በወላይታ አከባቢ ዘኦርቶዶክስ ተዋህዶ ልጆች ማህበር
Open in Telegram
እውነተኛ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ድምፅ!! በዚህ የቴሌግራም ቻናል የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ዶግማን፡ቀኖናን እና ትውፍትን የጠበቁ ስርዓተ አምልኮ ትምህቶች እና ዝማሬዎች ይቀርቡበታል!!!
Show more326
Subscribers
No data24 hours
No data7 days
No data30 days
Posts Archive
ያሳዝናል 😥
በአማራ ክልል እየተካሄደ ባለው ጦርነት በደብረ ታቦር ከተማ በሚገኘው ደብረ በረከት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተክርስቲያን በከባድ መሳሪያ መመታቱ ተገለጸ።
ለማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን መረጃውን ያደረሱን አገልጋዮች በጥቃቱ አንድ ዲያቆንና አንድ ምእመን መሞታቸውንና ስምንት አገልጋዮችና ምእመናን ተጎድተው በሕክምና ላይ እንደሚገኙ ነግረውናል።
በደብረ በረከት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተክርስቲያን ላይ ኅዳር 15 ቀን 2016 ዓ.ም ከጠዋቱ አንድ ሰአት ገደማ የሥርዓት ቅዳሴ አገልግሎት በመጠናቀቅ ላይ ሳለ ነው በቤተክርስቲያኗ ላይ ከባድ መሳሪያ የወደቀው ተብሏል።
ቤተክርስቲያኑም ከባድ ጉዳት እንደደረሰበት ተጠቁሟል።
ምንጭ ማህበረ ቅዱሳን
★16★. ኪዳነ ምህረት
በጨነቃችሁ ጊዜ ሁሉ እናታችን ቅድስት ኪዳነ ምህረት በዕለተ ቀኗ አለው ትበላችሁ።
በረድኤት በበረከት ትጎበኘን🥰🙏🥰
📌ጾም ሙሽሪትን ትመስላለች፤ ሙሽሪትን በሠርግ አዳራሽ ኾነው የሚቀበሏት ሰዎች ቤቱን ያስጌጡታል፤ ይሸልሙታል፡፡ ወደ ሠርጉ አዳራሽ የሚገባውን ሰው የሠርግ ልብስ ለብሶ እንደኾነ፣ የቆሸሸ እንዳልኾነ አይተው ያስገቡታል፡፡ እኛም እንዲኽ ልንኾን ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ልቡናችንን በማንጻት፣ ልል ዘሊል ከመኾን በመራቅ፣ የክፋት እርሾን በማስወገድ፣ ከጾም ጋር አብረው የሚመጡትን የሚያጅቧትን መልካም ምግባራትንም ለመቀበል የልቡናችንን ውሳጤ በመክፈት የምግባር እናት፣ የማስተዋል እንዲኹሉም ለሌሎች ምግባራት ኹሉ ንግሥት የምትኾን ጾምን ልንቀበላት ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ይኽን ያደረግን እንደኾነ ታላቅ ሐሴት እናደርጋለን፤ ርሷም ቁስለ ነፍሳችንን ትፈውስልናለች፡፡
በሌላ አገላለጽ ብነግራችኹ ሐኪሞች በአንድ ታማሚ ሰውነት ውስጥ ያለውን ቆሻሻ፣ መርዘኛ ፈሳሽን ማስገድ ሲፈልጉ መጀመሪያ የሚያደርጉት ነገር ቢኖር ታማሚው ምግብ ከመውሰድ እንዲቈጠብ ነው፡፡ ታማሚው ለጊዜው ምግብን ከመብላት ካልተከለከለ ሓኪሞቹ የሚሰጡት መድኃኒት እንደተፈለገው ውጤት አይሰጥም፡፡
እኛም ቁስለ ነፍስ ቁስለ ሥጋ የምትፈውሰውን ጾም ስንቀበላት ከዚኽ በላይ ልንኾን ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስን የምንሻ ከኾነ ልቡናችንን ንጹሕና ንቁ በማድረግ ልንወስዳት ይገባናል፡፡ እንዲኽ ካልኾነ ግን ከጥቅሟ ይልቅ ጉዳቷ ያመዝናል፡፡
#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ
ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ልጆች👇
•➢ ሼር // SHARE
🔸
🔸🔹🔸
🔸
✍️Comment
ቅዱስ ሲኖዶስ ባስተላለፈው ውሳኔ መሰረት ከኅዳር 15 አስከ21 ቀን 2016 ዓ.ም የሚካሔደው የምህላና የጸሎት መርሐ ግብር ከላይ በተጠቀሱት ሰባት ቀናት ከማለዳው 12:00 ሰዓት እስከ ጠዋቱ 1:00 ሰዓት በምሽት መርሐ ግብር ደግሞ ከምሽቱ 12:00 ሰዓት እስከ ምሽቱ 1:00 ሰዓት ድረስ የሚከናወን ሲሆን ሕዝበ ክርስቲያኑ በየ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ በመገኘት በመርሐ ግብሩ ላይ እንዲሳተፍ እየገለጸ አጠቃላይ መርሐ ግብሩ ቀደም ሲል በተሰጠው መግለጫ መሰረት የሚፈጸም መሆኑን ያስታውቃል።
የቅዱስ ሲኖዶስ ጽሕፈት ቤት
#ሰው_እናታችን_ጽዮን_ይላል፥ በውስጥዋም ሰው ተወለደ፤ እርሱ ራሱም ልዑል መሠረታት። መዝ 86/5
#ህዳር_ጽዮንን_በኦቶና_ደብረ_ጽዮን
የደብሩ ምግባረ ሠናይ ማኅበር ከሰበካ ጉባኤ ጋር በመተባበር
ታላላቅ መምህራንና ዘማሪያን የተጋበዙበት ድንቅ የትምህርተ ወንጌል ጉባኤ ተዘጋጅቷል!
የማይቀርበት ታላቅ ጉባኤ!!!
“አንተ ሰው የበደለህን ይቅር ሳትል ወደ ጾም አትግባ፡፡ አንተን በበደለህ ሰው ላይ በቁጣ እያለህ የምትጾመው ጾም ከንቱ ነው፤ እግዚአብሔርም አይቀበለውም፡፡ ጾምህን በፍቅርና እርሱን ተስፋ በማድረግ በእምነት ካላደረግኸው አንተን ፈጽሞ ሊረዳህ አይችልም፡፡ በጠብ ሆኖና በውስጡ ጠላትነትን አንግሦ የሚጾም ጸዋሚ እግዚአብሔርን ይጠላዋል፤ ከመዳንም ፈጽሞ የራቀ ነው፡፡"
ቅዱስ_ኤፍሬም
እንኳን አደረሳችሁ💕🙏💕
#ብፁዕ_አቡነ_ኤርሚያስ_የተናገሩት
"ጥቅል የንግግሬን ሃሳብ የወሰደልኝ የለም፣ ሁሉም መርጦ ነው የሚሰማው። መንግስትም በሚዲያው ቆራርጦ ቆራርጦ የሚመቸውን ወስዶ በሚዲያው አሰራጨ፣ ሌላውም የሚመቸውን ወሰደ ሁሉ አብጠለጠለኝ።
" ሁሉም ስቀለው ስቅለው አሉኝ። እግዚአብሔር ይርዳኝ ለመሰቀል ዝግጁ ነኝ። በዚህ ዘመን ምን እንድል ነበር የተፈለገው? እኔ ሸሽቼ ደኅንነቱ የተጠበቀ ቦታ ላይ ኾኜ ሳይሆን ከእናንተ ጋር መከራው ውስጥ ካላችሁት ጋር መሐል ኾኜ መታሰርም መሰደበም እያመንኩ ነው እየተናገርኩ ያለኹት።"
ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ
#followlikecommentandshare
የምሕላና የጸሎት መርሐ ግብርን በተመለከተ ከቅዱስ ሲኖዶስ ጽሕፈት ቤት የተሰጠ ማሳሰቢያ።
ቅዱስ ሲኖዶስ ባስተላለፈው ውሳኔ መሠረት ከኅዳር 15 አስከ 21 ቀን 2016 ዓ.ም የሚካሔደው የምሕላና የጸሎት መርሐ ግብር ከላይ በተጠቀሱት ሰባት ቀናት ከማለዳው 12:00 ሰዓት እስከ ጠዋቱ 1:00 ሰዓት በምሽት መርሐ ግብር ደግሞ ከምሽቱ 12:00 ሰዓት እስከ ምሽቱ 1:00 ሰዓት ድረስ የሚከናወን ሲሆን ሕዝበ ክርስቲያኑ በየ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ በመገኘት በመርሐ ግብሩ ላይ እንዲሳተፍ እየገለጸ አጠቃላይ መርሐ ግብሩ ቀደም ሲል በተሰጠው መግለጫ መሰረት የሚፈጸም መሆኑን ያስታውቃል።
የቅዱስ ሲኖዶስ ጽሕፈት ቤት
ምንጭ: EOTCPR
አማላጃችን ሚካኤል ሆይ ፈጥኖ ደራሻችን ሚካኤል ሆይ የጌታን ዙፋን ከሚያጥኑ ሱራፌል ካህናት አንዱ ሰማያዊ ካህን አንተ ነህ ። የሰማያውያን ሊቃነ መላእክት ሁሉ አንተ አለቃቸው ነህ ። ይልቁንም የልዑላንም ልዑል አንተ ነህና በጠራሁህ ጊዜ ሁሉ በይቅርታና በቸርነት ድረስልኝ አትራቀኝ።"
መልክአ ሚካኤል
የሊቀ መላእክቅዱስ ሚካኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል በወላይታ ሀ/ስብከት ውስጥ በተለያዩ ቦታዎች በድምቀት ተከብሮ ዉሏል!
ኂዳር 12.2016 ዓ/ም
የሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ዓመታዊ በዓል በወላይታ ሀገረ ስብከት በቦ/ሶሬ ወረዳ ቤተ-ክህነት #በአረካ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ክቡር አባታችን መላከ ሰላም ቀሲስ ቦክቻ ኤንጋ የወላይታ ሀገረ ስብከት ዋና ስራ-አስኪያጅና መጋቤ ብርሃናት ቀሲስ ዳዊት ደርቤ የወረዳው ሥራ አስካጅና የደብሩ ዋና አስተዳዳሪ በተገኙበት በታላቅ ድምቀት ተከብሮ ዉሏል
ምንጭ ዲ/ን አለሙ ከአረካ
፲፪
ህዳር ሚካኤል
ህዳር ሲታጠን
#እንኳን_ለቅዱስ_ሚካኤል ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ አደረሰን።
✝️ #ሚካኤል ማለት " መኑ ከመ እግዚአብሔር፣ እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው ?" ማለት ነው::
✝️ሚካኤል በስም ተለይቶ መጠቀስ የተጀመረው በመጽሐፈ ዳንኤል /ት.ዳን ፲፣፲፫ ውስጥ ነው:: በመጽሐፈ ሄኖክም ለበርካታ ጊዜያት ተጠቅሷል:: ከዚህ ሌላ በብሉይ ኪዳን አዋልድ መጻሕፍት 5:6 በኪዳነ አብርሃም ውስጥም ተጠቅሶ ይገኛል::
ቅዱስ ሚካኤል በየዘመኑ እየተገለጠ ከእግዚአብሔር ተልኮ ታላላቅ አባቶችን ረድቷል::
✝️እንደ ቅዱሳን አባቶቻችን አስተምህሮ ህዳር 12 ቀን ታላቁ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል በኢዮር ባለችው በአራተኛይቷ ከተማ በሚኖሩት ኃይላት እና በአሥሩ ነገደ መላእክት ላይ አለቃ ሆኖ የተሾመበት ቀን ነው፡፡እግዚአብሔር ሳጥናኤልን በትዕቢቱ ምክንያት ከሥልጣኑ ገፍፎ ወደ ምድር ሲጥለው ቅዱስ ሚካኤል በእርሱ ቦታ በዐሥሩ ከተማ በመቶውም ነገደ መላእክት ላይ ተሹሟል፡፡(ይህን ሁለተኛውን ሹመት ያገኘው በሚያዚያ 2 እንደሆነ አክሲማሮስ በሚባለው የቤተክርስቲያናችን መጽሐፍ ላይ ሰፍሮ አናገኛለን፡፡)
የቅዱስ ሚካኤል ሹመት በነገደ መላእክት ላይ ብቻ ግን አይደለም ፤ ነገር ግን የእግዚአብሔር ሕዝብ በሆኑት ላይም ጭምር ነው ፡፡
✝️ እንዲሁም ይህ ዕለት ቅዱስ ሚካኤል ሕዝበ እስራኤልን ከግብፅ ምድር ጀምሮ ከነዓን እስኪገቡ ድረስ እየመራ እየጠበቀ አብሯቸው በመጓዝ ምድረ ርስት እንዲገቡ ያደረገበት መታሰቢያ ነው:: በዚሁ ዕለት በመጽሐፈ ኢያሱ 5:13 በተጠቀሰው መሠረት ቅዱስ ሚካኤል የተመዘዘ ሰይፍ በመያዝ በምድርና በሰማይ መካከል ቆሞ ለኢያሱ ተገልጦለታል:: ኢያሱም አይቶ ሰግዶለታል:: በ እርሱ ላይ? እንዲህ ይላል:- "ሁልግዜ ከ እግዚአብሔር ዙፋን ፊት ቆሞ ለሰው ሁሉ የሚማልድ መልአክ ነው:: የነዌ ልጅ ኢያሱ በንጉሥ የጦር ቤት ወዳጅ፣ አምሳል፣ ክቡር፣ ገናና ሆኖ ያየው ይህ ሚካኤል ነው:: ባየውም ጊዜ ከግርማው የተነሣ ደነገጠ:: በግንባሩም ከምድር ላይ ወድቆ ሰገደለት:: ጌታዬ ሆይ ከሰማይ ሠራዊት ወገን አንዱ ከአለቆች አንዱ ነኝ"፡ብሎ ቅዱስ ሚካኤል መለሰለት::
✝️ ተራዳኢው መልአክ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ህዝበ እስራኤልን ከግብጽ ባርነት እየመራ ወደ ከነአን እንዳስገባቸው በስደት በባዕድ ሃገር የሚሰቃዩትን ወገኖቻችንን እየመራ ወደ ሃገራችን ያስገባልን! ጥላ ከለላ ሆኖ ይጠብቅልን! እኛንም ዛሬ ከተያዝንበት የመለያየት እና የመከፋፈል ባርነት ወደ አንድነት፣ ወደ ሰላም ፣ ወደ ፍቅርና ዘላለማዊ ህይወትን ወደምንወርስበት ወደ ንስሃ ህይወት ይምራን!!! የቅዱስ ሚካኤል አማላጅነቱ እና ጥበቃው አይለየን !!!
ቅዱስ ሲኖዶስ ሀገራዊ ሰላምን፣ መረጋጋትንና አንድነትን ለማስፈን የታወጀውን የጾምና የጸሎተ ምሕላ አፈጻጸምን አስመልክቶ መግለጫ ሰጠ !
ኅዳር 11 ቀን 2016 ዓ.ም (ተ.ሚ.ማ /አዲስ አበባ)
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ሀገራዊ ሰላምን፣ መረጋጋትንና አንድነትን ለማስፈን የታወጀውን የጾምና የጸሎተ ምሕላ አፈጻጸምን አስመልክቶ በዛሬው ዕለት መግለጫ ሰጥቷል።
የመግለጫው ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል።
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ
ሀገራዊ ሰላምን፣ መረጋጋትንና አንድነትን ለማስፈን የታወጀውን የጾምና የጸሎተ ምኅላው አፈጻጸም በቅደሱ ሲኖዶስ በተወሰነው መሠረት ከዚህ በመቀጠል አቀርባለሁ፡፡
ቀደም ሲል ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ መሠረት በመላው ዓለም ለሚገኙ ሕዝበ ክርስቲያን የታወጀውን አዋጅ አስተላልፈዋል፡፡ በዚሁ መሠረት ያለፈውን በይቅርታና በምህረት ዘግተን በእውነተኛ ንሥሓ ልቅሶና በምህላ፣ በጾምና በጸሎት ወደ ፈጣሪ እንድንቀርብ፣ በመካከላችንም ፍቅርና አንድነት እንዲመጣ ይኽንን ጾመ ነቢያት ወይም የገና ጾም በልዩ ሁኔታ እንድንጾም መንፈሳዊ አዋጅ ተላልፏል፡፡
ይኽ ጥንታዊ የአዋጅ ጾም ሁለት አበይት ታሪኮችን የያዘ ነው፡፡ የመጀመሪያው ክፍል ቅዱስ አብርሃም ሶርያዊ የተባለ ጻድቅ አባት በጸሎት፣ በጾምና በምኅላ ተራራን ከመሬት ከፍ በማድረጉ ኃይለ ጸሎቱና ክብረ አምለኩ የሚዘከርበት ነው፡፡ በሁለተኛው ክፍል ነቢያት የጌታችንን ሰው መሆን እያፈለጉ፣ ድህነትንና ሰላምን በመሻት መጾማቸው ይዘከራል፡፡ (፩ኛ ጴጥ ፩፡፲) እኛም ይኽንን አብነት አድርገን ታላቋ ቤተ ክርስቲያን፣ ኃላፊነቷን እንድትወጣ ስለችግራችን፣ ስለሀገር ሰላምና ስለ ሕዝቡ ደኅንነት በአንድነት ሆነን ወደፈጣሪያች እንድንጮኽ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በጥቅምት ወር ፳፻፲ወ፮ ዓ/ም ወስኖ መግለጫ ሰጥቷል፡፡
ሀገራችን እንድትፈወስ፣ የወገን በወገን ደም መፋሰስ እንዲቀር፣ ያለፈውን በይቅርታና በንሥሓ ዘግቶ ለወደፊቱ ብሩህ ዘመንን እንዲመጣ በንሥሓና በፍጹም ለቅሶ፣ በቁመትና በሰጊድ፣ በሰፊሕና በአንቅአድዎ፣ ወደፈጣሪ እንድንቀርብ የምልኣተ ጉባኤውን ውሳኔ መሠረት በማድረግ ቋሚ ሲኖዶስ በኅዳር ወር ፳፻፲ወ፮ዓ/ም የሚከተለውን ዝርዝር አፈጻጸም አውጥቷል፡፡
፩ኛ. የጾሙ የመጀመሪያ ሳምንት ከቅዳሜ ኅዳር ፲፭ እስከ ኅዳር ፳፩ ቀን ፳፻፲ወ፮ ዓ/ም በሁሉም የሀገራችን ክፍልና ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ባለችበት በመላው ዓለም የንሥሓ፣ የጾም፣ የጸሎትና የምኅላ ሳምንት እንዲሆን፤
፪ኛ. በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ በአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ በአጥቢያ አለቆችና በገዳም አበምኔቶች መሪነት ሁሉም ዲያቆናት፣ ቀሳውስት፣ መነኰሳት፣ ሰባክያንና ሊቃውንት በሙሉ በየመዐርጋቸው ልብሰ ተክህኖና ወጣት የሰንበት ትምህርት ቤት ዩኒፎርማቸው ለብሰው፣ ሁሉም ምእመናን ጋር በአንድነት በዐውደ ምህረት ጸሎተ ምኅላውን እንዲያደርሱ፤
፫ኛ. በላው ሕዝበ ክርስቲያን ከሊቅ እስከ ደቂቅ፣ ሕፃናት፣ ወጣቶች፣ እናቶች አባቶች አረጋውያን ሁሉ የቻለ በቤተ ክርስቲያን፣ ያልቻለ በያለበት ሆኖ የተጣላ ታርቆ፣ በፍቅርና በአንድነት፣ በእውነተኛ ንሥሓና ጸጸት በምኅላው እንዲሳተፍ፤ በማእከል የሚደረገው ጸሎተ ምኅላ በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ መሪነት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በተገኙበት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም ገዳም ሆኖ በመገናኛ ብዙኀን የቀጥታ ሥርጭት ለመላው ዓለም እንዲተላለፍ፤
፬ኛ. በመጀመሪያው የሱባኤ ቀን ኅዳር ፲፭ ቀንና፣ በሰባተኛው ቀን ኅዳር ፳፩ ቀን በጸሎተ ምኅላው በሚደረግበት ጊዜ ታቦቱ ከመንበሩ ተነሥቶ በዐውደ ምኅረት በቀሳውስት እንዲከብር ሆኖ፤ በሁሉም የምኅላው ቀናት ሥዕለ ማርያም፣ ወንጌልና መስቀል ወጥቶ በአራቱ መዐዝን ሥርዓተ ጸሎተ ምኅላው ከጸሎተ ወንጌል ጋር በየቀኑ በነግህና በሠርክ የሥራ ሰዓትን በማይነካ ሁኔታ እንዲፈጸም፤
፭ኛ. በየዕለቱ የሚነበቡት የወንጌል ክፍሎችን ስለ ሰላም፣ ስለንሥሓና ጸጸት፣ ስለ ፍቅርና አንድነት፣ ስለ በጎነትና መደማመጥ፣ ስለመሰማማትና ጥላቻን ስለማራቅ እንዲሆን፤
፮ኛ. በሰፊህና በአንቀዓድዎ፣ በሰጊድና በአስተብርኮ፣ ምኅላው ከደረሰና፣ ጸሎተ ወንጌል ደርሶ ዕለቱ ወንጌል ከተነበበ በኋላ በአንድነት የንሥሓ መዝሙር በመዘመር፣ ሕዝበ ክርስቲያን ስለሀገራቸውና ስለሰው ልጆ ደኅንነት እያሰቡ ወደቤታቸው እንዲሄዱ፤
፯ኛ. ከመጀመሪው ሳምንት በኋላ እስከ በዓለ ልደት ድረስ የሰርክ ምህላ ሳይቋረጥ መደበኛው ሥርዓተ ጾምና ጸሎት እንዲቀጥል፣ የቤተ ክርስቲያንን ታላቅነት፣ የአበውን ተቀባይነት በሚገለጽ፣ በቀጣይም ሁሉም ኦርቶዶክሳውያን በመንፈሳዊ ጽናት የሰላም ልዑካን ሆነው እንዲቀጥሉ በሚያደርግ ሁኔታ እንዲፈጸም፤
፰ኛ. አስቀድሞ የደረሰውንና፣ እየደረሰብን ያለው ችግር የጦርነትና የግጭት ብቻ ሳይሆን የረሀብ፣ የድርቅ፣ የኑሮ ውድነት፣ የመፈናቀልና የስደት ጭምር ስለሆነ ከጸሎትና ምኅላችን ጎን ለጎን መረዳዳትና መተዛዘን፣ ርኅራሄና መደጋገፍ አብሮ እንዲፈጸም፤
፱ኛ. ይኽንኑ መልእክት መላው ዓለም እንዲውቀው፣ በተለይም የኦሬንታል ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት በጸሎት እንዲያስቡን፣ የጸሎታችንና የምኅላችን መነሻ ምክንያቱ የሀገራችን ወቅታዊ ችግር ቢሆንም የምንጸልየው ለመላው ዓለም መሆኑ ተገልጾ በደብዳቤ እንዲላክ እንዲደረግ፣ በማለት ቅዱስ ሲኖዶስ ጥብቅ መመሪያ አስተላልፏል፡፡
እግዚአብሔር አምላካችን በእንባና በንሥሓ የምናቀርበውን ጸሎተ ምኅላችንን በምህረቱ ተቀብሎ ሀገራችንን ሰላም ያድርግልን፣ ሕዝባችንን ይጠብቅልን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
የኢትዮጵያ ኦርቶዶከስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
ቅዱስ ሲኖዶስ
