አጫጭር ግጥሞችና መጣጥፎች 📚
Open in Telegram
✔️📚ማንበብ ያሻግራል ❗️❗️❗️ በዚህ ቻናል እናንተን የሚመጥኑ የተለያዩ ግጥሞችን ፣ አጫጭር ና መሳጭ ታሪኮችን ታገኛላችሁ። እናንብብ ፤ በማንበባችን እናተርፋለን እንጂ ፤ ከቶ አንከስርም። @snetsehuf
Show more546
Subscribers
+324 hours
+127 days
+5230 days
Posts Archive
#2 # ፓውሎ ኩዌሎ
ከዚህ በኋላ ወጣቱ ፓውሎ የዘመኑ ሞገድ ላይ ተሳፈረ፡፡ ጊዜው እ.ጎ.አ 1967 ነው፡፡ የምዕራቡ ዓለም ወጣት በምንግዴ የአኗኗር ዘይቤ (Hippie) ባህል ተጠምዷል፡፡ ፓውሎም በዚሁ የባሕል ሞገድ ላይ ፊጥ አላ ! ቀንደኛ ሂፒም ወጣው፡፡ የዘመኑ ወጣት የምንግዴ (Hippie) አኗኗር ዘይቤ አንዱ መገለጫ መጓዝ ነውና፣ “200 ዶላር ብቻ ይዤ ደቡብ አሜሪካና ሰሜን አፍሪካ፣ ሜክሲኮና አውሮፓን ዞርኩ” ይላል ፓውሎ፡፡ የምንግዴው ዘመን ትውልድ ካደረገው አንዱም አልቀረው! ቤተሰብ እና ማሕበረሰብ አታድርጉ ያሉትን ሁሉ የማድረጊያው፣ ሁሉንም የመጠየቂያው ዘመን ነበርና ሌሎች ኃይማኖቶችን መርምሯል፡፡ ምትሀቱ (Magic) ሳይቀር የተለያዩ መንፈሳዊ ስልቶች ውስጥም ተሳትፏል - የዘመኑ አንዱ ፋሽን የነበረው አደንዛዥ ዕፅ መጠቀሙ ሳይቀር ነው ታዲያ፡፡“በሕይወቴ በምንም ነገር አልፀፀትም” የሚለው ፓውሎ ክዌሎ፣ “አንድን ነገር ሳደርግ በሙሉ ልቤ ሙሉ ለሙሉ ስለማደርግ አንዴ ካደረግኩ በኋላ አልመለስበትም፣ አልፀፀትም” ይላል፡፡ በወቅቱ አደንዛዥ ዕፅ መጠቀሙን አስመልክቶ በ2006 በራሱ የሕይወት ታሪክ ላይ ተመርኩዞ በተሰራው ኤላ ካሚኖ ኤ ሳንቲያጎ በተሰኘው ዘጋቢ ፊልም ላይ ሲናገር፣ “የአደንዛዥ ዕፅ (drug) መጥፎነቱ በውስጥህ ያለውን አደርገዋለሁ የሚለውን ስሜት፣ ነጻ ፍቃድህን ይገድለዋል” ይላል፡፡ “…አደንዛዥ ዕፅ መውሰድ የምትወደውንና የሕይወቴ ጥሪ ነው የምትለውን ነገር እንዳታከናውን ተነሳሽነትህን ይሰልበዋል - ሐሞትህን ያፈሰዋል፡፡ በቃ ዕፅህን ወሰድክ፣ ደስ አለህ፣ ረሳኸው…! አለቀ! …አደንዛዥ ዕፅ የመውሰድ ክፋቱ ይህ ነው” ይላል ስመጥሩ ደራሲ፡፡በ38 ዓመቱ የሕይወቴ የምንጊዜውም ግብ ወደሚለው የድርሰት ዓለሙ ሁሉንም ጣጥሎ በድፍረት እስኪገባ ድረስ ክዌሎ … አንዴ ተዋናይ፣ ሌላ ጊዜ የትያትር አዘጋጅና ጋዜጠኛ ሆኖ ሰርቷል፡፡ 2001 የተሰኘች መጽሄትም አቋቁሞ ነበር፡፡ ከዘመነ ምንግዴው የተለያዩ ሀገራት ዙረቱ በኋላ በ1972 ወደ ብራዚል ሲመለስ ደግሞ ራውል ስዬክሳስ፣ ኤልያስ ሬጂና እና ሪታ ሊ ለተሰኙ የብራዚል ሙዚቃ ክዋክብት የዘፈን ግጥም መጻፍ ጀመረ፡፡ብዙም ሳይቆይ፣ የክዌሎ የዘፈን ግጥሞች … መላው ብራዚል የሚያዜማቸው ሆኑ፡፡ በተለይም የሒንዱ እምነት ቅዱስ መጽሐፍ በሆነው ጊታ ውስጥ ባለውና አርጁና ክሪሽናን ‘አንተ ማን ነህ ?’ ሲል በሚጠይቀው ክፍል ላይ ተመርኩዞ ለራውል ስዬክሳስ የፃፈው ‘ጊታ’ የተሰኘው የዘፈን ግጥሙ ስዬክሳስን ወደ ላቀ ዝና መንጥቆት ዜማውም በመላው ብራዚላዊ አፍ የማይጠፋ ተወዳጅ ሆነ፡፡
በወቅቱ የነበረው የብራዚል ወታደራዊ መንግሥት ግን ሶሽያሊስት፣ ኮሚኒስት የሚሸቱት የክዌሎ የዘፈን ግጥሞችን አዝማሚያ አልወደደውም፡፡ ሁለቴ ታስሮ ተፈታ፡፡ ሦስተኛው ግን አፈናም ጭምር አለበት ሲል የሚያስታውሰው ክዌሎ፣ “ወታደራዊ ፖሊሶች የነበርንበትን መኪና አስቁመው አስወረዱን፡፡ ሳሩ ላይ ጥለውኝ አንገቴ ላይ መሳሪያ ደገኑብኝ፡፡ ቀና ብዬ ሳይ፣ መንገዱን ተሻግሮ ፊት ለፊቴ ሆቴል ይታየኛል፡፡ …ኦ አምላኬ…በሕይወቴ መጨረሻ ሆቴል እያየሁ ልሙት…? በቃ መሞቴ ነው አልኩ … ፍርሃት አይደለም … ገና 26 ዓመቴ ነበር፡፡ ሕይወትን ገና በቅጡ አልኖርኳትም” ሲል ያስታውሳል፡፡ አፋኞቹ የመንግሥት ወታደሮች አንጠልጥለው እስር ቤት ወረወሩት፡፡ በእስር ቤት ዘግናኝ ማሰቃያዎችን ቀመሰ፡፡ በእስር ቤት ያየውን አስከፊ ማሰቃያ (Torture) አስመልክቶ የአልጀዚራ ቴሌቪዥኑ ሪዝ ክሃን One On One በተባለው ፕሮግራሙ ላይ፣ “የእስር ቤቱ ማሰቃያ እንዳንተ አይነቱ ሰው ላይ የሚያሳድረው ተጽእኖ ምንድነው ?” ሲል ጠይቆት ነበር፡፡የክዌሎ መልስ ግልጽና ቀጥተኛ ነበር - “ፍርሃት…! ጥልቅ ፍርሃት!”“ፈራሁ…” ይላል ክዌሎ፣ “ከእሥር ቤት ከወጣሁ በኋላም ፍርሃቱ አልለቀቀኝም ነበር፡፡ ከእስር ቤት ብትወጣም፣ እስር ቤቱ ውስጥህ ይኖራል፡፡ እናም ፈራሁ! ከዛም ተፀፀትኩ - እዚህጋ ትክክል አልነበርኩም…፡፡ … ኦ … አበዛሁት! … ለምንድነው እንደሌላው ሰው ፀጥ ለጥ ብዬ የማልኖረው … አልኩ፡፡ ከዚያም ነውጠኝነቴን ትቼ አርፌ በስርዓት መኖር ጀመርኩ፡፡ በዚህ መልክ ለ7 ዓመታት ኖርኩ፡፡ ከዛ በኋላ ግን አልቻልኩም ! የእኔ ባልሆነ ባሕሪ እስከመቼ እኖራለሁ …፡፡ 7 ዓመት ላይ በቃኝ፡፡ ከዚህ በላይ መቀጠል አልቻልኩም፡፡ ፍርሃቱም ቀስ በቀስ ለቀቀኝ፡፡ ጊዜ … ሁሉንም ነገር ያድናል … ጊዜ አዳነኝ !!”የእሥር ቤት ቆይታውና በዛ ያየው ክፉ ትውስታ ቀስ በቀስ እየተረሳ ሲመጣ፣ በፍርሃት ተኮማትሮ የነበረው ሥነ ልቦናው እየተፍታታ መጣ፡፡ አንቀላፍቶ የነበረው እውነተኛ ማንነቱ ያንሰራራ ያዘ፡፡
#3 ይቀጥላል
@snetsehuf
ሰላም ሰላም ውድ ቤተሰቦቻችን ብዙዎቻችን ከምንወዳቸው የአለማችን ምርጥ ደራሲያን መካከል አንዱ የሆነው ደራሲ እነሆ.....
# ፓውሎ ኩዎሎ /The alchemist /
ደራሲ እሆናለሁ ማለቱ ያስደነገጣቸው ጥብቅ ኃይማኖተኛ ወላጆቹ ይሄስ የጤና አይደለም በሚል ከአንድም፣ ሁለት፣ ሦስቴ ወደ የአእምሮ ሕሙማን ሆስፒታል አስገብተውታል፡፡…ለታዋቂ ብራዚላውያን ድምጻውያን የሚጽፋቸው የዘፈን ግጥሞቹ መንፈስ ያልጣመው የወቅቱ ወታደራዊ መንግሥት ለ3 ጊዜያት ወደ ዘብጥያ ወርውሮት እስርና ማሰቃያውን ቀምሷል፡፡ የኋላ ኋላ ግን፣ በ38 ዓመቱ፣ ከህልሜና ከሕይወቴ ግብ ሸሽቼ እስከመቼ ብሎ ለመፃፍ ብዕሩን ቢያነሳ በመላው ዓለም የሚገኙ በርካታ ሚሊየን አንባብያን የጻፈውን አንብበው የማይጠግቡለት የዘመናችን ተወዳጁና ቁጥር አንድ ተነባቢ ደራሲ ወጣው… ብራዚላዊው ደራሲ - ፖውሎ ክዌሎ…
ትውልዱ በብራዚሏ ሪዮ ዲ ጄኔሮ ነው - ነሐሴ 18፣ 1938 ዓ.ም! አባቱ ፔድሮ መሐንዲስ ሲሆን እናቱ የቤት እመቤት ነች፡፡ ወለም ዘለም የማይወዱት ጥብቅ የካቶሊክ እምነት ተከታይ ወላጆቹ ሕጻኑ ፓውሎን ውልፍት ማለት የሌለበት የጄስዊት የካቶሊክ ትምህርት ቤት ውስጥ ዶሉት፡፡ ፓውሎ፣ ምንም እንኳ ኋላ ላይ ጉርምስናው ሲመጣ የወላጆቹን ሐሳብ አሻፈረኝ ባይ ቢወጣውም፣ በዲሲፕሊን ጸጥ ለጥ ብሎ ማደጉን ግን አይጠላውም፡፡“የቤተሰቤ ዲሲፕሊን ጠቅሞኛል” ባዩ ፓውሎ፣ “በዲሲፕሊን ማደጌ ነገሮችን ቶሎ እንድማር ረድቶኛል፤ ልቅ ሆኜ ባድግ ኖሮ ፈጽሞ የማልማራቸውን ነገሮችም ተምሬበታለሁ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ እንደ ታማኝነት፣ የዓላማ ጽናት አይነት ነገሮችን አውቄበታለሁ” ይላል፡፡ፓውሎ 17 ዓመት ሲሞላው ግን ነገር ተበላሸ - ደራሲ እሆናለሁ ማለት አመጣ፡፡ ጉዳዩን መጀመሪያ የሰማችው እናቱ፣ “ለመሆኑ ይህ ማለት ምን ማለት እንደሆነ ይገባሃል …? አባትህ መሐንዲስ ነው፡፡ በምክንያትና በአመክንዮ የሚመራ ! ለእንደዚህ አይነት ነገር ጨርሶ ቦታ የለውም፡፡ የምትለው ነገር ምን ማለት እንደሆነ ግን ገብቶሃል…? የኔ ልጅ” ፓውሎ ግን ማንም፣ ምንም ቢል ግድ የሚሰጠው አልሆነም፡፡ የወላጆቹ ሐሳብ ኮሌጅ ገብቶ ሕግ እንዲማር ነበር፡፡ እሱ ግን እቴ … ሕልሜ ደራሲ መሆን ነው ብሎ ከገጣሚ ጓደኞቹ ጋር በየባህር ዳርቻው መዞርን ሥራው አደረገው፡፡ የሕግ ኮሌጅ አልገባም ብሎ ደራሲ እሆናለሁ ማለት ለወላጆቹ ጨርቅን ከመጣል በምንም አይተናነስም፡፡ እናም ይሄ የያዘው አባዜ ቢለቀው በሚል አፋፍሰው የአእምሮ ሕሙማን መታከሚያ ሆስፒታል ውስጥ ጨመሩት፡፡የነፍስ ጥሪ በመርፌና ኪኒን ይድን ይመስል፣ በወቅቱ የነበረው የአሌክትሪክ ንዝረት ሕክምናው (Electroshock Therapyው) ሳይቀር ተሰጠው፡፡ …ፓውሎ በሴት ጓደኛው እርዳታ ከሆስፒታሉ አምልጦ ወጣ፡፡ ቤተሰቦቹ ዳግም ይዘው አስገቡት፡፡ አሁንም አምልጦ ወጣ፡፡ ቤተሰቦቹ ለሦስተኛ ጊዜ ወደ የአእምሮ ሕሙማን መታከሚያው ሆስፒታል ካስገቡት በኋላ፣ አዳንኩት ብሎ ይሁን አልያም ተስፋ ቆርጠው አይታወቅም ብቻ በስተመጨረሻ ሆስፒታሉ የ20 ዓመቱን ፓውሎን እንዳሻህ ሁን ብሎ አሰናበተው፡፡ “ከአእምሮ ሕክምና መስጫው ከወጣሁ በኋላ፣ መቼም ከዚህ በኋላ ፕሬዝዳንት መሆን አልችልም፡፡ ምክንያቱም አንዱ ይመጣና፣ ‘አይሆንም…አይሆንም፣ ይሄ ሰውዬ እብድ ነበር፡፡ ፕሬዝዳንት መሆን የለበትም’ ይል የለ…፡፡ ስለዚህ ፕሬዝዳንት መሆን አልችልም፡፡ ከዚህ ውጪ ግን የፈለግኩትን መሆን እችላለሁ” አልኩ የሚለው ፓውሎ ከሆስፒታሉ ከወጣ በኋላ ግን፣ እስቲ ቤተሰቦቼን ደስ ይበላቸው በሚል ሕግ ለመማር ሕግ ኮሌጅ ተመዝግቦ ነበር፡፡ ግን አልሆነም፡፡ አንዴውኑ የወጣት ልቡ ደራሲ እሆናለሁ ብላ ሸፍታለችና ትምህርቱን ከአንድ ሴሚስተር በላይ መቀጠል አልቻለም፡፡ አቋርጦ ወጣ !
#2 #ይቀጥላል
✔️📚ማንበብ ያሻግራል ❗️❗️❗️
@snetsehuf
" አትተኩሱ። ቼ ጉቬራ ነኝ። ከመሞቴ በላይ ቆሜ እጠቅማችኋለሁ። "
===========================
......ሰኔ 14፣1928(እ.ኤ.አ)በአርጀንቲና ተወለደ። ወላጆቹ ያወጡለት ስም ኸርኔስቶ ጉቬራ ነው። የወደዱት ኩባዎች ግን ስሙ መሃል <ቼ> ብለው ጨመሩለት። <ቼ> ማለት የእኛ ማለት ነው። ቼ ጉቬራ ለብዙዎች ጀግና ለሌሎች ደግሞ የክፉ ምሳሌ ነው። የብዙ ወጣቶች ጣኦት፣ የብዙ አብዮተኞች መንገድ - ቼ ጉቬራ!
ቤተሰቦቹበሃብት የናጠጡ ባይሆንም ያላቸው የሚባሉ አይነት ናቸው። ቼ ግና በማለዳው ጭቁን ማህበረሰብ፣ ተበዝባዢ ሰርቶ አደር ወደሚለው የግራ ዘመም ርዕዮተ ዓለም አጋደለ።
በ1948(እ.ኤ.አ)ወደ ቦነስ አይረስ ዩኒቨርስቲ ገብቶ በህክምና ት/ት ዶክትሯል። ከዳር እስከ ዳር ድህነትን እስኪበቃው አይቷል። እንዲህም አለ፦ <<እንዲህ ከዳር ዳር ለተንሰራፋው ጭቆና እና ድህነት መፍትሄው ሁለትና ሁለት ነው - የትጥቅ ትግልና ኮሚዩኒዝም!>>
ዶክተርቼ ጉቫራ ተብሏል። ቼ ግን ብዙም ሳይሰነብት የዱክትርና ስራውን ትቶ ፣ መርፌውንአስቀምጦ፣ ልቡ ላይ ያበበውን አብዮተኝነት አቅፎ ወደ ኩባ አቀና። ዶክተሩ አብዮተኛ ሆነ።
ካስትሮ የባስቲታን መንግስት ሲታገል፣ ቼ እኔም አለሁበት ብሎ ገባ። ዓለም ሁሉ ዜጋዬ፣ ጭቁን ሁሉ ወገኔ ብሎ ከኩባዊያኑ ጋር ተሰልፏል። ጠዋት ሲተኩስ ውሎ ከሰዓት በህክምና ሞያው በጦርነቱ ለተጎዱት ደርሷል።
በዚህም በ1956(እ.ኤ.አ)የባስቲታን መንግስት በቂጡ ቁጭ አደረጉት።
ቼ በዓለም ላይ ያሉ ጭቁኖችን ያፈነፍን ነበር። ኮንጎም ደርሷል፣ ቦሊቪያም አቅንቷል፣ ለጭቁኖች ዘብ ቁሟል። ነፍጥን አንግቦ ለነፍጠኛም ወኔ ሆኗል።
ቼ 1966(እ.ኤ.አ)ወደ ቦሊቪያ ሲያቀና በቦሊቪያ ያለው መንግስት ጨቋኝ መሆኑን ተረድቷል። ከስልጣን መውረድ አለበት፣ ሊያወርዱት የሚጥሩትም መታገዝ አለባቸው ብሎ የአብዮት ዘፈኑን ዘፈነ። በቦሊቪያም ከታጣቂዎቹ ጋር ታጠቀ። ጥያቄአችሁ ጥያቄዬ ነው አለ።
ግን በቦሊቪያ አመትም ሳይቆይ በሲ.አይ.ኤበሚታገዙ የቦሊቪያ ወታደሮች ተያዘ። በተያዘ በቀጣዩ ቀን ተገደለ። የሰው ፍቅር ያለው፣ የጭቁኖች እምባ አባሽ ፣ ቼ በ39 ዓመቱ ምድር ከዳችው። ነፃነት ሞተ።
<< ጠመንጃዬን ሌላ ሰው አንስቶ ትግሉን እስከቀጠለ ድረስ ለሞቴ ግድ የለኝ። >>
እንዲህም አለ፦ <<አትተኩሱ። ቼ ጉቬራ ነኝ። ከመሞቴ በላይ ቆሜ እጠቅማችኋለሁ። ብሎም ነበር። እሱነቱ እንቅልፍ የነሳቸው የ ሲ.አይ.ኤሰዎች ለሞቱ ቸኮሉ። ተያዘ። ተገደለም። ሬሳውን ሚዲያዎች እንዲያዩትም፣ ፎቶ እንዲያነሱም ተደረገ። ቼ ሞተ።
ስለ ቼ ጋሽ ስብሃት ገ/እግዚአብሔር እንዲህ አለ፦
<< የቼ ጉቬራ የህይወት ታሪክ እና አሟሟት ብዙ ሃሳቦችን ይቀሰቅሳሉ። ለምሳሌ የህንዱ ማህተመ ጋንዲ፣ የግብፁ ገማል አብዱል ናስር፣ የቻይናው ማኦ ዜ ቱንግ፣ የቬትናሙ ሆቺ ሚኒ፣ የሰሜን ኮርያው ኪም ኢል ሱንግ፣ የኬንያው ጆሞ ኬንያታ፣...እነዚህና ሌሎችም ጀግኖች ነፃ አውጭዎች ይህንን ክ/ዘመን አስውበውታል። ነገር ግን ሁሉም ተዋግተው ነፃ ያወጡት የገዛ ሃገራቸውን ሰው ነው። ጀግና ለእናት ሃገሩ ሲዋጋ ይሞታል። ቼ ግን ለሰው ሃገር ሲዋጋ ነው የሞተው። >>
መዳፍ ማንበብ ትችያለሽ ?
ድሮ ለታ የጨበጥሽኝ ቀኝ መዳፌን አሳከከኝ፣
ለእርግማን ነው ብየ ፈራሁ በልቶኝ መቼም አይባርከኝ፤
እስኪ እይልኝ እባክሽን የሚበላኝ የት ድረስ ነው ?
እኔስ ቁስሌን ሳባብለው የምኖረው እስከ የት ነው ?
መዳፍ ማንበብ ትችያለሽ?
አበባ አለ ከ ዕጣዬ ጋር አይተሽዋል ቅጠል ግንዱን፣
መርገፍ ሊሆን የነገ ዕጣው እንዴት ይኑር ሰው የግዱን፤
ወይንስ
ባጭር እሆናለሁ ያልኩት ተስፋ አጓጉቶ ያንቋጠጠኝ፣
በእፍኝ ተድላ ሊቀጨኝ ነው የእስከ ዛሬን ቀን የሰጠኝ፤
አንችስ... አንችስ...
አንችስ ብሞት ትመጫለሽ ?
በድኔን አፈር ታለብሻለሽ ?
በ እንባሽ ሽቶ ታብሻለሽ ?
ብቻ ተይው
መዳፍ ማንበብ ትችያለሽ ?
ነገን ገልጠሽ ባታሳይው ከህመሙ ባትፈውሺው፣
ለእድሌ እንደሁ ግድ የለኝም እስኪ በዛው የናፍቆቴን አንዴ ብቻ እጄን ዳብሽው።
©️አስታወሰኝ ረጋሳ
የእድሩ ስም ጠሪ
-----
ከተስፋዬ ገብረአብ
----
እለቱ ሰንበት ነው:: ደብረዘይት። የቢሾፍቱ ቀበሌ የሃዲድ በላይ እድርተኞች ለቀብር ቃጂማ ጊዮርጊስ ተሰብስበዋል። ሰንበት ስለሆነ ነው መሰል ቀብር ላይ በርከት ያለ ሸኚ ተገኝቶአል። በኦርቶዶክስ ሃይማኖት አማኞች ልማድና ደንብ መሰረት በቀብር የተገኘና ያልተገኘውን ለማጣራት የስም ጥሪ ይካሄድ ጀመር። ስም ጠሪው ባሻ መላኩ እርጅና ተጭኖአቸዋል። ቢሆንም ግን ድምፃቸው እንደ ባቡር ጡሩምባ ነው። በፀጥተኛው የመቃብር ስፍራ እየተምዘገዘገ ያለችግር ከአስከሬን ሸኚው ጆሮ ይደርሳል፣
“ወይዘሮ ፈትለወርቅ ሞላ”
“አቤት!”
“አስር አለቃ እርገጤ ሺባባው”
“አለሁ!”
“ወይዘሮ ከበቡሽ ደሜ”
“አቤት!”
“አቶ ዳኜ ተማም”
ምላሽ አልነበረም፣
“አቶ ዳኜ!?” አሉ ስም ጠሪው በድጋሚ፣
“አለሁ! አለሁ! “ የሚል ድምፅ ተሰማ፣
ይህን ጊዜ ሽማግሌው ስም ጠሪ እብድ የሚያህለውን ዶሴ አጥፈው እርሳሳቸውን ጆሮአቸው ላይ ሰክተው ከፊታቸው ለተኮለኮሉት የእድሩ አባላት ማስጠንቀቂያ ይሰጡ ጀመር፣
“ስሙኝ ቀባሪዎች! እኔ ላንቃዬ እስቲዘጋ የምጮኸው እንደ ፊልፕስ ሬድዮ ባትሪ ውጬ አይምሰላችሁ። በዚህ እድር በቀን አንድ ሰው ይሞታል። በየቀኑ እጮሀለሁ! በ75 ብር ስጮህ መዋሌ ወገኖቼን ልጠቅም ካልሆነ ገንዘቧ ምን አላት? ስለዚህ ካንድ ጊዜ በላይ አልጠራም! ቀሪ ተባልሁ ተብሎ ቅያሜ እንዲመጣብኝ አልፈልግም። ተቀጣሁ ተብሎ ወቀሳ እንዲወርድብኝ አልፈቅድም። ጆሮአችሁን ተክላችሁ ስማችሁን አዳምጡ። እኔ የቁራ ዘር የለብኝም። በየሜዳው የሚጮህ ቁራ ነው። በየባህር ዛፉ፣ በየገደሉ፣ በዋርካ ላይ ተጎልቶ ሲጮህ የሚውል ቁራ ነው፣ እኔ ግን ቁራ አይደለሁም”
ስም ጠሪው በተጨማደደች መሃረም ግንባራቸው ላይ ያቸፈቸፈውን ላብ አደራረቁና ጥሪውን ቀጠሉ፣
“ወይዘሮ የሁዋላሸት አለሙ”
“አለሁ!” አለ የወጣት ወንድ ድምፅ፣
“ደሞ አንተ ማነህ?”
‘ልጃቸው ነኝ!”
ጥሪው ቀጠለ፣
“አቶ ከበደ ማሞ”
ምላሽ የለም፣ ቀሪ።
“ፊታውራሪ የሽዋሉል ግርማቸው”
ምላሽ የለም፣ ቀሪ።
“እመት ጌጤ እሸቴ”
“ታመዋል!” የሚል ድምፅ ተሰማ።
“አቶ ተሰማ ታደለ”
ምላሽ የለም፣ ቀሪ። የእድሩ ስም ጠሪ ግምባራቸውን በመሃረም እያበሱ ቀና አሉ፣
“ስሙኝ ቀባሪዎች! ቀሪ በዝቶአል። እንዴት ነው ነገሩ? አዲስ ድንኩዋን ገዝተን የምረቃ ግብዣ የተባለ ለታ ግን እድርተኛው ግልብጥ ብሎ ነበር የመጣው። ትርፍ ሰው ሁሉ ነበር። የቀበርናቸው ሰው ወክለው ነው? ቀብር ሲባል ግን ቀሪ ይበዛል? ነግ በኔ ነው። ዛሬ ያላቃበርነው ነገ አይቀብረንም…”
ምክርና ተግሳፁን እንዳበቁ ጥሪውን ቀጠሉ፣
“አቶ ሃይለራጉኤል ተካ”
“አቤት”
“ወይዘሮ ኪሮስ ገብራይ”
“አለሁ!”
“ወይዘሮ አረጋሽ አባተ”
ምላሽ የለም፣ ቀሪ።
“አቶ ኩራባቸው ታዬ”
“አቤት!”
“መምህር ገረመው ደበላ”
“አቤት!”
“ወይዘሮ የወርቅውሃ ታደሰ!”
ምላሽ የለም። የእድሩ ስም ጠሪ በድጋሚ “ወይዘሮ የወርቅ ውሃ! ‘ሲሉ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ጠሩ። መልስ የለም። ሽማግሌው እንዲህ ሲሉ ተናገሩ።
"እኝህ ሴትዮን ምን አግኝቷቸው ነው? በጣም ደግ ሰው ናቸው። ቀብር ቀርተው አያውቁም። ወይዘሮ የወርቅውሃ!"
በዚህ ጊዜ አጠገባቸው ቆሞ የነበረ አንድ ጎልማሳ ወደ ጆሮአቸው ጠጋ ብሎ አንሾካሾከ።
“ይዝለሉት ባሻ፣ ዛሬ የቀበርነው ወይዘሮ የወርቅውሃን ነው”
-----
(ልቦለድ፣ 1989 አዲስ አበባ - ተስፋዬ ገብረአብ)
Via አፈንዲ ሙተቂ
ኢትዮጵያዊነት ) =============
ብራናው ይነበብ ልዩ ፊደላችን
የኢትዮጵያዊነት ጥልቅ ሚስጥራችን።
የጥት ታሪካችን ይታይ መሰረቱ በደንብ ተበርብሮ
የኢትዮጵያዊነት ረቂቁ ሚስጥር እዳይቀር ተቀብሮ
የተሰጠን ቀለም ሚስጥራዊ ፍሬው
ከሩቅ እንዲሰማ የአድነት ዝማሬ
የጎሳ አጥር ይፍረስ ይሰበር ድንበሩ
የአንድነት ጎዳናው እንዲከፈት በሩ
ሙሉን አጉድለን ሰብረን ሳንጠግን
ለአንደኛው አድልተን ላንዱ ሳንዎግን
ዘር ሀይማኖት መቁጠር ሁሉን እንተውና
በኢትዮጵያዊነት በአንድነት እንፅና
አንድነትን ሰብከው ፍቅርን ላስተማሩን
አጥንትን ከስክሰው በድል ላስከበሩን
የታሪክን ድግስ ጠምቀው ለዘከሩን
ታሪክን ከታሪክ ከፅናት ተቀባብለው
ሞተው ያወረሱነን ለሀገር ክብር ብለው
እኛም አሜን ብለን በክብር እንቀበለው።
@snetsehuf
#ሆናለች_ሞልቃቃ
:
:
አንድ ቀን በማታ፣ከፍቅሬ ጋር ሆኜ፤
ሽቅብ ሽቅቡን ሳይ፣በሀሳብ መንኜ፤
አንድ እውነት ተረዳሁ፣በልቤም ገነነ፤
ቀን በመሸ ጊዜ፣የሰማይ ውበቱ ኮከብ እንደሆነ።
:
:
ልክ ይሄ እንደገባኝ፣ወዲያው በሹክሹክታ፤
ለምወዳት ፍቅሬ፣እንዲ ብዬ አልኳታ።
:
:
ያለ ከዋክብት፣እንደማይደምቅ ሰማይ፤
እኔም ደንጋዛ ነኝ፣ካንቺ ውጪ ስታይ።
አንቺው ነሽ ኮከቤ፣ለህይወቴ ድምቀት፤
የኔነቴን ሰማይ፣እንዳይወርሰው ፅልመት።
:
:
ይህን ካልኳት ወዲ...
የሚገርመው ነገር፣ኮከቤ ያልኳትን ቃል፣በአምሮዋ ታጥቃ፤
ያለሷ እንደማልደምቅ፣በተጠንቀቅ አውቃ፤
ከዛን ለት ጀምሮ፣ሆናለች ሞልቃቃ።
ካነበብኩት @snetsehuf
By alex abreham
በዓሉ ግርማን ያስገደሉ 8 ጦሰኛ ገፆች!
(አሌክስ አብርሃም)
በስነፅሁፍ ውስጥ ከሚያስገርሙኝ ነገሮች አንዱ ‹‹ተራ›› የሚባል ገፅ አለመኖሩ ነው፡፡በቅሎ በማይችለው መፅሐፍ ውስጥ አንዲት ገፅ ነገሮችን ልትገለባብጥ፣ የአገርንም ይሁን የህዝብ ታሪክ ልትቀይር ትችላለች! ለምሳሌ ብዙ ሰዎች " ደራሲ በዓሉ ግርማን ያስገደለው ኦሮማይ የተባለው መፅሐፉ ነው" ይላሉ! በደፈናው ሐሳቡ ልክ ቢመስልም የበዓሉን ነፍስ ያስነጠቁት ከመፅሐፉ ገፆች የትኞቹ ናቸው ብለን አስበን እናውቅ ይሆን?
ኦሮማይን ደጋግሜ አንብቤዋለሁ... እና ባነበብኩት ቁጥር እንደ ስነፅሁፍ ሀያሲ ሳይሆን እንደአንድ መደበኛ አንባቢ የሚሰማኝ አጠቃላይ ነገር እንዲህ ነው! የስነፅሁፉን ጉዳይ አቆይተነው መፅሐፉ በዘመኑ ከነበረው ፖለቲካ አንፃር ከታየ በዓሉን ሽልማት በሽልማት የሚያደርግ፣ በስልጣን ላይ ስልጣን የሚያጎናፅፍ መፅሐፍ እንጅ ደራሲው ላይ ሰይፍ የሚያስመዝዝ አልነበረም፡፡ ይህ ዘግናኝ ሐሳብ በስርዓቱ ሰዎች አዕምሮ በለጭ እንዲል ያደረጉት ከአጠቃላይ መፅሐፉ ይልቅ ከገፅ 327 -334 ያሉት 8 የተረገሙ ገፆች ይመስሉኛል፡፡
እስካሁን በእኔ ንባብ በአማርኛ ስነፅሁፍ ውስጥ እንደበአሉ ግርማ ኮሎኔል መንግስቱ ሐይለማሪያምን በውብ አገላለፅ ከፍ አድርጎ ያንቆለጳጰሰ ፀሐፊ አላየሁም! ገና ከመፅሐፉ ጅማሬ ጀምሮ ኮሎኔሉን የገለፀባቸው መንገድ የማንንም ባለስልጣን ልብ በደስታ የሚያሞቅ ነበር፡፡ ‹‹ተርገብጋቢ ወንዳወንድ ድምፅ፣ እንደመብረቅ ድንገት ተግ የሚል ከልብ የሚመነጭ ፈገግታ፣ ቅስም ድንገት የሚሰብር ልባዊ ትሕትና …አይናፋር ገራም ጥቁር ነብር ፣አንዳንዴ ደግሞ ቆስሎ የተቆጣ ጥቁር ነብር ….ከተፈጥሮ የአዕምሮ ንቁነት ወደ አረጋዊ ብልህነት ፣ ከጋለ የአገር ፍቅር ስሜት ወደአብዮታዊ ሙህርነት ፣ ከቆፍጣና ወታደርነት ወደአርቆ አስታዋይ መሪነት (በስምት ዓመታት ውስጥ ) ሲለወጡ ዓይኔ አይቷል …… እያለ ይገልፃቸዋል፡፡ ገፅ 20 ላይ !
በመፅሐፉ ሌሎች ባለስልጣናት ላይ የሚጨክነውን ያህል እሳቸው ላይ ሲጨክን አናገኘውም፡፡ አለፍ አለፍ እያለ የሳቸውን ስም ባነሳበት ቦታ ሁሉ ከፍ ያለ አድናቆት ሲቸራቸው እንመለከታለን፡፡ ለአብዮታዊ ሰራዊቱም ከፍ ያለ አካላዊም ሆነ ስነልቦናዊ የጀግንነትና የአገር ወዳድነት ምስክርነቱን እጅግ ባማረ ትርክት ያስነብበናል፡፡ ከአተራረኩ ውበትና ከሰራዊቱ ገድል አንፃር ሰራዊቱ በምንም ምድራዊ ሐይል የሚበገር እስከማይመስለን ፣ ውጣውረዱን እየተረከ መስዋዕትነቱን እየዘከረ፣ በርሀ አቆራርጦ በሸለቆ ውስጥ አሳልፎ በጥይት ውርጅብኝ መሃል ሰቅዞ በሚይዝ ትረካ ያቆየናል፡፡
የሰው ልጅ እንደቅጠል ሲረግፍ እማኝ ያደርገናል፡፡ በደምና በተበጣጠቀ የሰው አካል፣ ቁጥር ስፍር በሌለው ለእናት አገሩ በተሰዋ የወገን እሬሳ በተሞላ የአለት ክምር አረማምዶ የቀይ እንቡጥ(ዋናው ተልዕኮ የተሰጠው አብዮታዊ ጦር) የዘመቻ ዓርማ ከፍታ 1702 ላይ ሲተከል በሲቃ ይሞላናል፡፡ ለወደቁት ጀግኖች መታሰቢያ ሩምታ ሲተኮስ እዛው ያለን ያህል ይሰማናል፡፡ ይህ የሚሆነው ገፅ 327 ላይ ነው፡፡ እስከዚህ ገፅ ሰይጣን ራሱ በዓሉ ላይ እንኳን ሞት ግልምጫ የሚያስብ አይመስለኝም፡፡
መፅሐፉ እዚች ገፅ ላይ ቢያልቅ ኑሮ በዘመኑ የበዓሉ ቦታ ከሚሾሙት ከሚሸለሙት ተርታ በሆነ ነበር፡፡ (አንዳንድ የበታች ባለስልጣኖችን የገለፀበት መንገድ ቅሬታ ቢፈጥርም ለክፉ የሚሰጥ አይመስለኝም) ግን ምን ዋጋ አለው ልክ ገፅ 337 የመጨረሻ መስመር ላይ የተረገሙት ገፆች ይጀምራሉ! ይህን ጀግና ጦር የመራው ኮሎኔል ታሪኩ ለጋዜጠኛው እንዲህ ይለዋል ‹‹ ድሉ የቀይ እንቡጦች ብቻ አልነበረም … ከላይ እስከታች ዕቅዱና ቅንብሩ የሚያስደንቅና የሚያስመሰግን ነበር ›› ካለ በኋላ ባለቀ ሰዓት ‹‹…ግን አሁን አንድ ችግር ይታየኛል…›› በቃ! ችግሩ ጠላት ሐይሉን አስተባብሮ ዳግም እንደሚመለስ …በወገን ጦር በኩል የሰው ሐይል እጥረት ፍጥነትም ችግር እንዳለ ….ወዘተ …! ያለውም አልቀረ ሻዕብያ ያንን ሁሉ መስዋእትነት የተከፈለበትን ከፍታ 1702 በመልሶ ማጥቃት ተቆጣጠረው.... ከፍታው ላይ የነበሩትን ሁሉ የኢትዮጵያ ወታደሮች ገደላቸው! ከፍታው መቃብራቸው ሆነ….ኦሮማይ! ትንቢቱ አልቀረም ኢትዮጵያ በአማፂያኑ ተሸነፈች አስመራ የብዙ ሽ ኢትዮጵያዊያን ወታሰሮች መቃብር ሆነች! ! ያ ሁሉ ዘመቻ ውሃ በላው ! ቀጣዮቹ ስምንት ገፆች የሚነግሩን ይሄንን ነው ! ከዛ በኋላ የተፃፈው የከተማ ድል ይህን ህመም አልፈወሰውም! በቁጣ የቀላውን የባለስልጣን አይን አላጠራውም ፣
ዛሬ ላይ ሁናችሁ የወቅቱን ትኩሳት ታስቡት ዘንድ ይህን ብየ ልጨርስ ….አንድ የዘመናችን ሚንስትር ወይም ከፍተኛ የብልፅግና ባለስልጣን መፅሐፍ ቢያሳትም ….አሁን ባለው የሰሜኑ ጦርነት …መንግስት ትግራይን ተቆጣጥሯል አሸንፏል፣ ግን ሕወሃት ተመልሶ ይመጣል፣ መንግስትም ይሸነፋል ትግራይ የሰራዊታችን መቃብር ትሆናለች ›› ብሎ ቢፅፍ ብላችሁ አስቡት በዚህ ዘመን ውግዘትና ቢበዛ ከስልጣኑ መነሳት ቢገጥመው ነው እንደዛም ሁኖ ማን ይደፍራል? … የበዓሉን አስደንጋጭ የደራሲ ድፍረት የምትረዱት ይሄኔ ነው! በግሌ ግን ስብሐት ገብረእግዚአብሄር እንዳለው ኦሮማይ ባይፃፍና በዓሉ በሕይዎት ቢኖር እመርጥ ነበር፡፡ ወይም እነዛ ጦሰኛ ስምንት ገፆች ባይፃፉ፡፡ የሆነ ሁኖ ምናልባት ተፅፎ ሳላየው ቀርቸ ካልሆነ በስተቀር እነዚህ ስምንት ጦሰኛ ግን ደግሞ የደፋር ደራሲን ድፍረት የአንባገነኖችን ፈሪነትና አጥፊነት የሚያሳዩ ገፆች ላይ ብዙ ብዙ ቢፃፍና ብናነብ እንዴት ጥሩ ነበር!መጽሐፉ "ሀዲስ ሳህሌ" በተባለ ሩጦ ባልጠገበ የ "ዩኒቨርስቲ" ወጣት ገጸባህሪነት ይዋቀራል። የኑሮ ውጣወረዱን ይተርካል። መፅሀፋ ወቅቱን ማዕከል ያደረገ አሳብን ለጉሟል። ከፊውዳል ስርዓት ዘግይቶ ወግ አጥባቂዋን የንግስት ዘውዲቱን ስርዓት አሸንፎ የመጣው የራስ ተፈሪን የለውጥ ጊዜን በትዝታ ዳስሶና አነጻጽሮ ቀጥሎም ሰፍ ብሎ እየመጣ ያለውን በተለይ የሶሻሊስትንና ካፒታሊዝም ስርዓትን እያስተጻመረ ያስቃኛል። ስርዓቱ የወለደውን የዩኒቨርስቲ ተማሪወች አመጽም ያትታል።
ምንም እንኳ መጽሐፉ በፖለቲካ መዋቅር የታጀበ ቢሆንም የአይናለምና ሀዲስ ፍቅርን የሚያትትም ነው። መጽሐፉ በጥቅሉ ጽኑነትን፣ ጽናትን፣ ፍቅርን ለአላማ መጽናትን ሁሉ ያስተምራል።
ደራሲ በዓሉ ግርማና ጋሽ ስብሐት የበዓሉ መኪና ውስጥ ቁጭ ብለው እያወጉ በሁዋላ አንድ የኔ ቢጤ ጠጋ ብሎ አንዳች ነገር ይለምናቸዋል! በዓሉ ለጠላቴ እስቲ ልስጥ ብሎ የሆነ ፍራንክ ከኪሱ አውጥቶ ይሰጠዋል። ስብሀት አልገባውም ነበር ምን ማለትህ ነው በዓሉ ሲል ይጠይቀዋል! በዓሉም "ለኔ ብለው የላኩት ሰላይ ነው፤ የምናወራውን ሊሰልል የመጣ...ነው! ሲል መለሰለት።
ከበዓሉ ግርማ ሀዲስ ውስጥ ተፈልፍሎ የወጣ የተውጣጣ።👇
"አንድ ሊቅ ነበር ይባላል። ማን ነው ብልህ ? ቢሉት
መልስ፦ 'ከእያንዳንዱ ሰው አንድ ነገር ሊማር የሚችል'
"ማን ነው ሀብታም?" ቢሉት
መልስ ፦ 'በቃኝን የሚያውቅ'
"ማን ነው የተከበረ ሰው?" ቢሉት
መልስ፦ 'ሰውን የሚያከብር' ብሎ መለሰ
"ማን ነው ቶሎ ነገር የሚገባው?" ቢሉ
'በትእግስት ሰውን የሚያዳምጥ ሰው እላለሁ።' መለሰ...!
"ማን ነው ጠንካራ ሰው?" ቢሉት
መልስ፦ ስሜቱን የሚቆጣጠር ሰው
ጎበዝ ስሜትን የመቆጣጠር ብልሀት እንዲሁ በቀላል የሚተገበር ወይም የሚመጣ አንዳች ነገር አይደለም። በጣም ብዙ ልፋት ይጠይቃል። ምን አልባት ለዚህ የታደሉ በተፈጥሮና ሐይማኖት የታገዙ ጥቂቶች ብቻ ሊሆኑ ይችላሉ።
በተለይ ለእንደኛ አይነት አገሮች ፊደል ከቆጠረ ይልቅ ሳይማሩ እንዲሁ በተፈጥሮ ባህሪና በሐይማኖት አስተምህሮ ታግዞ ስሜቱን ሊቆጣጠር የሚችል ትውልድ በእጅጉ ጠቃሚ ነው ሲሉ ምሁራን ጭምር ያምናሉ። ስሜትን መቆጣጠር ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ለማስረዳት ሰዎች ንዴታቸውን በመቆጣጠር ሂደት ውስጥ ሆነው እንኳ በቀን ውስጥ ቢበዛ ለአንድ አምስት ደቂቃ ቢያንስ ደግሞ ለአንድ አምስት ሰከንድ አዕምሯቸው የመዛባት ባህሪ ሊያሳይ ይችላል ታዲያ በዚያች ቅጽበት ውስጥ እነሱ ያልሆኑትን ባህሪ ሊያሳዩ ወይም ሊያንጸባርቁ ይችላሉ። ልክ አብሹ ቢጤ እንዳለበት ሰው ወፈፋ ሊያደርጋቸውም ይችላል።
ምንጭ:-ስነ ፅሑፍ እና ጋዜጠኝነት - Literature and Journalism (አውድማ/Awdimaከ 𝙗𝙤𝙤𝙠 𝙘𝙚𝙣𝙩𝙚𝙧
"አንድ ወጣት መንገደኛ አንድ ቀን አንድ በጣም ያረጀ ሽማግሌ የዛፍ ችግኝ ሲተክሉ ያገኛቸውና 'የምን ችግኝ ነው የሚተክሉት አባቴ?' ብሎ ይጠይቃቸዋል። ጣፋጭ ፍሬ የማያፈራ ዛፍ ነው ይሉታል። ከስንት አመት በኋላ በማለት ሲጠይቃቸው ተሰባት አመት በኋላ ሲሉት ወጣቱ በጣም ይገረምና "ከፍሬው ላይቀምሱ ምን ያደርግሎታል? እንዲያው በከንቱ ነው የሚለፉት ይላቸዋል። ሽማግሌውም በወጣቱ ነገር ተገርመው አይ ልጄ እንዳልከው እኔ አልደርስበትም። ግን ወደዚህ አለም ስመጣ አለም ባዶ አልነበረችም። እኔም ከሄድኩ በኋላ ባዶ አትሆንም። እኔ ስበላው የኖርኩት ፍሬ አባቶቼ የተከሉትን ዛፍ ነው። እኔም በተራዬ ለልጆቼ በመትከል ላይ ነኝ አሉት ይባላል "
እናም ከራሳችን አልፈን ለሌሎች የመኖር ጥበብ እንማር ከራስ በላይ ንፋስ የሚለውን ብሂል እንተው እናም እንደሰው እናስብ
እንደ ሰው ስላቹ አንድ የሎሬት ፀጋዬ አባባል አለ "እራስህን ሲያምህ በሕይወት አለህ አልሞትክም ማለት ነው ግን የሰዎች ህመም ሲሰማህ ያኔ ሰው ሆንክ ማለት ነው" ስለዚህ የራሳችንን ህመም ብቻ ሳይሆን የሌሎችንም ህመም አድምጥ።
@snetsehuf
📘የ17 ግመሎች ውርስ…
📒አንድ ሰውዬ ይሞታል፡፡ 17 ግመሎች እና ሦስት ልጆች ነበሩት፡፡ ኑዛዜው ሲነበብ፣ “የግመሎቼን ግማሽ ለመጀመሪያው ልጄ፣ አንድ ሶስተኛውን ለሁለተኛው ልጄ እንዲሁም የግመሎቹን አንድ ዘጠነኛ ለሦስተኛው ልጄ ተናዝዣለሁ” ይላል፡፡
📕ልጆቹ ግራ ተጋቡ፡፡ ምንድነው ማድረግ የሚችሉት ? የ17ቱ ግመሎች ግማሽ ለመጀመሪያው ልጅ ይሰጥ ተብሏል፡፡ እና አንዱን ግመል ለሁለት ሰንጥቀው ይካፈሉ ? ግራ የገባው ነገር ነው፡፡
📖ይሄንንም ቢያደርጉ እንኳ መፍትሄ አይሆንም፡፡ ምክንያቱም የግመሎቹ አንድ ሦስተኛ ደግሞ ለሁለተኛው ልጅ ይሰጥልኝ ብሏል አባትዬው፡፡ ይሄም ቢሆን ችግሩን አይፈታውም፤ የግመሎቹ አንድ ዘጠነኛ ለሦስተኛው ልጄ ይሰጥ ይላል ኑዛዜው፡፡ ግመሎቹ ሁሉ ተቆራርጠው አለቁ ማለት እኮ ነው…
📗ለጉዳዩ መፍትሄ ለማግኘት ወደ ከተማዋ የታወቀ ምሁር ዘንድ አመሩ፡፡ ሰውዬው በጉዳዩ ላይ በጥልቀት ቢያስብበትም መልስ ሊያገኝለት ግን አልቻለም፡፡
📖“እኔ በሕይወቴ ቁጥሮችን እንጂ ግመሎችን አካፍዬ አላውቅም፡፡ ይሄ ተራ ማጃጃያ ነገር ነው የሚመስለኝ፡፡ ለማንኛውም፣ ኑዛዜው በትክክል መተግበር ካለበት ግመሎቹን መሰንጠቅ የግድ ነው” አለ ሰውዬ፡፡
ልጆቹ በምክሩ አልተስማሙም፡፡ ግመሎቹን ቆራርጧቸው የሚለውን የምሁሩን ምክር አልተቀበሉትም፡፡ ስለዚህም ምን ተሻለ ?
ይሄኔ አንድ ሰው መጥቶ፣ “ከቁጥር ይልቅ ስለግመሎች የሚያውቅ ሰው ብታማክሩ ይሻላችኋል” አላቸው፡፡
📕ስለዚህም ልጆቹ፣ በሰው በሰው እያጠያየቁ፣ አንድ እርጅና የተጫጫነው፣ ያልተማረ፣ ግን ከሕይወት ልምዱ ብልህነትን የቀሰመ አዛውንት ሰው ዘንድ ሄደው ችግራቸውን ነገሩት…
አዛውንቱ ሰው ስቆ፣ “አይዟችሁ አታስቡ - ነገሩ ቀላል ነው” አላቸው፡፡
📒ከዚያም አዛውንቱ የራሱን አንድ ግመል ለልጆቹ አበደራቸውና የግመሎቹ ቁጥር 18 ሆነ፡፡ በውሉ መሰረትም፣ ለመጀመሪያው ልጅ የግመሎቹን ግማሽ፣ 9 ግመሎች ተሰጡት፣ ደስም አለው ! የ18ቱ ግመሎች አንድ ሦስተኛ ስድስት ነውና ለሁለተኛው ልጅ ስድስት ግመሎች ደረሱት፡፡ እርሱም ተደሰተ፡፡ የ18ቱ ግመሎች አንድ ዘጠነኛ፣ ሁለት በመሆኑ ለሦስተኛው ልጅም ሁለት ግመሎች ተሰጡት - እርሱም ደስ አለው፡፡
አንድ ግመል ቀረ…
📘አዛውንቱ አንድ ግመል አበድሯቸው አልነበር፤ ያበደረውን አንድ ግመል መልሶ ወሰደ፡፡
“አሁን መሄድ ትችላላችሁ” አላቸው፡፡
🔑ተራ ዕውቀት (knowledge) ተግባራዊ አይደለም፡፡ በልምድ የካበት ጥበብ (wisdom) ግን ተግባራዊ እና ተጨባጭ ነው፡፡
ዕውቀት ተጨባጭነት ይጎድለዋል፡፡ ጥበብ ወይም ብልህነት ግን ወደ መሬት የወረደ እና ተጨባጭ ነው፡፡ዕውቀት ተራ የቃላት ጨዋታ ነው፤ ጥበብ እና ብልህነት ግን ከሕይወት ልምድ የተጨለፉ ናቸው፡፡
📖Osho/ኦሾ
#አንድ ሰው አንዲት በጣም ቆንጆ ወፍ በመዳፉ ውስጥ ይዞ ጨምቆ
ሊገድላት ሲል ከመሞቷ በፊት አንድ ወይም ሁለት ቃላት ትናገር ዘንድ
እንዲፈቅድላት ጠየቀችው፡፡
እንዲህም አለች “እባክህ አትግደለኝ፡፡ ሶስት ጠቃሚ ምክሮችን
እሰጥሃለሁ፡፡
የመጀመሪያው ምክር፤ በእጅህ ያለውን ነገር አትልቀቅ፡፡
ሁለተኛው ምክር፤ ስለሆነው ነገር ሁሉ አትቆጭ፡፡” ካለችው በኋላ ዝም
አለች፡፡
ሶስተኛውንም ምክር ትነግረው ዘንድ ሲጠይቃት “ሶስተኛው ምክር
ለልጆችህና ለልጅ ልጆችህ በጣም ጠቃሚ ስለሆነ ካለቀከኝ
አልነግርህም፡፡” አለችው፡
በዚህ ጊዜ ሰውየው ሶስተኛውን ምክር ለመስማት በጣም ጓጉቶ ስለነበረ
ወፏን ሲለቃት ከአንድ ዛፍ ላይ በርራ ወጥታ “ምንድን ነበር ያልኩህ?
ታስታውሳለህ?” ብላ ጠየቀችው፡፡ እርሱም “በእጅህ ያለውን ነገር
አትልቀቅ ነው ያልሺኝ፡፡” አላት፡፡
“ሁለተኛውስ?”
“ስላለፈው ነገር ሁሉ አትቆጭ፡፡”
“አዎ፡፡ ነገር ግን የነገርኩህን ነገር አልተቀበልክም፡፡ ባትለቀኝ ኖሮ ከሆዴ
ውስጥ ለልጅ ልጆችህ የሚሆን ወርቅ ታገኝ ነበር፡፡ ይኸው ነው፡፡”
አለችው፡፡
ሰውየው “ሶስተኛውስ ታዲያ?” አላት፡፡
እሷም “ሶስተኛው የሁለተኛው ምክር ድጋሚ ነው፡፡ ስላጣኸው ነገር
አትቆጭ፡፡ ይኸው ነው፡፡ ደህና ሁን፡፡ ምክሬንም ባለመቀበልህ በድህነት
ትኖራለህ፡፡” አለችው፡፡**
ከወደዳችሁት share
@snetsehuf
ማፍቀርን ሳያውቁ
ማፍቀርን ሳያዉቁ አፈቀርን ይሉና።
መመገብ አቃተን ሰላም አጣን ጤና።
ከጎኔ እርቀሽ መኖር እያቃተኝ።
ወደፊት ስራመድ እግሬ እየጎተተኝ።
አልቻልኩም ያላንች ፍቅርሽ እያሳተኝ።
ደግሞ እሷ እንደሱ ቃላት አሽሞንሙና።
አንተ ብቻ አይደለም
እኔም አጥቻለሁ ሰላም ና ጤና።
በቃላት አጀባ በቃላት ሽንገላ
ማፍቀርን ሳያውቁ።
ስንት አሉ ከሰዎች ከፍቅር የራቁ።
ማፍቀር ሳይገባቸው ፍቅርን የወደቁ።
ቆይ ግን ማነህ አንተ ቆይ ግን ማነሽ አንቺ።
ሞትኩልህ ስላንተ ሞትኩልሽ ስላንቺ።
ሀሰት ቃላት ማዝነበ የማትሰለቺ።
አፈቀርኩሽ ብሎ።
በቃላት ሸንግሎ።
ከወላጅ ነጥሎ።
ይዞሽ ይጠፋና መጦ ይጥልሻል።
ሞትኩልሽ ሲል ኖሮ አንችን
ሲያገኝማ በቅፅበት ይሸሻል።
ጥረውና ለፍተው ለዚህ አብቅተዋት
እኔን አስበልጣ ከነሱ ከሸሸች።
የተሻለ ሀብታም ሰውካገኝችማ
ከእኔ ባላመሸች።
ብሎ ያስብና ወዲያው ይተውሻል።
ሞትኩልሽ ያለው ሰው በቶሎ ይሸሻል።
አንችም እጁን መተሽ ደጋግመሽ በቃላት
ድህነት ቢወርስህ ካንተማ አልሸሽም።
ሁሉን እተዋለሁ ከእናት አባቴ ቤት
ፈፅሞ አላመሽም።
እያልሽ ስትይ ኖረሽ
ስንት የሆኑሉሽን
ወላጅሽን ጥለሽ።
የተሻለ ሲገኝ ትናንት
እንዳረግሽው ከእሱም
ትሸሻለሽ።
እውነተኛን ፍቅር አውቀነው ከገባን
ወላጅ አያጣላም።
ከቤት አያስጠፋም
አያደፈርስም የቤተሰብ ሰላም።
@snetsehuf
➳ ስለደራሲ ዳኛቸው ወርቁ ህይወትና ሥራዎች
ዳኛቸው ልክ እነደ አባቱ ተራማጅ የሚባል ሰው ነበር። የዳኛቸው አባት አቶ ወርቁ በዛብህ ገና በወጣትነት እድሜው በድሬደዋ በኩል በባቡር ወደ ጅቡቲ ተጉዞ፣ ከዛም ወደ አውሮፓ ተሻግሮ ፈረንሳይ ገብቶ፣ በአንደኛው የዓለም ጦርነት የፈረንሳይ ወታደር ሆኖ የተዋጋ! በውጊያውም የቆሰለ፣ከዚያም በማዕድን ቁፋሮና በሆቴል መስተንግዶ ኑሮውን የገፋ ሰው ነበር። አቶ ወርቁ ከስደት ኑሮ ሲመለስ ትዳር መስርቶ ጎጆ ቀልሶ መኖር ጀመረ። ልጆችም ተወለዱ። ከተወለዱት ልጆች መካከል ደግሞ አንዱ አወዛጋቢው ደራሲ ዳኛቸው ወርቁ ነበር።
የዳኛቸው እናት ልጇን የተገላገለችው አገር በጣሊያን ወረራ ምጥ ተይዛ በምትሰቃይበት ዘመን ነበር። የካቲት 16/1928 ዓ.ም ከደብረሲና ወጣ ብላ በምትገኝ አንዲት ገጠር ውስጥ። በፈረንሳይ አገር የኖረው የዳኛቸው አባት ለትምህርት የነበረው ቦታና ግንዛቤ ላቅ ያለ ስለነበር ቤተሰቡን ይዞ ወደ ደብረሲና አቀና። በዛም ዳኛቸው የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን እስከ ስድስተኛ ክፍል ተከታተለ። 7ኛ እና 8ኛ ክፍልን ደግሞ በቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ ትምህርት ቤት በአዲስ አበባ ተምሮ ሊሴ ገ/ማርያም ት/ቤት ገባ። ሊሴ ግን ለዳኛቸው ባህሪ የሚመች ዓይነት ት/ት ቤት ሆኖ ስላላገኘው ትምህርቱን አቋርጦ ወደ ደብረሲና ተመለሰ።
ዳኛቸው በልጅነቱ የአባቱን ባህሪ እያጠና፣ የእናቱን ተረቶች እያዳመጠና እያብሰለሰለ ነበር ያደገው።
ዳኛቸው በልጅነቱ የአባቱን ባህሪ እያጠና፣ የእናቱን ተረቶች እያዳመጠና እያብሰለሰለ ነበር ያደገው። ወደ ደብረ ሲና ከተመለሰ በኋላ ግን ከአባቱ ጋር ሊጣጣሙ አልቻሉም። “ከጓደኞቼ ጋር እንደልብ ጊዜ እንዳላኣሳልፍ ጫና ታደርግብኛለህ” ብሎ ወደ ደብረ ብርሃን ኮበለለ። ድብረ ብርሃንም ብዙ አልቆየም ትምህርቱን ለመቀጠል ወደ አዲስ አበባ ተመልሶ ኮተቤ መምህራን ኮሌጅ ገባ። በኮተቤ መምህራን ኮሌጅ በትምህርት ላይ እንዳለ ዳኛቸው ከባድ የጉሮሮ ህመም አጋጠመው። ለህይወቱ ያሰጋ የጉሮሮ ህመም! ይድናል ብሎ የጠበቀም አልነበረም! ዳኛቸው ግን ለመለዓከ ሞት እጁን ሳይሰጥ ቀረ። ዳነና ከተኛበት ዳግማዊ ምንሊክ ሆስፒታል ወጣ። ይህ አጋጣሚ ለዳኛቸው ቤተሰቦች የልጃቸው ዳግም ልደት ነበር።
ዳኛቸው ከጉሮሮ ህመሙ ሲያገግም ኮከበ-ጽባህ መምህርነት ገባ ። ሁለት ዓመት በኮከበ-ጽባህ አስተምሮ ሀረር ዘለቀ። በሀረር መድኃኔዓለም ት/ት ቤት እያስተማረ “ሰቀቀንሽ እሳት” የሚል ትያትር ጽፎ ለመድረክ አበቃ። በተገኘችው ገንዘብ ደግሞ በድብረ ብርሃን ከጓደኞቹ ጋር ያሳለፈውን ህይወት የምትተርከው “ሰው አለ ብዬ!” መጽሀፉ ታተመች። በሀረር እያለ ዳኛቸው በጋዜጦች ላይ ጽሁፎቹን ያስነብብ ነበር። የሚያስነብባቸው ጽሁፎች ያነበባቸው መጻህፍት ላይ ያለውን ምልከታ የሚዳስሱ ነበሩ።
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለመጀመሪያ ጊዜ በአማርኛ ቋንቋና ስነ-ጽሁፍ ለማስተማር ሲወስን ዳኛቸው ከሀረር ገስግሶ ስድስት ኪሎ ደረሰ። ከመጀመሪያዎቹ የቋንቋና ስነ-ጽሁፍ ትምህርት ክፍል ተማሪዎችም አንዱ ለመሆን በቃ። ለሁለተኛ ዲግሪ ትምህርቱ ደግሞ ወደ ውጭ አገር አቀና። ይቀጥላል ...
@snetsehuf
የጦር አውሮፕላን አብራሪዎቹ ሳያቅማሙ ተስማሙ! እራሳቸውንም "kamikaze pilots" ብለው ሰየሙ። ለሃገራቸው እና ለንጉሱ ክብር ሲሉ የሚያበሩት የጦር አውሮፕላን ውስጥ ቦንብ እና ጋዝ(ነዳጅ) ጭነው ቀጥታ የአሜሪካ የጦር መርከቦች ያሉባቸው ቦታዎች ጋር በከፍተኛ ፍጥነት በመብረር እራሳቸው መከስከስ ጀመሩ! አባዬ! ይሄንን ያደረገው አንድ ጃፓናዊ ፓይለት አይደለም! በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ጃፓናዊ ፓይለቶች ናቸው። በዚህ ሂደት 34 ግዙፍ የአሜሪካ የጦር መርከቦች እንዲሰምጡ እና ከፍተኛ ውድመት እንዲደርስባቸው አደረጉ! በአንድ ተልኮ ብቻ ከ 5000 በላይ የአሜሪካ ባህር ሃይሎች እንዲሞቱ ማድረግ ችለዋል።
እንደምትሞት እያወክ የጦር አውሮፕላንህ ውስጥ ቦንብ እና ጋዝ ጭነህ የጠላት መርከብ ላይ ወስደኸው መከስከስ ምን ያህል ድፍረት እንደሚጠይቅ አስበው እንግዲህ!
አሰቃቂ መገባደጃ!
በጃፓን ጥቃት ደርሶብኛል በማለት አሜሪካ ለመጀመርያ ግዜ በሰው ልጅ ላይ "ሄሮሺማ" እና "ናጋሳኪ" የሚባሉ ሁለት ከተሞች ላይ "አቶሚክ ቦንቦችን" ጣለች! በአንዴ ከ 150 ሺህ እስከ 200 ሺህ የሚጠጉ ንፁሃን ጃፓናዊያኖችን በሁለት ቦንብ ስልቅጥ አድርጋ በላች። ጃፓንም በመጨረሻ "ተሸንፌያለው፣ ጦርነቱ ይብቃ!" ብላ እጅ ሰጠች! ሁለተኛው የዓለም ጦርነትም ያኔ አበቃ። የሩቅ ምስራቋ ጃፓን "አቶሚክ ቦንብ" የተጣለባት የመጀመርያዋም የመጨረሻማው ሃገር ሆና አለፈች።
ግን... ግን ፍፁም ይቅር ይባባላሉ ተብለው የማይታሰቡት ሁለቱ ሃገራት ከአመታት በኃላ ወዳጅ ሆኑ፣ ታሪክ አለፈ፣ አሜሪካ ይህንን ታሪክ ይቅር የማይለውን ወንጀል ለማንጣት በሚመስል መልኩ ፅኑ የጃፓን ወዳጅ ሆነች፣ መሰረተ ልማቶቿን እና ከተሞቿን ገነባች! ሁለቱ ሃገራት በውትድርና፣ በንግድ፣ በኢንቨስትመንት እና ቴክኖሎጂ እጅግ የተሳሳሩ ሃገራት ሆኑ!#ጃፓን
ቤትህ አልበላሽ ያለህ "Sony" ቴሌቪዥን የነሱ ነው፣ ያሳደገህ ብረቱ "Hitachi" ፍሪጅ የነሱ እጅ ያረፈበት ነው፣ ሃገራችንን ብቻ ሳይሆን ዓለማችንን ያጥለቀለቀው "Toyota" መኪና የነሱ ጥበብ ውጤት ነው፣ "Nikon" እና "Canon" ካሜራዎች የነሱ አሻራዎች ናቸው፣ እንደዛ በፍቅር የምትወደው "Toshiba" ላፕቶፕህ የነሱ ነው፣ "Mazda", "Lexus", "Mitsubishi", "Honda", "Nissan", "Isuzu", "Suzuki" ምናምን የምትላቸው መኪናዎች የተፈበረኩት በነሱ ነው። እጃቸው የነካው ምርት ሁሉ ብሩክ እና ብረት ነው።
ከሁሉም በላይ የሚደንቀኝ የጃፓናዊያን የስራ ባህል ነው። የእረፍት ትርጉሙ አይገባቸውም! የዓለማችን ረጅም ሰዓታቸውን በስራ ላይ የሚያሳልፉ ዜጎች ጃፓናዊያን ናቸው። በስራ ብዛት የሰው ልጅ የሚሞተው ጃፓን ውስጥ ብቻ ነው! ሞቱን "Karoshi" ብለው ይጠሩታል። በዓመት ካላቸው የ 20 ቀን እረፍት ውስጥ 10 የሚሆነውን እንኳን በአግባቡ አይወስዱም። 63% የሚሆኑ ጃፓናዊያን በእረፍት ሰዓታቸው በሚከፈላቸው ገንዘብ ደስተኛ አይደሉም። ጌታዬ! መንግስት "....የአመት እረፍታችሁን እባካችሁ ውሰዱ! በስራ ብዛት እና ጭንቀት እየሞታችሁ ነው! እስቲ ትንሽ ዘና በሉ!..."ብሎ ሲለምን የምትሰማው የጃፓን መንግስትን ብቻ ነው።
ከለሊቱ 9 ሰዓት ላይ የጃፓን መንገዶችን ብትመለከት ሽክ ብሎ ሱፉን ለብሶ እና "briefcase" ይዞ ወደ ስራ የሚሄድ ብዙ ሰው ታያለህ። አብዛኛው ጃፓናዊ "ለምን ትሰራለህ?" ተብሎ ሲጠየቅ "ሃገሬን ስለምወድ እና ብቁ ዜጋ ሆኜ መገኘት ስላለብኝ!" ብሎ ይመልስልሃል። ያለ እረፍት ከመስራታቸው ብዛት የጃፓን መስሪያ ቤቶች ውስጥ ጠረጴዛቸውን ተደግፈው የሚያንቀላፉ ሰዎችን ማየት የተለመደ ነው። የታታሪነት፣ የብርቱነት እና ሃገር ወዳድነት መገለጫ ነው። ከአጠቃላይ ህዝብ ቁጥሩ ውስጥ 3% የሚሆነው ብቻ ስራ አጥ ሲሆን ሰዎች ስራ ፈትተው በመቀመጣቸው ምክንያት በጭንቀት እራሳቸውን የሚያጠፉባት ሃገር ናት።
ተማሪዎቿ!
ከዓለማችን ብቁ ተማሪዎች ተርታ ይሰለፋሉ። 100% የሚሆነው የሃገሪቷ ወጣቷ በሚገባ ፊደል የቆጠረ እና ቀጥቅጦ የተማረ ነው። ህፃናት ሃገራቸውን እንዲወዱ፣ ቤተሰባቸውን እና ማህበረሰባቸውን እንዲያከብሩ ተድርገው ያድጋሉ! የጃፓን ትምህርት ቤቶች ውስጥ የፅዳት ሰራተኛ አይቀጠርም! "ለምን?" ካልከኝ ከትምህርት በኃላ ሁሉም መምህራን እና ተማሪዎች ለ 15 ደቂቃ ልብሳቸውን ቀይረው ትምህርት ቤቱ ውስጥ የሚገኙ ሁሉንም ክፍሎች(መፀዳጃ ቤትን ጨምሮ) እኩል ያፀዳሉ! የጃፓን ተማሪዎች በሂሳብ፣ ፊዚክስ እና ቋንቋ መጎበዝ ግዴታቸው ነው። ተማሪዎች የፍቅር ግንኙነት መመስረት አይችሉም! እሱ ብቻ ሳይሆን ትምህርት ቤት ውስጥ መሳሳምም ሆነ መተቃቀፍ አይቻልም፣ ያስቀጣል፣ አለፍ ካለም ያስባርራል!
ገራሚ ነገር አንድ!
የዓለማችን ትልቁ አማካይ የመኖርያ እድሜ ያለው ጃፓን ነው። አንድ ጃፓናዊ በአማካይ 83 ዓመት ይኖራል። ውፍረት እንደ ሃጥያት የሚቆጠርባት ጃፓን ውስጥ የተዝረጠረጠው ህዝብ ከ 4% አይበልጥም። ጌታዬ! ይህ አሃዝ አሜሪካ ውስጥ 40% ነው! የመኖራችን ሚስጥር ስፖርት፣ አሳ እና ቅጠላ ቅጠል ነው ይላሉ! ብታምነኝም ባታምነኝም ጃፓን ውስጥ 50 ሺህ እድሜያቸው ከ 100 በላይ የሆኑ ሰዎች ይኖራሉ!
ገራሚ ነገር ሁለት!
የጃፓን ዋና ከተማ የሆነችው "ቶክዮ" ውስጥ ብቻ 38 ሚልዮን ህዝብ ይኖራል! አባዬ! አዲስ አበባ ከ 10 ሚልዮን በታች ሆና ነው እንግዲህ ልንፈነዳ የደረስነው!😀
ይህንን 38 ሚልዮን ህዝብ በብዛት ከቤት ወስዶ ወደ ቤት የሚመልሰው ባቡር ነው። ባቡር ስልህ ታድያ መሃል ላይ መብራት ጠፍቶበት የሚቆመውን አይደለም! የዓለማችን ቁጥር አንድ ቀጠሮ አክባሪ ባቡሮች ያሉት እዛ ነው። አረፈዱ ከተባለ 6 ሰከንድ ነው! አንዴ አንድ ባቡር 18 ሰከንድ አርፍዶ ጉድ ተብሏል! ስራ በሃገሪቷ ባቡሮች መዘግየት ምክንያት ብታረፍድ እራሱ ባቡር ጣብያው "...እገሌ የሚባለው ስራተኛችሁ ያረፈደው በእርሱ ድክመት ሳይሆን በእኛ እንዝላልነት ነውና ይቅርታ!..." የሚል ደብዳቤ ሰጥቶህ ትሄዳለህ! በሰዓት ከ 320 ኪሎ ሜትር በላይ የሚበሩ "bullet train" የሚባሉ ባቡሮች ያሉት እዛ ነው! ጃፓኖች ጋር ባቡር ውስጥ ድምፅን ከፍ አድርጎ ማውራት ሳይቀር እንደ ነውር ይቆጠራል!
ገራሚ ነገር ሶስት!
የምትስተናገድበት ሆቴል ወይም ሬስቶራንት ውስጥ "Tip" ለአስተናጋጅ መስጠት ነውር ነው። ለአንድ አስተናጋጅ "Tip" አስቀምጠህለት ብትሄድ እየሮጠ ተከትሎህ ይመልስልሃል! ለምን?
"...አንተን ማስተናገድ እና መንከባከብ ግዴታችን ነው፣ ስራችን ነው! ለዚህ ስራችን ደግሞ ደሞዝ ይከፈለናል! ስለዚህ ተጨማሪ ብር በ "Tip" መልክ መስጠት አይጠበቅብህም!..." ይሉሃል! እጅግ ሰው አክባሪ እና ትሁት ከመሆናቸው የተነሳ ማንኛውንም እቃ፣ ምግብ ወይም መጠጥ በሁለት እጃቸው እንጂ በአንድ እጃቸው በፍፁም አይቀበሉህም! እሱንም ከወገባቸው ጎንበስ ብለው ነው። የሚገርመው ቤት ውስጥ ውጪ የዋልክበትን ጫማ አድርጎ መግባት ነውር ነው። አይደለም ቤትህ አንዳንድ ምግብ ቤቶች ሳይቀር ተስተናጋጆች ጫማቸውን አድርገው እንዲገቡ አይፈቀድም! በር ላይ ሸበጥ/ሲሊፐር ስለሚቀመጥልህ ቀይረህ መግባት ግድ ነው።
ገራሚ ነገር አራት!
የዓለማችን ሶስተኛው ግዙፍ ኢኮኖሚ የጃፓን ሲሆን ከአጠቃላይ ኤክስፖርት ከሚያደርጉት ምርት 23% የሚሆነው መኪና ነው። 38% የሚሆነው ደግሞ ኤሌክትሮኒክስ ምርት ነው። 98% የሚሆነው ህዝብ በብሄር፣ በቋንቋ እና በባህል ተመሳሳይ(Homogeneous) ነው። ጃፓናዊያን እጅግ ስርዓት ያላቸው፣ ሰው አክባሪዎች እና በህግጋት የተመሉ ስለሆኑ ከሌላ ሃገራት ለስራም ሆነ ለጉብኝት የሚመጡ ሰዎች ጃፓን ውስጥ መኖር ይቸገራሉ!
ገራሚ ነገር አምስት!
ለሃገር ቅድሚያ መስጠት፣ ለሃገር ክብር መሞት(መሰዋት) እና ለሰዎች ቅድሚያ መስጠት ጃፓን ውስጥ እንደ ባህል ይቆጠራል። የ "Titanic" መርከብ በሰመጠችበት ወቅት እንደምንም ብሎ የተረፈ አንድ ጃፓናዊ ወደ ሃገሩ ሲመለስ "እራስ ወዳድ ነህ! እንዴት መርከቧ ስትሰጥም ከሞቱት ሰዎች ጋር አብረህ አትሞትም!?" ተብሎ እንደተንቋሸሸ ይነገራል!
አስደማሚ ታሪክ!
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት (እ.ኤ.አ 1939-1945) ጃፓን በአሜሪካ ከፍተኛ ሽንፈት እየገጠማት ትመጣለች! የጃፓን የጦር ጀቶች በቀላሉ በአሜሪካ እየተመቱ መውደቅ ይጀምራሉ! ወታደሮቿም ማለቅ ጀመሩ! ጦርነቱን መሸነፋቸውም እውን እየሆነ ይመጣ ጀመር!
በወቅቱ የጃፓኑ ንጉስ ጋር ወታደሮች እና የጦር አውሮፕላን አብራሪዎች እየተሸነፉ መምጣታቸው አሸማቋቸዋል! እንደ አምላክ የሚታየው የሃገሪቱ ንጉስም "...ተሸንፋችሁ ከምትመጡ ለሃገራችሁ እና ለዙፋኔ ክብር ስትሉ አጥፍታችኃቸው ጥፉ!..." ብሎ አዘዛቸው!
ጌታዬ!
አንድ ለማኝ ከሰላሳ አምስት አመታት በላይ ከመንገድ ዳር ተቀምጦ ይለምን ነበር። አንድ ቀን አንድ እንግዳ ሰው ወደ እርሱ መጣ፤ ለማኙም ገንዘብ መቀበያ ኮፍያውን እያሽከረከረ ለእንግዳውን ሰው "ገንዘብ ስጠኝ" አለው። "እኔ የምሰጥህ የለኝም" አለ እንግዳው ሰው። ለማኙንም ጠየቀው
"ምን ላይ ነው የተቀመጥከው?"
"ምንም አይደለም" አለ ለማኙ "አንድ ተራ ሳጥን ነው። እስከማስታውሰው ድረስ እዚህ ላይ ለብዙ አመታት ተቀምጬያለሁ።"
"ውስጡንስ አይተኸው ታውቃለህ?" እንግዳ ሰው ጠየቀ
"አይ" አለ ለማኙ "ምን ይፈይድልኛል ብለህ ነው። ምንምም አይኖረውም"
"እስኪ ውስጡን ክፈትና ተመልከት" እንግዳው ለማኙን እንዲመለከት ገፋፋው።
ለማኙ እንደምንም ታግሎ የሳጥኑን ክዳን ከፈተው። በአግራሞት እና ባለማመን ፈዞ ቀረ። ሳጥኑ በወርቆች ተሞልቷል።
እኔ እንግዳ ሰው ነኝ፤ ወደ ውስጥ እንድትመለከትም እገፋሃለሁ።
"እኔ ለማኝ አይደለሁም" ስትል ይሰማኛል።
እነዚያ ምን እንደሚፈልጉ የማያውቁ፣ የሚወዱትንም ህይወት የማይኖሩ - ለማኞች ናቸው። ገንዘብ ቢኖራቸው እንኳ ለማኝ ናቸው። ሁሌም ቢሆን ውጪያዊ ከሆነው አለም የሆነ ነገርን ይፈልጋሉ። ፍቅርን፣ ደህንነትን ተቀባይነትን፣ ደስታን ወዘተ የማይፈልጉት የለም። እኔ ግን እልሃለሁ፤ የማያልቅ እልፍ ዋጋ ያለው ወርቅ በውስጥህ አለ፤ ወደ ውስጥም ተመልከት።
መጽሐፉ አስተሳሰባችንን ልከኛ ያደርገዋል
ተግባራችንን ውጤታማ ያደርገናል
ምስቅልቅላችንን አስተካክሎ ቅርጽ ይሰጠዋል
በዘፈቀደ መኖር አቁመን በተግባር በተፈተኑ የስኬት መርሆዎች አማካይነት በልኬት ወደ ስኬት የምንሻገርበት መጽሐፍ ነው፡፡
መለኪያውም፣ ማሳኪያውም መንገድ በመጽሐፉ ውስጥ ተቀምጧል፡፡ እንለካለን፣ እናሳካለን!!
በልኬት ወደ ስኬት
@snetsehuf
ዛሬ ምን አነበቡ?
*****
"ቱትሲ የሆናችሁ ሁሉ ከመቀመጫቹህ አንዴ ብድግ በሉ" መምህር ቡሆሮ ጮክ ብሎ ተናገረ፡፡ በእጁ ላይ የክፍል ተማሪዎች ስም ዝርዝር ይዟል፡፡ በትኩረት እያጠናው ነው፡፡ ድንገት የኔስምን ሲያይ ወደኔ ማፍጠጥ ጀመረ፡፡
"ኢማኩኤሌ ኢሊባጊዛ..ለምንድን ነው የማትነሺው? ሁቱዎች ተነሱ ስል አልተነሳሽም፡፡ ትዋም ስል ቁጭ ብለሻል አሁን ቱትሲዎችም ብድግ በሉ ስል ንቅንቅ አላልሽም..ለምንድን ነው?" አለኝ ፈገግታ ፊቱ ላይ ቢታይም በድምፁ ግን ማስፈራራት ይነበባል፡፡
"አላውቅም መምህር" መለስኩለት
"እንዴ..ምኑን ነው የማታውቂው..ጎሳሽ ምንድን ነው እኮ ነው ያልኩሽ?"
"እኮ.እኔ እንጃ አላወቅም?"
"ሁቱ ነሽ ወይስ ቱትሲ?"
"እ..አላ..አ..ላውቅም መምህር"
"ውጪ....ጎሳሽን ካላወቅሽ ሁለተኛ እዚች ክፍል እንዳትረግጪ" በጩኸት አባረረኝ፡፡
ደብተሮቼን ሰብስቤ በሀፍረት ከክፍሌ ወጣው፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ በሀገሬ ሩዋንዳ ያለው የጎሳ ክፍፍል ጉዳይ በመጥፎ ሁኔታ አነቃኝ፡፡
*
Left to Tell
ታሪካዊው የሩዋንዳ ጭፍጨፋ ላይ ተመስርቶ የተፃፈ እውነተኛ ታሪክ፡፡
ከጎሰኝነት የተነሳ ስር የሰደደ ጥላቻ፣ ቂም እና በቀል፣ እምነትና ይቅርባይነት መልኮችን ኩልል አድርጎ የሚያሳይ.
ከአሰቃቂ የዘር ፍጅት ለወሬ ነጋሪ የቀረች አንዲት ወጣት አስገራሚ ህይወት የሚተርክ፡፡
"Left to tell"(ሁቱትሲ ተብሎም በአማርኛ ተተርጉሟል) .ቀላል የሚመስሉ ማህበራዊ ሁኔታዎች በግዜ ካልታከሙ ምን ያህል እልቂት ሊያስከትሉ እንደሚችሉ በግልፅ የሚያስተምር ነው፡፡
መፅሀፉ በ100 ቀናት ውስጥ ከ 800,000 በላይ ቱትሲ ሩዋንዳውያን አሳዛኝ እልቂት ይተርካል፡፡ እኛም በጊዜ ባይባልም ብዙ ሳይረፍድ የምንማርበት ነውና.
አንብቡት!
@snetsehuf
ማነው ላገር ያላት አለሁሽ የሚላት
እቅፍ ድግፍ አርጎ የሚንከባከባት።
መዋረድን ጠልቶ ኩራቷን ተጠምቶ
ጥቅሙን ወዲያ ጥሎ ድምጹን አሰምቶ
ህብረትን ሰንቆ ባንድነቱ ፀንቶ
የሚታደግ ማነው? ህይወቱን ሰውቶ ።
ግጥሙ ከተመቻችሁ ሼር አድርጉ @snetsehuf
