የእግዚአብሔር ሀሳብ እና የሙሴ ትህትና
በሙሴ ህይወት የተመለከትናቸው ያልተደገሙ ተአምራት የሙሴን የአገልግሎት ከፍታ በሚገባ የሚያመለክቱ ናቸው ።
ሙሴ ምንም እንኳን በብዙ ግፊት ወደ ግብጽ ቢሄድም ተልእኮውን ከተቀበለበት እስከ ፈጸመበት የ40አመት ጉዞ እግዚአብሔርም እንደመሰከረለት ፍጹም ትሁት ነበር ። በግብጽ ከነበሩት ጠንቋዮች የላቀ ተአምራት ቢያደርግ የሚኮራ አልነበረም ፣ በፈርኦን ፊት ቆሞ ቤተ መንግስትን እስኪንጥ ድረስ የእግዚአብሔርን ክንድ ቢገልጥ አይመጻደቅም፣ በግብፅ እና በእስራኤል መካከል ግልጽ ልዩነት እስኪታይ ድረስ የእግዚአብሔርን ክንድ ቢገልጥ እራሱን አይኮፍስም ፣ ውሀ እንደ ግርግዳ ቆሞ እያየ
''
እኔ '' ብሎ ወደራሱ አያመለክትም ። የሙሴ ህይወት ብዙ የሚያስተምረን ቁም ነገር ቢኖርም ለዛሬ ግን ልቤን የነካኝን የሙሴን የትህትና ጥግ ላካፍላችሁ ።
“እግዚአብሔርም ሙሴን፦ ከአንተ ጋር ስነጋገር ሕዝቡ እንዲሰሙ፥ ደግሞም ለዘላለም እንዲያምኑብህ፥ እነሆ በከባድ ደመና እመጣልሃለሁ አለው። ሙሴም የሕዝቡን ቃል ለእግዚአብሔር ነገረ።”
— ዘጸአት 19፥9
ይህ ክፍል በግልጽ የሚናገረው እግዚአብሔር ለሙሴ በህዝቡ ዘንድ ቅቡልነትን እንዲያገኝ ያሰበውን ሀሳብ የሚያወሳ ነው።
እግዚአብሔር ህዝቡ በሙሴ እንዲያምን ፣ እውጥቶ በሜዳ እንደማይጥላቸውና እግዚአብሔር ያለው ቦታ እንደሚያደርሳቸው እንዲተማመኑ ፈልጓል ። ለዚህም
'' ...በከባድ ደመና እመጣልሀለሁ...'' በማለት የአሁኑ መገለጥ ህዝቡ ሁሉ በሙሴ እንዲያምኑ መሆኑን ያስረዳል ።
ብዙ ታምራቶች ታይተዋል ነገር ግን በተገለጡት ተአምራት ሳይሆን ፤ በተገለጠ እግዚአብሔር የሙሴ መመረጥ በህዝቡ ልብ እንዲታተም ያስፋልጋል ። ይህ ትልቅ እድል ይመስላል እራስን ከፍ ለማድረግ ። በሰወች አንቱታን ለማግኘት ከዚህ የተሻለ አጋጣሚ ምን ይገኛል ? ያህዌ ሙሴን ሊያስተዋውቅ ሰው ሁሉ እያየው በደመና ሲገለጥ ፣ ከዚያም አልፎ ..ድሮ ''
ተናገረኝ'' ብሎ መልዕክት የሚያመጣ ሙሴ ዛሬ ግን ህዝብ ሁሉ እየሰማ ታላቁን አምላክ ሲያወራው መስማት ። ይገርማል!! አብሶ በእኛ ዘመን እንዲህ ያለ እድል ቢገኝ ምን እንዳምንሆን አላውቅም ። ምክንያቱም ትንሽ የመለኮት እሳት በጉባኤያችን ስትገለጥ የብዙዎቻችን አራማመድ ሲቀየር ፣ ስማችን ለራሳችን አልጥም ብሎን ሜጀር ማይነር ስንል፣ የመለኮትን ዙፋን ለመጋራት ሲዳዳን ተመልክተናል።
ምንም እንኳን እግዚአብሔር የተገለጠበት አላማ ይሄ ቢሆንም ሙሴ ግን ከዚህ አስፈሪ እና ባለብዙ ግርማ ከሆነ የመለኮት መገለጥ ለራሱ ክብርን ለማትረፍ አልሞከረም ።
“ሙሴም በምድር ላይ ካሉት ሰዎች ሁሉ ይልቅ እጅግ ትሑት ሰው ነበረ።”
— ዘኍልቁ 12፥3
የሙሴ አንዱ የትህትና ጥግ ይሄ ነበር
👉እግዚአብሔር እንደተናገረ በህዝቡ ሁሉ ፊት ተገለጠ !!
👉በጣም የሚያስፈራና የሚያስደነግጥ ነበር 🔥🔥ህዝቡ ሁሉ በፍርሀት እንኪንቀጠቀጡ ድረስ የእግዚአብሔር ክብር የሚያስፈራ ነበር።
ዘጸአት 20
¹⁸ ሕዝቡም ሁሉ ነጐድጓዱንና መብረቁን፥ የቀንደ መለከቱን ድምፅ፥ ተራራውንም ሲጤስ አዩ፤ ሕዝቡም ባዩ ጊዜ ተርበደበዱ፥ ርቀውም ቆሙ።
👉ድምጹን ለመስማት አቅም ስላልነበራቸው ...
ዘጸአት 20
¹⁹ ሙሴንም፦ አንተ ተናገረን እኛም እንሰማለን፤ እንዳንሞት ግን እግዚአብሔር አይናገረን አሉት።
ሙሴ በዚህ ሰአት ምን መለሰ ?
''እኔ ማለት''ብሎ እራሱን ከማሳየት ይልቅ የተገለጠውን እውነተኛ አምላክ ማሳየትን መርጧል ። ምንም እንኳን የእግዚአብሔር መገለጥ ሙሴን ህዝቡ እንዲያምነው ፣ በፍጹም ልቡ እንዲቀበለው ቢሆንም ፤ ሙሴ ግን ህዝቡን ወደ ልኡሉ አመለከተ።
ዘጸአት 20
²⁰ ሙሴም ለሕዝቡ፦ እግዚአብሔር ሊፈትናችሁ፥ ኃጢአትንም እንዳትሠሩ እርሱን መፍራት በልባችሁ ይሆን ዘንድ መጥቶአልና አትፍሩ አለ።
👉 ይሄ ሞኝነት ሳይሆን ትህትና ነው ።
👉ሙሴ ያገኘውን እድል አላበላሸም፤ ነገርግን :-
✔የመክበሩን ምክንያት አከበረ ፣
✔የከፍታውን ምንጭ ከፍ አደረገ ፣
✔የሰው ሁሉ ትኩረት ሊሆን የሚገባውን አሳየ እንጂ።
👉 በህይወታችን እግዚአብሔር ከከበረ በውጭ ማክበር አይከብደንም!
👉በግል እግዚአብሔርን ካየነው እራሳችንን ለማሳየት አቅም እይኖረንም!
👉የጸጋ ስጦታ መንፈስ ቅዱስን በመግለጥ ቤተ ክርስትያንን ለማነፅ ፡ ከዛም እየሱስን ማክበር እንጂ ግቡ ፤ እኛን የመግለጥና የማክበር አላማ የለውም ። “ነገር ግን መንፈስ ቅዱስን መግለጥ ለእያንዳንዱ ለጥቅም ይሰጠዋል።” 1ኛ ቆሮንቶስ 12፥7
🙏 በዘመናችን ከእግዚአብሔር በተቀበሉት እግዚአብሔርን የማይጋርዱ ፣ ይልቁንም አጋጣሚዎችን ሁሉ እሱን ለማክበርና ለማሳየት የሚጠቀሙ ሀያላን ይነሱልን !!
🙏 እንደተቀበለ ሰው የሚመላለሱ፣ ለራሳቸውም ለቤተ ክርስቲያንም የሚበጀውን የሚያዩና ዝቅ ብለው የሚሮጡ ይብዙልን!!!
የጌታ ሰላም ይብዛላችሁ🙏🙏
🖋🖋🖋
ሱራፌል አማሀ
👇👇👇👇👇Join👇👇👇👇👇
https://t.me/Diorthosis
https://t.me/Diorthosis
https://t.me/Diorthosis