አጫጭር ግጥሞችና መጣጥፎች 📚
Open in Telegram
✔️📚ማንበብ ያሻግራል ❗️❗️❗️ በዚህ ቻናል እናንተን የሚመጥኑ የተለያዩ ግጥሞችን ፣ አጫጭር ና መሳጭ ታሪኮችን ታገኛላችሁ። እናንብብ ፤ በማንበባችን እናተርፋለን እንጂ ፤ ከቶ አንከስርም። @snetsehuf
Show more546
Subscribers
+324 hours
+127 days
+5230 days
Posts Archive
ጎልፃን
፨፨፨
ጎልፃን የግሪክ ቃል አይደለም፣ ላቲንም አይደለም ። እንዲሁም የግዕዝ የት-መጣ ያለው ቃልም አይደለም ። "ጎልፃን" የፒያሣ ናዝራውያን(ጠቢባን) የፈጠሩት ሁለት የአማርኛ ውህድ ቃል ነው ። ጎልማሳ እና ህፃን...በጉልምስናው እንደ ህፃን የሚያስብ በዕድሜው መግፋት ቁጥርን እንጂ የህይወት ልምድን ማካበት ያልቻለ ሰው "ጎልፃን" ይባላል ። ለፒያሳ ናዝራውያን ባልተፃፈ መዝገበ ቃላታቸው ውስጥ ።
፧
ጎልፃኖች ሁሉን ነገር ፓለቲካ ማድረግ መለያቸው ነው ። እናንተ አንድ ልታደርጉት ስለምታስቡት መልካም ሃሳብ ስታወሯቸው እነሱ ሃሳባችሁ መሆን የማይችልበትን መቶ መንገዶች ይጠቁሟችኋል ። የህይወታቸው ፍልሥፍናም ከዚህ ተቃራኒ ልማዳቸው የተቀዳ ነው ። ነገር በመጥለፍ እና የሚሆነው እንዳይሆን በማሠብ ።
፧
ብቻቸውን ሃገር ወዳድ ናቸው ። ብቻቸውን ለሃገር አሳቢ ናቸው ። ሁሉም ነገር የመንግስት ሥህተት ነው ። የነሱ የመሆን ፍላጎት ፍላጎት ብቻ ሆኖ የቀረው የመንግስት ሥህተት ነው ። በመንግስት አቅጣጫ የሚገኙ ጎልፃኖች ከሆኑ ደግሞ በተቃራኒው ናቸው ። እነዚህ መንግስት ሲሉ እነዚህ ደግሞ ህዝብ ይላሉ ። በቀኝም ሆነ በግራ በኩል የተሰለፉ ጎልፃኖች አንድ የሚያደርጋቸው ነገር ቢኖር በግለሠብ አመለካከት የማያምኑ መሆናቸው ነው ። ሁሉም ማለት ይቻላል መናጆዎች ናቸው ። ከመንጋጋት በስተቀር ነጠል ብለው መቆም አይችሉም ። በአንድነት እንጂ አንድ በመሆን አያምኑም ።
፧
ጎልፃኖች በግለሰብ አመለካከት የማያምኑበት ትልቁ ምክንያት ብቻቸውን ሆነው ስለማያውቁ ነው ። ለብቻ ቆም ብሎ ማሰብ ለጎልፃኖች ሞት ነው ። ዕድሜያቸውን የሚገፉት በብቸኞች ሃሳብ ላይ በማሳደም ስለሆነ ። ለብቻቸው ሲሆኑ የሚፈጠውን እውነት መሸከም ስለማይችሉ ግርርር ማለት እንጂ ነጠል ብሎ መገኘት እርማቸው ነው ።....
፧
ጎልፃኖች የዘር ሃረጋቸው የሚመዘዘው ከተረት እና ከጭፍን ስሜተኝነት ነው ። ናዝራውያን ዘወትር የሚያነሱት ምክንያተኝነት በጎልፃኖች ዘንድ የሚታየው እንደ አባታቸው ገዳይ ነው ። ሁሉን እሺ ባይ ያልሆነ ሰው ከእነሱ ጋር መኖር አይችልም ። እነሱም ሁሉን ከሚጠይቅ ሰው ጋር ሰላምታ የላቸውም ። ጎልፃኖች ሰውን ጠልፈው የሚጥሉበት አንድ መፈክር አላቸው ። " ከእኛ ጋር ያልሆነ ከማንም አይሆንም " ከራሱም ጭምር እንደማለት ነው እንግዲህ ።
፧
"እንደኔ ካላሠብክ......ሃሳብህን ትተህ እኛን ምሰል..."ከሚል የጅምላ አስተሳሰብ ናዝራውያኑ የተለዩ ስለሆኑ ሁለት በደም የሚፈላለጉ ጎልፃኖች በአንድ ናዝራዊ ፊት "ከየት የመጣ ፍቅር ነው?" እስኪባሉ ድረስ ወዳጃሞች ይሆናሉ ። " የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው " እንዲል የጎልፃኖች የተረት አባት...
፨፨፨
ምንጭ ፦ "የአዋጁ ግዜ ምልክት ፍለጋ እና ሌሎችም ሃሳቦች" ከሚለው የደራሲ ኤፍሬም ስዩም መጽሐፍ የተቀነጨበ
ስንት ጎልፃኖች በየግዜው ያጋጥሙን ይሆን ግን...?
፧
ፍርዱን ለአንባብያን...
ያነበቡትን ለወዳጅዎ ያጋሩ
ለመቀላቀል ደግሞ
👇👇👇
@snetsehuf
#እግረ_መንገድ ከተሰኘው የጋሽ ስብሀት መጽሐፍ የተቆነጠረች ንባብ...
፧
<<…ልጅ ሆኜ ነብሴን እጅግ ደስ የሚላት ጢቢ፣ ጢቢ ስጫወት ነበር። ጎረምሳ ሆኜ ነብሴን እጅግ ደስ የሚላት ሴት ልጅን ሳቅፍ ነበር። ዛሬ አርጅቼ ነብሴን እጅግ ደስ የሚላት ልጄ ስትስቅ ሳይ ነው። አሁን እነዚህን ሶስት እኔዎች ሳስተያያቸው አንድ ሰው ናቸው? እርግጠኛ መሆን ያስችላል። እኔ ሽማግሌውስ አንድም፣ አራትም ብሆን ይኸው እዚህ አለሁ። ያ እኔ የምለው ልጅና ያ እኔ የምለው ጎረምሳ ግን የት ሄዱ? የኔ ትውስታ ውስጥ ከልጅየውም ከጎረምሳውም ከብዙ በጥቂቱ እንደ ፊልም ተቀርፆ ይገኛል እንጂ እነሱ ግን የሉም። እኮ እንዴት እኔ ውስጥ ተቀርፀው ሊገኙ ቻሉ? ያን ጊዜ ልጅየው ሆነ ጎረምሳው ሲኖሩ እኔ እዚያ አልነበርኩም'ኮ። ገና አልመጣሁም ነበራ። ያን ጊዜ ያልነበርኩ ሰውዬ ትውስታ ውስጥ አሁን የሌሉ ያን ጊዜ የነበሩ ሰዎች ተቀርጸው ይገኛሉ። ይሄ እንዴት ሊሆን ቻለ? የጊዜና የትውስታ ምስጢራዊ ምትሀት ነው። ለመሆኑ ጊዘና ትውስታ ምንና ምን ናቸው?...>>
፧
ምንጭ ፦ እግረ-መንገድ...ገጽ 206-207
ስብሃት ገብረ እግዚአብሄር
ጋሽ ስብሃት እቺን መጠይቃዊ ሃሳብ ያሰፈራት ከጆ እና ሀሪ "አራቱ እኔዎች" ፍልስፍና ተነስቶ ነበር...እኛም በጋሽ ስብሀት ሀሳብ ውስጥ እራሳችንን ልንመለከትበት እንችላለን...እሄንን ስናነብ ያለንበትን የዕድሜ ደረጃ እና ያ ካለፈ በኋላ የሚኖረን ስሜት...አሁን በአፍላነታችን የምንመለከትበት አይንና በዕሜው በሰል ስንል የሚኖረን ትርጓሜ ልዩነት እንደሚኖረው የሚካድ አይደለም...
እግረ-መንገድ የሀሳብ እና የፍልስፍና ባህር ነው...እስካሁን ያልሰጠማችሁ ስመጡበት ለማለት እወዳለሁ...!
መልካም ንባብ
✔️📚ማንበብ ያሻግራል ❗️❗️❗️
በዚህ ቻናል እናንተን የሚመጥኑ የተለያዩ ግጥሞችን ፣ አጫጭር ና መሳጭ ታሪኮችን ታገኛላችሁ። እናንብብ ፤ በማንበባችን እናተርፋለን እንጂ ፤ ከቶ አንከስርም። @snetsehuf
መስታወት ፊት ቆሜ እንዲህ እላለሁ
(በእውቀቱ ስዩም)
"በለስ ፍሬ ባትሰጥ" ፤ሎሚ መሽተት ቢሳናት
ኤሊ ላባ ብትለብስ ፤ ወፌን ድንጋይ ቢጫናት
ሰማይ እንዳለት ቢወቀር
ጊዜ ደክሞት ቆሞ ቢቀር
ጨረቃ አመድ ብትቅም
ፀሀይ ጥርሷን ብትለቅም
ስልጣኔን ነቀዝ በልቶት ፤ ኦና ቢሆን አገር ምድሩ
ፒራሚዶች ባንድ ሌሊት፤ የኩበት ክምር ሆነው ቢያድሩ
ተፈጥሮ ለህዝብ ቅነሳ
ሰው በሰው ላይ ብታስነሳ
አንዱ ካንዱ ቢታረረድ
ጠፈር በከል ቢጋረድ
ሙሴን ባህር ቢበላው፤ የኖህ መርከብ ቢሰጥም
ህይወት ምስጢር ባትገልጥም
የድል ድርሻየን ጥዋ፤ ጭላጭ ሳይቀር እስካጣጥም
የምሻውን እስከማገኝ፤ ለመሸነፍ እጅ አልሰጥም
እንኳን ተስፋ ፤ ጢም አልቆርጥም::
@snetsehuf
#አለ ማወቅ
#ሰው ከአፈር ነው የሚሰራው ካሉኝ ጊዜ አንስቶ፥ ዝናብ በዘነበ ቁጥር በጎርፍ ተሸርሽሬ የማልቅ እየመሰለኝ እሰጋ ነበር - በልጅነቴ።
#የእናቴ ድምጽ እና ንግግር ከነዜማው የመጀመሪያው የርህራሄ ግንኙነቴ ነበር፤ ሰዎች ከርህራሄ ጋር የምንተዋወቀው በእናቶቻችን ድምጽ ነው።
#ረሀብ አንድም የእርዳታ ጥሪ ማቅረቢያ ... በመሰረታዊነት ግን ለመኖራችን የሌሎች ሰዎች መኖር አስፈላጊነት ማስታወሻ ነው።
#መኖር የሚጀምረው አለመኖርን በመፍራት ቢሆንም፥ የመኖር መሰረቱ ግን አለማወቅ ነው። በህይወት ውስጥ ካሉ ጥቂት ቋሚ ሁኔታዎች መካከል አንዱ አለማወቅ ነው።
#ጥልቅ ሃዘን ማለት ማዘን ሲያቅት ነው። ... ማዘን አለመቻል ግን ከሞት ይከፋል። ሰው በመጀመሪያ ስሜት ነው፥ ሌላው ሁሉ ተከታይ ነው። ሰው ስሜቱን ካጣ ጎዶሎ ነው።
#ያልተመለሱ ጥያቄዎች የመኖር ሞተሮች ናቸው።
#የመናገር ነጻነት ሮጦ ከማምለጥ አቅም ጋር ካልተቆራኘ ትርፉ ድካም ነው።
#አለማወቅ
#ዳዊት ወንድማገኝ
Share @snetsehuf
አንድ ካህን በሞቃታማ ዕለት ብቻቸውን ጭር ባለ ጎዳና ላይ ሲሔዱ አንድ መሣሪያ ያነገተ የሚያስፈራ ሰው ድንገት ከዛፎች መሃል ዘልሎ ወጣና ከፊታቸው ቆመ። ቄሱ ላይ አፍጥጦ "እስካሁን ዘጠና ዘጠኝ ሰዎች ገድያለሁ አንተ መቶኛው ትሆናለህ!" አላቸው።
ካህኑም መልሰው "ለመሞት ዝግጁ ነኝ ፣ ነገር ግን በጣም ስለጠማኝ ትንሽ ውኃ ሥጠኝና ትገድለኛለህ" አሉት። ነፍሰ ገዳዩ ለአፍታ ግራ ከተጋባ በኋላ በቄሱ ላይ መሣሪያውን እንደደገነ በዛፎቹ መካከል ካለው ምሽጉ ውስጥ በኩባያ ውኃ አምጥቶ እንዲጠጡ ሠጣቸው። ካህኑ ውኃውን እየጠጡ እያለ ግን ሽፍታው ድንገት በልብ ድካም ሕይወቱ አለፈች።
የዚህን ሰው ነፍስ ወደ ገነት ለመውሰድ መላእክት በመጡ ጊዜ አጋንንት ነፍሱ የእኛ ፈንታ ናት ብለው ተከራከሯቸው። "ይህ ሰው ዘጠና ዘጠኝ ሰዎችን የገደለ ሲሆን እጅግ ብዙ ትንንሽ ኃጢአቶችንም ፈጽሟል። ነፍሱ የሚገባው ለእኛ ነው" አሉ። መላእክቱ ግን እንዲህ ብለው ለአጋንንቱ መለሱላቸው "ያደረገው እንዳለ ሆኖ ይህ ሰው ከሠራቸው ኃጢአቶች የበለጠ የሚመዝኑ በክርስቶስ ወንጌል የታዘዙ ሁለት ታላላቅ ተግባራትን ፈጽሟል። የመጀመሪያው ዘጠና ዘጠኝ ሰው እንደገደለ ለካህን መናዘዙ ሲሆን ሁለተኛው ለተጠማ ውኃ ማጠጣቱ ነው!" አሏቸው።
━━━━━━━━━━━━━━━━━━━━━━━ ቅዱስ ኒኮላይ ቬሊሚሮቪች
ከወደዳችሁት share @snetsehuf
የልደት ኩሸት
(በእውቀቱ ስዩም)
የተወለድሁበት ዘመን እጅግ ከመራቁ የተነሳ አመተ -ምህረት ይሁን አመተ- ፍዳ ተዘንግቶኛል፤ የሚካኤል በአል ሁለት ቀን ሲቀረው እናቴ የምጥ ምልክት ይታይባት ጀመር ፤ እማየ ፥ ድፍን ማንኩሳን ያዋለዱትን ፥ አዋላጅ ወይዘሮ አዛለች ፈጥነው እንዲደርሱ መልክት ላከች፤ አባቴ ግን ሀሳቡን በመቃወም ዘመናዊ ሀኪም እና አምቡላንስ ለመጥራት ወደ ፍኖተሰላም ከተማ ገሰገሰ፤ ይህንን የሰሙ የአዋላጂቱ የወይዘሮ አዛለች ጎረምሳ ልጆች ፤ ከፍኖተሰላም ወደ ማንኩሳ እሚያስገባውን መንገድ በድንጋይ እና በአጣና ዘጉት፤
አፌን የፈታሁት በተወለድሁ በጥቂት ወራት ውስጥ ነው፤ ትዝ ይለኛል፤ አባቴ እና አያቴ እንደ ጥምቀት እምቧይ እየተቀባበሉ ሲያጫውቱኝ ወይም ሲጫወቱብኝ ቆዩ፤ ድንገት “ አ” እሚል ቃል ካፌ ወጣ፤ አባቴ “ አባየ” ሊል ፈልጎኮ ነው “ ብሎ ፈነደቀ፤ አያቴ ደግሞ “ አያቴ ለማለት እንዳሰበ ያፍ አከፋፈቱ ያስታውቃል” ብሎ ገገመ፤ በግራና ቀኜ ቆመው" አይዞህ ! ጨርሰው ! ልትል የፈለግኸውን ጨርሰው “ እያሉ ያጣድፉኝ ጀመር፤
በመጨረሻ “ አትሞትም እንዴ ሼባው ?” የሚል ቃል ካንደበቴ ሲወጣ አያቴ ራሱን ስቶ ወደቀ፡ ፡
በልጅነቴ በጣም አስቸጋሪ ልጅ ነበርኩ፤ እናቴ የሆነ ጊዜ ላይ በጣም ምርር ስላላት “ ባጭር ያስቀርህ “ ብላ ረገመችኝ ፤
ቆይታ ፥ንዴቷ ሲበርድላት በማንኩሳ ሚካኤል ገዳም የታወቁና የበቁ ባህታዊ ዘንድ ሄዳ ፤ “ ልጄ! ለጊዜው ቢያናድደኝ ፤ ቢያስከፋኝ ባጭር ያስቀርህ ብየ ረገምኩት ፤ እባክዎ ርግማኑ እንዲከሽፍ ያድርጉልኝ “ ብላ ተማጸነች ፤ ባህታዊው “ ርግማኑን አንዴ ካፍሽ ከወጣ በሁዋላ ሙሉበሙሉ ማክሸፍ አይቻልም፤ ይሁን እንጂ ሶሰት ቀን ሱባኤ ከገባሽ፥ ርግማኑ ከእድሜው ላይ ቀርቶ በቁመቱ ላይ እንዲደርስበት ማድረግ ይቻላል” ብለው አሰናበቷት፤
ዛሬ ልደቴ መሆኔን ረስቸው ነበር፤ ከተከራየሁበት ኮንዶሚኒየም ስወጣ ጎረቤቱ ‘ እንኩዋን ተወለድህ አለኝ” አመስግኘ አለፍ ስል፤ ግቢውን የምትጠርገው ወዛደር “ መልካም ልደት “ ብላ ተጠመጠመችብኝ ፤ በሩ አካባቢ ስደርስ ሌላ ነዋሪ የመኪና ጥሩንባውን እንደ ሰርግ አጃቢ በረጅሙ ከለቀቀ በሀዋላ “ Happy birthday “ካለኝ በሁዋላ “ ደሞ ይሄን እንዳትጸፈው “ ብሎኝ አለፈ፤
ይሄን ሲታዘብ የቆየው የኮንዶሚኒየሙ ዘበኛ እንዲህ አለኝ፥
“ እዚህ ግቢ ብዙ ሰው ያውቅሀል! የዲሽ ሰራተኛ ነህ እንዴ”
ከወደዱት ለወዳጅዎ ያጋሩት!
@snetsehuf
#ማንዴላ (MADIBA)
ኔልሰን ማንዴላ የህግ ትምህርት በሚማሩበት ወቅት ነጭ ፕሮፌሰር አስተማሪ ነበራቸው። ስሙም ፒተር ይበላል...
አንድ ቀን ፕሮፌሰር ፒተር በአንድ ምግብ ቤት ምግባቸውን እየበሉ ሳለ ማንዴላ በአጋጣሚ ምግብ ይዘው ከአጠገባቸው ይቀመጣሉ..
ዘረኛው ፒተርም 🗣 "አቶ ማንዴላ! አሳማና 'እርግብ ለመብል አብረው አይቀመጡም!" አላቸው።
ኔልሰን ማንዴላም 🗣 "አይጨነቁ ፕሮፌሰር በርሬ እሄዳለሁ" ብሏቸው ሌላ ወንበር ላይ ይቀመጣሉ...
በዚህ የተናደደው ፒተር በሌላ ቀን ቂሙን ሊወጣ ያስባል። አንድ ቀንም
ፕሮፌሰሩ ክላስ ውስጥ እያስተማሩ
🗣 " ማንዴላ በመንገድ ላይ እየሄድክ ሁለት ቦርሳዎችን ብታገኝና በአንደኛው
ቦርሳ 'ገንዘብ' በሌላኛው ቦርሳ ደግሞ 'ጥበብ' ቢኖር የትኛውን ትወስዳለህ?" ብሎ ማንዴላን ጠየቀው....
ማንዴላም 🗣 " ገንዘቡን እወስደዋለሁ" …ብሎ መለሰለት። ፕሮፌሰሩ "አንተ ሞኝ ነህ እኔ አንተን ብሆን ኖሮ ጥበብ ያለበትን ቦርሳ እወስድ ነበር" ማንዴላ ፈገግ አለና "ልክ ነህ ማንም የሌለውን ነው የሚወስደው" ።
በዚህ ሁሉ ነገር የተበሳጨው ፕሮፌሰር ፒተር የማንዴላ የፈተና ወረቀት ላይ 'ደደብ' ብሎ ይፅፋል..
ሌሎች ተማሪዎች የታረመላቸውን የፈተና ወረቀት ሲያዩ ማንዴላ ደደብ የሚለውን ፅሁፍ ከወረቀቱ ላይ አየና ተገረመ ከዛም ወደ ፕሮፌሰሩ ሄዶ
🗣 " ይቅርታ ቲቸር ፊርማህን ብቻ ነው ያስቀመጥክልኝ ውጤቴን ረስተኸዋል"
ብሎት እርፍ ፡፡
@snetsehuf
የህይወት ዋጋው ስንት ነው?
ከእለታት ባንዱ ቀን አንድ ታዳጊ አባቱን “የህይወት ዋጋው ስንት ነው?” ሲል ጠየቀው፡፡ አባትም መልስ በመስጠት ፈንታ ልጁን እንዲህ ሲል አዘዘው፡፡ “እንካ ይህንን የድንጋይ ቁራጭ...ወደ ገበያ ውሰደው፡፡ ሰዎችም ዋጋውን ከጠየቁህ በጣቶችህ ሁለት ቁጥርን ብቻ አሳያቸው እንጂ ምንም አትናገር” አለው፡፡ ልጁም ድንጋዩን ወሰደ፡፡ ወጥቶም በገበያ መሃል ቆመ፡፡ አንዲት ሴትም መጣች፡፡ “ይህ ድንጋይ ዋጋው ስንት ነው? ብትሸጥልኝ ወስጄ ግቢዬ ውስጥ አስቀምጠዋለሁ” አለችው፡፡ ልጁም እንደታዘዘው ምንም ሳይናገር ሁለት ጣቶቹን አሳያት፡፡ እሷም አለች “ሁለት ብር?
እወስደዋለሁ!!”
ልጁም ወደ ቤቱ ተመለሰ፡፡ በገበያ ያጋጠመውንም ለአባቱ ነገረው፡፡
አባትየውም አለው “አሁን ደግሞ ድንጋዩን ይዘህ ወደ ሙዚየም ሂድ፡፡ ዋጋውን ሲጠይቁህም ሁለት ጣቶችህን አሳይ”፡፡ ልጁም ወደ ሙዚየም ወጣ፡፡ ገዢም መጥቶ ዋጋ በጠየቀው ጊዜ ሁለት ጣቶቹን አሳየው፡፡ ገዢውም “ሁለት መቶ ብር? እወስደዋለሁ!” አለው፡፡ ልጁም በድንጋጤ ወደ ቤቱ ተመለሰ፡፡ ያጋጠመውንም ለአባቱ ነገረው፡፡
አባትየውም ተናገረ፡፡ “አሁን ደግሞ በመጨረሻ ድንጋዩን ይዘህ ወደ የከበሩ ማዕድናት መሸጫ ሂድ ለባለቤቱም አሳየው”
አለው፡፡ ልጁም ሄደ፡፡ ለሱቁም ባለቤት አሳየው፡፡ የሱቁ ባለቤት በመገረም “ይህ እኮ አለም ላይ እጅግ ውድ ከሆኑ የከበሩ ድንጋዮች አንዱ ነው” አለ፡፡ “ከየት አገኘኸው? ስንትስ ትሸጠዋለህ?” ሲል ጠየቀው፡፡ ልጁም ምንም ሳይናገር ሁለት ጣቶቹን አሳየ፡፡
የሱቁም ባለቤት አለ.... “ይህንን ድንጋይ በሁለት መቶ ሺህ ብር እወስደዋለሁ፡፡”
ልጁም በመገረም እየሮጠ ወደ ቤቱ ተመልሶ ያጋጠመውን ለአባቱ ነገረው፡፡
አባትየውም “ልጄ አሁን የህይወትህ ዋጋ ተገልጦልሃል” አለው፡፡
አየህ የመጣህበት ቦታ፣ ዘርህ፣ ሃይማኖትህ፣ የቤተሰቦችህ ሃብት፣ የተወለድክበት ቦታ ልዩነት አይፈጥርም፡፡ ዋናው ራስህን የምታስቀምጥበት ቦታ፣ ራስህን የምታገኝበት የሰዎች ስብስብ ነው፡፡ ልዩነቱ ያለው ራስህን ለመሸከም በምትመርጥበት መንገድ ነው፡፡ ህይወትህን ሙሉ የሁለት ብር ድንጋይ ዋጋ ስትሰጠው ኖረህ ይሆናል፡፡ ህይወትህን ሙሉ የኖርከው ዋጋህ ሁለት ብር ብቻ እንደሆነ በሚያስቡ ሰዎች ተከበህ ይሆናል፡፡ ነገር ግን እያንዳንዱ ሰው ውድ የሆነ የከበረ ድንጋይ በውስጡ ይዟል፡፡ ልዩነቱም ያለው ውስጣችን
ያለውን የከበረ ድንጋይ አይተው ዋጋ በሚሰጡን ሰዎች መሃል መገኘትን ስንመርጥ ነው፡፡ ራሳችንን በገበያ ወይም በከበሩ ማዕድናት ሱቅ የማስቀመጥ ምርጫው አለን፡፡ በሌሎች ሰዎች ውስጥ ያለውንም ውድ ዋጋ ለማየት ምርጫው የኛው ነው፡፡ ሌሎች ሰዎችም የከበረ ዋጋቸውን እንዲረዱ ማድረግ
እንችላለን፡፡ አብረህ የምትውላቸውን ሰዎች በጥንቃቄ ምረጥ፡፡ ይህ በህይወትህ ልዩነትን ይፈጥራልና፡፡
ሻውን ቡንደናሂራን ከተረከው የተተረጎመ
@snetsehuf
#ሀገር_ማለት የኔ ልጅ - በዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ
ሀገር ማለት ልጄ፣ ሀገር ማለት፣
እንዳይመስልሽ የተወለድሽበት ቦታ ፣
የተወለድሽበት አፈር፤
እትብትሽ የተቀበረበት ፣ ቀድመሽ የተነፈሽው
አየር፤
ብቻ እንዳይመስልሽ።
ሀገር ረቂቅ ነው ቃሉ፤
አገር ውስብስብ ነው ውሉ።
ሀገር ማለት ልጄ ፣
ሀገር ማለት ምስል ነው ፣በህሊና የምታኖሪው፤
ከማማ ማህጸን ከወጣሽበት ቀን ጀምሮ ፤
በጠባሽው ጡት፣ ወይም ጡጦ ፣
በዳህሽበት ደጃፍ፣ በወደቅሽበት ፈፋ፤
በተማርሽበት ትምህርት ቤት፣
በተሻገርሽው ዥረት ፤
በተሳልሽበት ታቦት ፣ወይ በተማፀንሽው ከራማ ፤
በእውቀትሽና በህይወትሽ፣
በእውነትሽና በስሜትሽ ፣
የምትቀበይው ምስል ነው ፣ በህሊናሽ
የምታኖሪው፤
ስትወጅ ሰንደቅ ታደርጊው፡፡
ቢያስጠላሽ የማትቀይሪው።
ሀገር ማለት የኔ ልጅ ፣
ሀገር ማለት ቋንቋ ነው በአንደበት አይናገሩት፤
በጆሮ አያዳምጡት፤
አማርኛ ኦሮሞኛ ፣ አፋርኛ ቅማንተኛ፤
ጉራግኛ ወይ ትግርኛ፣ ብለው የማይፈርጁት ።
የኔ ልጅ፣
አማራውና አፋሩ፣ ኦሮሞው ሲዳማው ፣
ጉራጌኛሽን ባይሰማ፤
ያለገባው እንዳይመስልሽ ፣ ሀዘን ደስታሽን
ያልተጋራ።
የየልቦናችንን ሀቅ፣ ፍንትው አድርጎ እያሳየ፤
ህዝቦችን ከሰንደቃቸው፣ አስተሳስሮ ያቆየ፡፡
ሀገር ቋንቋ ነው ልጄ፣ የሁለንተናሽ መስታወት፤
ሲከፋሽ ትሽሽጊበት ፣ ሲደላሽ ትኳኳየዪበት ።
የኔ ልጅ ፣
አያት ቅም አያትሽ ፣ሰላም ሲሆን ከወልቂጤ
አድማስ ማዶ ሸቅጦ፣
ሲያቀና ወረቱን፤
ለእኔና ለአንቺ መኖሪያ፣ ሲያቀና ቀዬና ቤቱን፤
ሀገር ጠላት ሲደፍራትም፣ ጦሩን ሰብቆ እየፎከረ፤
ከኦሮሞው ከትግሬው፣ ከአፋሩ ከወላይታው፣ . . .
ከሁሉም የጦቢያ ልጆች ፣
አጥንቱን እየማገረ፤
ሀገር ይሉት መግባቢያ ፣ሰንደቅ ይሉት መለያ ፣
ሲያቆይልሽ፤
በጉራግኛ ማትገልጭው፣ በጎጥ የማትገድቢው፣
ስንት አለ ታሪክ መሰለሽ!
እና የእኔ ልጅ፣
ለዚህ ነው ሀገር ይሉት ቋንቋ፣ ላንቺ
የሚያስፈልግሽ፤
ከወልቂጤ አድማስ ማዶ፣ ለተሳሰረ ታሪክሽ፤
ከወልቂጤ አድማስ ማዶ ፣ ለተወጠነው
እድገትሽ።
እና ልብ በይ ልጄ ! ሀገር ማለት ቋንቋ ነው፣
ባንደበት አይናገሩት፤
በጆሮ አያዳምጡት።
ከሁሉም በላይ ልጄ ፣
ተፈጥሮ ከቸረው በረከት ፣ የላቡን ፍሬ የሚበላ፤
ሀገር ማለት ወገን ነው፣ የእኔ የምትይው ከለላ።
ትመኪበት ጥሪት፣ ትደምቂበት ብርሃንሽ፤
የሰብዕናሽ ግማሽ ውል ፣ወገን ነው ማሕተምሽ፡፡
ዜጋው ነው ልጄ ሀገርሽ።
መሬትማ የእኔ ልጅ፣
በእምነትሽና እውቀትሽ፣ ከልለሽ ካላበጀሽው፤
ለእድገትሽ ውጥን ካልሆነ ፣ለተስፋሽ
ካልተመገብሽው፤
መሬትማ ባዳ ነው፣ ላለማው የሚለማ፤
ለተስማማው የሚስማማ።
ዥረቱም ግድ የለውም ፣ ቦይ ለማሰለት ይፈሳል
ተራራውም ደንቆሮ ነው ፣ ለቦረቦረው ይበሳል።
መሬቱ አደለም የኔ ልጅ፣ እድርተኛው ነው
ሃገርሽ፤
ስትቸገሪ ታድጎ፣ ስትታመሚ አስታሞ፣ ስትሞቺ
አፈር ሚያለብስሽ።
በእጅሽ ያለ ብሩህ ጽጌ ፣ ሰው ነው ልጄ ሀገርሽ፤
ወገን ነው ልጄ ሀገርሽ።
እና የኔ ልጅ፣
ሀገር ረቂቅ ነው ቃሉ፤
ሀገር ውስብስብ ነው ውሉ።
🔘በድሉ ዋቅጅራ🔘
Join and share
@snetsehuf
ከሚያዛጋ አንበሳ … ቆርጫለሁ እንጥል
በጥቅሻ ነበር … የሴት ዘርን ምጥል
ማን ተገዳደረኝ … በጦርነት በጥል ?
እግዜር መሀንዲሱ
ሰይጣን ተንከሲሱ
በፍቅር በጥላቻ … ገጠሙኝ ለየቅል
እግዜርን ሰቀልኩት…
ተረታ ዲያብሎስ … አምላኩን ስሰቅል ።
ነጥዬ እነቅላለሁ … ቅንድብ ከቁንጫ
ተኩሼ እጥላለሁ … ትንኝ በጠመንጃ
ቆንጆ ሴት ላከብኝ … ዘንድሮን ግን እንጃ !
በመቃቃር እቶን … በጥላቻ ሰደድ
ምድር ተንተክትካ … እንደቋያ ስትነድ
እኔን የገደለኝ … ሰው ማፍቀር ሰው መውደድ !
@snetsehuf
#ስለምወድሽ_አላገባሽም
የምልሽ ነገር ፥ ቢገባሽም ባይገባሽም
ስለምወድሽ አላገባሽም።
የምን ችቦ አይሞላም? ፥ የምን አሸወይና?
በሰው አፍ መፈተል ፥ በሰው አፍ ሽመና
የምን ሽማግሌ? ፥ የምን ጥሎሽ መጣል?
የምወደው ልብሽ ፥ ስንት ብር ያወጣል?
ስንት ብር? ፥ ስንት ወርቅ?
ስንት ከብት? ፥ ስንት ጨርቅ?
ስንት ምን ብሰጥሽ ፥ አንቺን ይመዝናል?
አንቺን ይወክላል ፥ ያንቺን ስም ያክላል?
ድካም ነው ይቅርብን! ፥ ጉዳጉድ ማብዛቱ
የሳቅሽ አፀድ ነው ፥ መኖሬ ግዛቱ።
ልክ እንደዚህ...
ክራር በጣቶቼ ፥ ባልችልም መደርደር
አንቺን እየነካው
ሙዚቃ ባይሆንም
የሰማው መሰለኝ ፥ ጥቂት ዜማ ነገር
ቃላትን በሃሳብ
ተርኬ መንዝሬ ፥ ሰውን ባላሰጥም
ከአጠገቤ ሆነሽ
የሰማው መሰለኝ ፥ አንድ ትንሽ ግጥም
በነፍስ የተፃፈ ፥ በነፍስ የሚነበብ
በነፍስ የሚገለጥ ፥ ደግሞም የሚከተብ
በነፍስ የተሳለ ፥ በነፍስ የተኳለ
ልክ እንደዚ ያለ
አንቺዬ...
እድሜ ላንቺ እድሜ
ቅዳሴ አስካድሺኝ ፥ ኪዳን አስረሳሺኝ
"ሰው ቀን የለውም! ፥ ቅጽነት ነው!" እያልሺኝ
እድሜ ላንቺ እድሜ...
ያነበብኩት ገድል
ያ የእልፍ ድርሳን ፥ የቃረንኩት መጣፍ
ብነካሽ ሄድኩበት ፥ እንደመሬት ምንጣፍ
አቤት! አቤት! አቤት!
ይህንን ቢሰሙ ፥ የኔታ ምን ይሉ?
ያኖርኩትን ኪዳን ፥ ድንግልና አንግሼ
"ታቦቴ ነሽ" አልኩኝ ፥ መቅደሴን አፍርሼ
እንኳን ከአንድ ካህን ፥ ከአንድ አማኝ
የማይሆን ድርጊት ፥ እየፈፀምኩ እየተኮነንኩኝ
ያን ሁሉ እምነቴን ፥ ምን ስትዪኝ ካድኩኝ?
እንተዋወቅ!
ገዳሙን ልዘንጋው ፥ ባንቺ እንድመነኩስ
ከአዲስ ቤቴ ገቢ
ከመፍራቴ ብዛት
ውሃ ልጣድልሽ ፥ ቡታጋዝ ሳለኩስ
ልፈር በውርደቴ! ፥ ዳግም ልንተፋተፍ
የማረገው ይጥፋኝ ፥ የተላጠ ልክተፍ
"ሳቂ ከት ብልሽ!" ፥ አከራዬ ይስሙ!
አገኘ መባል ነው ፥ ሰው የመሆን ስሙ
እስቲ እንተዋወቅ!
በርዶናል እያልን ፥ አውቀን ተጠጋግተን
ልባችን ይምታብን ፥ የምንለው አጥተን
ዝምታ ነግሶብን ፥ እየተነፈስን
እቃ ጠፋን እንበል ፥ እጅ እየዳሰስን
ምነው ባልመጣውኝ! ፥ የሚያስብል ፍርሃትሽ
"ምነው ነይ ባላልኳት?" ፥ ከአፌ ሊያመልጥልሽ?
ትንሽ እየቀረኝ ፥ ትንሽ እየቀረሽ
ጆሮ ጌጥሽ ጋር ሆንኩ ፥ ማህተቤ ጋር ደረስሽ
ውዴ
ይህ ሁሉ ስብከቴ ፥ ቢገባሽም ባይገባሽም
ስለምወድሽ አላገባሽም።
የአገባሁሽ እንደው...
ባለቤት በሚል ስም ፥ አጥሬው አጥሬሽ
ከአንድ እቃ እኩል ፥ ቆጥረሽኝ ቆጠሬሽ
እንዳንረሳሳ...
እሽ በይ ዓለሜ! ፥ መጋባት እንርሳ።
ባታገቢኝ ይቅር
ባላገባሽ ይቅር ፥ ቀኔ እንዳይለያይ
ሰው ከእጁ ያለን ሰው ፥ ከመዳብ ነው የሚያይ!
ቤቴ ካገባሁሽ...
ስለምድሽ ስለምጂኝ ፥ ሃሳቤ ግድ የለው
ያው ሰው አይደለው!
መልመድ ያረክሰናል ፥ ጠዐምን ይሸኛል
"አለች" እንደማለት ፥ ንቀት የት ይገኛል!?
ልጅነቴ ይኑር ፥ እደግ ፍርሃቴ
በምን ልሙላው ያልኩት ፥ ደግሞ ይጥበብ ቤቴ
እንዳዲስ ፃፊኝ ፥ እንዳዲስ እንቀልም
ፍቅረኛ እንደሆንን ፥ ማርጀት ነው የኔ ህልም
የምን ችቦ አይሞላም? ፥ የምን ጥሎሽ መጣል?
የምወደው ልብሽ ፥ ስንት ብር ያወጣል?
ጉዳጉድ ነው ጉዱ
ባይጨፈር ይቅር ፥ የቤተ-ዘመዱ
እድሜ ላንቺ እድሜ ፥ ህልሜን አስቀየርሺኝ!
"ሰው ዘመን የለውም! ቅጽበት ነው!" እያልሺኝ
አሁን ያልኩሽ ሁሉ ፥ ቢገባሽም ባይገባሽም
ስለምወድሽ አላገባሽም።
┈┈┈┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈
✍🏽© ኤልያስ ሽታኹን
╰══•••┈ ┈ ┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈
@snetsehuf
#የአራት_ኪሎ
#ኪሎ
በአራት ኪሎ አጸድ
ታሪክና ሥልጣን ፥ በዘመን ሲቀለም
መታዘብ አይቀርም
ግራ የገባውን ፥ የጦቢያን ዓለም
በልጅነት አመት ፥ በምስኪኗ ነፍሴ
በጀንበር ስንጓዝ ፥ ለጥር ሥላሴ
ድንገት!
ከመንገዱ በላይ...
አታልፉም እያለ ፥ ፖሊሱ ሲገታን
ሓሳብ ተሸክመን ፥ ስንርቀው ጌታን
ተከልክለን መሄድ ፥ መራመድ ካደምን
ጥያቄ ነበረን ፥ እኮ ለምን ?
መልስ
የሀገሪቱ መሪ ፥ በመንገድ ስላሉ አትነቃነቁ
እሳቸው እስኪያልፉ ፥ ቆማችሁ ጠብቁ!
ጀመርና ምርምር
ልጅ እንደው ፥ ጅል አይምር
ምርምር ፩
ያንን ሁሉ አማኝ
አታልፉም የሚሉን ፥ አታልፍም የሚሏቸው
ጸሎቱ ምሕሏው
መሪን አውርድልን ፥ መሆኑ ገብቷቸው ?
ምርምር ፪
የምእመን ልመና
ደግ ንጉሥ አምጣ ፥ በጎ መሪ እንኳን ላክ ?
ወትሮስ ምን ሊጠየቅ
ቤተ-መንግሥት ጎን ፥ የተገኘን አምላክ።
ምርምር ፫
የፖለቲካ ጽንስ ፥ በጊዜ ሲታቀፍ
በህዝቡ መቆም ነው
የንጉሥ አካሄድ ፥ የማይደናቀፍ
ጠቢብ ገዢ ማለት ፥ ቅኔው ሲተረተር
እስከሚያልፉ ድረስ
ተራማጅን ሁሉ ፥ በአለበት መገተር።
በአራት ኪሎ አጸድ
ታሪክና ሥልጣን ፥ በዘመን ሲቀለም
መታዘብ አይቀርም
ግራ የገባውን ፥ የሀገሬን ቀለም
ከመንግሥት ፓርላማ
መካከል የቆመ ፥ የሥላሴ ዋርካ
ጠመንጃ አጅቦት ፥ ከቶ ማይነካ
ከካህኑ ይልቅ
ጦረኛ የበዛው ፥ የደብሩ ኪዳን
የአማኙ ጸሎት
ከሲኦል አይደለም ፥ ከሰደፍ ነው መዳን።
በፓርላማው ጫፍ ላይ ፥ ከበላይ ከአናቱ
ሰቅለው ያስቀመጡት ፥ አይሰራም ሰዓቱ።
እንደ መሥሪያ ቤቱ ።
በመሥሪያ ቤት ውስጥ
እጅ እየተነሳ ፥ እንባ እየወደቀ
ከቤተ-መቅደሱ
ወርሰው ነው መሰለኝ
ያገኙትን ሁሉ ፥ የሚሉት ጸደቀ
ቅኔ ማህሌቱ
ከቤተ-ፓርላማው ፥ ስለተሳከረ
የአምናውን አርሞት
ባለሱፍ በሙሉ
አይኑን እንደገለጠ ፥ መተኛት ጀመረ
ተሻሻለ...
በረቂቋ ሀገር
በፖርላማው ጓዳ ፥ ካገኘን አማካይ
አባሉ አይደለም
ድምጽ ቆጣሪው ነው ፥ የህዝቡ ተወካይ።
መቁጠር ነው...
መቁጠር ነው...
መቁጠር ነው...
ያጸደቀን መዳፍ ፥ የወሰነን ወንበር
ስንት እጅ ነው? ፥ በእጅ ወድቆ የሚሰባበር
በአራት ኪሎ አጸድ
ቅድስት ሥላሴን ፥ የሻተ መሳለም
ማየቱ አይቀርም
ግራ የገባውን ፥ የጦቢያን ዓለም
በሥላሴ አጸድ
እማማ ጦቢያ
ሰብስባ ስትቀብር ፥ በታንቡር በዕንባ
ቀብር ይፋለሳል
ከመቅደሱ አጠገብ ፥ ከፓርላማው ጀርባ
ሰው ስሙን ቀይሮ ፥ አፈር ተጠልሎ
በአራት ኪሎ ሰማይ
ማየትህ አይቀርም
የጦቢያም ዋርካ
የጦቢያም እሾህ ፥ በአንድ አፈር ተጥሎ።
የዓለም ፈጣሪ
በአንድ እያደሩ ፥ ከሀገር ከመሪ
የተረሳ ወገን
በቢጫ አረንጓዴ ፥ አጥር የታጠረ
የህዝብ ተወካይ
ከፊቱ አቁሞ ፥ ሳይገኝ የቀረ
ከአርበኛ ህንጻ ሥር
ማንነቱን ያጣ ፥ ቀልቡ የቀለለው
አራት ኪሎ ራሱ
ኪሎው ፥ ምን ያህል ነው?
ቅኔ ነው!
ምስጢር ነው! ፥ ለንጉሥ ፍርሐት
ረቂቅ ግንዝ ነው
መፈታት የሚሻ ፥ የዘመን ፍትሐት
በፍትሐት እውነት
የወታደሩን ደንብ ፥ ቃሉን ተቀብዬ
ይኸው እቆማለሁ
የዘመኔ መሪ ፥ እስኪያልፉ ብዬ
ተራማጅ አራማጅ ፥ በአንድ ላይ ሲያስቆም
ትርጉሙ ብዙ ነው!
መሪያችን እስኪያልፉ ፥ ህዝብ ሆኖ መቆም
ባለጊዜ እስኪሄድ
አንዱ በሌላው ላይ ፥ ጣት እየጠቆመ
ዘመን እንደመሪው ፥ እስኪያልፍ እየቆመ
የሐበሻ ምሱ...
ቀጥ ብሎ ከርሞ ፥ ቁም በተባለበት
ንጉሥ አልፎም እንኳን
ሂድ ቢባል አይሄድም ፥ መገተር ለምዶበት።
ቁም በል በቆምክበት።
┈┈┈┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈
✍🏽© ኤልያስ ሽታኹን
╰══•••┈ ┈ ┈•◦●◉❖◉●••
"በኔ መንገድ ካልሔድክ
መንገድህ ገደል ነው" ፥ ማለት የሚከጅል
"እንደኔ ካላሰብክ
ማሰብ አትችልም" ፥ ሊል የሚዳዳው ጅል
በህይወት መንገድ ላይ...
እንደራሴ ስጓዝ ፥ ነፍሴ ምትሞግተው
ስንት ገደል አለ
"ድልድይህ ነኝ" የሚል ፥ መሻገር ሲያቅተው ።
┈┈┈┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈
✍🏽© በላይ በቀለ ወያ
╰══•••┈ ┈ ┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈
@snetsehuf
⏫የቀጠለ
ምስኪኒቷ እናቴ!
በሞላ ጎዳና
ባልጠበበ ድንበር ፥ በዘር ገመድ ታግዳ
ነጻ ነኝ ትላለች
መንጋነት ያሰረው ፥ ባሪያ ትውልድ ወልዳ፡፡
የጀግንነት እብሪት
ልባችንን ደፍኖት ፥ ማሰብ እየከዳን
እንዴት ነው ነጻነት
እንዳበደ ፈረስ ፥ ስሜት እየነዳን፡፡
ገድሎ የመንገስ ጥማት
ጩኀት ላገነነ ፥ አመጽ ላጀገነው
ለዚህ ምስኪን ትውልድ
በጅምላ እየነዱት
በመንጋ እያሰበ ፥ ነጻነት እንዴት ነው?
ነጻነት ምርጫ ነው!
አምሮ ቢደላደል
ጥፋት ያመነነው ፥ የመንጋዎች መንገድ
እንቅፋቱን ወዶ
ለኖሩለት እውነት ፥ ለብቻ መራመድ!
ነጻነት ማመን ነው
ቀን ወዶ ቢያጀግን ፥ ቀን ጠልቶ ቢከዳም
ቢቆሽሹም ቢደምቁም
እራስን መቀበል
ራስን መምሰል ነው ፥ የነጻነት ገዳም!
ነጻነት ማሰብ ነው
በአንድነት መለምለም
የኔነትን አረም ፥ ከህሊና ማጥፋት
ዘር ሆኖ ከማነስ
ሀገር ሆኖ ማበብ ፥ ዓለም ሆኖ መስፋት።
ንገሯት ለሀገሬ ...
በጀግኖቿ ትግል
ድንበር ባታስደፍር ፥ ከእጀ ገዥ ብትወጣ
ነጻ ነኝ እንዳትል
በገዛ ልጆቿ ፥ በእጅ አዙር ተሸጣ ፡፡
ስሩን ካልሸመነው
በመዋሃድ ጥለት ፥ በማስተዋል ሸማ
ታሪክ አናደምቅም
በጭብጨባ ድግስ ፥ በሆይ ሆይታ ዜማ፡፡
ምን ብናቀነቅን
በየሰልፉ ሜዳ ፥ ወኔ ብንደግስም
በፈረሰ አይምሮ
በደቀቀ አንድነት ፥ ሀገር አናድስም፡፡
በጭፍን ከመሮጥ
አስቦ ማዝገም ነው ፥ የመራመድ ውሉ
ሁሉም እንቅፋቶች
እስኪጥሉን ድረስ ፥ ምርኩዝ ይመስላሉ፡፡
በድፍን ግልብ እሚያጋድል
ህዝብ የመሆን ፥ መንጋ አይንዳን
በማሰብ ስር እንፈወስ ፥ በሰውነት ፀበል እንዳን፡፡
ከእግዜር ልንወዳጅ
ለምህረቱ ጥላ ፥ እምባ ብንደግስም
ልብን ሳይመልሱ
ለንስሃ መሮጥ ፥ ከጽድቅ አያደርስም፡፡
ውብ ነገን እናውርስ
ትላንትን አክመን ፥ በይቅርታ ፀበል
ትውልድ ይጨርሳል
ያረገዝነው እምባ ፥ የቋጠርነው በቀል
ከመስጠት አንጉደል
ከቀማኞች ገደል ፥ ተረግጠን ብንጣል
ካሸከሙን በቀል
ምናወርሰው ፍቅር ፥ ሀገር ይለውጣል፡፡
ከዕድሏ ጣሪያ ላይ
ዘር የቀዳደው ፥ ሽንቁሯ ቢበዛም
ያ ከንቱ ፎካሪ
ባፈጀ ቀረርቶ ፥ ሺህ ጉራ ቢነዛም
ሚሊዮን ዘር ቢሸጥ ፥ አንድ ሀገር አይገዛም፡፡
ኢትዮጵያዊነት ነው
የትርታችን ልክ ፥ የነፍሳችን ግጥም
መልስ ቤት በራቀው
በከረመ ፀሎት ፥ ሰርክ ብታንጋጥም
አጎንብሳ ድሃ
ባፀናችው ጉልበት ፥ ብትረጋገጥም
ነፍሷን አደህይታ
ባሻረችው ቁስል ፥ ብትገሸለጥም
ሀገር ሆና ገዝፋ
በየ ጎጣጎጡ ፥ አትርመጠመጥም፡፡
የዘመን እውነት ነን
ከደግነት ሰማይ ፥ በጥበብ የኖርን
ትዕግስትም ልክ አለው
ፈርተን እንዳይመስለው ፥ ስላቀረቀርን፡፡
ማተብ አስሮን እንጂ
ተጣልተን እንዳንቀር ፥ በክፍፍል ገደል
ከሀገር ክብር በልጦ ፥ ሞት ብርቃችን አይደል፡፡
ንገሩት ለዛ ሰው
ከዓለም ጫፍ እስከ ጫፍ
ኃይል እንደ ተራራ ፥ ገዝፎ ቢከመርም
ክንዱን አፈርጥሞ
እልፍ የሰገደለት ፥ ጀግና ቢሰድርም
ዓለም የሞተበት
የጠላት ማርከሻ ፥ ጦር ቢደረድርም
በአንድ ዓይናችን ሰላም
በኢትዮጵያችን ክብር፥ አንደራደርም !!!
┈┈┈┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈
✍🏽© ሕሊና ደሳለኝ
╰══•••┈ ┈ ┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈
፳፻፲፪ ዓ.ም
#የማጀት_ሥር_ወንጌል
ሙያተኛ ሀገሬ
ከማጥገብ ጎደለ
በረከት እራቀው ፥ የገበታሽ ለዛ
ተሻምቶ ለመጉረስ
ከበላነው ይልቅ ፥ የደፋነው በዛ፡፡
ሙያሽ ባያስደፍር ፥ አጀብ ቢሰኙበት
ማዕዱ ቢሙላላ ፥ ዓይነቱ ቢያምርበት
አበዛዙ አይደለም
አበላሉ ላይ ነው ፥ የገበታሽ ውበት፡፡
እየተማመንን!
የፉክክር ቅሚያ ፥ በርሃብ እየናጥን
ከደፋነው ጠግቦ ፥ ውሻችን በለጠን፡፡
ከምርት አላነስን
ጎተራችን ሙሉ
ጀግና አራሽ ፥ መች አጥተን?
ማሰብ የጎደለው
አያያዛችን ነው ፥ ገደል የከተተን፡፡
ይልቅ ግዴለሽም!
ከምግባር ምጣድ ላይ
ሳንበስል አንጋግተሸ ፥ ከማዕድ አትምሪን
ገበታሽ እንዲያምር
ከእግዜር የሚያስታርቅ ፥ ፍቅር አስተምሪን።
ገበታ ዕድሜ ነው ፥ ባለ ማሰብ መክነን
ሳንፀነስ ጃጀን ፥ ሳንጣድ አረርን
ከዘመን ገበታ
ከፊደል አቅድመን ፥ ዘር እየቆጠርን
ገበታ ሀቅ ነው
በክፋት ሊጥ ጋግረው ፥ ያሻገቱት እውነት
በሆዳም እስክስታ
ረግጠው ያፈኑት ፥ የምስኪናም ጩኸት
እስከ ልጠይቅሽ...
በጥም ደዌ ደቆ
የረሃብ ጠኔ ደፍቶት ፥ እልፍ ትውልድ ያልፋል
ቢራ ለመጥመቂያ
ሚበተን ገብስ ግን ፥ ከሀገር መች ይጠፋል፡፡
ከሆድ በማይሻገር
የማጀት ቤት ዕውቀት ፥ አጥብበሽ አትለኪን
እስቲ መኖር ይግባን
ከማስተዋል መቅደስ ፥ ሰው መሆን ስበኪን።
ዘመን ካልገበረው
ከችጋር ተራራ ፥ ከሲኦል ዳር ኑሮ
እንዴት ነው መሻገር
ከመርፌ ቀዳዳ ፥ በጠበበ አይምሮ።
ከምስኪን ዘመን ላይ
የማይኖሩበትን ፥ ዕድሜ መበዳደር
ለአንዲት ማምሻ ደስታ
በአያት እስትንፋስ ላይ ፥ ቁማር መደራደር
ያሳፍራል አይደል?
እያደጉ ማነስ ፥ እያነሱ መዝቀጥ
አጎንብሶ ያፀናን
የድሃ እናት ጉልበት ፥ በጭካኔ መርገጥ
ያሳምማል አይደል?
መንገስ ከሚያባላስ
መጥገብ ከሚያቃቅር ፥ ማግኘት ከሚያጎለን
ማጣት ውሎ ይግባ
ባርነት ይሰንብት ፥ ድህነት ይግደለን፡፡
ከረፈደ ፀፀት
ደረት እየደቁ ፥ ከእግዜር ቢዋቀሱ
ትርጉሙ ምንድነው ?
ሲኖር ተቃቅሮ ፥ ሲሞት መላቀሱ።
በእናታችን አድባር ፥ በፍቅሯ ይሁንብን
መድመቅ ካጋደለን ፥ ቆሽሸን ይመርብን
በመጠማት ሲቃ
እስትንፋስ እስኪያንቃት ፥ ነፍሳችን ትርበትበት
ብቻህን ከመጥገብ
አብሮ መራብህ ነው ፥ ሰው የመሆን ውበት፡፡
በድፍን ግልብ እሚያጋድል
ህዝብ የመሆን መንጋ ፥ አይንዳን
በማሰብ ስር እንፈወስ ፥ በሰውነት ፀበል እንዳን።
አየህ! ሰው ስትሆን
ከመንጋነት ሚያግድ
እረኛ አያሻህም ፥ ከህሊናህ በላይ
ስታስብ መሪ ነህ
በብስለት ከፍታ ፥ በማስተዋል ሰማይ፡፡
አየህ! ሰው ስትሆን
የጎጥ አረም ነቅለህ
በአንድነት መስክ ላይ ፥ ፍቅር ትዘራለህ፣
በወረወሩብህ የጥላቻ ድንጋይ
ትውልድ የሚያፋቅር ፥ ድልድይ ታበጃለህ፡፡
አየህ! ሰው ስትሆን
ዝምታህ ኃያል ነው
ጀግና የሚያንበረክክ
ከፈሪ ቀረርቶ ፥ ከባዶ ሰው ጩኀት
ሀገር ላምስ ከሚል
በመንደር አጀንዳ ፥ በአሽኮለሌ ተረት፡፡
አየህ! ሰው ስትሆን
ነጻ ነህ እያሉህ
መታሰር ያምርሃል
መቀመቅ መበስበስ
የኖርክለት እውነት ፥ ሀገር እስኪፈታ
በሀቁ እስኪመዘን
ስለ በርባን ክብር
የቆሸሸው ፍቅር ፥ የታሰረው ጌታ
ከድል ታሪክ ሰማይ
ከሥልጣኔ ዳር ፥ ከጥበብ ከፍታ
እንሻገራለን
ህዝብነትን ትተን ፥ ሰው የሆንን ለታ፡፡
በትረ ጥበበ ቢካን
ዓለም ሊያንቀጠቅጥ ፥ ድል ሥልጣን ቢሰጠው
ጀግና መሪ አይደለም
ብርቱ ተመሪ ነው ፥ ሀገር ሚለውጠው፡፡
አስተውል ወዳጄ
ጠልተን ላንጣላ
ችለን ላንጋደል ፥ ነደን ላንፋጀው
የኛው ትርምስ ነው
በልቶ ለሚያባላ ፥ ጠላት ሚበጀው፡፡
ስጋና ደም እንጂ
የአንድነታችን ውል ፥ የፍቅራችን ቀለም
ያሰመርነው ክልል
የታጠርንበት ዘር ፥ ቋንቋችን አይደለም፡፡
ከመዋሃድ መቅደስ
ትውልድ እናስተምር ፥ ዘመን ይመርቀን
ፍቅራችን ምን ጎድሎት ፥ ደማችን ያስታርቀን፡፡
በልጆቿ አጥንት
በደም ኪዳን ምለን ፥ የገባንላት ቃል
ከጩኀት ያለፈ
ዘመን የሚሻገር ፥ ተግባር ይጠይቃል፡፡
በአንድ ሃሳብ ተጋምደን
በድል ድር እናብር
ውድቀታችን ያንቃን ፥ ሠርተን እናሳምን
ሆነን ድል እንንሳ ፥ የአፍ ጀግንነት ይብቃን፡፡
#ተነሳ_ተራመድ
ተነሳ ተራመድ ፥ ክንድህን አበርታ
ላገር ብልፅግና ፥ ለወገን አለኝታ
ሀሁ ኢትዮጵያ ትቅደም
ሀሁ ኢትዮጵያ ተትቅደም
ወንዞች ይገደቡ ፥ ይዋሉ ለልማት
በከንቱ ፈሰዋል ፥ ለብዙ ሺ ዓመታት
ይውጡ ማእድናት ፥ ለሃገራችን ጥቅም
ህዝቧ ታጥቆ ይስራ ፥ በተቻለ አቅም።
አሸብርቃ ታይታ ፥ በተፈጥሮ ሃብት
ተብላ እንዳነበር ፥ የአፍሪካ መሬት
ብለው እንዳልጠሯት ፥ የዳቦ ቅርጫት
እንዴት እናታችን ፥ ይጥማት ይራባት፡፡
ይቅር ማንቀላፋት ፥ ያበቃል መኝታ
ይጥፋ ከሃገራችን ፥ ድህነት በሽታ
ይነገር ይለፈፍ ፥ ይታወጅ በይፋ
አንድነት ሃይል ነው ፥ የሁላችን ተስፋ፡፡
የእናት ሃገራችን ፥ ጥቃቷን አናይም
ህዝቧ ተበድሎ ፥ ማየት አንፈልግም
የዘር የሃይማኖት ፥ ልዩነት አንሻም!
ይላሉ ልጆችሽ ፥ ኢትዮጵያችን ትቅደም!
━━━━━━━━━━━━━━━━━━━━
@snetsehuf
ኦርቶዶክሳዊ አዳዲስ እና የቆዩ መዝሙሮችን የሚፈልግ በዚህ ሊንክ ያገኛል።
https://youtube.com/channel/UCH-ySyaIEpsyXSMesboJFUw
ስምንተኛው ንጉስ ስሙ ማሞ ነው !
(በአፍሪካ ቀንድ ፖለቲካ የብሔር ዘረ መል ተመራማሪ አሌክስ አብርሃም)
ሰሞኑን ግን የማያቸው የምንም ነገር ተንታኞች ምን እያጨሱ ነው የሚገቡት? ...ማለቴ ሄሮይን ምናምን ተፈቀደ እንዴ ?… በቃኮ አንደኛ ክፍል እያለን በጨዋታ መልክ የምናወራውን የቃል ጨዋታ ሱፍ ለብሰው ከረቫት አስረው የሚያወሩ ‹‹አባባ ማሙሾች›› ናቸው የወረሩን! እንዴ ለምሳሌ … ‹‹ጎደሎ›› ከሚለው አማርኛ ቃል ‹‹ባትሪ ሎ›› የሚል እንግሊዝኛ ተፈጠረ ዓይነት!😀 አያችሁ በዚህ አይነት ጉዳዮች ከመሳቅና ከመሳለቅ ይልቅ ህዝብና ህዝብን ለማቀራረብ ብንጠቀምብት አዋጭ ይመስለኛል!እኔም ለዚህ ፅሁፍ ሲባል ብቻ ከላይ ለራሴ በሰጠሁት ማእረግ በመጠቀም ስለአማራና ኦሮሞ ብሔሮች አሰያየም …ስለስሞቹ ታሪካዊ ዳና …ወቅታዊ ቃና …እንዲሁም አንድነት እና ልዩነት ጥልቅ ማብራሪያ እሰጣለሁ!
well ! እንደምታዩት አ ማ ራ በ (አ) ይጀምራል ኦሮሞ በ (ኦ) ይጀምራል !
(አ) ኡ ኢ ኣ ኤ እ (ኦ) ጥግና ጥግ ይዘው ለምን እንደሚጠዛጠዙ ከፊደሎቹ አቀማመጥ አልተረዳችሁም? 😎
በሁለቱ መሀል በ አ እና ኦ (ኢ) አለች ኢትዮጵያ ማለት ነው! ኢትዮጵያ ተጨነቀች ወገኖቸ! …ኤ ትታያችኋለች? ኤርትራ ማለት ነው! ይሄ ጭንቀት እስከኤርትራ የዘለቀ ነው ! ሌላ ኣ አለች አሜሪካና አውሮፓ ማለት ነው … እ አለች እንግሊዝን በተለይ ሲጠቅሳት ነው! (አያችሁ ስለማታስተውሉ እንጅ ቀላል ነው!) አሁን የስንት አገራት ጣልቃ ገብነት እንዳለና የእነዚህን የሁለት ብሄሮች ምሁራን በስውር እጅ እያጋጩ እንዳሉ ሚስጥሩ ፊደሎቻችን ውስጥ አለ! አናስተውልማ!😀
ይታያችሁ ወገኖቸ አ ማ ራ ኦ ሮ ሞ ሁለቱም ውስጥ የ መ ዘር አለ …ስታገጣጥሙት ማ ሞ (ወደፊት ማሞ የሚባል ሁሉን ያማከለ ንጉስ ይመጣል) ሁለቱም ውስጥ የ ረ ዘር አለ … እንዴት ይሄ ሁሉ ነገር ሊመሳሰል ቻለ ካላችሁ ከልዩነታችን አንድነታችን ስለሚበዛ ነው …የቅርፅ እንጅ የዘር ልዩነት የለንም ወገኖቸ !😀
እና አሁን እነዚህን ሁለት ብሔሮች በስያሜ ደረጃ እንዴት እናስማማቸው ለሚለው ቀላሉ መፍትሄ ወይ አ ፊደልን እግሯን ማሳጠር ነው ወይም ኦ ፊደልን እግሯን ማስረዘም ነው!🤐 አመሰግናለሁ! በቀጣይ በምጋበዝባቸው መድረኮች ቀሪዎቹን ሁለት ፊደሎች እንዴት ማስተካከል እንደምንችል አብራራለሁ …ፈጣሪ አገራችንን ይባርክ !
@snetsehuf
"የሕይወት ትርጉም ምንድ ነው? እንወለዳለን፥ እድለኛ ከሆንን እናድጋለን፥ እናረጃለን፥ እንሞታለን። ከእንሰሳት የተለየ ሕይወት አይደለም። ልዩነት ቢኖር የሰው ልጅ ስለመኖር ያለው የማሰብ ችሎታ ብቻ ነው። ማሰብ ባይኖር ኖሮ ክፉን ለበጎ ለይቶ ለማወቅ ሕሊናችን አይጨነቅም ነበር። ህይወት አጭር እና ጅል ነገር ናት! ግን ታስጨንቃለች። የጭንቀቱ መሠረት የማሰብ ችሎታችን (conscious) ነው። ሌላ አይደለም። የማሰብ ችሎታችን ሲቆም እፎይታ፥ ሠላም፥ ዘላለማዊ ፀጥታ! የሰው ዘር ሞኝ ነው፤ ጅል ነው። ለሚኖረው አጭርና ጅል ሕይወት፥ ገና ለገና የማሰብ ችሎታ አለኝ ብሎ፥ ለእንሰሳት ባህርይው የረቀቀና የላቀ ትርጉም ሊሰጠው ይሞክራል። የስቃዩ ዋነኛ ምንጭ ነው…"
•
"የቀይ ኮከብ ጥሪ" ከበዓሉ ግርማ (241)
@snetsehuf
በጀርመን ሐገር የሒትለር ልጅ አብሮ ከሚማርበት ክፍል አንድ መምህር "ተማሪዎች በክንፋቸው ከሚበሩት እንሰሳት መኻል አንድ ጥቀሱ?" ብሎ ይጠይቃል።
በዚህ ቅፅበት የሒትለር ልጅ እጁን አውጥቶ "ዝሆን!" በማለት መለሰ።
አስተማሪውም "አጨብጭቡለት! ሞቅ አድርጋችሁ አጨብጭቡለት…የኔ አንበሳ!" ይላል። ክፍሉም በጭብጨባ ብዛት ቀውጢ ሲሆን ይሄን የሰማ ርዕሰ-መምህር ይመጣና "ምንድነው?" ሲል ቢጠይቅ አስተማሪው ጉዳዩን ሹክ ይለዋል።
ከዚያም ርዕሰ-መምህሩ "ደግማችሁ አጨብጭቡለት እንዲህ አይነት እሳት የሆነ ተማሪ ከየት ይገኛል!" እያለ ጠጋ ብሎ ለመምህሩ በጆሮው "ወንድሜ እኛ ከምንበር ዝሆኑ ቢበር ይሻላል!" አለው።
•••
"ሉባር" ከበረደድ ገዳሙ (115)
@snetsehuf
