ወንጌሉ አገልግሎት | Wongelu Ministries
Open in Telegram
ጤናማ አብያተክርስቲያናትን ለክርስቶስ ክብር መፍጠር | Healthy Churches for the Glory of Christ Follow us on Instagram, Facebook, Tiktok, and Youtube @wongeluministries http://wongelu.com
Show more4 202
Subscribers
No data24 hours
+37 days
+17030 days
Posts Archive
ታሕሳስ 18 | ለሕዝቡ ተጨባጭ እውነታ ያደርገዋል
ኢየሱስ መካከለኛ የሆነበት ኪዳን ከቀድሞው እንደሚበልጥ ሁሉ፣ የተቀበለውም አገልግሎት ከእነርሱ አገልግሎት ይበልጣል፤ ይህም የተመሠረተው በተሻለ የተስፋ ቃል ላይ ነው። ዕብራውያን 8፥6 (አ.መ.ት)
ዕብራውያን 8፥6 እንደሚነግረን ክርስቶስ የአዲሱ ኪዳን አማላጅ ነው። ይህ ምን ማለት ነው? የእግዚአብሔር የተስፋ ቃል ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ በማይገረሰስ መልኩ በአዲሱ ኪዳን ደም (ሉቃስ 22፥20፤ ዕብራውያን 13፥20) አማካኝነት ለእኛ ተገዝቶልናል፣ ተጠብቆልናል።
ይህ ማለት እግዚአብሔር በአዲስ ኪዳን የተስፋ ቃሉ መሠረት ውስጣዊ የሆነ ሥር ነቀል ለውጥ በክርስቶስ መንፈስ በኩል አስገኝቶልናል ማለት ነው።
በተጨማሪም ደግሞ እግዚአብሔር ይህንን ውስጣዊ መለወጥ በእኛ ውስጥ የሚሠራው በእምነት ነው። ይህም እምነት እግዚአብሔር በክርስቶስ ስለ እኛ የሠራውን እና የሆነውን ሁሉ በማመን የሚገኝ ነው።
አዲሱ ኪዳን በክርስቶስ ደም ተገዝቶ፣ በክርስቶስ መንፈስ ተግባራዊ እንዲሆን ተደርጎ፣ በክርስቶስ ላይ ባለን እምነት ደግሞ ወደ እኛ ይተላለፋል።
ክርስቶስ የአዲሱ ኪዳን አማላጅ ሆኖ ሲሠራ ለመመልከት ወሳኙ ቦታ ዕብራውያን 13፥20-21 ነው፦
“በዘላለም ኪዳን ደም ለበጎች ትልቅ እረኛ የሆነውን ጌታችንን ኢየሱስን ከሙታን ያወጣው የሰላም አምላክ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በፊቱ ደስ የሚያሰኘውን በእናንተ እያደረገ፥ ፈቃዱን ታደርጉ ዘንድ በመልካም ሥራ ሁሉ ፍጹማን ያድርጋችሁ፤ ለእርሱ እስከ ዘላለም ድረስ ክብር ይሁን፤ አሜን።”
“…በፊቱ ደስ የሚያሰኘውን በእናንተ እያደረገ…” የሚሉት ቃላት የሚያብራሩት እግዚአብሔር ከአዲሱ ኪዳን ጋር በተስማማ መልኩ ሕጉን በልባችን ሲጽፍ ምን እንደሚፈጠር ነው። “በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል” የሚሉት ቃላት ደግሞ የሚያብራሩት የዚህ አስገራሚ የሉዓላዊ ጸጋ ሥራ አማላጅ ኢየሱስ መሆኑን ነው።
ስለዚህም የገና ዋና ትርጉም እግዚአብሔር ጥላውን በትክክለኛው ነገር መተካቱ ብቻ ሳይሆን፣ ያንን ትክክለኛ ነገር ወስዶ ለሕዝቡ ተጨባጭ እውነት ማድረጉም ጭምር ነው። በልባችን ላይ ይጽፈዋል። የዘለዓለም ሕይወትን እና መለወጥን የገና ስጦታ አድርጎ ሲሰጠን እንዲያው እንደታሸገ በራሳችን አቅም እንድናነሣው ከገና ዛፉ ሥር አይደለም ያስቀመጠው። አንስቶ በልባችሁ እና በአእምሯችሁ ካጸናው በኋላ የእግዚአብሔር ልጅ መሆናችሁን የሚያረጋግጥላችሁ ማኅተም ይሰጣችኋል።
Telegram | YouTube | Facebook | Instagram | TikTok | Website
#ዛሬ
ታሕሳስ 17 | የመጨረሻው እውነታ ተገልጧል
እንግዲህ የምንናገረው ዋናው ነገር ይህ ነው፤ በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፤ እርሱም በሰው ሳይሆን በጌታ በተተከለችው፣ እውነተኛ ድንኳን በሆነችው ቤተ መቅደስ አገልጋይ ነው … እነርሱ ያገለገሉት በሰማይ ላለችው መቅደስ ምሳሌና ጥላ በሆነችው ውስጥ ነው፤ ሙሴ ድንኳኒቱን ለመሥራት በተነሣ ጊዜ፣ “በተራራው ላይ በተገለጠልህ ምሳሌ መሠረት ሁሉን ነገር እንድታደርግ ተጠንቀቅ” የሚል ትእዛዝ የተሰጠው በዚህ ምክንያት ነበር። ዕብራውያን 8፥1-2፣ 5 (አ.መ.ት)
ከዚህ በፊት አይተነው ነበረ፤ ተጨማሪ ደግሞ አለ። ገና ማለት ጥላውን በዋናው አካል መተካት ማለት ነው።
ዕብራውያን 8፥1-2፣ 5 የመደምደሚያ ዐይነት ዓረፍተ ነገር ነው። ዋነው ነጥብ በእኛ እና በእግዚአብሔር መካከል ገብቶ ከእግዚአብሔር ጋር የሚያስታርቀን እና የሚጸልይልን ሊቀ ካህናት በብሉይ ኪዳን ዘመን እንደነበሩት ደካማ፣ ኀጢአተኛ፣ ለሞት የተገዙ ሊቀ ካህናት አይደለም። የእግዚአብሔር ልጅ የሆነ፣ ብርቱ፣ ኀጢአት የሌለበት፣ እና ሊጠፋ የማይችል ሕይወት ያለው ነው።
ይህ ብቻ አይደለም፤ የሚያገለግለው ምድራዊ በሆነ፣ በቦታ እና በስፋት በታጠረ፣ በሚያረጅ እና ተባይ በሚያጠቃው፣ በሚበሰብስ እና በሚቃጠል፣ በሚቀደድ እና በሚሰረቅ የመገናኛ ድንኳን አይደለም። ክርስቶስ ስለ እኛ የሚያገለግለው በሰው ሳይሆን በጌታ በተተከለች እውነተኛ ድንኳን እንደሆነ ዕብራውያን 8፥2 ይነግረናል። ይህ ጥላው አይደለም። በመንግሥተ ሰማይ ያለው ዋነው ነገር ነው። በሲና ተራራ ላይ ሙሴ እንዲገለብጥ የተነገረው ጥላ የሚመነጨው ከዚህ ከዋናው አካል ነው።
ዕብራውያን 8፥1 በሚነግረን መሠረት ከጥላው የሚበልጠው እውነታ የሚነግረን ሌላ አስደናቂ ነገር የኛ ሊቀ ካህናት በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ መሆኑ ነው። አንድም የብሉይ ኪዳን ሊቀ ካህናት ይህንን ከቶ ሊናገር አይችልም።
ኢየሱስ በቀጥታ ከእግዚአብሔር አብ ጋር ይነጋገራል። በእርሱ ዘንድ የከበረ ቦታ አለው። በእግዚአብሔር የተወደደ እና እጅግ የተከበረ ነው። ሁልጊዜ ከእግዚአብሔር ጋር ነው። ይህ እውነታ እንደ በፊቶቹ መጋረጃዎች፣ ሳህኖች፣ ጠረጴዛዎች፣ ሻማዎች፣ መጎናጸፊያዎች፣ ዘርፎች፣ በጎች፣ ፍየሎች፣ እና ርግቦች አይደለም። ይህ የመጨረሻው እና ጥላው ሲጠቁምለት የነበረው እውነታ ነው። እግዚአብሔር አብ እና ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ በፍቅር እና በፍጹም ቅድስና ሆነው ለእኛ የዘለዓለም ደኅንነት አብረው የሚሠሩት ታላቅ ሥራ!
ዋናውና የመጨረሻው እውነታ የሥላሴ አካላት በሕብረት ሆነው የእነርሱ የሆነውን ንግሥና፣ ቅድስና፣ ፍቅር፣ ፍትሕ፣ መልካምነት፣ እና እውነት በዳኑት ሕዝቦች እንዲታይ ማድረጋቸው ነው።
Telegram | YouTube | Facebook | Instagram | TikTok | Website
#ለዛሬ
ታሕሳስ 16 | ጥላዎቹን መተካት
እንግዲህ የምንናገረው ዋናው ነገር ይህ ነው፤ በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፤ እርሱም በሰው ሳይሆን በጌታ በተተከለችው፣ እውነተኛ ድንኳን በሆነችው ቤተ መቅደስ አገልጋይ ነው። ዕብራውያን 8፥1-2 (አ.መ.ት)
የዕብራውያን መጽሐፍ ዋና ነጥብ፣ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ኢየሱስ ወደ ምድር የመጣው የመጨረሻውና ምርጡ ሊቀ ካህናት በመሆን ምድራዊውን የሊቀ ካህናት አገልግሎት ለመፈጸም ብቻ አለመሆኑን ማሳየት ነው። ይልቁኑም፤ ያንን አሠራር ራሱ ፈጽሞ በቃ ሊል፣ ትኩረታችንንም ሁሉ ወደ ራሱ ሊያዞር፣ እና በቀራንዮ የመጨረሻው መሥዋዕታችን በመሆን የጀመረውን አገልግሎቱን በመንግሥተ ሰማይ የመጨረሻው ሊቀ ካህናታችን በመሆን ሊፈጽም እንደሆነ ማብሰር ነው።
የብሉይ ኪዳን መገናኛ ድንኳን፣ ካህናት፣ እና መሥዋዕት ሁሉ ለሚመጣው እውነታ ጥላዎች ነበሩ። አሁን ፍጹም የሆነው እውነታ መጥቷል፤ እነርሱም አልፈዋል።
ለልጆች እና ልጆች ለነበሩ ሁሉ የሚሆን የገና በዓል ምሳሌ ልስጣችሁ። ከእናታችሁ ጋር የገበያ አዳራሽ ሄዳችሁ ድንገት ሳታስቡት ብትጠፋፉ ብላችሁ አስቡ። በፍርሀት እና ድንጋጤ ሆናችሁ የምትሄዱበት ጠፍቷችሁ ማልቀስ ልትጀምሩ ስትሉ፣ ከግድግዳው ጀርባ የእናታችሁን የሚመስል ጥላ ድንገት መሬቱ ላይ ብታዩ በቅጽበት ተስፋ ታደርጋላችሁ። ግን የቱ ይሻላል? ጥላ በማየት የሚሰነቅ ተስፋ፣ ወይስ ራሷ እናታችሁ ከተሸፈነችበት ብቅ ስትል ያለው ስሜት?
ኢየሱስ ሊቀ ካህናታችን ሊሆን ሲመጣ ያለውም ስሜት ልክ እንዲሁ ነው። የገና በዓል ማለት ይህ ነው። ገና ማለት ጥላ የነበረው ሥርዓት በትክክለኛው ማንነት ሲተካ ማለት ነው። እናቱ የጠፋችበት ሕፃን ከተከለለችበት ግድግዳ ብቅ ስትል የሚሰማው የእፎይታ እና የደስታ ስሜት።
(ኢየሱስ ብሉይ ኪዳንን እንዴት እንደተካው ተጨማሪ ለማንበብ፣ በዚህ መጽሐፍ መጨረሻ ላይ ያለውን ዐባሪ ይመልከቱ።)
Telegram | YouTube | Facebook | Instagram | TikTok | Website
#ለዛሬ
ታሕሳስ Daily Devotionals (16-30)..................................................... ታሕሳስ 16 | ጥላዎቹን መተካት ታሕሳስ 17 | የመጨረሻው እውነታ ተገልጧል ታሕሳስ 18 | ለሕዝቡ ተጨባጭ እውነታ ያደርገዋል ታሕሳስ 19 | ሕይወት እና ሞት በገና በዓል ታሕሳስ 20 | ስኬታማው የእግዚአብሔር ውድቀት ታሕሳስ 21 | ሊታሰብ የሚችለው ታላቁ መዳን ታሕሳስ 22 | ለሚሲዮናዊነት ሥራ የሚውለው የገና ሞዴል ታሕሳስ 23 | ገና ለነፃነት ነው ታሕሳስ 24 | በገና የሚገኘው አንድነት ታሕሳስ 25 | "በዘመናት የሸመገለው" መወለድ ታሕሳስ 26 | ታምኑ ዘንድ ታሕሳስ 27 | ወደር የሌለው የእግዚአብሔር ስጦታ ታሕሳስ 28 | የገና ሁለት ዓላማዎች ታሕሳስ 29 | ሦስት የገና ስጦታዎች ታሕሳስ 30 | የመከራ አምስት ዓላማዎች .....................................................
ታሕሳስ 15 | ኢየሱስ የመጣበት ምክንያት
ልጆቹ በሥጋና በደም እንደሚካፈሉ እርሱ ራሱ ደግሞ ያንኑ ተካፈለ፤ ይኸውም በሞት ላይ ኀይል ያለውን ዲያቢሎስን በሞቱ ኀይል እንዲደመስስ ነው፤ እንዲሁም በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ በሞት ፍርሀት ባርነት የታሰሩትን ነጻ እንዲያወጣ ነው። ዕብራውያን 2፥14-15 (አ.መ.ት)
ስለ ኢየሱስ መወለድ ከሚናገሩ ጥቅሶች መካከል፣ ዕብራውያን 2፥14-15ን ከሁሉም ይልቅ እወደዋለሁ ብዬ አስባለሁ። ምክንያቴ ደግሞ እንደዚህ ጥቅስ የኢየሱስን ምድራዊ ሕይወት አጀማመር እና አጨራረስ፣ ተሰግኦውን እና ስቅለቱን በአንድ ላይ አያይዞ የሚገልጽ ሌላ ጥቅስ ስለማላውቅ ነው። ኢየሱስ የመጣበት ዋነኛ ምክንያት ለመሞት እንደሆነ ከእነዚህ ሁለት ቁጥሮች በግልጽ እንረዳለን። አማኝ ላልሆኑ ጓደኞቻችን ወይም ቤተሰቦቻችን የገናን በዓል ምንነት በሒደት ለማስረዳት በጣም የሚጠቅም ጥቅስ ነው። ሐረጎቹን አንድ በአንድ እየነጠልን በዚህ መልኩ ልናብራራው እንችላለን፤
…ልጆቹ በሥጋና በደም እንደሚካፈሉ…
“ልጆቹ” የሚለው ቃል የተወሰደው ቀደም ብሎ ካለው ቁጥር (ዕብራውያን 2፥13) ሲሆን የሚወክለውም የመሲሑን መንፈሳዊ ልጆች ነው (ኢሳይያስ 8፥18፣ 53፥10ን ይመልከቱ)። የእግዚአብሔር ልጆችም ናቸው (ዮሐንስ 1፥12)። በሌላ አገላለጽ፣ እግዚአብሔር የልጆቹን መዳን ታሳቢ አድርጎ ነው ክርስቶስን የላከው ማለት ነው።
“እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ዓለሙን እንዲሁ ወድዷልና” (ዮሐንስ 3፥16) የሚለው እውነት እንደሆነ እናውቃለን። ግን ደግሞ ሌላው እውነታ እግዚአብሔር “የተበተኑትን የእግዚአብሔርን ልጆች በአንድነት” (ዮሐንስ 11፥52) ልዩ በሆነ መንገድ ለመሰብሰብ እንደነበር እናውቃለን። የእግዚአብሔር ዕቅድ ክርስቶስን ለዓለም ሊያቀርብ እና ለልጆቹ ደግሞ መዳናቸውን ሊፈጽም ነው (1ኛ ጢሞቲዎስ 4፥10ን ይመልከቱ)። ክርስቶስን በመቀበል የማደጎ ልጆች ልትሆኑ ትችላላችሁ (ዮሐንስ 1፥12)።
… እርሱ ራሱ ደግሞ ያንኑ [ሥጋና ደምን] ተካፈለ …
ይህ ማለት ክርስቶስ ሰው ሆኖ ወደ ምድር ከመምጣቱ በፊት በሕልውና ነበር ማለት ነው። ከእግዚአብሔር ጋር ነበር፤ እግዚአብሔር ነበር (ዮሐንስ 1፥1፤ ቆላስያስ 2፥9)። ነገር ግን ሥጋና ደምን ተካፈለ፣ አምላክነቱንም ላይ ሰውነትን ለበሰ። ፍጹም አምላክነቱን ሳይለቅ ፍጹም ሰው ሆነ። ከብዙ ነገር አንጻር ይህ አስደናቂ ሚስጥር ነው። ሆኖም ግን የእምነታችን ማዕከል እና የመጽሐፍ ቅዱስም አሰተምህሮ ነው።
… በሞቱ …
ይህ ነው የመጣበት ዓላማ። ለመሞት። በግልጽ የምናውቀው ነገር እንደ አምላክ ለኀጢአተኞች ሊሞት አይችልም። ነገር ግን እንደ ሰው ይችላል። ግቡ መሞት ነበር። ስለዚህም፤ ሰው ሆኖ መወለድ ነበረበት። የተወለደው ለመሞት ነበር። የገና በዓል ዋና ዓላማው የስቅለት በዓል ነበር። ብዙዎች ስለ ገና ትርጉም ዛሬ ሊሰሙት የሚገባው ሐቅ ይህ ነው።
… ይኸውም በሞት ላይ ኀይል ያለውን ዲያቢሎስን በሞቱ ኀይል እንዲደመስስ ነው …
ክርስቶስ በሞቱ የዲያቢሎስን ኀይል አድቅቋል። እንዴት? ኀጢአታችንን ሁሉ በመሸፈን። ይህ ማለት ሰይጣን እኛን በእግዚአብሔር ፊት ለመክሰስ አንዳች መሠረት የለውም ማለት ነው። “እግዚአብሔር የመረጣቸውን ማን ይከሳቸዋል? የሚያጸድቅ እግዚአብሔር ነው፥ የሚኰንንስ ማን ነው?” (ሮሜ 8፥33)። በምን መሠረት ነው የሚያጸድቀው? በክርስቶስ ደም ላይ (ሮሜ 5፥9)።
ሰይጣን በእኛ ላይ ሊጠቀመው የሚችለው ከፍተኛው መሳሪያ የራሳችንን ኀጢአት ነው። ኀጢአታችንን ደግሞ የኢየሱስ ሞት የሚሽርልን ከሆነ፣ ሰይጣን ያለው ዋነኛ መግደያ መሣሪያ ከእጁ ተነጥቋል ማለት ነው። ዳኛው በልጁ ሞት ምክንያት ነጻ ናችሁ ብሎ ክሱን ስለዘጋው ከሳሻችን እኛ ላይ ሞት ለማስፈረድ አንድም ክስ ሊያቀርብ አይችልም።
… እንዲሁም በሕይወት ዘመናቸው ሁሉ በሞት ፍርሀት ባርነት የታሰሩትን ነጻ እንዲያወጣ ነው።
ስለዚህ ከሞት ፍርሀት ነፃ ወጥተናል ማለት ነው። እግዚአብሔር አጽድቆናል። ሰይጣን ይህንን ውሳኔ ሊያስቀለብስ ፈጽሞ አይችልም። ዘላቂውና የመጨረሻው ደህንነታችን ደግሞ አሁን ላይ ላለው ሕይወታችን አፋጣኝ የሆነ ውጤት እንዲኖረው እግዚአብሔር ይፈልጋል። አሁን ላይ የተጋረጠብንን ባርነት እና የሞት ፍርሀት አስደሳቹ ፍጻሜ እንዲያስወግድልን ይሻል።
የመጨረሻው እና ዋነኛውን ጠላታችንን ሞትን የምንፈራው ካልሆነ፣ አንዳች የምንፈራው ነገር ሊኖር አይችልም ማለት ነው። ነጻ መሆን እንችላለን። ለደስታና ለሐሴት ነፃ፣ ሌሎችን ለመውደድና ለማገልገል ነጻ ልንሆን እንችላለን።
እግዚአብሔር የሰጠን የገና ስጦታ ምንኛ ታላቅ ነው!? እኛ ደግሞ ይህንን ስጦታ ለዓለም ሁሉ እንሰጣለን!
Telegram | YouTube | Facebook | Instagram | TikTok | Website
#ለዛሬ
ታሕሳስ 14 | ወርቅ፣ ከርቤ፣ እና ዕጣን
ኮከቡንም ባዩ ጊዜ በታላቅ ደስታ እጅግ ደስ አላቸው። ወደ ቤትም ገብተው ሕፃኑን ከእናቱ ከማርያም ጋር አዩት፥ ወድቀውም ሰገዱለት፥ ሣጥኖቻቸውንም ከፍተው እጅ መንሻ ወርቅና ዕጣን ከርቤም አቀረቡለት። (የማቴዎስ ወንጌል 2፥10-11)
እግዚአብሔር አንዳች ነገር እንደሚጎድለው በሰዎች እጅ አይገለገልም (ሐዋርያት ሥራ 17፥25)። የሰብዓ ሰገል ስጦታዎች የቀረቡለት እርዳታ ስለሚያሻው ወይም የሚጎድለው ነገር ስለነበር አይደለም። የሌላ አገር እንግዶች ወደ አንድ ንጉሥ ሲመጡ የእርዳታ ጥቅል ይዘው ቢመጡ የንጉሡን ክብር ያሳጣሉ።
አልያም ደግሞ እነዚህ ስጦታዎች በጉቦ መልክ የቀረቡ አልነበሩም። ዘዳግም 10፥17 ላይ በግልጽ የሚነግረን እግዚአብሔር መማለጃን የሚቀበል አምላክ አለመሆኑን ነው። ታዲያ ትርጉማቸው ምንድን ነው? እንዴት ነው አምልኮ የሚሆኑት?
ራሳቸውን ሙሉ በሙሉ ለቻሉ ባለጠጋ ሰዎች የሚሰጥ ስጦታ የሚያስተጋባው፣ ሰጪው ለሰዎቹ ያለውን ክብር እና አድናቆት ነው። በአንድ መልኩ ለክርስቶስ ስጦታ መስጠት ማለት እንደ መፆም ሊታይ ይችላል። መፆም ማለት አንድን ነገር በመተው ክርስቶስ ከዚያ ከምንተወው ነገር ይልቅ የላቀ ዋጋ እንዳለው ማሳየት ማለት ነው።
ለክርስቶስ እንዲህ ያለ ስጦታ ስትሰጡ፣ ስታሳድዱ የነበረው ደስታ እርሱ እንደሆነ ትናገራላችሁ (ማቴዎስ 2፥10ን ልብ በሉ፤ “ኮከቡንም ባዩ ጊዜ በታላቅ ደስታ እጅግ ደስ አላቸው”)። የማሳድደው ደስታ ከአንተ ጋር ነግጄ በማተርፈው ላይ ወይም የምቀበልህ ክፍያ ላይ የተመረኮዘ ከንቱ ተስፋ አይደለም። ወደ አንተ ስመጣ አንተኑ እንጂ ከአንተ የማገኛቸውን ነገሮች ፈልጌ አልመጣሁም። ይህን ፍላጎቴን ይበልጥ ለማቀጣጠል እና ለአንተ ለማሳየት ስል ደግሞ በእጄ ያሉ ነገሮችን አሳልፌ በመስጠት በአንተ የበለጠ ለመደሰት እተጋለሁ። ለአንተ የማያስፈልግህን እኔን ግን የሚያረካኝን ነገር አሳልፌ በመስጠት፣ ሀብቴ አንተ መሆንህን እና እነዚህ ነገሮች አለመሆናቸውን በሙሉ ልቤ አውጃለሁ።
እግዚአብሔርን በወርቅ፣ በከርቤ፣ እና በዕጣን ማምለክ ማለት ይህ ይመስለኛል። እነዚህም ሆኑ ሌሎች ለእግዚአብሔር ልንሰጥ የምናስባቸው ነገሮች ሁሉ አምልኮ ናቸው።
እግዚአብሔር በልባችን ውስጥ ለክርስቶስ ያለንን ፍላጎት ያቀጣጥልልን። ከልባችን በመነጨ ደስታ እንዲህ እንበል፤ “ጌታ ኢየሱስ፣ አንተ የእስራኤል ንጉሥ የሆንከው መሲሑ ነህ። ነገሥታት ሁሉ በፊትህ መጥተው ይሰግዳሉ። አንተ እንድትመለክ እግዚአብሔር ዓለምን ሁሉ ወደፈቀደበት ይመራል። ስለዚህም ምንም ዐይነት ተግዳሮት ቢያጋጥመኝ ሥልጣንህን በመቀበል፣ ክብርን ለአንተ በማስገባት፣ አንተ ብቻ ነህ ልቤን የምታረካልኝ በማለት ስጦታዎቼን በፊትህ አቀርባለሁ።”
Telegram | YouTube | Facebook | Instagram | TikTok | Website
#ለዛሬ
ታሕሳስ 13 | ለኢየሱስ ሁለት ዐይነት ተቃውሞዎች
"ንጉሡ ሄሮድስ ይህን በሰማ ጊዜ ታወከ፤ እንዲሁም መላዪቱ ኢየሩሳሌም አብራ ታወከች።"
የማቴዎስ ወንጌል 2፥3 (አ.መ.ት)
ኢየሱስን ሊያመልኩ የማይፈልጉ ሰዎች በእርሱ ይታወካሉ፤ ሊያመልኩት በወደዱ ላይ ደግሞ ተቃውሞ ያስነሣባቸዋል። ምናልባት የማቴዎስ ዋነኛ ነጥብ ይህ ሐሳብ ላይሆን ይችላል፤ ነገር ግን ታሪኩ ሲቀጥል ልናመልጠው የማንችለው ወሳኝ አንድምታ ነው።
በዚህ ታሪክ ውስጥ ኢየሱስን ማምለክ የማይፈልጉ ሁለት ዐይነት ሰዎች አሉ።
የመጀመሪያው ዐይነት ስለ ኢየሱስ ምንም ግድ የማይሰጣቸው እና ምንም የማያደርጉ ሰዎች ናቸው። ኢየሱስ በሕይወታቸው ምንም ሚና የለውም። የካህናት አለቆች እና ጻፎች ይህንን ቡድን በኢየሱስ ሕይወት መጀመሪያ ሰሞን ወክለው ይገኛሉ። ማቴዎስ 2፥4 እንዲህ ይላል፤ “[ሄሮድስም] የካህናትንም አለቆች የሕዝቡንም ጻፎች ሁሉ ሰብስቦ ክርስቶስ ወዴት እንዲወለድ ጠየቃቸው።” እነርሱም ነገሩት፤ ከዚያ ግድም ሳይሰጣቸው ወደተለመደው ኑሯቸው ተመለሱ። እነዚህ መሪዎች ከክስተቱ ግዝፈት እና ወሳኝነት አንፃር ሲታይ፣ በጉዳዩ ላይ ያላቸው ዝምታ እና ግድ የለሽነት ያስጨንቃል።
ከዚያ ደግሞ ማቴዎስ 2፥3 የሚለውን አስተውሉ፤ “ንጉሡ ሄሮድስ ይህን በሰማ ጊዜ ታወከ፤ እንዲሁም መላዪቱ ኢየሩሳሌም አብራ ታወከች” (አ.መ.ት)። በሌላ አነጋገር፣ መላው የኢየሩሳሌም ከተማ በመሲሕ መወለድ ወሬ ታምሶ ያለበት ሁኔታ ነው ያለው። በዚህ ሁሉ ውስጥ የካህናት አለቆች ዝምታ አስደንጋጭ ነው። ወደ ሰብዓ ሰገል ለመሄድ ለምን ጥረት አላደረጉም? ፍላጎቱም ሆነ ተነሣሽነቱ የላቸውም። የእግዚአብሔርን ልጅ የማግኘት እና የማምለክ ጥማት አይታይባቸውም።
ኢየሱስን ማምለክ የማይፈልጉት ሁለተኞቹ ዐይነት ሰዎች ደግሞ በኢየሱስ ጥልቅ የሆነ ሥጋት ያደረባቸው ሰዎች ናቸው። በዚህ ታሪክ ውስጥ ሄሮድስ ይህንን ጎራ ይወክላል። ሄሮድስ እጅግ ፈርቷል፤ ከፍርሃቱም ጥልቀት የተነሣ ይዋሻል፤ ያጭበረብራል፤ ከዚያም አልፎ ኢየሱስን ለማጥፋት ሲል የጅምላ ጭፍጨፋ ያውጃል።
ዛሬም ላይ እነዚህ ሁለት ዐይነት ተቃውሞዎች በክርስቶስ እና እርሱን በሚያመልኩት ሁሉ ላይ ይከሰታሉ። ግድ የለሽነት እና ጠላትነት። ከሁለቱም ጎራዎች እንደማትሰለፉ ከልቤ ተስፋ አደርጋለሁ።
ክርስቲያን ከሆናችሁ ደግሞ ይህ የገና በዓል መሲሑን መከተል እና ማምለክ ማለት ምን ማለት እንደሆነ እና ምንኛ ዋጋ እንደሚያስከፍል የምታብሰለስሉበት ወቅት እንዲሆንላችሁ እጓጓለሁ።
Telegram | YouTube | Facebook | Instagram | TikTok | Website
#ለዛሬ
ታሕሳስ 12 | የቤተ ልሔም ልዕለ-ተፈጥሯዊ ኮከብ (ቀን 8)
የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው? ኮከቡን በምሥራቅ አይተን ልንሰግድለት መጥተናልና። (የማቴዎስ ወንጌል 2፥2)
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተለያየ ቦታ የተከሰቱ አንዳንድ ክስተቶች እንዴት ተከሰቱ ብለን እንድንገረም ያደርጉናል። እንዴት ነው ይህ “ኮከብ” ሰብዐ ሰገልን ከምሥራቅ ወደ ኢየሩሳሌም እየመራ ያመጣቸው?
በርግጥ ኮከቡ እየመራቸው ወይም መንገድ እያሳያቸው ስለመምጣቸው የሚናገር ነገር የለም። ኮከብ በምሥራቅ አይተው ወደ ኢየሩሳሌም መጡ ብቻ ነው የሚለን (ማቴዎስ 2፥2)። እንዴትስ ነው ይህ ኮከብ ማቴዎስ 2፥9 ላይ እንደሚናገረው፣ ከፊታቸው እየሄደ ከኢየሩሳሌም ወደ ቤተ ልሔም ያለውን የስምንት ኪሎ ሜትር መንገድ የመራቸው? እንዴት ነው አንድ ኮከብ ህፃኑ ባለበት ላይ መጥቶ መቆምስ የቻለው?
መልሱ፥ አናውቅም ነው። ይህንን ጥያቄ ለመመለስ ከፕላኔቶች፣ ኮሜቶች፣ ወይም ተዓምራዊ ብርሃኖች መገጣጠም አኳያ የተለያዩ ጥረቶች ተደርገዋል። ሆኖም ግን በርግጥ የምናውቀው ነገር የለም። እናም በስተ መጨረሻ ምንም መንፈሳዊ ጥቅም በሌላቸው በእነዚህ ጊዜያዊ መላምቶች አእምሯችሁን እንዳታጨናንቁ ወይም እንዳትተክሉ ልመክራችሁ እወዳለሁ።
በዚህ ጉዳይ እናንተን ለማሳሰብ ስል በጅምላ መናገር ሊኖርብኝ ይችላል፤ ሆኖም ግን በእንደነዚህ ዐይነት – ማለትም – ከዋክብቱ እንዴት ሊመሯቸው እንደቻሉ፣ የቀይ ባህር እንዴት እንደተከፈለ፣ መና እንዴት እንደወረደ፣ ዮናስ በዓሣ ነባሪ ሆድ ውስጥ እንዴት እንዳደረ፣ ጨረቃ ወደ ደም እንዴት እንደምትቀየር እና በመሳሰሉት ነገሮች አእምሮአቸውን የሚያጨናንቁ ሰዎች፣ አብዛኛውን ጊዜ ዳር ላይ ላሉ ነገሮች ትኩረት መስጠት የሚወዱ ሰዎች ናቸው።
ታላላቅ እና ማዕከላዊ ለሆኑት የወንጌል እውነቶች ጥልቅ ፍቅር ሲኖራቸው አይታዩም። ስለ እግዚአብሔር ቅድስና፣ ስለ ኀጢአት አስከፊነት፣ ስለ ሰው አቅም አልባነት፣ ስለ ክርስቶስ ሞት፣ በእምነት ብቻ ስለሚገኘው ጽድቅ፣ ስለ መንፈስ ቅዱስ የመቀደስ ሥራ፣ ስለ ክርስቶስ በክብር መመለስ፣ እና ስለ መጨረሻው ፍርድ ግድ ሲላቸው ብዙም አይታዩም። ሁልጊዜ ልባቸውን የሚያነቃቃው እና በተመስጦ የሚያነቡት ርዕስ፣ ከዋናው መንገድ የወጣና የጎንዮሽ ጉዳይ ላይ የሚያተኩር መጽሐፍ ወይም አጭር ጽሑፍ ነው። በታላላቆቹ እና ማዕከላዊ በሆኑት የወንጌሉ እውነታዎች እምብዛም አይደነቁም።
ሆኖም ግን፣ በዚህ ኮከብ ዙሪያ ግልጽ የሆነው ነገር በራሱ ከሚያደርገው እና ከተለመደው ውጪ እያደረገ መሆኑ ነው። ይህ ኮከብ ሰብዓ ሰገል የእግዚአብሔርን ልጅ የሆነውን ያመልኩ ዘንድ እየመራቸው ይገኛል። መጽሐፍ ቅዱሳዊ በሆነው አረዳድ ደግሞ የከዋክብትን ፈቃድ የሚመራ አንድ አካል ብቻ ነው፤ እርሱም እግዚአብሔር ነው።
በመሆኑም ከዚህ የምንማረው ዋነኛ ነገር፣ አሕዛብ ክርስቶስን ያመልኩ ዘንድ እግዚአብሔር እየመራቸው መሆኑን ነው። ይህንንም እያደረገ ያለው ዓለም ዓቀፍ ተጽእኖን በመፍጠር እና ሥልጣኑን በመጠቀም ነው።
ማንም የማያውቃት አንዲት ድንግል ሴት በምትወልድበት ጊዜ የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ በተመሳሳይ ወቅት እና ሰዓት፣ እግዚአብሔር ጠቅላላውን የሮምን ግዛት በቆጠራ እንዲንቀሳቀስ እንዳደረገ ሉቃስ ያሳየናል። ማቴዎስ ደግሞ በሰማይ ያሉት ከዋክብት በምድር ያሉ ጥቂት የውጭ አገር ሰዎች ልጁን ያመልኩ ዘንድ እንዴት አድርገው ወደ ቤተ ልሔም እንደመሯቸው ይገልፅልናል።
ይህ የእግዚአብሔር አሠራር ነው። በዚያን ጊዜ ይህ እንዲሆን አድርጎ ነበር። አሁንም ደግሞ ይህንን ይሠራል። ትኩረቱ ሕዝቦች ላይ ነው። የእግዚአብሔር ፍላጎት ሁሉም ሕዝቦች ልጁን ያመልኩት ዘንድ ነው (ማቴዎስ 24፥14)።
የእግዚአብሔር ፈቃድ ለሥራ ባልደረቦቻችሁ፣ አብረዋችሁ ለሚማሩት፣ ለጎረቤቶቻችሁ፣ እና ለቤተሰቦቻችሁ ይህ ነው። ዮሐንስ 4፥23 ላይ እንደሚል፤ “ነገር ግን በእውነት የሚሰግዱ ለአብ በመንፈስና በእውነት የሚሰግዱበት ጊዜ ይመጣል አሁንም ሆኖአል፤ አብ ሊሰግዱለት እንደ እነዚህ ያሉትን ይሻልና።”
በማቴዎስ ወንጌል ጅማሮ ላይ፣ የ”ኑ እና እዩ” ድግምግሞሽ እናገኛለን። በወንጌሉ ፍፃሜ ላይ ግን ወደ “ሂዱ አና ንገሩ” ተቀይሮ እናገኘዋለን።
በዚህ ሁሉ መካከል የእግዚአብሔር ዓላማ አልተቀየረም። አሕዛብን ሁሉ ለልጁ አምልኮ የሚሰበስብበት ኀይሉም አልደከመም። ይህ ዓለም የተፈጠረው እና እስካሁንም የቆየው ክርስቶስ እንዲከብር፣ እንዲገንን፣ እና በሕዝብ ሁሉ እንዲመለክ ነው።
Telegram | YouTube | Facebook | Instagram | TikTok | Website
#ለዛሬ
በአምስቱ_የካልቪኒዝም_ነጥቦች_የማመን_ዐሥር_ውጤቶች_ten_results_of_believing_in_five.mp317.54 MB
ታሕሳስ 11 | የሰብዓ ሰገል መሲሕ (ቀን 7)
ኢየሱስም በይሁዳ ቤተ ልሔም በንጉሡ በሄሮድስ ዘመን በተወለደ ጊዜ፥ እነሆ፥ ሰብአ ሰገል፦ የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው? ኮከቡን በምሥራቅ አይተን ልንሰግድለት መጥተናልና እያሉ ከምሥራቅ ወደ ኢየሩሳሌም መጡ። (የማቴዎስ ወንጌል 2፥1-2)
ከሉቃስ በተለየ መልኩ ማቴዎስ ስለ እረኞቹ የበረት ጉብኝት አይነግረንም። ይልቁኑም አትኩሮቱን ከምሥራቅ በኩል ወደ መጡት አይሁዳዊ ያልሆኑ አሕዛብ (የውጭ ዜጎች) ላይ ያደርጋል።
ማቴዎስ በወንጌሉ መጀመሪያ እና መጨረሻ ላይ፣ ኢየሱስ ዓለም ዐቀፍ መሲሕ መሆኑን እና ሊያድን የመጣው አይሁድን ብቻ ሳይሆን ዓለምን ሁሉ እንደሆነም ያስረዳናል።
በዚህ ክፍል ውስጥ የመጀመሪያዎቹ አምላኪዎች የሆኑት የንጉሥ አስማተኞች ወይም ኮከብ ቆጣሪዎች ወይም ጠቢባን ከእስራኤል የመጡ ሳይሆኑ ከምሥራቅ አካባቢ፣ ምናልባትም ከባቢሎን ግዛት የመጡ አሕዛብ ናቸው። አሕዛብ በአይሁድ የብሉይ ኪዳን የመንፃት ሕግጋት መሠረት የረከሱ ሰዎች ነበሩ።
በማቴዎስ ወንጌል መጨረሻ የኢየሱስ የመጨረሻ ቃላት እኚህ ነበሩ፤ “ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጥቶኛል፤ ስለዚህ ሂዱና ሕዝቦችን ሁሉ በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” (ማቴዎስ 28፥18-19)።
ይህ እውነት አሕዛብ ለሆንን ለእኛ፣ በመሲሑ መደሰት የምንችልበትን በር ከመክፈቱ ባሻገር፣ ነገሥታት እና ሕዝቦች ሁሉ ወደ እርሱ የሚመጡለት የዓለም ገዢ እንደሚሆን በተደጋጋሚ የተተነበየለት መሲሑ መሆኑን ማረጋገጫ ሆኗል። ለምሳሌ፤ ኢሳይያስ 60፥3፦ “ሕዝቦች ወደ ብርሃንሽ፣ ነገሥታትም ወደ ንጋትሽ ጸዳል ይመጣሉ።”
በዚህም ማቴዎስ ኢየሱስ እውነተኛው መሲሕ ለመሆኑ ማስረጃ የጨመረ ሲሆን፣ ከዚህም ባለፈ ኢየሱስ ለእስራኤል ብቻ ሳይሆን ለዓለም ሁሉ የሚሆን እውነተኛ መሲሕ፣ ንጉሥ፣ እና የተስፋ ቃሉ ፍጻሜ መሆኑን በግልጽ ያሳየናል።
Telegram | YouTube | Facebook | Instagram | TikTok | Website
#ለዛሬ
ታሕሳስ 10 | እግዚአብሔር ለሚወዳቸው ሰዎች ሰላም ይሁን (ቀን 6)
“ይህ ምልክት ይሁናችሁ፤ ሕፃን ልጅ በጨርቅ ተጠቅልሎ በግርግም ተኝቶ ታገኛላችሁ።” ድንገትም ብዙ የሰማይ ሠራዊት ከመልአኩ ጋር ታዩ፤ እግዚአብሔርንም እያመሰገኑ፣ እንዲህ አሉ፤ “ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም፣ ሰላምም እርሱ ለሚወዳቸው ሰዎች በምድር ይሁን!”
የሉቃስ ወንጌል 2፥12-14 (አ.መ.ት)
ሰላም ለእነማን? በመላእክቱ ውዳሴ ውስጥ ጠንከር ያለ እውነታ አለ። እግዚአብሔር ለወደዳቸው ሰዎች ሰላም ይሁን። እርሱ ለሚደሰትባቸው ሰዎች ሰላም ይሁን። ነገር ግን ያለ እምነት እግዚአብሔርን ማስደሰት አይቻልም (ዕብራውያን 11፥6)። ስለዚህም የገና በዓል ለሁሉም ሰው ሰላምን ሊያመጣ አይችልም።
“ፍርዱም ይህ ነው” አለ ኢየሱስ፤ “ብርሃን ወደ ዓለም መጣ፤ ሰዎች ግን ሥራቸው ክፉ ስለነበረ፣ ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ወደዱ” (ዮሐንስ 3፥19)። ወይም ደግሞ በዕድሜ ያረጀው ስምዖን ሕፃኑን ኢየሱስን ሲመለከት የተናገረው፣ “እነሆ፥ የብዙዎች ልብ አሳብ ይገለጥ ዘንድ፥ ይህ በእስራኤል ላሉት ለብዙዎቹ ለመውደቃቸውና ለመነሣታቸው ለሚቃወሙትም ምልክት ተሾሞአል…”(ሉቃስ 2፥34-35)። ብዙዎች የገና በዓልን ሊቃወሙት እንደሚገባ ምልክት አድርገው ይመለከቱታል!
“የእርሱ ወደ ሆነው መጣ፥ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም። ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው” (ዮሐንስ 1፥11-12)። ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ብቻ ነበር እንደዚህ ያለው፦ “ሰላምን እተውላችኋለሁ፥ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም። ልባችሁ አይታወክ አይፍራም” (ዮሐንስ 14፥27)።
አእምሮን ሁሉ የሚያልፈውን የእግዚአብሔርን ሰላም ተቀብለው ሊደሰቱበት የሚችሉት፣ በነገር ሁሉ በጸሎት እና በምልጃ ከምስጋና ጋር ልመናቸውን ለእግዚአብሔር የሚያስታውቁት ናቸው (ፊልጵስዩስ 4፥6-7)።
የእግዚአብሔርን የሰላም ሀብት ካዝና መክፈቻ ቁልፉ፣ በእግዚአብሔር የተስፋ ቃል ላይ ያለ እምነት ነው። ስለዚህም ጳውሎስ ሲጸልይ እንዲህ ይላል፤ “የተስፋ አምላክም በመንፈስ ቅዱስ ኃይል በተስፋ እንድትበዙ በማመናችሁ ደስታንና ሰላምን ሁሉ ይሙላባችሁ” (ሮሜ 15፥13)። በዚህም መሠረት፣ የእግዚአብሔርን የተስፋ ቃል በማመናችን ደስታን፣ ሰላምንና ፍቅርን ስንሞላ፣ ያኔ እግዚአብሔር ይከብራል።
ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም፣ ሰላምም እርሱ ለሚወዳቸው ሰዎች በምድር ይሁን! ለሁሉም ሕዝብ፣ ነገድ፣ ወገን፣ እና ቋንቋ! ለሚያምኑ ሁሉ!
Telegram | YouTube | Facebook | Instagram | TikTok | Website
#ለዛሬ
Tahesas_10_እግዚአብሔር_ለሚወዳቸው_ሰዎች_ሰላም_ይሁን_Wongelu_Ministries.mp35.13 MB
