ስንክሳር
Open in Telegram
#ስንክሳር የቴሌግራም ቻናላችንን ይከታተሉ። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ዶግማ ቀኖና ስርአትና ትውፊትን በጠበቀ መልኩ የእለቱ ስንክሳር ላይ የተጻፉ የጻድቃን፣ የሰማዕታት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት፣ የቅዱሳን አበው መነኮሳት፣ የቅዱሳት አንስትና የደናግላን ገድላቸው ይዘከርበታል:: 👇ይህ ቻናል ለሌሎችም እንዲደርስ #Share #ሼር አድርጉ! ◈ https://t.me/Sincsar
Show more397
Subscribers
No data24 hours
No data7 days
No data30 days
Posts Archive
397
✅ስንክሳር
🚩ሐምሌ 24
✅አቡነ ዘዮሐንስ ጻድቅ
✏ኢትዮጵያዊው ጻድቅ የተወለዱት በ13ኛው መቶ ክ/ዘመን መጨረሻ አካባቢ ሲሆን ሃገረ ሙላዳቸው ሸዋ (መርሃ ቤቴ) ነው:: ወላጆቻቸው ዘካርያስ እና ሶፍያ እግዚአብሔርን የሚፈሩ : እመ ብርሃንን የሚወዱና ለነዳያን የሚራሩ ነበሩ::
✏ደጉ ዘካርያስ መስፍን ሲሆን እርሱ በሌለበት የሸዋ ገዢ ሊያገባት በመሞከሩ ቅዱስ ገብርኤል ቀስፎታል:: ሕዝቡ ገዢነቱን ለዘካርያስ ሰጥተውታል:: ከቆይታ በኋላም ድንግል ማርያም የተባረከ ፍሬ ሰጠቻቸው:: ስሙን "ዮሐንስ" አሉት:: በሒደት ግን ዘዮሐንስ (የዮሐንስ) ተብሏል::
✏ቅዱሱ ዘዮሐንስ እስከ ሰባት ዓመቱ ድረስ በእናቱ እቅፍ ቆይቶ ወደ ትምሕርት ገብቷል:: ጸጋ እግዚአብሔር ጠርቶታልና በአጭር ጊዜ ብሉይ ከሐዲስ ጠነቀቀ:: አደን ይወድ ነበርና ሊያድን ሲወጣ 'ብርሕት ደመና' ድንገት ነጥቃ ከኢትዮጵያ (ሽዋ) ወደ ኢየሩሳሌም (ጐልጐታ) አደረሰችው::
✏ደስ ብሎት ቅዱሳት መካናትን ተሳልሞ ደመናዋ ወደ ሃገሩ መለሰችው:: ከጥቂት ጊዜ በኋላም ከሰማይ ነቢዩ ኤልያስና መጥምቁ ወርደው ባረኩትና "ክፍልህ ከእኛ ጋር እንዲሆን መንን" አሉት::
✏ዘዮሐንስ ወላጆቹንና ቤተ ክርስቲያንን እያገለገለ (ዲቁና ነበረውና) ሃያ አምስት ዓመት ሞላው:: ያን ጊዜ ወላጆቹ "እንዳርህ" ቢሉት "የለም! አይሆንም" አላቸው:: አርጅተው ነበርና ስለእነርሱ ዕረፍት ጸለየ:: ፈጣሪም ሰምቶታልና ሁለቱም በክብር ተከታትለው ዐረፉ::
✏ሕዝቡ በወላጆቹ ፈንታ "እንሹምሕ" ቢሉት "እንቢ" ብሎ ወርቁን : ብሩን : ርስቱን : ቤቱን ሁሉ ለነዳያን አካፍሎ ወደ ደብረ ሊባኖስ ገባ::
ጊዜው አቡነ ተክለ ሃይማኖት ባረፉ በሃምሳ ዓመት አካባቢ ሲሆን አባ ሕዝቅያስ አበ ምኔት ነበሩ::
(ከዚህ በኋላ አንቱ እያልን እንቀጥል)
✏አባ ዘዮሐንስ ለሰባት ዓመታት ገዳሙን ረድተው መነኮሱ:: እንደ ልማዱ ደመና ነጥቆ ወስዷቸው ከኢየሩሳሌሙ ሊቀ ጳጳሳት ቅስና ተቀብለዋልና በደብረ ሊባኖስ ለሃያ አምስት ዓመታት አገለገሉ:: ቤተ መቅደሱን በመዓልት ሰባት ጊዜ በሌሊት ሰባት ጊዜ ያጥኑ : እልፍ እልፍ ይሰግዱ : ተግተው ይጸልዩ : ይታዘዙም ነበር::
✏ከዚያም በፈጣሪ ትዕዛዝ በትግራይና በሌሎቹ የሃገራችን ክፍሎች ወንጌልን ሰብከዋል:: እድሜአቸው ሰባ በሆነ ጊዜ ወደ ጌታ መቃብር (ጐልጐታ) ሔደው ተሳልመው በእርሱ (በጌታ) ትዕዛዝ ወደ ደራ (ጣና ዳር) ተመለሱ::
✏በአካባቢውም ገብርኤልና መስቀል ክብራ የሚባሉ ደጋግ ባለ ትዳሮች ነበሩና በእንግድነት ከቤታቸው አደሩ:: ቤቱ በቅጽበት በበረከት ሞላ:: እነርሱም የጻድቁን አምላክ አመሰገኑ::
✏ቀጥሎም በመስቀል ክብራ መሪነት ጻድቁ ዘዮሐንስ ወደ ክብራን ገብርኤል ደሴት ገቡ:: (በነገራችን ላይ ደሴቱ ክብራን የተባለ መስቀል ክብራ በምትሰኘው ደግ ሴት ስም ነው:: እርሷና ባሏ ገብርኤል የተቀደሱ ሰዎች ነበሩና::)
✏ጻድቁ አቡነ ዘዮሐንስ ወደ ደሴቶቹ (ክብራንና እንጦንስ ኢየሱስ) እንደ ገቡ ደሴቶቹ በግማሹ የስውራን ቤት : እኩሉ ደግሞ የጣዖት (ዘንዶ) አምላኪዎች መኖሪያ ነበር:: ጻድቁ ክብራን ገብርኤልንና እንጦንስ ኢየሱስን የመሠረቱት በ1315 ዓ/ም አካባቢ በዐፄ ዓምደ ጽዮን ዘመን ነው:: በአካባቢው ዘንዶ ይመለክ ነበርና ያንን በጸሎታቸው አጥፍተው ሕዝቡን አጥምቀዋል::
✏በዚያም ገዳሙን የወንድና የሴት ብለው ከፈሉ:: የወንዶች ክብራን ሲሆን ሴት አይገባበትም:: አበ ምኔቱም ራሳቸው ጻድቁ ነበሩ::
የሴቶች እንጦንስ ኢየሱስ ከካህናት በቀር ወንድ አይገባበትም:: እመ ምኔቷም እናታችን ቅድስት ክብራ (መስቀል ክብራ) ሆነች::
✏ጻድቁ አቡነ ዘዮሐንስ በክብራን ለሰላሳ አምስት ዓመታት ተጋድለዋል:: ለጸሎት ከመቆማቸው ብዛት እግራቸው አብጦ : ቆሳስሎ ነበር:: የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘወትር ይገለጽላቸው : ያነጋግራቸውም ነበር::
✏እጅግ ድንቅ የሆኑ ተአምራትን ሠርተው: ለወንጌል እንደሚገባ ኑረው: በተወለዱ በመቶ አምስት ዓመታቸው በዚህች ቀን ዐርፈዋል:: ጌታችንም በስማቸው ለተማጸነና ገዳማቸውን ለሳመ የምሕረት ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል:: ልደታቸው ደግሞ ኅዳር 13 ቀን ይከበራል:: ገዳማቸው (ክብራን ገብርኤልና እንጦንስ ኢየሱስ) ድንቅ ነውና እንድታዩት ተጋብዛቹሃል::
✅ ቅዱስ አባ ኖብ ሰማዕት
✏በምድረ ግብጽ ከታዩ ታላላቅ ከዋክብት አንዱ ቅዱስ ኖብ በሃገረ ንሒሳ ተወልዶ ያደገ ሲሆን ዘመኑም ዘመነ ሰማዕታት (3ኛው መቶ ክ/ዘመን) ነው:: ወላጆቹ በልጅነቱ ብዙ ሃብት ትተውለት ያርፋሉ:: ወደ ቤተ ክርስቲያን ሔዶ ካህኑ ስለ ምናኔና ሰማዕትነት ሲሰብክ ይሰማዋል::
✏ገና በአሥራ ሁለት ዓመቱ በቤቱ የነበረውን ሁሉ ለነዳያን አካፍሎ መስቀለ ክርስቶስን ሊሸከም ወደ ዐውደ ስምዕ (የምስክርነት አደባባይ -የክርስቲያኖች መገደያ ቦታ) ተጓዘ:: በዚያም በጉባዔ መካከል ክርስቶስን ሰበከ:: በዚህ ምክንያት በሰብዓዊ አካል ሊሸከሙት የማይችሉትን መከራ በልጅ ገላው ተቀብሏል::
✏በዚያው ልክም ብዙ ተአምራትን ሰርቷል:: በተአምራቱና በጣዕመ ስብከቱም ከመቶ ዘጠና ሺህ በላይ አሕዛብን ወደ ክርስትና መልሶ ሁሉም ተሰይፈዋል:: በእሳት: በስለት: በሰይፍ: በባሕርና በየብስ መከራን ከተቀበለ በኋላ በዚህች ቀን አክሊለ ክብርን ይቀበል ዘንድ አንገቱን ተከልሏል::
✏ጌታችን የገባለት ቃል ኪዳኑ ግሩም ነውና ዛሬ በግብጽ በድምቀት ይከበራል:: ምንም በእድሜ ልጅ ቢሆን ቤተ ክርስቲያን አባ (አባታችን) ኖብ ትለዋለች::
✥ ቸር ጌታ መድኃኔ ዓለም በጻድቁና በሰማዕቱ ጸሎት ይማረን:: ከበረከታቸውም ይክፈለን::
✅ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.አቡነ ዘዮሐንስ ጻድቅ ዘክብራን (ኢትዮጵያዊ)
2.ቅዱስ አባ ኖብ ሰማዕት
3.መቶ ዘጠና ሺህ ሰማዕታት (የአባ ኖብ ማኅበር)
4.አባ ተክለ አዶናይ ዘደብረ ሊባኖስ
5.አቡነ ተወልደ መድኅን (ኢትዮጵያዊ)
6.አባ ስምዖን ጻድቅ ሊቀ ጳጳሳት
7.ቅድስት ክብራ (መስቀል ክብራ) ዘእንጦንስ ኢየሱስ
✅ ወርኀዊ በዓላት፦
1.ቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት
2.ቅዱስ አጋቢጦስ (ጻድቅ ኤጲስቆጶስ)
3.ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ
4.ቅዱስ ቶማስ ዘመርዐስ
5.ቅዱስ አብላርዮስ ታላቁ
6.ሃያ አራቱ ካኅናተ ሰማይ (ሱራፌል)
7.ቅዱስ አባ ሙሴ ጸሊም (ኢትዮጵያዊ)
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
397
✅ስንክሳር
🚩ሐምሌ 23
✅ታላቋ ቅድስት መሪና ሰማዕት
✏እናታችን ቅድስት መሪና ስም አጠራራቸው ከከበረ : ተጋድሏቸው ካማረ ታላላቅ ሴት ሰማዕታት አንዷ ናት:: ተወልዳ ያደገችው ከዋናው ዘመነ ሰማዕታት በፊት በ2ኛው መቶ ክ/ዘመን ሶርያ አካባቢ ነው:: አባቷ ዳኬዎስ የሚባል ጣዖት አምላኪ ቢሆንም እናቷ ግን ክርስቲያን ነበረች::
✏ነገር ግን እናቷ ገና በ5 ዓመቷ ሞተችባትና ለሞግዚት ተሰጠች:: የእግዚአብሔር ጥበብ ሆኖ ሞግዚቷ ደግ ክርስቲያን ነበረችና ለ10 ዓመታት ሃይማኖተ ክርስቶስን እና ምግባረ ጽድቅን አስተማረቻት:: ዕድሜዋ 15 ዓመት ሲሆን አባቷ ዳኬዎስ አረፈ::
✏በዘመኑ ዳኬዎስ የሚሉት (ቅዱስ መርቆሬዎስን የገደለው) ክፉ ንጉሥ ነበርና ክርስቲያኖችን አሳደዳቸው:: ይህን ዜና ቅድስት መሪና ስትሰማ ደስ አላት:: እጅግ ባማረ ንጽሕና እንደ ኖረች ሁሉ በክርስቶስ ስም ደሟን ለማፍሰስ አስባ ወደ ንጉሡ መኮንን ሔደች::
✏ አበው እንዳስተማሩን ከሴቶች ሰማዕታት በውበትና ደም ግባት እንደ ቅዱሳት:-
*መሪና
*አርሴማ እና
*ጣጡስ የሚያክል የለም:: ዐይንን ማፍዘዝ የሚችል ውበት ነበራቸው::
✏መኮንኑ መልኩዋን ዐይቶ ሰውነቱ ተናወጠ:: "ጣዖት አምልኪና የእኔ ሚስት ሁኚ" አላት:: እርሷ ግን መኮንኑን ከነ ጣዖቱ አቃለለችው:: "እኔ የክርስቶስ ሙሽራ ነኝ" አለችው::
✏መኮንኑ ካነጋገሯ የተነሳ ተቆጥቶ ይገርፏት ዘንድ አዘዘ:: መሬት ላይ ጥለው በብረት ዘንግ ቢመቷት አካሏ እየተቆረጠ ብዙ ደም ፈሰሰ:: ወስደውም ጨለማ ውስጥ ጣሏት:: ቅዱስ ሚካኤል ከሰማይ ወርዶ አድኗት: አጽንቷትም ዐረገ::
✏በማግስቱ በመጋዝ አካሏን ቆራርጠው ጣሉ:: ዳግመኛ ሊቀ መላእክት አዳናት:: ወደ ጨለማ ክፍል ወስደው ሲጥሏት ትልቅ ዘንዶ መጣባት:: እጆቿ ተዘርግተው እጸለየች ዋጣት:: እርሷ ግን ጸሎቷን ቀጠለች:: ከደቂቃዎች በሁዋላ ግን ዘንዶው ለ2 ተሰነጠቀና እጆቿ እንደተዘረጉ ወጣች::
✏በሌላ ቀን ግን ሰይጣን ፊት ለፊት መጥቶ ታገላት:: ከሰማይ ነጭ ርግብና መስቀል ወርዶላታልና አልቻላትም:: ከእግሯ በታች ጥላ ደጋግማ ረገጠችው:: ሰይጣንም በሐፍረት እየጮኸ ሔደ::
"ለሰይጣን ኬደቶ ከመ አሣዕን በእግር" እንዲል:: (እንዲህ ነበሩ የቀደመው ዘመን እናቶቻችን)
✏መኮንኑ ከክርስትና ያስወጣት ዘንድ በትልቅ ጋን ውሃ አስፈልቶ "በዚያ ላይ ቀቅሏት" አለ:: ድንገት ግን ከሰማይ ነጭ ርግብ ወርዳ: ውሃውን አቀዝቅዛ: 3 ጊዜ በውሃው አጠመቀቻት:: (እስከዚህ ሰዓት ድረስ አልጠመቀችም ነበርና)
✏ርግቧ የብርሃን ልብስ አልብሳ: አክሊለ ክብር ደፋችላት:: መኮንኑ ተስፋ ስለ ቆረጠ "አንገቷን በሰይፍ ምቱ" አለ:: በዚያች ሰዓት የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወርዶ "ብጽዕት መሪና ብጽዐን ይገባሻል" አላት::
✏"ስምሽ በሚጠራበት: መታሰቢያሽ በሚደረግበት ሁሉ በዚያ ረድኤት: በረከት ይበዛል:: አንቺን ያከበረውን አከብረዋለሁ:: ከርስትሺም አስገባዋለሁ" ብሏት ጌታችን ዐረገ::
✏ወታደሮቹ አንገቷን በሰየፉ ጊዜ ታላቅ መነዋወጽ ሆነ:: ድውያን ተፈወሱ: ዕውሮች አዩ: አንካሶች ረቱ: የማይሰሙትም ሰሙ:: ቅዱሳን መላእክትም ከሰማያት ወርደው የቅድስት መሪናን ነፍስ በዝማሬ አሳረጉ::
✅ ቅዱስ ለንጊኖስ ሰማዕት
✏ለንጊኖስ ማለት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የስብከት ዘመን የዺላጦስ ወታደር የነበረ ሰው ነው:: ስለ ጌታችን ተአምራት በየጊዜው ይሰማ ነበር:: ሔዶ እንዳያገኘው ግን አይሁድን ይፈራ ነበር:: እነርሱ "በክርስቶስ ያመነ ሁሉ ከምኩራብ ይባረር" ብለው ነበርና:: (ዮሐ. 9:22)
✏ጌታችን በተሰቀለባት ዕለተ ዐርብ ግን ጭንቅ ሆነበት:: ጌታን እንዲሰቅሉ ከታዘዙ ወታደሮች እንደ አንዱ ተመርጦ ነበርና በዘዴ "አሞኛል" ብሎ እስከ 9 ሰዓት ድረስ ቆየ::
✏በሁዋላ ግን አይሁድ "በክርስቶስ ሞት ያልተባበረ ሁሉ ወንጀለኛ ነው" የሚል አዋጅ በማስነገራቸው እየፈራ ቀራንዮ ሲደርስ "ጐኑን ውጋው" ብለው ረዥምና ጥቁር ጦር ሰጡት:: ለንጊኖስ ወደ ጌታችን ዐይን ተመለከተ:: እያየው እንዳልሆነ ገመተ::
✏ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በባሕርይ ሥልጣኑ ለይቷልና ጦሩን ጨብጦ ወደ ጌታ ጐን ልኮ ወጋው:: ከጌታ ቀኝ ጐንም በ"ለ" አምሳል ትኩስ ደምና ውሃ ፈሰሰ:: አንዷ ፍንጣቂ ሔዳ የታወረች ዐይኑ ላይ ዐርፋ ዐይኑን አበራች::
✏ለለንጊኖስ ታላቅ ደስታ ሆነ:: ለእኛ ግን ማየ ገቦና ደመ ገቦ ፈለቀልን:: የጌታችን ትእግስቱና ቸርነቱ ግን ይደንቃል::
"ከመ ኢየሐስብ ቦቱ ዘኩናተ እዱ ርግዘቶ::
በኃጣውኢሁ ለዘኢፈቀደ ሞቶ::
ምሕረቶ እሴብሕ ወዐዲ ትዕግስቶ::" እንዳሉ ሊቃውንት::
✏ጌታችን ከተነሳ በሁዋላ ለንጊኖስ ወደ ቅዱስ ዼጥሮስ ዘንድ ሒዶ ስለ እውነት : ስለ ሃይማኖትም ተማረ:: ተጠምቆ: ምድራዊ ወታደርነቱን ትቶ እየሰበከ ከኢየሩሳሌም ወደ ቀዸዶቅያ ወረደ:: ለዘመናትም ጌታችን ክርስቶስን በሥርዓተ ወንጌል አገለገለ::
✏በመጨረሻም በጢባርዮስ ቄሣር ዘመን አይሁድ አሳደዱት: አንገላቱት:: የነርሱ ወገን ስለነበረም መከራ አጸኑበት:: የጽድቅ አርበኛና የክርስቶስ ሐዋርያ ቅዱስ ለንጊኖስ ግን ጸና:: በዚህች ዕለትም አይሁድ አንገቱን ቆርጠውት ለሰማዕትነት በቃ:: ቅዱሱ በሕይወቱም በዕረፍቱም ተአምራትን ሠርቷል::
✥ እግዚአብሔር በቸር ጥሪው ሁላችንም ወደ ቀናው የጽድቅ ጐዳና ይጥራን:: ከሰማዕታቱም ረድኤት በረከት ይክፈለን::
🚩 ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.ቅድስት መሪና እናታችን (ታላቋ ሰማዕት)
2.ቅዱስ ለንጊኖስ ሐራ (ሐዋርያና ሰማዕት)
3.ቅዱስ አብጥልማዎስ
🚩 ወርኀዊ በዓላት፦
1.ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት
2.ቅዱስ ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት
3.ነቢየ ጽድቅ ቅዱስ ሰሎሞን (ንጉሠ እሥራኤል)
4.አባ ጢሞቴዎስ ገዳማዊ
5.ቅዱስ ዳንኤል ነቢይ
6.አባ ሳሙኤል
7.አባ ስምዖን
8.አባ ገብርኤል
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
397
✅ስንክሳር
🚩ሐምሌ 22
✅ ቅዱስ መቃርስ ሰማዕት
✏ሰማዕቱ ተወልዶ ያደገው በአንጾኪያ (ሶርያ) በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን ሲሆን የታላቁ ቅዱስ ፋሲለደስ እና የቅድስት ሶፍያ ልጅ ነው:: ምንም በቤተ መንግስት ውስጥ ቢያድግም ከወላጆቹ ፍቅረ ክርስቶስን : ንጽሕናንና ደግነትን ወርሷል::
✏በተለይ ነዳያንን ሰብስቦ ዕለት ዕለት ያበላ ነበር:: (መቃርስ ማለት በልሳነ ዮናኒ ብጹዕ : ንዑድ : ክቡር ማለት ነው::) ቅዱሱ ያ የመከራ ዘመን ሲመጣ ሁሉም ቤተሰብ ስለ ክርስቶስ መሞትን በመምረጡ እርሱም ደስ እያለው የመከራው ተካፋይ ሆኗል::
✏ያን የመሰለ የቤተ መንግስት ክብር ስለ ክርስትና ናቀው:: ተገረፈ:: ተሰቃየ:: በእሳትም ተቃጠለ:: አንድ ጊዜም በአደባባይ የሞተ ሰው በጸሎቱ አስነስቶ "መስክር" አለው:: ከሞት የተነሳውም የክርስቶስን አምላክነት በመመስከሩ በአደባባይ የነበሩ ብዙ አሕዛብ በክርስትና አምነው ተሰይፈዋል::
✏ቅዱስ መቃርስን ግን ብዙ አሰቃይተው በዚህች ቀን አንገቱን ቆርጠውታል:: ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ አጽሙን አፍልሶ በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን በስሙ ቤተ ክርስቲያን አንጾለታል::
✅ቅዱስ ለውንትዮስ ሰማዕት
✏ቅዱሱ የተወለደው በተመሳሳይ ዘመን (በቅዱስ መቃርስ) ሲሆን ሃገሩ ጠራብሎስ ትባላለች:: በወቅቱ በወታደርነት ነገሥታቱን ያገለግል ነበር:: ድንግል : ደም ግባት የሞላለት ወጣት ስለ ነበር በሰዎች ፊት ሞገስ ነበረው::
✏እርሱ ግን ምንም ወታደር ቢሆን ጾምና ጸሎትን ያዘወትር ነበር:: በተለይ ደግሞ የዳዊትን መዝሙር እየመላለሰ ይጸልየው : ይወደው ነበር:: ንግግሩ ሁሉ በመንፈስ ቅዱስ ጨውነት የታሸ ነውና ብዙ ጓደኞቹን ከክህደት ወደ ሃይማኖት : ከክፋት ወደ ደግነት መልሷል::
✏የመከራ ዘመን በደረሰ ጊዜም በገሃድ ስመ ክርስቶስን ይሰብክ ነበር:: ክፉ ሰዎች ከሰውት በመኮንኑ ፊት በቀረበ ጊዜም አልፈራም:: ወታደሮቹ መሬት ላይ ጥለው እየደበደቡት : ደሙ እንደ ጐርፍ እየተቀዳ እርሱ ግን ይዘምር ነበር::
✏በመጨረሻም ስለ ክርስቶስ ፍቅር በዚህች ቀን አንገቱን ተሰይፏል:: ቅዱስ ለውንትዮስ እጅግ ተአምረኛ ሰማዕት ነውና በእምነት እንጥራው::
✥ እግዚአብሔር ዐጽመ ሰማዕታትን ይጠብቅልን:: ከሰማዕታቱ ጽናትን : ጸጋ በረከትን ይክፈለን::
🚩ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.አቡነ ጴጥሮስ ሰማዕት (ኢትዮጵያዊ)
2.ቅዱስ መቃርስ ሰማዕት (የፋሲለደስ ልጅ)
3.ቅዱስ ለውንትዮስ (ክቡር ሰማዕት)
4.አባ እንጦንስ አበ መነኮሳት (ቅዳሴ ቤታቸው)
5.ቅዱስ መርካሎስ
🚩ወርኀዊ በዓላት፦
1.ቅዱስ ዑራኤል ሊቀ መላእክት
2.ቅዱስ ሉቃስ ወንጌላዊ
3.ቅዱስ ደቅስዮስ (የእመቤታችን ወዳጅ)
4.አባ ጳውሊ የዋህ
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
https://t.me/Sincsar
397
+ ከባለ ትዳሮች ማእረግ ያልደረሰ ምንኩስና +
----------***------------
ምንኩስና (መነኮሰ) ማለት ከዓለም የራቀ፤ መናኝ ማለት ነው።
ምንኩስና ማለት አንድ ልብ አንድ ሐሳብ ሆኖ እግዚአብሔርን
በማገልገልና እሱን ብቻ በማሰብ ተወስኖ መላእክትን በመምሰል በምስጋና የሚኖር ማለት ነው። ምንኩስና ማለት ክብረ ዓለምን ንቆ፣ ንፅህናን ጠብቆ ፣ በጾም በፀሎት ፣ በገድል፣ ተጠምዶ የሚኖር ማለት ነው።
የምንኩስና ሕጉ ራስን ለመከራ ማዘጋጀት ለመከራ አሳልፎ መስጠት እንዲገባ ያዝዛል እንጅ ራስን ለሹመት ለሽልማት ማደላደል አይደለም። ምክንያቱም "ልጄ ለእግዚአብሔር ትገዛ ዘንድ ወደ ገዳም ሂድ ሰውነትህን ለመከራ አዘጋጅ" ተብሎ ተጽፏልና። አሁን ግን የከተማ መነኩሴ በዝቶ የምንኩስናን ማንነት የጠፋባቸው አቅለ ቢሶች ብዙ ናቸው።
ሐምሌ 21 ቀን ታስቦ የሚውል አስተዋይ የሆነ የተመሰገነ ቅዱስ አወ ክርስቶስ አረፈ። ሚስት ባገባ ጊዜም በጾምና በጸሎት እያገለገሉ በድንግልና በአንድነት ኖሩ በሌሊትም ማቅ ለብሰው እየብቻቸው ይተኙ ነበር። በቀንም እርሱ በጎችን እየጠበቀ በዱር ይውል ነበር። እርሷም ለእንግዳ ምግብ እያዘጋጀች ትውል ነበር።
ከበግ ጥበቃ (ከስምሪቱ) በገባ ጊዜ የእንግዶችን እግር ያጦብ ነበር። ማእድንም በማዘጋጀት ታገለግል ነበር። ፍጹማንም መነኵሳትም ሥራቸው እንዴት እንደሆነ ይገልጥላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር በጠየቁ ጊዜ ገድላችሁ በአወ ክርስቶስና በሚስቱ ተጋድሎ መጠን አልደረሰም የሚል ቃል ከሰማይ ወደ እርሱ መጣ።
መንኩሰናል ይላሉ ነገርግን ከባለ ትዳሮች ክብር ማረግ ያልደረሱ እንደነዚህ መነኵሳት ብዞዎች ናቸው። እንደውም አሁን አሁንማ ሀሃገርንም ቤተ ክርስትያንንም የሚበጠብጡ ኦርቶዶክሳውያን ደማቸው ለመፍሰሱ ምክንያት የሆኑ ብዙዎች ናቸው። ከባለ ትዳሮች ያልተሻለ ማእረግ ከባለ ትዳሮች ያልተሻለ አኗኗር እየኖሩ መንኩሻለሁ ቢሉት ከንቱነት ነው።
ሲጀመር ዓለምን ንቆ በፍላጎቱ ተገንዞ የሄደ በተለያየ ምክንያት ቤተ ክርስቲያንን እየፈተነ ያለ መነኩሴ ሁሉ ቢችል ወደ ገዳሙ በደ በአቱ ወደ መኗሪያው ይመለስ።
እነዚያም መነኵሳት ሄደው የቅዱስ አወ ክርስቶስንና ሚስቱን ሥራቸውን መረመሩ በጭንቅ በግዳጅም ሥራቸውን ገለጡላቸው እያደነቁም ተመለሱ በእንዲህ ያለ ሥራም ኖረው በሰላም አረፉ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘለአለሙ አሜን
21/11/2015
397
✅ ስንክሳር
🚩ሐምሌ 21
✅ ድንግል እመቤታችን እና ቅዱስ ዑራኤል
✏በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት በዚህች ቀን ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ
የሆነው ቅዱስ ዑራኤል:-
1.ድንግል ማርያም በአካለ ሥጋ እያለች ወደ ሰማይ አሳርጓታል:: በሠረገላ ብርሃን ጭኖ:
በክንፎቹም ተሸክሞ: አስቀድሞ ገነትን ቀጥሎም ሲዖልን አስጐብኝቷታል:: በዚህም ምክንያት
እመ ብርሃን ስለ ኃጥአን የምታለቅስ: የምትለምንና የምትማልድ ሆናለች:: ለምናም
አልቀረች የምሕረት ቃል ኪዳን ተቀብላለች::
2.ቅዱሱ መልአክ እመ ብርሃንን በስደቷ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ መርቶ አምጥቷታል:: በክንፉ
ተሸክሞ: በአራቱም አቅጣጫ አዙሮ አሳይቶ አሥራት እንድትቀበል አድርጓል::
3.ጌታችን በተሰቀለ ጊዜ ደሙን በጽዋዕ አድርጐ በኢትዮጵያ ወንዞች ላይ አፍስሷል::
4.ለብዙ ቅዱሳን (አባ ጊዮርጊስን ጨምሮ) ጽዋዐ ልቡናን አጠጥቷል::
✅ አቡነ በጸሎተ ሚካኤል ኢትዮጵያዊ
✏ወላጆቻቸው ማርቆስ እና እግዚእ ክብራ ይባላሉ:: ተአምራትን ገና ከእናታቸው ማኅጸን
ጀምሮ ይሠሩ የነበሩት ጻድቁ በልጅነታቸው መጻሕፍትን ተምረው መንነዋል:: በስብከተ
ወንጌልም ትግራይና አካባቢውን አድርሰዋል:: በነዚህም ጊዜያት ብዙ አርድእትን
አፍርተዋል::
✏በጋስጫ ገዳም መስርተው የወንድና የሴት ብለውም ለይተዋል:: ሲጸልዩም ሆነ ሲያስተምሩ
ተደሞ ይመጣባቸው የነበረ ሲሆን አንድ ቀን እባቡን ዓሣ አድርገው ደቀ መዛሙርትን
አስደንቀዋል::
✏ከጾም: ከጸሎትና ከስግደት ባሻገር ከወቅቱ ንጉሥ ዓምደ ጽዮን መከራ በመቀበላቸው እንደ
ሰማዕትም ይቆጠራሉ:: ከብዙ የገድል ዓመታት በኋላም በ1330 ዓ/ም በዚህች ቀን
ትግራይ ውስጥ ዐርፈዋል:: በቆይታ ግን ወደ ጋስጫ ዐጽማቸው ፈልሷል::
✅ቅዱስ ላዕከ ማርያም ኢትዮጵያዊ
✏ቅዱሱ የአፄ ናዖድ የልጅ ልጅ : የቅድስት ሮማነ ወርቅ ልጅ : የልብነ ድንግል የእህት
ልጅና የገላውዴዎስ አጐት ነው:: በግራኝ አህመድ ዘመን ተማርኮ ወደ የመን : ከዛም ቱርክ ተወስዷል::
ሃይማኖቴን አልክድም ስላለ ብዙ አሰቃይተው : አባለ ዘሩን ቆርጠው ጃንደረባ አደረጉት:: በድንቅ ተአምር ግን ወደ ሃገሩ ተመለሰ:: እስከ ዕለተ ሞቱም ነዳያንን ሲያበላ ኑሮ ዛሬ ዐርፏል::
✅ቅዱስ ሱስንዮስ
✏በ5ኛው መቶ ክ/ዘመን የነበረ የኤፌሶን ሰው ሲሆን ጃንደረባም ነበር:: በ431 ዓ/ም ሁለት
መቶውን የጉባዔ ኤፌሶን ሊቃውንት አገልግሎ በዛው ዓመት አርፏል:: ቅዱስ ቄርሎስ ገንዞ
ቀብሮታል::
✅ብጹዕ አወ ክርስቶስ
✏ከተባረከች ሚስቱ ጋር በአንድ ቤት ውስጥ : ግን ደግሞ በድንግልና ኑረዋል:: ቀን ቀን
እንግዳ ሲቀበሉ: ነዳያንን ሲያበሉ ውለው ሌሊት ሲገሰግዱና ሲጸልዩ ያድሩ ነበር:: ጌታችን
ከሰማይ መስክሮላቸው ዛሬ ዐርፈዋል::
✅ቅዱስ ዮራኖስ
✏በሉቃስ ወንጌል ላይ (ሉቃ. 23:47) የምናገኘው የመቶ አለቃው ሲሆን በጌታችን ትንሣኤ
ቀን የጠፋች ዓይኑ በርታለት በክርስቶስ አምኖ ለሰማዕትነት በቅቷል::
✥ከእመቤታችን ድንግል ማርያም ጣዕሟን ፍቅሯን : ከቅዱሳኑ ሁሉ ጸጋ በረከትን እግዚአብሔር ያድለን::
🚩ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.ቅድስት ድንግል እግዝእትነ ማርያም ወላዲተ አምላክ
2.ቅዱስ ዑራኤል ሊቀ መላእክት
3.አቡነ በጸሎተ ሚካኤል ጻድቅ (ኢትዮጵያዊ)
4.ቅዱስ ላዕከ ማርያም ሔር (ኢትዮጵያዊ)
5.አቡነ ኤዎስጣቴዎስ (ኢትዮጵያዊ) ልደታቸው
6.ብጹዕ አወ ክርስቶስና ሚስቱ (ጻድቃን)
7.ቅዱስ ሱስንዮስ ጻድቅ
8.ቅዱስ ዮራኖስ መኮንን (የመቶ አለቃው)
🚩ወርኀዊ በዓላት፦
1.አበው ጎርጎርዮሳት
2.አቡነ ምዕመነ ድንግል
3.አቡነ አምደ ሥላሴ
4.አባ አሮን ሶርያዊ
5.አባ መርትያኖስ ጻድቅ
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
397
✅ስንክሳር
🚩ሐምሌ 20
✅በዓታ ለእግዝእትነ ማርያም
✏ለስም አጠራሯ ክብር ይሁንና እመ ብርሃን ድንግል ማርያም በዚህች ቀን ወደ ቤተ መቅደስ ገብታለች:: በዓሉ ከሰላሳ ሦስቱ የእመቤታችን በዓላት እንደ አንዱ አይቆጠርም:: ምክንያቱም ቅዱሳን ሊቃውንት በዓታ ከበዓታ ጋር ይስማማል ብለው የታኅሣሥ ሦስትን በዓል ከሰላሳ ሦስቱ ደምረውታል::
✏እመቤታችን ወደ ቤተ መቅደስ የገባችው ሁለት ጊዜ ሲሆን:-
1.ዛሬ የምናከብረውና በተወለደች በሰማንያ ቀኗ የገባችበት ነው:: (ከግንቦት 1 ጀምረን እናስላው: 80 ቀን ይመጣል::) ኦሪት እንዳዘዘው ቅዱሳን ኢያቄምና ሐና ንጽሕት ሕፃን ድንግል ማርያምን ታቅፈው: የርግብ ልጆች (ግልገሎች): ዋኖስም ይዘው ወደ ቤተ መቅደስ ሒደዋል:: ካህናቱ ዘካርያስና ስምዖን ወጥተው በደስታ ተቀብለዋቸዋል:: እመቤታችን ለወላጆቿ ማኅጸን የከፈተች በኩር ናትና በእግዚአብሔር ፊት አቅርበዋታል::
2.ከሦስት ዓመታት በኋላ እንደ ስዕለታቸው ወደ ቤተ መቅደስ ወስደው ለእግዚአብሔር ሰጥተዋት ተመልሰዋል::
እግዚአብሔር ዛሬ ያልቃል: ነገ ይደቃል የማይባለውን የድንግል እናቱን ፍቅር አብዝቶ ያድለን:: በረከቷም በእኛ ላይ ጸንቶ ይኑር::
✅ ቅዱስ ቴዎድሮስ ሰማዕት
✏በቤተ ክርስቲያን የሰማዕታት አለቅነት ከተሰጣቸው ሰማዕታት አንዱ የሆነው ማር ቴዎድሮስ የተወለደው በምድረ አንጾኪያ (ሶርያ) በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው:: አባቱ ዮሐንስ በትውልድ ግብጻዊ የሆነ ክርስቲያን ነው:: እናቱ ግን አስቸጋሪና ጣዖት አምላኪ ሶርያዊት ነበረች::
✏ባልና ሚስት አብረው ሲኖሩ ሚስት ባሏ ክርስቲያን መሆኑን አታውቅም ነበር:: ቴዎድሮስ (የእግዚአብሔር ስጦታ ማለት ነው) በተወለደ ጊዜ ግን ጠብ ተነሳ:: እሱ ክርስትና ለማስነሳት: ሚስት ደግሞ ወደ ጣዖት ቤት ለመውሰድ ተጋጩ:: ሚስት ወገኖቿ ባለስልጣኖች ናቸውና ልጁን ቀምታ ባሏን ዮሐንስን ወደ ግብጽ አሳደደችው::
✏ዮሐንስ በስደት ባለበት ሃገር ስለ ልጁ ፈጽሞ ይጸልይ: ያለቅስም ገባ:: እግዚአብሔር ደግሞ ልመናውን ሰማ:: ማር ቴዎድሮስ ወጣት በሆነ ጊዜ ማንም ሳይጠራው ወደ ቤተ ክርስቲያን ሔዶ ተማረ: ተጠመቀ:: ዕለት ዕለትም ጾምና ጸሎትን ከምጽዋት ጋር ያበዛ: ድንግልናውን ለመጠበቅ ይተጋ ነበር::
✏በዛው ልክ ደግሞ ገና በሃያ ዓመቱ በጉልበቱ ኃያል: በውበቱም ደመ ግቡ: በጠባዩም ገራገር ነበርና ተወዳጅ ነበር:: ነገሥታቱም የአንጾኪያ የጦር ሠራዊት አለቃ አድርገው ሾሙት:: እነሆ እስከ ዛሬ "የሠራዊት አለቃ" ተብሎ ይጠራል::
✏ማር ቴዎድሮስ በተሳተፈባቸው ጦርነቶች ሁሉ ተሸንፎ አያውቅም:: ይልቁኑ የነገሥታቱን (የጠላት) ልጆች በመማረክ ነው የሚታወቀው:: እንዲያውም አንድ ጊዜ ከአሕዛብ ጋር በተደረገ ጦርነት ብቻውን አሸንፏቸዋል::
✏የፋርስ ሰዎች ሊዋጉ ሲመጡ መልአክ ከሰማይ ወርዶ ሰይፍ ሰጠው:: ፋርሶችን "በከንቱ ከምትጠፉ ወደ ሃገራችሁ ተመለሱ" አላቸው:: እነርሱ ግን ተሳለቁበት:: ከፈረሱ ወርዶ ወደ ምስራቅ ዙሮ ጸልዮ በመስቀል አማተበ:: በመካከላቸው ገብቶም በመልአኩ ሰይፍ ለወሬ ነጋሪ ሳያስቀር አጠፋቸው::
✏አንድ ቀን ወደ አንድ ከተማ ቢገባ ዘንዶ ሲመለክ አገኘ:: ይባስ ብሎ የአንዲት ክርስቲያን ልጆችን ለመስዋዕትነት ሲያቀርቧቸው ተመለከተ:: በስመ ሥላሴ አማትቦ: በፈረሱ ላይም ተቀምጦ ዘንዶውን በጦር ገደለው:: የዘንዶውም ርዝመት ሃያ አራት ክንድ ነበር::
✏ከነገር ሁሉ በኋላ ቅዱስ ቴዎድሮስ ስለ አባቱ ወሬ ሰምቶ: ካለበት ሥፍራ አፈላልጎ አግኝቶ ደስ አሰኘው:: እስኪያርፍ አብሮት ቆይቶ: ቀብሮት ወደ አንጾኪያ ሲመለስ ግን የሚያሳዝን ነገር ጠበቀው::
ክርስቶስ ተክዶ: ጣዖት ቁሞ: አብያተ ክርስቲያናት ተቃጥለው: የክርስቲያኖች ደም ፈሶ:
ከተማዋ በግፍ ተሞልታ ተመለከተ:: እርሱም በዚያች ሰዓት መወሰን ነበረበትና አደረገው:: የሁሉ ሠራዊት አለቃ ቢሆንም የክብር ልብሱን አውልቆ: ባጭር ታጥቆ በንጉሡ ዲዮቅልጢያኖስ ፊት ቆመ::
✏ማር ቴዎድሮስ በአደባባይ እንዲህ ተናገረ:- "አንሰ አመልኮ ለክርስቶስ ንጉሠ ስብሐት በኩሉ ልብየ: ወእሠውዕ ሎቱ - እኔስ የክብር ባለቤት ክርስቶስን በፍጹም ልቤ አመልከዋለሁ: ለእርሱም ብቻ እሠዋለሁ::" ንጉሡ በቁጣ መሬት ላይ ጥለው እንዲደበድቡት አዘዘ:: ወታደሮቹ ደሙ እስኪንጠፈጠፍ ገረፉት::
✏በብዙ መክፈልተ ኩነኔ አሰቃይተው በእሳት አቃጠሉት:: እርሱ ግን በጸሎቱ እሳቱን ውኃ አደረገው:: ወታደሮቹ እርሱን በብዙ አሰቃዩ:: እርሱ ግን በእግዚአብሔር ኃይል ጸና: ታገሠ::
✏በመጨረሻም ጌታችን በግርማ ወርዶ "ወዳጄ ቴዎድሮስ ስምህን የጠራ: መታሠቢያህን ያደረገ: ገድልህን (ዜናህን) የጻፈ: ያጻፈ: ያነበበ: ገዝቶ በቤቱ ውስጥ ያኖረውን ሁሉ እምርልሃለሁ" አለው::
✏በስሙም ረድኤት እንደሚደረግ ነግሮት ዐረገ:: ወታደሮቹም በዚህ ቀን አንገቱን ሰይፈው የክብር አክሊልን ተቀብሏል:: እጅግ ብዙ ሺህ ሰዎችም አብረውት ተሰይፈዋል::
✥ ቸሩ ፈጣሪ ከሰማዕቱ በረከት ይክፈለን::
🚩ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.በዓታ ለእግዝእትነ ማርያም (በሰማንያ ዕለት)
2.ቅዱስ ወክቡር ማር ቴዎድሮስ ሰማዕት (የሠራዊት አለቃ)
3.ቅዱስ ጢሞቴዎስ ዘእስክንድርያ
4.አራት መቶ አራት ሰማዕታት (የቅዱስ ቂርቆስ ማኅበር)
5.ቅድስት አውስያ (የማር ቴዎድሮስ እናት - በልጇ ምክንያት ያመነች እናት ናት)
🚩ወርኀዊ በዓላት፦
1..ቅዱስ ዮሐንስ ሐፂር
2.ቅዱስ አክሎግ ቀሲስ
3.ቅዱስ አፄ ካሌብ ጻድቅ (ንጉሠ ኢትዮጵያ)
4.አባ አሞንዮስ ዘሃገረ ቶና
5.ቅድስት ሳድዥ የዋሒት
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
https://t.me/Sincsar
397
+ እምቢተኞች እናትና ልጅ +
--------***--------
ቅድስት ኢየሉጣ በሮም ግዛት በሚገኝ አንጌቤን በሚባል አገር በፈሪሃ እግዚአብሔር፣ በክርስትና ሃይማኖት እና በበጎ ምግባር ጸንታ ትኖር የነበረች ደግ ሴት ናት፡፡ በሥርዓት ያሳደገችው ቂርቆስ የሚባል ሕፃን ልጅም ነበራት፡፡ የንጉሡ ወታደሮችም እግዚአብሔርን እንዲክዱ፤ ለጣዖት እንዲሰግዱ ቅድስት ኢየሉጣንና ቅዱስ ቂርቆስን አስፈራሯቸው፡፡ ቅዱሳኑ ግን ሃይማኖታቸውን ለመለወጥ ፈቃደኛ አልኾኑም ክህደትን እምቢ አሉ፡፡ እምቢ የሰውን ልጅ ከብዙ መከራ ሊያወጣ የሚችል መፍትሔ ነው። እግዚአብሔሮን መካድ ለጣኦት መስገድን እምቢ ያሉ እምቢተኞች እናትና ልጅ ናቸው።
በዚህም መኰንኑ ተቈጥቶ በዓይንና በአፍንጫቸው ውስጥ ጨውና ሰናፍጭ በመጨመር፤ በጋሉ የብረት ችንካሮች በመቸንከርና መላ
ሰውነታቸውን በመብሳት በብዙ ዓይነት መሣሪያ አሠቃያቸው፡፡ እግዚአብሔርም የጋሉ ብረቶችን እንደ ውኀ ያቀዘቅዝላቸው፤ ሥቃያቸውንም ያቀልላቸው ነበር፡፡ አስባችሁታል ለጣኦት አንሰዋም አንክድም የሚል የእምነት ጥንካሬ ቢኖረን ስንኳ አፍንጫ ሲመታ ዓይን አስቀድሞ በሚያለቅሰው ሰውነታችን ጨውና ሰናፍጭ ሲጨመርበት ምን እንደምንሆን? እሾህ ሲነካን በሚንሰፈሰፈው የአካል ክፍላችን የጋለ ብረት ቢያገኘን ምን ልንሆን እንደምንችል?
በሌላ ጊዜም በገመድ አሳሥሮ ንጉሡ ሲያስጨንቃቸው ከቆየ በኋላ ራሳቸውን ከቆዳቸው ጋር አስላጭቶ እሳት አነደደባቸው፡፡ ጸጉራችንን ውሃ ሳይነካ ምላጭ በማያርፈው የእራስ ቅላችን ላይ ንጉሡ ጨክኖ ቆዳ ሲገፍ ይህን መቋቋም መቻል ከክርስቶስ ካልሆነ ከሰው የሚገኝ ሃይል አይደለም። ዳግመኛም ከትክሻቸው እስከ እግራቸው ድረስ በሚደርሱ ችንካሮች ቸነከራቸው፡፡ በዚህ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ ከሥቃያቸው አድኗቸዋል፡፡ ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰባቸውም፡፡
እንደ ገናም በመጋዝ ሰንጥቀው በብረት ምጣድ በቆሏቸው ጊዜ
ጌታችን ከሞት አነሣቸውና በመኰንኑ ፊት ድንቅ ተአምራትን አደረጉ፡፡ ከተአምራቱ መካከልም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ የመኰንኑን ጫማ በጸሎት ወደ በሬነት እንዲቀየር ማድረጉ ተጠቃሽ ሲኾን፣
መኰንኑ በተአምራቱ ተቈጥቶ የቅዱስ ቂርቆስን ምላስ አስቈርጦታል፤ ጌታችንም ምላሱን አድኖለታል፡፡
ዳግመኛም በፈላ የጋን ውኀ ውስጥ ቅዱሳን ቂርቆስና ኢየሉጣን ሊጨምሯቸው ሲሉ ቅድስት ኢየሉጣ በፈራች ጊዜ ቅዱስ ቂርቆስ ‹‹እናቴ ሆይ አትፍሪ፤ አናንያ፣ ዓዛርያና ሚሳኤልን ከእሳት ነበልባል ያዳናቸው እግዚአብሔር እኛንም ከዚህ የፈላ ውኀ ያድነናል›› እያለ ያረጋጋትና በተጋድሎዋ እንድትጸና ወደ እግዚአብሔር ይጸልይላት ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ሻወር እንደሚወስድ ሰው ተያይዘው ጋኑ ውስጥ ገቡ፡፡ ያ ውኀም እንደ ውርጭ ቀዘቀዘ፡፡
ስንት እናቶች ነን የመንግስተ ሰማይ መክፈቻ ሊሆኑ የሚችሉ ሕፃናትን ቢወለዱ አገር መሪ እንዲሁም ተወልደው ከዲቁና እስከ ጵጵስና ስልጣን ይዘው ቤተ መቅደስ የሚያገለግሉትን በመድኃኒት ያመከን? ምነው አንተን ከምወልድ መሃን ሆኜ በቀረሁ ነበር እያልን መውለዳችንን የምናማርር? ልጆችስ ብንሆን ከደሃ ቤተሰብ ተወልጄ ይኼን አይገዙልኝም እያልን በረንዳ ለበረንዳ የምንዞር ስንቶች ነን? ከክፉ ቤተሰብ ተወልጄ ኳስ ፊልም እንዳይ አይፈቅዱም እያልን ዜና የምንዘግብም አንጠፋም።
ምን አድርጋ ብታሳድገው ይሆን እናቱ ስትፈራ አይዞሽ ድፈሪ ብሎ ያረጋጋት? የትኞቻችን ወላጆች ነን ልጆች ያጸድቁናል ሰማያዊ አክሊል ያቀዳጁናል ብለን ጆሮ ሰጥተን የምናደምጣቸው? ቤት ውስጥ ሳይቀር እንዲያወሩ እድል አንሰጣቸውም። በሰንበት አንድ ቀን ከቤታችን አንድ የ6ዓመት ሕፃን በሌሊት ተነስታ ቤተ ክርስቲያን እንሂድ ተነሱ ብትለን መቼም ቤተ ክርስቲያን መመላለስ ለምዳ እንጂ ቤተ ክርስቲያን ሄደን ጸልየን እንድንጸድቅ "መንፈስ ቅዱስ አናገራት" አንልም እርግጠኛ ነኝ።
በመጨረሻም ከእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ተቀብለው በመንፈቀ ሌሊት አንገታቸውን ተቈርጠው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ በታመኑበት ተጋድሏቸውም ከእግዚአብሔር ዘንድ
የሕይወትን አክሊል ተቀብለዋል፡፡ 19/11/2015 ዓ/ም
ቤተ ክርስትያንን ለሚያፈርስ ኦርቶዶክሳውያንን ለሚገድል አላዊ ንጉሥ እጁን ታጥቦ ሊበለጽግ በሚፈሰው የሰው ልጅ ደም እንደዳንተባበር እምቢተኞች እንድንሆን እግዚአብሔር ይርዳን።
ምንጭ ሐምሌ 19 ስንክሳር
19/11/2015 ዓ/ም
397
🚩ወርኀዊ በዓላት፦
1.ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት
2.አቡነ ዓቢየ እግዚእ ጻድቅ
3.አቡነ ስነ ኢየሱስ
4.አቡነ ዮሴፍ ብርሃነ ዓለም
✥የቅዱስ ገብርኤል፣ ቅድስት ኢየሉጣ እና ቅዱስ
ቂርቆስ ጸሎታቸው፣ ምልጃቸው ይጠብቀን፡፡
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
https://t.me/Sincsar
397
✅ስንክሳር
🚩ሐምሌ 19
✅ቅዱስ ቂርቆስ እና ቅድስት ኢየሉጣ
✏ቅድስት ኢየሉጣ በሮም ግዛት በሚገኝ አንጌቤን በሚባል አገር በፈሪሃ እግዚአብሔር፣ በክርስትና ሃይማኖት እና በበጎ ምግባር ጸንታ ትኖር የነበረች ደግ
ሴት ናት፡፡ በሥርዓት ያሳደገችው ቂርቆስ የሚባል ሕፃን ልጅም ነበራት፡፡ ይህቺ ቅድስት የዘመኑን አረማዊ መኰንን እለእስክንድሮስን በመፍራቷ ከልጇ ጋር ከሮም ወደ ጠርሴስ በተሰደደች ጊዜ መኰንኑ እነርሱ ከሚገኙበት አገር ገብቶ ክርስቲያኖችን እያሳደደ መግደል ጀመረ፡፡
✏የንጉሡ ወታደሮችም እግዚአብሔርን
እንዲክዱ፤ ለጣዖት እንዲሰግዱ ቅድስት ኢየሉጣንና ቅዱስ ቂርቆስን አስፈራሯቸው፡፡ ቅዱሳኑ ግን ሃይማኖታቸውን ለመለወጥ ፈቃደኛ አልኾኑም ነበር፡፡
በዚህም መኰንኑ ተቈጥቶ በዓይንና በአፍንጫቸው ውስጥ ጨውና ሰናፍጭ በመጨመር፤ በጋሉ የብረት ችንካሮች በመቸንከርና መላ ሰውነታቸውን በመብሳት
በብዙ ዓይነት መሣሪያ አሠቃያቸው፡፡ እግዚአብሔርም የጋሉ ብረቶችን እንደ ውኀ ያቀዘቅዝላቸው፤ ሥቃያቸውንም ያቀልላቸው ነበር፡፡
✏በሌላ ጊዜም በገመድ አሳሥሮ ንጉሡ ሲያስጨንቃቸው ከቆየ በኋላ ራሳቸውን
ከቆዳቸው ጋር አስላጭቶ እሳት አነደደባቸው፡፡ ዳግመኛም ከትከሻቸው እስከ እግራቸው ድረስ በሚደርሱ ችንካሮች ቸነከራቸው፡፡ በዚህ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ ከሥቃያቸው አድኗቸዋል፡፡
✏በልዩ ልዩ የሥቃይ መሣሪያዎች ቢያስጨንቃቸውም የእግዚአብሔር ኃይልና የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት አልተለያቸውም ነበርና
ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰባቸውም፡፡ እንደ ገናም በመጋዝ ሰንጥቀው በብረት ምጣድ በቆሏቸው ጊዜ ጌታችን ከሞት አነሣቸውና በመኰንኑ ፊት ድንቅ
ተአምራትን አደረጉ፡፡
✏ከተአምራቱ መካከልም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ የመኰንኑን ጫማ በጸሎት ወደ በሬነት እንዲቀየር ማድረጉ ተጠቃሽ ሲኾን፣ መኰንኑ በተአምራቱ
ተቈጥቶ የቅዱስ ቂርቆስን ምላስ አስቈርጦታል፤ ጌታችንም ምላሱን አድኖለታል፡፡
✏ዳግመኛም በፈላ የጋን ውኀ ውስጥ ቅዱሳን ቂርቆስና ኢየሉጣን ሊጨምሯቸው ሲሉ ቅድስት ኢየሉጣ በፈራች ጊዜ ቅዱስ ቂርቆስ ‹‹እናቴ ሆይ አትፍሪ፤ አናንያ፣ ዓዛርያና ሚሳኤልን ከእሳት ነበልባል ያዳናቸው እግዚአብሔር እኛንም ከዚህ የፈላ
ውኀ ያድነናል›› እያለ ያረጋጋትና በተጋድሎዋ እንድትጸና ወደ እግዚአብሔር ይጸልይላት ነበር፡፡
✏ከዚህ በኋላ ተያይዘው ወደ ጋኑ ውስጥ ገቡ፡፡ ያ ውኀም እንደ ውርጭ ቀዘቀዘ፡፡ ደግሞም ወታደሮቹ መንኰራኵር ባለበት የብረት ምጣድ ውስጥ
አስገብተው ሥጋቸው እስኪቈራረጥ ድረስ በጎተቷቸው ጊዜ ቅዱስ ገብርኤል አድኗቸዋል፡፡
✏በመጨረሻም ከእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ተቀብለው በመንፈቀ ሌሊት አንገታቸውን ተቈርጠው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ እስከ ሞት ድረስ በታመኑበት
ተጋድሏቸውም ከእግዚአብሔር ዘንድ የሕይወትን አክሊል ተቀብለዋል፡፡
✏በአጠቃላይ ቅዱስ ቂርቆስና ቅድስት ኢየሉጣ የዚህን ዓለም ጣዕም በመናቅ ‹‹ሞት ቢኾን፣ ሕይወትም ቢኾን፣ መላእክትም ቢኾኑ፣ ግዛትም ቢኾን፣ ያለውም ቢኾን፣ የሚመጣውም ቢኾን፣ ኃይላትም ቢኾኑ፣ ከፍታም ቢኾን፣ ዝቅታም ቢኾን፣ ልዩ ፍጥረትም ቢኾን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ
ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቼአለሁ፤›› (ሮሜ. ፰፥፴፰-፴፱) በማለት ቅዱስ ጳውሎስ የተናገረውን ቃል በተግባር በማሳየት ለክርስቶስ ፍቅር ሲሉ ራሳቸውን ለመከራና ለሞት አሳልፈው ሰጥተዋል፡፡
✏ቅዱሳኑ ተጋድሏቸውን እስኪፈጽሙ ድረስም ቅዱስ ገብርኤል አልተለያቸውም፡፡ በቅዱስ ገብርኤል
ተራዳኢነት ቅድስት ኢየሉጣና ቅዱስ ቂርቆስ ብቻ ሳይኾኑ ብዙ ምእመናንም ተጠቅመዋል፡፡ ስሙ በሚጠራባቸው ገዳማትና አድባራት መልአኩ የሚያደርጋቸው ድንቅ ድንቅ ተአምራት ለዚህ ማስረጃዎች ናቸው፡፡ ይህም ቅዱሳን መላእክት
በእግዚአብሔር ስም መከራ የሚቀበሉ ምእመናንን እንደሚጠብቁና ከልዩ ልዩ ደዌ እንደሚፈውሱ የሚያስረዳ ታሪክ ነው፡፡
✏እኛም በሃይማኖታችን ምክንያት መከራ ባጋጠመን ጊዜ ቈራጥ ልብ ያለው ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ‹‹እናቴ ሆይ አትፍሪ›› እያለ እናቱን በመከራ እንድትጸና እንዳረጋጋትና ለሰማዕትነት እንድትበቃ እንዳደረጋት ዅሉ፣ ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔርን መንግሥት በአንድነት ለመውረስ እንድንችል ‹‹አይዞህ! አይዞሽ! አትፍራ! አትፍሪ›› በመባባል በዚህ ዓለም የሚገጥመንን መከራ ታግሠን፣ እስከ ሞት ድረስ በሃይማኖታችን ጸንተን መኖር ይገባናል፡፡
✏ክርስትና ለብቻ የሚጸደቅበት መንገድ ሳይኾን በጋራ ዋጋ የሚያገኙበት የድኅነት በር ነውና፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም ቅዱስ ቂርቆስንና ቅድስት ኢየሉጣን የተራዳው የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል
በአማላጅነቱ እንዲጠብቀን ‹‹በተአምኖ ንሴፎ ትንባሌ ዚአከ መዓልተ ወሌሊተ፤ በእግዚአብሔር ታምነን በቀንም በሌሊትም የአንተን ልመና ተስፋ እናደርጋለን ›› እያልን ዘወትር ልንማጸነው ያስፈልጋል፡፡
✏እርሱ ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር በተሰጠው ቃል ኪዳን መሠረት ከሚደርስብን ልዩ ልዩ መከራና ሥቃይ ያድነናልና፡፡ ‹‹የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙርያ ይሠፍራል፤ ያድናቸውማል፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፴፬፥፯)፡፡ ይህን እንድናደርግም
የቅዱሳን ተራዳኢነት አይለየን፡፡
✅ቅዱስ በጥላን ጠቢብ
✏ቅዱሱ ከአሕዛብ ወላጆቹ ተወልዶ: ያደገውም በጣዖት አምልኮ ነው:: በሙያው እጅግ የተመሠከረለት ሐኪም ነበር:: የሃገሩ ሰዎች "ጠቢብ" እያሉም ይጠሩታል:: በጥላን ምንም ጣዖት አምላኪ ቢሆን በተፈጥሮው ተመራማሪና ቅን ነበር::
✏አንድ ካህንም በጐረቤቱ ነበርና ዘወትር ስለ ሃይማኖት ይከራከሩ ነበር:: ካህኑ ሌሊት ሌሊት ስለ በጥላን ተግቶ ይጸልይ ነበርና ተሳክቶለት አሳመነው::
✏አንድ ቀን በጥላን መንገድ ሲሔድ እባብ ሰው ነድፎ ለሞት ደርሶ አየውና ጸሎት አድርሶ ስመ ክርስቶስን ቢጠራ የተነደፈው ድኖ እባቡ ሞተ::
✏በዚህ ተዓምር ደስ ብሎት ወደ ካህኑ ሒዶ ተጠመቀ:: ከዚያም ጾም ጸሎትን ጀመረ:: በየቦታው እየዞረ ሕሙማንን እንደ ቀድሞው በመድኃኒት ሳይሆን በጸሎት ያድናቸው ነበር:: ስላዳናቸውም በርካቶቹ ወደ ክርስትና መጡ::
✏የአካባቢው ሰው: ወላጆቹን ጨምሮ ክርስቲያኖች ሆኑ:: በመጨረሻም ቅዱስ በጥላን: ቤተሰቦቹ: ካህኑና ከደዌ የዳኑት ወገኖቹ በአካባቢው ጣዖት አምላኪ ንጉሥ ፊት ቀርበው ክርስቶስን ሰብከው በሰማዕትነት ዐርፈዋል::
✅ቅዱሳን ሰማዕታተ እስና
✏እስና ማለት ግብጽ ውስጥ የምትገኝ የቀድሞ አውራጃ ናት:: በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን በከተማዋ በርካታ ክርስቲያኖች ይኖሩ ነበር:: የእንዴናው መኮንን መጥቶ "ክርስቶስን ካዱ: ለጣዖት ስገዱ" አላቸው:: ሕዝቡ በአንድ ድምጽ መለሱ:- "ይሕማ ፈጽሞ ሊደረግ አይችልም::" መኮንኑ ተቆጥቶ "ሁሉንም ግደሉ" አለ::
✏ወታደሮቹ ሰው አልመረጡም:: ከታዘለ ሕፃን አልጋ ላይ እስካለ ሽማግሌ: ከጤነኛ እስከ ሕመምተኛ: ሁሉንም ጨፈጨፏቸው:: ከተማዋ በደም ተነከረች:: ከከተማዋ ክርስቲያኖች ወሬ ለመንገር አንድ ሰው እንኳ አልተረፈም:: ሁሉም ስለ ክርስትና ደማቸውን አፈሰሱ::
✏ጌታችን ስለ ሰማዕታቱ ብሎ: ደማቸውንም አስቦ በሃይማኖታችን ያጽናን:: ከመከራም ይሰውረን:: በረከታቸውንም ያድለን::
🚩ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት
2.ቅዱስ ቂርቆስ ወእሙ ኢየሉጣ
3.ቅዱስ በጥላን ጠቢብ ሰማዕት እና ማኅበሩ
4.ቅዱሳን ሰማዕታተ እስና
397
✅ስንክሳር
🚩ሐምሌ 18
✅ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ
✏"ሰላም ለያዕቆብ እኍሁ ለእግዚእነ በሥጋ ዘቀደመ ተሠይሞ ውስተ አብያተ ክርስቲያናት ወተጰጰሰ እምኀበ ሐዋርያት"። ትርጉም፦ ከሐዋርያት ጵጵስናን
የተቀበለ በአብያተ ክርስቲያናት ውስጥ መሾሙ የቀደመ በሥጋ ዝምድና የጌታችን ወንድም ለኾነ ለቅዱስ ያዕቆብ ሰላምታ ይገባል። ሊቁ አባ ጊዮርጊስ
በተአምኆ ቅዱሳን ላይ።
✏የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ የጌታን ወንድም ቅዱስ ያዕቆብ፦ ይህም ቅዱስ የጠራቢው የዮሴፍ ልጅ ነው። እርሱም ከልጆቹ ሁሉ የሚያንስ ነበር። እርሱም
ንጹሕ ድንግል ነበር ከጌታችንም ጋራ አደገ ስለዚህም ክብር ይግባውና የጌታችን ወንድም ተባለ። ከጌታችን ዕርገትም በኋላ ሐዋርያት በኢየሩሳሌም ላይ ኤጲስቆጶስ አድርገው ሾሙት። ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አስተምሮ ብዙዎችን ወደ ቀናች ሃይማኖት መለሳቸው የክርስትና
ጥምቀትንም አጠመቃቸው። እግዚአብሔር በእጁቹ ታላቅ ድንቆችንና ተአምራቶችን አደረገ።
✏በአንዲት ዕለትም በጎዳና ሲጓዝ አንድ ሽማግሌ አገኘ። ቅዱስ ያዕቆብም "ሽማግሌ ሆይ በቤትህ ታሳድረኛለህን" አለው። አረጋዊውም እሺ እንዳልክ
ይሁን አለ በአንድነትም ሲጓዙ ጋኔን ያደረበት ሰው አገኘው በአየውም ጊዜ የክርስቶስ "ሐዋርያ ሆይ እኔ ካንተ ጋር ምን አለኝ ልታጠፋኝ መጣህን" ብሎ
ጮኸ። ሐዋርያውም "በናዝሬቱ ኢየሱስ ስም ተዘጋ ከሰውዬውም ውጣ" አለው። ወዲያውም ያ ጋኔን ከሰውዬው ወጣ።
✏ያ ሽማግሌም ይህን ድንቅ ተአምር አይቶ ደነገጠ ከሐዋርያው እግር በታችም ወድቆ እንዲህ አለው "ወደ ቤቴ ልትገባ አይገባኝም ነገር ግን እድን ዘንድ ቤተሰቦቼም ሁሉ ይድኑ ዘንድ ምን ላድርግ" አለ ያን ጊዜም ሐዋርያው "አቤቱ ጌታዬ ሆይ መንገዴን አሳምረህልኛልና አመሰግንሃለሁ" ብሎ ጌታችንን አመሰገነው። ወደ ሽማግሌውም ተመልሶ "የድኅነትን ነገር ነገረው ክብር ይግባውና ስለጌታችን
ሰው መሆን ስለ መከራው ስለ ሞቱና ስለ መነሣቱ አስተማረው።
✏ከዚህም በኋላ ያ ሽማግሌ ሐዋርያውን ወደ ቤቱ አስገባው ቤተ ሰቦቹም ሁሉ ወደርሱ ተሰበሰቡ ቅዱስ ያዕቆብም አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው። ሥጋውንና ደሙንም አቀበላቸው። የከተማው ሰዎችም በሰሙ ጊዜ በሽተኞችን ሁሉ ወደርሱ አመጡ ሁሉንም አዳናቸው ለእነርሱም
ሃይማኖትን አስተምሮ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው። ቀሳውስትንና ዲያቆናትንም ሾመላቸው ያንን ሽማግሌም ኤጲስቆጶስ አድርጎ
ሾመው ክብር ይግባውና የጌታችንንም ወንጌል ሰጣቸው ከዚህም በኋላ ያስተምር ዘንድ ወደ ሌሎች አገሮች ወጥቶ ሔደ።
✏አንዲት መካን ሴት ነበረች እግዚአብሔር ልጅን ይሰጣት ዘንድ ዘንድ ስለእርሷ እንዲጸልይላት ቅዱስ ያዕቆብን ለመነችው። እርሱም ጸለየላትና ወንድ ልጅን
ወለደች ስሙንም ያዕቆብ ብላ ጠራችው ልጅዋንም ተሸክማ ወደ ሐዋርያው መጥታ ሰላምታ አቀረበችለት ከልጅዋም ጋር ከእርሱ ተባረከች።
✏ከዚህም በኋላ በአንዲት ቀን ብዙዎች አይሁድ ወደርሱ ተሰብስቡ ስለ ጌታ ስለ ኢየሱስ የማን ልጅ እንደሆነ ይነግራቸው ዘንድ ጠየቁት እነርሱ እርሱ ጌታን የዮሴፍ ልጅ እንደሆነ እርሱም ወንድሙ እንደሆነ እንደሚነግራቸው አስበው ነበርና። ቅዱስ ያዕቆብም ሦስተኛ ደርብ ላይ ወጥቶ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነም ከአብ ጋራም ትክክል እንደሆነ ይገልጽላቸው ጀመረ። ይህንንም በሰሙ ጊዜ እጅግ ተቈጡ ከደርቡ ላይ አውርደው የጸና ግርፋትን ገረፉት ከእነርሱም ውስጥ የልብስ ማጠቢያ የዕንጨት ገበታ የያዘ አንድ ሰው መጣ በዚያ ዕንጨትም ቅዱስ ያዕቆብን ራሱ መታው ያን ጊዜ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ።
✏ስለእርሱም ወይን እንዳልጠጣ ደም ካለው ወገን እንዳልበላ በራሱም ላይ ምላጭ እንዳልወጣ በውሽባ ቤት እንዳልታጠበ ሁለት ልብስንም እንዳልለበሰ
ሁልጊዜም እንደሚቆምና እንደሚሰግድ ተጽፎአል። ከመቆም ብዛት የተነሣም እግሮቹ አብጠው ነበር ከዚህም በኋላ ሐምሌ 18 ቀን ዐረፈና በቤተ መቅደሱ
ጎን ቀበሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘለዓለሙ አሜን።
✏የቊልዝም ከተማ የሆነው ቅዱስ አትናቴዎስ፦ ይህም ቅዱስ ከነገሥታት ወገን ነበር በሃይማኖት ጸና ነበረ። እኒህ ከሐድያን ነገሥታት ዲዮቅልጥያኖስምና መክስምያኖስ የጣዖታትን አምልኮ በዓወጁ ጊዜ ይህ
አትናቴዎስን ለግብጽ አገር ገዥ አድርገው ሾሙት አብያተ ክርስቲያናትንም እንዲፈርስ አዘዘት። እርሱም ግን ወደ ግብጽ በደረሰ ጊዜ ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ሒዶ
በረከትን ተቀበለ እርሱም ክርስቲያን እንደሆነ ነገረው በእርሱም ደስ አለው።
✏ንጉሡም በሰማ ጊዜ ይዞ ይመረምረው ዘንድ ሌላ መኰንን ላከ። መኰንኑም በደረሰ ጊዜ ተገናኘውና "የአማልክትን ፍቅር ለምን ተውክ" አለው።
አትናቴዎስም እንዲህ ብሎ መለሰለት "እኔ ከታናሽነቴ ጀምሬ ክብር ይግባውና የክርስቶስ ነኝ የቀናች ሃይማኖቴንም አልተውም"። መኰንኑም "የንጉሥን
ትዕዛዝ የሚለውጥ ሁሉ ቅጣት እንዲአገኘውና በጽኑ ሥቃይ እንዲሠቃይ አታውቅምን" አለው።
✏ቅዱስ አትናቴዎስም እንዲህ አለው "አንተ ሰነፍ በአንተ ላይና በንጉሥህ ላይ ቸር ሰጭ እግዚአብሔርን በሚጠላ በአባትህ ሠይጣን ላይ የሚመጣው
የዘላለም ሥቃይን እስከምታይ ጥቂት ታገሥ" አለው። መኰንኑም በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ ራሱንም በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ። ቅዱስ አትናቴዎስም ነፍሱን
ከቅዱሳኑ ጋራ እንዲያሳርፍ ከቤተ ክርስቲያንም መከራን እንዲያርቅ የሮምንና የአኵስምን የክርስቲያን መንግሥት እንዲያጸና ወደ እግዚአብሔር ጸለየ
ጸሎቱንም በፈጸመ ጊዜ በርከክ ብሎ ሰገደ ጭፍሮችም ራሱን በሰይፍ ቆረጡ።ምእመናንም ሥጋውን ወስደው ቀበሩት። ከመቃብሩም ቁጥር የሌላቸው ተአምራት ተገለጡ።
✥ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ አትናቴዎስ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
397
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
https://t.me/Sincsar
397
✅ስንክሳር
🚩ሐምሌ 17
✅ቅድስት አውፎምያ ሰማዕት
✏እናታችን # ቅድስት አውፎምያ በ3ኛው መቶ
ክ/ዘመን ከነበሩ ወጣት ክርስቲያኖች አንዷ ናት:: ገና ከልጅነቷ ልቧ በፍቅረ ክርስቶስ የተነደፈ
ነበር::በዚህም ምክንያት ራሷን በጾምና በጸሎት ወስና ትኖር ነበር:: እድሜዋ ገና በአሥራዎቹ
ቢሆንም በመንኖ ጥሪት መኖር ምርጫዋ ነበር:: ሊቃውንት አበው ከሰማዕትነቷ ደርበው
"ጻድቅት አውፎምያ" እያሉም ይጠሯታል::
✏አንድ ቀን ግን መንገድ ወጥታ ነበርና ክርስቲያኖች ሲሰቃዩ ተመለከተች:: ምንም ጥፋት
ሳይገኝባቸው ክርስቶስን ስላመለኩ ብቻ ይሙት በቃ ተፈርዶባቸው ሊገደሉ እየተወሰዱ
ነበር:: አሕዛብ ግብራቸው የአውሬ ነውና ርሕራሔ የላቸውም:: ሰማዕታቱ ደማቸው
በየመንገዱ እየፈሰሰ ጥቁር ሰንሰለት በአንገታቸው: በእጃቸውና በእግራቸው ላይ አድርገው
ይጐትቷቸው ነበር::
✏ቅድስት አውፎምያ የተደረገውን ሁሉ ተመልክታ አምርራ አለቀሰች:: ፈጠን ብላም ወደ
መኮንኑ ቀርባ ገሰጸችው:: "አንተ አእምሮ የጎደለህ! እንዴት ክርስቲያኖችን እንዲህ
ታሰቃያለህ? አምላካቸው # ጌታ_ክርስቶስ ታጋሽ ባይሆን ኑሮ በቅጽበት ከገጸ ምድር
ባጠፋህ ነበር" አለችው::
✏በድፍረቷ የተገረመው መኮንኑ "አንቺስ ማንን ታመልኪያለሽ?" ሲል ጠየቃት:: እርሷም
"ሰማይና ምድርን የፈጠረውን: ስለ እኛ ሲል በቀራንዮ አንባ የተሠዋውን # ኢየሱስ
ክርስቶስን አመልካለሁ" ስትል መለሰችለት:: በዚያች ሰዓት የመኮንኑ ቁጣ በቅድስቷ ላይ
ነደደ::
✏ነገር ግን ቁጣውን ከቁም ነገር አልቆጠረችውምና እንዲያሰቃዩዋት አዘዘ:: ወታደሮቹ
ሥጋዋን በብዙ አሰቃዩ:: ብላቴናዋ አውፎምያ ግን ጽንዕት ናትና አልቻሏትም:: በመጨረሻ
በእሳት ተቃጥላ ትሞት ዘንድ ተፈረደባት::
✏እሳቱ ከመሬት ከፍ ባለ ጊዜ ወደ ውስጥ ወረወሯት:: በእሳቱ መካከል ቁማ ለረዥም ጊዜ
ጸለየች:: ከዚያም ነፍሷን አሳልፋ ሰጠች:: ምዕመናን በክብር ገንዘው ቀብረዋታል::
✅ቅዱስ እስጢፋኖስ
✏ቅዱስ እስጢፋኖስ የተወለደው በኢየሩሳሌም በምትገኝ ሐኖስ በተባለች ቦታ ነው። አባቱ
ስምዖን ሲባል እናቱ ደግሞ ሐና ትባላለች ነገዱ ከነገደ ብንያም ነው። የኦሪትን ሕግና ሥርዓት
ከኦሪቱ ምሁር ከገማልያል ተምሯል። በሐዋርያት ሥራ ምዕ. 6 እንደምናነበው ሕዝቡን
በማዕድ ያገለግሉ ዘንድ ሰባት ዲያቆናት ተመርጠዋል ከእነዚህ መካከል ቅዱስ እስጢፋኖስ
አንዱ ሲሆን ለስድስቱ ዲያቆናት ደግሞ አለቃ( ሊቀ ዲያቆን) ሆኖ ተሹሟል ይህም የሆነው
በጥቅምት 17 ነው።
✏የስሙ ትርገጓሜ ወደብ ጸጥታ ማለት ሲሆን ቁጥሩ ከ 72ቱ አርድዕት ነው፤ ለምን ቀዳሚ
ሰማዕት ተባለ ከሱ በፊት ሰማዕታት የሉም ነበርን ? ቢሉ መኖርስ አሉ የእርሱ ግን ቀዳሚ
መባሉ ከጌታችን እርገት በኃላ ስለ ጌታችን መውረድ መወለድ መስክሮ የሞተ የመጀመሪያው
እርሱ ስለሆነ ነው፤ እሺ ለምንስ ሊቀ ዲያቆናት ተባለ ቢሉ በሐዋርያት እጅ ከተሾሙት ሰባቱ
ዲያቆናት ውስጥ የሁሉም አለቃ እርሱ ስለሆነ ነው ሐዋ 6፥5።
✏መጽሐፍ ቅዱስ ስለ እስጢፋኖስ እንዲህ ሲል በእውነት መሰከረ "እስጢፋኖስም ጸጋንና
ኃይልን ተሞልቶ በሕዝቡ መካከል ድንቅንና ታላቅ ምልክትን ያደርግ ነበረ...ፊቱም የመልአክ
ፊት ይመስል ነበር ፤ ይናገርበት የነበረውን ጥበብና መንፈስ ይቃወሙ ዘንድ አልቻሉም ሐዋ
6፥8 ።
✏አይሁድ አማፂያን መልስ መስጠት ቢያቅታቸው ድንጋይ አነሱ ልብ አናቱን እያሉ ወገሩት፤ ቀና ብሎ ቢመለከት ቅድስት ሥላሴን አየ፤ አቤቱ ይህን ኃጢያት አትቁጠርባቸው ይቅር በላቸው እያለ ነፍሱን ሰጠ። ሐዋ ፯፥፷ ቅዱስ እስጢፋኖስ በማዕድ አገልግሎት ሕዝቡን ከማገልገሉ በተጨማሪ ወንጌልን ይሰብክ
ነበር ተአምራትን የማድረግ ጸጋም ተሰጥቶት ነበር በዚህም አገልግሎቱ ብዙዎችን ወደ ክርስትና መልሷል።
✏በዚህም አይሁድ በቅናት ተነሳስተው በሐሰት ከሰሱት ከከተማውም ወደ
ውጭ አውጥተው ቄዳር በተባለ ቦታ በድንጋይ ወገሩት በሚወግሩትም ጊዜ ሰማያት
ተከፍተው ምሥጢረ ሥላሴን (እግዚአብሔርን በሦስትነቱ ) ተመለከተ ኢየሱስ ክርስቶስንም
በአብ ቀኝ ተቀምጦ አየ ለሚወግሩትም ሰዎች ከአምላኩ እንዲህ በማለት ምሕረትን ለመነ
"ጌታ ሆይ ይህንን ኃጢአት አትቁጠርባቸው "በመጨረሻም "ጌታ ኢየሱስ ሆይ ነፍሴን
ተቀበል" ብሎ ነፍሱን ሰጠ። የሐዋርያት ሥራ ምዕ 7 በተወለደ በ 30 ዓመቱ በ35 ዓ.ም
በሰማዕትነት ዐረፈ።
✅ቅዱስ ዮናስ ነቢይ
✏በቤተ ክርስቲያን አስተምሕሮ ከ12ቱ # ደቂቀ_ነቢያት አንዱ የሆነው # ቅዱስ_ዮናስ
ከክርስቶስ ልደት 800 ዓመታት በፊት እንደ ነበረ ይታመናል:: # ሊቃውንት እንዳስተማሩን
ደግሞ እናቱ # ቅዱስ_ኤልያስን የመገበችው የሰራፕታዋ መበለት ናት:: ቅዱስ ዮናስ ገና
ሕጻን ሳለ በእሥራኤል ምድር ዝናብ ለ3 ዓመታት ከ6 ወራት ተከልክሎ ነበር::
✏ይሕንንም ያደረገው ደጉ ነቢይ ኤልያስ ለአምልኮተ እግዚአብሔር ቀንቶ ነው:: በወቅቱ
ኤልያስ በሰራፕታ ሳለ ሕጻኑ ዮናስ ታሞ ሞተ:: ልጇ የሞተባት መበለትም ኤልያስን
ለመነችው:: ኤልያስም ወደ ፈጣሪው ማልዶ ሕጻኑን ዮናስን ከሞት አስነስቶታል:: ትንሽ ከፍ
ባለ ጊዜም ከጉዋደኞቹ (ከነቢያቱ) # አብድዩና # ኤልሳዕ ጋር ሆነው ታላቁን ነቢይ ኤልያስን
ተከትለውታል::
✏ኤልያስ ካረገ በሁዋላ ሁሉም በየተሰጣቸው አገልግሎት ተሠማርተዋል:: ቅዱስ ዮናስን
# እግዚአብሔር "ወደ ነነዌ ሒደሕ ንስሃን ስበክ" አለው:: ዮናስ ግን የፈጣሪውን መሐሪነት
ጠንቅቆ ያውቃልና አልሔድም አለ:: (ተመልከቱ የየዋሕነት ብዛት)
✏እግዚአብሔር እየደጋገመ እንዲሔድ ሲነግረው ነቢዩ "እንዲሕ የሚዘበዝበኝ ከፊቱ
ብቀመጥ አይደል" ብሎ ሊኮበልል ወጣ:: ነገር ግን አልቀናውም:: በእርሱ ምክንያት ማዕበል
ተነሳ:: ሕዝቡም ሊያልቁ ሆነ:: ከእንቅልፉ የነቃው ዮናስ ከመርከቡ ላሉት አሕዛብ አምልኮተ
እግዚአብሔርን ሰብኮላቸው: በእርሱ ጠያቂነት ሐምሌ 15 ቀን ወደ ባሕር ጥለውታል::
✏አሣ አንበሪም ተቀብሎታል:: በግዙፉ አሣ ውስጥም ያለ እንቅልፍ በጾም: በጸሎትና
በምስጋና 3 ለቀን ቆይቷል:: ሙስና ሳያገኘውም በዚህች ቀን አሣ አንበሪው # ነነዌ ዳር ላይ
ተፍቶታል:: ቅዱስ ዮናስ እግዚአብሔር እንዳዘዘው "እስከ ሠሉስ ዕለት ትትገፈታእ ነነዌ ዓባይ
ሃገር" /እስከ ሦስት ቀን ድረስ ነነዌ ትገለበጣለች (ዮናስ 3:4)/ ብሎ አሰምቶ ሰበከ::
✏የነነዌ ሰዎችም በስብከተ ዮናስ አምነው: ንስሃም ገብተው ድነዋል:: በዚህም ጌታችን
በወንጌል ላይ አመስግኗቸዋል:: ቅዱስ ዮናስ መኮብለሉ # በሐዲስ_ኪዳን ለሚደረገው
ምስጢረ ትንሳኤ ጥላ (ምሳሌ) ነውና ይደነቃል:: (ማቴ. 12:38) ነቢዩ ግን በተረፈ ሕይወቱ
ሕዝቡን ሲያስተምር: ፈጣሪውን ሲያገለግል ኑሮ በመልካም ሽምግልና ዐርፏል::
🚩ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.ቅዱስ ዮናስ ነቢይ (ከአሣ አንበሪ ሆድ የወጣበት)
2.ቅድስት አውፎምያ (ጻድቅትና ሰማዕት)
3.ቅዱስ ዮስጦስ ሰማዕት (ታላቁ)
4.ቅዱስ ዘካርያስ
🚩ወርኀዊ በዓላት፦
1.ቅዱስ እስጢፋኖስ ሊቀ ዲያቆናት (ቀዳሜ ሰማዕት)
2.ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ (ወልደ ዘብዴዎስ)
3.ቅዱሳን አበው መክሲሞስና ዱማቴዎስ
4.አባ ገሪማ ዘመደራ
5.አባ ዸላሞን ፈላሢ
6.አባ ለትጹን የዋህ
7.ቅዱስ ኤዺፋንዮስ ሊቅ (ዘደሴተ ቆዽሮስ)
