en
Feedback
Tariku Abera

Tariku Abera

Open in Telegram

ኦርቶዶክሳዊ የወንጌል አገልግሎት

Show more
5 173
Subscribers
No data24 hours
-87 days
-2530 days
Posts Archive
photo content

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከልዩ ልዩ ሀገሮች ክርስቲያኖች የሰበሰበውን ዕርዳታ ለኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያን በመያዝ ሦስተኛውን ጉዞ አጠናቅቆ ኢየሩሳሌም ገባ። ነገር ግን ኢየሩሳሌም የገባበት ጊዜ የፋሲካ በዓል ስለነበር ከልዩ ልዩ ሀገሮች የተሰበሰቡ አይሁድ በከተማዋ ነበሩ። እነዚህ በዝርወት የሚኖሩ አይሁድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን በየሀገራቸው በትምህርቱ የተነሣ ሲቃወሙት የነበሩ ናቸው። እኒህ አይሁድ ቅዱስ ጳውሎስን በኢየሩሳሌም ሲያዩት ታላቅ ተቃውሞ አነሡበት። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ተቃውሞ አነሡበት። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ተቃውሞአቸውን ለመግታት እንደ አይሁድ ሕግ በቤተ መቅደስ የመንጻት ሥርዓት መፈጸም ጀመረ። ነገር ግን ከኤፌሶን የተከተለውን ጥሮፊሞስን ወደ መቅደስ ያስገባው ስለመሰላቸው ተቃውሞአቸው በረታ። ከተማውንም አወኩት፤ ይህ ቅዱስ ጳውሎስን በ58 ዓ.ም. ለሮም እሥር የዳረገው። ከብዙ መከራና ስቃይ በኋላ ታስሮ ሮም ገባ። በዚያም በቁም አሥር ለሁለት ዓመታት ያህል ወንጌልን ሰበከ። የሁለቱን ዓመት የቁም እሥር እንደጨረሰ ወደ ኔሮን ፍርድ ቤት ቀረበ። ይህም በ60 ዎቹ ዓ.ም. ነው። በፍርድ ቤቱ በተደረገው ምርመራ የሮሜን ሕግ የሚቃወም ምንም ወንጀል ስላልተገኘበት በነፃ ተለቀቀ፤ ከዚህ በኋላ ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አራተኛውንና የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ያልመዘገበውን ጉዞውን ያደረገው። ይህ ጉዞው በመታሠሩ አዝነው ተክዘው የነበሩ ክርስቲያኖችን ለማጽናናት የጀመራቸውን ሥራዎች ፍጻሜ ለማየት የተደረገ ጉዞ ነው። በዚህም ጉዞው ኢየሩሳሌምን፣ ኤፌሶንን፣ ሎዶቅያን፣ መቄዶንያን፣ ቀርጤስን፣ ጢሮአዳን፣ ድልማጥያን፣ እልዋሪቆን፣ ኒቆጵልዮን፣ ብረንዲስን፣ ጎብኝቷል። በዚህ የመጨረሻ የስብከት ጉዞው ለአራት ዓመታት ያህል ቆይቷል። በመጨረሻ በ64 ዓ.ም. ኔሮን በጥጋቡ የሮማ ከተማ ስትቃጠል ምን እንደምትመስል ማየት እፈልጋለሁ ብሎ አቃጠላት። የሮም ሕዝብ በከተማው መቃጠል በማዘኑና በማመፁ ነገሩን ሁሉ በክርስቲያኖች ላይ አሳበበ። በዚህም የተነሣ ክርስቲያን የተባለ ሁሉ መሰደድ፣ መሠየፍ፣ መታረድ ዕጣ ፈንታው ሆነ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በኒቆጵልዮን ከተማ ሲያስተምር በ65 ዓ.ም. ተይዞ ወደ ወኅኒ ገባ። ለሁለት ዓመት ከስድስት ወር በጨለማ ቤት ታሥሮ ከቆየ በኋላ በ74 ዓመት ዕድሜው በሮም ከተማ በኦስትያ መንገድ አንገቱን ተሰይፎ በ67 ዓ.ም. ሐምሌ ፭ ቀን በሰማዕትነት ዐረፈ። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ሁለት ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ ዐስራ አራት መልእክታትን ጽፈዋል። የቅዱሳኑ ሐዋርያት ረድኤትና በረከታቸው ከሁላችን ጋር ይሁን፤ አሜን። ለሌሎችም አጋሩት

ክፍል 2 2. ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ዘሩ ከዕብራዊያን፣ ከብንያም ነገድ ሲሆን የተወለደውም በጠርሴስ ከተማ ነው። ጠርሴስ በንግድዋ የታወቀች የኪልቂያ ዋና ከተማ ናት። በከተማዋ እስከ አምስት መቶ ሺህ የሚገመቱ ከየሀገሩ የተሰባሰቡ ሕዝቦች ነበሩባት። ሮማውያን በሥራቸው ለሚተዳደሩት ሕዝቦች ሮማዊ ዜግነትን ይሰጡ ስለነበር፥ የቅዱስ ጳውሎስ አባት በዜግነት ሮማዊ ነበር። ይህም ለቅዱስ ጳውሎስ ተላልፎለታል። ቅዱስ ጳውሎስ በ15 ዓመት ዕድሜው ወደ ትውልድ ሀገሩ በመመለስ በኢየሩሳሌም ከነበረው የታወቀው የገማልያል ትምህርት ቤት ገባ። በዚያም የአይሁድን ሕግና ሥርዓት እየተማረ እስከ 30 ዓመቱ ቆየ። ገማልያል ፈሪሳዊ ስለነበር ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ይህን ተቀብሎታል። በ30 ዓመቱ የአይሁድ ሸንጎ አካል ሆኖ ተቆጠረ። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚያስተምርበት ዘመን ቅዱስ ጳውሎስ በኢየሩሳሌም ስለነበረ ሁኔታዎቹን ሁሉ ያውቃል። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በአይሁድ ሸንጎ አባልነት ለሁለት ዓመታት በሠራበት ወቅት ለኦሪታዊ እምነቱ ቀናተኛ ፈሪሳዊ በመሆኑ ክርስቲያኖችን በማናቸውም አጋጣሚ ይቃወም ነበር። እንዲያውም ሊቀዲያቆናት እስጢፋኖስን በማስተማሩ ምክንያት ተከሶ ለአይሁድ ሸንጎ በቀረበ ጊዜ የተከራከረው እርሱ ነበር። በድንጋይ ተወግሮ በሰማዕትነት ሲያርፍም የወጋሪዎችን ልብስ ይጠብቅ የነበረው እርሱ ነው። ቅዱስ አውግስጢኖስ «በእስጢፋኖስ ጸሎት፣ ቤተ ክርስቲያን የተፋውን ጳውሎስን አገኘች፤» በማለት ተናግሯል። በ32 ዓመት ዕድሜው ከኢየሩሳሌም 223 (ሁለት መቶ ሃያ ሦስት) ኪ.ሜ. ርቀት በስተሰሜን በኩል በምትገኘው የደማስቆ ከተማ ብዙ ክርስቲያኖች መኖራቸውን ሲሰማ ወደ ሊቀ ካህናቱ ቀርቦ ክርስቲያኖችን ለማጥፋት የሚያስችለውን የፈቃድ ደብዳቤ አገኘ። ከዚህም በኋላ ጭፍሮችን አስከትሎ ወደ ደማስቆ አመራ። ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ከተማዋ ለመድረስ ጥቂት ሲቀረው ነበር ከሰማይ የወረደው ብርሃን አካባቢውን ያለበሰውና «ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ?» የሚለውን ድምፅ የሰማው። ሐዋርያው ጳውሎስም «ጌታ ሆይ ማን ነህ?» ብሎ ጠየቀ። «አንተ የምታሳድደኝ እኔ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ። የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብሃል» ሲል መድኃኒታችን ተናገረው። ያን ጊዜም በወደቀበት ሆኖ እየተንቀጠቀጠ «ጌታ ሆይ ምን አደርግ ዘንድ ትወዳለህ?» ሲል ጠየቀ። ከዚህ በኋላ ተነሥቶ ወደ ደማስቆ እንዲገባ ተነገረው። (የሐዋ. 9፥1) የሐዋርያው ዓይኖች ለማየት አልቻሉም። እየተመራ ወደ ደማስቆ ገባ። ለሦስት ቀናት ያህልም እህል ሳይቀምስ ቆየ። በዚያች ዕለት እግዚአብሔር አምላክ በደማስቆ ለሚገኘው እና ሐናንያ ለተባለው አባት በራእይ ተገለጠለት። ቅዱስ ጳውሎስም ያለበትን አድራሻ ነገረውና ሄዶ እንዲያጠምቀው አዘዘው። ሐናንያ አስቀድሞ የቅዱስ ጳውሎስን ማንነት ያውቃል። አብዛኞቹ በደማስቆ የሚገኙት የቅዱስ ጳውሎስን ማንነት ያውቃል። አብዛኞቹ በደማስቆ የሚገኙት ክርስቲያኖች ከኢየሩሳሌም በስደት የመጡ ናቸው። ያን ስደት ያስነሣው ደግሞ በቅዱስ እስጢፋኖስ ላይ የደረሰው መከራ ነው። በዚህ የቅዱስ እስጢፋኖስ ሰማዕትነት ደግሞ ዋናው ተዋናይ ሐዋርያው ጳውሎስ ነበር። ይህን የሚያውቀው ሐናንያ በቅድሚያ ከእግዚአብሔር ጋር መከራከር ጀምሮ ነበር። እግዚአብሔር አያውቀው ይመስል ስለ ቅዱስ ጳውሎስ ማስረዳት ጀመረ። በመጨረሻ ግን «ይህ በአሕዛብም በነገሥታትም በእሥራኤልም ልጆች ፊት ስሜን ይሸከም ዘንድ ለእኔ የተመረጠ ዕቃ ነውና ሂድ፤ ስለ ስሜ ስንት መከራ ሊቀበል እንዲያስፈልገው እኔ አመለክተ ዋለሁና» በማለት እግዚአብሔር ሐናንያን ላከው። ሐናንያ ቅዱስ ጳውሎስን ካጠመቀውና ካስተማረው በኋላ ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ዓረብ ሀገር መሄዱን ራሱ ተናግሮአል። (ገላ 1፥17) ለ3 ዓመታት በዓረቢያ በረሃ ከቆየ በኋላ ወደ ደማስቆ ከተማ ተመለሰ። በዚያም በነበሩ አይሁድ መካከል በፊት ያሳድደው የነበረውን ኢየሱስ ክርስቶስን መስበክ ጀመረ። ከዚያ በፊት በፈሪሳዊነቱና ለአይሁድ ሕግ በነበረው ቅንዓት የሚታወቀው ጳውሎስ ዛሬ ወንጌል ሲሰበክ በማየታቸው አይሁድ ተነሡበት። በዚህም የተነሣ የደማስቆ ክርስቲያኖች በቅርጫት አውርደው ወደ ኢየሩሳሌም ላኩት። ቅዱስ ጳውሎስ ኢየሩሳሌም ሲደርስ የገጠመው ሁለት ችግር ነበር። በቅድሚያ አይሁድ ጳውሎስን እንደሚያውቁት እና እንደለመዱት ሆኖ ስላላገኙት ሊገድሉት ተነሡ። በሌላ በኲል ደግሞ ክርስቲያኖች የቅዱስ ጳውሎስን መመለስ ሊያምኑ አልቻሉም። በመጨረሻ ግን በርናባስ ወደ ሐዋርያት ዘንድ ወስዶ የጳውሎስን መመለስ በመተረክ እንዲያምኑት አደረጋቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በኢየሩሳሌም በድፍረት በማስተማሩ አይሁድ ስለተቃወሙት ከተማዋን ትቶ በቂሳርያ በኲል ወደ ትውልድ ሀገሩ ጠርሴስ ተመለሰ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በጠርሴስ ከተማ ለዘጠኝ ዓመታት ቆይቷል። ከኢየሩሳሌም ውጭ የአሕዛብ ከተማ በነበረችው በአንጾኪያ የክርስትና ሃይማኖት ተስፋፋ። ከኢየሩሳሌም የተሰደዱት ክርስቲያኖች የአንጾኪያን ሕዝብ ተግተው በማስተማራቸው ዝናው እስከ ኢየሩሳሌም ደረሰ። በዚህም ምክንያት በኢየሩሳሌም የነበሩት አበው በርናባስን ወደ አንጾኪያ ላኩት። በርናባስ የግሪክ ቋንቋ ችሎታ ያለውን፣ ከማንኛውም ሰው ጋር መግባብ የሚችለውን፣ ደግሞም እግዚአብሔር ለአሕዛብ ሐዋርያ እንዲሆን የመረጠውን ቅዱስ ጳውሎስን ከጠርሴስ በማምጣት በአንጾኪያ ሥራቸውን ጀመሩ። በገላትያ መልእክቱ ምዕራፍ ፪ ላይ ራሱ እንደገለጠው ከአሥራ አራት ዓመት በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ከአንጾኪያ ክርስቲያኖች የሰበሰበውን ርዳታ ይዞ ወጣ። በዚህም በአይሁድና በአሕዛብ መካከል የነበረውን መለያየት ክርስትና አንድ እንዳደረገው አስመሰክሯል። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመጀመሪያው ጉዞ ያደረገው ከኢየሩሳሌም ወደ አንጾኪያ ከተመለሰ በኋላ በልዑል እግዚአብሔር ጥሪ በአሕዛብ ሀገር ወንጌልን ለመስበክ ከበርናባስ ጋር ወጡ። በዚህ ጉዞአቸው በጠቅላላ ወደ ፪፼ (ሁለት ሺህ) ኪሎ ሜትር የሚደርስ መንገድ በእግር ተጉዟል። ይህም ጉዞ የተከናወነው በ46 ዓ.ም. አካባቢ ነው። የተሸፈኑትም ሀገሮች ሲሊንውቂያ፣ ቆጵሮስ፣ ስልማን፣ ጳፋ፣ ጰርጌን፣ ገላትያ፣ ጵስድያ፣ ኢቆንዮን፣ ሊቃኦንያ፣ ልስጥራ፣ደርቤን፣ጵንፍልያ፣አታልያና አንጾኪያ ናቸው። ሁለተኛው ጉዞ የተከናወነው በ50 ዓ.ም. ገደማ ነው። በመጀመሪያው ጉዞ ማርቆስ አብሮ ተጉዞ ነበር። ነገር ግን ጵንፍልያ ከተማ ሲደርስ እናቱ ስለናፈቀችው መመለስ በመፈለጉ በርናባስ ወደ ኢየሩሳሌም ይዞት መጣ። ስለዚህም በሁለተኛው ጉዞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲላስን ይዞ ወደ ኪልቂያ ሶርያ ሲጓዝ በርናባስ ደግሞ ማርቆስን አስከትሎ ወደ ቆጵሮስ ሄደ። በዚህ ጉዞው ቅዱስ ጳውሎስ እስከ ግሪክ ደርሶአል። የተጓዘባቸውና ያስተማረባቸው ከተሞችም፦ ደርብያ፣ ልስጥራ፣ፍርግያ፣ ገላትያ፣ ሚስያ፣ጢሮአዳ፣ ሳሞትራቄ፣ ናፑሊ፣ ፊልጵስዩስ፣ ተሰሎንቄ፣ በርያ፣አቴና፣ ቆሮንቶስ፣ አንክራኦስ፣ አፌሶን፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌምና አንጾኪያ ናቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመንፈስ ልጁ ጢሞቴዎስን ያገኘው በዚሁ ጉዞው በልስጥራ ከተማ ነው። ሦስተኛው ጉዞ የተከናወነው በ54 ዓ.ም. ሲሆን የተሸፈኑትም ሀገሮች የሚከተሉት ነበሩ። ገላትያ፣ ፍርግያ፣ ኤፌሶን፣ መቄዶንያ፣ ፊልጵስዩስ፣ ቆሮንቶስ፣ ጢሮአዳ፣ አሶን፣ ሚልጢኒን፣ አንጠቀከስዩ፣ ትሮጊሊዩም፣ መስጡ፣ ቆስ፣ ሩድ፣ ጳጥራ፣ ጢሮስ፣ ጵቶልማይስ፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌም ናቸው።

photo content

አካባቢ በኢየሩሳሌም በተደረገው የሐዋርያት ሲኖዶስ ከአንጾኪያ ክርስቲያኖች ለቀረበው ጥያቄ የመጀመሪያውን መልስ የሰጠው እርሱ ነበር። ስለ ቅዱስ ጴጥሮስ መልክና ቁመና ጥንታዊያን መዛግብት እንደሚከተለው ያቀርቡታል። «ፊቱ ሰፋ ያለ ሲሆን ሪዛምና መካከለኛ ቁመት የነበረው ራሰ በራ ሰው ነው። በማናቸውም ነገር ፈጣንና ቀልጣፋ ነበር።» በቤተ ክርስቲያን ታሪክ መሠረት ቅዱስ ጴጥሮስ በፍልስጥኤም፣ በሶርያ፣ በጳንጦን፣ በገላትያ፣ በቀጰዶቅያ፣ በቢታንያ እና በሮሜ ሰብኳል። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በሮሜ አንድ ዓመት ከቅዱስ ጳውሎስ ጋር ካስተማረ በኋላ የሮሜ ክርስቲያኖች እየበዙ ከመምጣታቸውም በላይ የክርስትናው ጉዞ እስከ ሮማ ባለሥልጣናት ደረሰ። የኔሮን የቅርብ ባለሥልጣናት የሆኑት የአልቢኖስና የአግሪጳ ሚስቶች ወደ ክርስትናው ገቡ። በዚህን ጊዜ ኔሮን ንጉሠ ሮማ በቅንዓት ተነሣባቸው። ኔሮን በሮም የነገሠው በ54 ዓ.ም. ነው። በመንግሥቱ መጀመሪያ ደግ ሰው ነበረ። ነገር ግን በነገሠ በዓመቱ የጨካኝነት ዐመሉ ብቅ ማለት ጀመረ እና የአባቱን ልጅ አስገደለ። በ 59 ዓ.ም. ደግሞ እናቱን በመርዝ ገደለ። በ63 ዓ.ም. እያስተማረ ያሰደገውን መምህሩን ፣ በ62 ዓ.ም. የልጅነት ሚስቱን አግታሺያን አስገደለ። ከእርስዋ በኋላ ያገባትን ሚስቱንም ፓፒያን በርግጫ ብሎ ገደላት። ኔሮን በ 64 ዓ.ም. እርሱ ከከተማው ወጣ ብሎ በሚገኘው ቤተ መንግሥቱ ተቀምጦ የሮማን ከተማ እሳት ለቀቀባት። የሮም ሕዝብ በደረሰው አደጋ እጅጉን ተቆጣ። ኔሮንም በክርስቲያኖች አመካኘ። በዚህም የተነሣ በሮማ ከተማ ሁለት ዓይነት ወሬ መናፈስ ጀመረ። የሮማ አማልክት በክርስቲያኖች ሃይማኖት ስለተቆጡ በከተማዋ እሳት አዘነቡባት የሚለው የመጀመሪያው ሲሆን ክርስቲያኖች ሆን ብለው ከተማዋን አቃጥለዋታል የሚለው ደግሞ ሁለተኛው ወሬ ነበር። የከተማው መጋየት ያበሳጨው የሮማ ሕዝብ፣ ክርስቲያን የሆነውን ሁሉ እያወጣ መግደሉን ተያያዘው። ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ ሰዓት በእሥር ነበርና ይህን የሰሙት የአግቢኖስና የአግሪጳ ሚስቶች (የሮም ባለሟሎች ነበሩ) «ባይሆን አንተ ትረፍልን» ብለው በከተማዋ ግንብ በገመድ አሥረው በቅርጫት በማውረድ ቅፅረ ሮማን ለቅቆ እንዲወጣ አደረጉት። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በኦፒየም ጎዳና ጉዞውን ቀጠለ። ሮማን ለቀቀ። እያዘገመ በሸመገለ ጉልበቱ ሲጓዝ አንድ ቀይ ጐልማሳ ወደ እርሱ ሲመጣ አየ። እየቀረበ ሲመጣ ጌታችን መሆኑን ተረዳ። ወዲያው በፊቱ ተደፋና «ጌታዬ ወዴት እየተጓዝክ ነው?» አለና ጠየቀው። «ዳግም በሮም ልሰቀል» አለው። በዚህ ሰዓት ቅዱስ ጴጥሮስ አዘነና እንደገና ወደ ሮማ ተመለሰ። የኔሮን ወታደሮች እየፈለጉት ነበር። «እነሆኝ ስቀሉኝ» አለ ቅዱስ ጴጥሮስ። ያን ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስን ይዘው አሠሩት። ከጥቂት ቀናት በኋላም ሮማውያን የመስቀያውን እንጨት አቀረቡለት። ያን ጊዜ «እኔ እንደ ጌታዬ ልሰቀል አይገባኝም» በማለት ቁልቁል እንዲሰቅሉት ለመነ። ያለውንም አደረጉለት። ሐምሌ 5 ቀን 67 ዓ.ም. በሰማዕትነት ዐረፈ። ክፍል 2 ይቀጥላል

† ብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወቅዱስ ጳውሎስ † ክፍል - 1 ከመጽሐፍ ቅዱስ የአዲስ ኪዳን ክፍል የሆነው የሐዋርያት ሥራ በቅዱስ ሉቃስ የተጻፈ ሲሆን ይህ ክፍል ቅዱሳን ሐዋርያት በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ተመልተው አገልግሎት መጀመራቸውንና በወቅቱ ስለ ነበራቸው አገልግሎት በጥቂቱ ይናገራል እንጂ መላ ሕይወታቸውን እንዴት አድርገው እንደተጋደሉና ወንጌልን እንዴት እንደ ሰብኩ በስፋት አያትትም።ስለ ቅዱሳን ሐዋርያት የእያንዳንዳቸውን የሕይወት ዘመናቸውን ታሪክና አገልግሎት በስፋት የሚያስረዱት የቤተ ክርስቲያን የታሪክ መጻሕፍት ናቸው። የሐዋርያት ደቀመዛሙርት እነ ፓፒያስ፣ ፖሊካርፐስ፣ አግናጥዮስ፣ ቀሌምንጦስ ዘሮም ወዘተ. የአባቶቻቸውን ታሪክ ጽፈው አቆይተውልናል። ከእነርሱ በኋላም በ2ኛውና በ3ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሱት የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፍት እነ አውሳብዮስ፣ ሩፊኖስ፣ ጄሮም፣ ወዘተ. በትውፊት የተቀበሉትን መዝግበው አልፈዋል። ቅዱሳን ሐዋርያት ገድላቸው የተጻፈላቸው፣ በዓላቸው የተከበረላቸው የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ናቸው። በቤተ ክርስቲያናችን በሐምሌ 5 ቀን በታላቅ ድምቀት በዓላቸው ከሚከበረው ሐዋርያት መካከል የሐዋርያው የቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስን ታሪክ እንደሚከተለው አቅርበነዋል። ፩. ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የተወለደው በገሊላ ባሕር ዳር በምትገኘው በቤተሳይዳ ነው። የአባቱ ስም ዮና ይባላል። ከአምስት ዓመቱ ጀምሮ ያደገው በቅፍርናሆም ከተማ ሲሆን በጐልማሳነቱ ከወንድሙ ከእንድርያስ ጋር በገሊላ ባሕር ዓሳ ማሥገር ጀመረ። ለደቀመዛሙርነት ሲመረጥ ዕድሜው 55 ዓመት እንደነበረ ይነገራ፤ ወደ ጌታችን ያመጣውም ወንድሙ እንድርያስ ነው። ቅዱስ ጴጥሮስ በርናባስና ወንጌላዊው ማርቆስ ቤተ ዘመድ ናቸው። የማርቆስ አባት አርስጦቡሎስና በርናባስ በእናት የሚገናኙ ወንድማማች ናቸው። ቅዱስ ጴጥሮስ ያገባው የበርናባስና የአርስጦቡሎስን እኅት ስለነበር በጋብቻ ይዛመዳሉ። ቅዱስ ጴጥሮስ ለሐዋርያነት ሲጠራ መተዳደሪያው የነበረውን መረቡንና ታንኳውን እንዲሁም አባቱን እርግፍ አድርጐ ትቶ ጌታውን የተከተለ ሐዋርያ ነው። የቅዱስ ጴጥሮስ በመጀመሪያ ስሙን ስምዖን ብላ እናቱ የጠራችው በነገዷ ስም እንደሆነ ይነገራል። በቂሳርያ ከተማ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ «ማን ትሉኛላችሁ?» ብሎ በጠየቀ ጊዜ «አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ» ብሎ ለአይሁድ ሊቃውንት የተሰወረውን ምሥጢረ ተዋሕዶ ገልጦ በመመስከሩ ጌታችን «አንተ ጴጥሮስ ነህ» ብሎታል ይህም በላቲን ቋንቋ ዐለት ማለት ነው፤ በአርማይክ ደግሞ ኬፋ ይባላል። ቅዱስ ጴጥሮስ ከአዕማድ ወይንም የምሥጢር ሐዋርያት ከእነ ዮሐንስ እና ያዕቆብ ጋር የሚቆጠር ነው። ከሐዋርያት ሁሉ ቀደም ቀደም የማለት ባሕርይ ነበረው። ጌታ በጥብርያዶስ ባሕር ላይ ሌሊት በእግሩ ሲመጣ ቢመለከት ወደ አንተ እመጣ ዘንድ እዘዘኝ በማለት ካስፈቀደ በኋላ ወደ ጌታ ለመምጣት መንገድ ጀምሮ በመሐል ቤት ጥርጣሬ ገባውና መስጠም ስለጀመረ ጌታችን «ያመንክ እንጂ ያላመንክ አትሁን» ብሎ ገስፆ ከመስጠም አድኖታል። (ማቴ 14፥22-23) በቅፍርናሆም ጉባኤ ጌታን ምሥጢረ ቁርባንን ሲያስተምር፣ አይሁድ ስላልገባቸው ወደ ኋላ አፈገፈጉ። ከደቀ መዛሙርቱም «ብዙዎቹ ወደ ኋላ ተመለሱ» በዚህን ጊዜ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ «እናንተ ደግሞ ልትሄዱ ትወዳላችሁ?» ብሎ ሐዋርያትን ጠየቃቸው። በዚህ ሰዓት «ጌታ ሆይ ወደ ማን እንሄዳለን? አንተ የዘላለም የሕይወት ቃል አለህ። እኛስ አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆንክ እናምናለን» በማለት ሐዋርያትን ወክሎ የመለሰ እርሱ ነው። (ዮሐ 6፥66-68) ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታን ይወድ ነበር። ፍቅሩ ግን ቅንዓት የተቀላቀለበት በመሆኑ ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ የሞቱን ነገር ቀድሞ ሲነግራቸው አይሁንብህ በማለት ተከራክሯል። (ማቴ 16፥23) በኋላም «ሁሉም በአንተ ቢሰናከሉ እኔ ከቶ አልሰናከልም» ብሎ በራሱ ቅንዓት ተማምኖ ተናግሮ ነበር። ጌታችን «ዶሮ ሳይጮህ ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ» እያለው እንኳን «ከአንተ ጋር መሞት እንኳን የሚያስፈልገኝ ቢሆን ከቶ አልክድህም» በማለት የተናገረ ሰው ነው። (ማቴ 26፥34) ቅዱስ ጴጥሮስ አስቀድሞ የተናገረውን ቃል ለመጠበቅ ሞክሮ ነበር። ጌታ ዛሬ «የሰው ልጅ አሳልፎ ይሰጣል» ብሎ አስተምሮአቸው ነበርና መከላከያ ይሆነኛል ብሎ ሠይፍ ደብቆ ይዞ ነበር። የሮም ጭፎሮችም ጌታን ለመያዝ ሲጠጉ የሊቀ ካህናቱን ባርያ (ማልኰስን) በሠይፍ ጆሮውን ቆረጠው። ጌታችን ግን ሞቱ በፍቃዱ ለድኅነተ ዓለም ነውና «ሠይፍህን ወደ ሰገባው» መልስ ሲል ገሠፀው። ቅዱስ ጴጥሮስ የሚታወቅበት ሌላው ትልቁ ነገር ንስሐው ነው። ጌታው የነገረው መድረሱን፣ ቃል የገባለትን አምላኩን መበደሉን እንዳወቀ ከግቢው ወጥቶ አለቀሰ። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በዕድሜው ታላቅነት በሐዋርያት ዘንድ እንደ አባት ይታይ ስለነበር ጌታ በተለያቸው ጊዜ ሐዋርያቱን ሊመግብ ወደሚያውቀው ሙያ ዓሳ ወደ ማሥገሩ ተሠማራ። ጌታም አስቀድሞ የመረጠው እርሱ ነውና ቢክደው እንኳን በንስሐ በመመለሱ ንስሐውን መቀበሉን፤ ዛሬም እንደሚወደው ይገልጽለትም ዘንድ በጥብርያዶስ ባሕር ተገለጠለት። (ዮሐ 18፥10) ሦስት ጊዜ ክዶት ነበርና ቀኖና ሰጠው። አሁን ቅዱስ ጴጥሮስ በራስ መተማመኑ እንዳላዋጣው ዐውቆአልና «ትወደኛለህን?» ተብሎ ሲጠየቅ «አንተ ታውቃለህ» ነበረ መልሱ። የራሱ ዕውቀት የት እንዳደረሰው ያውቃልና ጌታችንም ኀዳጌ በቀል (በቀልን የሚተው) ነውና ዛሬም እንደሚወደው፣ በንስሐ ተመልሶአልና ዛሬም ለእርሱ የሰጠውን ክብር እንደማያጐድልበት ሲነግረው ግልገሎቼን አሠማራ፣ ጠቦቶቼን ጠብቅ፣ በጐቼን አሠማራ» በማለት አደራውን አስረከበው። ከዚያም በሞቱ እንደምን አድርጐ እግዚአብሔርን አንደሚያከብረው ነግሮት ወደ ሰማያት ዐረገ። (ዮሐ 22፥15) ቅዱስ ጴጥሮስ በአራቱም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ላይ በተቀመጡት የሐዋርያት ዝርዝር ቀዳሚውን ሥፍራ ይዞ ይገኛል። ይህም፦ ፩. በሽምግልና አባትነቱ፣ ፪. ጌታ በቂሳርያ በሰጠው ቃል ኪዳን፣ ፫. የሐዋርያት አፈ ጉባዔ ሆኖ ይናገር ስለነበር፣፬. በጥብርያዶስ ባሕር በተሰጠው ቃል መሠረት ነው። በዚህም የተነሣ በይሁዳ ምትክ ሌላ ሐዋርያ እንዲመረጥ ሐሳብ ያቀረበ እርሱ ነበር። በበዓለ ሃምሳም ለደቀመዛሙርቱ መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ጊዜ ለተሰበሰቡት አይሁድ አፈ ጉባዔ ሆኖ ወንጌልን የሰበከ ፫፼ (ሦስት ሺህ) ምዕመናንንም አሳምኖ የመጀመሪያዋን አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በኢየሩሳሌም የመሠረተ እርሱ ነው። (የሐዋ. ፩፥፲፮-፳፫፣ ፪፥፲፬-፴) አስቀድሞ ፈሪ የነበረውና በሊቀ ካህናት ቀያፋ ግቢ ጌታውን የካደው ቅዱስ ጴጥሮስ፣ የመንፈስ ቅዱስን ኃይል ካገኘ በኋላ ግን በአይሁድ ሸንጐ ድውይ ፈወስክ ተብሎ በተከሰሰ ጊዜ በድፍረት ስለ መድኃኔዓለም ክርስቶስ መሰከረ። ቆርነሌዎስን በማጥመቅ ወንጌልን ለአሕዛብ አስቀድሞ የሰበከው ሐዋርያ ነው። ይህ ሐዋርያ ልዑል እግዚአብሔር ባደለው ጸጋ ጥላው እንኳን ድውያንን ይፈውስ ነበር። የሐዋ 5፥15። በሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ 15 ላይ በ50 ዓ.ም.

photo content

"መስቀል ቤዛችን ነው" ለምን ይባላል ? « አኮ ከመ ይትርአይ አላ ከመ ይትኀለይ» ሰላም ለሁላችሁ ይሁን ።መስቀል ቤዛችን ነው የምንለው በመስቀል ላይ በክርስቶስ ደም የተሰራውን የቤዛነት ሥራ ነው እንጂ ዕፀ መስቀሉን አይደለም።ዕፀ መስቀሉማ በክርስቶስ ኢየሱስ ለተፈጸመልን ቤዛነት የመዳናችን ምልክት ነው።ቤዛችን የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው። ቤዛ ማለት ምትክ፣ነጻ አውጪ ፣ዋጋ ከፍሎ የሚያድን አዳኝ ማለት ነው።በብሉይ ኪዳን መጻሕፍት በብዛት እንደምናነበው ሰዎች ምሕረትና ይቅርታን ለማግኘት ቤዛ የሚሆኗቸውን የበግና የጊደሮችን መስዋዕት በመገናኘው ድንኳን በማቅረብ እጃቸውን በእንስሶቹ ላይ ጭነው ኃጢአታቸውን ይናዘዙ ነበር።የሰዎቹን በደል የተሸከመው በግ ይሰዋና በደሙ መፍሰስ የኃጢአትን ሥርየት ያገኙ ነበር።ዘሌ 4፥1 ሌላም ምሳሌ ብንመለከት አብርሃም ልጁ ይስሐቅን ሊሰዋ ሲል እግዚአብሔር ልጅህን ፍታው ብሎ በይስሐቅ ፈንታ ነጭ በግ ሰጥቶታል ነጩ በግ ለይስሐቅ ቤዛ ሆነው ይስሐቅ ሊቀበል የነበረውን ስቃይና ሞት ወስዶ ነጻ አወጣው።ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለሙን ኃጢአት በደሙ ያስተሰረየ የእግዚአብሔር በግ ነው።እርሱ ክርስቶስ ብቸኛው የሰው ልጆች ሁሉ ቤዛ ነው።“በውድ ልጁም፥ እንደ ጸጋው ባለ ጠግነት መጠን፥ በደሙ የተደረገ ቤዛነታችንን አገኘን እርሱም የበደላችን ስርየት።” ነው ተብሎ ተጽፏል።ኤፌሶን 1፥7 መስቀል ማለት መከራ ማለት ነው።መስቀል ቤዛችን ነው ስንል ደግሞ የክርስቶስ መከራና ሕማም የነፍሴ ቤዛ ነው ማለታችን ነው። ዕፀ መስቀሉ ግን ከባርነት ወደ ነጻነት፣ከሞት ወደ ሕይወት በክርስቶስ ደም ለተሸጋገርንበት ድኅነት የማረጋገጫ አርማችን ነው። ዕፀ መስቀል ከዲያብሎስ ቀስት የምናመልጥበት መንፈሳዊ መሣሪያችን ነው ። ዕፀ መስቀል የክርስቶስ ተከታዮች መለያ ምልክታችን ነው።ስለሆነም በመስቀል ላይ የተሰዋውን የእግዚአብሔር በግ እያሰብን ዕፀ መስቀሉን እናከብረዋለን፣እንስመዋለን፣በመቅደሳችን ጉልላት ላይም ከፍ አድርገን እናስቀምጠዋለን። በቤተርስቲያናችን መስተብቊዕ ዘመስቀል በተባለው ጸሎት ላይ ይህ ቃል ይገኛል። «መስቀለ ክርስቶስሰ ቤዛነ ወኃይልነ። አግዓዘ ጻድቃነ ወኃጥአነ እምግብርናተ ሰይጣን ጻላዒነ።ነሲዖ ሥልጣነ እምኃበ እግዚአብሔር አምላክነ።» «የክርስቶስ መስቀል ቤዛችን ኃይላችን ነው።ከእግዚአብሔር በወሰደው ሥልጣን ጻድቃንና ኃጥአንን ከጠላታችን ዲያብሎስ ባርነት ነጻ አድርጓል።» ትምህርተ ኅቡአት በተባለው ታላቅ ጸሎት ላይ ደግሞ ቤዛ የተባለው መስቀል በአዕምሯችን ዕለት ዕለት የምናስበው የክርስቶስ ሕማምና መከራ እንጂ የሚታየው ግዙፉ ዕፀ መስቀል አለመሆኑን እንዲህ በግልጽ አስቀምጦታል። «ዘእምትካት ኅቡአ ኮነ ይእዜሰ ክሡት ምሥጢር ኮነ ለምዕመናን አኮ ከመ ይትርአይ አላ ከመ ይትኀለይ ውእቱ ዝንቱ መስቀል ወቦቱ ንትመካሕ ከመ ንሰብሖ።» «ለዘመናት ለምዕመናን ስውር የነበረው ምሥጢር ዛሬ የተገለጠ ሆኗል ይህውም የምነመካበትና የምናመሰግነው መስቀል በአዕምሮ የሚታሰብ እንጂ በዓይን የሚታይ አይደለም።» ስለዚህ "መስቀል ኃይላችን ነው"፣ "መስቀል ቤዛችን ነው" ፣"መስቀል የነፍሳችን መዳኛ ነው"እያለ የሚጸልይ ክርስቲያን በክርስቶስ መከራና ሕማም የነፍስ ድኅነት በማግኘቱ የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ሕያው መታረቂያና መጽደቂያው መሆኑን እየመሰከረ ነው።ክርስቲያን በልቡ አምኖ በአፋ መስክሮ ይጸድቃል። በአንገታችን የምናስረውና በሰውነታችን የምንነቀሰው የመስቀል ምልክት ደግሞ በደሙ የዳንን፣ጽድቅን በክርስቶስ ቤዛነት ያገኘን ሕዝቦች በመሆናችን በደሙ ድኛለሁ እያልን የምንመስክርበት ምልክታችን ነው። ጌታ ክርስቶስ በሰው ፊት የሚመሰክርልኝን በሰማያዊ አባቴ ፊት እመሰክርለታለው ስላለ መስቀሉን በግልጽ በአንገታችን አስረን የክርስቶስ መሆናችንን ልናውጅ ይገባል ከቃል በላይ መስቀሉ ብዙ ይናገራል። "በኢየሱስ፡ክርስቶስም፡በኾነው፡ቤዛነት፡በኩል፡እንዲያው፡በጸጋው፡ይጸድቃሉ።" ሮሜ 3፥24 የመስቀሉ በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን። እባካችሁ ለሌሎችም ሼር አድርጉት። መ/ር ታሪኩ አበራ

photo content
+2

photo content

† ደብረ ገሊላ ቅዱስ አማኑኤል † የደብረ ገሊላ ቅዱስ አማኑኤል ካቴድራል የተተከለው በ1905 ዓ.ም በልጅ ኢያሱ ዘመነ መንግሥት ነው። የመጀመሪያውን መቃኞ ያሰሩት ፊት አውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ ሲሆኑ ጽላቱም በጎንደር ክፍለ ሀገር የነበረና ከዚያ መጥቶም በቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የተቀመጠ ነበር። ታድያ ፊት አውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ ያሰሩት የመጀመርያው መቃኞ ለአገልግሎት ምቹ ስላልነበር ሁለተኛ መቃኞ ድጋሚ ተሰርቶ ታቦቱ እንዲገባ ተደርጓል። ንግሥት ዘውዲቱ በግንቦት 28 በ 1914 ዓ.ም የአማኑኤል በዓል ተገኝተው ሲያስቀድሱ ምርጊቱ ተደርምሶ ሲወድቅ በማየታቸው ሦስተኛ መቃኞ እንዲሰራ አዘዙ። የደብሩ አስተዳዳሪ በጊዜው የተክለ ሃይማኖትን ቤተ ክርስትያንንም አንድ ላይ ያስተዳድሩ የነበረ በመሆኑ ንግሥቲቷ የቤተ መንግስታቸውን አጣኝ የመጀመርያው አስተዳዳሪ ሆነው ደብሩን እንዲጠብቁ አደረጉ። አለቃው ሦስተኛውን መቃኞ አሰርተው ታቦቱ ወደ ተዘጋጀለት መቃኞ ገባ። በ1920 ህዝቡ እየበዛ በመምጣቱ አገልግሎቱ እንዲሰፋ ስላስፈለገ በንግሥት ዘውዲቱ አማካኝነት አዲስ ሕንጻ ቤተ መቅደስ ግንባታ ተጀመረ። በ1931 ታህሳስ 28 ቀን ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ ታቦቱ ወደ መንበሩ ገብቷል። ንግሥት ዘውዲቱ ፍጻሜውን ሳያዩ ያረፉ ሲሆን ቤተ መቅደሱ ደግሞ ክብ ቅርጽ ነበረው። አሁን ያለው ቤተ ክርስቲያን በጥር 28 ቀን 1969 ዓ.ም በብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የመሠረት ድንጋይ ተጥሎ ግንባታው የተጀመረ ሲሆን የወቅቱ የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ በነበሩት በሊቀ ሊቃውንት ንቡረ ዕድ አባ ተፈራ መልሴ አስተባባሪነት በምእመናን ርብርብና በቅዱስ አማኑኤል አከናዋኝነት ግንቦት 28 ቀን 1978 ዓ.ም ተጠናቆ ታቦተ ህጉ ወደ ህንጻ ቤተ ክርስቲያን ገብቷል። አማላካችንና አባታችን ቅዱስ አማኑኤል ሆይ ሃገራችንን ሰላም አድርግልን። መ/ር ታሪኩ አበራ

photo content
+3

† ክርስቶስ ሲሰቀል ፀሐይ መጨለሟን ናሳ/NASA/ እውነት መሆኑን በመረጃ ይፋ አደረገ † «ከስድስት፡ሰዓትም፡ጀምሮ፡እስከ፡ዘጠኝ፡ሰዓት፡ድረስ፡በምድር፡ዅሉ፡ላይ፡ጨለማ፡ኾነ።በዘጠኝ፡ሰዓትም፡ኢየሱስ፦ኤሎሄ፥ኤሎሄ፥ላማ፡ሰበቅታኒ፧ብሎ፡በታላቅ፡ድምፅ፡ጮኸ።» ማቴ 27፥45 ዓለም አቀፉ የሕዋና የጠፈር ምርምር ተቋም ናሳ በሺ የሚቆጠሩ ዓመታትን ወደ ኋላ በማስላትና እንዲሁም በ ሺ የሚቆጠሩ ዘመናትን ወደፊት በመቁጠር ምድር በጨለማ የተዋጠችባቸውንና የምትዋጥባቸውን ሰዓትና ደቂቃዎች የሚመራመርበት ቴክኖሎጂ ማግኘቱን ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ክርስቶስ በኢየሩሳሌም በተሰቀለበት ዓመትና ቀን ለሦስት ሰዓታት ምድር ላይ ታላቅ ጨለማ ተከስቶ እንደነበር በተጨባጭ ማስረጃ ማግኘቱን ይፋ አድርጓል። እንግዲህ የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት እውነትና ዓለም የዳነበት የጽድቃችን ታሪክ መሆኑን ሕዝብና አሕዛብ እንዲያውቁት ይህ ሳይንሳዊ ግኝት ይፋ አድርጎታል። መረጃውን ከድኅረ ገጻቸው ማግኘት ይቻላል። NASA Eclipse Web Site eclipse.gsfc.nasa.gov መ/ር ታሪኩ አበራ

photo content

በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ያለን ምዕመናን ከጌታችን ልደት ቀጥሎ በታላቅ ድምቀት የምናከብረው የልደት በዓል የእመቤታችንን የቅድስት ድንግል ማርያም የልደት ቀን ነው፡፡ ስለ ቅዱስ ዮሐንስ ‹‹በመወለዱ ብዙዎች ደስ ይላቸዋል (ሉቃ 1፡14)›› ከተባለ የድንግል ማርያም ልደት ምንኛ የሚያስደስት ይሆን?! የነቢያቱ ትንቢት የተፈፀመበት፣ የታየው ራዕይም በገሀድ የተከናወነበት፣ የብሉይ ኪዳን ማብቂያ የሐዲስ ኪዳን መጀመሪያ ናትና ልደቷ ለሰው ልጆች ሁሉ (ለሕያዋን ሁሉ) ታላቅ የደስታ ቀን ነው፡፡ ሰማያውያን ቅዱሳን መላእክትም በንጽህናዋ በቅድስናዋ ተደንቀው “እህትነ ነያ/እህታችን እነኋት” ብለው ያመሰግኗታል፡፡ በዘመናችን ያሉ የሰዎች ልደት በድምቀት የሚከበር ከሆነ ለሰው ልጅ መዳን ምክንያት የሆነች የአምላክ እናት የተወለደችበት ቀን ምንኛ ሊከበር ይገባው ይሆን?! ቤተ ክርስቲያን የቅድስት ድንግል ማርያምን ልደት በታላቅ ድምቀት የምታከብረው ከዚህ ታላቅ በዓል በረከት ረድኤትን እንድናገኝበት ነው፡፡ የሕይወት ክርስቶስ እናት ዛሬ ተወልዳለችና፡፡ በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትዉፊት መሰረት ሐና እና ኢያቄም ከአይሁድ ለማምለጥ ተሰደዉ በአድባረ ሊባኖስ ስር እመቤታችንን ወለዱ፡፡ በወቅቱ ከቤት የወጡት ለሽሽት ነበርና ስንቅ ስላልያዙ ምግባቸዉ ‹‹ንፍሮና ጥራጥሬ›› ነበር፡፡ይህንን ትዉፊት በመያዝ በዓሉ ከቤት ዉጭ ንፍሮ እየተበላ ይከበራል፡፡ነገር ግን በበጎ ነገሮች ሰበብ ክፉ ዓላማዉን ማስፈጸም የሚፈልገዉ ዲያቢሎስ በማር መካከል መርዝን ከሚጨምርባቸዉ መንፈሳዊ በዓላት አንዱ የግንቦት ልደታ (የእመቤታችን የልደት በዓል) ነዉ፡፡ በዚህ ዕለት አንዳንዶች ባለማወቅ ሌሎች ደግሞ በድፍረት ‹‹ለአድባር አዉጋር ነዉ፤ ቆሌዉን ለመለመን ነዉ›› እያሉ ለማያውቁት አምልኮ ንፍሮ የሚበትኑ፣ ቡና የሚረጩ፣ ቅቤ የሚቀቡ፣ የከብት ደም የሚያፈሱ አሉ፡፡ እውነታው እነዚህ በእርግጥም ጣዖት አምላኪዎች ናቸው፡፡ እኛ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ግን እነዚህን የሃይማኖት ለዋጮች ሥራቸውን እንጸየፋለን፡፡ ስለሆነም ከእንደዚህ ዓይነቱ ባዕድ አምልኮ በመለየት ይህንን ታላቅ በዓል በተገባና በተረዳ ነገር ልናከብረው ይገባል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በሠራችልን ሥርዓት መሰረት በቀናች በተዋሕዶ እምነት ሆነን፤ በምሕረቱ የጎበኘንን አምላካችንን ብቻ እያመለክን፤ የድኅነታችን ምክንያት የሆነችውን ድንግል ማርያምንም እያመሰገንን ልናከብረው ይገባል፡፡ አምላካችን እግዚአብሔር ከእመቤታችን ረድኤት በረከት ይክፈለን፡፡ አሜን፡፡ ለሌሎችም ሼር አድርጉት

ኢያቄምና ሐና መካን ስለነበሩ እግዚአብሔር ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ጸልየው፤ ሲሰጣቸውም መልሰው ለእርሱ እንደሚሰጡ ስዕለትን ተስለው ነበር፡፡ ጸሎታቸው ሲደርስ ለሐና በሕልም ተገልጾላት ለባለቤቷ ለኢያቄም ‹‹ብእሴሃ አነኑ ርኢኩ በሕልምየ ርግብ ጸዐዳ መጽአት ኀቤየ ወነበረት ዲበ ርእስየ ወቦአት ውስተ እዝንየ ወኀደረት ውስተ ከርሥየ /ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብቶ በማሕፀኔ ስትተኛ አየሁ፡፡›› ብላዋለች፡፡ የዚህ ራእይ ምስጢርም ርግብ የተባለች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስትሆን፤ ፀዓዳ (ነጭ) መሆኗ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ዘላለማዊ ድንግልናዋ ነው፡፡ ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማሕፀኔ ስትተኛ አየሁ›› ማለቷ ብሥራተ ገብርኤልን በጆሮዋ ሰምታ በግብረ መንፈስ ቅዱስ አምላክን የምትፀንሰውን ንጽሕት ርግብ የተባለችውን እመቤታችንን የምትወልድ መሆኗን ሲያጠይቅ ነው:: ከሰባተኛው ሰማይ ነጭ ዖፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ (ቅዱስ ኢያቄም) በተመሳሳይ ኢያቄምም በሕልሙ ያየውን ለባለቤቱ ለሐና ‹‹እንዘ ይትረኀዉ ሰብዐቱ ሰማያት ዖፍ ጸዐዳ መጽአ ኀቤየ ወነበረ ዲበ ርእስየ /ሰባቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ዖፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ›› ብሎ በሕልሙ የተገለጸለትን ነግሯታል፡፡ የዚህም ራዕይ ምስጢር ዖፍ የተባለው አካላዊ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን፤ ነጭነቱ ንጽሐ ባሕርዩ ነው፡፡ ኢያቄም ‹‹ከላይ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ›› ማለቱ የኢያቄምን ባሕርይ ባሕርይ እንደሚያደርግ የሚያጠይቅ ሲሆን ሰባቱ ሰማያት የተባሉ የጌታችን ልዩ ባህርይው፣ ምልአቱ፣ ስፍሃቱ፣ ርቀቱ፣ ልእልናው፣ ዕበዩና መንግስቱ ናቸው:፡ የድንግል ማርያም ልደት በሐዲስ ኪዳን ሊቃውንት የሐዲስ ኪዳን ሊቃውንትም ትንቢተ ነቢያትንና ወንጌልን በማጣጣም የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ልደት አመስጥረው አስተምረዋል፤ አመስግነዋል፤ ተቃኝተዋልም፡፡ የእርሷን ልደት እጅግ ብዙ ሊቃውንት በስፋትና በጥልቀት ያመሰጠሩት ሲሆን ለምሳሌ ያህል የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡፡ ማርያምስ ከጥንት ጀምሮ በአዳም ባሕርይ ውስጥ እንደ ነጭ ዕንቁ ታበራለች (ቅዱስ ያሬድ) ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ስለእመቤታችን ልደት ‹‹ማርያምሰ ተኀቱ እምትካት ውስተ ከርሱ ለአዳም ከመ ባሕርይ ጸዓዳ/ ማርያምስ (ማርያም ግን) ከጥንት ጀምሮ በአዳም ባሕርይ ውስጥ እንደ ነጭ ዕንቁ ታበራለች፡፡›› በማለት እርሷ በደፈረሰው ዓለም በንጽሕና፣ በቅድስናና በድንግልና ስታበራ እንደነበርና ኋላም የዓለም ብርሃን የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን መውለዷን አመስጥሮ ተናግሯል፡፡ በተጨማሪም ስለ ሥርወ ልደቷ ‹‹እንተ በምድር ሥረዊሃ ወበሰማይ አዕጹቂሃ…ሐረገ ወይን/ ሥሮቿ በምድር ጫፎቿም በሰማይ ያሉ…የወይን ሐረግ›› በማለት የተወለደችው በምድር ከነበሩት ኢያቄምና ሐና መሆኑን የወለደችው ግን ሰማያዊውን ንጉሥ እንደሆነ በማመስጠር ዘምሯል፡፡ በዚህም ሰውና እግዚአብሔርን ያገናኘች መሰላል መሆኗል ገልጾ አስተምሯል፡፡ ድንግል ሆይ በኃጢአት ፍትወት የተፀነስሽ አይደለም፤ በሕግ በሆነ ሩካቤ ከሐናና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ (አባ ሕርያቆስ) የብህንሳው ሊቀ ጳጳስ አባ ሕርያቆስም በቅዳሴ ማርያም ‹‹ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ/ ድንግል ሆይ በኃጢአት ፍትወት የተፀነስሽ አይደለም፤ በሕግ በሆነ ሩካቤ ከሐናና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ›› በማለት የድንግል ማርያም ጽንሰትና ልደት እንዴት እንደነበር በድርሰቱ አስፍሮታል፡፡ ትውልድ ሁሉ ብፅዕት የሚላት የሁላችን እናት ድንግል ማርያም በሕግ በሆነ ሩካቤ ከሐናና ከኢያቄም ነሐሴ 7 ቀን ተፀንሳ ከዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በኋላ ግንቦት 1 ቀን ተወልዳለች፡፡ እርስዋም ስትፀነስ ጀምሮ መንፈስ ቅዱስ ከጥንተ አብሶ (original Sin) ጠብቋታል፤ አበሳው አልነካትም፡፡ ይህንንም ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ በኃጢአት በተከበበ፣ መርገም በሞላበት ዓለም ውስጥ ከኃጢአት ከበደል ርቃ (ተለይታ) እንደ ጌዲዮን ጸምር በንጽህና የጠገኘች ንጽህት ዘር መሆኗን ሲያስረዳ ‹‹የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ዘርን ባያስቀርልን ኖሮ እንደ ሰዶም በሆንን እንደ ገሞራም በመሰልን ነበር (ኢሳ 1፡19)፡፡›› በማለት ተናግሯል፡፡ እንዲሁም ጠቢቡ ሰሎሞን ንጽህናዋን በትንቢት መነጽር አይቶ “ወዳጄ ሆይ፣ ሁለንተናሽ ውብ ነው፣ ምንም ነውር የለብሽም፡፡ ሙሽሪት ሆይ ከሊባኖስ ነዪ፡፡” (መሓልይ 4፡7-16) በማለት በንጽህና በቅድስና ያጌጠች፣ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ ያልነካት፣ የድህነታችን ምክንያት፣ የንጽህናችን መሰረት የሰው ባህርይ ከእግዚአብሔር ጋር እንዲዋሀድ ምክንያት የሆነች ንጽሕት የሰርግ ቤት ድንግል ማርያም በሊባኖስ የመወለዷን ነገር አስቀድሞ ነግሮናል፡፡ ይህች ዕለት ትልቅ ሕንፃ የታነጸበትና ፍጡር የፈጣሪ ማደሪያ ለመሆን የተዘጋጀባት ዕለት ናት (ቅዱስ እንድርያስ) የቀርጤሱ ቅዱስ እንድርያስ የከበረ ስለሆነው ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልደት ታላቅነት ‹‹ይህ በዓል በሐዲስና በብሉይ ኪዳን መካከል መገኛ ሆነ፡፡ ምሳሌዎቹ በእዉነታ፣ አሮጌው በአዲስ ቃል ኪዳን ተተኩ፡፡ ፍጥረት ሁሉ በደስታ ይዘምራል፤ የዚህን ቀንም ደስታ ይካፈላል፡፡ ይህ ዕለት (ጌታ) መቅደሱን የሰራበት ዕለት ነው፡፡ ይህ ዕለት ትልቅ ሕንፃ የታነጸበትና ፍጡር የፈጣሪ ማደሪያ ለመሆን የተዘጋጀበት ዕለት ነው፡፡” በማለት ገልጾታል፡፡ በእውነት የእርሷ ልደት የልዑል ማደሪያው መቅደስ የተሰራበት ዕለት ነውና ሁላችን እናከብረዋለን፡፡ በዚህም ዕለት ‹‹ዮም ፍስሐ ኮነ በእንተ ልደታ ለማርያም/ እነሆ ዛሬ በእመቤታችን ልደት ደስታ ሆነ›› እያልን እንዘምራለን። ይህችን የልዑል ማደሪያ እናቷ ሐናና አባቷ ኢያቄምም በእጅጉ ተደስተው በተወለደች በስምንተኛ ቀኗ ስሟን ‹‹ማርያም›› ብለው ሰይመዋታል፡፡ የእመቤታችን የልደት በዓል አከባበር አባታችን አዳም በኃጢአት ከወደቀ በኋላ፣ ንስሃ በገባ ጊዜ አምላካችን ጌታ እግዚአብሔር የድህነት ቃል ኪዳን ገባለት፡፡ ቃል ኪዳኑም “ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ” የሚል ነበር፡፡ ስለሆነም አዳም 5500 ዘመን የሕይወት ምክንያት የሆነች የልጅ ልጁ እመቤታችን ድንግል ማርያም ከአብራኩ ከተከፈሉ ቅዱሳን ልጆቹ የምትወለድበትን ቀን ተስፋ እያደረገ ኖረ፡፡ የእመቤታችንን የድንግል ማርያምን የመወለዷን ዜና ተስፋ በማድረግ “ሴት” ይላት የነበረውን ሚስቱን ሔዋንን በእመቤታችን ምሳሌነት “ሔዋን”፣ የሕያዋን ሁሉ እናት ብሎ ሰየማት፡፡ (ዘፍ. 3፡20) ዳግማዊ አዳም የተባለ ክርስቶስም የአዳምን ተስፋ በመስቀል ላይ በፈጸመ ጊዜ እውነተኛዋን ሔዋን (ዳግሚት፣ አማናዊት ሔዋንን) ድንግል ማርያምን በዮሐንስ ወንጌላዊ በኩል ለሕያዋን ምዕመናን ሁሉ እናት አድርጎ ሰጠ፡፡ (ዮሐ. 19፡26) ይህን የከበረ ምስጢር የማይረዳ “ክርስቲያን” እንዴት ያሳዝናል!? እኛ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ግን የቀዳማዊ አባታችንን የአዳምን፣ እንዲሁም በዳግም ተፈጥሮ ያከበረንን ዳግማዊ አዳም የተባለ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ቃል ተቀብለን “የሕያዋን ሁሉ እናት” ድንግል ማርያምን ልደቷን በፍፁም ደስታ እናከብራለን፣ ከተወደደ ልጇ ምሕረትን ትለምንልን ዘንድም ወደ እርሷ እናንጋጥጣለን፡፡

† ልደታ ለማርያም † ★ የእመቤታችንን ክብርና መመረጥ ለሌሎችም ሼር በማድረግ መስክሩ ★ በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ግንቦት አንድ ቀን (የግንቦት ልደታ) የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ልደት የሚከበርበት ዕለት ነው፡፡ ይህ ዕለት ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ማርያም ‹‹የመመኪያችን ዘውድ፣ የንጽሕናችንም መሰረት›› ያላት ወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያም የተወለደችበት ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ ‹‹ድንግል ትጸንሳለች፤ ወንድ ልጅም ትወልዳለች (ኢሳ 7፡14)›› ብሎ ትንቢት የተናገረላት ያቺ ድንግል በዚህች ዕለት ተወለደች፡፡ ይህች ቀን ልበ አምላክ ክቡር ዳዊት ‹‹ የወርቅ ልብስ ተጎናጽፋ ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች (መዝ 44፡9)›› ብሎ የተናገረላት ንግሥት የተገኘችባት ዕለት ናት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም በራዕዩ ‹‹ፀሐይን የተጎናጸፈች፣ ጨረቃን የተጫማች፣ አስራ ሁለት የክዋክብት አክሊል በራሷ ላይ ያላት (ራዕ 12፡1)›› ብሎ የመሰከረላት የብርሃን እናቱ ድንግል ማርያም የተወለደችባት ቀን ናት፡፡ የእርስዋም ልደት እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ ድንገት የተከሰተ ሳይሆን አስቀድሞ በትንቢት፣ በምሳሌና በራዕይ የሰውን ልጅ ድኅነት በጉጉት ሲጠባበቁ ለነበሩ ቅዱሳን ሲገለጽ የነበረ ነው፡፡ የድንግል ማርያም ልደት በነቢያት አንደበት መሠረታቲሃ ውስተ አድባር ቅዱሳን፡ መሠረቶችዋ በተቀደሱ ተራሮች ናቸው፡፡ መዝ 86፡1-7 እግዚአብሔር የዝማሬና የትንቢት ጸጋን ያበዛለት ክቡር ዳዊት ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥርወ ልደት አስቀድሞ በመንፈስ ቅዱስ መነጽርነት ተገልጾለት ‹‹መሠረታቲሃ ውስተ አድባር ቅዱሳን /መሠረቶችዋ በተቀደሱ ተራሮች ናቸው/›› በማለት ትንቢት ተናግሯል፡፡ ‹‹የተቀደሱ ተራሮች›› ያለውም የእመቤታችን ሥርወ ልደት ከቤተ መንግሥትና ከቤተ ክህነት ከሆኑት ከተቀደሱት ከኢያቄምና ከሐና የመሆኑን ነገር ሲያመለክት ነው፡፡ ይህንን ትንቢትና እውነተኛውን የእመቤታችንን የትውልድ ሀረግ አስማምታ ቤተክርስቲያን ‹‹የእመቤታችን ማርያም ትውልዷ ባባቷ በኩል ከንጉሡ ከዳዊት ወገን ነው፤ በናቷም በኩል ከካህኑ ከአሮን ወገን ነው፤ የአባቷ ስም ኢያቄም ነው፤ የእናቷም ስም ሐና ነው፡፡›› ብላ ታስተምራለች፡፡ ትወፅእ በትር እምሥርወ ዕሴይ ወየዐርግ ጽጌ እምኔሃ፡ ከዕሴይ ሥር በትር ትወጣለች፤ አበባም ከእርሷ ይወጣል፡፡ ኢሳ 11፡1 ቁጥሩ ከዐበይት ነቢያት ወገን የሆነው ነቢዩ ኢሳይያስም ጥበብንና እውቀትን በሚገልጽ ስለሚመጣውም ነገር ትንቢትን በሚያናግር በመንፈስ ቅዱስ ተመርቶ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ልደት ከነገደ ዕሴይ እንደሚሆንና እርሷም ጽጌ (አበባ) የተባለ አካላዊ ቃል ክርስቶስን በሕቱም ድንግልና እንደምትወልድ ተገልጾለት ‹‹ትወፅእ በትር እምሥርወ ዕሴይ ወየዐርግ ጽጌ እምኔሃ /ከዕሴይ ሥር በትር ትወጣለች፤ አበባም ከእርሷ ይወጣል/›› በማለት ታላቅ ትንቢትን ተናግሮ ነበር፡፡ ይህች በትርም ከእሴይ ዘር የተገኘችው በዚህች ዕለት ነውና ልደቷን በታላቅ ድምቀት እናከብራለን፡፡ ይህንን መሰረት በማድረግ ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም ‹‹መልካሟ ርግብ ማርያም ሆይ ደስ ይበልሽ፤ ከእሴይ ሥር የተገኘሽ መዓዛሽ ያማረ አበባ አንቺ ነሽ›› በማለት በውዳሴ አመስግኗታል፡፡ ‹‹በአባቶችሽ ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ (መዝ 131፡13)›› የተባለልን የአባቶቻችን ልጆች እኛም እንዲሁ እያልን እናመሰግናታለን፡፡ ንዒ እምሊባኖስ መርዓት ንዒ እምሊባኖስ፡ ሙሽራዬ ሆይ ከሊባኖስ ከእኔ ጋር ነይ፡፡ መኃ 4፡8 በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት መሰረት የእመቤታችን የትውልድ ስፍራ ሊባኖስ የተባለው ተራራማ ሀገር ነው፡፡ በሊባኖስ ስለመሆኑ አስቀድሞ ጠቢቡ ሰሎሞን ‹‹ንዒ እምሊባኖስ መርዓት ንዒ እምሊባኖስ ንዒ ወተወፅኢ እምቅድመ ሃይማኖት እምርእሰ ሳኔር ወኤርሞን አምግበበ አናብስት ወእምአድባረ አናምርት /ሙሽራዬ ሆይ ከሊባኖስ ከእኔ ጋር ነዪ ከሊባኖስ ከእኔ ጋር ነዪ ከአማና ራስ ከሳኔር ከኤርሞን ራስ ከአንበሶች መኖሪያ ከነብሮችም ተራራ ተመልከች/›› በማለት ተናግሮ ነበር፡፡ የዚህ ትንቢት ምስጢርም የእመቤታችን መካነ ልደት የሊባኖስ ተራራ ስለመሆኑ የሚያጠይቅ እንደሆነ ምስክርነታቸው የታመነ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ያስረዳሉ፡፡ ትንቢቱም ሲፈጸም ቅድስት ድንግል ማርያም ግንቦት 1 ቀን በ15 ዓ.ዓ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በሊባኖስ ተራራ ተወልዳለች፡፡ ኢትዮጵያዊ ቄርሎስ የተባለው የነገረ ማርያም ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ እመቤታችን በሊባኖስ እንደምትወለድ አስቀድሞ ሰሎሞን የተናገረው ቃልም መፈጸሙን ሲገልጽ ‹‹….የአናብስት ልጅ አልኩሽ፡፡ ሰሎሞን እንዲህ ሲል እንደተናገረ፡- ሙሽራዪት ሆይ ከሊባኖስ ተራራ ነዪ፤ ከአንበሶች ጒድጓድ ወጥተሽ ነዪ፤ ከምርጥ ነገድነት የተነሣ ከሚመካ ወገን የመወለድሽ ዜና እጅግ ግሩም ነው፡፡›› በማለት አመስጥሮታል፡፡ እመቤታችንም በሊባኖስ ተራራ እንድትወለድ ምክንያት የሆነው በማሕፀን ሳለች የአርሳባንን ልጅ ዓይን በማብራቷና ሳሚናስ የሚባለውን የጦሊቅን ልጅ ከሞት በማስነሳቷ አይሁድ በቅናት ተነሳስተውባቸው ስለነበር ሐናና ኢያቄም ወደ ሊባኖስ ተራራ እንዲሄዱ ታላቁ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ለኢያቄም ተገልጾ ስለነገራቸው እንደሆነ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ የድንግል ማርያም ልደት በራዕይና በምሳሌ ከትንቢቱ በተጨማሪም የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ልደት በራዕይና በምሳሌም አስቀድሞ የተገለጸ ነበር፡፡ ከእነዚህም መካከል ከእርሷ ሰባት ትውልድ አስቀድሞ ለነበሩት ደጋግ ሰዎች እንዲሁም ለእናትና ለአባቷ የተገለጹት ምሳሌዎች በቅዱሳት መጻሕፍት በሰፊው ሰፍረው ይገኛሉ፡፡ ሰባተኛዪቱ እንቦሳ ጨረቃን ስትወልድ ጨረቃዋ ደግሞ ፀሓይን ስትወልድ አየሁ (ቴክታ) በቅድስና የሚኖሩ ነገር ግን መካን የነበሩት ቴክታና ጴጥርቃ ነጭ እንቦሳ ከበረታቸው ስትወጣ ፤ እንቦሳይቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ስድስት ስትደርስ ፤ ስድስተኛዪቱ ጨረቃን ጨረቃዋም ፀሐይን ስትወልድ አይተው በሀገራቸው መፈክረ ሕልም (ሕልም ፈች ሊቅ) አለና ሂደው ነገሩት፡፡ ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ፤ ጨረቃይቱ ከፍጡራን በላይ የምትሆን ልጅ ትወልዳላችሁ፡፡ የፀሐይ ነገር ግን አልተገለጸልኝም፤ እንደ ነቢይ እንደ ንጉሥ ያለ ይሆናል አላቸው፡፡ እነርሱም ጊዜ ይተርጉመው ብለውት ሄዱ፡፡ ከዚህ በኋላ ልጅ ወለዱ፡፡ ስሟንም ‹‹ረከብኩ ስእለትዬ፤ ረከብኩ ተምኔትዬ›› /የተሳልኩትን አገኘሁ፤ የተመኘሁትን አገኘሁ/ ሲሉ ‹‹ሄኤሜን››አሏት፡፡ ሄኤሜን ዴርዴን፤ ዴርዴ ቶናን፤ ቶና ሲካርን፤ ሲካር ሄርሜላን፤ ሄርሜላ ሐናን ወለደች፡፡ ሐና ለአካለ መጠን ስትደርስ ከቤተ ይሁዳ ለተወለደ ኢያቄም ለሚባል ደግ ሰው አጋቧት፡፡ ከኢያቄምና ከሐናም በጨረቃ የተመሰለች ድንግል ማርያም ተወለደች፡፡ ፀዓዳ ርግብ ሰባቱ ሰማያትን ሰንጥቃ መጥታ በማሕፀኔ ስታድር አየሁ (ቅድስት ሐና)

photo content

መድኃኔዓለም ክርስቶስ እኛን የወደደበት ሕይወቱን እስከመስጠት ደርሶ ቤዛ የሆነበትን ምሥጢር የሰው ሕሊና መርምሮ ሊደርስበት የሚችል አይደለም፡፡ ተነጻጻሪ ተወዳዳሪ አቻ ምስያ የሌለው ልዩ ነው፡፡ ከቀደምት አበው እነ አብርሃም ልጆቻቸውን በቁርጥ ሕሊና ለመሥዋዕት አቅርበዋል፡፡ እነ ሙሴ እነ ዳዊት ይመሩት ይጠብቁት ለነበረው ሕዝብ ተላልፈን እንሙት እንቀጣ የሕዝቡን ቅጣት እንቀበል ብለው እንደነበረ ተጽፎአል፡፡ ግን በቅርብ ለነበረ፣እንዲያስተዳድሩ ለተሾሙለት ለተወሰነ ሕዝብና ለወገናቸው ብቻ ነበር፡፡ ሁሉን የሚያጠቃልል ሁሉን የሚያድን አልነበረም፡፡ መድኃኒታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስግን በመስቀል ላይ መከራ ተቀብሎ የሞተው፥ ለመላው የሰው ዘር ለአዳም ልጆች ሁሉ ነው፡፡ ቤተሰብና ዘመድ ወዳጅ፣ ጠላት ፣ባዳ ወንዝና አካባቢ የሚለው አልነበረም፡፡ ከሰው አስተሳሰብ ሚዛንና ግምት የራቀ የጠለቀ ነው፡፡ የወደደን መከራ የተቀበለው እኛ ስለወደድነው አልነበረም፡፡ እሱ ስለ ወደደን ብቻ ነው፡፡ እንኳንስ ቀድሞ ዛሬም ያደረገልንንና ያደለንን አስበን፥ ፍቅሩን ተገንዝበን፥ ለሰው በጎ ማድረግ፤ በፍቅሩ መመላለስ እጅግ ያዳግተናል፡፡ ከሁሉም የሚረቀውና የሚደንቀው ያጠፋን የበደልን፣ በጥፋታችን ሞትን በራሳችን ላይ ያመጣን እኛ ስንሆን፥ እሱ ስለኛ በደል ተላልፎ በእኛ የተፈረደውን የሞት ፍርድ ተቀብሎ መሞቱ ይደነቃል፡፡ ለዚህም አንክሮ ይገባል፡፡ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ርእዩ መጠነ ዘአፍቀረነ እግዚአብሔር … ወሶበ እንዘ ፀሩ ንሕነ ተሣሃለነ በሞተ ወልዱ።" "እግዚአ ብሔር ምን ያህል እንደወደደን አስተውሉ ጠላቶቹ ስንሆን በልጁ ሞት ይቅር አለን” ብሎ እንዳስተማረው ስንኳን ተላልፎ እስከመሞት የሚያደርስ ፍቅርና ከፍርድ የሚያድን ምንም መልካም ሥራ ሳይኖረን፤ በሱ ፍቅር የተደረገልንን ቸርነት የምናስብበት የነፃነት የምስጋና ዕለት ነው፡፡ ሮሜ 5 ፥6 በልጁ ሞት ስለካሰልን ይቅርታን አገኝን፤ በአንድ አዳም በደል ምክንያት ኃጢኣት ወደ ዓለም እንደ መጣች፤ በዚችም ኃጢኣት ምክንያት፥ በሰው ሁሉ ሞት እንደተፈረደበት፤ ሰውን ሁሉ በደለኛ፣ ኃጢአተኛ፣ አሰኝቸው፡፡ በአዳም ኃጢአት ምክንያት የመጣ ሞት ከአዳም እስከ ክርስቶስ የነበሩትን የበደሉትንና ያልበደሉትን ሁሉ ገዛቸው፡፡ ታላቁ ሙሴ እንኳን ሌላውን ሲያድን ራሱን ከነፍስ ሞት ማዳን አልቻለም።የኦሪት ነቢያትና ካህናት ራሳቸውንም ከሞት ማዳን ስላልተቻላቸው ለሞት ተገዝተዋል፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔር የጸጋው ስጦታ በኃጢአታችን ልክ የተደረገብን አይደለም፡፡ ራሱን ቤዛ አድርጎ ካሰልን፤ ከዳግማዊ አዳም ኢየሱስ ክርስቶስ በተሰጠን ጸጋ በጥምቀት፣ በሃብት፣ በልጅነት ለሰው ሁሉ ሕይወት በዛለት፡፡ ሮሜ5፥16 በመለኮታዊ ስልጣኑ የተነሣውን ክርስቶስን ሐዋርያት አይተውታል ገጽ በገጽ ዓይን በዓይን ፊት ለፊት ተያይተዋል፡፡ ሰግደውለታል፤ አመስግነውታል፤ ደስታቸው ፍጹም ሆኖላቸዋል፡፡ “… እናንተ አሁን ታዝናላችሁ ነገር ግን እንደ ገና አያችኋለሁ ልባችሁም ደስ ይለዋል ደስታችሁንም የሚወስድባችሁ የለም” ያለው የተፈጽሞላቸዋል፡፡ ዮሐ 16፥12 ለትምህርታቸው መሠረት ለስብከታቸው መነሻ የሆነው የጌታ ትንሣኤ ነው ምስክርነታቸውም የጸናው በትንሣኤ ነው፡፡ የተልእኳቸው ዋነኛ ዓላማ ሞቱንና ትንሣኤውን በመመስከር ላይ ያተኮረ ነው፡፡ ሐዋ 1፥8፣ ሐዋ 2 ፥32፣ ሐዋ 4፥ 20 ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ከተነሣ በኋላ በተለያዩ ቦታዎችና ጊዜያት እየተገለጠ ታይቶአል፡፡ እስከ ዓረገበት አርባኛው ቀን ድረስ ከሐዋርያት ብዙ አልተለየም፡ ከዚህም ሁሉ ጋር በሐዋርያት ትምህርትና ሥርዓተ ጸሎት አካባቢ የነበሩ ሳይቀሩ ብዙዎች አይተውታል፡፡ ከሁሉም በቀዳሚነት ማርያም መግደላዊት ዮሐ፳፥፲፬‐፲፰ በመቃብሩ አካባቢ ነበሩ እነማርያም ባውፍልያ ማቴ ፳፰፥፱ ወደ ኤማሁስ ይጓዙ የነበሩ ሁለት ደቀመዛሙርት ሉቃ ፳፬፥፲፫‐፴፩ ስምኦን ጴጥሮስ ሉቃ ፳፬፥፴፬፣፩ቆሮ ፲፭፥፭ አሥሩ ደቀመዛሙርት ዮሐ ፳፥፲፱ አሥራ አንዱ ሐዋርት ዮሐ፳፥፳፮ከዳግም ትንሣኤ/ከሁለተኛው ሰንበት/ ደቀመዛሙርቱ ዮሐ፳፩፥፩‐፳፪ በገሊላ አሥራ አንዱ ሐዋርት ማቴ ፳፰፥፲፮ ማትያስ ባለበት አሥራ አንዱ ፩ቆሮ ፲፭፥፭ ሐዋ ፩፳፥፮ ከአምስት ጀምሮ (፭፻) የሚበዙ ወንድሞች ፩ቆሮ ፲፭፥፯ሐዋርያው ያዕቆብ ፩ቆሮ ፲፭፥፯-፲፪ ሁሉም ሐዋርያት በየጊዜውና በየቦታው አይተውታል፡፡ማር ፲፮፥፲፱፣ ሉቃ ፳፬፥፶፣ ሐዋ ፩፥፫‐፲፪፣ ቁ ፳፮ በመጨረሻም ለቅዱስ ጳውሎስ ተገልጦለታል፡፡ ፩ ቆሮ ፲፭፥፰ ክብርና ምሥጋና ለትንሣኤው ጌታ ይሁን። ለሌሎችም ሼር አድርጉት

† ትንሣኤ ክርስቶስ † ትምህርቱን ለሌሎችም ሼር አድርጉት ትንሣኤ ማለት ተንሥአ ካለው የግዕዝ ግሥ የተወረሰ ሲሆን ትርጉሙም መነሣት አነሣሥ ማለት ነው ።እስራኤል ዘሥጋ ያከብሩት የነበረው በዓለ ፋሲካ ከባርነት ቀንበር ወደ ነጻነት የተላለፉበት ከኃዘን ወደ ደስታ የተሸጋገሩበት በዓል ነበር ። የአዲስ ኪዳን ፋሲካ ወይም በዓለ ትንሣኤ ግን እሥራኤል ዘነፍስ የሆን ክርስቲያኖች ከኃጢአት ወደ ጽድቅ የተመለስንበት ከውርደት ወደ ክብር፣ ከአሮጌው ወደ ሐዲስ ሕይወት፣ከባርነት ወደ ልጅነት ክብር የተሸጋገርንበት መንፈሳዊ የነጻነትበዓል ነው ።ፋሲካ በዐረብኛ ፓስኻ ማለት ሲሆን ትርጉሙም ማዕዶት መሸጋገሪያ ማለትነው ። ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ በቀደምት ነቢያት የተነገሩና የተጻፉ አንቀጾች ብዙ ናቸው፡፡ የሞቱና የትንሣኤው ምሥጢርም በቅዱሳን መጻሕፍት ሰፊ ቦታ ያለው ነው፡፡ እሱ ራሱ መድኃኒታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥርዓተ ቊርባንን በሠራበት ምሽት የሞቱንና ትንሣኤውን ነገር አንሥቶ ለደቀ መዛሙርቱ በሰፊው ገልጿል፡፡ “በዚች ሌሊት ሁላችሁ ትክዱኛለችሁ መጽሐፍ እረኛው ይመታል የመንጋው በጎች ይበተናሉ ያለው ይፈጸማል” ብሎ ነግሯቸዋል፡፡ ከዚህም ቀደም ብሎ በጉባኤው ይሰበሰብ ለነበረው ሕዝብ ዮናስ በከርሠ አንበሪ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት እንደኖረ የሰው ልጅ ክርስቶስም ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በከርሠ መቃብር ያድራል፡፡ ነገር ግን ወደገሊላ እቀድማችኋለሁ እያለ ይነግራቸው፥ ያስተምራቸው ነበር፡፡ ማቴ 12፥40፣ 27፥31 መድኃኔዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ የመስቀልን ፀዋትወ መከራ ተቀብሎ በመስቀል ላይ ሞቶ፥ ሞትን ይሽረው ዘንድ ሙታንንም በሞቱ ሕያዋን ያደርጋቸው ዘንድ ሞተ፡፡ በዕለተ ዓርብ የፈጠረውን አዳም በፈጸመው በደል ከተፈረደበት የሞት ፍርድ ነፃ ይሆን ዘንድ፥ በባሕርዩ ሞት የሌለበት አምላክ በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ ዋለ፡፡ ወዳጆቹ የአርማትያሱ ዮሴፍና፥ አስቀድሞ በሌሊት ወደ ጌታ የሄደው ኒቆዲሞስ በመስቀል ላይ የዋለውን ሥጋውን አውርደው፥ ለመቅበር፤ ከገዥው ከጲላጦስ ለምነው እንዲቀብሩ ተፈቅደላቸው፡፡ በምሽትም ከመስቀሉ አወረዱት እንደቤተ አይሁድ የአቀባበር ሥርዓትና ልማድ የደቀቀና መዓዛው የጣፈጠ ሽቱ አዘጋጅተው፥ ከጥሩ ሐር በተሠራ በፍታ ገንዘው ዮሴፍ ለራሱ አስወቅሮ ባሳነፀው አዲስ መቃብር ቀበሩት፡፡ታላቅ ድንጋይም ገጠሙት ማቴ 27፥57፣ ዮሐ 19 ፥ 38 ይህ ሁሉ ለአይሁድ ሊቃናትና ሕዝብ ደስ የሚያሰኝ አልነበረም፡፡ ስለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚደረገው ጥንቃቄና የሚሰጠው ክብር ሁሉ፥ በነሱ ዘንድ ተቀባይነት አልነበረውም፡፡ “ያ በሕይወተ ሥጋ ሳለ በሦስተኛው ቀን እነሣለሁ ብሏልና ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት ሰርቀው፥ ወስደው ከሙታን ተለይቶ ተነሣ ብለው ሕዝቡን እንዳያስቱ መቃብሩ ይጠበቅ” በማለት ወስነው ነበር፡፡ በእያንዳንዱ አራት አባል የሚገኝበት በሦስት ፈረቃ የሚጠብቅ የጭፍራ ቡድን ተመድቦ መቃብሩን በንቃትና በጥንቃቄ እንዲጠብቅ ተደርጓል፡፡ ባለሥልጣኖችም ጭፍራው ባለበት መቃብሩን አስቆልፈው በየቀለበታቸው (ማኅተማቸው) አትመውት ነበር፡፡ ማቴ 27፥62 ይህ ሁሉ በሚፈጸምበት ዕለትና ጊዜ እነማርያም መግደላዊት፣ ማርያም ባው።ፍልያና እና ሰሎሜ ከእግረ መስቀሉ ሳይለዩ ከመቃብሩ ፊት ለፊት ቆመው በኃዘን፣ በተሰበረ መንፈስ የነገሩን ፍጻሜ የሚመለከቱ የዓይን ምስክሮች ነበሩ፡፡ ይሁን እንጂ ሰውን ለመዳን በፈቃዱ ባደረገው የቸርነት ሥራ፥ በሥጋ ቢሞትም በባሕርዩ ሞት የሌለበትን ጌታ ሞትና መቃብር ይዘው ሊያስቀሩት የማይቻላቸው በመሆኑ፤ ኃጢአትን፣ ሞትንና መቃብርን ደምስሶ፥ መቃብር ክፈቱልኝ፣ መግነዝ ፍቱልኝ፣ ሳይል በሦስተኛው ቀን በሌሊት ከሞት ተነሥቷል፡፡ ሲነሳም መቃብሩ እንደተዘጋ ድንጋዩም ሳይንከባለል በዝግ መቃብር ላይ ነው ቆሞ የታየው።ድንጋዩን ያንከባለለው የእግዚአብሔር መልአክ ነው ያውም ክርስቶስ መነሳቱንና መቃብሩ ባዶ መሆኑን ለእነ ማርያም መግደላዊት ለማሳየት ነው። ጌታ በኅቱም በድንግልና ተጸንሶ እንደተወለደ በኅቱም መቃብርም ተነስቷል ይህም መለኮት ከሥጋ ጋር ከትንሣኤውም በኋላ እንደ ተዋሐደ ያሳያል። የአይሁድ ጎመድ ሁሉ አልነበረም፡፡ ለጥበቃ ተመርጠው ልዩ መመሪያና ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶአቸው የነበሩ ጭፍሮችም ራሳቸውን እንኳ መጠበቅ ተስኗአቸው በያሉበት ወድቀው እንደ በድን ሆነው ነበር፡፡ ትንሣኤውን ለማየት ወደ መቃብሩ ሲመላለሱ ያነጉት ቅዱሳት አንስት ከሞት የተነሣውን ክርስቶስን ለማየት ቀዳሚ ዕድል ነበራቸው፡፡ አስቀድማ ለማየት የበቃችው ማርያም መግደላዊት መሆኗን ቅዱስ ወንጌል አስቀምጦታል፡፡ ከሷ በማስከተል፥ ሁሉም ሴቶች አይተዋል፡፡ ጌታችን በተነሣ ጊዜ፥ መልአኩ እንደ ፀሐይ በሚያበራ ልብስ እንደ በረዶ በነጣ ግርማ በሚያሰፈራ ሁኔታ ተገልጦ ነበር፡፡ ሴቶቹንም “አይዞአችሁ አትፍሩ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንድትሹ ዐውቃለሁ፤ እሱ ከዚህ የለም እንሣለሁ እንዳለ ተነሥቷል፡፡ ነገር ግን ኑ የተቀበረበትን ቦታ እዩ ካያችሁም በኋላ ፈጥናችሁ ሄዳችሁ ከሙታን ተለይቶ እንደተነሣ ለደቀ መዛሙርቱ ንገሩአቸው በገሊላ ይቀድማች ኋል (መታየትን ይጀምርላችኋል) በገሊላ ታዩታላችሁ”ብሎአቸው፥ ወደ መቃብሩ እየመራ ወሰዳቸው፡፡ ሴቶችም ፍርሃትና ድንጋጤ በተቀላቀለበት የደስታ መንፈስ ተውጠው ወደ መቃብሩ ሄዱ፡፡ ፍርሃት የእግዚአብሔርን መልአክ ማየታቸው፤ ደስታው ደግሞ፥ ትንሣኤውን መስማታቸው ነው፡፡ በደስታ ተሞልተው ዜናውን ለደቀ መዛሙርቱ ነግረው፥ እየተቻኮሉ ሲሄዱ ጌታችንን በመንገድ ተገለጠላቸው፡፡ ቀርበውም ሰገዱለት፤ እሱም አይዞአችሁ አትፍሩ፤ ሂዱ ለወንድሞቻችሁ ገሊላ ይሂዱ ዘንድ ንገሩአቸው በዚያ ያዩኛል” አላቸው፡፡ ዐሥራ አንዱ ሐዋርያትም ዜናውን ሰምተው ወደተባሉበት ቦታ ወደ ገሊላ ሄዱ፡፡ በዚያም ጌታችንን ከሙታን ተነሥቶ አዩት፤ ሰገዱለትም፡፡ ማቴ 28፣ ማር 16 ፥1፣ ለፍቅሩ ይሳሱ፥ ይናደዱ የነበሩ ጴጥሮስና ዮሐንሰም በጊዜው ወደ መቃብሩ ሄደው መነሣቱን አረጋገጡ፡፡ ዮሐ 20፥1 የክርስቶስ ትንሣኤ በስሙ ላመኑ ክርስቲያኖች ሁሉ ትንሣኤ ነው፡፡ ክርስቶስ ለሙታን ሁሉ በኲር ሆኖ ተነሥቶአል፡፡ የሙታንን ሁሉ መነሣት የሚያረጋግጥልን የጌታ ትንሣኤ ነው፡፡ የክርስቶስም ትንሣኤ መርገመ ሥጋ፥ መርገመ ነፍስ፤ ሞተ ሥጋ፥ ሞተ ነፍስ የተሻረበት ርደተ ገሃነም ጠፍቶ፥ በአዳም የተፈረደው ፍርድ ሁሉ ተደምስሶ፤ ፍጹም ነፃነት፣ የማይለወጥ ደስታ፣ የተገኝበት ስለሆነ ፋሲካ ይባላል፡፡ ፋሲካ ደስታ ነው እስራኤል ከግብጽ ባርነት ነፃ የወጡበትን ቀን ፋሲካ ብለውታል፡፡ የእርቅ፣ የሰላም፣ የድኅነት ቀን ነው ከሞት ከመነሣት ከመቃብር ጨለማ ከመውጣት ከዲያብሎስ ቁራኝነት ከመላቀቅ፥ ከሲኦል እስራት ከመፈታት የሚበልጥ ምን ደስታ ሊኖር ይችላል? የክርስቶስ ትንሣኤ እግዚአብሔር እኛን ምን ያህል እንደ ወደደን የምናስተውልበት፣ የፍቅሩን ጥልቀት፤ የቸርነቱን ስፋት የምናደንቅበት፤ የነፍሳችን የዕረፍት ቀን ነው፡፡ በሰው ዘንድ በቃል ሲነገር በተግባር ሲፈጸም የሚታየው ፍቅር ዘመድ ወዳጅ የሚለይበት ሰው ከሰው የሚዳላበት፤ ባለ ካባ ከባለ ካባ፣ ባለዳባ ከበለዳባ የሚበልጥበት፤ የሚወደውን የሚወዱበት፤ የሚጠላውን የሚጠሉበት ነው፡፡ ለሚጠሉት ይቅርና ለሚወዱት ተላልፎ የሚሞቱበት ፍጹም ፍቅር በዓለማችን አይታይም፡፡