en
Feedback
አጫጭር ግጥሞችና መጣጥፎች 📚

አጫጭር ግጥሞችና መጣጥፎች 📚

Open in Telegram

✔️📚ማንበብ ያሻግራል ❗️❗️❗️ በዚህ ቻናል እናንተን የሚመጥኑ የተለያዩ ግጥሞችን ፣ አጫጭር ና መሳጭ ታሪኮችን ታገኛላችሁ። እናንብብ ፤ በማንበባችን እናተርፋለን እንጂ ፤ ከቶ አንከስርም። @snetsehuf

Show more
546
Subscribers
+324 hours
+127 days
+5230 days
Posts Archive
ገዢ ሀሳብ . . . . . . . መአዚ ፦ " ከሰራህባቸው ሀገራት የቱን በተለየ ትወዳለህ ? " ዶ/ር ምህረት ፦" አንደኛ ምወደው ኮንሶን ነው ካራቴ ከተማ ለሰባት ወራት ነው የኖርኩት ። ሰዉ በጣም አሪፍ ሰው ነው። ኮንሶ ሕይወት ማለት መሮጥ ብቻ ሳይሆን ተረጋግቶ ቀስ ብሎ ተስማምቶ ብዙ ስላለሽ ሳይሆን ያለሽን ( Enjoy ) እያረግሽ መኖርሽ መሆኑን ተገንዝቢያለው። ለካ ሞያሽ ላይ ሳይሆን ህይወት ላይ ነው መጀመሪያ specialiazed ማረግ ያለብሽ በጣም የተረጋጉ ሰዎች ናቸው ። ከስልጣኔ መብዛት ብዙ መሰብሰብ ይመስለናል ህይወት ግን የ ሰበ ሰብነውን ነገር አንዳንድ ግዜ አናውቅም ። " "ማነው ብዙ ዘመድ ያለው ? " "ማነው ብዙ ደስታ ያለው ? " " ማነው ለብዙ ሰው የጠቀመው ?" " ማነው ብዙ የተረጋጋ ሰዓት በቀን ውስጥ የሚኖረው ? " " በዚህ ነው ህይወት መለካት ያለባት ። " ~ ~ ~ ~ ~ ~ ~ ~ ~ ~ ~ ~ ~ ~ ~ ምንጭ ፦ ሸገር FM የጨዋታ እንግዳ . ዶክተር ምህረት ደበበ ከጋዜጠኛ መአዛ ብሩ ካደረገው ቆይታ የተወሰደ . @snetsehuf

ቀና በል መንገድ ሁሉ እንቅፋት በሆነበት አለም መነሳት ነው እንጂ መውደቅ ብርቅ አይደለም ሰው ብታጣ ዛሬ አትዘን ወንድሜ አግኝቶ ማጣትን ያስተምራል እድሜ ሲኖርህ የኖረ ስታጣ ብታጣው አለኝ ያልከው ወዳጅ ከፊት ባታገኘው የዛሬው ውድቀትህ መማሪያህ ነውና ባጣኸው ሳይጨንቅህ ባለህ ላይ ተፅናና መሙላት ቢቸግርህ ቀን እየጎደለ አታቀርቅር ተነስ ቀና በል ቀን አለ። ምንጭ:fb @snetsehuf ከተመቻችሁ ለወዳጆቻችሁ share አድርጉ

መዳፍና ዓይን" (ያሬድ ሹመቴ) ለፊልም ስራ አባይ ማዶ ተሻግሬ በነበረበት ጊዜ እንዲህም ሆነ! ፊልሙ - የገጠር ያውም የሽፍታ ታሪክ ነበረና "አብራራው" የተባለው የድሮ ጠመንጃ አስፈለገ። "አብራራው" ስሙን ያገኘው ለማቀባበል ከሚወስደው ጊዜ ተነስቶ ይመስላል። አንድ ሰው ነገር ስያረዝም "አብራራው" እንደሚባለው ማለት ነው።... የምንሰራው ፊልም ርዕሱ "ገዳይ ሲያረፋፍድ" ይሰኛል። እኔ በፕሮዲዩሰርነት እና በኤዲተርነት ተሳትፌበታለሁ። ዝግጅቱ የናኦድ ለማ ነው። የቀረጻ ቦታውም የጣና ሐይቅ ደቡብ ምዕራባዊ አቅጣጫ ላይ የምትገኘው ቆራጣ ላይ ነው።....ይህን ጠመንጃ ፈልጎ ማግኘት ቀላል ቢሆንም ፈቃጅ ማግኘቱ ግን እጅጉን ያለፋል። ምክንያቱም የጦር መሣሪያ ነዋ። ከፖሊስ ሊገኙ የሚችሉት መሣሪያዎች ዘመናዊ በመሆናቸው አንዱን የየአካባቢው ሰው ማሳመን ግድ ሆነ። "አብራራው"ን አስፈቅደን ቀረጻ ላይ ለማዋል "አብራራው" ከሆኑ [አቶ አዝመራው ከተባሉ] የአካባቢው ነዋሪ ጋር ስንለማመጥ ስንነታረክ አረፈድን። በኋላ በቀን 50 ብር ክፍያ ተስማምተን ያለ ጥይት አብራራውን ተከራየነው። "አብራራው" ፀሐይ ስትወጣ ስራ ይጀምርና ፀሀይ ስትጠልቅ "በሞክሼው" (የጠመንጃው ባለቤት) ወደ ቤቱ ይወሰዳል። እንዲህ እንዲህ እያለ ጥይት አልባው ጠመንጃ የፊልም ባለሙያ ሆነ። ብዙውን ጊዜ በቀረጻ ወቅት ደጋግሞ ማቀባበልና ቃታ መሳብ የተለመደ ስለሆነ ከዚህ ቀደም ሰርቶ የማያውቀውን ከባድ እንቅስቃሴ ለመደ። ለካንስ ይህ አሮጌ መሳሪያ ዕለት በዕለት በሚገጥመው ከባድ ስራ የቃታው ማስፈንጠሪያ እየላሸቀ ሄዷል። ከተቀባበለ በኋለ ቃታውን ለመሳብ በማሰብ ብቻ ተወንጭፎ መርፌውን ይመታል። ጠመንጃ በባህሪው ልክ እንደ ውሀ እያሳሳቀ ነው የሚወስደው። "ወይ ወደ መሬት፥ አልያም ወደ ሰማይ ተደርጎ ነው የሚነጣጠረውም፥ የሚተኮሰውም።" የሚለውን መርህ ለመሻር ጥይት አልባውን አብራራው ለሁለት ቀናት ብቻ ሲያቀባብሉ እና ቃታ ሲስቡ መዋል በቂ ነው። ከዛ በኋላ ማቀባበሉም ሆነ መተኮሱ በወዳጅ ላይ ልክ እንደ ቀልድ ነው የሚቆጠረው። ጥይት የጎረሰለት መጉረሱ ይዘነጋና የዕለት ቀልድ ሊቀጥል ይችላል። አንድ ቀን ታዲያ ጠመንጃው ጥይት ሲጎርስ መቀረጽ ስለነበረበት ባለ ንብረቱ ጥይቶች ይዞልን መጣ። ጥይቱን ተከትሎ ዝናብ መጣ። ቀረጻው ተስተጓጎለ። ጠበቅን ጠበቅን አያባራም። "ለበጎ ነው" የሚለውን ጥቅስ ያስታወሰ ማንም አልነበረም። ተበሳጭተን ተስፋ ቆርጠን እቃችንን ጠቅለን የገጠሩን መንደር ለቀን ወደ ባህር ዳር ተመለስን። የአብራራው ባለቤት እዛችው መንደር ባለች "አንጓች አረቄ ቤት" ውስጥ የላሸቀውን ጠመንጃ ጥይቱን አጉርሶ፥ እንደነገሩ ነቅነቅ ሲያደርገው ተፈትልኮ መርፌና እርሳስ ተገናኝተው ባረቀ። በተአምር ማለት ይቻላል አንድም ሰው ሳይጎዳ አካባቢውን አሸብሮ የአንጓችን የተደረደሩ 6 ትላልቅ ጋኖችን በታትኖ ቤቱን በጠላ ጎርፍ ሞላው። የተፈጠረውን ድንጋጤና ረብሻ ለመረዳት ቦታው ላይ መድረስ አላስፈለገንም ወሬው 42 ኪ.ሜትሮችን አቆራርጦ ባህርዳር ሳለን ሰማን። የነበረን ምርጫ ከቦታው መሰወር ብቻ እስኪመስለን ድረስ ተደናገጥን። እየመነታን እያማተብን በማግስቱ ማልደን ቆራጣ ገባን። የአብራራው ባለቤት አቶ አዝመራው ግን "የምወዳትን ጠመንጃዬን አሰሩልኝ እንጂ እግዚአብሔር ባዘዘው ገብቼ እናንተን አልወቅስም" አለ። ያስጠነቀቀው ግን ታዲያ "ጠመንጃዬ ያልተሰራች እንደው ይቅርታም አላደርግ" ብሎ ነው። በአካባቢው አሉ የተባሉ የመሳሪያ አዋቂዎች ዘንድ ተንከራተትን። የመሳሪያው አሮጌነትና በአይን ለማየት አስቸጋሪ የሆነውን የውስጡን ክፍል ለይቶ ማን ይወቀው። እንግዲህ ፀባችን እርግጥ ሆነ ስንልም ሁላችንም ሰጋን። በዚህ ግዜ ነበር አንድ ወዳጄ ባህር ዳር ሆስፒታል አካባቢ አንድ ባለሙያ መኖራቸውን የጠቆመኝ። ወደተባሉት ሰው የመጨረሻ እድል ለመሞከር ሄድኩ። አሮጌ ጠመንጃ ታጥቄ ባህርዳር ከተማ ውስጥ መታየት ችግር እና ትኩረት መሳብ ሊፈጥርብኝ ይችላል ብዬ ስላሰብኩ ጋቢ ጣል አድርጌ አብራራውን ታጠቅኩት። መኪና መግባት እስከሚችልበት ቦታ ድረስ በመኪና ሔጄ ጠመንጃውን አንግቼ ከመኪና በመውረድ እየተንጎራደድኩ የባለሙያውን ቤት ፍለጋ የሰፈሩን ሰዎች ማጠያየቅ ጀመርኩ። አንድም አተኩሮ ያየኝ ሰው የለም። ቤቱን ጠቆሙኝ። እኚህ ሰው ጋሽ ጥላሁን ይባላሉ። በአካባቢው ስመጥር ናቸው። ግን ሸምግለዋል። ሽማግሌ መሆናቸውን ስሰማ አይሳካም ስልም አመነታው። ነገር ግን "ለካስ የባሰም አለ" አልኩ ቤታቸው ደርሼ ሳያቸው። በእርጅና ምክንያትም አንደኛው ዓይናቸው ከናካቴው ሲጠፋ ሁለተኛው ደግሞ ከጥላ ውጪ ማየት አይችልም ነበር። "አሰላሳይ አገናዛቢ" ነኝ ብሎ ለሚታበይ ሰው በሙሉ የሚመጣለት፥ "ጊዜ መግደል ጥሩ አይደለም" የሚል ሀሳብ ነው። እኔም ቢሆን እንዲያ ማለቴ አልቀረም። ነገር ግን ሰውየው። አብራራውን ተቀበሉኝና ከመቅፅበት በእጃቸው ዳብሰው በስሙ ጠሩት። "አብራራው" አሉ። ትንሽም ቢሆን ላምናቸው ሞከርኩ። እሳቸው ለዘመናት የሚያውቁትን መሳሪያ እኔ ያን ሰሞን ስላወኩት የምበልጣቸው መስሎኝ ነበር። የስህተቴ ብዛት። እኚህ ሰው ፊታቸውን ወደ ጣራው መልሰው ጥቂት ዳብሰውት "ሰው አገኘባችሁ ታዲያ?" አሉ። "ሰምተው ነበር እንዴ?" አልኳቸው። "ኣረ የለ! ምላጭ ማስወንጨፊያው ከጥቅም ውጪ መሆኑን እያየሁት?" አሉኝ ቆጣ ብለው። ዋጋ ነግረውኝ በኋላ ተመለስ ብለው ቀጠሩኝ። ከቀጠሩኝ ሰዓት ትንሽ ረፈድ አድርጌ ደረስኩ። ጊዜ ልስጣቸው ብዬ ነበር። ቤታቸው ደርሼ ወደ ውስጥ ገባሁ። ከድምፄ ቀድመው በጥላዬ አውቀውኛል። ተቆጡኝ። "ምነ ቆየህ? አንተን ጥበቃ በር በር ልይ እንዴ? ሽማግሌ እኮ ማረፍ አለበት" አሉኝ። ማስረዳት ስላቃተኝ ይቅርታ ጠየቅኳቸው። ልቅም አድርገው ስራቸውን አጠናቀው ነገረኛውን አብራራው ጤነኛ አድርገው ጠበቁኝ ነበር። በጣም ገረመኝ። ለሙከራም አንገላታሁት። ወይ ፍንክች። እንደ ጠላት የታየንበት መንደር በኩራት ተመልሰን የፊልማችንም ቀረጻ ቀጠለ። አብራራውም አደብ ገዛ (ከነ ሞክሼው) ጤነኛውን ጠመንጃም ለባለንብረቱ አቶ አዝመራው ሳስረክበው አንድ ጥያቄ ደጋግሞ ጠየቀኝ። "ማነው የሰራው?" የሰውየውን ማንነት "አብራራሁለት"። ዐይናቸው እንደማያይላቸው ስነግረው ትልቅ ቁም ተናገረ፦ "እጃቸው ላይ ሸምግለው ነዋ" አለኝ። በአንድ ሙያ ውስጥ ማርጀት፥ አይን እንኳ ጠፍቶ ጠቢብነትን አይነጥቅም" ወደ ፊልም ሙያ አንድ አፍታ ልመለስ። በሆሊውድ እና በሌሎቹም ግዙፍ የፊልም ኢንዱስትሪዎች ውስጥ ታዋቂና ስኬታማ የተባሉት የፊልም ዳይሬክተሮች በሙሉ (99%) ሽማግሌዎች ናቸው። ምክንያቱም በፊልም ሙያ ውስጥ የተራቀቀ ጥበበ የሚወለደው በሙያው ሲያረጁበት ነውና። በየሙያቸው፣ ሙያቸው ላይ ያረጁ ሰዎችን እናክብር!! እውቀት ከዚያ አለች!! አመሰግናለሁ። @snetsehuf

#አዲስ ህይወት .. ..አባትና ልጅ አህያቸውን ለመሸጥ ከቀያቸው ርቆ ወደሚገኘው የገበያ ስፍራ እየነዱት ይሄዳሉ :: አህያውን ከፊት አስቀድመው ሁለቱም ጎን ለጎን እያወጉ በመሄድ ላይ ሳሉ መንግድ ላይ ሰዎች አዩአቸውና «እነዚህ ምን አይነት ሞኝ ሰዎች ናቸው? አህያውን ባዶውን እየነዱ እነሱ በእግር ይሄዳሉ እንዴት? ምን አለበት ዝም ብለው ከሚደክሙ አንዳቸው እንኳን ወጥተው ቢሄዱበት ::»አሉ ::ይህንንም የሰሙት አባትና ልጅም የሰዎቹን ንግግር ሰሙና ተመካክረው አባትየው አህያው ላይ ወጥቶ እንዲሄድ ልጁም እንዲከተል ተስማምተው ጉዟቸው ጀመሩ:: ጥቂት አለፍ እንዳሉ ሌሎች መንገደኞች አዩአቸውና «ይህ ሽማግሌ ምን አይነት አረመኔና ጨካኝ ሰው ነው? ይህንን አቅሙ ያልጠነከረ ትንሽ ልጅ በእግሩ እያስኬደ እሱ በአህያው ይጎዛል እንዴ? ምን አለ ለልጁ ቢያዝንልነትና እሱ በእግሩ ቢሄድ? አሉ +: ይህንን የሰማው አባት በድርጊቱ እጅግ ተፀፅቶ ከአሕያው ወረደና ልጁን አህያው ላይ አስቀምጦ እሱ ከኃላ እየነዳ መጕዝ ጀመሩ:: ትንሽ ከተጕዙ በኃላ ሌሎች መንገደኞች አዩአቸውና «አይ የዛሬው ልጆች!እንደው እንዴት አይነት የተረገመ ዘመን ላይ ደረስን? ሽማግሌውን በእግር እያስኬደ እሱ አህያየሚሄድ ምን አይነት ልጅ ቢሆን ነው? ትንሽ እንኳን አይከብድህም? ብለው የስድብና የእርግማን መዓት በልጁ ላይ አወረዱበት :: ይህንን የሰማው ልጅ በሰዎቹ ንግግር ተደናግጦ በድርግቱም አፍሮ ከአሕያው ላው ወርደ :+ አባትና ልጅም እሰካሁን ነገሮች ከሰሙና ከተመካከሩ በኃላ ሁለቱም እንዳይተቹ በማሰብ አህያው ላይ ወጥተው መጋለብ ጀመሩ:: ነገር ግን ገና መጎዝ ከመጀመራቸው ሌሎች መንገዶኞች አዩአቸውና «ተመልከቷቸው እነኚህን ጨካኝ አባትና ልጅ! ፈፅሞ ርህራሄ የሚባል ነገር ያልፈጠረባቸው :: ምን አለበት ለአሕያው ቢያስቡለት? እንደዚህ ደክሞ እያዩት እንኳን አያዝኑለትም? አህያው እኮ መሞቱ ነው»:: አለ :: አባትና ልጅ ደንግጠው ወረዱ ሊሸጡት የሚውስዱት አህያ ሊሞት መሆኑን እስካሁንም ተሸክሟቸውእንዲመጣ ማድረጋቸው ስለፀፀታቸው ለአሕያው በማዘን እግሮቹን ወደላይ በገመድ በማሰርና መሃል ለመሃል ትልቅ ዱላ በመአስገባት አባትና ልጅ አህያውን በማሾፍ ተቀበሏቸው :: «ተመልከቱ እነዚህ ሞኞች አህያ ተሽክመው ሲሄዱ»ብለው ተሳለቁባቸው::............. ገፅ :- 66-67 @snetsehuf

ግንቦት እና ኢትዮጵያ ! በቀረበኝ ኖሮ ለምን በላሁት አያበቅለው የለ ሰኔና ግንቦት የግንቦቱ ባሰ አረም በዝቶበት ግንቦት ወር በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ብዙ ክስተቶችን ያስተናገደች ታሪካዊ ወር ናት። ኢትዮጵያ በዚህ ግንቦት ወር ታዋቂ ልጆቿን ወልዳለች ፤ ወደማይቀረው ዓለምም ሸኝታለች ፤ መሪዎቿን ወደ ስልጣን አምጥታለች ፤ ከስልጣናቸው ሽራለች፤ አስከፊ ጦርነቶችን አስተናግዳለች፤ ከእነዚህ ታሪካዊ ክስተቶች በተጨማሪ ግንቦት ያልተለመዱ ክስተቶች የተስተናገዱበት ወርም ነው። አሁን አሁን ላይ እየቀረ መጥቶ ነው እንጂ በዚህ ወር ከተፈጠሩ መጥፎ አጋጣሚዎች ጋር በማያያዝ ወሩን በገደቢስነት በመፈረጅ በተለይ በመሃል ሃገር ጋብቻ አይፈፀምም ነበር። በግንቦት ወር የተመዘገቡ አብየት ክስተቶች እጅግ በጥቂቱ ፦ ➨ የታላቋ አክሱም ንጉስ አፄ ካሌብ ያረፉት በግንቦት ወር ነው። አፄ ካሌብ ከአክሱም እና አካባቢው አልፈው ቀይ ባህር ተሻግረው የደ/ አረቢያ ህዝቦችን ያስገበሩ ንጉስ ነበሩ። ➨ እቴጌ ምንትዋብ ያረፉት በግንቦት ወር ነው። እቴጌ ምንትዋብ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ታሪክ ስማቸው በጉልህ ከሚነሳ እንስቶች መካከል አንዷ ነበሩ። ➨ የውጫሌ ውል የተፈረመው በግንቦት ወር ነው። ➨ ለንግስና ያልበቁት ልጅ እያሱ ምኒልክ የተሾሙት በዚህ ወር ነው። ➨ ልዑል መኮንን ኃይለስላሴ የመኪና አደጋ ደርሶባቸው ህይወታቸው ያለፈው ግንቦት 1949 ነበር። ➨ ጋዜጠኛ ጳውሎስ ኞኞ ህይወታቸው ያለፈው ግንቦት 29/1984 ነበር። ➨ ሀገራችን በታርክ በግንቦት ወር አስከፊ ጦርነቶችን አስተናግዳለች። ➨ የቀድሞ የኢትዮጵያ ፕሬዜዳንት ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም የተወለዱት ግንቦት 19 ነው። ➨ በቀድሞ ፕሬዜዳንት ኮ/ል መንግስቱ ኃለማርያም ላይ መፈንቅለ መንግስት የተሞከረው ግንቦት 8 ነበር። ➨ በኮ/ሌ መንግስቱ ኃ/ማርያም ላይ የተሞከረው መፈንቅለ መንግስት በአዲስ አበባ ግንቦት 8 ከሸፈ፥አስመራ ላይ ግንቦት 9/1981 ከሸፈ። ➨ በኮ/ሌ መንግስቱ ኃይለማርያም ላይ በተሞከረው መፈንቅለ መንግስት አ/አ ላይ ሙከራውን ያደረጉት ጄነራሎች ራሳቸውን ገደሉ፣ ተገደሉ፣ ታሰሩ። አስመራ ላይ ግንቦት 9 የ102ኛ አየር ወለድ ክ/ጦር በምስራቅ እና በሰሜን የገጠማትን ጦርነት ሲመሩ የኖሩት ጄነራሎች ተገደሉ። ➨ ኮ/ሌ መንግስቱ ሀገር ጥለው የወጡት ግንቦት 13/1983 ነበር። ➨ 12 ከፍተኛ ጄነራሎች የተገደሉት ግንቦት 11/1982 ነበር። ➨ ኢህአዴግ አዲስ አበባን የተቆጣጠረው ግንቦት 20/1983 ነው። ➨ የቀድሞው ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ የተወለዱት ግንቦት 1 ነው። ➨ በኢትዮጵያ ታሪካዊ ነው የተባለው ምርጫ የተካሄደው ግንቦት 7 ቀን 1997 ነው። በዚህ መነሻ በርካታ ወጣቶች በአደባባይ ተረሽነዋል ፥ ሺዎች ታስረዋል ፤ የተቃዋሚ አመራሮች ዘብጥያ ተጥለዋል። ➨ የደረግ ከፍተኛ አመራሮች ሞት የተፈረደባቸው ግንቦት 18 ቀን 1999 ነው። ➨ ሞት የተፈረደባቸው የደርግ አመራሮች ፍርዱ ወደ እድሜ ልክ የተቀየረላቸው ግንቦት 2003 ነው። ምንጭ ፦ ሌተናል ኮሎኔል ፍስሃ ደስታ (አብዮቱና ትዝታዬ)፣ ታሪከ ነገስት-በደሴ ቀለብ ፣ፀሀፊ ተክለፃዲቅ መኩሪያ፣ ኢፕድ ድረገፅ፣ አዲስ ማለዳ ጋዜጣ @snetsehuf

ሽልማቱ (በእውቀቱ ስዩም) በቀደም ሰይፉ ላይ የሰማሁት ዜና እንዲህ ይላል” የናይጀርያ ዜግነት ያላቸው ሌቦች አዲሳባ ገብተዋል” 🙂ከኢትዮጵያ አቻዎቻቸው ጋራ ልምድ ልውውጥ ለማድረግ መሆን አለበት! ሌብነት ሲነሳ የሚከተሉት አስተካዥ ገጠመኞች ትዝ ይሉኛል፤ ሰውየው የበግ ነጋዴ ናቸው፤ ወደ ገበያ ሲሄዱ ከፍተኛ ጥንቃቄ ያደርጋሉ፤ እንደተለመደው አንድ ማለዳ ገንዘባቸውን ከፍየል የቆለጥ ማቀፍያ ቆዳ የተሰራች ትንሽየ ቦርሳ ውስጥ ጠቀጠቁት፤ ከዚያ ቦርሳውን እንደ ቡዳ መዳኒት አንገታቸው ላይ አንጠለጠሉት ፤ በላዩ ላይ ግድንግድ የድሮ ቢትልስ ለበሱበት፤ በዚያ ላይ ካሽሚር ጃኬት በጃኬቱ ላይ ጋቢ፥ በጋቢው ላይ ደግሞ መለስተኛ ቤተሰብ ማስጠለል እሚችል ካፖርት ደረቡበት፤ ከዚህ ሁሉ ጥንቃቄ በሁዋላ ገበያ ውለው ሲወጡ እጃቸውን ወደ አንገታቸው ሲሰዱ ቦርሳው አምልጡዋል ፤ ቤታቸው ገብተው የደንቡን ያክል አልቅሰው ሲያበቁ ወደ ሚስታቸው ዞረው “ ጉድ እኮ ነው! ይሄን ሁሉ አለባብሼው፥ ሌባው እንዴት አርጎ ወሰደው?” አሉዋቸው’?’ ሚስትዮም እንዲህ መለሱ ፥ “ አንተ ደሞ! ላት ያላት በግ አትሰረርም ያለህ ማነው?” 2 ሸገር ውስጥ "የሌባ ሰፈር " ነው እየተባለ የሚታማ ሰፈር አለ! እስከ ሰባ አመት ፥በዚህ አለም መቆየት ስለምፈልግ ስሙን አልጠቅሰውም! አንድ ጋዜጠኛ ወዳጄ በሬድዮ ፕሮግራሙ ላይ ስለዚህ ሰፈር ለየት ያለ ቆንጆ ፕሮግራም ሰራ፤ የሰፈሩ ልጆች ሰምተው ፈነጠዙ! “ በስርቆት ብቻ ሲነሳ የነበረ ሰፈራችንን ገፅታ ስለገነባህልን የምስጋና ድግስ አዘጋጅተንልሀል ፤ ሽልማትም ተሰናድቶልሀል” ብለው ጋበዙት፤ እሱም ልቡ በጣም ተነክቶ በዝግጅታቸው ላይ ታደመ፤ መኪናውን ዝግጅቱ ከሚዘጋጅበት አዳራሽ ጀርባ አቆመና ወደ ውስጥ ዘለቀ፤ ድብልቅልቅ ባለ ጭብጨባ ተቀበሉት:: የተለያየ የኪነጥበብ ድግስ ተከታትሎ መቅረብ ጀመረ፤ አንድ ወጣት “ ካልተሳፈሩበት ቶሎ ተሽቀዳድሞ ጊዜ ታክሲ አይደለም አይጠብቅም ቆሞ” የሚል ግጥም አነበበና በቅርቡ ከሚታተመው መድብሌ የተወሰደ ነው ብሎ ከመድረክ ወረደ:: የስነፅሁፍ ዝግጅቱ ሲጠናቀቅ ምሳ አበሉት፤ ምን ምሳ ብቻ፤ በሹርቤ ብርሌ ጠጅ አቀረቡለት፤ ብርሌውን ሾፍ ሲያደርገው “ ብሄራዊ ሙዝየም “ የሚል ማህተም ተለጥፎበታል፤ በመጨረሻወደ መኪናው ሄደ፤ ባየው ነገር ክው ብሎ ቀረ፤ የመኪናው ሁለት ስፖኪዮ በቦታው የለም፤ የደረሰበትን የነገረኝ ቀን በምን ቃል እንዳፅናናሁት አልረሳም ” ጎማውን ስለማሩልህ እንደ ሽልማት ቁጠረው” @snetsehuf

:::::::::::::::::::::::: ዉለታ :::::::::::::::::::::::: ሁለት ጓደኛሞች እጅግ ሞቃት በሆነ በረሃ እየተጓዙ በነበረ ወቅት የቀረውን የኮዳ ዉሃ ማን መጠጣት እንዳለበት እየተከራከሩ በድንገት አንደኛው በብስጭት በአይበሉባ ጥፊ መታዉ:: የተመታውም ግለሰብ እንዲህ ሲል በበረሃ አሸዋ ላይ ጻፍ:~ <<ዛሬ ጓደኛዬ በጥፊ መታኝ>> ከዚህም ክስተት በኃላ የአንደኛቸዉ መኖር ለሌላኛቸዉ እንደሚበጅ ተነጋግረዉ ጉዞቸዉን ተስማምተዉ ቀጠሉ:: በሚጓዙበት ወቅትም ትንሽዬ ኩሬ አግኝተዉ ለመጠጥ የሚበቃቸዉን ዉሃ በኮዳቸው ከሞሉ በኃላ ገላቸዉን ለመታጠብ ተስማሙ:: እንደተንጋገሩትም በቂ ዉሃ ከያዙ በኃላ ገላቸዉን ለመታጠብ ወደ ኩሬዉ ገቡ:: ከገቡ በኃላ ግን ያልጠበቁት ገጠማቸዉ ኩሬው እንዳሰቡት ትንሽ አልነበረም:: ከሰአታት በፊት በጥፊ የተመታዉ ልጅም ፈፅሞ ዋና ሰለማይችል ወደ መሃል በገባ ጊዜ ሰመጠ ይህን የተመለከተዉ ጓደኛዉም እንደምንም ወደመሃል ተወርውሮ አየገፋ ይዞት ወጣ:: ከወጡ በኃላም ከሞት የተረፈዉ ልጅ ዳግመኛ እንዲህ ሲል በድነጋይ ላይ ፃፈ:~ << ዛሬ ጓደኛዬ ህይወቴን አተረፈዉ>> ጓደኛዉም የህን በተመለከተ ጊዜ እንዲህ ሲል ጠየቀዉ:~ ቅድም በጥፊ በመታሁህ ጊዜ በአሽዋ ላይ ነበር የጻፈከው ታዲያ አሁን ለምን በድንጋይ ላይ ፃፍከዉ:: እሱም እንዲህ ሲል መለሰለት:~ ተመለከት ሰው መጥፎን ባደረገብህ ጊዜ በአሸዋ ላይ መፃፍ ይኖርብሃል ምክንያቱም የሕይወት እስትንፋስ የሆነዉ የየቀርታ ነፋስ በነፈሰ ጊዜ ቂምህ የጠፋልና :ሰዎች መልካምን ባደረጉልን ጊዜ ግን ነፋስ በማያገኘው ድንጋይ ላይ ልንቀረፀዉ ለዘላለምም በልባችን ልናሰፍረዉ ይገባል:: ይህን ማድረጋችንም ለመጥፎ ሃሳብ እና ተግባር ቦታ እንዳንሰጥ በመልካምነት እንፀናም ዘንድ ይረዳናል::

ጳውሎስ ኞኞ "አንድ ጥያቄ አለኝ" የተሰኘ አምድ አዲስ ዘመን ላይ ነበረው። እዛ ላይ አንዱ ነገረኛ ተከታይ "ከሙስሊም እና ከክርስቲያን ማነው የሚፀድቀው?" ሲል ጠየቀው። ጳውሎስም አጣብቂኝ ውስጥ እንደከተተው በማስተዋል አሰብ አድርጎ "ከሁለት አንዱ" ብሎ መለሰለት። የቤተ-ክህነት ሰዎች ይሄን ሲሰሙ በጣም ተቆጡ። ነገሩ ጳጳሱ ዘንድም ደረሰ። ከዛ ጃንሆይ ጋር ቀረበ። "እንዴት እንደሱ ይላል? ራሱ ክርስቲያን ሆኖ ክርስቲያን ነው የሚፀድቀው ይበል እንጂ፤ እንዴት ከሁለቱ አንዱ ይላል" ብለው ከሰሱት። "ይቀጣ። ከደሞዙም፣ ከሥራውም እንዲታገድ እንፈልጋለን" የሚል ማመልከቻም አቀረቡ። ጃንሆይም "መልሱን ከቻላችሁት ይመጣና እዚሁ ይጠየቃል" አሉ። ጳውሎስም ተጠርቶ "እንዴት እንደዚህ ትላለህ? ተብሎ ሲጠየቅ ጉዳዩን በቀጥታ ወደ ንጉሱ ወሰደው። "ግርማዊነቶ እርሶ የኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት ኖት አይደል?" "አዎን" "እናስ የማን ንጉስ ኖት? የክርስቲያን እና የሙስሊም አይደሉም እንዴ?" "ትክክል" "ሐይማኖትስ አይመለከቶትም" "በሚገባ ይመለከተኛል" "ጋዜጠኛም ልክ እንደሱ ነው። የክርስቲያንም፣ የሙስሊምም ሊሆን አይችልም። ወገን አይዝም፤ እውነት ወዳለበት፣ አውቀት ወዳረፈበት ያዘነብላል እንጂ" አለ። ጃንሆይም ወደ ቤተ-ክህነት ሰዎች ዞረው "በሉ መልሱ" ቢሊ የሚመልሱት ጠፋቸው። እናም ጳውሎስ ኞኞ ለዚህ ሐቀኝነቱ፣ ሚዛናዊነቱ ከጃንሆይ ሽልማት ተበርክቶለታል። እንዳውም የተባለው "ምን ይሸለም?" ሲባል ያው ርስት ይጠይቃል ብለው ስለጠበቁ፤ "ርስት ይሰጥህ?" ተባለ። "ምን ያደርግልኛል? ይልቅስ አዲስ የመጣች ታይፕ ራይተር አለች፤ እሷ ትሻለኛለች" አለ አሉ። ዓለማየሁ ገላጋይ ከጋዜጠኛ ጀማል አህመድ ጋር ለኢድ-አልድሃ ያደረገው ቆይታ ••• ደራሲስ የማነው? አንባቢስ የቱ ጋር ነው መቆሚያው? ለምን እና ለማን ነው መወገን ያለበት? ••• @snetsehuf

" ዒድ አልፈጥር " ውድ የእስልምና እምነት ተከታይ የሆናችሁ ቤተሰቦቻችን እንኳን ለ1443ኛው የዒድ አልፈጥር በዓል አደረሳችሁ። ዒድ ሙባረክ ! በዓሉ የሰላም ፣ የአንድነት ፣ የፍቅር እና የመተሳሰ
" ዒድ አልፈጥር " ውድ የእስልምና እምነት ተከታይ የሆናችሁ ቤተሰቦቻችን እንኳን ለ1443ኛው የዒድ አልፈጥር በዓል አደረሳችሁ። ዒድ ሙባረክ ! በዓሉ የሰላም ፣ የአንድነት ፣ የፍቅር እና የመተሳሰብ ይሆንላችሁ ዘንድ እንመኛለን።

ክርስቶስ ወ ገብረክርስቶስ (በቴዎድሮስ ካሣሁን) እዩት ይሔን ጠቢብ ሸራው እስኪደማ፡ በቀይ እየወጋ በደም እየሣለው፡ እንጨት አመሳቅሎ፡ ዳግም ክርስቶስን ጨርቁ ላይ ሰቀለው፡፡ ቀራንዮ ሆነ የወጠረው ሸራ፡ ጎለጎታ ሆነ የወጠረው ሸራ፡ አሁን እስኪመስል ስቃዩ እያስፈራ፡፡ ደም ከደም አረገው አበዛበት ጣር ብሩሹን አሹሎት እንደ ጎኑ ጦር፡፡ እየወጋ ሣለው፡ በጣም ጨከነበት፡ ገብረክርስቶስም ክርስቶስ ላይ ከፋ፡ የቆዳው ዓይነቱ በደም ተከልሎ ዘሩ እስከሚጠፋ እየወጋ ሣለው፡ እየሣለ ወጋው፡ ዘሩ እስከማይለይ መልኩ ዝም ብሎ ደሙ እስከሚናገር፡ የትም ያለ ፍቅር እንዳይኖረው አገር፡ እንዳንለው ፈረንጅ እንዳንለው ጥቁር፡ እንዳንለው ቀይ፡ በመስቀል ላይ ሞቶ ያየውን ስቃይ በቆዳ በቀለም እንዳናሳንሰው በደሙ ተሰቅሎ ሰው ያዳነውን ሰው፡፡ ከቀናት ባንዱ ዕለት፡ ሰዎች ሲሟገቱ በቀለሙ ጉዳይ፡ ሲከራከሩበት በተመፃዳቂ የምሑር አንደበት፡ ባንዱ አፍ ሲጠቁር፡ ባንዱ አፍ ሲነጣ፡ መታገስ አቃተው ሠዓሊው ተቆጣ! ሥሜቱ ገንፍሎ በብሩሽ ጫፍ ወጣ፡፡ ሐሣቡን የሚገልፅ ቀለም እስከሚያጣ፡ ሸራ ላይ ሰቀለው እንጨት አመሳቅሎ፡ አልወጣልህ አለው ፍቅርን ሥሎ ሥሎ፡፡ ሥሎ---ሥሎ----ሥሎ፡ ፍቅርን ሥሎ ሥሎ፡ በሣለው እየወጋ፡ በደማው እየቀባ፡ 'ክርስቶስ ደሙ እንጂ ዘሩ አልተሰቀለም እንጨቱ ላይ ያለው ዕውነት ይሔ አይደለም፡፡' እያለ እስኪናገር የሥዕሉ አንደበት ገብረክርስቶስም ለክርስቶስ 'ሚሆን ቀለም እስኪያልቅበት፡ በነጩ ሸራ ላይ እስካሁን የሚወርድ ደም አፈሰሰበት፡፡ ቀለም፡ ቀይ ቀለም የደም ቀለም፡ የጥላ ቀለም የሁሉም ነው'ንጂ የማንም አይደለም፡ ፍቅር ዘር አይደለም፡፡ ለሠዓሊና ገጣሚ ገ/ክርስቶስ ደስታ የተፃፈ @snetsehuf

#እኔ በጣም ውድ ነኝ! እኔ በጣም ውድ ነኝ ብለህ በልበ ሙሉነት ተናገር ። ምክንያቱም አንተን ሊገዛ የሚችል የገንዘብ መጠን በዚህች ምድር ላይ የለም። ታዲያ ውዱ ሰው ሆይ አንተ ውድ መሆንህን ካመንክ ሰዎች ሀሉ እንዳንተ ውድ ናቸውና ሰው በመሆናቸው ብቻ አክብራቸው። """"""""" መልካም ሌሊት ቤተሰብ"""""""" ማንበብ ያሻግራል ! ከተመቻችሁ ለወዳጆቻችሁ share አድርጉ @snetsehuf

ለክርስትና እምነት ተከታዮች በሙሉ እንኳን ለብርሃነ ትንሳኤው በሰላም አደረሳችሁ። መልካም በዓል ይሁንላችሁ ። @snetsehuf
ለክርስትና እምነት ተከታዮች በሙሉ እንኳን ለብርሃነ ትንሳኤው በሰላም አደረሳችሁ። መልካም በዓል ይሁንላችሁ ። @snetsehuf

ለክርስትና እምነት ተከታዮች በሙሉ እንኳን ለብርሃነ ትንሳኤው በሰላም አደረሳችሁ። መልካም በዓል ይሁንላችሁ ። @snetsehuf

#አንቺዬ... ... ይዤሽ በወጣሁኝ ፣ በዚህ ድቅድቅ ምሽት "ባሕር ያሞራል”፣ አትበይ ከኔ ልብ ሽሽት። የባሕር ዳር ውበት ፣ በስሜትሽ ዐይተሽ ጨረር አታድንቂ ፤ ጨረቃን ረስተሽ፤ ዕዪው... ልብ ብለሽ! ባሕር ለጨረቃ ፣ ደረቱን ገልብጦ፤ የጨረቃ ጨረር፣ በባሕር ተውጦ፤ ሲግባቡ እያየሽ፣ አንቺ ግን ሔዋኔ ብርሃን ፍላጋ ፣ጨለማ ላይ ቆየሽ። ባሕር ምን ቢሰፋ ፣ጨረቃ ሞላችው ጨረቃስ ብትሞቅ ፣ አላደረቀችው። የመዋዋስ ፍቅር፣ከልባቸው ጠፍቶ ሲሞላሉ ዐየሽ ፣ኀይሏቸው ሰፍቶ። ተቃርኖ ተመልከች! ጨረቃ ወላድ ናት፣ እናት ብርሃን፤ ባሕር ጨለማ ነው፤ የብልጭታ መሀን። ተቃርኖ ተመልከች! ባሕር ሕይወት አለው፤ ከሰው የረቀቀ፤ ጨረቃ ግን በድን ፣ ከሕይወት የራቀ። የዋጡትን ዐየሽ... የሌላትን ሕይወት በብርሃን ቀዘፋ ጨረቃን ተመልከች ፣ ከባሕሩ ገዝፋ። የዋጡትን ዐየሽ... ሕይወትን ቢቀዝፍ ፤ ጨለማን ተዋርሶ፣ ዕድሜ ለጨረቃ... ባሕሩን ተመልከች ፣ እስከሰማይ ደርሶ፡፡ ያዋጡትን ዐየሽ ሕይወት ከጨለማ ፣ ጨለማ ከሕይወት፣ በድን ከብርሃን ፣ ብርሃን ከበደን ሲሰጣጡ ጊዜ ትንሿ ጨረቃ ፣ ባሕር ስትከድን። ይዤሽ የወጣሁት ፣ በዚህ ድቅድቅ ሞሽት ባሕር ያምራል አትበይ ፤ከኔ ልብ ሽሽት። ጨረቃና ባሕር ፣ሲግባቡ ያስቃል፤ ያአዳሜ ና ሔዋን ፣ፍቅሩ በቃል ያልቃል። ያዋጡትን ዐየሽ! 🔘ኤልያስ ሽታኹን🔘 @snetsehuf

#ብዙዎች_ይላሉ . . ! ብዙዎች ይላሉ . . . እንዴት ትችላለኽ ... ? ከነፋስ መፏከር ከግዑዝ መማከር እንደምን ይቻላል . . . ? ውቅያኖስን መክፈል ተራራን ማካፈል እኮ እንዴት ይኾናል . . . ? ከዋክብትን ማርገፍ ጨረቃን መደገፍ እንዴትስ ይኾናል . . . ? ብርሃንን ሽሮ ፣ መቆም በጨለማ ፍጥረታትን ረስቶ . . . ተፈጥሮን መጋጠም በሰውኛ ዜማ። ብዙዎች ይላሉ . . .! ይኽን የማያውቁ . . አንቺ ካለሽ ጎኔ ኹሉም ይታለፋል እንኳንስ ተፈጥሮ እግዜር ይሸነፋል። 🔘ተስፋሁን ከበደ🔘 @snetsehuf

#ጉዞ_ወደ_ፍቅር ቀድሞም አምን ነበር አካላቴ እንደኾንሽ ፤ ቀድሞም ዐውቀው ነበር ለ'ኔ እንደተፈጠርሽ። ይኸው . . በጉዘቴ መኻል መንፈሴ ተረታ ድንገት ባጋጣሚ ፣ ታየኝ ውብ ፈገግታ። የዘላለም ሣቅሽ በቅጽበት ተሰማኝ ግብሬን ዘነጋኹት እንደኾንኩኝ መናኝ። ቢኾንም ዐውቃለኹ . . ብዙ ጊዜ አይወስድም ባ'ንቺ በኩል ብኼድ ፍቅር አይደለም ወይ ? የፈጣሪስ መንገድ። 🔘ተስፋኹን ከበደ🔘 @snetsehuf

#ሰው_ማለት_ሽቶ_ነው ከገል ግብሩ በረት ፥ ከስምኦን ድግስ ዓለም ያነበበው ፥ የጋለሞታ ጥቅስ እኔ ነኝ! በመሲሁ መዳፍ የመኖሯ ዋሻ ፥ ዳግም ሲፈለፈል የዕንባዋ ጥያቄ ፥ በሳቋ እንዲከፈል ሐዘን ቤቱ ጠቦት ፥ መደሰቷ ሰፋ ወንድ የቀዳደደው ፥ ቆዳዋ ተሰፋ የዛች ሴት... ከክርስቶስ ነገድ ፥ ከሐዋሪያቱ ተረስቶ የኖረው ፥ ያ የናርዶስ ሽቱ እኔ ነኝ! ናርዶሷ እኔ ነኝ! ከሴትነቷ ጋር ፥ በግዢ የታሰርኩ መቆሟ እንዲሰምር ፥ ቁሜን የተሰበርኩ ከአይኖቿ ውሃ እኩል ፥ እግሮቹ የነኩኝ ናርዶሷ እኔ ነኝ! ዘላለም ልሰረዝ ፥ አንዴ የተፃፍኩኝ። ብልቃጧ እኔ ነኝ! ነውሯ ሊገፈፍ ፥ በእጇ የምሰበር በዛች ዕለት ምሽት እግርህን ያጠበው ፥ የኔም ዕንባ ነበር። ሀቄን ተቀበለው! ሀቄን ተቀበለው...! ጌታሆይ... እኔኮ እንደአንተ ፥ ከስምኦን ማጀት ስመገብ አይደለም ፥ አጋር የሆንኩላት ከአንተ ቀድሜ ነው ገላዋን ሳልንቀው ፥ ከገል ያነስኩላት ሀቄን ተቀበለው...! በነዳዱ ፀሐይ አንተ ጋር ለመምጣት ፥ ቅንጣት ሳያሳሳኝ በመዳኗ ሰዓት ፥ ይቅርታዋ ረሳኝ። ልክ ነች ልክ ነች! በሰማይ ነው እንጂ ፥ ማንም በሌለበት ከዛፎች ስርማ ይሄ ድኩም ልብሽ ፥ የትም ይሸሸጋል አንቺም እውነት አለሽ መሬት ከደረሱ ፥ ክንፍ ምን ያደርጋል? ግና... በመቀበል ዓለም መባውን ዘንግቶ በማዕረግ መዓት ፥ መባ ሰጪን ማደል ልጅ የሰጠን አባት አከብራለሁ ብሎ ፥ ልጅን እንደመግደል ግና... በመቀበል ዓለም በመቀበል ዓለም ስጦታውን ጥሎ በምስጋና ዳና ፥ ሰጪን መቀራረብ ክርስቶስን ክዶ ፥ መቅደስ እንደመቁረብ እንዲያ ነው ነገሩ... በአሳር ስንክሳር ሰው መሆን ሲተረት ፥ ሞት ቤቱን ቀልሶ መስማት ለማይችል ሟች ፥ እዬዬ ነው ለቅሶ ትሽሽሽ... ትሽሽሽ... የኔ አይነቱ ሽቶ በተጫኑት ቁጥር "ትሽ" "ትስ" እያለ ፥ ነፍሳቱን ያወጣል ለጋለሞታ ዕንባ የሚሰበር ብልቃጥ ፥ በየቀን ይሸጣል ትሽሽሽ! ደግሞ ደጋግሞ ትሽ ኧረ ወዲያ ይቅር ፥ ህይወት ምናምንትሽ ስትፀነሺ ነው ፥ የታወጀው ሞትሽ ትሽሽሽ! በአለማወቅ ድምቀት ፥ ነፍሱ የሚኮፈስ ሰው ማለት ሽቶ ነው ፥ ሲጫኑት የሚያፈስ። ትሽሽሽ! በኖርኩኝ አባዜ ፥ ከመኖር ሲታጎል ሰው ማለት ሽቶ ነው ፥ ሲነኩት የሚጎል። በቀትር ብርሃን ሲታየው ጨለማ ፥ ቀልቡ የሚደማ ሰው ማለት ብልቃጥ ነው አንዱ እንዲወለድ ፥ ነፍሱን የሚቀማ! ልክ እንደእኔ! እኔ ነኝ ባርያዋ! እርሷ ናት ገዢዋ! መኖር ያልገባሁት ፥ የማያውቀኝ ሀሴት ባክኜ የቀረው ፥ በስምኦን ደሴት እርሷ ናት ያቺ ሴት! በመፍረሴ ሰበብ በአፈር ሰውነቷ መዳራት ሲታነፅ ፥ በዝሙት ሲቀለስ የሳቋ ጥያቄ ፥ በዕንባዋ እንዲመለስ እርሷ ናት ያቺ ሴት! ባህሯ ያፈናት ፥ ይዟት ሕይወት መረብ በመቅደስ ገላዋ ፥ ሆይሆይታ ሲወረብ ፊት ኋላ በሌለው ፥ በመኖሯ ቀመር በዜማ አካሏ ፥ ወንድነት ሲዘመር እርሷ ናት ያቺ ሴት! በዓለም ከማንም ፥ በሩቁ ተጥላ በቋንጣዋ ገመድ ፥ ልብሷን አንጠልጥላ እርቃነ ስጋዋ ፥ ለስጋ ሲከተት! በማንም ምላስ ላይ ፥ ስሟ ሲንከራተት ከድቅድቁ ወጥታ ፥ ብትናፍቅ ወገግታ መዳራት ከፍታለች ፥ መራራቷን ዘግታ አዎን ኖሬያታለሁ... ስጋዋን ሊሞቃት ወንድ እየበረዳት ፥ ሰቀቀን ቀጭኗ አይቻት አቃለሁ ፥ ጭኗ ላይ ሰው ጭና አዎ ኖሬያታለሁ... ሴትነቷን ይዛው ሰውነቷ ጠፍቷት ፥ ስትደነባበር "አምላክሽ ወንድ ነው" ስትባል ያንጊዜ ለአይኗ ፥ ጠልታው ነበር እድሜ ለኔ ትበል! መድረሷን ነው እንጂ መውጣቷን ሳታውቀው ፥ ከአምላኳ ከፍታ እሷ ናት ያቺ ሴት! እራሷን ያገኘች ፥ እግሩ ስር ተደፍታ እሷ ናት ያቺ ሴት! ሽቶዋን ሸምታ ሽታዋን ቀይራ ፥ ጌታን የወደደች ከህመሟ ድና ፥ በአምላኳ ያበደች በማበዷ ሰዓት በምሬሻለው ቆብ ፥ ከወንድ መመንኮስ አይቻት አቃለሁ በሩሀማ ጨለማ ፥ ክርስቶስ ሲለኮስ። ግና... በሴቲቷ ታሪክ ፥ ናርዶሱና ጌታ እንደተሳከረ ያልነበረው እርሱ ያልነበርኩት እኔ ፥ አለመኖር ቀረ መኖሯ ሲበራ በደሏ ሲቀበር ፥ ንጋቷ ሲሰፋ ያልቆየው ናርዶሷ ፥ እፍ ያለው ሰው ጠፋ እፍፍፍ! እፍፍፍ! ተመልከች አንቺ ሴት በኔ ጠረን ነበር ፥ የሚደበቅ እድፍ። እፍፍፍ! በእኔ መስመር ላይ ነው ፥ እግዜርሽ የሚጽፍ። እፍፍፍ! ተመልከች አንቺ ሴት! ፥ ተመልከች አንቺ ዓለም! የእራት ግብዣን እንጂ የብልቃጥን ውድቀት አይቶ የሚከትብ ደህና ሃዋሪያ ፥ ለአመል እንኳን የለም! ሁሉም ደርሶ እስኪያዝ... ሁሉም ደርሶ እስኪያዝ... በከሀዲ ካህን ፥ በዕለተ ኀሙስ ማን ገብቶት ይጽፋል? ምሳሌ መሆኑን ለክርስቶስ ስቅለት ፥ የወደቀ ጠርሙስ ተመልከች አንቺ ሴት! ተመልከች አንቺ ሴት! ​​ ┈┈┈┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈ ✍🏽© ኤልያስ ሽታኹን ╰══•••┈ ┈ ┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈ Join and share @snetsehuf

❤️እስቲ አፍቅሩ ! ✍አሌክስ አብርሃም 💙በምድር ላይ ያልባከነ ምርጥ ጊዜ ማለት በፍቅር ያሳለፋችኋቸው ደይቃዎች ናቸው … እስቲ አፍቅሩ …መልካችሁ ምንም ይሁን አፍቅሩ …እድሚያችሁ ምንም ይሁን አፍቅሩ … ኑሮ ቢከብዳችሁ ራሱ ኑሮ ከከበደው ጋር ተፋቀሩ …ፍቅር ተያይዞ ማደግ ብቻ አይደለም ተያይዞ መውደቅም ነው ! በጥላቻና በድርቅና ከመቆም ለፍቅር መውደቅ ተለማመዱ ! 💜``አገር፣ህዝብ ፣ፖለቲካ በሚል ግዙፍ ነገር ውስጥ እየዳከራችሁ የጤፍ ቅንጣት አክላችሁ አትሙቱ … ፍቅር የሚባል እጅግ ረቂቅ አየር ወደውስጥ ሳቡና አገር አክሉ ! የማታፈቅሩበት አገር ምን ያደርግላችኋል? ገብስ ልታመርቱበት ነው? …የማታፈቀሩበት ህዝብ ምን ያደርግላችኋል ቀብራችሁን እንዲያደምቅ ነው …?የማታፈቅሩበት ፖለቲካ ምን ያደርግላችኋል? ፓርላማ ልተሰየሙበት ነው? …የማታፈቅሩበት ህገ መንግስት ምን ያደርግላችኋል ሲጀመር ይልተጣመራችሁትን መገንጠል እንዲፈቅድላችሁ ነው? … 💙ተያዩ ተነጋገሩ ትዝብት ጥርጣሬ ፍርሃትን ወደዛ ጣሉና በፈገግታ በተሞላ ፊታችሁ የወደዳችኋትን ወደእናተ ሳቡ የወደድሽውን ወደራስሽ ጋብዥ ! ተቃቀፉ …አብራችሁ ቡና ጠጡ … ተደዋወሉ ‹ቴክስት› ተላላኩ ! በሚወዷችሁ ሰዎች እቅፍ ውስጥ ስጋችሁ ይድላው !ነፍሳችሁም ደስ ይበለው !ተሳሳሙ …ለመጨረሻ ጊዜ በፍቅር ከተሳማችሁ ስንት ቀን ስንት ወር ስንት ዓመት ሆናችሁ … ኪሳራ ! ❤️ ህግ ስርዓትና አሉባልታ አትፍሩ …ደግሞ አትንቀዠቀዡ! ብቻ ማፍቀርም መፈቀርም ፈልጉ ..ራሳችሁን ብቻ ቀለል አድርጉት አየሩ ራሱ ወደየት እንደሚወስዳችሁ ያውቃል !…ለምርጫችሁ ብዙ መስፈርት አታስቀምጡለት ….ፈልጉ ተፈላለጉ ያለምንም ወሰን በነፍስም በስጋም ወደፍቅር ድንበር ቅረቡ ….ፀብ አትፍሩ መለያየት አያስጨንቃችሁ …ዘላለማዊ ጥላቻም ሆነ ጊዚያዊ ፍቅር ብሎ ነገር የለም ! አልፎ ሂያጅ ፍቅር የሚባል ነገር የለም ፍቅር ወደየትም አያልፍም …ፍቅር ራሱ መንገዱ ነው ! ተራመዱበት ፍጠኑበት …ብቻ አትቁሙ ! መንገድ ላይ በቆማችሁ ቁጥር ለሌላው እንቅፋት ትሆናላችሁ ! 💙ማህበረሰቡ የሰከነ... ረጋ ያለ... ቁም ነገር …ሁነኛ ሰው… የማይሆን ሰው…የሚሆን ሰው… እያለ ከጫነባችሁ የጉልት ሂሳብ ውጡና እብደታችሁ በሰፈረላችሁ ልክ ከዚህ ነዝናዛ አዕምሮ ተላቃችሁ በልባችሁ ደስታ ኑሩ ! ካለፈ ታሪካችሁ ውጡ …ካለፈ ህመማችሁ አገግሙ … በዘፈን ስም ሙሾ ከሚያስወርዱ ሙዚቃዎች ራቁ ….እንዴ…! …እንዳሰባችሁና እንደተመኛችሁ እስከመቸ ትኖራላችሁ ?! ባለፈ ጥላቻችሁ ከሬዲዮና ከምናምን በተለቃቀመ የመካካድና ተጎዳሁ ተሰበርኩ ታሪክ (ያውም እንደዛም ብለው ማፍቀር ላያቆሙ) በፍርሃት ተሸማቃችሀ ትኖራላችሁ እንዴ ?! ❤️አንዳንዴማ ልብሳችሁን ጣሉ …እራቁታችሁን መኖር ተለማመዱ …እራቁታችሁን ከሆናችሁ ልብስ አይኖራችሁም… ልብስ ከሌላችሁ ኪስ አይኖራችሁም ….ኪስ ከሌላችሁ በኪስ ከሚያዙ ነገሮች ሁሉ ነፃ ናችሁ … ምንም ነገር ልትይዙ የምትችሉት ብቸኛ ነገር ልባችሁ ብቻ ይሆናል … እንደልባችሁ ኑሩ ! የነፍሶቻችሁ ባሉን ላይ የተቋጠሩ ክሮችን ከራሳችሁ የፍርሃት እጅም ይሁን ከሌሎች ሰዎች የቁጥጥር እጅ ላይ አላቁና ወደሰፊው ህዋ ልቀቋቸው በአየሩ ላይ ይንሳፈፉ ! ✍ አሌክስ አብርሃም @snetsehuf

በዩቲዩብ ምን ማግኘት ይፈልጋሉ። ስብከቶች ፦(የተዋሕዶ ዕንቍ መምህራንን) መዝሙራት፦ (የንስሐ / የከበሮ) መንፈሳዊ ፊልሞች ፦(የተተረጎሙ / ያልተተረጎሙ) ማኅሌት (ወረቦች / የሌሊት ሥርዓተ ማኅሌት) ሁሉንም በማዕዶት ዘኦርቶዶክስ ቲዩብ ያገኛሉ። subscribe በማድረግ አገልግሎቱን ይደግፉ።