የልቤን ለእናንተ
Open in Telegram
እንኳን ወደ ቻናላችን በደህና መጡ! በዚህ ቻናል:- * አጫጭር ልቦለዶች * ረጅም ልቦለዶች *አጫጭር ታሪኮች *ግጥሞች * የጉዞ ማስታወሻዎች *እንዲሁም ኢትዮጵያዊነትን በሰፊው የሚዳስሱ ፅሁፎች! * መፅሐፍትን በpdf ስለተቀላቀሉን ከ❤ እናመሰግናለን!! t.me/yelbenlenante
Show more626
Subscribers
No data24 hours
No data7 days
No data30 days
Posts Archive
626
ከተማሩ ሰዎች ይልቅ በመከራ ያለፉ ሰዎችን አከብራለሁ
አልማዝ የሚሆነው የድንጋይ ከሰል ነው !
አልማዝ በተፈጥሮ መንገድ እንዴት እንደሚሰራ ልንገራችሁ። አልማዝ የሚሰራው HPHT በሚባል Process ነው። HPHT ማለት High Pressure High Temperature ማለት ነው። አንድ አልማዝ አልማዝ ከመሆኑ በፊት አራት ደራጃዎችን ማለፍ ይኖርበታል። አንደኛ ከምድር በታች ከ300 እስከ 600 ኪሎ ሜትር ዝቅ ብሎ መቀመጥ። ሁለተኛ ከፍተኛ ሙቀት መታደል፣ ከ1200 ዲግሪ ሴንቲ ግሬት ቃጠሎ ውስጥ መቀመጥ። ሶስተኛ ከፍተኛ ጭነት ማግኘት። አራተኛ ለረዥም ጊዜ ውስጥ በነዚህ ሁኔታ ውስጥ መቆየት ! እንግዲህ አንድን የድንጋይ ከሰል ወስዳችሁ ከምድር በታች 600 ኪሎ ሜትር ብታወርዱት፣ 1200 ዲግሬ ስንቲ ግሬት ቃጦሎ ውስጥ ብታኖሩት፣ በከፍተኛ ፕሬዠር ውስጥ ብታስቀምጡት እና ለረዥም ጊዚያት በዚህ ሁኔታ ውስጥ ብትተዉት። ከሱሉ አልማዝ ይሆናል ! ከሰሉ ወደ ዳይመንድ ይለወጣል።
አንዳንዶቻችሁ በህይወታችሁ ግራ ይገባችኋል፣ በጣም የሚወዳችሁ አምላካችሁ ከጓደኞቻችሁ በታች 600 ኪሎ ሜትር አውርዷችሁ ይሆናል። በማይገባችሁ ፈተና 1200 degree cent great ቃጠሎ ውስጥ አስቀምጧችሁ ፤ በማጣት፣ በመገለል፣ በመገፋት ለረዥም ጊዚያት እየፈተናችሁ "ምንድነው እየተካሄደ ያለው" ብላችሁ እስክትጠይቁ ድረስ ለአምስት አመት፣ ለአስር አመት ከሰው፣ ከወዳጅ፣ ከዘመድ፣ ከጓደኛ ዝቅ አድርጓችሁ ይሆናል። ....
"ምን ማለት ነው የሚወደኝ አምላክ ይሄን የሚፈቅደው" ስትሉ .... አልማዝ አድርጎ ሊሰራችሁ፣ ውብ አድርጎ፣ ሊሰራችሁ፣ የምታበሩ አድርጎ ሊያበጃችሁ፣ እንቁ፣ ዳይመንድ፣ አልማዝ ሊያደርጋችሁ ስላሰበ ነው !
አልማዝ ሰባት ባህሪዎች አሉት። አንደኛ ጠንካራ ነው። ወስዳችሁ በድንጋይ ቀጥቅጡት አይሰበርም። በሰይፍ ምቱት አይሰነጠቅም። በመጋዝ ገዝግዙት አይቆረጥም። በአልመዝ ግን ብረት ይቆረጣል፣ በአልማዝ ግን ሰይፍ ይቆረጣል። በአልማዝ ግን ድንጋይ ይፈርሳል። አልማዝ የሚቆረጠው በሌላ አልማዝ ነው። ሁለተኛ የአልማዝ ባህሪ ልንገራችሁ። ከፍተኛ የማንጸባረቅ ባህሪ አለው። refractive index ይባላል። የተቀበለውን ብርሃን መልሶ የማብራት ባህሪ አለው። ያንጸባርቃል። ሶስተኛው የአልማዝ ባህሪ የተቀበለውን የጸሐይ ብርሃን፣ ነጩን ብርሃን ወደ ተለያዩ በርካታ ቀለማት የመበተን ችሎታ አለው። አራተኛ የአልማዝ ባህሪ ልንገራችሁ። እጅግ በጣም ንጹህ ነው። አልማዝ የሚታወቀው በነጹህነቱ ነው። አምስተኛ የአልማዝ ባህሪ ልንገራችሁ። አልማዝ በእሳት አይቃጠልም። አንድ ቤት ውስጥ አልማዝ አለ እንበል ያ አልማዝ ያለበት ቤት ሙሉ ለሙሉ ቢቃጠል አልማዙ ምንም አይሆንም። ምንም። በነበረው ቅርጹ፣ በነበረው ንጽህናው እናገኘዋለን። የሚያስገርመኝን ስድስተኛውን የአልማዝን ባህሪ ልንገራችሁ። ወርቅ ላይ አሲድ ድፉበት ወርቁ ይበላሻል። አልማዝ ላይ አሲድ አፍስሱበት ምንም አይሆንም። አይበላሽም። የመጨረሻው እና ሰባተኛው የአልማዝ ባህሪ በጣም ውድ ነው። በጣም ውድ ነው። የአውራጣትህን ራስ የምታክል ዳይመንድ አንድ ትልቅ ፎቅ ይገዛል። በጣም ውድ ነው።
ከጓደኞቻችሁ በታች 600 ኪሎ ሜትር ወርዳችሁ ፣ በ1200 ዲግሪ ሴንቲ ግሬት ስቃይ ውስጥ ያለፋችሁ፣ በፕሬዠር ውስጥ ለበርካታ አመታት ያለፋችሁ እናንተ አልማዝ ሁናችሁ የተሰራችሁ ሰዎች ናችሁ። ሰዎች ጠጠር ብትመስሏቸውም አልማዞች ናችሁ። ዋጋችሁ በጣም ውድ ነው። ... ከተማሩ ሰዎች ይልቅ፣ ብዙ ድግሪ ከተሳካላቸው ሰዎች ይልቅ፤ በመከራ ያለፉ ሰዎችን አከብራለሁ። ዋጋ የከፈሉ ሰዎችን አከብራለሁ። በስቃይ ውስጥ ያለፉ ሰዎችን አከብራለሁ። ምክንያቱም ዋጋቸው በጣም ውድ ነው።
መልካም ምሽት
(የዶክተር ወዳጀነህ ንግግርን ለንባብ እንዲመች አድርጋ አሳጥሬ አሰናደሁላችሁ 😃)
626
ግዜ /time/፦
ግዜ አከራክሯል ታላላቅ ሳይንቲስቶችንና የፍልስፍና ሠዎችን ፣አነደነ አይዛክ ኒውተን፣ አልበርት አንስታየንና ካርል ማርክስ ያሉትን። እነዚህ ታላላቅ ሠዎች ግዜን ገልፀውታል፣ በግዜ ተመራምረውበታል፣ ግዜ ቁልቁል ሯጭ መሆኑን አስገንዝበዋል። ለአይዛክ ኒውተን ግዜ ፍፁም ነው፣ ለአልበርት አንስታዬን ግዜ አንፃራዊ ነው፣ ለፈላስፋውና ለምጣኔ ሐብት ተንታኙ ካርል ማርክስ ግዜ ለካምፖንዎች ምርት መሸጫ አገልግሎትን አበርካች ነው።
ማንም ሠው ስለ ግዜ በትንሹም ቢሆን ሚስጥራቱን ማወቅ አለበት፣ አለማችን /the universe/ ከግዜ ጋር የተዋሀደና የተገናኘ በመሆኑና ስለ ግዜ የእውቀት ማነስ እውቀታችንን በጣም አናሳ ስለሚያደርገው።
ግዜ ለግዜ ዋጋ በሠጡ ታላላቅ ሠዎች አንዲህ ይታወቃል። " ግዜ እንደ ወንዝ ውኃ ተጓዥ ነው፣ ግዜ አቅጣጫ አለው ወደፊት እንጂ ወደኋላ አይጓዝም፣ ግዜ ወቅትንና ተራን ጠብቆ ተጓዥ ነው ቅደም ተከተል አለው፣ ግዜ ተቆጣሪ ነው ከአንድ ድርጊት ወደሌላ የሚሸጋገር።
እንደ አይዛክ ኒውተን ግዜ እያንዳንዱን ድርጊት የምንረዳበት በመቁጠሪያ የምናስቀምጠው ነው በቀናት፣ በወራት፣ በአመታት ከፋፍለን፣ ለምሳሌ አስር ሚሊዮን አመታት ፍፁም የሆነ ግዜን አመላካች ሲሆን፣ አሁን ልክ 7:30 ነው ስንልም ትክክለኛውን ግዜ ጠቋሚ ነው። ይህን አልበርት አንስታዬን በንፅፅር ያስቀምጣል። ለምሳሌ አሁን የምሳ ግዜ ነው ስንል ግዜን በምንመገበብት ወቅት አንፃር አስቀመጥነው ማለት ነው ፣ ያው ምሣ የምንበላበት የራሡ የሆነ ሠአት ስላለውና ያም እንዲሁ ግዜን አመላካች በመሆኑ።
አለማችን በግዜ አንፃር መች ተገኘች፣ ይህንን ጂኦሎጂስቶች /አለትን አጥኚ ሊቃውንት/ በአለቱ ለውጥ በመነሳት ያረጋግጣሉ።አለም ከተፈጠረች እጅግ ብዙ ዘመናትን አስቆጥራለች ይላሉ የአለት አጥኚ ሊቃውንት፣ በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ አመታትን አስቆጥራለች፣ ይህን ማረጋገጫቸውም የአለቶች ከአንዱ አይነት ወደሌላ የሚለወጥበትን የግዜ ብዛት በመተንተን ነው። ምሣሌዎችን መጥቀስ ይቻላል፦
በአለቶች ቅደም ተከተል /geologic time/ ግዜን ስንተነትን እንደሚከተለው ይቀመጣል በቅደም ተከተል ስናስቀምጣቸው በአምስት ዋና ዋና ግዜን ተንተራሽ ክፍልፋዮች ይቀመጣሉ፣ በአለት አለዋወጥ ቋንቋ ስናስቀምጣቸው eons,eras,periods, epochs, ages በመባል በቅደም ተከተል ይታወቃሉ። እያንዳንዱ ምን ያህል ግዜን አመላካች ይሆኑ? እስቲ እንያቸው፦
eon በቢሊዮኖች አመታት የሚመነዘር እጅግ በጣም የረዘመ ወቅት ነው ከ4.6 ቢሊየን እስከ 542 ሚሊዬን አመታትን በውስጡ የሚያካትት። ተከታዩ ERA በመቶ ሚሊዮኖች የታቀፈቱን አመታት የሚያጠቃልል ሲሆን period በአሥርት ሚሊዬን ተቆጣሪ አመታትን የሚጠቀልል ነው።
ሶስቱም እጅግ በጣም ብዙ አመታትን እንደሚያጠቃልሉ ነው የምንረዳው። ወደ ብሊዬኑ ሳንሄድ እስቲ አንድ ሚሊዬን አመታትን አስቡ ሚሊዬን አመት ማለትኮ 1000*1000 አመታትን የሚጠቀልል ነው የትዬሌለ መሥሎ የሚታዬን። የሠውን እድሜ በአንፃሩ ስናይ ሳንኖር የሞትን ያስመሥለናል አጅግ በጣም አናሳ በአሥርቶች የሚቆጠር በሁለት ዲጅቶች። 99አመትን አስቡ ያን የኖረ የታደለ አይደለምን ? 100ና ከዚያ በላይ እድሜን በእድሜ ለታደሉ እንተውና።
ይህን ግዜ ከምንከተለው እምነት እንዴት እናስታርቃለን? የቀን ቆጠራ በርግጥ አለም ከተፈጠረች ጀምሮ ነውን ? በትክክል። በእግዚአብሔር አምላክ ዘንድ ሺህ አመታት አንደ አንድ ሰኮንድ ስለሚቆጠር፣ ከሣይንሱ ያልራቁ የኃይማኖት ሊቃውንትም በዚህ ይስማማሉ። የግዜን ቀመር አሳምሮ የሚያውቀው ቀምሮ የፈጠረው ታላቁ ሣይንቲስት በመሆኑ እርሱ የደረሠበትን ደርሰን አፍ መክፈት አይቻልም። መመራመሩን ግን ስላልከለከለን ክብሩ የሠፋ ይሁን፣ ሶቅራጢስም ታላቁ ፈላስፋ ብዙ ከተመራመረ በኋላ የማይታወቀውን ማወቅ ባለመቻሉ በታላቅ አባባል አለማወቁን አስታወቀን እንዲህ በሚል "እኔ የማውቀው ምንም አለማወቄን ነው ።" What I know is that I know nothing." አወን ይህ ሃቅ ነው ሁላችንም የምናውቀው አለማወቃችንን በመሆኑ።
626
ዶክተር ዳኛቸው አሰፋ ይህንን ተናግረዋል ፦ " ፍልስፍና ያስፈልጋል ስትሉም ትፈላሰፋላችሁ ፤ ፍልስፍና አያስፈልግም ስትሉም ትፈላሰፋላችሁ " አርስቶትልን ጠቅሰው ። ፍልስፍና ምንድን ነው ? የሚለው ጥያቄ በፍልስፍና ውስጥ ወሳኝ ጥያቄ ነው ። ጂኦግራፊ ምንድን ነው የሚለው ጥያቄ የጂኦግራፊ ማዕከላዊ ጥያቄ አይደለም ። (በቀጥታ ስለ ጂኦግራፊ ያጠናል እንጂ )። ህግ ምንድነው የሚለው ጥያቄም የህግ ማዕከላዊ ጥያቄ አይደለም (ስለህግጋት ድንጋጌ ያጠናል እንጂ) ። ሌሎችም ሳይንሶች እንደዛው ። ፍልስፍና ምንድነው ስንል ግን የፍልስፍና መሠረታዊና ማዕከላዊ ጥያቄ ነው ። ምክኒያቱም ፍልስፍና የገዛ ስያሜዋን ጠረጴዛ ላይ አስቀምጣ ምትንቀሳቀስ ዲስፕሊን ስለሆነች ነው ። መጀመሪያ ፊሎሶፊያ ያሉት ግሪኮቹ ጥንታዊ እና አዲስ ትርጉም ነው ።ሁልጊዜ እየታደሰ ሚቀጥል ትርጓሜ ነው። የቃሉን አመጣጥ (ethnologyውን) ስናየው ፊሎ (love) ፍቅር ማለት ማለት ሲሆን ሶፊያ ደግሞ ጥበብ ማለት ነው ። እዚህ ጋር ማፍቀርን ምን አመጣው ? ለምን ( Desire ) መሻት አላሉትም ? መሻት የፈለግሽውን ነገር ስታገኚ ያበቃል ። ትረኪያለሽ ። ለምሳሌ ዛሬ ማታ ክትፎ / ላዛኛም ይችላል አግኝተሽ ከበላሽ በኋላ እዛ ላይ ያከትማል ፤ እርካታ ላይ ። ፍቅር ካልን ግን ማብቂያ የለሽ ጉዞ ነው ። እገሌን አፈቀርሁ ስትይ ማብቂያ የሌለው ጉዞ ውስጥ ነሽ ። ሶረን ኪየርኪጋርድ " እገሌን እወደው ነበር ፤ አሁን ጠላሁት አትበሉ ።መጀመሪያም አልወደዳችሁትም ።" ይላል ። ስለዚህ ፊሎሶፊያ Love of wisdom ስንል እርካታ ላይ የማይቆም ማለቂያ የሌለው የጥበብ ፍቅር ማለታቸው ነው ። እንግዲህ ሳርቴር ከመሞቱ በፊት አይኑ ጠፍቶ ነበር እንኳን መፅሐፍ ይነበብለት ነበር ። ሶክራቲስ ክሪይቶ ዲያሎግ ላይ ከነ ክሪቶ ጋር ሲመላለስ ይህንን ግቻ ፍልስፍናህን ተውና ክሱ ይነሳልህ ።አልያም ገንዘብ አሰባስበን እናስመልጥህ ቢሉት እስኪ ለምን ? አንድ ምክኒያት ስጡኝ አሳቤን እንድቀይር እያለ ሲከራከር ነበር ። የሰውየውን አካሄድ ስታይው የጤነኛ አይመስልም ምናልባት ወፈፍ አርጎት ይሆን አይታወቅም ። የኛው ፈላስፋ ዘርዓያዕቆብም ከእንፍራንዝ ናና እዚህ አክሱም በከፍተኛ የክህነት ማዕረግ አገልግል ቢሉት የለም! እዚያ መጥቼ የማለምንበትን ከማስተማር እዚሁ (ከፍልስፍናዬ ጋራ ) ምናምንቴ ሆኜ ብቀር እመርጣለሁ ብሏል ። አንዳዶች አሉ ሳያፈቅሩ ሙዚቃን አርትን ሳያጣጥሙ የሚያረጁ ። ምክንያቱም በቫይረሱ መለከፍ ያስፈልጋል ። በጥበብ መንፈስ መዳሰስ ይጠይቃል ። ሆኖም ማንም በጥቂቱም ከመፈላሰፍ አያመልጥም ። ፍልስፍና አልወድም የሚለው ሰው ለምንድንነው ብሎ ራሱን ቢጠይቅ መፈላሰፍ ጀመረ ማለት ነው ። እንዲሁም የትኛውም የትምህርት ጥናት ዘርፍ ሄዶ ሄዶ መጨረሻው ፍልስፍና ነው ። ለ40አመታት ታሪክ ሲያጠኑ ቆይተው በስተመጨረሻ ዞረው ይጠይቃሉ ።' ታሪክ ራሱ ምንድነው? ምን ማለት ነዉ ?' ብለው። በህግም በማቲማቲክስም PhD ሰራህ ማለት Doctor of philosophy ሆንክ ማለት ነው ።Phd ቃሉም ይህንን እሴት ለመጠበቅ ታስቦ የተፈጠረ ነው ። አላለቀም ...
626
" አራዳ ለመሆን ከፈለግክ ፣ ሁሉን አውቅ ለመሆን ካሰብክ ፣ በአንድ ነፍስ ብዙ ለመኖር ከወሰንክ ፣ ዓለማችንን በንስር ዓይን ለማየት ከቆረጥክ ፣ ወደድክም ጠላህ መፃህፍትን ማንበብ አለብህ፤ ያላነበበ ሁሉ ድብን ያለ ፋራ ነው። ዓይኑ የሩቁን አይደለም ፣ የቅርቡንም አጥርቶ አያይም።"
መልሕቅ ገፅ 14
በዘነበ ወላ
t.me/yelbenlenante
626
"ትንሽ ቦታ"
በዚህ አመት:
ብንጣላ መታረቂያ:
ብንታረቅ ለመጣያ:
ትንሽ ቦታ መጠለያ:
ትንሽ ቦታ መሰደጃ።
ምናለበት:
ለምናልባት ብንተውለት
ፍጹም መሆን ስለማንችል
ትንሽ ቦታ እንዋዋል
በልባችን ደግ በኩል።
ለአንጎላችን መላወሻ:
ትንሽ ቦታ እንተውለት
"ምናልባት" የምንልበት!!
ልክ እንደአምና ለዚህ አመት።
ብንጣላ መታረቂያ:
ብንታረቅ ለመጣያ:
ብንታሰር ይቅር ማያ
ይቅር ብንል መታሰሪያ
ትንሽ እንተው ባዶ ቦታ
ጥግ ድረስ የለም ስራ : ጥግ ድረስ የለም ፋታ።
በልባችን ደግ በኩል : እንፈልግ ባዶ ቦታ
የጷግሜ አይነት ትንሽ ቦታ።
ለዘመን መለዋወጫ ።
ገጣሚና ጋዜጠኛ ነብይ መኮንን
626
...ጭንላቴ ውስጥ ምንነቱን ያልተረዳሁት ሀሳብ ይራወጣል። አነባለሁ አይሰምርልኝም። እበላለሁ አልጠረቃም። እጠጣለሁ ጥሜን አልቆርጥም። ከሰዎች ጋር እወራለሁ ፤ እስቃለሁ ነገር ግን ሁሉም ነገር የእውነት አይደለም።
ልቤ ላይ እንደ መርግ የከበደኝ ስሜት አለ። በቻልኩና ጉጠት ፈልጌ ባወጣው ደስ ባለኝ።
በጣም የህመም ስሜት አለው ነገር ግን ውስጡ ደግሞ የተደበቀ ደስ የሚል ስሜትም ይንጸባረቅበታል።
አንዳንድ ጊዜ እናቴ ጉያ ስር ውሽቅ አላለሁ። ፀጉሮቼን ስትደባብሰኝ ከሚሰማኝ ስቃይ እፎይ የምል ይመስለኛል።
እጆቿን በፀጉሮቼ መሃል እያርመሰመሰች ሩቅ ስትመለከት ምናልባት ትላንትናዋን እያስታወሰች ይሆን ? ወጣትነቷን ፣ አፍላነቷን እላለሁ።
አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ብቻዬን ስሆን እርቃኔን መስታወት ፊት እሆንና ሁሉ ነገሬን እቃኛለሁ።
እንደጅብራ የተገተሩ ጡቶቼን ፣ ሴቴነት ውልብ ሲለኝ የምሰራው ፀጉሬ ፣ ቀጭን ሽንጥና ዳሌዬን ፣ የእግርና የእጅ ጣቶቼን ፣ ውፍረትና ቅጥነቴን በደንብ አያቸዋለሁ። በእርግጥ ከስንጥር መለስ የምል ይመስለኛል ።
እነዚህ ሁሉ ስሜት አይሰጡኝም።
አንዳንድ ጊዜ ልቤ ውስጥ ተሸጉሮ የሚያሰቃየኝን ስሜት ለመፃፍ እሞክራለሁ። ነገር ግን ጠብ የሚል ነገር አይኖርም። ወይም እፅፍ እፅፍና መልሼ ሳነበው ተራ ነገር ስሜት አልባ ሆኖ አገኘዋለሁ። ጥሩ እንቅልፍ ለመተኛት አእምሮ ሊደክመው ይገባል። አእምሮ ሲነቃ ስራውን በምንም ብታስተኛው አይተኛም።
ስሜትን መግለጽ አለመቻልን የመሰለ ህመም ይኖር ይሆን?
ወጣትነት አስቸጋሪ ነው። በተመጠነ አካሄድ ካለመራነው እርምጃችን ወደ አዘቅት ሊሆን ይችላል። ስለዚህ እያንዳንዱ ወጣት መጠነ ርዕይ ሊኖረው ይገባል።
የዚህ ሁሉ መንስኤ ግን አንተ ነህ አንተ !!
626
#የከሸፈ_ምኞት!!
"ከዳቦና ከውሃ ፣ ከአየርና ከብርሃን የበለጠ ፍቅር ያሻችኋል!!
ከፍቅር ወሮታ አትጠብቅ፣ ፍቅር በራሱ ለፍቅር ትልቅ ሽልማቱ ነው።" ከሚርዳድ
እነዚህ ሀሳቦች ፍቅር ምን ያህል ግዙፍና ሃያል መሆኑን በሚገባ ይመሰክራሉ!!
በእርግጥ እኔ ከፍቅር ወሮታን ብፈልግም አላገኝም ።
ነገር ግን ሳልም የነበረው !!
ንፁህ ልቤን በንፁህ ልብሽ አስተሳስሬ ያልኖርኩትን ልጅነት ያባከንኩትን ጊዜዬን ...ያላጣጣምኩትን የወላጆቼን ፍቅር ፤ ከአንቺ ...ከልጆችሽ ሳገኝ ዘመኔን በደስታ ስኖር ነበር የማልመው።
ከመጋባታችን በፊት በየመስኩ ስንሯሯጥ በሜዳ ሸንተረሩ የሀገሬን ዳር ድንበር በጋራ ሆነን ስንጓዘው .... በየ ሃይቁ ደርቻ ... በየ ጥቅጥቅ ጫካው ፣ ባማረው ባህላችን... በኢትዮጵያዊነታችን .... !!
በቤት ህይወታችን ማታ ማታ ውሱን ሰዓት አንቺ ግጥም እኔ ልቦለድ... እየጻፍን የአንቺን ገጥም እየሰማሁ
ለድርሰቴ ማጣፈጫ
ለህይወቴ መለወጫ
እንዳልሆን አልጫ
እሰማለሁ በብዙ ምርጫ
ፍቅራዊ ሰመመን ...የዜጎችን ህመም ... እውነትን ብቻ ብዙ ነገር እኔ እጻፍኩኝ ላነብልሽ ነበር ብዙ ህልሜ ....
ከገጥምና ከፅሁፎቻችን በኋላ አጭር ሰፊ ቀሚስ( ሰፊ ቲሸርት) ለብሰሽ ከስር በባዶ እግርሽ .... ፀጉሮችሽን በተን አርገሽ አልያም ጉንጉን ተሰርተሽ ... እኔ በእስፖርት የዳበረ ሰውነቴን ... ደረቴን ክፍቱን ትቼ ... በሱሪ ብቻ በባዶ እግር ሁነሽ ... ሁለት እጆችሽን ትከሻዬ ላይ አድርገሽ ..እኔ እጆቼን ወገብሽ ላይ ጠምጥሜ .... ደረቴ ከጡቶችሽ ተሰናስለው አንቺ በእቅፌ ውስጥ እኔ በእቅፍሽ ውስጥ እሳት እንደነካው ቅቤ አንችን በአንዳችን ውስጥ ስንቀልጥ ... ተንጠራርተሽ .....ከናፍሮቻችን የፍቅርን ትኩሳት ... የፍቅርን ዜማ የፍቅርን ወይን እየተቀባበሉ እንዲዘምሩ ... የፀጉርሽ ዘለላ ሰውነቴን ሲነካው በሰመመን እንድጠፋ .... ዐይኖቼን አንቺ ብቻ እኔድትታዪኝ ዐይኖቼን ስከፍት አንቺ ብቻ እንድትታዪኝ ....
ጠረንሽ ጠረኔን እንዲወርሰው ከላቦትሽ ጋር ላቦቴ እንዲዋሃድ... .....
እያለምኩ እያለምኩ እያለምኩ እያለምኩ እያለምኩ ህልሜን መኖር ሳልጀምር በመንገድ ቀረሁ ..... ስቃይና ህመም ወዳጆቼ ሆኑ ... ለቅሶ የዘወትር ስራዬ ሆነ ሰዎች እንባዬን እንዳያዩት ብቸኝነትን መረጥኩ .... ከሰዎች ጋር ለመገናኘት ዝናብን መጠበቅ ሳይኖርብኝ አይቀርም የዝናቡ ጠብታ በፍቅር ማጣት የሚፈሱ እንባዎቼን ለማጠብ .... በእንቅልፍ እጦት ያበጡ ዐይኖቼን ሊያነቃ .....ዝናብ አስፈላጊዬ ነው!!
ለአንድ ቀን አይደለም !!
ዘወትር እያደር እንደ ወይን እየጣፈጠን !!
አሁን !
ህልሜ የለም ስቃይ አርግዟል
ምኞቴ ከመጠን በላይ ሆኖ ...... ጸሎቴ በመሰማት ፈንታ "ምን ታመጣለህ?" በሚል የተቀየረ ይመስለኛል!!
ሰውነቴ በምኞት ጠውልጎ መከሽለል ቃጥቶታል!!
" እራስ ሲከብ እግር ባዶ" በብዙ ነገር እውነት እየሸመትኩ የሌለኝን ጸሐፌ ድርሰት አድርገሽኝ ወኔ አስታጥቀሽ የድርሰት መልዓክን ቁሞ እንዲያገለግለኝ እንዲታዘዘኝ አድርገሽ ግን ከህልሜ ውስጥ ጠፋሽ
ህልሜ በድን ሆኖ ቀረ!!!
እበላለሁ ...እሰጣለሁ... እጫወታለሁ ...እስቃለሁ ነገር ግን ....ህመሜ በርትቷል ላልጠገን ተሰብሬያለሁ .... ባለቅስ አይወጣልኝ ... ጫካ ብውል ...ብጮህ ኡኡኡኡኡኡ ብል ቅንጣት ንቅንቅ ወይ ፍንክች.....!!
መፍትሄው!
ነገሩን ለመርሳት .... ህመምን ለማድረቅ ብዙ አልኮል መጠጥ ሊያውም አረቄ ህእ ...ህቅ ..ህእ ..ብስስስስስ በቃ ብስብስ ጥንብዝ ማለት እራስን መርሳት ...ከቻሉ ቶሎ ለመገላገል ሲ.......ራ .......ጫ.......ት ....በቃ ሱስ ውስጥ መደበቅ ...ጥርስን አበልዞ.....ጠረንን አጥፍቶ መጥፋት በቃ !!
የታባቱ !!
✍አብርሃም ኑናቶ ❤
626
« ከበረደልሽ ድገሚኝ!! እ? በያ!» እያለ ለፀብ ይጋብዘኛል። ትቼው ወደመኪና ልገባ ስል እየተከተለ ሆነ ብሎ ይገፋፋኛል። «ይህችን ታህል ነው የተናደድሽብኝ? ለዝህችው ነው የጎፈላሽው?» ሲለኝ እንዴት ዥው ብዬ እንደዞርኩ አላውቀውም። እጄን ስሰነዝር በሚያስደነግጥ ፍጥነት በመዳፉ ቀለበው። ያልቆጠርኩትን ያህል ጊዜ ተከላክሎ አንዴ ነው አጓጉል ያገኘሁት። ዋጥ አደረጋት!! ቁጣዬ ረጭ ማለቱን ያወቅኩት ይሄኛው የድሮዋ ሜላት ማንነት መሆኑን መገንዘብ ስጀምር ነው።
«ደግ! አሁን ከሰከንሽ እየተጓዝን ስለኪዳን እናውጋ?» አለኝ የመታሁትን ጉንጭ እያሻሸ ወደመኪናው እየገባ
«ጉንጭህን አገላብጠህ ስለሰጠኸኝ እንዳምንህ ነው የምትጠብቀው?»
«እና ምን ይሁን ነው የምትይ? እዚሁ ቁመን ይምሽ? አንዱን አካሉን እዚሁ እንዲልኩልሽ ነው ያሰብሽ?» እየጮኸብኝኮ ነው። ከቃላት ሁላ በላይ ሆነብኝ እና አፌን ከፍቼ አፍጥጬ አየው ጀመር
«አንተ ግን የምርህን ነው? ካንተም ብሶ …….. » አልጨረስኩትም እየሮጥኩ መኪና ውስጥ ገባሁና ስልኬን አነሳሁ። አጎቴጋ ደወልኩ። ተከትሎኝ ገብቶ የማደርገውን በትኩረት ያያል።
«አጎቴ እናቴን አገናኘኝ እስቲ የሆነ ሳልጠይቃት የረሳሁት ነገር ትዝ አለኝ።» አልኩት
«እናቴ ? በቀደም <አምላክን በልመና አታድክሚ!!! የምትችውዪውን አድርጊና በተረፈው አመስግኚው!! ። ያመሰገንሽው አምላክ የጎደለውን ይሞላልሻል> ብለሽኝ ነበርኣ?»
«አዎ የእኔ አበባ ምነው?»
«አጎቴንም እንደዛው ስትዪው ሰምቻለሁኣ?»
«ሁሌምኮ የምለው ነገርኮ ነው ልጄ?» አለች ግራ እየገባት።
«የተለየ ትርጉም ነገር አለው እንዴ?»
«ኸረ ምንም ቅኔ የለውም ልጄ! ምን ጉድ ነው?»
«እንዲሁ ነው የሆነ ሚስጥር የያዘ አረፍተነገር ይመስል ውስጤ ተመላለሰ። ድንገት ሌላ መልዕክት ካለው ብዬ ነው።»
«በፍፁም! ሁሌም ሰዎች እጅ እግራቸውን አጣጥፈው በቀላሉ መስራት በሚችሉት ነገር ሁሉ ሳይቀር ፈጣሪን በልመና ሲያደክሙ እንደዛ እላለሁ። »
«እሺ በቃ እናቴ» ስልኩን ዘግቼ አስባለሁ። ምንም ሳይለኝ መኪናውን መንዳት ቀጠለ።
«እኔን አይደል የሚፈልጉት? እኔ ሄድላቸዋለሁ! እኔን የሚያደርጉትን ያድርጉና ወንድሜን ይለቁታል።» አልኩኝ ለራሴ ያሰብኩትን ድምፄን አውጥቼ እየተናገርኩት
«ህእ! አንቺን ቢፈልጉ እስከዛሬ ላንቺ የሚሆን አንድ ጥይት ጠፍቷቸው ይመስልሻል? ካንቺ በላይ የያዝሽባቸውን መረጃ ይፈልጉታል።» አለ <ቂል ነሽ እንዴ?> በሚል ለዛ
«ሊገድሉኝ ሞክረው የለ?»
«እኔን ከጠየቅሽኝ በፍፁም እነሱ አይመስሉኝም!!»
«እሺ ያለውን ቪዲዮ የምናገኝበት ፍንጭ ታውቃለህ? መቼም የማታውቀው ነገር የለም!» አልኩት አፍንጫዬን እየነፋሁ።
«አላውቅም!!» አለኝ በመድከም አይነት።
«ስለዚህ እሄዳለሁ። አትከተለኝም። እውነቱን እነግራቸዋለሁ።» አልኩኝ ፍርጥም ብዬ
«የማይደረገውን!!» አለ ኮስተር ብሎ
............ አልጨረስንም ..........
ውብ ቀን ውብኛ ዋሉልኝማ ❤️❤️❤️
626
#የመኖር አካፋይ ፣ የመ ፤ ሞ ፣ ት ሲሶ ፣ መንገድ መሃል ………… (ክፍል አስራ አምስት)
(ሜሪ ፈለቀ)
በአትኩሮት ቢያየኝ እኮ በአፌ ልትወጣ የደረሰች ልቤ ስትደልቅ የለበስኩትን ሸሚዝ እያርገበገበችው ነው። በጀርባዬ የሚንቆረቆር ላቤ ለአፍታ ሌሎች ድምፆች ረጭ ቢሉ፤ ከማጅራቴ ወደ መቀመጫዬ ሲወርድ እንደ ዝናብ <ጠብ> ሲል ይሰማ ነበር። ስክሪኑ ላይ ያለውን የራሴን ምስል ሳየው ለመኮሳተር (የማላስታውሳትን የድሮዋን ሜላት ለመምሰል) በታገልኩ ቁጥር የዞረበት ፊት እያሳየሁ እንደሆነ ገባኝ። እጄን የያዘው የጎንጥ እጅ (ገባቶት ነው መሰለኝ) እንደመጭመቅ ሲያደርገኝ ትኩረቴን ከራሴ ፊት ላይ ወደ ኪዳን መለስኩ። መስሎኝ የነበረው ከወንበር ጋር ታስሮ እየተሰቃየ የማየው ወይም ያ ድምፁን የሰማሁት ሰውዬ ግንባሩ ላይ ሽጉጥ ደግኖበት አልያም ፊቱ በድብደባ ብዛት አባብጦ እና በደም ተለውሶ ነገር የማየው ነበር የመሰለኝ። የሆነው ግን ሌላ ነው። ኪዳንና ሰውየው እየተዝናኑ እንጂ አጋች እና ታጋች በማይመስል ሁኔታ አጠገብ ላጠገብ ተቀምጠዋል። ኪዳንን ለመለየት አልተቸገርኩም። የስልኬ ስክሪን ላይ ካለው መልኩ ምንም ለውጥ የለውም። አስቀድሞም በግራ መጋባት የጦዘውን ጭንቅላቴን ልክነት ያጠራጠረኝ የኪዳን መረጋጋት ነው። የሆነ ልክ ሰላም ልንባባል የተደዋወልን አስመስሎ
«ሜልዬ! ደህና ነሽልኝኣ?» አለ። ምንድነው እየሆነ ያለው? ኪዳን አይደለም ይሆን? ሰውየው ቅድም 12 ቦታ ቀነጣጥሼ እልክልሻለሁ ሲለኝ አልሰማም ማለት ነው? አሁንም የጎንጥ እጅ አነቃኝ።
«እኔ ደህና ነኝ! አንተስ?» ይባላል ቆይ? ከአጋቹ ጋር የተቀመጠ ሰው ደህና እንደማይሆን ግልፅ አይደል? እሱ ዝንቡ እንኳን እሽ እንዳልተባለ ሰው ዘና እያለ ታዲያ ምን ልበል? ምናልባት ለእኔ ብሎ ይሆን? እኔን ለማረጋጋት?
«አታስቢ ደህና ነኝ! ከልቤ ደህና ነኝ።» እያለ ምንም ያለመጎዳቱን ሊያሳየኝ ስልኩን እያራቀ ከተቀመጠበት ተነስቶ መላ አካላቱን አሳየኝ። እያባበለኝ ነገር መሰለኝ።
«እንዴት ነው የማላስበው? መዝናኛ ቦታ …… » እኔ ባልገባኝ ምክንያት ለእርሱ ግን ልክ በመሰለ እንድናገር አልፈለገም። ወዲያው አቋርጦኝ
«ሜል እንዲሁ ተጨነቂ ስልሽ ነው። እኔኮ ደህና ነኝ አልኩሽ። » ሲለኝ ጎንጥ ምን እንዳናደደው ሳይገባኝ ተበሳጭቶ ጥርሱን ነክሶ እኔን ባልያዘው እጁ አየሩን በቦክስ ጠለዘው። እየሆነ ያለው ነገር አፍና ጭራው የጠፋኝ እኔን ብቻ ነው? እኔ ሳይገባኝ እሱ የገባው አብረን ከሰማነው የደህና ነኝ መልእክት ውጪ ውስጠ ወይራ አለው? « በኋላ እንገናኝ የለ? እስከዛ ደህና ሁኚልኝ! ደግሞ አምላክን በልመና አታድክሚ!!! የምትችውዪውን አድርጊና በተረፈው አመስግኚው። ያመሰገንሽው አምላክ የጎደለውን ይሞላልሻል።» አለኝ ጭራሽ። የድሮዋ ሜላት ፀሎተኛ እንዳልነበረች ጠፍቶት ነው? ይሄንኑ ዓረፍተ ነገር ግን ከዚህ በፊት የሆነ ሰው ብሎት ሰምቻለሁ!! የት ነው የሰማሁት?
እስካሁን ድምፁ ያልተሰማው ሰውዬ ስልኩን ተቀበለውና በአይኑ እንደመጥቀስ አድርጎኝ ዘጋው!! አፌን እንደከፈትኩ ስልኩ ላይ አፍጥጬ ቀረሁ።
«ይሄ የውሻ ልጅ አውቆታል!» አለ ጎንጥ። መኪና ውስጥ ሆነ እንጂ ሜዳ ላይ ቢሆን <ዘራፍ> የሚል ነው የሚመስለው።
«ምኑን?» አልኩኝ ከድንዛዜዬ ሳልወጣ
«እየቀረፅሽው እንደሆን !» ብሎ ስልኩን እንድሰጠው እጁን ዘረጋልኝ። ስሰጠው ስልኩ ስክሪኑ ቆልፎ ስለነበር እንድከፍትለት መልሶ ሰጠኝ። ያለኝን የምከውነው ምኑም ገብቶኝ አይደለም። ያለውም የገባኝ ነገር የለውም።
«ማን ነበርኩ? ከምን ጋር የተቆላለፈ ህይወት ነው የነበረኝ? የምን ቪዲዮ ነው የምወስድለት? ስልኬ ውስጥ ያለ ነገር ይሆን?»
«ህም! ስልክሽ ውስጥ ልታኖሪው አትችዪም!» ሲለኝ አፌን ከፍቼ ቀረሁ። ስለቪዲዮው ያውቃል!!
«ምን ይመስልሃል ቪዲዮው?»
«እሱን በምን አውቄው! ብቻ ቅሌቱን የተሸከመ ነገር ነው የሚሆን»
ድንዝዝ እንዳልኩ አይኔ ብቻ ሲንቀዋለል ስልኩ ላይ ቅድም የተጫናት ምልክት ስክሪኑን መቅጃ መሆኗን እና ሰውየው እንደመረጃ እንዳንይዝበት ኪዳንን ምንም የተለየ ምልክት እንዳይሰጥ አስጠንቅቆት እንደሆነ እርግጠኛ ሆኖ ከነገረኝ በኋላ እኔን ረስቶ የተቀዳውን ቪዲዮ እየደጋገመ ወደፊት ወደኋላ ቅርብ …. ራቅ እያደረገ ያያል። እኔ ደግሞ ዝም ብዬ እሱን አየዋለሁ።
«በስተመጨረሻ ልመና አታብዥ ያለው ነገር ያላስፈላጊ ቦታ የተዶለ አይመስልሽም? ላንቺ የሚያስታውስሽ ነገር አለ?» አለኝ አሁንም ከስክሪኑ አይኑን ሳይነቅል።
«የሆነ ሰው ሲለው የሰማው ይመስለኛል። አላውቅም!! ራሴም እለው የነበረ ነገር ይመስለኛል። ምንም መጨበጥ አልቻልኩም።» ስለው እንባዬ ዓይኔን ሞልቶታልኮ እሱ ግን አላየኝም። ቪዲዮውን ኪዳን ስለምስጋና ያነሳበት ጋር አቁሞ
«ተመልከች እዚህ!!» ብሎ ሰውየውን ጠቆመኝ « ልክ ኪዳን ሲናገር ፊቱ አንድ አፍታ ይቀየራል። ተመልከች! ያ ማለት ይህ መስመር እንዲናገር ከተፈቀደለት ውጪ ነው ማለት ነው! ሊገልጥልሽ የፈለገው አንድ መልእክት ቢኖረው ነው።»
«ጎንጥ?» አልኩት ፍስስ ባለ ድምፅ
«ወይ!» አለ አይኑን እዛው እንደሰነቀረ
«ማ ነ ህ? » አልኩት እንባዬ አብሮ ከቃላቱ ጋር ዱብ ዱብ እያለ። እዛ ነጥብ ላይ ጎንጥ ዘበኛዬ ብቻ እንዳልሆነ ገብቶኛል። የሚያስለቅሰኝ በትክክል ምን እንደሆነ እንጃ።
«ኸረ በመድሀንያለም?! » አለ ደንግጦ የሚያደርገው ጠፍቶት ። እጄን ሊይዘኝ እጁን ሲሰድ መንጭቄ ቀማሁት
«እንዳትነካኝ! ሁሉንም ነገር ታውቃለህ! ይሄን ሁሉ ጊዜ ስሰቃይ እያወቅክ ምንም እንደማያውቅ አብረህ ስታፋልገኝ ነበር። ሰውየው ያወራው ሁሉ ነገር ገብቶሃል። ንገረኝ አንተም የእነሱ ወገን ነህ? ምን ፈልገህ ነው?» እንባዬ ባይቆምልኝም ሰውነቴ ሲቆጣ ፣ ደሜ ሲሞቅ ይታወቀኛል።
«መድሀንያለም በሚያውቀው እንደሱ አይደለም!! አንች ያሰብሽውና የእኔ ድርጊት ለየቅል ነው!! ሀሳቤ ጠላትነት ከነበር ምን እጠብቅ ነበር? ከጠዋት እስከማታ እጀ ላይ አልነበርሽ?»
«አላውቅም! የሆነ የምትፈልገው ነገር ይኖራላ!!» ተነስቼ ከመኪናው ወረድኩ። ትንፋሽ እስኪያጥረኝ ድረስ ንዴቴ ያጨሰኝ ጀመር። የመኪናውን ጎማ በሃይል መጠለዜን ያወቅኩት የእግሬን አውራ ጣት ሲያመኝ ነው። የሆነ ውስጤ ተኝቶ የነበረ አውሬ የነቃ ይመስል የምቦጫጭቀው ነገር ፣ ቁጣዬን የምወጣበት ነገር ፈለግኩ። እሪሪሪ ብዬ መጮህም ፈለግኩ። የመኪናውን ኮፈን በቡጢ እየነረትኩ ማቆም እፈልጋለሁ ግን እጄን የምሰነዝርበት ቁጥር በጨመረ ልክ ሰውነቴ እየረገበ ፣ ቁጣዬ እየበረደ ስለተሰማኝ አላቆምኩም። ከመኪናው ወርዶ መምጣቱን ያወቅኩት አጠገቤ መጥቶ ሁለቱን እጄን ለቀም አድርጎ ሲያስቆመኝ ነው።
«አትንካኝ አልኩኮ!! » ብዬ ከመጮሄ እኩል በምን ቅፅበት እንደሰነዘርኩት ያልተቆጣጠርኩት ለቡጢ የተጨበጠ እጄ ጉንጩ ላይ አርፏል። ያደረግኩትን ሳውቅ ደንግጬ የመታሁበትን እጄን እንደበዓድ እጅ አየሁት። ከመኪናው ኮፈን ድብደባ ይሆን ከእርሱ ጉንጭ እጄ በልዟል። ወደኋላ ዞሮ አፉ ውስጥ የሞላውን ደም ከተፋ በኋላ ወደ እኔ እየዞረ በሱ ብሶ ይጮህ ጀመር
626
«እኔኮ ኪዳንን እንኳን ላልለየው እችላለሁ?» አልኩ አፌ ውስጥ ምራቄ ደርቆብኝ ትን የሚለኝ እየመሰለኝ። ስልኩ ጠርቶ እንዳይዘጋ እየተቻኮለ ስልክ ያልያዝኩበትን እጄን ቀለብ አድርጎ ጨብጦ ከቅድሙ በተረጋጋ ድምፅ
«ትለይዋለሽ ግድ የለም!» አለኝ። የድምፁ መርገብ ይሁን የያዘኝ እጁ ያረጋጋኝ መርበትበቴን ገትቼ የያዘኝን እጄን አስለቅቄ ስልኩን ካነሳሁ በኋላ እንዲይዘው መልሼ ሰጠሁት።
........ አልጨረስንም......
ለአዳርም ለውሎም ያልሆነ ሰዓት ሆነሳ ...... ዋሉልኝ ልበል እደሩልኝ? ብቻ አንደኛው ውብ ይሁንላችሁ❤️❤️❤️❤️
626
«ህም መች ሰው ባሰበበት ይውላል?» አለ ከንፈሩን ብቻ ሸሸት አድርጎ። እኔ አንድ ሀገር አውርቼ ከአምስት ቃል ያልዘለለ ነው የሚመልስልኝ። ያለማቋረጥ መለፍለፌ ለራሴ እንኳን እንግዳ አይነት ስሜት ሰጥቶኛል። መልሼ ይሄንንም ያንንም ሳወራ ራሴን አገኘዋለሁ እንጂ። ምናልባት ከእናቴ ጋር የነበረኝ ጊዜ፣ ወይ ደግሞ ያስታወስኩት የትውስታዬ ሽራፊ፣ ወይም ትውስታዬ የመመለስ ተስፋ እንዳለው ማወቄ፣ አልያም አጎቴ ያወራልኝ የህይወቴ ክፍል …… አላውቅም! አንዳቸው ወይም ሁሉም ተደምረው ግን የሆነ ስሄድ ከነበረው ቅልል ያለ ስሜት ስመለስ እንዲኖረኝ አድርገውኛል።
«ከመመታቴ በፊት ለመጨረሻ ጊዜ ያደረግኩት ምን ይሆን? ለመጨረሻ ያገኘሁት ሰው ማን ይሆን? ያስቀየምኩት ወይስ በጥሩ የሚያስታውሰኝ ሰው ይሆን?» ያልኩት እንዲመልስልኝ አልነበረም።
«የዚያን እለት ከቤት ወጥተሽ ብዙም ሳትቆዪ ነው የሆነው ነገር የሆነው። በመንገድሽ የገጠመሽ ካልነበረ ለመጨረሻ ያወራሽው እኔን ነው የሚሆን!» አለ ስሜቱን ለማንበብ በሚከብድ ፊት። ያልጠበቅኩት መልስ ሆኖ መሰለኝ ተስተካክዬ ተቀመጥኩ።
«ምንድነው ያወራሁህ? መጥፎ ነገር ነው? ጥሩ?»
«ያለፈውን ከኋላችን እንተወው ተባብለንም የለ?» መመለስ የማይፈልገው ነገር ሲሆን የሚያመልጥበት ዘዴው ነው።
«በናትህ? ለምንድነው ግን ያለፈውን ስጠይቅህ የምትሸሸው? ልቤ የሚነግረኝ ከነገርከኝ በላይ ብዙ የምታውቀውን ነገር እንደደበቅከኝ ነው ግን ዝም ብዬ እያመንኩህ ነው።» ….. ብዬ ጥርጣሬዬን ላስከትል ስንደረደር የሚቀጥለውን ለማስቆም በሚመስል
«ፀያፍ ነገር ነው!! እኔ አሁን የማልደግመውን ፀያፍ ነገር ብለሽኝ ነው የወጣሽ! እንደእውነቱስ አፍሽን ከፈትሽ ነው የሚባል።» አለ እንዲመልስልኝ ስላደረግኩት እየተናደደብኝ።
«እሺ በሙሉ ልቤ እንዳምንህ አስረዳኝ! እንደዛ ፀያፍ ነገር የምናገርህ ሴት ሆኜ እቤቴ ምን አቆየህ? ስራዬ ፣ እንጀራዬ ምናምን ብለህ ልትሸነግለኝ አትሞክር! እኔ የምከፍልህን ደመወዝ ብዙ እጥፍ ከፍሎ የሚያሰራህ ሰው አታጣም ባንተ ብዙ ችሎታ! ሲጀመር የአንድ ቤት ዘበኛ፣ መኪና መንዳት የሚችል፣ ሽጉጥ የታጠቀ ፣ ክብር ሀቅ እውነት እሴቶቹ የሆነ ሰው …… አፏን የምትከፍትበት ሴት ደጅ ምን ያደርጋል?»
«ውል የሌለው አድርገሽ አትቆጣጥሪውማ! ሹፍርና እሰራ እንደነበርኮ አውግቼሽ ነበር። ወታደር ቤት ስለነበርኩ መሳሪያውም አዲሴ አይደለም። ሽጉጡንም ያስታጠቅሽኝ አንቺው ነበርሽ! ይከው ነው!!» አለ
«አሁን ያልከው በሙሉ ለምን እኔጋ እንደቆየህ አያብራራም! እሺ ንገረኝ እስኪ የት ነው የተገናኘነው? ማለቴ ስራውን እንዴት አገኘኸው? ወይም እኔ እንዴት ቀጠርኩህ?»
ለማውራት አፉን ከመክፈቱ በፊት በረጅሙ ተነፈሰ። ግንባሩ ላይ ያሉት መስመሮች ብዛታቸው ጨመረ። ዞር ብሎ ሳያየኝ
«ሰው ነው ያገናኘን! አንቺ ጠባቂ እንደምትፈልጊ እኔ ስራ እንደሚያስፈልገኝ የሚያቅ ሰው!» አለ በድፍኑ። አጀማመሩ እስከነገ የማያልቅ ታሪክ ሊያወራኝ ነበርኮ የሚመስለው።
«በቃ!? ሰው?» ድምፄን ጨመርኩ።
«ቆይ እኔ የምጎዳሽ አለመሆኔን እንድታምኚ ምንድነው ማድረግ ያለብኝ?»
«እያወራን ካለነው ጋር ይሄ የሚያገናኘው ነገር የለም! ትጎዳኛለህ ብዬ ባስብማ አብሬህ አልገኝም!! አንተ መናገር ያልፈለግከው ወይም እየደበቅከኝ ያለ ነገር እንዳለ እየተሰማኝ ግን ምንም ሳትጠይቂ በጭፍኑ እመኚኝ ማለት አይዋጥልኝም።» አልመለሰልኝም። አሁንም በረዥሙ ተንፍሶ ዝም አለ። በዝምታችን ውስጥ ከራሴ ሳወራ ለካንስ ምንም ነገር ለእኔ የማስረዳት ግዴታም የለበትም። <የራስሽ ጉዳይ> ብሎ ጥሎኝ ቢሄድስ መብቱ አይደል? ያኔም ለምን አብሮኝ እንደቆየ አሁን ለምን አብሮኝ እንዳለ ምክንያቱን ማወቅ አልችልም። ስለእርሱ የማወቅ መብት እንዳለኝ እንዲሰማኝ ያደረገኝ ራሱ አይደል ግን?
ሀሳብ ሳዛቁል ስልኬ ጠራ። የማላውቀው ቁጥር ነው። ለምን እንደማደርገው ባላውቅም የማላውቀው ስልክ ሲደወል ጎንጥ አጠገቤ ካለ ድምፁን ስፒከር ላይ አደርገዋለሁ። ምናልባት የመጀመሪያ ቀን ስልኬ ሲከፈት ድንብርብሬ ወጥቶ ስንተባተብ እሱ ስልኩን ተቀብሎኝ ስላወራ እንደልምድ ወስጄው ይሆናል። አነስቼ ሀሎ አልኩ።
«እሺ ሜላት!! ሁልጊዜ ጀግና አይኮንም! አንድ ቀን አገኝሻለሁ ብዬሽ አልነበር?» ወፍራም ድርብ የወንድ ድምፅ ነው።
«ማን ልበል?»
«ማን እንደሆንኩማ አሳምረሽ ታውቂዋለሽ!! ዛሬውኑ እስከማታ ድረስ የምልሽን ታደርጊያለሽ!! ህም እመኚኝ ይሄ እንደሌላ ጊዜው ማስፈራሪያ አይደለም። ምንም አይነት ወጥመድ ከጀርባዬ ሸርባለሁ ብትዪ ወንድምሽን 12 ትንንሽ አድርጌ በየተራ እልክልሻለሁ። ……. » ጎንጥ መኪናዋን ሲጢጥ አድርጎ አቆማት። እየሆነ ያለው ነገር በቅጡ ሳይገባኝ ሰውየው ማውራቱን ቀጠለ « …… ልታናግሪው ከፈለግሽ አጠገቤ ነው። ቪዲዮ ላድርግልሽ ከፈለግሽ?» (እያላገጠብኝ ነው የሚያወራው) ይሄኔ ጎንጥ ከመኪናው ፊትለፊት ያለ ወረቀት አንስቶ ከኪሱ እስኪሪብቶ አውጥቶ የፃፈውን አሳየኝ። <ምንድነው የምትፈልገው? በይው።> ሰውየው ይሄን ሲሰማ እንደመደሰት አደረገው።
« የሰውን ስስ ጎን ማግኘት ደስ ሲል።አየሽ የምትሳሺለት ነገር ሲያዝብሽ እንዲህ ነው የሚያንገበግበው። ከገባሽ! አንደኛ ወለም ዘለም ሳትዪ የቪዲዮን ያሉሽን ቅጂዎች በሙሉ ካስቀመጥሽበት ሰብስበሽ ነይ የምልሽ ቦታ ይዘሽ ትመጫለሽ። ሁለተኛ አንቺን ማመን ስለማይቻል ማስተማመኛ እንዲሆነኝ እዚህ ከመጣሽ በኋላ በይ የምልሽን እያልሽ እንቀርፅሻለን። ይቅርታ እንግዲህ ባላምንሽ … ያለመታመን ልምድሽ አቻ ባይኖረው ነው።» እኔ እሱ የተናገረው ምኑም አልገባኝ እሱ ይገለፍጣል። ጎንጥ ፅፎ ያሳየኛል።
«እኮ ምንድነው እንድቀርፅልህ የምትፈልገው?»
«ቆቅ አልነበርሽ? ይህቺ ትጠፋሻለች? በማስፈራራት ያለፍሻቸውን እዚህም እዛም የሰራሻቸው ህገወጥ ነገሮች ሲሰበሰቡ እድሜ ልክ ዘብጥያ የምትበሰብሺበት ሆኖ አጊንቼዋለሁ። ብዙም እንዳትቸገሪ መረጃዎቹንም ሰብስቤልሻለሁ። አንቺ የሚጠበቅብሽ የሰራሻቸውን ወንጀሎች በመረጃ አስደግፈሽ አምነሽ ቃል መስጠት ነው። ከምታምኛቸው ውስጥ ፌክ የምስል ቅንብር እና መረጃ ሰርተሽ እኔን በማስፈራራት የግል ጥቅም ለማግኘት ያለመታከት መልፋትሽ ይካተትበታል። ያው እዝህችጋ ምንም ያህል የረቀ ሴራ ብትሰሪ እኔ ወደር የሌለኝ ለሀገሬ ታማኝ አገልጋይ መሆኔን አክለሽ ብትጠቅሽም አይከፋኝም። ሃሃሃሃሃ» እኔ ምኑም እየገባኝ ካለመሆኔ እየተነጋገሩ ያሉት ሰውየውና ጎንጥ ናቸው የሚመስሉት
«ኪዳንን አገናኘኝ? ማስረጃ እፈልጋለሁ።» ብሎ ጎንጥ የፃፈልኝን አነበብኩለት
«ምን ችግር። ቆዪማ ቪዲዮ ላድርገው?» ሲለኝ ጎንጥ ስልኩን ዘጋው እና እኔ ላይ አፈጠጠ።
«ወንድምሽን ስታዪው የተደናገጠ ሰው እንዳትመስዪ ፣ ድሮ የሚያውቋትን ሜላት መሆንሽን አሳምኛቸው። ምንም እንደማያውቅ ሰው አትምሰዪ ….. የማታውቂውን ነገር አትጠይቂ!! ምንም ቢፈጠር እንደማታስታውሺ እንዳትናገሪ ….. የምልሽን ብቻ አድርጊ!!» ብሎ በቁጣ እያስጠነቀቀኝ ስልኬን ተቀብሎኝ የሆነ ነገር እንደሚፈልግ ሰው ጣቱን ካመላለሰ በኋላ ከመጡለት ዝርዝሮች የሆነች ቀይ ምልክት ነገር ተጭኖ እየመለሰልኝ ስልኩ ጠራ። ድንብርብሬ ሲወጣ በሁለቱም እጆቹ ትከሻዬን በሁለቱም በኩል አጥብቆ እየያዘ « ታምኚኛለሽ?» ያለኝ ስለምን እንደሆነ ሳይገባንኝ ጭንቅላቴን ወደ ላይ ወደታች ናጥኩ!! «ተረጋጊና ያልኩሽን አድርጊ!!»
626
#የመኖር አካፋይ ፣ የመ ፤ ሞ ፣ ት ሲሶ ፣ መንገድ መሃል ………… (ክፍል አስራ አራት)
(ሜሪ ፈለቀ)
«ከዛ ሰውዬ ጋር አብሬው ተኛሁ? ምንድነው ያደረግኩት?» መልሱን ማናቸውም እንደማያውቁት እያወቅኩ ደጋግሜ እጠይቃቸዋለሁ። እነርሱም መልሱን ጠብቄ እንዳልጠየቅኳቸው ስለልገባቸው አይመልሱልኝም። ከዚህ ቀዬ ከወጣሁ በኋላ የተፈጠረውን ነገር ካወቀ ሊያውቅ የሚችለው ኪዳን ብቻ ነው።
እናቴን ካገኘሁ በኋላ ያለፈውን ራሴን የመፈለግ ውጥረቴ ትቶኝ ነበር። አጎቴ ታሪኬን ነግሮኝ ሲያበቃ እንደአዲስ ያቅበጠብጠኝ ጀመር። ምንድነው ያደረግኩት? ምን ዓይነት አቅል መሳት ላይ ደርሼ ነው ያን ሰውዬ ያገባሁት?
«እናቴ? ስለኪዳን የነገርኩሽን የምታስታውሺውን ሁሉ እስኪ ንገሪኝ! ከተመታሁኮ ሁለት ወር አለፈ። እንዴት አይፈልገኝም? እንዴት አይደውልልኝም?»
«እኔ እንጃ ልጄ! ብዙውን ያወራሽኝ ስለመውደድሽ ፤ ጎበዝ ተማሪ ሆኖ በማዕረግ ስለመመረቁ ፣ ፈረንጅ ፍቅረኛ እንዳለችው እና ሰርጉ ሀገሩ እንዲሆን ፈልጎ አንቺ እንቢ ማለትሽን …… እንዲህ እንዲህ ያለ ነገር ነው የነገርሽኝ እንጂ የምትገናኙበትን መንገድ አላውቅም ልጄ። ከመሞቴ በፊት ባየው ብዬሽ <በህይወት መኖርሽን አያውቅም። እንዴት እንደምነግረው እንጃ ግን እነግረዋለሁ> አልሽኝ።» እያለችኝ ሌላ የምታስታውሰው ነገር መኖሩን የጭንቅላቷን ጓዳ ትበረብራለች
«ለምን እንቢ አልኩት? ማለቴ ሰርጉን?»
«አንቺን ማጥቃት የፈለገ ሰው ሊያጠቃሽ የሚችልበት ብቸኛ መንገድ እሱ በመሆኑ አንድ ነገር እንደሚያደርጉብሽ ነው የነገርሽኝ። ሁኔታውን ልትነግሪኝ አልወደድሽም እንጂ ከዚህ በፊት በእሱ እንዳገኙሽ ነግረሽኛል።»
ድፍንፍን ያለ ነገር ሆነብኝ። ወደቤቴ መመለስ ፈለግኩ። ፍለጋዬን የት እንደምጀምር ባላውቅም እዛ የሆነ ፍንጭ አላጣም መሰለኝ። ያቺ መልእክት አስቀምጣ የነበረችው እመቤትስ? ያ የደወልንለት ሰውዬ ቃሊቲ እስር ቤት ናት ያላት እመቤት! ማን ያውቃል ለእሷ የሆነ ነገር ነግሬያት ይሆናል። ግን እስር ቤቱጋ ሄጄ በደፈናው እመቤትን ነው የምለው? ምናልባት አንድ ሀገር እመቤት የሚባል ሴት ይኖራል። አላውቅም ብቻ እዚህ ተቀምጬ ሀሳብ ከማመነዥክ መሞከሩ አይከፋም!
ምናልባት ደግሞ ያ ስልባቦት የመሰለ ዳዊት የሚሉት ፍቅረኛዬ! ለእርሱስ ምንም ልነግረው አልችልም ኸረ! ማን ያውቃል ግን? ግን እንዴት ባለ ዘዴ ነው ትውስታዬን ማጣቴን ሳልነግረው ስለኪዳን የሚያውቀው ነገር መኖሩን የማወጣጣው?
እናቴ የቀሯትን ቀናት እዛው መሆን መፈለጓን እኔ እንዳይከፋኝ በማባበል በማስፈቀድ ለዛ ስትጠይቀኝ ግራ ገባኝ። በሽታዋ የማህፀን ካንሰር ነው። ምንም ማድረግ እስከማይችሉበት ሰዓት ድረስ ሀኪሞች ብዙ ትሪትመንት ሞክረውላታል። ያገኘኋት ጊዜ ሀኪም ቤት ካልወሰድኩሽ ብዬ ስነዘንዛት
«ልጄ አንቺው እኮ ነሽ ስታሳክሚኝ የቆየሽው! ከሀገር ውጪ ወጥተሽ ካልታከምሽ ብለሽኝኮ ምንም ፋይዳ እንደሌለው ሀኪሞቹ ነግረውሽ ነው የተውሽው። አምላክ በታምሩ ይሄን ደስታ ቀምሰሽ ሙቺ ሲለኝ እንጂ እንዲህም መች ትቆያለች ተባልኩ?» ብላኝ ነበር። ሀኪሞቹ ከገመቱት ቀን በላይ መቆየቷ ተዓምር እንደሆነ ሁሉ ብትታከም ድጋሚ ተዓምር ሊፈጠር ይችል ይሆናል ብዬ ላሳምናት ብሞክርም <ደከመኝ> አለችኝ። ማረፍ ብቻ ነው የፈለገችው። መሞትን ሳትፈራው ቀርታ ይሁን ወይስ እንዳይታወቅባት ውጣው ለመሞት የተዘጋጀች ነው የምትመስለው። በመጣ ቀን <እንኳን ደህና መጣህ! ስጠብቅህ ነበር> ብላ የምትቀበለው።
«እሺ!» አልኳት እና ወደጎንጥ ዞሬ «አንተ ነገውኑ ባሻህ ሰዓት ተመለስ! እኔ እዚህ ከእናቴ ጋር እሆናለሁ! » አልኩት
«ማይደረገውን!! እኔ እዚህ መሆኔ ካልከበዳችሁ በቀር ወደየትም የመሄድ መሻት የለኝም!!» (አለ ወደአጎቴ እያየ)
«ኸረ ምን ከብደኸኝ? ባደረገውና እዚሁ በባጀህ! እኔማ የሚያነጋግረኝ አገኘሁ!» አለ አጎቴ።
ከመጣን ጀምሮ ጎንጥ ከዚህ በፊት የሚያውቀው ቤት እና ቤተሰብ ውስጥ የተቀላቀለ ነበር የሚመስለው። እጅጌውን ሰብሰብ አድርጎ እንጨት ለመፍለጥ ሰዓታት አልፈጀም። ሊወድቅ ያዘመመውን የከብቶቹን ቤት ያጋደለውን እንጨት እያስተካከለ ሲተክል በእንግድነት ውሎ አላደረም ነበር። ሱሪውን ሰብስቦ እንደቁምጣ አሳጥሮ የአጎቴን የጓሮ ማሳ ሲያርም …… የኖረበት …. የሚያውቀው እንደሆነ ያሳብቅበት ነበር። አጎቴ በእርሱ መገኘት ደስ መሰኘቱን ለማወቅ ብዙ ሂሳብ አያሰራም።
«እኔ እዚህ ምን እሆናለሁ? እዚህ ጠላት የለኝም ሲገባኝ። ዝምብዬ ነው የምፈራው እንጂ ምናልባትም ማንም እያደባብኝ አይደለም። የሚያስፈልግ ነገር ሲኖር ባይሆን ትመጣለህ።» አልኩት እናቴን ላገኛት የሄድኩ ቀን እንደዛ ተንበጭብጬ ምንም ያለመፈጠሩን እያሰብኩ።
«ህም!! ክፋት የከጀለ ልብ አይደለም እዝህች ሲኦል ከመውረድ የሚያግደው የለም!» አባባሉ ስለእርሱ ያለኝን ጥርጣሬ ቀሰቀሰብኝ። የሆነ ያልነገረኝ የሚያውቀው ነገርማ አለ።
«አይሆንም አንቺም እዚህ አትከርሚም!» አለች እናቴ ጠልቃ ገብታ « ….. በአካል ባልዳብሰው እንኳን የኪዳንን ድምፅ ሰምቼ አንዴ አውርቼው ባልፍ …… ይሄ ባይሆን እንኳን ለወንድምሽ ታስፈልጊዋለሽ። አግኝው!» አለችኝ አሁንም በልምምጧ። ልቤ መሃል ላይ ዋለለብኝ። እሺ የት ብዬ ነው የምፈልገው? እሱን ለማግኘት እኔ ስዳክር እናቴ ብታመልጠኝስ? ምን ያህል እንደሆነ የማላውቀውን የቀረንን ቀን ትቻት እንዴት ነው የምሄደው?
«የእኔ አበባ ? አትከፊብኝ! እዚህ አብረሽኝ ብትሆኝም ሞትን አታስመልጪኝም! ለእኔ አምላክ በእድሜዬ ማታ አንቺን መልሶልኝ ሀሴት ሰጥቶኛል። ወንድምሽን ባላገኘው እንኳን ደህና መሆኑን ማወቄ እረፍት ነው!! ስንት ቀኖች እና ስንት ለሊቶች <ልጆቼን ለየትኛው ጅብ ዳርጌያቸው ይሆን? ምን ዓይነት ህይወት እየኖሩ ይሆን? ትቻቸው ባልሄድ የተሻለ ህይወት ይሆንላቸው ነበር?> እያልኩ በፀፀት ነድጃለሁ መሰለሽ? ያንቺ እናት ስለሆንኩ እኔ እድለኛ ነኝ። ብቻ አንድ ነገር ቃል ጊቢልኝ! ያለፍሽውን ብታስታውሺም ባታስታውሺም ወደቀደመው ህይወትሽ ላትመለሺ ቃል ጊቢልኝ!! ልብሽን ያየ አምላክ ሁለተኛ እድል ሰጥቶሻል። ያለፈውን ለመድገም ሌላ አዲስ ህይወት ባላስፈለገሽ ነበር። አዲስ ህይወትን ገንቢ የእኔ አበባ! ……. » የስንብት የሚመስል ብዙ አለችኝ። ያለእርሷ የኖርኩትን ህይወት እንዴት እንደኖርኩት ባላውቅም አሁን ያለእርሱ የምኖራቸውን ቀናት ሳስብ በረደኝ።
ግማሽ ልቤን እናቴጋ ትቼ፤ ፈጣሪ ትንሽ ቀን ቢጨምርላት፣ ኪዳንን ባገኝላት እና ብትሰማው ወይ ብታየው እየለመንኩ በተከፋች ግማሽ ልቤ ከጎንጥ ጋር ወደቤት መንገዱን ተያያዝነው።
«ይገርማል! የዛን ቀን ሞቼ ቢሆን ኖሮምኮ መሞቴን እናቴም አጎቴም አይሰሙም። በዚህ አይነት ኪዳንም አይሰማም ነበር። ሊቀብረኝ ራሱ የሚመጣ ሰው ይኖር ይሆን?» አልኩኝ
« ህም የሌላውን እንጃ። እኔ የት ሄጄ ነው የማልኖር?»
«ሬሳዬን የሚሸኝ ስለማይኖር ሰብአዊነት ተሰምቶህ እንጂ መቼም <ወየው እትይ!> እያልክ አትቀብረኝም ነበር።» ስለው አይኑን ለአፍታ ከመንገዱ ወደእኔ አዙሮ ፈገግ ብሎ ዝም አለ። በሱው የፈገግታ ለዛ ቀጥዬ «ሆስፒታል እንኳን መጥተህ እየኝ ብዬ ብልክብህ <የቀጠሩኝ ደጆን እንድጠብቅ ነው > ብለህ አልላክብኝም? ዛሬ ቤቱን ጥለህ ገጠር ለገጠር አብረኸኝ ልትንከራተት?»
