Mahtot Eshetie / ማኅቶት እሸቴ
Open in Telegram
መንፈሳዊ የቤተክርስቲያን አስተምህሮና ሙሉ የግእዝ ቋንቋ ሥልጠና ትምህርት ማስተማሪያ የቴሌግራም ገጽ። በመደበኛ መርሐ ግብር የግእዝ ቋንቋ ሥልጠናን መከታተል የምትሹ በኮሜንት መስጫው ጻፉልኝ።
Show more4 654
Subscribers
+5624 hours
+1677 days
+17430 days
Posts Archive
የዐርብ ውዳሴ ማርያም ማብራሪያ
#ክፍል_ዘጠኝ
ከቡርክት አንቲ - ትጸርሕ
♦️🔹♦️ቡርክት አንቲ እምአንስት
"ቡርክት አንቲ እም አንስት ወቡሩክ ፍሬ ከርሥኪ ... ፤ ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ። የማኅፀንሽ ፍሬ የተባረከ ነው ያለርኩሰት አምላክን የወለድሽ ድንግል ማርያም ሆይ እውነተኛ ፀሐይ ከአንቺ ወጣልን (ጌታ ተወለደልን) በክንፈ ረድኤቱም አቀረበን። እርሱ ፈጥሮናልና። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹እምቤታችንን ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ ስንላት ፤ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሌለብሽ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን እያማለድሽ የምታሰጭን ነሽ ማለታችን ነው።
እርሷን የተባረክሽ ነን ብለን የማኅፀንሽ ፍሬ ኢየሱስ ክርስቶስም የተባረከ ነው ስንል ፤ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሚያርቅ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን የሚያድል ማለታችን ነው።
🔹🔸🔹 በክንፈ ረድኤቱ አቀረበን ማለት በሥልጣኑ በመለኮቱ ወደ አባቱ አቀረበን በመስቀል በመሰቀሉ ወደ አባቱ አቀረበን በኋላም በሐዋርያት ሥልጣንና ትምህርት ወደ እግዚአብሔር አቀረበን ማለት ነው።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። በጥንተ ተፈጥሮ በሐዲስ ተፈጥሮ ከፈጠረን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ለኪ ለባሕቲትኪ
"ለኪ ለባሕቲትኪ ኦ እግዝእትነ ወላዲተ አምላክ ... ፤ አምላክን የወለድሽ እመቤታችን ሆይ የብርሃን እናት ነሽና አንቺን በክብር በምስጋና እናገንሻለን።
የተባረክሽ አንቺ ከመላእክት ትበልጫለሽ ከደቂቀ አዳምም ትበልጫለሽ ከአሳቦች ሁሉ ትበልጫለሽ ገናንነትሽን መናገር የሚቻለው ማነው አንቺን የሚመስል የለምና። ማርያም ሆይ መላእክት ያገኑሻል ሱራፌልም ያመሰግኑሻል። በኪሩቤልና በሱራፌል ላይ አድሮ የሚኖር ጌታ መጥቶ በማኅፀንሽ አድሮአልና። ሰውን የሚወድ ወደ እርሱ አቀረበን። ክብር ምስጋና ያለው እርሱ የእኛን ሞት ተቀብሎ የእርሱን ሕይወት ለእኛ ሰጠን። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 እመቤታችን ከሰማይ ከምድር ትበልጫለሽ መባሏ ሰማይና ምድረሰ የማይችሉትን ችላዋለችና። ሰው በሆነ ጊዜ በሥጋማ ሰማይና ምድር ችለውት የለምን ቢሉ እሊያ እርስዋን ምክንያት አድርገው ነው። እመቤታችን ግን በባሕርይዋ ነውና።
#አንድም :- ከመላእክት ከደቂቀ አዳም ትበልጫለሽ።
🔹🔸🔹 ክብርሽን ገናትነትሽን መናገር የሚቻለው ማነው ማለት ክብርሽን ገናንነትሽን ዘርዝሮ ወስኖ መናገር የሚቻለው የለም ማለት ነው።
አንቺንም የሚመስል የለም። እመቤታችን ማን ይመስላታል ብቸኛዋ አምላክን በድንግል የፀነሰች ፣ የወለደች ፣ የድንግልና ጡቶቿን አጥብታ ያሳደገች ፤ አምላክን በክንዷ የታቀፈች በጀርባዋ ያዘለች በከንፈሯ የሳመች እሷ ብቻ ናት። አምላክን ልጄ ብላ የምትጠራ እና አምላክ ልጅ ያላት እሷ ብቻ ናት። አምላክ እናቴ የሚላት እሷ ብቻ ናት። ስለዚህም እሷን የሚመስል የለም።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ክብር የክብር ክብር ካለው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ቡርክት አንቲ ማርያም ወቡሩክ ፍሬ ከርሥኪ ... ፤ የደናግል መመኪያቸው አምላክን የወለድሽ ድንግል ማርያም ሆይ የተባረክሽ ነሽ የማኅፀንሽ ፍሬ የተባረከ ነው። ከዓለም በፊት የነበረ እርሱ ሰው ሆንዋልና ከአንቺ የተወለደ ሥጋችንን ነሣ (ተዋሐደ) መንፈስ ቅዱስንም ሰጠን። በቸርነቱ ብዛት መሳዮቹ አደረገን። ጸጋንና ክብርን ከተቀበሉ ብዙ ሴቶች አንቺ ትበልጫለሽ። አምላክን የወለድሽ ማርያም ሆይ ልዑል እግዚአብሔር ያደረብሽ (የከተመብሽ) ረቂቅ ከተማ ነሽ። በኪሩቤል እና በሱራፌል ላይ የሚኖረውን ጌታን በመኻል እጅሽ ይዘሽዋልና። በቸርነቱ ብዛት ሥጋዊ ፍጥረትን ሁሉ የሚመግብ እርሱ ጡትሽን ይዞ ጠባ። ይኸውም ሁሉን የሚያድን አምላካችን ነው። ለዘለዓለሙ ይጠብቀናል። እንሰግድለትና እናመሰግነው ዘንድ እርሱ ፈጥሮናልና። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹እመቤታችን የደናግል መመኪያ መባሏ ፤ ቀድሞ ወንዶች በሴቶች ይመኩባቸው ነበር። እናንተ ከእኛ ተገኝታችኋል እንጂ እኛ ከእናንተ ተገኝተናልን እያሉ። ሔዋን ከአዳም ብትገኝ ጌታችን ከእመቤታችን ተገኝቶ የለምን ብለው የሚመኩባት ሁነዋልና።
"ለወንዶች የሚከፈለው ዕዳ በሴቶች ላይ ነበረ ፤ ያለ እናት ሔዋን ተገኝታ ነበርና ፤ ስለዚህም ድንግል ግን ያለ ወንድ ዘር ክርስቶስን ወለደች ፤ የሔዋንን ብድራት ለአዳም ትከፍለው ዘንድ አዳም ያለ እናት ሔዋንን ስለአስገኘ እንዳይመካ ድንግል ያለ አባት ክርስቶስን ወለደች ድንቅ በሚሆን አንድነት ይህ አንድ የፍጥረት እኩልነት ይታወቅ ዘንድ።" ዮሐ.አፈ ሃይ.አበ 66÷29
#አንድም : ቀድሞ ወንዶች ሴቶችን በእናንተ ምክንያት ከገነት ወጣን እያሉ ርስት አያካፍሏቸውም ነበር። በሔዋን ምክንያት ከገነት ብትወጡ በእመቤታችን ምክንያት ገነት መንግሥተ ሰማያት ገብታችሁ የለምን ብለው የሚመኩባት ሁነዋልና።
#አንድም : በእናንተ ምክንያት ሞት መጣብን እያሉ ይመኩባቸው ነበር። በእመቤታችን ምክንያት ሕይወት ተገኝቷልና።
#አንድም በማቴዎስ ወንጌል ያሉ የአምስቱ ጥበበኞች ደናግላን መመኪያቸው አንቺ ነሽ። እኒያ ዘይት ከመብራት ጋር የያዙ ናቸው ሙሽራው ሲመጣም አብረው ወደ ሠርጉ ቤት ይገባሉ። ዘይቱና መብራቱ ምግባርና ሃይማኖት ነው። ምግባርና ሃይማኖት ያላቸው በኋላ ከእመቤታችን የተወለደው የቤተክርስቲያን ሙሽራዋ ክርስቶስ በሚመጣ ጊዜ በደስታ አብረው የሚገቡ ናቸውና። ይኸውም የሚሆነው በእመቤታችን በነሣው ሥጋ በመዳናችን ነውና መመኪያቸው ናት።
#አንድም : ለደናግለ ሥጋ ለደናግለ ነፍስ የድንግልናቸውን ዋጋ ታሰጣቸዋለችና የደናግል መመኪያቸው አላት።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ስግደት ከሚገባው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ማርያም ድንግል ሙዳይ ዕፍረት
"ማርያም ድንግል ሙዳይ ዕፍረት ነቅዓ ፈልፈለ ማየ ሕይወት ... ፤ ድንግል ማርያም የሽቱ ሙዳይና (መኖሪያ) የሕይወት ውኃ ምንጭ ናት። የማኅፀኗ ፍሬ ሰውን ሁሉ አድኖአልና። ከእኛም እርግማንን አጠፋልን። በመካከላችንም ሆኖ በመስቀሉ አስታረቀን በልዩ ትንሣኤውም ሰውን ዳግመኛ ወደ ገነት መለሰው። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹በልዩ ትንሣኤው ሰውን ዳግመኛ ወደ ገነት መለሰው። ትንሣኤውን ልዩ አለው ፤ ከሞት ከተነሡት ከእነ አልዓዛር ትንሣኤ ሲለይ ነው። ይኸውም
➣ የእነአልዓዛር ትንሣኤ አስነሽ ይሻል። እርሱ ግን የተነሣ በገዛ ሥልጣኑ ነውና።
"በእራሴ ሥልጣን ተነሣው" እንዳለ ቄር ሃይ.አበ 73÷14
የቡዩ በቤተልሔም ሲያል ምድረ በዳ ሁኖ ታሪኳ ጠፍቶ ይመለከታል እንዲህ እንደሆንሽ አትቀሪም ንጉሥ ይነግሥብሻል ፣ የነጋሪት ድምፅ ይሰማብሻል ፣ ድንኳን ይተከልብሻል ፣ እስራኤል ደጅ ይጠኑብሻል ፣ አሕዛብ ይገብሩብሻል በማለት ትንቢት ተናገረ።
ይኸውም አልቀረ ዘሩባቤል ነግሦባታል ፣ የነጋሪት ድምፅ ተሰምቶባታል ፣ ድንኳን ተተክሎባታል ፣ እስራኤል ደጅ ጠንተውባታል ፣ አሕዛብ ገብረውባታል።
#አንድም : የትንቢቱ ፍጻሜ በሆነ ጊዜ በቤተልሔም ጌታ በመወለዱ ይህ ሆነ። ዘሩባቤል እንደ ነገሠባት ጌታ ተወልዶባታል። የነጋሪት ድምፅ እንደ ተሰማባት የመላእክት ቅዳሴ ተሰምቶባታል። ድንኳን እንደ ተተከለባት የብርሃን ድንኳን ተተክሎባታል። እስራኤል ደጅ እንደጸኑባት መቶው ነገደ መላእክት ደጅ ጸንተውባታል። አሕዛብ እንደ ገበሩባት ሰብአ ሰገል ወርቅ ዕጣን ከርቤን ገብረውባታልና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ክብር ምስጋና ከሚገባው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ዳዊት ዘነግሠ ለእስራኤል
"ዳዊት ዘነግሠ ለእስራኤል ... ፤ ለእስራኤል የነገሠ ዳዊት ጠላቶቹ በተነሡበት ጊዜ ከቤተልሔም ምንጭ ውኃ ይጠጣ ዘንድ ወደደ የጭፍሮቹ አለቆች ፈጥነው ተነሡና በጣላቶች ከተማ ተዋግተው ሊጠጣ የወደደውን አመጡለት። ጻድቅ ዳዊት ግን ጨክነው ሰውነታቸውን ስለ እርሱ ለጦርነት ለሞት አሳልፈው እንደሰጡ ባየ ጊዜ ያን ውኃ አፈሰሰ ከእርሱም አልጠጣም ከዚህ በኋላ ለዘለዓለም ጽድቅ ሆኖ ተቆጠረለት ሰማዕታት የዚችን ዓለም ጣዕም በእውነት ናቁ ደማቸውንም ስለ እግዚአብሔር አፈሰሱ ስለ መንግሥተ ሰማያትም መራራ ሞትን ታገሡ እንደ ይቅርታህ ብዛት ይቅር በለን። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 ዳዊት ለበጎ የነገሠ ነውና ለእስራኤል የነገሠ ይባላል ለክፉ ቢሆን በእስራኤል የነገሠ ባለ ነበር።
ንጉሥ ዳዊት ታሞ ሳለ ካደገባት ከቤተልሔም ምንጭ ውኃ ማን ባመጣልኝ አለ። የጦር አዛዦቹ አዲኖን ኢያቡስቴ ኤልያና አፋቸውን ታጥቀው ፣ ዘገራቸውን ነጥቀው ፣ ረዋታቸውን ጭነው ሊያመጡለት ተነሡ። ዜና መዋዕል እንደሚነግረን
"ዳዊትም በበሩ አጠገብ ካለችው ከቤተ ልሔም ምንጭ ውሃ ማን ይሰጠኛል? ብሎ ተመኘ።
እነዚህም ሦስቱ የፍልስጥኤማውያንን ሠራዊት ቀድደው ሄዱ፥ በበሩም አጠገብ ካለችው ከቤተ ልሔም ምንጭ ውሃ ቀዱ፤ ይዘውም ለዳዊት አመጡለት። እርሱ ግን ሊጠጣ አልወደደም፥ ነገር ግን ለእግዚአብሔር አፍስሶ። ይህን አደርግ ዘንድ አምላኬ ይከልክለኝ፤ በነፍሳቸው የደፈሩትም እነዚህ ሰዎች ደም እጠጣለሁን? በነፍሳቸው አምጥተውታል አለ። ስለዚህም ይጠጣ ዘንድ አልወደደም። ሦስቱም ኃያላን ያደረጉት ይህ ነው።"
1ኛ ዜና 11 ÷ 17-19
ዳዊት ያመጡለትን ውኃ አልጠጣም ማለቱ የእናንተን ደም መጠጣት አይደለምን የእኔ ብላችሁ የጠላትን ጦር ሰጥቃችሁ ደፍራችሁ ያመጣችሁልኝ ጠላት ቢያጠቃችሁ ስለ እኔ ደማችሁን ማፍሰሳችሁ አይደለምን ይህንን ውኃስ መጠጣቴ የእናንተን ደም እንደመጠጣት ነው ብሎ ስለ እግዚአብሔር ብሎ አፈሰሰው። ይህም ጽድቅ ሁኖ ተቆጠረለት።
ይኸውም የዳዊት ውኃ ማፍሰስ እና የጦር አበጋዞቹ ስለ ዳዊት ደማችንን እናፍስስ ማለት በክርስቶስ ስም ደማቸውን የሚያፈሱ የሰማዕታት ምሳሌ ነው።
🔹🔸🔹 በንጽጽር ስናየው
💥የዳዊት የጦር አበጋዞች የዓለምን ጣዕም ስለ ዳዊት እንደናቁ ፣ ዳዊት ስለ ጦር አበጋዞቹ የውኃ ጥምን እንደናቀ ሰማዕታት ስለ ክርስቶስ የዓለምን ጣዕም ናቁ።
💥የዳዊት የጦር አበጋዞች ስለ ዳዊት ብለው ደማችንን እናፍስስ እንዳሉ ፣ ዳዊት ስለ ጦር አበጋዞቹ ፍቅር ውኃውን እንዳፈሰሰ ፣ ሰማዕታትም ስለ እግዚአብሔር ብለው ደማቸውን አፈሰሱ።
💥 የዳዊት የጦር አበጋዞች ስለ ዳዊት መራራ ሞትን እንደታገሡ ፣ ዳዊት ስለ ጦር አቀጋዞቹ ጽምዓ ማይን (የውኃ መጠማትን) እንደታገሠ ፣ ሰማዕታትም ስለ መንግሥተ ሰማያት መራራ ሞትን ታገሱ።
➣የሞት ጣፋጭ ኑሮት ሳይሆን መራራ ሞት ያለው ፤ በሰው ሀገር ሆኖ አባት እናት እኅት ወንድም ዘመድ ጠያቂ አጥቶ የሞተውን ሞት መራራ ሞት ይለዋልና ስለዚህ ነው።
🔹🔸🔹እንደ ቸርነትህ ብዛት ይቅር በለን። ሊቁ ይህንን ማለቱ እንዲህ ሲል ነው።
እኛስ እንደ ሰማዕታት ከዓላውያን ነገሥታት ከዓላውያን መኳንንት ገብተን መከራውን ታግሠን ተቀብለን ፤ እንደ ምእመናን ከፍትወታት (ከክፉ ምኞት) ፣ ከኃጢአት ጋር ተዋግተን ድል ነሥተን መዳን አይቻለንምና እንደ ቸርነትህ እንደ ምሕረትህ ብዛት ይቅር በለን።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። እንዲህ ካለው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ አሐዱ ዘእም ቅድስት ሥላሴ
"አሐዱ ዘእም ቅድስት ሥላሴ ... ፤ ከቅድስት ሥላሴ አንዱ ወልድ መዋረዳችንን አይቶ ከሰማየ ሰማያት ወረደና ባሕርዩን ዝቅ አደረገና መጥቶ በድንግል ማኅፀን አደረ ከብቻዋ ከኃጢአት በቀርም እንደኛ ሰው ሆነ ነቢያት ትንቢት እንደተናገሩለት በቤተልሔም ተወለደ ፈጽሞ ወገኖቹም አደረገን። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹"ከቅድስት ሥላሴ አንዱ ወልድ መዋረዳችንን አይቶ ከሰማየ ሰማያት ወረደና ባሕርዩን ዝቅ አደረገና መጥቶ በድንግል ማኅፀን አደረ" መዋረዳችን የተባለው በእግረ አጋንንት መረገጣችንን በመንጸፈ ደይን በሲዖል መውደቃችንሰ አይቶ ፤ የመላእክትን ባሕርይ ባሕርይ ሳያደርግ የእኛን ባሕርይ ባሕርይ አድርጎ ሰው ሆኖ አዳነን ሲል ነው።
"የአብርሃምን ዘር ይዞአል እንጂ የያዘው የመላእክትን አይደለም።" (ዕብ 2:16)
🔹🔸🔹ክርስቶስ ሰው ሆኖ እንደኛ የሰውነትን ሥራ ቢሠራም ቅሉ ሰዎች ሰው እንደመሆናችን የምንሠራውን ማናቸውም ኃጢአት አልሠራም።
➣ሰው ሆኖም አዳነን ቤዛም ሆነን።
አዳነን ስንል እንደ አምላክነቱ ፣ ቤዛ ሆነን ስንል እንደ ሰውነቱ ነው።
"አምላክ በመሆኑ ያድነን ዘንድ ፤ ሰው በመሆኑም ለእኛ ቤዛ ሆኖ ይሞትልን ዘንድ ፤ እግዚአብሔር ቃል ሰው ሆነ።" ኤጲ.ሃይ.አበ 58÷50
➣ወገኖቹ አደረገን ሲል ፤ በመበደላችን ምክንያት ከእግዚአብሔር ርቀን ከልጅነቱ ተፍቀን ነበርና እግዚአብሔር ቃል ሰው ሆኖ ወደ እግዚአብሔር አቀረበን ልጅነትንም አደለን።
#አንድም ቀድሞ በረድኤት ነው የእግዚአብሔር ወገኖች የምንባል የነበረ ዛሬ ግን በመሆን ነውና። ይህም ሲባል ሥጋችንን ገንዘቡ አድርጎ ወገኖቹ አደረገን ስንል ነው።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ወገኖቹ ካደረገን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
➢➢ የቀጣይ ትምህርት
#ክፍል_ዘጠኝ
የዐርብ ውዳሴ ማርያም
➜ ነሐሴ / 8 / 2018 ዓ.ም
©መ/ር ማኅቶት እሸቴ
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
የኀሙስ ውዳሴ ማርያም ማብራሪያ
#ክፍል_ስምንት
ኦ ዝ መንክር ነሥአ - አሐዱ
♦️🔹♦️ ኦ ዝ መንክር ነሥአ
"ኦ ዝ መንክር ነሥአ ... ፤ ከአዳም ጎን አንዲት ዐፅም መንሣቱ ምን ይደንቅ? ከእርሱ ሴትን ፈጠረ የሰው ፍጥረትንም ሁሉ ፈጠረ። ጌታ የአብ ቃል ተሰጠ። ከልዩ ድንግልም ሰው ሆነና አማኑኤል ተባለ ስለዚህ ሁል ጊዜ እርስዋን እንለምን። ከተወደደ ልጅዋ ታማልደን ዘንድ። በቅዱሳንና በሊቃነ ጳጳሳት ዘንድ ቸር ናት ደጅ የሚጠኑትን ወልዳላቸዋለችና። ለነቢያትም ትንቢት የተናገሩለትን ወልዳላቸዋለችና። ለሐዋርያትም እስከ ዓለም ዳርቻ በስሙ ያስተማሩለትን ወልዳላቸዋለችና። ሰማዕታትና ምእመናንም የተጋደሉለት የጥበቡ ጸጋ ብዛት የማይታወቅ ኢየሱስ ክርስቶስ ከእርስዋ ተወልዷልና። የይቅርታውን ብዛት መርምረን እንወቅ መጥቶ አድኖናልና። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም አስቀድሞ እግዚአብሔር ከአዳም አጥንት ሔዋንን ማስገኘቱን አድንቆ ይናገራል። ከዚህ በፊት በነበረው ምስጋና እመቤታችን ያለ ወንድ ዘር ጌታን መውለዷን አድንቆ እንደተናገረ ሁሉ ከዚህም ላይ የሔዋንን መገኘት አድንቆ ይናገራል። ይኽም ሁለቱን ሲያነጻጽር ነው። ሁሉም በፍጡር የማይቻል ሊቻል ይቅርና ታስቦ ለመርምሮ የማይደረስበት በመሆኑ ነው።
ይህንንም ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንደዚህ ይገልጸዋል።
"ለወንዶች የሚከፈለው ዕዳ በሴቶች ላይ ነበረ ፤ ያለ እናት ሔዋን ተገኝታ ነበርና ፤ ስለዚህም ድንግል ግን ያለ ወንድ ዘር ክርስቶስን ወለደች ፤ የሔዋንን ብድራት ለአዳም ትከፍለው ዘንድ አዳም ያለ እናት ሔዋንን ስለአስገኘ እንዳይመካ ድንግል ያለ አባት ክርስቶስን ወለደች ድንቅ በሚሆን አንድነት ይህ አንድ የፍጥረት እኩልነት ይታወቅ ዘንድ።" ሃይ.አበ 66÷29
🔹🔸🔹ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም ከእመቤታችን ዘንድ እንለምን በቅዱሳን ዘንድ ቸር ናትና። የእመቤታችን ቸርነቷ በኃጢአተኞች ብቻ ሳይሆን በቅዱሳንም ዘንድ ነው። ይኸውም ሊቃነ ጳጳሳት አስበ ጵጵስናችንን ይሰጠናል ብለው ፣ ነቢያት የትንቢታችንን ዋጋ ይሰጠናል ብለው ፣ ሐዋርያት የስብከታችንን ዋጋ ይሰጠናል ብለው ፣ ሰማዕታት የሰማዕትነታችንን ዋጋ ይሰጠናል ብለው ከዓላውያን ነገሥታት ከዓላውያን መኳንንት ፊት ገብተው መከራውን ታግሰው የተቀበሉለትን ፣ ምእመናን የተጋድሏችንን ዋጋ ይሰጠናል ብለው ከክፉ ምኞት ከኃጢአት ተጠብቀው የተዋጉለትን ጌታን ወልዳላቸዋለችና።
#አንድም : ሰማዕታት የሰማዕትነታችንን ዋጋ ይሰጠናል ብለው ከዓላውያን ነገሥታት ከዓላውያን መኳንንት ፊት ገብተው መከራውን ታግሰው የተቀበሉለት ፣ ምእመናን የተጋድሏችንን ዋጋ ይሰጠናል ብለው ከክፉ ምኞት ከኃጢአት ተጠብቀው የተዋጉለት ጌታ ከእርሷ ተወለደ።
🔹🔸🔹ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን የጥበቡ ጸጋ ብዛት የማይታወቅ ማለቱ : የባሕር ክብሩ የማይታወቅ ሲል ነው የባሕርይ ክብሩን ለሰው በጸጋ ስለሚሰጠው ጸጋ አለው።
#አንድም : ብዑለ ጸጋ በተዋሕዶ የከበረ ማለት ነው። ይህም ሲባል የባሕርይ አምላክ ሰው በሆነ ጊዜ ሰውነቱን አክብሮ በተዋሕዶ የባሕርይ አምላክ አደረገው እንጂ ከባሕርይ ክብሩ አልጎደለበትም ማለት ነው።
#አንድም : የጥበቡ ጸጋ ብዛት የማይታወቅ ማለቱ በለጋስነት የከበረ ማለት ነው። ይኸውም ሰው ቢለግስ በእልፍኙ የተዘጋጀውን አቅርቦ ብሉልኝ ጠጡልኝ ይላል እንጂ እኔን ብሉኝ ጠጡኝ አይልምና። እርሱ ግን በዝናብ አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ ፍጥረቱን ያለ አድሎ ከመመገቡም በላይ ሥጋየን ብሉ ደሜን ጠጡ ብሎ ራሱን የሕይወት እንጀራ አድርጎ ሰጥቶናልና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ሰው ሁኖ ከአዳነን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ መሐለ እግዚአብሔር ለዳዊት
"መሐለ እግዚአብሔር ለዳዊት ... ፤ እግዚአብሔር የባሕርይህን ፍሬ በዙፋንህ ላይ አኖራለሁ ብሎ ለዳዊት በእውነት ማለ አይጸጸትም። ጻድቅ እርሱ (ዳዊት) ክርስቶስ በሥጋ ከእርሱ እንዲወለድ ባመነ ጊዜ የእግዚአብሔርን ቃል ማደር ፈልጎ ያገኝ ዘንድ ወደደ ይህንንም በታላቅ ትጋት ፈጸመ። ከዚህ በኋላ እነሆ በኤፍራታ ሰማነው ብሎ በመንፈስ ቅዱስ ጮኸ ይህችውም አማኑኤል እኛን ለማዳን በሥጋ ይወለድባት ዘንድ የመረጣት የያዕቆብ አምላክ ማደሪያ ናት። ዳግመኛም ከነቢያት አንዱ ሚክያስ አንቺ ቤተልሔም ከይሁዳ ነገሥታት ሀገር አታንሽም ወገኖቼ እስራኤልን የሚጠብቃቸው ንጉሥ ካንቺ ይወጣልና ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘለዓለም ድአስ ከቸር አባቱና ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ ምስጋና ስለተገባው ስለ ክርስቶስ ባንድ መንፈስ ቅዱስ ትንቢት የተናገሩ የነዚህ የሚክያስና የዳዊት ነገር ምን ይረቅ። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 እግዚአብሔር ማለ መባሉ ሰው ስመ እግዚአብሔር ጠርቶ ወይም የሚወደውን ስም ጠርቶ እንዲመለው አይደለም ፤ የማለ ሰው የነገሩን ጥብቅነት እና ተፈጻሚነት እንዲያሳይና እንዲያረጋግጥ ፤ በእግዚአብሔር ዘንድ ነገሩ ጥብቅና ተፈጻሚ መሆኑን ቃል ለተገባለት ሰው ተማስገንዘብ ነው እንጂ።
" እግዚአብሔር ለዳዊት በእውነት ማለ አይጸጸትምም፥ እንዲህ ብሎ። ከሆድህ ፍሬ በዙፋንህ ላይ አስቀምጣለሁ።" (መዝ 131:11)
ከሆድህ ፍሬ በዙፋንህ አስቀምጥልሃለው የተባለ ለጊዜው ሰሎሞንን በራሱ በዳዊት ዙፋን እንደሚያስቀምጥለት ከእርሱ ቀጥሎ የሚነግሥ ልጁ መሆኑን መናገሩ ሲሆን ፍጻሜው ግን አድያ ልጄ ከዘርህ ተወልዶ በአንተ ስም ወልደ ዳዊት (የዳዊት ልጅ) ተብሎ ይጠራል ፤ አንተ በነገሥክባቸው እስራኤል ዘሥጋ እስራኤል ዘነፍስ አድርጎ ይነግስባቸዋል ሲለው ነው።
ይህንንም አስቀድሞ ልዑለ ቃል ኢሳያስ በትንቢቱ
"ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል።
ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም ድረስ በፍርድና በጽድቅ ያጸናውና ይደግፈው ዘንድ በዳዊት ዙፋንና በመንግሥቱ ላይ አለቅነቱ ይበዛል፥ ለሰላሙም ፍፃሜ የለውም። የእግዚአብሔር ቅንዓት ይህን ያደርጋል።" ኢሳ ።9÷6-7 እንደተናገረ።
🔹🔸🔹ክርስቶስ በቤተልሔም እንደሚወለድ ከተናገሩት መካከል ንጉሥ ዳዊትና ነቢዩ ሚክያስ ናቸው።
ዳዊት ስለ ቤተመቅደሱ መሠራት እግዚአብሔርን በቀኖና በጠየቀ ጊዜ የበለጠ ምሥጢር የክርስቶስ ሰው መሆን ተገልጾለት "እነሆ፥ በኤፍራታ ሰማነው፥ በዱር ውስጥም አገኘነው።"
(መዝ 131:6) በማለት በቤተልሔም በበረት መወለዱን አስቀድሞ ተናገረ።
ሚክያስም " አንቺም ቤተ ልሔም ኤፍራታ ሆይ፥ አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ፤ ከአንቺ ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘላለም የሆነ፥ በእስራኤልም ላይ ገዥ የሚሆን ይወጣልኛል። " (ሚክ 5:2) በማለት በቤተልሔም መወለዱን ተናገረ።
ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም ቤተልሔምን "አንቺ ቤተልሔም ከይሁዳ ነገሥታት ሀገር አታንሽም ወገኖቼ እስራኤልን የሚጠብቃቸው ንጉሥ ካንቺ ይወጣልና" በማለት የነቢዩን ቃል ወስዶ የማመስገኑም ምሥጢር እንዲህ ነው ፤
#አንድም :-
💥ወርቅ ጽሩይ ነው። በአንተ ያመኑ ምእመናን ጽሩያነ ምግባር ወሃይማኖት ናቸው ሲሉ።
💥ዕጣን ምዑዝ ነው። በአንተ ያመኑ ምእመናን ምዑዛነ ምግባር ወሃይማኖት ናቸው ሲሉ።
💥ከርቤ በዕለተ ሞቱ ለጌታ ያቀምሱታልና።
#አንድም :-
💥ወርቅ የሃይማኖት ምሳሌ ፤ የወርቅ ግብዝነቱ ጽሩይነቱ የሚታወቀው በእሳት ነው። የሃይማኖትም ጽሩይና ግብዝነቱ የሚታወቀው በመከራ ነው።
💥ዕጣን የተስፋ ምሳሌ ፤ ዕጣን ከሩቅ እንዲሸት ተስፋም ያላዩትን እንዳዩት ያልያዙትን እንደያዙት ታደርጋለችና።
💥ከርቤ የፍቅር ምሳሌ ፤ ከርቤ አንድ እንዲያደርግ ፍቅርም አንድ ታደርጋለችና።
ስለዚህም ሃይማኖት ፍቅር ተስፋ ገንዘቦችህ ናቸው ሲሉ ወርቅ ዕጣን ከርቤ አመጡለት።
#አንድም :-
💥ወርቅ የሰማዕታት ምሳሌ። "እንደ ወርቅ ሰማዕታትን በእሳት ፈተናቸው" እንዳለ አረ.መን 33
💥ዕጣን የባሕታውያን ምሳሌ ፤ ዕጣን ከሩቅ እንዲሸት ባሕታውያንም በተስፋ ነዋሪዎች ናቸውና።
💥ከርቤ የምእመናን ምሳሌ ፤ ከርቤ አንድ እንድያደርግ ምእመናንም በፍቅር በአንድነት ይኖራሉና።
ሰማዕታት ባሕታውያን ምእመናን ገንዘቦችህ ናቸው ሲሉ ወርቅ ዕጣን ከርቤ አመጡለት።
#አንድም
💥ወርቅ የመላእክት ምሳሌ
💥ዕጣን የደቂቀ አዳም ምሳሌ
💥ከርቤ የካልዕ ፍጥረት ምሳሌ። ካልዕ ፍጥረታትን እግዚአብሔር ብቻ ነው የሚያውቃቸው። ሐዋርያው ስለ እነርሱ መኖር ተናግሯል። " ይህም በሰማይና በምድር ከምድርም በታች ያሉት ሁሉ በኢየሱስ ስም ይንበረከኩ ዘንድ፥" (ፊል 2:10)
ስለዚህም መላእክት ፣ ደቂቀ አዳም ፣ ካልዕ ፍጥረት ገንዘቦችህ ናቸው ሲሉ ፤ ወርቅ ዕጣን ከርቤ አመጡለት።
🔹🔸🔹ሰአሊ ለነ ቅድስት። ኃዳሪም ማኅደርም ካይደለ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
➢➢ የቀጣይ ትምህርት
#ክፍል_ስምንት
የኀሙስ ውዳሴ ማርያም
ከኦ ዝ መንክር ነሥአ - አሐዱ
➜ ነሐሴ / 7 / 2018 ዓ.ም
©መ/ር ማኅቶት እሸቴ
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
የኀሙስ ውዳሴ ማርያም ማብራሪያ
#ክፍል_ሰባት
ከዕፀ እንተ ርእየ - ኦ ዝ መንክር ወዕፁብ
♦️🔹♦️ ዕፀ እንተ ርእየ ሙሴ
"ዕፀ እንተ ርእየ ሙሴ በነደ እሳት ... ፤ ርኵሰት የሌለባት ድንግል ማርያም ሙሴ በበረሃ በነደ እሳት ጫፎቿ ሳይቃጠሉ ያያት ዕፅን ትመስላለች። የአብ ቃል በእርሷ ሰው ሆኗልና እሳተ መለኮቱ (የመለኮቱ ባሕርይ) አላቃጠላትምና። ከወለደችውም በኋላ ድንግልናዋ አልተለወጠምና። ሰውም ሲሆን መለኮቱ አልተለወጠም። በእውነት አምላክ ነውና በእውነት አምላክ የሆነ እርሱ መጥቶ አዳነን። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 ነቢየ እግዚአብሔር ሙሴ በሲና ያያት ዕፀ ጳጦስ የእመቤታችን ምሳሌ ናት ያቺን እሳቱ እንዳላቃጠላት ሁሉ እመቤታችንም ጌታን በፀነሰች ጊዜ የመለኮት እሳት አላቃጠላትምና።
እመቤታችን ጌታን ስትፀንሰው ማኅተመ ድንግልናዋ እንዳልተለወጠ ሁሉ ጌታም ሰው ሲሆን ባሕርየ መለኮቱ አልተለወጠምና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ሰው ሁኖ ከአዳነን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ናዐብየኪ ኵልነ
"ናዐብየኢ ኦ እግዝእትነ ወላዲተ አምላክ ... ፤ አምላክን የወለድሽ እመቤታችን ሆይ ሁላችን እናገንሻለን። ይቅርታሽ ለሁላችን ይሆን ዘንድ ነውና። ሔዋን ዕፀ በለስን በልታ ባደረገችው ዓመፅ በባሕርያችን ያደረ የቀድሞው እርግማን በእርስዋ የጠፋልን አምላክን የወለደች ድንግል ማርያም የሁላችን መመኪያ ናት። ስለ ሔዋን የገነት ደጅ ተዘጋ ዳግመኛም ስለ ድንግል ማርያም ተከፈተልን። ከዕፀ ሕይወት እንበላ ዘንድ አደለን። ይኸውም እኛን ስለመውደድ መጥቶ ያዳነን የክርስቶስ ክቡር ሥጋው ክቡር ደሙ ነው። ስለ እርሷ ድንቅ ሆኖ የሚነገረውን ይህን ምስጢር ማወቅ የሚቻለው ምን ልቡና ነው? መናገር የሚቻለው ምን አንደበት ነው? መስማት የሚቻለው ምን ጀሮ? ሰውን የሚወድ እግዚአብሔር አንድ ብቻ የሆነ አምላክነቱ ሳይለወጥ ከዓለም በፊት የነበረ የአብ ቃል ከአብ ዘንድ መጥቶ ልዩ ከሆነች እናቱ ሰው ሆነ። ከወለደችውም በኋላ ድንግልናዋ አልተለወጠም። ስለዚህ አምላክን የወለደች እንደሆነች ታወቀች። የእግዚአብሔር የጥበቡ ስፋት ምን ይጠልቅ? በጻእር በምጥ በልብ ጋር ትውልድ ዘንድ የፈረደባት ማኅፀን የሕይወት መገኛ ሆነች ከባሕርያችን እርግማንን የሚያጠፋልንን ያለ ወንድ ዘር ወለደችልን። ስለዚህም ሰውን የምትወድ ሆይ ክብር ለአንተ ይገባል ቸርና የሰውነታችን መድኃኒት ነህ እያልን እናመስግነው። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 ድንግል ማርያም የሁላችንም መመኪያ ትባላለች። "የሚመካ በእግዚአብሔር ይመካ" እንደ ተባለ መመኪያችን እግዚአብሔርን ወልዳልናለችና። በባሕርያችን ጸንቶ የነበረ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ በእርሷ ምክንያት ጠፍቶልናልና።
ዳግመኛም በሔዋን ምክንያት የተዘጋው ገነት በድንግል ማርያም ምክንያት ተከፈተልን። አዳምና ሔዋን በገነት ያልበሉትን ዕፀ ሕይወት ጌታ ከእመቤታችን ሰው በመሆኑ እኛ ልጆቻቸው በላነው ይኸውም ቅዱስ ሥጋው ክቡር ደሙ ነው።
🔹🔸🔹 የሔዋን ማኅፀን የሞት ምክንያት የግድያ አባት የሆነ ቃየልን አስገኘ የድንግል ማርያም ማኅፀን ግን የሕይወት መገኛ ፣ ሞትን በሞቱ የገደለው ክርስቶስን አስገኘልን።
"የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ባለመስማት እባብ መርዙን የጣለበት ዲያብሎስ ፍዳ መርገም ያሳደረበት ማኅፀን ፤ አካላዊ ቃል ውረድ ተወለድ ያለውን በመስማት አዳነ። ቀድሞ የኃጢአት ምክንያት ቃየል ከዚያች ማኅፀን ተገኝቶ ነበር። ዛሬ ግን እንበለ ዘር የተገኘ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከዚች ማኅፀን ተወለደ።" እንዳለ ቄርሎስ ተረ.ቄር 18÷11
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ቸርና የሰውነታችን መድኃኒት ከሆነ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ኦ ዝ መንክር ወዕፁብ
"ኦ ዝ መንክር ወዕፁብ ኃይለ ከርሣ ... ፤ ያለ ወንድ ዘር አምላክን የወለደች ድንግል የማኅፀንዋ ሥራ ምን ይደንቅ። ለዮሴፍ የታየው መልአኩ ከእርሷ በመንፈስ ቅዱስ የሚወለደው ያለ መለወጥ ሰው የሚሆነው የእግዚአብሔር ቃል ነው ብሎ መስክሯልና። ማርያም የደስታዋ ዕጥፍ ድርብ የሆነ እርሱን ወለደችው። መልአኩ ልጅ ትወልጃለሽ ስሙም አማኑኤል ይባላልና አላት። ትርጓሜውም እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ሆነ ማለት ነው። ዳግመኛ ወገኖቹን ከኃጢአታቸው የሚያድናቸው ኢየሱስ ይባላል። በችሎታው (በኃይሉ) ያድነን ዘንድ ኃጢአታችንንም ያስሠርይልን ዘንድ ለዘለዓለም ክብር ይግባውና ሰው የሆነ እርሱን አምላክ እንደሆነ በረዳ ነገር አውቀነዋልና። ልዩ ከሆነች ድንግል ማርያም ይህ የአምላክ መወለድ ምን ይደንቅ ቃልን ወሰነችው። ልደቱንም ዘር አልቀደመውም። በመወለዱም ድንግልናዋን አለወጠውም። ቃል ከአብ ያለ ድካም ወጣ። ከድንግልም ያለ ሕማም ተወለደ። ሰብአ ሰገል ሰገዱለት አምላክ ነውና ዕጣን አመጡለት። ንጉሥም ነውና ወርቅ አመጡለት። ስለእኛ በፈቃዱ ለተቀበለው መዳኛችን ለሆነ ሞቱም ከርቤ አመጡለት። ቸርና ሰውን ወዳጅ የሆነ አንድ እርሱ ብቻ ነው። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 እመቤታችን ጌታችንን እንበለ ዘር በድንግልና እንደ ፀነሰችው ሲጨነቅ ለነበረው አረጋዊ ዮሴፍ በህልም እንዲህ አለው " እርሱ ግን ይህን ሲያስብ፥ እነሆ የጌታ መልአክ በሕልም ታየው፥ እንዲህም አለ። የዳዊት ልጅ ዮሴፍ ሆይ፥ ከእርስዋ የተፀነሰው ከመንፈስ ቅዱስ ነውና እጮኛህን ማርያምን ለመውሰድ አትፍራ።"
(ማቴ 1:20)
🔹🔸🔹እመቤታችን የደስታዋን ዕፅፍ ድርብ ወለደችው ሲባል ፤ ሴቶች ልጅ ትወልዳላችሁ ሲሏቸው ደስ ይላቸዋል። ይልቁንም ወንድ ትወልዳላችሁ ሲሏቸው ደስ ይላቸዋልና ከዚያውም አምላክ መሆኑ ደስ ያሰኛልና።
#አንድም : የኢሳይያስን ትንቢት ስታነብ "ድንግል በድንግልና ፀንሳ በድንግልና አምላክን ትወልዳለች" ከሚለው በደረሰች ጊዜ ከዚች እሴት ከዘመኗ ደርሼ ወጥቼ ወርጄ አገልግያት ብላ ነበርና ከዘመኑ መድረስ ደስ ያሰኛልና ይልቁንም እሷ መሆኗ ደስ ያሰኛልና።
🔹🔸🔹 ሰብአ ሰገል ጌታ በተወለደ ጊዜ ያመጡለት ወርቅ ፣ ዕጣንና ከርቤ ምሳሌነት አላቸው።
💥ወርቅ ማጣታቸው ይህን እንገብርላቸው የነበሩ ነገሥታት ቀድሞም ፍጡራን ኋላም ኃላፍያን ናቸው። አንተ ግን ቀድሞውንም ያልተፈጠርክ ኋላም የማታልፍ ነህ ሲሉ።
💥ዕጣን ማምጣታቸው ፡ ይህን እናጥናቸው የነበሩ ጣዖታት ቀድሞውን ፍጡራን ኋላም ኃላፍያን ናቸው። አንተ ግን ቀድሞውንም ያልተፈጠርክ ኋላም የማታልፍ ነህ ሲሉ።
💥ከርቤ ማምጣታቸው ፡ ምንም እንኳ ቀድሞውንም ያልተፈጠርክ ኋላም የማታልፍ ብትሆን በሰውነትህ መራራ ሞትን ትቀበላለህ ሲሉ።
#አንድም
💥ወርቅ ጽሩይ ነው። አንተም ጽሩየ ባሕርይ ነህ ሲሉ።
💥ዕጣን ምዑዝ ነው። አንተም ምዑዘ ባሕርይ ነህ ሲሉ።
💥ከርቤ የተሰበረውን ይጠግናል ፣ የተለያየውን አንድ ያደርጋል። አንተም ከማኅበረ መላእክት የተለየ አዳምን አንድ ታደርገዋለህ ጽንዓ ነፍስን ሰጥተህ ታጸናዋለህ ሲሉ።
አቶ ፌስቡክ በተከታታይ የምለቃቸውን ትምህርቶች ተደራሽነታቸውን እየገደባቸው ነው።
የተከበራችሁ የቴሌግራም ቤተሰቦቼ በፌስቡክ ቤተሰብ ያልሆናችሁ #follow_Like_share
በማድረግ ተደራሽነቱን እንዲታሰፉልኝ በትሕትና እጠይቃለሁ።
በፌስቡክ የተለቀቀው የዕለቱ ትምህርት
👇👇👇👇
https://www.facebook.com/100012388235278/posts/pfbid027r96X51qp8dWMDPZdqY2cx41KqHyUBBFQ4njxfyuQ1fvr34E7yMFtwEAw6AJLFgFl/
መደበኛ የፌስቡክ አድራሻ
👇👇👇👇
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 እመቤታችን ንጹሕ የሽቱ ሙዳይ ትባላለች። የሽቱን እቃ ጢስ እንዳይተንበት ትቢያ እንዳይበንበት ቤት ሰፍተው ሰቅለው ተንከባክበው ያኖሩታል። እርሷንም መንፈስ ቅዱስ ከእናቷ ማኅፀን ጀምሮ ጠበቃት ይላታልና።
#አንድም : በየጊዜው የጸጋ ክብር ይጨመርላታልና።
#አንደም : የሽቱ እቃ ሽቱው በውስጡ ሳለ ሽቱው ከወጣ በኋላ መዓዛው እንዳይለየው። እርሷም ጌታን ፀንሳ ሳለች ተአምራት ታደርግ ነበርና። ጌታንም ከወለደችው በኋላ መዓዛ መለኮቱ አልተለያትምና።
#አንድም : በሽቱ እቃ አራቱን ሽቱ አምስተኛ ዘይት አጣፍጠው ቀኝ ቀኝ አካላቸውን በመቀባት ከቤተ ይሁዳ የተወለደውን መንግሥትን ከቤተ ሌዊ የተወለደውን ክህነትን እንዲሾሙበት ፤ ጌታም ከእመቤታችን አራቱን ባሕርያተ ሥጋ አምስተኛ ባሕርየ ነፍስን ነሥቶ ክህነትን መንግሥትን ገንዘብ አድርጓልና።
🔹🔸🔹በክብር ጌጥ ሁሉ ያጌጠ እርሱ መጥቶ ሰው የሆነብሽ ንጽሕት የሠርግ ቤት ሆይ ደስ ይበልሽ። ማለቱ : የሠርግን ቤት አስቀድመው በሐር ያንቆጠቁጡታል ፣ ያነጥፉታል ፣ ይጎዘጉዙታል ፣ ሽቱ ያረበርቡበታል ፣ ሐረግ ወርድ ይስሉበታል። እንደዚሁም ሁሉ እመቤታችን መንፈስ ቅዱስ ከእናቷ ማኅፀን ጀምሮ ጠበቃት ይላታልና ፤ በየ ጊዜው የጸጋ ክብር ይጨመርላታልና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። አንቺን ለእናትነት ከመረጠ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ የዐቢ ክብራ ለማርያም
"የዐቢ ክብራ ለማርያም እም ኵሎሙ ቅዱሳን ... ፤ ከቅዱሳን ክብር የማርያም ክብር ይበልጣል የአብን ቃል ለመቀበል በተገባ ተገኝታለችና። መላእክት የሚፈሩትን ትጉሆች በሰማያት የሚያመሰግኑትን ድንግል ማርያም በማኅፀንዋ ተሸከመችው። ይህች ከኪሩቤል ትበልጣለች ፣ ከሱራፌልም ትበልጣለች ከሦስቱ አካል ለአንዱ ማደሪያ ሆናለችና። የነቢያት ሀገራቸው ኢየሩሳሌም ይህች ናት። ለቅዱሳን ሁሉ የደስታቸው ማደሪያ ናት። በጨለማና በሞት ጥላ ውስጥ ለሚኖሩ ሰዎች ታላቅ ብርሃን ወጣላቸው። በቅዱሳን ላይ የሚያድር እግዚአብሔር እኛን ለማዳን ልዩ ከሆነች ከድንግል ሰው ሆኗልና። ኑ ይህን ድንቅ እዩ። ስለተገለጥልን ምስጢር ምስጋና አቅርቡ። ሰው የማይሆን ሰው ሆኗልና። ቃል ተዋሕዷልና። ጥንት የሌለው ሥጋ ጥንታዊ ቀዳማዊ ሆነ ዘመን የማይቆጠርለት መለኮት ዘመን ተቆጠረለት። የማይታወቅ ተገለጠ የማይታይ ታየ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ በእርግጥ ሰው ሆነ። ትላንት የነበረው ዛሬም ያለው መቼም የሚኖረው ኢየሱስ ክርስቶስ እንሰግድለት እናመሰግነው ዘንድ አንድ ባሕርይ ነው። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹ከቅዱሳን ሁሉ ክብር የእመቤታችን ክብር መብለጡ እመቤታችን እግዚአብሔር የወለደች የእግዚአብሔር እናት መባል የቻለች እርሷ ብቻ ስለሆነች ነው።
በዚህም ከኪሩቤል ከሱራፌል ትበልጣለች። ኪሩቤል ሱራፌል ፈርተው ተንቀጥቅጠው የሚያመሰግኑትን እርሷ ታቅፋዋለች ስማዋለች ፣ ኪሩቤል ሱራፌል ዙፋኑን የሚሸከሙለትን እርሱን በማኅፀኗ ተሸክማዋለችና ከኪሩቤል ከሱራፌል ትበልጣለች።
🔹🔸🔹 ከቅድስት ሥላሴ ለአንዱ አካል ማደሪያ ሁናለች ማለት ከቅድስት ሥላሴ አንዱ አካላዊ ቃል እግዚአብሔር ወልድ በማኅፀኗ አድሮ ሥጋዋን ሥጋ ነፍሷን ነፍስ አድርጓልና (ነሥቷልና)።
ለሥላሴ ቅድስት ብሎ የሴት ቅጽል መቀጸሉ ፤ ልጅ ከእናቱ ባሕርይ እንዲገኝ ዓለሙ ሁሉ ከሥላሴ ባሕርይ ተገኝቷልና። #አንድም ሴት ለልጇ እንድታዝን እንድትራራ ሥላሴም ለፈጠሩት ፍጥረት ይራራሉና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ አንድ ከሚሆን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ሕዝቅኤል ነቢይ ኮነ ስምዐ
"ሕዝቅኤል ነቢይ ኮነ ስምዐ በእንቲአሃ ... ፤ ነቢዩ ሕዝቅኤል ስለ እርስዋ መሰከረ ድንቅ በሆነ ታላቅ ቁልፍ የተዘጋች ደጅ በምሥራቅ አየሁ አለ። ከኃያላን ጌታ በቀር ወደ እርስዋ ገብቶ የወጣ የለም። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 በትንቢተ ሕዝቅኤል ም 44 ÷ 1 ጀምሮ እንደተገለጠው ነቢየ እግዚአብሔር ያያት ያቺ የተዘጋች ደጅ የእመቤታችን ምሳሌ ናት።
➣ የተዘጋጅ ደጅ የእመቤታችን ምሳሌ።
➣ ተዘግታ ተቆልፋ ማየቱ የማኅተመ ድንግልናዋ ምሳሌ።
➣ ቀይ ጎልማሳ ሳይከፍታት ገብቶ ሳይከፍታት መውጣቱ ጌታ ከእመቤታችን በድንግልና ተፀንሶ በድንግልና የመወለዱ ምሳሌ ነው።
➣ የኃያላን ጌታ ገብቶባታልና ለዘላለሙ ተዘግታ ትኖራለች ናለቱ እመቤታችን ጌታን ከወለደች በኋላ ለዘላለሙ በድንግልና የመኖሯ ምሳሌ።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። የኃያለን ጌታ ከሚባል ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ኆኅትሰ ድንግል ይእቲ
"ኆኅትሰ ድንግል ይእቲ እንተ ወለደት ለነ መድኅነ ... ፤ ኆኅትም ደጅም መድኃኒታችንን የወለደች ድንግል ናት። እርሱን ከወለደች በኋላ እንደ ቀድሞ በድንግልና ኖራለችና። መጥቶ ምሕረት ከሌለው ጠላት እጅ ያዳነን ጌታን የወለድሽ ሆይ የማኅፀንሽ ፍሬ የተባረከ ነው። አንቺ ፍጽምትና የተባረክሽ ነሽ የእውነት አምላክ በሆነ በክብር ባለቤት ዘንድ ባለሟልነትን አግኝተሻልና በምድር ላይ ከሚኖሩ ሁሉ ይልቅ ገናንነትና ክብር ለአንቺ ይገባል። የአብ ቃል መጥቶ በአንቺ ሰው ሆነ። ከሰው ጋርም ተመላለሰ። መኃሪ ይቅር ባይ ሰውን ወዳጅ ነውና በልዩ አመጣጡ አዳነን። ቅድስት ሆይ ለምኝልን"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 በልዩ አመጣጡ መጥቶ አዳነን ማለቱ ፣ ጌታ ሰው ከመሆኑ አስቀድሞ በረድኤት በአበው በነቢያት እየተገለጠ ሕዝቡን ይጠብቅ ነበር። አምስት ሽህ ከአምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ግን እንደኛ ሰው ሁኖ የእኛን ሥጋ ገንዘቡ አድርጎ ከኃጢአት በቀር የእኛን ሥራ ሠርቶ አድኖናልና በልዩ አመጣጡ መጥቶ አዳነን አለ።
#አንድም : በጽኑ ቀጠሮው መጥቶ አዳነን ሲል ነው። አምስት ሽህ ከአምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከዓመቱ ዓመት ፣ ከወሩ ወር ፣ ከዕለቱ ዕለት ፣ ከሰዓቱ ሰዓት ሳያጎድል ሰው ሆኖ አድኖናልና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። በልዩ አመጣጡ መጥቶ ከአዳነን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
➢➢ የቀጣይ ትምህርት
#ክፍል_ሰባት
የሐሙስ ውዳሴ ማርያም
➜ ነሐሴ / 6 / 2018 ዓ.ም
©መ/ር ማኅቶት እሸቴ
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
የረቡዕ ውዳሴ ማርያም ማብራሪያ
#ክፍል_ስድስት
ከኵሉ ሠራዊተ ሰማያት - ኆኅትሰ
♦️🔹♦️ኵሉ ሠራዊተ ሰማያት
"ኵሉ ሠራዊተ ሰማያት ይብሉ ... ፤ የምድር ሁለተኛ የሆንሽ ሰማይ ሆይ የሰማያት ሠራዊት (መላእክት) ንዕድ ነሽ። ድንግል ማርያም የምሥራቅ ደጅ ናት። ሙሽራዋ ንጹሕ የሆነ ንጽሕት የሠርግ ቤት ናት። አብ በሰማይ አይቶ እንደ አንቺ ያለ አላገኘምና አንድ ልጁን ላከው በአንችም ሰው ሆነ። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 እመቤታችንን ከምድር በላይ ያለሽ ሁለተኛ ሰማይ ማለቱ ሰማይ ለእግዚአብሔር ዙፋኑ ነው እመቤታችንም የእግዚአብሔር ዙፋኑ ናትና።
እመቤታችንን ሙሽራዋ ቅዱስ የሆነ ንጹሕ የሠርግ ቤት ማለቱ እመቤታችን በሠርግ ቤት ትመሰላለችና። በሠርግ ቤት አራት ነገሮች ይደረጋሉ። እሊህም ዘፈን ፣ ጨዋታ ፣ መብል ፣ መጠጥ ፣ የሙሽራውና የሙሽሪት ተዋሕዶ ፣ የሙሽራው ዘመዶችና የሙሽሪት ዘመዶች አንድ ይሆኑባታል። የዚህም ምሥጢር
➣ እንደ መብልና መጠጥ ትምህርት #አንድም : ሥጋው ደሙ።
➣ እንደ ዘፈንና እንደ ጨዋታ ተአምራት።
➣ እንደ ሙሽራውና ሙሽሪት ተዋሕዶ የመለኮትና የትስብእት ተዋሕዶ።
➣ የሙሽራው ዘመዶችና የሙሽሪት ዘመዶች አንድ እንዲሆኑባት ሰውና መላእክት ፣ ሰውና እግዚአብሔር ፣ ነፍስና ሥጋ ፣ ሕዝብና አሕዛብ አንድ ሁነዋልና። በሠርግ ቤት ይህ ሁሉ እንደሚደረግ በእመቤታችንም ይህ ሁሉ ተደርጓልና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ተቀዳሚ ተከታይ ከሌለው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ኵሉ ትውልድ ያስተበፅኡኪ
"ኵሉ ትውልድ ያስተበፅኡኪ ... አምላክን የወለድሽ እመቤታችን ሆይ ትውልድ ሁሉ አንችን ብቻ ያመሰግኑሻል። የእግዚአብሔር ሀገር (ከተማ) ሆይ ነቢያት ድንቅ ድንቅ የሆነ ነገርን ተናገሩልሽ ደስ የተሰኙ የጻድቃን ማደሪያ ሆነሻልና የምድር ነገሥታት ሁሉ በብርሃንሽ ይሄዳሉ። ሕዝቡም ሠራዊቶቻቸውም በብርሃንሽ ይሄዳሉ ፤ ማርያም ሆይ ትውልድ ሁሉ ያመሰግኑሻል። ካንቺ ለተወለደውም ይሰግዱለታል ያገኑታልም። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 እመቤታችንን ሁሉም ትውልድ ያመሰግኗታል ሲል ሁሉም የአዳም ልጅ በኋላም የኖኅ ልጆች ነገድ የሆኑ የሚያመሰግኗት ስለሆነ ነው። #አንድም በዚህ ዓለም በምድር ያሉ በገነት በመንግሥተ ሰማያት ያሉ ያመሰግኗቷልና። እርሷም በሉቃስ ወንጌል እነሆ ከዛሬ ጀምሮ ትውልድ ሁሉ ያመሰግኑኛል ብላለችና።
🔹🔸🔹 እመቤታችን የእግዚአብሔር ከተማ ሀገር ትባላላች። ንጉሥ በከተማው ነግሦ እንዲኖር እግዚአብሔር ማኅፀኗን ዓለም አድርጎ ነግሦባታልና።
ነቢያት ስለ አንቺ ድንቅ ድንቅ ነገር ተናገሩ የተባለው ስለ እመቤታችን የተናገሩትን ትንቢት ነው። ከእነዚህም ውስጥ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት እንዲህ ብሏል "የእግዚአብሔር ከተማ ሆይ ስለ አንቺ የተነገረው ድንቅ ነው"
መዝ 86 ÷ 3
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ዐቢይ እግዚአብሔር እያሉ ከሚያከብሩት ከሚያገኑት
ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ አንቲ ዘበአማን ደመና
"አንቲ ዘበአማን ደመና እንተ አስተርአይኪ ለነ ማየ ዝናም ... ፤ የዝናብ ውኃ የታየብሽ የእውነት ደመና አንቺ ነሽ። አብ የልጁ ምልክት አደረገሽ መንፈስ ቅዱስ አደረብሽ የልዑልም ኃይል ጋረደሽ ማርያም ሆይ ለዘለዓለም የሚኖር የአብን ልጅ ቃልን የወለድሽልን መጥቶም ከኃጢአት አዳነን። ደስ የተሰኘህ ሆነህ ምሥራችን የተናገርክ መልአኩ ገብርኤል ሆይ የተሰጠህ ክብር ታላቅ ነው። ወደእኛ የመጣ የጌታን ልደት ነገርኸን ለድንግል ማርያም ጸጋን የተመላሽ ሆይ እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ነውና ደስ ይበልሽ ብለህ አበሰርኻት። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹እመቤታችን እውነተኛ ደመና መባሏ
✍️ በኖኅ ደመና ትመሰላለች : ጌታ ለኖኅ በአራት ቀለማት በነጭ በጥቁር በቀይ በቢጫ አድርጎ ቀስተደመና አሳይቶ ምድርን ድጋሜ በጥፋት ውኃ እንደማያጠፋት ቃል ኪዳን ሰጥቶታል። ዘፍ 9÷13 ምሳሌነቱም ይህ ነው።
➣ደመና የእመቤታችን
➣ አራቱ ቀለማት የአራቱ ባሕርያት ፣ ጌታ ከእመቤታችን አራቱን ባሕርያት ለመንሣቱ ምሳሌ ነው።
✍️ በኤልያስ ደመና ትመሰላለች : የኤልያስ ደመና በአራተኛው ዓመት ዝናመ ምሕረትን እንዳዘነበች እመቤታችንም በአራተኛው ክፍለ ዘመን (በዘመነ ነቢያት ወይም ካህናት) ከአራተኛው ትውልድ ከይሁዳ ተወልዳ ዝናመ ምሕረት ጌታን ወልዳ ተገኝታለችና።
🔹🔸🔹 አብ የልጁ ምልክት አደረገሽ ማለቱ እመቤታችን ለወልድ ምሳሌ መሆኗን መናገሩ ነው። ይኸውም : ስትወልደው ማኅተመ ድንግልናዋ አለመለወጡ ፤ ጌታ ሰው ሲሆን አምላክነቱ ላለመለወጡ ምሳሌ። ዳግመኛም ድንግልም እናትም ስትባል መኖሩ ፤ አምላክም ሰውም ሲባል ለመኖሩ ምሳሌ ናትና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ዝናመ ምሕረት ከተባለ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ረከብኪ ጸጋ
"ጸጋን አገኘሽ መንፈስ ቅዱስ አደረብሽ የልዑል ኃይልም ጋረደሽ (ጸለለብሽ) ማርያም ሆይ በእውነት ቅዱሱን ወለድሽ ዓለምን ሁሉ የሚያድን መጥቶ አዳነን። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 በእውነት ቅዱሱን ወለድሽ ማለቱ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ተብለው ከሚመሰገኑ ከሥላሴ አንዱን ቅዱስ እግዚአብሔር ወልድን ወለድሽልን ማለቱ ነው።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ሰው ሆኖ ከአዳነን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ግብረ ድንግል ይሴብሕ ልሳንነ
"ግብረ ድንግል ይሴብሕ ልሳንነ ... ፤ አንደበታችን የድንግልን ሥራ ያመሰግናል። ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዳዊት ሀገር ከእርስዋ ስለተወለደ አምላክን የወለደች ማርያም ዛሬ እናመስግናት። አሕዛብ ኑ ማርያምን እናመስግናት። እናትና ድንግል ሆናለችና። ርኵሰት የሌለብሽና የአብ ቃል መጥቶ ካንቺ ሰው የሆነ ንጽሕት ድንግል ሆይ ደስ ይበልሽ ከአባቱ ያልተለየ አንድ እርሱን የተሸከምሽ ሆይ ደስ ይበልሽ ፣ ነውር የሌለብሽ ፍጽምትና ጉድፍ የሌለብሽ ሙዳይ ሆይ ደስ ይበልሽ። ስለ ቀደመ ሰው አዳም ሁለተኛ አዳም የሆነ ክርስቶስ ማደሪያው የምትናገሪ ገነት ሆይ ደስ ይበልሽ። በክብር ጌጥ ሁሉ ያጌጠ እርሱ መጥቶ ሰው የሆነብሽ ንጽሕት የሠርግ ቤት ሆይ ደስ ይበልሽ። የመለኮት እሳት (ባሕርይ) ያላቃጠለሽ ዕፀ ጳጦስ ሆይ ደስ ይበልሽ።
በኪሩቤል ላይ የሚቀመጠውን ሰማያዊ መለኮትን በሥጋ የተሸከምሽ ገረድና እናት ድንግልና ሰማይ ሆይ ደስ ይበልሽ። ስለዚህ ንጹሓን ከሆኑ መላእክት ጋር በፍጹም ደስታ ደስ ተሰኝተን እናመስግን። በሰማይም ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን በምድርም ዕርቅ ይሁን እንበል ክብርና ምስጋና ጌትነት ያለው እርሱ አንቺን ወዷልና። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
ትርጓሜን በሊቃውንት አንደበት
በሊቀ ሊቃውንት ሳሙኤል አስናቀ
የቅዱስ ላሊበላ ገዳም የአራቱ ጉባኤ መጻሕፍት ትርጓሜ ምስክር መምህር
የተለቀቀበት ሚዲያ የጉባኤ ቤቱ ዩቲዩብ ነውና Subscribe በማድረግ ቤተሰብ በመሆን ትምህርታቸውን ተከታተሉ።
የፌስቡክ ገጻቸው
✍️✍️✍️✍️
https://www.facebook.com/6bcctdpck1
የጉባኤ ቤቱ ዩቲዩብ
✍️✍️✍️✍️
https://youtu.be/IM-NNCLFsKQ?si=FFSyvvu03xU4Hz37
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹ስለ አንቺ የሚነገረውን ነገር መናገር የሚቻለው ምን አንደበት ነው ማለቱ የእመቤታችንን ክብሯን ገናንነቷን እንዲሁም አምላክን በማኅፀኗ መሸከሟን በድንግልና ፀንሳ በድንግልና መውለዷን መናገር የሚቻለው አንደበት የለምና ስለዚህ ይህንን አለ።
🔹🔸🔹እመቤታችን በርግብ ትመሰላለችና መልካሟ ርግብ ትባላለች። ርግበ ኖኅም ትባላለች። የኖኅ ርግብ የጥፋት ውኃ ጎደለ ስትል ቅጠል ይዛ እንደ ታየች እመቤታችንም የፍዳ የመርገም የኃጢአት ዘመን አለፈ አበቃ ስትል ጌታን ፀንሳ ተገኝታለችና።
♦️🔹♦️ ተፈሥሒ ኦ ማርያም
"ተፈሥሒ ኦ ማርያም እም ወአመት ... ፤ እናትና ገረድ የሆንሽ ማርያም ሆይ ደስ ይበልሽ። የታቀፍሽውን መላእክት ያመሰግኑታል ኪሩቤልም በፍርሐት ይሰግዱለታልና ሱራፌልም ክንፋቸውን ዘርግተው ያለማቋረጥ የሚመሰገን ንጉሥ (የክብር ባለቤት) ይህ ነው በይቅርታው ብዛት የዓለምን ኃጢኣት ያስተሠርይ ዘንድ የመጣው ይህ ነው ይላሉ። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 እመቤታችን እናትነትን ከገረድነት ወይም ከአገልጋይነት አስተባብራ ይዛለች። እናትነቷን "እናቱን እና ሕፃኑን ይዘህ ወደ ግብፅ ሂድ" ብሎ መልአኩ ነግሮናል። አገልጋይነቷን መልአኩ ባበሠራት ጊዜ እነሆኝ እንደ ቃልህ ይደረግልኝ እኔ ለእግዚአብሔር ባሪያው ነኝ ስትል ሰምተናታልና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። የሰውን ኃጢአት በቸርነቱ ከሚያስተሠርይ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
➢➢ የቀጣይ ትምህርት
#ክፍል_ስድስት
የረቡዕ ውዳሴ ማርያም
➜ ነሐሴ / 5 / 2018 ዓ.ም
©መ/ር ማኅቶት እሸቴ
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
የማክኞ ውዳሴ ማርያም ማብራሪያ
#ክፍል_አምስት
ከቃለአብ ሕያው - ተፈሥሒ ኦ ማርያም
♦️🔹♦️ ቃለ አብ ሕያው
"ቃለ አብ ሕያው ዘወረደ ውስተ ደብረ ሲና ... ፤ ወደ ደብረ ሲና የወረደ ለሙሴ ሕግን የሰጠ የተራራውን እራስ በጭጋግ በጢስ በጨለማና በነፋስ የሸፈነ ፈርተው የቆሙትንም በነጋሪቶች ድምፅ የገሠፀ የአብ አካላዊ ቃል ነው። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።
#ማብራሪያ
🔹🔸🔹 በደብረ ሲና ሙሴና አሮን በተራራው ራስ ፣ ሌዋውያኑ በተራራው ወገብ ፣ ሕዝቡ በተራራው እግር ሆነው ፤ ተራራው በደመና ፣ በጭጋግ ፣ በእሳት ፣ በጨለማ ተጋርዶ እግዚአብሔር ሙሴን ቃል በቃል ተነጋግሮ ዐሠርቱ ትእዛዛትን ሰጥቶታል። ዘጸ 19÷18
♦️🔹♦️ ውእቱኬ ዘወረደ ኀቤኪ
"ውእቱኬ ዘወረደ ኀቤኪ ... ፤ በትሕትና የተናገርሽ ተራራ ሆይ ይኸውም ወደ አንቺ የወረደው ነው። ሰውን የወደደ እርሱ ያለመለወጥ ባንቺ ሰው ሆነ እንደ እኛ በሚናገር ሥጋ ፍጹም ሆኖ አምላክ በመንፈስ ቅዱስ በማኅፀኗ አደረና ፍጹም ሰው ሆነ። አዳምን ያድነው ዘንድ ኃጢአቱንም ያስተሠርይለት ዘንድ በሰማያዊ ማዓርግ ያኖረው ዘንድ በቸርነቱና በይቅርታው ብዛት ወደ ቀድሞው ቦታው ይመልሰው ዘንድ። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ
🔹🔸🔹 ዕበያና ውእቱኬ ተያይዘው ነው የሚተረጎሙት። ወደ አንቺ የወረደው እርሱ ነው ማለቱ በሲና ተራራ ለሙሴ የተናገረው ለሕዝቡ የተገለጠው እግዚአብሔር ወደ አንቺ የወረደውም እሱ ነው ሲል ነው።
🔹🔸🔹እመቤታችንን የምትናገር ተራራ አላት በደብረ ሲና ብትመሰልም ቅሉ በሲና ተራራ ጌታና ሙሴ ተነጋግረውባታል እንጂ እሷ አልተናገረችምና ከዚያ ሲለያት የምትናገር ተራራ አላት። በትሕትና የምትናገር ማለቱም የኢሳይያስን ትንቢት ስታነብ "ድንግል በድንግልና ፀንሳ በድንግልና አምላክን ትወልዳለች" ከሚለው በደረሰች ጊዜ ከዚች እሴት ከዘመኗ ደርሼ ወጥቼ ወርጄ አገልግያት አለች እንጂ እኔ ብሆን አላለችምና።
ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም የደብረ ሲናውን ለእመቤታችን ሰጥቶ ሲናገር እንዲህ ይላል።
"ከደብረ ሲና እሳትና ጨለማ ወጣ ከአንቺ ግን ሰው የሆነ አምላክ ተገኘልን። በደብረ ሲና በአይሁድ ላይ ድንጋፄ ሀውክ ተደረገ። በአንቺም በአይሁድ ፣ በሄሮድስ ፣ በዲያብሎስና በሠራዊቱ ላይ ጽኑ ድንጋፄ ተደረገ።" ሃይ.አበ 47÷8-9
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። በቸርነቱ ብዛት አዳምን ወደቀደመው ቦታው ከመለሰው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ዕበያ ለድንግል
"ዕበያ ለድንግል ኢይትከሀል ለተነግሮ ... ፤ የድንግልን ገናንነቷን ሊናገሩት አይቻልም። ጌታ መርጧታልና የሚቀርበው በሌለ ብርሃን ውስጥ የሚኖር እርሱ መጥቶ አደረባት። ዘጠኝ ወር በማኅፀኗ አደረ የማይታይና የማይመረመር እርሱን በድንግልና ወለደችው። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ
🔹🔸🔹 የድንግልን ክብሯን ሊናገሩት አይቻልም ማለት ለክብሯ እንደሚመጥን አድርጎ መናገር አይቻልም ክብሯን የፍጡር አንደበት ተናግሮ አይፈጽመውም አይገልጸውምና። ጌታ መርጧታል ማለትም በእግዚአብሔር የተመረጠችው እንድትመረጥ ሁና በመገኘቷ ነው።
🔹🔸🔹 የማይታይና የማይመረመር እርሱን በድንግልና ወለደችው ሲል ጌታ ሰው ከመሆኑ አስቀድሞ ሰው በሆነ ጊዜ ሰው ከሆነ በኋላ በፍጡራን አንደበት እንዲህ ነው ተብሎ ሊነገር ሊታሰብና ባሕርይው ሊመረመር አይችልም ሲል ነው። ሰውም ቢሆን የባሕርይ አምላክ ነውና። የባሕርይ አምላክን ደግሞ ፍጡር ሊያውቀው ሊመረምረው አይቻለውም ከሕሊናት ሁሉ በላይ ነውና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ሰው ከመሆኑ አስቀድሞ ሰው በሆነ ጊዜ ሰውም ከሆነ በኋላ ከማይመረመረው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ዘውእቱ ዕብን
"ዘውእቱ ዕብን ዘርእየ ዳንኤል ነቢይ ... ፤ ነቢዩ ዳንኤል ያየው ያለ እጅ ከረጅም ተራራ የተፈነቀለው ያ ደንጊያ ከአብ ዘንድ የመጣው ቃል ነውና መጥቶ ያለ ወንድ ዘር ከድንግል ተወልዶ አዳነን። ቅድስት ሆይ ለምኝልን"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 ነቢየ እግዚአብሔር ዳንኤል ለንጉሡ ታይቶት የተሰወረበትን ሕልም እግዚአብሔር ለእርሱ ባሳየው ጊዜ ከረጅም ተራራ የሰው እጅ ሳይፈነቅለው ወርዶ ጣዖቱን ሰብሮ ተመልሶ ተራራ ሲያክል አየና ወልደ እግዚአብሔር ሰው የመሆኑን ምሥጢር ተረዳ። ምሳሌነቱም ይኸው ነው።
➣ ደንጋይ የወልደ እግዚአብሔር ምሳሌ።
➣ የሰው እጅ ሳይፈነቅለው መውረዱ ያለ ወንድ ዘር የመፀነሱ ምሳሌ።
➣ ጣዖቱን ሰባብሮ ተመልሶ ተራራ ሲያክል ማየቱ : አምላክ ሰው ሁኖ አምልኮ ጣዖትን አጥፍቶ በጣዖቱ አድሮ የሚመለከውን ዲያብሎስንና ሠራዊቱን ድል የመንሣቱ። ተመልሶ ተራራ ማከሉም ደካማ ሥጋ ኃያል አምላክ የመሆኑ ምሥጢር ነው። ይህ ሁሉ የሆነው ከእመቤታችን ተወልዶ ነውና የዳንኤልን ራዕይ አነሣ።
♦️🔹♦️ ኮንኪ
"ኮንኪ ዐፅቀ ንጹሐ ... ፤ እንደ ንጹሕ ጫፍ ሆንሽ ፤ የሃይማኖትም መገኛ ነሽ የቀናች የቅዱሳን አባቶቻችን ሃይማኖታቸው ነሽ። አምላክን የወለድሽና በድንግልና የታተምሽ ንጽሕት ሆይ የአብን ቃል ወለድሽልን። ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ለማዳን መጣ። ቅድስት ሆይ ለምኝልን"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹እስራኤላውያን ተማርከው ፋርስ ባቢሎን በወረዱ ጊዜ የበለስ ቅጠል እንዲያመጣ በመምህሩ ኤርምያስ የታዘዘው አበሜሌክ በለሱን በሙዳይ አድርጎ ይዞ ሲመጣ ከመንገድ አንቀላፍቶት ተኛ ከስልሳ ስድስት ዘመን በኋላም ከእንቅልፉ ነቃ። ነቅቶ ሙዳዩን ቢከፍተው የበለሱ ቅጠል ሳይጠወልግ ደሙ ሳይደርቅ አገኘው።
ይህች በለስ የእመቤታችን ምሳሌ ናት ከስልሳ ስድት ዓመት በኋላ የበለሷ ደም እንዳልደረቀ ቅጠሏም እንዳልጠወለገ ሁሉ እመቤታችንም በስልሳ ስድተኛው ትውልድ (ከአዳም እስከ እመቤታችን ሲቆጠር) ንጽሓ ጠባዕይ (የመጀመሪያ የሰው ንጽሕና) ሳያድፍባት ተገኝታለች።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። እኛን ለማዳን ሰው ከሆነ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ አንቲ እሙ ለብርሃን
"አንቲ እሙ ለብርሃን ... ፤ የከበርሽ ጌታን የወለድሽ ሆይ የማይታይ ቃልን የተሸከምሽው የብርሃን እናቱ አንቺ ነሽ። እርሱን ከወለድሽው በኋላ በድንግልና ኖረሻልና በፍጹም ምስጋና ያገኑሻል። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 እመቤታችን ሁልጊዜም ድንግል ትባላለች እናትነቷ ድንግልናዋን ያላስቀረባት ድንግልናዋ ከእናትነት ያለገዳት ናትና።
♦️🔹♦️ አይ ልሳን
"አይ ልሳን ዘይክል ነቢበ ... ፤ የአብ ቃል እናቱ ንጽሕት ድንግል ሆይ ስለ አንቺ የሚነገረውን ነገር መናገር የሚቻለው ምን አንደበት ነው። ኪሩቤል ለሚሸከሙት ንጉሥ ዙፊኑ (ማደሪያው) ሆንሽ። የተከበርሽ ሆይ እናመሰግንሻለን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ መልካሟ ርግብ ሆይ ስምሽን ለልጅ ልጅ እንጠራለን። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 እመቤታችን የመላእክት ደስታቸው ናት። ለነቢያት ትንቢት ያናገሩለትን ጌታን ወልዳላቸዋለችና። ዳግመኛም ንጽሕናዋን ቅድስናዋን ወላዲተ አምላክነቷን እያዩ ደስ ይላቸዋልና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ሃያው ዓለማትን ከፈጠረ ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ተፈሥሒ እስመ ድልወ
"ተፈሥሒ እስመ ድልወ ተሰመይኪ ... ፤ በሚገባ የአምላክ እናት ተብለሻልና ደስ ይበልሽ። የሔዋን መድኃኒት ሆይ ደስ ይበልሽ ፍጥረቱን ሁሉ የሚመግበውን እሱን ጡትሽን አጥብተሽዋልና ደስ ይበልሽ። የሕያዋን የጻድቃን ሁሉ እናታቸው ሆይ ደስ ይበልሽ። ትለምኝልን ዘንድ ወደ አንቺ እናጋጥጣለን። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 እመቤታችንን በሚገባ ወላዲተ አምላክ ተብለሻልኛ ሲላት በእውነት አምላክን የወለድሽ ነሽ ፣ የታመንሽ አምላክን የወለድሽ ነሽ ፣ ለእናትነት በቅተሽ ብትገኝ የአምላክ እናት ሆንሽ ማለቱ ነው።
🔹🔸🔹 የሔዋን መድኃኒት ማለቱ : ሔዋን ዕፀ በለስን በልታ ሞትን አምጥታ ነበር ሞቱም ለሁሉም ለሰው ልጆች (ለልጆቿ) ተረፈ በሰው ልጆች የተፈረደው ሞት የተወገደው ጌታ ከእመቤታችን ተወልዶ ስለሆነ እመቤታችን መድኃኒቱን ያስገኘችልን ምክንያተ ድኅነት ናትና የሔዋን መድኃኒቷ አለ።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ምልዕተ ጸጋ ምልዕተ ክብር ሆይ ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ኦ ድንግል ኦ ቅድስት
"ኦ ድንግል ኦ ቅድስት ኦ ወላዲተ እግዚእ ... ፤ ድንግል ሆይ ቅድስት ሆይ ጌታን የወለድሽ ሆይ እኛን ለማዳን ድንቅ ምሥጢር (ተዋሕዶ) በአንቺ ቢደረግ ንጉሥን ወልደሽልናልና ፍጥረታትን በልዩ ልዩ መልክ የፈጠረ የርሱን የገናንነቱን ነገር ፈጽመን መናገር አይቻለንምና ዝም እንበል። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።"
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 ፍጥረታትን በልዩ ልዩ መልክ የፈጠረ የርሱን የገናንነቱን ነገር ፈጽመን መናገር አይቻለንምና ዝም እንበል ማለቱ ፡
➣ ሃያ ሁለቱን ስነ ፍጥረት የፈጠረ የእርሱን ሰው የመሆኑን (የሥጋዌውን) ነገር ፈጽመን ጠንቅቀን ወስነን እንዲህ ነው ብለን መናገር አይቻለንምና ዝም እንበል ሲል ነው።
➣#አንድም : በብዙ ወገን የተመሰለ (በእሳት ፣ በፀሐይ ፣ በቀላይ የተመሰለ) የእርሱን የአንድነቱን የሦስትነቱን ነገር ፈጽመን ጠንቅቀን ወስነን እንዲህ ነው ብለን መናገር አይቻለንምና ዝም እንበል።
➣#አንድም : ሰው መሆኑ አስቀድሞ በብዙ ትንቢት የተነገረ በብዙ አምሳል የተመሰለ የእርሱን የሥጋዌውን (ሰው የመሆኑን ነገር) ፈጽመን ጠንቅቀን ወስነን እንዲህ ነው ብለን መናገር አይቻለንምና ዝም እንበል ሲል ነው።
ለእግዚአብሔር ቃል ሰው መሆን ከተነገሩት ትንቢቶችና ከተመሰሉት ምሳሌዎች መካከል
#ትንቢት
➣ "በምድራቸን አበባ ታየ" መኃ 2:12
➣ "ምድር ፍሬዋን ትስጥ" መዝ 85:12
➣ "ንጉሥ ከአንቺ ይወጣል" ሚክ 5:2
➣ "እነሆ ድንግል በድንግልና ፀንሳ በድንግልና ትወልዳለች" ኢሳ 7:14
#ምሳሌ
➣ በእሳትና በቅጠል ➺ ሙሴ ያየው
➣ በጠልና በፀምር ➺ ለጌዴዎን በተደረገው
➣ በኃያል ሰው ➺ ኢሳይያስ የመሰለው
➣ በሚያስፈራ አንበሳ ➺ ኤርምያስ የመሰለው
➣ በቆመ ደንጋይ ➺ ዳንኤል ባየው
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ሥጋዌው በአምሳለ ነበልባል ወሐመልማል ፣ በአምሳለ ጠል ወፀምር ከተመሰለለት ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጕት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
➢➢ የቀጣይ ትምህርት
#ክፍል_አምስት
የማክሰኞ ውዳሴ ማርያም
(ቃለ አብ ሕያው - ተፈሥሒ ኦ ማርያም)
➜ ነሐሴ / 4 / 2018 ዓ.ም
©መ/ር ማኅቶት እሸቴ
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
የማክኞ ውዳሴ ማርያም ማብራሪያ
#ክፍል_አራት
ከአክሊለ - ኦ ድንግል
♦️🔹♦️ አክሊለ
"አክሊለ ምክሕነ ... ፤ የመመኪያችን ዘውድ የድኅነታችን መጀመሪያ የንጽሕናችንም መሠረት እኛን ስለማዳን ሰው የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል በወለደችልን በድንግል ማርያም ተገኘልን። ሰው ከሆነ በኋላም ፍጹም አምላክ ነው። ስለዚህም በድንግልና ወለደችው። ድንቅ የሆነ የመውለዷ ችሎታ የማይመረመር ሊነገር የማይቻል ነው። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹በዚህ ዕለት ከደናግል ኤልያስን ፣ ከመሳፍንት ኢያሱን ፣ ከነገሥታት ዳዊትን አስከትላ መጥታ ነበርና። ዳዊት ንጉሠ ነገሥት ብትባል የመመኪያችን ዘውድ ማምጣት አልተቻለህም። ኢያሱ መድኃኒት ብትባል የድኅነታችን መጀመሪያ መሆን አልተቻለህም። ኤልያስ ንጹሕ ድንግል ብትባል የንጽሕናችን መሠረት መሆን አልተቻለህም። የመመኪያችን ዘውድ የድኅነታችን መጀመሪያ የንጽሕናችንም መሠረት ድንግል ማርያም ናት። #አንድም የሰማዕታት አክሊላቸው ፣ የሕይወት መገኛ ፣ የዓለም መሠረት የሚባል ጌታ ከድንግል ማርያም ተገኘልን።
🔹🔸🔹 የእመቤታችን የስሟ ትርጓሜ : #ማርያም ማለት
➣ ፍጽምት ማለት ነው። ለጊዜው መልክ ከደም ግባት አስተባብራ ተገኝታለች። ፍጻሜው ግን ፤ ንጽሐ ሥጋ ፣ ንጽሐ ነፍስ ፣ ንጽሐ ልቡናን ፤ ድንጋሌ ሥጋ ፣ ድንጋሌ ነፍስ ፣ ድንጋሌ ልቡናን አስተባብራ ተገኝታለችና።
➣#አንድም : ጸጋ ወሀብት ማለት ነው። ለጊዜው ለእናት ለአባቷ ጸጋ ሁና ተሰጥታለች ፍጻሜው ግን ለሰው ሁሉ ጸጋ ሁና ተሰጥታለችና።
➣#አንድም : መርሕ ለመንግሥተ ሰማያት ማለት ነው። ምእመናንን መርታ ገነት መንግሥተ ሰማያት አግብታለችና።
➣#አንድም : ልዕልት ማለት ነው። ከፈጣሪ በታች ከፍጡራን በላይ ናትና።
➣#አንድም : የምእመናንና የሕዝብ አንድነት ፣ የሰውና የእግዚአብሔር ተላላኪ ፣ የእሥራኤል ቤትና የይሁዳ ቤት ደስታ ማለት ነው።
➣#አንድም : እግዝእተ ብዙኃን የብዙኃን እመቤት እናት ማለት ነው።
🔹🔸🔹 ሰው ከሆነ በኋላም ፍጹም አምላክ ነው ማለቱ መናፍቃን ቃል ሥጋ ሆነ ያለውን ይዘው ተለወጠ ብለው ነበርና ፍጹም አምላክ ነው አለባቸው። የእመቤታችን የመውለዷ ነገር ፍጡር ሊመረምረው አይችልም። በግብረ መንፈስ ቅዱስ ነውና። የመንፈስ ቅዱስ ሥራ ደግሞ ፈጣሪ እንጂ ፍጡር ሊያውቀው ሊረዳው አይቻለውምና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። በማይመረመር ግብር ከወለድሽው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ እስመ በፈቃዱ
"እስመ በፈቃዱ ወበሥምረተ አቡሁ ... ፤ በእርሱ ፈቃድ በአባቱም ፈቃድ በመንፈስ ቅዱስም ፈቃድ መጥቶ አዳነን። በድንግልና ፍጽምት የሆንሽ ማርያም ሆይ የድንግልናሽ ምስጋናና ክብር ታላቅ ነው። እግዚአብሔር ካንቺ ጋር ቢሆን ባለሟልነትን አግኝተሻልና። ያዕቆብ ከምድር እስከ ሰማይ ደርሳ የእግዚአብሔር መላእክት ሲወጡባት ሲወርዱባት ያያት መሰላል አንቺ ነሽ። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 ጌታ ሰው መሆኑ በእርሱ ፈቃድ በአባቱ ፈቃድ በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ነው። ሦላሴ በፈቃድ አንድ ናቸውና።
"ውእቱ ወልድ ዘኀደረ ውስተ ከርሠ ድንግል በፈቃደ አቡሁ ወበሥምረተ መንፈስ ቅዱስ። እስመ አሐቲ ይእቲ ሥምረት ዘሥሉስ ቅዱስ። የሥላሴ ፈቃድ አንዲት እንደመሆኗ በአባቱ ፈቃድ በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ በድንግል ማኅፀን ያደረ ወልድ ነው።" እንዳለ ሳዊ. ሃይ.አበ 84÷11
🔹🔸🔹 ያዕቆብ በሎዛ ያያት መሰላል አንቺ ነሽ ማለቱ መሰላሉ የእመቤታችን ምሳሌ ስለሆነ ነው።
"እነሆም መሰላል በምድር ላይ ተተክሎ፥ ራሱም ወደ ሰማይ ደርሶ፥ እነሆም የእግዚአብሔር መላእክት ይወጡበት ይወርዱበት ነበር።" (ዘፍ 28:12)
➣የወርቅ መሰላል የእመቤታችን ምሳሌ።
➣ መሰላሉ የቆመበት ደንጋይ የነቢያት ትንቢት ምሳሌ። መሰላሉ በደንጋዩ ላይ ጸንቶ መታየቱ እመቤታችን በነቢያት ትንቢት ጸንታ ለመገኘቷ ምሳሌ።
➣ ዙፋን የመኅፀኗ። በዙፋኑ የተቀመጠው ንጉሥ የጌታ ምሳሌ።
➣መላእክት ሲወጡ ሲወርዱ ማየቱ ጌታችን ከእመቤታችን በተወለደ ጊዜ ለምስጋና ለተልእኮ የሚወጡ የሚወርዱ ሁነዋልና።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ያዕቆብ በፍኖተ ሎዛ በአምሳለ ንጉሥ ካየው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ አንቲ ውእቱ ዕፅ
"አንቲ ውእቱ ዕፅ ... ፤ ሙሴ በነደ እሳት ሳትቃጠል ያያት ዕፅ አንቺ ነሽ ይኸውም መጥቶ በማኅፀንሽ ያደረው የእግዚአብሔር ልጅ ነው። የመለኮቱ እሳትነት ሥጋሽን አላቃጠለውም። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹እመቤታችንን ሙሴ ያያት ዕፅ ማለቱ ምሳሌዋ ስለሆነ ነው።
"እነሆም ቍጥቋጦው በእሳት ሲነድድ ቍጥቋጦውም ሳይቃጠል አየ። " (ዘጸ 3:2)
➣ ሐመልማሉ (ቅጠሉ የእመቤታችን) ፡ እሳቱ የጌታ ምሳሌ ሲሆን። እሳቱ ቅጠሉን ሳያቃጥለው ማየቱ እመቤታችን ጌታን በፀነሰች ጊዜ እሳተ መለኮቱ አላቃጠላትም።
"ድንግል ሆይ እሳተ መለኮት በሆድሽ ውስጥ ባደረ ጊዜ እንደምን አላቃጠለሽም" እንዳለ። አባ ሕር
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ሙሴ በእሳትና በቅጠል አምሳል ካየው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ አንቲ ውእቱ ገራኅት
"አንቲ ውእቱ ገራኅት ... ፤ ዘር ያልተዘራባት እርሻ አንቺ ነሽ። የሕይወት ፍሬ ከእንቺ ወጣ። ዮሴፍ የዋጃትና የከበረ ዕንቍን ያገኘባት ሣጥን አንቺ ነሽ። ይኸውም መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። በማኅፀንሽ አደረ በዚህ ዓለምም ወለድሽው። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 እመቤታችንን በማክሰኞ እርሻ ይመስላታል ያቺ ዘር ሳይዘራባት "ምድር ታብቅል" ባለው ቃል ብቻ አትክልትን ፣ አዝእርትን ፣ ዕፅዋትን እንዳስገኘች እመቤታችንም ትፀንሻለሽ ያለውን ቃል ብቻ ከመልአኩ በመስማት አካላዊ ቃልን አስገኝታለች።
🔹🔸🔹 ዮሴፍ የተወዳጃት ሣጥን የተባለች እመቤታችን ናት። ያቺ ሣጥን በቁልፍ የተቆለፈችና በውስጧ ዕንቍ ያለባት ናት።
ቍልፉ የእመቤታችን የማኅተመ ድንግልናዋ ፤ በውስጧ ያለው ዕንቍ የጌታ ምሳሌ ነው።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። በዕንቍ ከተመሰለው ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
♦️🔹♦️ ተፈሥሒ ኦ ወላዲተ እግዚእ
"ተፈሥሒ ኦ ወላዲተ እግዚእ ... ፤ የመላእክት ደስታቸው የሆነ ጌታን የወለድሽ ሆይ ደስ ይበልሽ። የነቢያት ዜናቸው ንጽሕት ሆይ ደስ ይበልሽ። እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ቢሆን ባለሟልነትን አግኝተሻልና ደስ ይበልሽ። የዓለም የሰው ሁሉ ደስታ የሆነ የመልአኩን ቃል ተቀብለሻልና ደስ ይበልሽ። ዓለምን ሁሉ የፈጠረ ጌታን የወለድሽ ሆይ ደስ ይበልሽ። ቅድስት ሆይ ለምኝልን።
#ማብራሪያ :-
🔹🔸🔹 ብርሃን ያለው ጌታን ነው። እርሱ የዓለምን የኃጢአት ጨለማ ያስወገደ እውነተኛ ብርሃን ነውና። የሰው ፍቅር አገብሮትም ወደ ዓለም መጥቷል።
"ኃያል ወልድን ፍቅር ከዙፋኑ ጎትቶ አወረደው።" እንዳለ አባ ሕርያቆስ
"ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም መጣ።" (ዮሐ 1:9)
" በዓለም ሳለሁ የዓለም ብርሃን ነኝ።" (ዮሐ 9:5)
🔹🔸🔹 ፍቅር ስቦህ ወደ ዓለም በመምጣትህም ፍጥረት ሁሉ ደስ አለው። ፍጥረት ያላቸው ሰው ፣ መላእክት ፣ እንስሳት አራዊት ናቸው። እሊህ ሁሉ በጌታ ሰው መሆን ደስታን ገንዘብ አድርገዋልና።
🔈መላእክት :- ሰው እንደሚሆን አስቀድመው ተልከው ለነቢያት ትንቢት የሚናገሩ እነርሱ ነበሩና ሰው ሁኑ አይተውት የማያውቁትን አምላክ በቤተልሔም ተወልዶ ሲያዩት ፤ አዲስ ምስጋና "ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን ለሰውም በጎ ፈቃድ" በማለት አመስግነዋል።
🔈እንስሳት አራዊት ጌታቸው አዳም ከፈጣሪው ጋር ስለታረቀላቸው ደስ ብሏቸዋል። በተጣላ ጊዜ ለሰው የመጣው ጥፋት እነርሱንም በጥፋት ውኃ ፣ በሰዶም አጥፍቷቸው ነበርና ከእንግዲህ ወዲህ ከጌታው ጋር ከታረቀ እኛንም ጥፋት አያገኘንም ሲሉ።
የልደት ዕለት ሚዳቋ "የዓለም መድኅን ዛሬ ተወለደ" እያለች ስትዘል አንድ ባሕታዊ እንዳያት።
🔹🔸🔹ከክርስቶስ መወለዳችን ረቂቅ ልደት ይባላል ይኸውም በጥምቀት የምናገኘው ልደት ነው። ከመላእክት ጋር አመሰገንህ ማለቱ ልደት ስለሚያገናኘን ነው። በልደቱ ተገናኝተናልና።
"ይህንን የክርስቶስን ልደት ሰዎች ብቻ የሚሹት አይደለም መላእክትና ሊቃነ መላእክት እንጂ" እንዳለ አረ.መን ድር ÷ 19
መላእክት ይሹታል ማለት ለዘመናት ያላዩትን አምላክ ያዩት በልደቱ ነውና። ከሰው ልጅ ጋር የነበራቸውም ጥል የተቋጨውና በዕርቅ የተፈጸመው በጌታ ልደት ነውና ስለዚህ ነው።
🔹🔸🔹 ሰአሊ ለነ ቅድስት። ብርሃን ከሚባል ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድሪብን።
🔹🔸🔹 ቅድስት አለ እመቤታችንን ፤ ንጽሕት ፣ ጽንዕት ፣ ክብርት ፣ ልዩ ነሽ ሲል ነው።
✍️ ንጽሕት አላት ፡ ሌሎች ሴቶች ከነቢብ (ከመናገር) ፣ ከገቢር (ከመሥራት) ቢነጹ ከሐልዮጨኃጢአት (ከማሰብ) አይነጹምና።
እሷ ግን ከሁሉም ንጽሕት ናትና።
"ከፈጠራት ጀምሮ በምንም በምን ከድንግልናዋ አልተለወጠችምና" እንዳለ ቴዎ ሃይ.አበ 53÷22
✍️ ጽንዕት አላት ፡ ሌሎች ሴቶች በድንግልና ቢጸኑ ለጊዜው ነው በኋላ ግን (ቢያገቡ ፣ ቢጸንፁ ፣ ቢወልዱ) ተፈትሖ አለባቸው። እርሷ ግን ከመፅነሷ አስቀድሞ ፣ በፀነሰች ጊዜ ፣ ከፀነሰች በኋላ ፣
ከመውለዷ አስቀድሞ ፣ በወለደች ጊዜ ፣ ከወለደች በኋላ በድንግልና ጽንዕት ናትና።
✍️ ክብርት አላት ፡ ሌሎች ሴቶችን ብናከብራቸው ጻድቃንን ፣ ሰማዕታትን ፣ ጳጳሳትን ፣ መነኰሳትን ፣ ሊቃውንትን ፣ መምህራንን ወለዱ ብለን ነው። እርሷን ግን የምናከብራት ወላዲተ አምላክ (አምላክን የወለድሽ) ፡ እመ አምላክ (የአምላክ እናት) ብለን ነውና። ስለዚህ በክብሯ ከሌሎች ሴቶች ብቻ ሳይሆን ከሁሉም ፍጡራን ከሰው ከመላእክት ትከብራለች ትበልጣለች።
✍️ልዩ አላት እመቤታችንን ፡ እናትነትን ከድንግልና ድንግልናን ከእናትነት አስተባብራ የያዘች ፣ እናት ስትሆን ድንግል ድንግል ስትሆን እናት የሆነች ከእመቤታችን በቀር ማን አለና።
"ድንግል ሆይ እናት ስትሆኝ ድንግል ነሽ ድንግል ስልሽም እናት ነሽ ፣ እመቤቴ ሆይ አንቺን ለመጥራት እንደዚህ ከተቸገርኩ ልጅሽን ለመጥራትማ እንደምን እቸገር እሆን" እንዳለ ቅዱስ ኤፍሬም።
✍️ ሠዐሊ (ሰአሊ) ለነ ቅድስት ፡
➣ ሠዐሊ : ዐይኑ "ዐ" ቢሆን አእምሮውን ማስተዋሉን በልቡናችን ሳይብን አሳድርቢን ማለት ነው።
➣ ሰአሊ : አልፋው "አ" ቢሆን ለምኝልን ማለት ነው። ልመና ስንኳን በእርሷ በሌሎቹ ቅዱሳንም የለባቸው። በቀደመ ልመናቸው በቀደመ ቃልኪዳናቸው ያስምራሉ እንጂ። መውደቅ መነሣት እባክህ እገሌን ማርልኝ ይቅር በልልኝ ብሎ መመጸን የለባቸውምና።
"ጻድቃን ባንዲት ልመናቸው የሹትን ሁሉ ያገኛሉ" እንዳለ ዮሐ. አፈ. ድር 13
ባንዲት ልመናቸው የተባለ በምድር በነበረ ልመናቸው ተጋድሏቸው ነው።
እመቤታችንም በቀደመ ቃልኪዳኗ የምታስምር ስለሆነ ለምኝልን እንላታለን።
✍️ ቅዱስ ኤፍሬም ይህንን የዕለቱን ምስጋናዋን ሲጨርስ ፤ አንተ ክፍልህ ቦታህ ከእኔ ጋር ነው ፤ ይህንን ውዳሴዬን ያሰሙ ፣ የሰሙ ፣ የጸለዩ ክፍላቸው ቦታቸው ከአንተ ጋር ነው ብላ በያዘችው የብርሃን መስቀል ባርካው ታርጋለች። እርሱም ተባርኮ እጅ ነሥቶ ይቀራል።
ይህም የሚያሳየው የእመቤታችንን ውዳሴዋን የሰሙ ያሰሙ በገነት በመንግሥተ ሰማያት የቅዱስ ኤፍሬምን ክብር እንደሚያገኙ ነው።
#የሰኞ_ውዳሴ_ማርያም_ተፈጸመ
◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊◈◊
➢➢ የቀጣይ ትምህርት
#ክፍል_ሦስት
የማክሰኞ ውዳሴ ማርያም
(አክሊለ - ኦ ድንግል )
➜ ነሐሴ / 3 / 2018 ዓ.ም
©መ/ር ማኅቶት እሸቴ
👇👇👇
የቴሌግራም ሊንክ
https://t.me/MEBspiritualtraining21
👇👇👇
የፌስቡክ አድራሻ
https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1
