈስ ቅዱስ ተናገር ፤ መንፈስ ቅዱስ በገለጠልህ መጠን ተናገር" አለችው።
🔹እርሱም "ባርክኒ ፣ ባርኪኝ" ይላታል።
🔹እመቤታችንም "በረከተ ወልድየ ወአቡሁ ወመንፈስ ቅዱስ ይኅድር በላዕሌከ ፤ የልጄ በረከት የባሕርይ አባቱ የአብ የባሕርይዐሕይወቱ የመንፈስ ቅዱስ በረከት ይደርብህ" አለችው።
🔹እርሱም ተባርኮ ምስጋናዋን ይጀምራል።
🔹🔸🔹 ቅዱስ ኤፍሬም ሲያመሰግናት ደቀመዝሙር ቅኔ ቆጥሮ እንዲቀኝ ድርሰት አስቦ እንዲጽፍ አይደለም ብልህ ደቀመዝሙር ያጠናውን ቀለም ከመምህሩ ፊት ሰተት አድርጎ እንዲያቀርብ እንደዛ ነው እንጂ።
#ማብራሪያ :- የቅዱስ ኤፍሬም ድርሰት የመንፈስ ቅዱስ በመሆኑ በቃል መላልሶ እንደተጠና ቀለም ያለምን መቆራረጥና መጥፋት ሰተት አድርጎ ደርሶታል።
🔹🔸🔹እመቤታችን ምስጋናውን ስታስደርሰው በሰባት ከፍላ አስደርሳዋለች። ይህም በሰባቱ ዕለታት መመስገን ፈቃዷ ቢሆን ነው።
#አንድም ፡ በሰባቱ ዕለታት ትመሰላለችና።
♦️🔹♦️በዕለተ እሑድ ትመሰላለች
በዕለተ እሑድ የፍጥረታት ሥር መሠረት መገኛ የሚሆኑ አራቱ ባሕርያት (መሬት ፣ ውኃ ፣ እሳት ፣ ነፋስ) ተገኝተዋል።
ከእርሷም በአነዋወሩ የፍጥረታት የፍጥረታት የመገኘት ምክንያት የተባለ የፍጥረታት መገኛና ፈጣሪ ጌታ ተገኝቷልና።
♦️🔹♦️ በዕለተ ሰኑይ ትመሰላለች
በዕለተ ሰኑይ ፡ ከዚህ እስከ ብሩህ ሰማይ የነበረውን ውኃ ከሦስት እጅ ከፍሎታል። አንዱን እጅ ከላይ ሰቅሎታል #ሐኖስ ነው። አንዱን እጅ በዚህ ዓለም በዙሪያው ወስኖታል #ውቂያኖስ ነው። አንዱን እጅ አጽንቶ የብርሃን ማኅደር (መመላለሻ) አድርጎታል #ጠፈር ነው።
ይኸውም ምሳሌ ነው።
➣ዕለተ ሰኑይ - የእመቤታችን
➣ጠፈር - ከእርሷ የነሣው ሥጋ
➣ብርሃን - የጌታ ምሳሌ።
♦️🔹♦️ በዕለተ ሠሉስ ትመሰላለች
በዕለተ ሠሉስ : ምድር ያለዘሩባትን
"ዘርን የሚሰጥ ሣርንና ቡቃያን በምድርም ላይ እንደ ወገኑ ዘሩ ያለበትን ፍሬን የሚያፈራ ዛፍን ታብቅል አለ፤ እንዲሁም ሆነ። " (ዘፍ 1:11)
ባለ ጊዜ በእጅ የሚለቀሙ አትክልት ፣ በማጭድ የሚታጨዱ አዝእርት ፣ በምሳር የሚቆረጡ ዕፅዋት ለሥጋውያን ምግብ የሚሆኑ ተገኝተዋል።
ከእርሷም የመንፈሳዊያን ምግብ የሚሆን ጌታ ተገኝቷልና።
♦️🔹♦️ በዕለተ ረቡዕ ትመሰላለች
በዕለተ ረቡዕ ፡ " እግዚአብሔርም አለ። ቀንና ሌሊትን ይለዩ ዘንድ ብርሃናት በሰማይ ጠፈር ይሁኑ፤ ለምልክቶች ለዘመኖች ለዕለታት ለዓመታትም ይሁኑ፤ " (ዘፍ 1:14)
ባለ ጊዜ ፀሐይ ፣ ጨረቃ ፣ ከዋክብት ተገኝተዋል።
ከእርሷም ብርሃን ጌታ ተገኝቷልና።
♦️🔹♦️ በዕለተ ሐሙስ ትመሰላለች
በዕለተ ሐሙስ : " እግዚአብሔርም አለ። ውኃ ሕያው ነፍስ ያላቸውን ተንቀሳቃሾች ታስገኝ፥ ወፎችም ከምድር በላይ ከሰማይ ጠፈር በታች ይብረሩ።" (ዘፍ 1:20)
ባለ ጊዜ በእግራቸው የሚበሩ ፣ በክንፋቸው የሚበሩ ፣ በደረታቸው የሚሳቡ በደመ ነፍስ ሕያዋን የሚሆኑ ፍጥረታት ተገኝተዋል።
ይኸውም ምሳሌ ነው።
➣ በልባቸው የሚሳቡት ፍጥረታት በሕግ አግብተው ተወስነው የሚኖሩ የምእመናን ምሳሌ።
➣ በእግራቸው የሚሽከረከሩ ከትሩፋት ወደ ትሩፋት ከገድል ወደ ገድል የሚሸጋገሩ የባሕታውያን ምሳሌ።
➣ በክንፋቸው የሚበሩ ተመስጦ ያላቸው የሰማዕታት ምሳሌ።
➣ ዕለቲቱ የእመቤታችን
➣ ባሕር የጥምቀት ምሳሌ።
♦️🔹♦️ በዕለተ ዐርብ ትመሰላለች
በዕለተ ዐርብ : የፍጥረታት ሁሉ በኵር አዳም ተፈጥሯል። ከእርሷም ሁለተኛው አዳም ጌታ ተገኝቷልና።
♦️🔹♦️ በዕለተ ቀዳሚት ትመሰላለች
በዕለተ ቀዳሚት : ሥጋዊ ረፍት ተገኝቷል። " እግዚአብሔርም የሠራውን ሥራ በሰባተኛው ቀን ፈጸመ፤ በሰባተኛውም ቀን ከሠራው ሥራ ሁሉ ዐረፈ።" (ዘፍ 2:2) እንዳለ።
ከእርሷም የመንፈሳውያን ረፍት የሚሆን ጌታ ተገኝቷል።
#ማብራሪያ :- ሥጋዊ ረፍት ማለት በዚህ ዓለም ከሥጋዊ ሥራ ከማረስ ከመቆፈር ከመጽሐፍ ከመደጎስ ማረፍ ማለት ነው። መንፈሳዊ ረፍት ማለት ደግሞ ከዚህ ዓለም ድካም መከራ ማረፍ ይኼውም በገነት በመንግስተ ሰማያት የሚገኝ ነው።
ይህ መቅድም ነው።
➢➢ የቀጣይ ትምህርት
#ክፍል_ሁለት
የሰኞ ውዳሴ ማርያም
➜ ነሐሴ / 1 / 2018 ዓ.ም
©መ/ር ማኅቶት እሸቴ
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
እንኳን ለጾመ ፍልሰታ አደረሳችሁ።
ጾሙን ታሳቢ በማድረግ በቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ የተደረሰውን ተወዳጁን የእመቤታችንን ውዳሴ ማርያም ትርጓሜና ማብራሪያ በሚዲያ በጽሑፍ መልኩ የምንማር ይሆናል።
በውዳሴ ማርያም ምስጋናዋ ላይ ያላችሁን ማናቸውንም ጥያቄ መጠየቅ ትችላላችሁ ለምትጠይቋቸው ጥያቄዎችም መልስ ለመስጠት ዝግጁ ነን።
የማስተማሪያ ሚዲያዎች
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
መ/ር ማኅቶት እሸቴ
ሐምሌ 30 / 2018 ዓ.ም
የክርስቶስ መወለዱ እንዴት ነው?
ዕቅበተ እምነት
ክፍል አምስት
🖋#ጥያቄ :- የክርስቶስ መወለዱ እንዴት ነው?
🖋#መልስ :- ክርስቶስ ሁለት ልደታት አሉት እነዚህንም በዝርዝር እናያለን።
✍️የመጀመሪያ ልደቱ ቅድመ ዓለም ከአብ አካል ዘእም አካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ የተወለደው ነው።
✍️ሁለተኛው ልደቱ ድኅረ ዓለም ከእመቤታችን ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ የተወለደው ነው።
🖋#ጥያቄ :- የመጀመሪያ ልደቱ እንዴት ነው?
🖋#መልስ :- የመጀመሪያ ልደቱ ከአብ አካል ዘእም አካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ የተወለደው ዓለም ከመፈጠሩ ዘመን ከመቆጠሩ በፊት የተወለደ ሲሆን ይህም አይመረመርም።
አብ አባቱ ሲሆን ልጁን በዘመን አይቀድመውም። ወልድም ከአብ ቢወለድ በዘመን ወደ ኋላ አይሆንም። በአብና በወልድ መቀዳደም መበላለጥ የለምና።
🔹🔸🔹ቀዳማዊ ልደቱን በጎላ በተረዳ ያወቅነው በደኃራዊ ልደቱ ነው።
"ልደት ቀዳማዊ ተአውቀ በደኃራዊ ልደት : የመጀመሪያው ልደት በሁለተኛው ልደት ታወቀ" እንዳለ ኤራቅሊስ። ሃይ.አበ ም : 49
ይህም ማለት ጌታችን ከእመቤታችን ከተወለደ ወዲህ አንድነት ሦስትነት በጎላ በተረዳ ስለታወቀ ነው። አንድነት ሦስትነት ሲታወቅ ወልድ ከአብ ያለ እናት እንደተወለደ ታወቀ።
አብም ይህ ልጄ ነው ብሎ በዮርዳኖስና በደብረታቦር መሰከረ። ወልድም አባቴ እያለ ተናገረ።
✍️ የአብ አባትነትን የወልድ ልጅነትን መጻሕፍት የተናገሩትን በክፍል ሦስት ታገኙታላችሁ።
🔹🔸🔹 ቀዳማዊ ልደቱ አይመረመርም።
የወልድ ከአብ በቅድምና መወለዱ እንደዚህ ብሎ ነው በዚህ ጊዜ ነው ተብሎ አንደበት ሊናገረው ሕሊና ሊመረምረው አይችልም።
ዲዮናስዮስ የተባለ ሊቅ በሃይማኖተ አበው "ልደተ ወልድ ወጸአተ መንፈስ ቅዱስ እም አብ ይትነከር ወኢይትነገር ወይትሌዓል ላዕለ ኵሉ ሕሊናት ፤ የወልድ ከአብ መወለድና የመንፈስ ቅዱስ ከአብ መገኘት ይደነቃል እንጂ እንዲህ ነው ተብሎ ደአይነገርም። ከሕሊናት ሁሉ በላይ ከፍ ከፍ ያለ ነውና።" እንዳለ ሃይ.አበ 10÷12
🖋#ጥያቄ :- ሁለተኛ ልደቱስ እንዴት ነው?
🖋#መልስ :- ሁለተኛ ልደቱ ለአዳም የገባው ቃል ሲፈጸም ከአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን በኋላ በብስራተ መልአክ ከእመቤታችን በድንግልና ተጸንሶ በድንግልና የተወለደው ነው።
ይህንንም መጻሕፍት እንደዚህ ይመሰክራሉ።
➣" ስለዚህ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል፤ እነሆ፥ ድንግል ትፀንሳለች፥ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፥ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች።"
(ኢሳ 7:14)
➣ " የኢየሱስ ክርስቶስም ልደት እንዲህ ነበረ። እናቱ ማርያም ለዮሴፍ በታጨች ጊዜ ሳይገናኙ ከመንፈስ ቅዱስ ፀንሳ ተገኘች።"
(ማቴ 1:18)
➣ " እነሆ የጌታ መልአክ በሕልም ታየው፥ እንዲህም አለ። የዳዊት ልጅ ዮሴፍ ሆይ፥ ከእርስዋ የተፀነሰው ከመንፈስ ቅዱስ ነውና እጮኛህን ማርያምን ለመውሰድ አትፍራ። ልጅም ትወልዳለች፤ እርሱ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን ኢየሱስ ትለዋለህ።"
(ማቴ 1:21- 22)
➣ " መልአኩም እንዲህ አላት። ማርያም ሆይ፥ በእግዚአብሔር ፊት ጸጋ አግኝተሻልና አትፍሪ።
እነሆም፥ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፥ ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ።እርሱ ታላቅ ይሆናል የልዑል ልጅም ይባላል፥ ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል፤ በያዕቆብ ቤትም ላይ ለዘለላም ይነግሣል፥ ለመንግሥቱም መጨረሻ የለውም። ማርያምም መልአኩን። ወንድ ስለማላውቅ ይህ እንዴት ይሆናል? አለችው። መልአኩም መልሶ እንዲህ አላት። መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፥ የልዑልም ኃይል ይጸልልሻል ስለዚህ ደግሞ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል።" ሉቃ 1÷30-35
➣ " በታላቅ ድምፅም ጮኻ እንዲህ አለች። አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ፥ የማኅፀንሽም ፍሬ የተባረከ ነው። የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ እንዴት ይሆንልኛል?" ሉቃ 1÷42-43
➣ " ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ።"
(ዮሐ 1:14)
➣ " ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን የተወለደውን ልጁን ላከ።"
(ገላ 4:4)
➣ "ድንግል ማርያም ሥጋን በወለደች ጊዜ ቃልን ወለደችው ፣ ቃልንም በሥጋ ስለወለደች በእውነት ወላዲተ አምላክ ናት።" ሃይ.አበ.አቡ 41÷4
➣ "ከሕሊናት ሁሉ ለራቀ ለዚህ ድንቅ ምሥጢር አንክሮ ይገባል ፤ ምድራዊት ሴት ሰው የሆነ እግዚአብሔር ቃልን ወለደችው። ድንግል ፈጣሪዋን ወለደችው እርሱም እናቱን ፈጠረ። ከእርሷም እርሱ የፈጠረውን ሥጋ ተዋሐደ።" ሃይ.አበ.ኤፍ 47÷2
🔹🔸🔹ቀዳማዊ ልደቱ እንደ ማይመረመር ደኃራዊ ልደቱም አይመረመርም የተወለደው በድንግልና ነውና። ይህንንም ቅዱስ ኤፍሬም በሃይማኖተ አበው አስረድቷል። አባ ሕርያቆስም በቅዳሴው ተናግሯል።
አብ ያለ እናት የወለደውን ድንግል ማርያም ያለ አባት ወለደችው። አብ ብቻውን የወለደውን ድንግል ማርያም ብቻዋን በመውለድ አብን መሰለችው።
ምንም እንኳ ለቀዳማዊ ልደቱ ዘመን ባይቆጠርለትም በሥጋ ለተወለደው ልደቱ ግን ዘመን ተቆጥሮለታል። በአስራ ሁለት ዓመቱ ወደ ቤተ መቅደስ ወጣ ፣ በሠላሳ ዘመኑ ተጠመቀ ይላልና።
#ማጠቃለያ :- ስለዚህም ለክርስቶስ ሁለት ልደታት አሉት። እሊህ ቅድመ ዓለም ከአብ ያለ እናት ድኅረ ዓለም ከእመቤታችን ያለ አባት በሥጋ የተወለደው ነው።
"ዳግመኛም ለወልደ እግዚአብሔር ሁለት ልደታት እንዳሉት እናምን ዘንድ ይገባናል። አንዱ ከዘመን አስቀድሞ ከእግዚአብሔር አብ የተወለደው ልደት ነው። ሁለተኛውም ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በኋላ ዘመን የተወለደው ልደት ነው።" ሃይ.አበ.ባስ 34÷6
➢➢ የቀጣይ ትምህርት
ክፍል ስድስት
የመለኮት እና የሥጋ ተዋሕዶ እንዴት ነው?
➜ ሐምሌ / 29 / 2018 ዓ.ም
©መ/ር ማኅቶት እሸቴ
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
ችግኝን ጠብቃ የቆየች ቤተክርስቲያን በችግሯ ጊዜ ችግኝ ትከሉ የሚል አባት በማየታችን እጂግ ያሳዝናል።
ክርስቲያኖች እየተነቀሉ ችግኝ ትከሉ የሚል አባት ሊሆን አይችልም።
+1
መጋቤ ሐዲስ የኔታ ቃለ ሕይወት በዛ ማን ናቸው?
ለዓመታት ትርጓሜን በጎንደር መካነ ነገሥት ግምጃ ቤት ማርያም በማስተማር ላይ ያሉት እና ወንጌልን ጨምሮ ከአምስት በላይ መጻሕፍትን በጻፍ ያሳተሙት የሐዲሳት የሊቃውንት የፍትሐ ነገሥት ትርጓሜ መምህር መጋቤ ሐዲስ ቃለ ሕይወት በዛ ያደረጉትን ቃለ መጠይቅ በፍኖተ ያሬድ ሚድያ ተከታተሉት።
👇👇👇
https://youtu.be/lXIMaZgwgUY?si=ShDfU7NngM-hqi_m
"አፍቅሮሙ ለነዳያን እስመ በእንቲአሆሙ ትረክብ ምሕረተ ፡
ነዳያንን ውደዳቸው ስለ እነርሱ ምሕረትን ታገኛለህና።"
ከአበው አንዱ
ክቡር ሊቀ ሊቃውንት የኔታ ዕዝራ ሐዲስ ከኢየሩሳሌም የአንድ ዓመት ጉብኝት ቆይታ በኋላ ወደ ታሪካዊቷ የጎንደር ከተማ ወደ ጉባኤ ቤታቸው በሰላም ተመልሰዋል።
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
በሁላችንም ዘንድ እጅግ የምንወደውን የእመቤታችን ውዳሴ ማርያም ትርጓሜና ማብራሪያ በጾመ ፍልሰታ የምንማማር ይሆናል።
የማስተማሪያ ሚዲያዎች እነዚህ ሲሆኑ #follow #share #Join በማድረግ ቤተሰቦቻችንን እያበዛን ትምህርቱን ተደራሽ እናድርገው።
መ/ር ማኅቶት እሸቴ
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
የክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት ማሳያዎቹ ምንድን ናቸው?
ዕቅበተ እምነት
ክፍል አራት
✍️ከክፍል ሦስት የቀጠለ
🖋#ጥያቄ :- የክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት ማሳያዎቹ ምንድን ናቸው?
🖋#መልስ :- የክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት ማሳያዎች ወይም ማረጋገጫዎች በዋናነት እነዚህ ናቸው።
➣፩፡ የአብ ገንዘብ ገንዘቡ መሆኑ።
➣፪፡ ከአብ ጋር አንድ መሆኑ።
➣፫፡ አብ የሚሠራውን መሥራቱ።
➣፬፡ አብ ባለበት ሁሉ መኖሩ።
#ማብራሪያ :- የክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት ማሳያዎቹ ከእነዚህ ከተጠቀሱት ሌሎች ተጨማሪ ነገሮች ቢኖሩም በእነዚህ ውስጥ መጠቃለል ይችላሉ።
ከዚህ በፊት ከክፍል አንድ እስከ ክፍል ሦስት ያየናቸው ትምህርቶች አንድና አንድ ዋና ዓላማቸው ክርስቶስ የባሕርይ አምላክ መሆኑን ማሳየት መሆኑን ልብ ልንል ይገባል። በዚህ በክፍል አራት ትምህርታችንም መጻሕፍትን መሠረት አድርገን የምናረጋግጠው የክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት ነው።
✍️ የባሕርይ አምላክነት ማሳያዎቹን በዝርዝር እንመልከታቸው።
♦️፩፡ የአብ ገንዘብ ገንዘቡ መሆኑ።
የአብ ገንዘብ የሆነ ሁሉ የወልድ ገንዘቡ ነው። ይህም ማለት አብ ከወልድ የተለየ ገንዘብ የለውም ወልድም ከአብ የተለየ ገንዘብ የለውም።
ገንዘብ ስንልም በሰማይ በምድር ያሉ ፍጥረታት ፣ ምስጋናው ፣ አምልኮቱ ፣ ሥልጣኑ ፣ አገዛዙ ፣ መለኮቱ ፣ ፈጣሪነቱ ፣ ቅድስናው ይህንን የመሰሉትን ሁሉ ማለታችን ነው።
ይህንንም መጽሐፍ ቅዱስ እንደዚህ ይነግረናል።
➣ " ለአብ ያለው ሁሉ የእኔ ነው፤ ስለዚህ። ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋል አልሁ።"
(ዮሐ 16:15)
➣ " የእኔም የሆነ ሁሉ የአንተ ነው የአንተውም የእኔ ነው።"
(ዮሐ 17:10)
♦️፪፡ ከአብ ጋር አንድ መሆኑ።
ወልድ ከአብ ያለመለየት ያለ ማነስ ያለ መበላለጥ አንድ ነው። አንድ ፈቃድ ፣ አንድ አገዛዝ ፣ አንድ ሥልጣን ፣ አንድ መለኮት ፣ አንድ ባሕርይ ፣ አንድ እሪና አላቸው።
ሊቁ አባ ሕርያቆስ "አብ ከልጁ አይበልጥም ፣ ወልድም ከመንፈስ ቅዱስ አይበልጥም ፣ መንፈስ ቅዱስም ከወልድ አያንስም ፣ ወልድም ከአባቱ አያንስም" በማለት አንድነታቸውን ይናገራል።
መጽሐፍ ቅዱስም አንድነታቸውን እንደዚህ በማለት ይመሰክራል።
➣ " እኔና አብ አንድ ነን።"
(ዮሐ 10:30)
➣ " እኔን ያየ አብን አየ።"
(ዮሐ 14:9)
♦️፫፡ አብ የሚሠራውን መሥራቱ።
አብ ያለ ልጁ ብቻውን ተይቶ የሠራው ሥራ የለም።
መጽሐፍ ቅዱስም ይህንን ይነግረናል።
➣ " ሁሉ በእርሱ ሆነ፥ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም።"
(ዮሐ 1:3)
➣ " እኔ በአብ እንዳለሁ አብም በእኔ እንዳለ አታምንምን? እኔ የምነግራችሁን ቃል ከራሴ አልናገረውም፤ ነገር ግን በእኔ የሚኖረው አብ እርሱ ሥራውን ይሠራል። እኔ በአብ እንዳለሁ አብም በእኔ እንዳለ እመኑኝ፤ ባይሆንስ ስለ ራሱ ስለ ሥራው እመኑኝ።"
(ዮሐ 14: 10-11)
➣ " አባቴ እስከ ዛሬ ይሠራል እኔም ደግሞ እሠራለሁ።"
(ዮሐ 5:17)
♦️፬፡ አብ ባለበት ሁሉ መኖሩ።
አብ ባለበት ወልድ አለ። ወልድም ባለበት አብ አለ። አብ ያለ ወልድ ብቻውን የኖረበት ዘመን የለምና።
የስለዚህም መጻሕፍትን ምስክርነት እንይ
➣ " እኔ ወደ አብ እሄዳለሁና፤ አብም ስለ ወልድ እንዲከበር በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ አደርገዋለሁ።"
(ዮሐን 14:13)
➣ " ወደ አብ ስለምሄድ ከዚህም በኋላ አታዩኝም።"
(ዮሐ 16:10)
➣ " ጥቂት ጊዜ አለ፥ አታዩኝምም፤ ደግሞም ጥቂት ጊዜ አለ፥ ታዩኛላችሁም፥ እኔ ወደ አብ እሄዳለሁና።"
(ዮሐ 16:16)
➣ " ከአብ ወጥቼ ወደ ዓለም መጥቻለሁ፤ ደግሞ ዓለምን እተወዋለሁ ወደ አብም እሄዳለሁ።"
(ዮሐ 16:28)
➣ " ያዕቆብ ሆይ፥ የጠራሁህም እስራኤል ሆይ፥ ስማኝ፤ እኔ ነኝ፤ እኔ ፊተኛው ነኝ እኔም ኋለኛው ነኝ።" የተባለ ለአብ ነው።
(ኢሳ 48:12)
➣ " ያለውና የነበረው የሚመጣውም ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ። አልፋና ዖሜጋ እኔ ነኝ ይላል።" የተባለ ለወልድ ነው።
(ራእ 1:8)
ኢሳይያስ ለአብ የተናገረውን ዮሐንስ በራእዩ ለወልድ መናገሩ አብ ባለበት ወልድ መኖሩን ያጠይቃል።
#ማጠቃለያ :- ከክፍል አንድ እስከ ክፍል አራት በተከታታይ ያየናቸው በሙሉ የክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት የሚያስረዱ ናቸው። ምስክር ያደረግነውም መጽሐፍ ቅዱስን ነው።
➢➢ የቀጣይ ትምህርት
ክፍል አምስት
የክርስቶስ መወለዱ እንዴት ነው?
➜ ሐምሌ / 25 / 2018 ዓ.ም
©መ/ር ማኅቶት እሸቴ
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
ተከታታይ መንፈሳዊ ትምህርቶችን ፣ ጥያቄ እና መልሶችን እንዲሁም ለጥያቄዎት መልስ ለማግኘትና እና የትርጓሜ ማብራሪያዎችን ለመከታተል በፌስቡክ እና በቴሌግራም ይወዳጁን።
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
የክርስቶስን የእግዚአብሔር ልጅነት ማን መሰከረ?
ዕቅበተ እምነት
ክፍል ሦስት
ከክፍል ሁለት የቀጠለ
✍️ በክፍል ሁለት ጽሑፋችን ላይ የባሕርይ አምላክ መሆን ያለበት ማን ነው ብለን እግዚአብሔር ብቻ ብለናል።
በመቀጠልም ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ነውን ብለን የእግዚአብሔር ልጅነቱን የመሰከሩ የነቢያትና የሐዋርያትን ምስክርነት አይተናል።
🖋#ጥያቄ :- የክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅነት ማን መሰከረ?
🖋#መልስ :- ነቢያትና ሐዋርያት ፣ አብ ፣ እራሱ ክርስቶስ መስክረዋል።
🎤#ማብራሪያ :- ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ስለመሆኑ ሦስት ምስክሮች እንዳሉት አይተናል።
የመጀመሪያ የነቢያትና የሐዋርያት ምስክርነት ነው (ይህም በክፍል ሁለት ተቀምጧል)።
ሁለተኛው የአብ ምስክርነት ሲሆን የመጨረሻው የራሱ ምስክርነት ነው።
💥የአብ ምስክርነት
እግዚአብሔር አብ ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ ልጁ እንደሆነ መስክሯል። ምስክሮቹም እነዚህ ናቸው።
➣ " እነሆም፥ ድምፅ ከሰማያት መጥቶ። በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው አለ።
" (ማቴ 3:17)
➣ "እርሱም ገና ሲናገር፥ እነሆ፥ ብሩህ ደመና ጋረዳቸው፥ እነሆም፥ ከደመናው። በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት የሚል ድምፅ መጣ።"
(ማቴ 17:5)
🔹🔸🔹በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ ከሰማይ ድምፅ መጥቶ ልጄ ብሎ የተነገረለት ለክርስቶስ ብቻ ሲሆን ይህም አብ ብቸኛ የባሕርይ ልጁ እንደሆነ ሲመሰክር ነው።
💥 የራሱ የክርስቶስ ምስክርነት
ኢየሱስ ክርስቶስ በቅዱስ መጽሐፍ ከአምሳ ጊዜ በላይ አብን አባቴ በማለት የእግዚአብሔር አብ ልጅነቱን ተናግሯል። ከእነዚህም ውስጥ ጥቂቶቹን እንይ።
➣ " በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ፥ ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም።"
(ማቴ 7:21)
➣" ስለዚህ በሰው ፊት ለሚመሰክርልኝ ሁሉ እኔ ደግሞ በሰማያት ባለው በአባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ፤"
(ማቴ 10:32)
➣ "በሰው ፊትም የሚክደኝን ሁሉ እኔ ደግሞ በሰማያት ባለው በአባቴ ፊት እክደዋለሁ።"
(ማቴ 10:33)
➣ " ሁሉ ከአባቴ ዘንድ ተሰጥቶኛል፤ ከአብ በቀር ወልድን የሚያውቅ የለም፥ ከወልድም በቀር ወልድም ሊገለጥለት ከሚፈቅድ በቀር አብን የሚያውቅ የለም።"
(ማቴ 11:27)
➣ " ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው። የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ በሰማያት ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና ብፁዕ ነህ።"
(ማቴ 16:17)
➣ " እነሆም፥ አባቴ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለሁ።"
(ሉቃ 24:49)
➣ " የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉት አላቸው።"
(ዮሐ 2:16)
➣ " እኔንም ወይም አባቴንም አታውቁም፤ እኔንስ ብታውቁኝ አባቴን ደግሞ ባወቃችሁ ነበር አላቸው።"
(ዮሐ 8:19)
➣ " ኢየሱስም። ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና አትንኪኝ፤ ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሄደሽ። እኔ ወደ አባቴና ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ ዓርጋለሁ ብለሽ ንገሪአቸው አላት።"
(ዮሐ 20:17)
➣ " እኔ ደግሞ ድል እንደ ነሣሁ ከአባቴም ጋር በዙፋኑ ላይ እንደተቀመጥሁ፥ ድል ለነሣው ከእኔ ጋር በዙፋኔ ላይ ይቀመጥ ዘንድ እሰጠዋለሁ።"
(ራእ 3:21)
🔹🔸🔹 አብ በሰማይ ልጄ ብሎ የመሰከረለትን ክርስቶስ ደግሞ በሰማይ ያለ አባቴ ብሎ የአብ የባሕርይ ልጅ መሆኑን ነገረን።
🎤#ማብራሪያ :- የሰው ልጅ ሰው ፣ የእንስሳ ልጅ እንስሳ እንደ ሆነ ሁሉ የእግዚአብሔር ልጅ ደግሞ እግዚአብሔር ነው። ስለዚህም ክርስቶስ የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ መሆኑን መጻሕፍት ስለ ነገሩን ክርስቶስ እግዚአብሔር ነው ማለት ነው።
➢➢ የቀጣይ ትምህርት
ከክፍል ሦስት የቀጠለ ...
የክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት ማሳያዎቹ ምንድን ናቸው?
➜ ሐምሌ / 24 / 2018 ዓ.ም
© ማኅቶት እሸቴ
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
