ስንክሳር
Open in Telegram
#ስንክሳር የቴሌግራም ቻናላችንን ይከታተሉ። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ዶግማ ቀኖና ስርአትና ትውፊትን በጠበቀ መልኩ የእለቱ ስንክሳር ላይ የተጻፉ የጻድቃን፣ የሰማዕታት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት፣ የቅዱሳን አበው መነኮሳት፣ የቅዱሳት አንስትና የደናግላን ገድላቸው ይዘከርበታል:: 👇ይህ ቻናል ለሌሎችም እንዲደርስ #Share #ሼር አድርጉ! ◈ https://t.me/Sincsar
Show more397
Subscribers
No data24 hours
No data7 days
No data30 days
Posts Archive
397
“ድንግል ሆይ! ባማረ በተወደደ ነገር ሁሉ መሰልኹሽ ምስጋናሽን ግን ለመፈፀም አልቻልኩም፡፡ እግዚአብሔርን ባመሰገንሁ ጊዜ ባንቺ ለስሙ ምስጋና አቀርባለሁ፤ በስምሽም ጸሎቴን በጸለይሁ ጊዜ ጸሎቴን ለልጅሽ አቀረብሁ፤ ዳግመኛም ውዳሴሽን ወደማወቅ ባህር ልዋኝ ወደድሁ፣ ወደ ክብርሽ ገናንነት ወደብ እደርስ ዘንድ ደከምሁ፣ ያንዲቷን ማእበል ሞገድ ያህል ስንኳን አላለፍሁም። ወደ ጽርሐ አርያም ጠፈር ለመድረስ የሚቻለው ማነው? ከምድር በታች ወዳለው ባሕር መሠረትስ መዋኘት ማን ይችላል? ድንግል ሆይ! ክብርሽን ገናንነትሽን ጠንቅቆ መናገር የሚቻለው ማነው?''
#ቅዱስ_አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ
397
“ስለ መተላለፋችን ምንም ዓይነት ቅጣት የማንቀበል ብንሆን ኖሮ እግዚአብሔር ኅሊናን የሚያህል ፈራጅ ዳኛ በውስጣችን አይፈጥርም ነበር፡፡”
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
397
✅ስንክሳር
🚩ነሐሴ 26
✅አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ
✏️አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ የተወለዱት ጐንደር : የድሮው ስማዳ (ዳኅና) አካባቢ ሲሆን ወላጆቻቸው ዘክርስቶስና እግዚእ ክብራ ይባላሉ:: የተወለዱት በ1210 ዓ/ም ነው:: ነገር ግን አንዳንድ ምንጮች በ1196 ዓ/ም ያደርጉታል::
✏️ጻድቁ ከክርስቲያን ወላጆቻቸው ጋር እንደሚገባ አድገዋል:: በልጅነታቸው በብዛት ወላጆቻቸውን ያግዙ ነበር:: በትርፍ ጊዜአቸው ደግሞ ትምሕርተ ሃይማኖትንና ሥርዓቱን ያጠኑ ነበር:: በ1240 ዓ/ም ግን (ማለትም 30 ዓመት ሲሞላቸው) ይሕቺን ዓለም ይተዋት ዘንድ አሰቡ::
✏️አስበውም አልቀሩ ፈጣሪን እየለመኑ ደብረ ዳሕሞ ገቡ:: በወቅቱ ዳሞ የትምሕርት : የምናኔ ማዕከል ከመሆኑ ባሻገር የአቡነ አረጋዊ 5ኛ የቆብ ልጅ ካልዕ ዮሐኒ ነበሩና የእርሳቸው ደቀ መዝሙር ሆኑ::
✏️አቡነ ኢየሱስ ሞዐ በደብረ ዳሞ በነበራቸው ቆይታ ቀን ቀን ሲታዘዙ : ሲፈጩ : ውሃ ሲቀዱ ውለው ሌሊት እኩሉን በጸሎት በስግደትና የቀረውን ሰዓት ደግሞ ቅዱሳት መጻሕፍትን በመገልበጥ አሳለፉ::
✏️በመጨረሻም ልብሰ ምንኩስናን ለበሱ:: ይህን ጊዜ 37 ዓመታቸው ሲሆን ዘመኑም 1247 ዓ/ም ነው:: ወዲያውም በዳሞ ሳሉ መልአከ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ተገልጦ "ወደ ወሎ ሐይቅ ሒድ : ብዙ የምትሠራው አለና" አላቸው::
✏️በአንዴም ከዳሞ (ትግራይ) ነጥቆ ሐይቅ እስጢፋኖስ (ወሎ) አደረሳቸው:: በዚያም ለ7 ዓመታት በዼጥሮስ ወዻውሎስ ቤተ መቅደስ በተጋድሎ : በስብከተ ወንጌል : በማዕጠንትና ሐይቁ ውስጥ ሰጥሞ በመጸለይ ኖሩ::
✏️ቅድስናቸውን የተመለከቱ አበውም በግድ አበ ምኔት አድርገው ሾሟቸው:: ይህ ነው እንግዲህ በኢትዮዽያ ቤተ ክርስቲያን ላይ ትልቁ መሠረት የተጣለበት አጋጣሚ:: ነገሩ እንዲህ ነው:-
✏️ስም አጠራሯ የከፋ ዮዲት ጉዲት ለ40 ዓመታት ሃገሪቱን እንዳልነበረች ብታደርጋት ክርስትና ተዳከመ:: ባዕድ አምልኮም ነገሠ:: አቡነ ኢየሱስ ሞዐ (ትርጉሙ ኢየሱስ ክርስቶስ አሸነፈ ማለት ነው) ደግሞ ሃይማኖታቸው የቀና ከ800 በላይ ክርስቲያኖችን ሰበሰቡ::
✏️በሃገሪቱ ትልቅና የመጀመሪያው ሊባል የሚችል ቤተ መጻሕፍት አደራጁ:: እነዚያን አርድእት በቅድስናና በትምሕርት አብስለው አመነኮሱና "ሒዱ! ሃገሪቱን ታበሩ ዘንድ ተጋደሉ" ብለው አሰናበቷቸው::
✏️ክእነዚህ መካከልም ታላላቁን አቡነ ተክለ ሃይማኖትን: አቡነ በጸሎተ ሚካኤልን እና የሁዋላውን ፍሬ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫን መጥቀስ እንችላለን:: በዚህም ምክንያት ጻድቁ "ወላዴ አእላፍ ቅዱሳን - አእላፍ ቅዱሳንን የወለደ" ሲባሉ ይኖራሉ::
✏️ጻድቁ ከዚህ በተጨማሪ የወቅቱን ንጉሥ አፄ ይኩኖ አምላክን በማስተማር ለሃገርና ለቤተ ክርስቲያን ጠቃሚ ሰው አድርገዋል:: በግላቸው ሐይቅ ውስጥ ገብተው ሲጸልዩ የብርሃን ምሰሶ ይወርድላቸው ነበር:: ሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳምንም ከጠፋ ከ300 ዓመታት በሁዋላ አቅንተዋል::
✏️እንዲህ ለቤተ ክርስቲያን ሲተጉ : በተለይ በአበ ምኔትነት በቆዩባቸው 45 ዓመታት ለዓይናቸው እንቅልፍን አላስመኙትም:: ጐድናቸውም ከምኝታ ጋር ተገናኝቶ አያውቅም::
"እንዘ የኀሊ ዘበሰማያት ዐስቦ::
መጠነ ዓመታት ሃምሳ ኢሰከበ በገቦ::" እንዲል::
✏️ከዚህ በሁዋላ የሚያርፉበት ዕለት ቢደርስ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወርዶ ቃል ኪዳን ሰጥቷቸዋል:: በተወለዱ በ82 ዓመታቸው (በ86 ዓመታቸው የሚልም አለ) በ1282 ዓ/ም በዕለተ ሰንበት ዐርፈው ተቀብረዋል::
✥ ቸር አምላክ በክብረ ቅዱሳን ይከልለን:: ከበረከታቸውም ያብዛልን::
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
397
✅ስንክሳር
🚩ሰኔ 1
✅ቅዱስ_ዮሴፍ_ጻድቅ
✏ቤተ_ክርስቲያን በዚህ ስም ብዙ ቅዱሳን አሏት:: በተለይ ደግሞ እስራኤል የተባለ የቅዱስ_ያዕቆብ
ልጅ ቅዱስ ዮሴፍ ከሁሉም ቅድሚያውን ይይዛል::
ታላቁ ቅዱስ_መጽሐፍ ላይ በስፋት ታሪካቸው ከተጻፈላቸው ቅዱሳን አንዱ ነው::
✏ስለዚህ ቅዱስ ዝርዝር መረጃን ለማግኘት ኦሪት_ዘፍጥረትን ከምዕራፍ 39 እስከ 50 ድረስ ማንበብ ይኖርብናል:: ከዚህ በተረፈም በዜና ቤተ ክርስቲያን ስለ ቅዱሱ ብዙ ተብሏል::
✏መጽሐፍ ቅዱስ ሲጀምር ስለ ቅዱስ ሰው አዳም
ይነግረናል:: ቀጥሎም ስለ ቅዱሳኑ
ሴት
ሔኖክ
ኖኅ
ሴም
አብርሃም
ይስሐቅና
ያዕቆብ
ነግሮን ቅዱስ_ዮሴፍ
ላይ ይደርሳል::
✏ቅዱስ ዮሴፍ ያዕቆብ (እስራኤል) ከሚወዳት
ሚስቱ ራሔል ከወለዳቸው 2 የስስት ልጆቹ አንዱ ነው:: ቅዱሱ ምንም እናቱ ብትሞተበትም በአባቱና በፈጣሪው ፊት ሞገስ ነበረው::
ምክንያቱም ቅን: ታዛዥና የፍቅር ሰው ነበርና::
✏እንዲያ አምርረው ለሚጠሉት ወንድሞቹ እንኳን ክፋትን አያስብም ነበር:: ይልቁኑ ለእነሱ ምሳ (ስንቅ) ይዞ ሊፈልጋቸው በበርሃ ይንከራተት ነበር እንጂ::
+መንገድ ላይ ቢርበው አለቀሰ እንጂ ስንቃቸውን
አልበላባቸውም:: የአባቶቹ አምላክ ግን ድንጋዩን ዳቦ
አድርጐ መግቦታል:: 10ሩ ወንድሞቹ ግን ስለ በጐነቱ ፈንታ ሊገድሉት ተማከሩ:: ከፈጣሪው አግኝቶ በነገራቸው ሕልም "ሊነግሥብን
ነው" ብለው ቀንተውበታልና::
✏በፍጻሜው ግን በይሁዳ መካሪነት ለዐረብ ነጋድያን
ሸጠውታል:: በዚህም ለምስጢረ ሥጋዌ (ለጌታ መሸጥና ሕማማት) ምሳሌ ለመሆን በቅቷል:: ወንድሞቹ ለክፋት ቢሸጡትም ቅሉ ውስጡ ፈቃደ እግዚአብሔር ነበረበትና በባርነት በተሸጠበት በዺጥፋራ ቤት ፈጣሪው ሞገስ ሆነው::
✏ወጣትነቱን በፍቅረ እግዚአብሔር ሸብ አድርጐ አስሮ ነበርና የዺጥፋራ ሚስት የዝሙት ጥያቄ
አላንበረከከውም:: "ማንም አያየንም" ስትለውም "እፎ እገብር ኃጢአተ በቅድመ እግዚአብሔር" (ማንም ባያይስ እንዴት በፈጣሪየ ፊት ኃጢአትን
አሠራለሁ?) በማለት ከበደል አምልጧል:: ስለዚህ
ፈንታም የእሥር ቅጣት አግኝቶታል::
✏ጌታ ከእርሱ ጋር ቢሆን በእሥር ቤትም ሞገስን አገኘና አለቅነትን ተሾመ:: "ኢኀደረ ዮሴፍ ዘእንበለ ሲመት" እንዲል መጽሐፍ:: ከዚያም የንጉሡን (የፈርዖንን) ባለሟሎች ሕልም ተረጐመ:: ቀጥሎም ንጉሡን በሕልም ትርጓሜ አስደመመ::
ፈርዖንም ቅዱሱን በግዛቱ (ግብጽ) ላይ ሾመው::
+ቅዱስ ዮሴፍ በምድረ ግብጽ ነግሦ ሕዝቡን ከረሃብ
ታደገ:: ለቅዱስ አባቱ ለእሥራኤልና ክፉ ለዋሉበት
ወንድሞቹም መጋቢ ሆናቸው:: አስኔት (አሰኔት) የምትባል ሴት አግብቶም ኤፍሬምና ምናሴ የተባሉ ልጆችን አፍርቷል::
✏በመንገዱ ሁሉ እግዚአብሔርን አስደስቶ: ከአባቱ
ዘንድም ምርቃትና በረከትን ተቀብሎ በ110 ዓመቱ
በዚህች ቀን በመልካም ሽምግልና ዐርፏል:: ወገኖቹም በክብርና በእንባ ቀብረውታል:: "አጽሜን አፍልሱ" ብሎ በተናገረው ትንቢት መሠረትም ልጆቹ
(እነ ቅዱስ ሙሴ) ከግብጽ ባርነት ሲወጡ አጽሙን ወደ ከነዓን አፍልሠዋል::
✅ቅዱስ ለውንትዮስ ሰማዕት "
✏ቅዱሱ የተወለደው በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን አካባቢ
ሲሆን ሃገሩ ጠራብሎስ ትባላለች:: በወቅቱ በወታደርነት ነገሥታቱን ያገለግል ነበር:: ድንግል: ደም ግባት የሞላለት ወጣት ስለ ነበር በሰዎች ፊት ሞገስ ነበረው::
✏እርሱ ግን ምን ወታደር ቢሆን ጾምና ጸሎትን ያዘወትር ነበር:: በተለይ ደግሞ የዳዊትን መዝሙር እየመላለሰ ይጸልየው: ይወደው ነበር:: ንግግሩ ሁሉ በመንፈስ ቅዱስ ጨውነት የታሸ ነውና ብዙ ጉዋደኞቹን ከክህደት ወደ ሃይማኖት: ከክፋት ወደ ደግነት መልሷል::
✏የመከራ ዘመን በደረሰ ጊዜም በገሃድ ስመ ክርስቶስን ይሰብክ ነበር:: ክፉ ሰዎች ከሰውት በመኮንኑ ፊት በቀረበ ጊዜም አልፈራም:: ወታደሮቹ መሬት ላይ ጥለው እየደበደቡት: ደሙ እንደ ጐርፍ እየተቀዳ እርሱ ግን ይዘምር ነበር::
✏በመጨረሻም ስለ ክርስቶስ ፍቅር አንገቱን ተሰይፏል:: ቅዱስ ለውንትዮስ እጅግ ተአምረኛ ሰማዕት ነውና በእምነት እንጥራው:: ቤተ ክርስቲያንም ዛሬ የቅዱሱን ተአምራት ታስባለች:: ቅዳሴ ቤቱም የተከበረው በዚሁ ዕለት ነው::
✥አምላከ ቅዱሳን ወርኀ ሰኔን የፍሬ: የበረከት: የንስሃና
የጽድቅ አድርጐ ይስጠን:: ከሰማዕቱ ጽናትን: ጸጋ በረከትን ይክፈለን::
🚩ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.ቅዱስ ዮሴፍ ጻድቅ (የያዕቆብ ልጅ)
2.እናታችን አስኔት (የቅ/ ዮሴፍ ሚስት)
3.ቅዱስ ለውንትዮስ ክቡር ሰማዕት
4.ቅዱስ ቢፋሞን ሰማዕት
5.ቅዱስ ቆዝሞስ ሰማዕት
🚩ወርኃዊ በዓላት፦
1፡ ልደታ ለማርያም
2፡ ቅዱስ በርተሎሜዎስ ሐዋርያ
3፡ ቅዱስ ሚልኪ ቁልዝማዊ
4፡ ቅዱስ ራጉኤል ሊቀ መላእክት
5፡ ቅዱሳን ኢያቄም ወሐና
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
397
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
397
✅ስንክሳር
🚩ሐምሌ 30
✅ቅዱስ እንድርያስ
✏መሐሪ #እግዚአብሔር ኃጢአታችሁ በዛ : ሰውነታችሁ ከፋ ሳይል በአባታዊ ርሕራሔው ጠብቆ ይሔው ወርኀ ሐምሌን በሰላም አስፈጸመን:: አይመስለንም እንጂ በእነዚህ 30 ቀናት ሚሊየኖች አንቀላፍተዋል:: ሚሊየኖች በደዌ ዳኝነት ተይዘዋል:: በርካቶቹም ከሃይማኖታቸው ወጥተዋል::
✏ታዲያ እኛ ይህ ሁሉ ያልደረሰብን በጐ ስለሆንን አይደለም:: ይልቁኑ ቸርነቱ በእኛ ላይ ስለበዛ ብቻ ነው እንጂ:: አሁንም በሰላም ከአዲሱ ዘመን እንዲያደርሰን ልንማጸነው ይገባል::
✥ በዚህች ዕለት ደግሞ እነዚህን ቅዱሳን እናከብራለን:-
✅ቅዱስ እንድርያስ ሐዋርያ
✏ቅዱሱ ሐዋርያ ተወልዶ ያደገው #በቤተ_ሳይዳ አካባቢ ሲሆን የሊቀ ሐዋርያት #ቅዱስ_ዼጥሮስ ትንሽ ወንድም ነው:: አባቱም #ዮና ይባላል:: ገና ከልጅነቱ ጀምሮ አሣ ማጥመድን ከትልቅ ወንድሙ ተምሯል:: እድሜው ከፍ ባለ ጊዜ ኦሪትን ተምሮ የመጥምቁ #ቅዱስ_ዮሐንስ ደቀ መዝሙር ሆኗል::
✏ከእርሱም እያገለገለ ለ6 ወራት ተምሯል:: በወቅቱ ከወንጌላዊው (ወልደ ዘብዴዎስ) #ዮሐንስ ጋር ቅርብ ባልንጀራም ነበር:: ጌታችን #ኢየሱስ_ክርስቶስ በተጠመቀ ጊዜ ያን ድንቅ #ምሥጢረ_ሥላሴ ከተመለከቱትም አንዱ ነው::
✏ጌታ ከጾም (ከገዳመ ቆረንቶስ) በተመለሰ ጊዜ እንድርያስ #መንፈስ_ቅዱስ አነሳስቶት ተከትሎታል:: መጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ "ነዋ በግዑ ለእግዚአብሔር ዘያዐትት ኃጢአተ ዓለም - የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ እነሆ" ማለቱን ሰምቶ ቅዱስ እንድርያስ ጌታን ተከተለ::
✏በዚህም የመጀመሪያው የክርስቶስ ደቀ መዝሙር ለመባል በቃ:: (ዮሐ. 1:47) ሊቁ #ማር_ገላውዴዎስም እመቤታችንን ሲያመሰግናት
"ለሐዋርያ #እንድርያስ ቀዳማዊ ማርያም ሃይማኖቱ::
ለመጀመሪያው ሐዋርያ ለእንድርያስ ሃይማኖቱ ማርያም አንቺ ነሽ::" ብሏል:: (#መልክዐ_ስዕል)
✏ቅዱሱ ሐዋርያ ስሉጥ (ፈጣን) አገልጋይ እንደ ነበርም ወንጌል ይነግረናል:: (ዮሐ. 6:5) ለ3 ዓመታት ከ3 ወት ከጌታ እግር ሥር ተምሮ : በበዓለ ሃምሳ መንፈስ ቅዱስን ተቀበሎ : ምን ሃገረ ስብከቱ #ልዳ ብትሆን ብዙ አሕጉረ ዓለምን ሰብኩዋል::
✏ይህች ቀን ሐዋርያው ከጌታ ጋር በመርከብ ውስጥ የተነጋገረባትና ቅዱስ ማትያስን ሰውን ከሚበሉ ሰዎች እጅ ያዳነባት ናት:: ቅዱስ እንድርያስ 30 ቀናት የሚፈጅ የባሕር ላይ ጉዞ ለማድረግ ከአርድእቱ ጋር ወደ ወደብ ቢሔድም መርከበኞች ሁሉ አናሳፍርም በማለታቸው የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወጣት መርከበኛ መስሎ ሐዋርያውንና አርድእቱን የሠላሳውን ቀን መንገድ በሰዓታት ልዩነት እንዲጨርሱ አድርጉዋል::
✏ቅዱስ እንድርያስም ፍጡር (እንዲሁ ሰው) መስሎት ለጌታችን ስለ ጌታችን ሰብኮለታል:: መርቆታልም:: መርከበኛው ጌታችን መሆኑን ሲያውቅም ደንግጦ አልቅሷል::
✏"ሶበ አእመረ ኪያሁ ወጠየቀ አምሳሎ::
ዘተናገርኩ በድፍረት ምስሌከ ኩሎ::
ሥረይ ሊተ ጌጋይየ ወኅድግ ይቤሎ::" እንዲል::
✏"ማረኝ?" ብሎታል:: ጌታችንም "አይዞህ እኔ ካንተ ጋር ነኝ" ብሎታል:: ቅዱሱ ሐዋርያ ለወንጌል አገልግሎት ተግቶ ያረፈው ታሕሳስ 4 ቀን ነው::
✅ቅዱስ ዻውሎስ መናኒ
✏ይህ ቅዱስ መላ ሕይወቱ ድንቅ ነው:: በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን የነበረ ሲሆን የተባረከች ሚስት እና 2 ቡሩካን ልጆች የነበሩት አባት ነው:: #ቅዱስ_ዻውሎስ የነዳያን አባት : እጅግ ባለ ጸጋ : ቤተሰቡን የቀደሰና ባለ ሞገስ ሰውም ነው::
✏ታዲያ ምጽዋት ወዳጅ ነውና ሲመጸውት : ሲመጸውት ሃብቱ አለቀ:: አሁንም መመጽወቱን አላቆመምና ቤቱ : ንብረቱ አልቆ ከነ ቤተሰቡ ነዳያን ሆኑ:: እርሱ ግን ያለ ምጽዋት ማደር አይችልምና አንድ ሃሳብ መጣለት:: ሚስቱንና ልጆቹን መሸጥ እንዳለበት ወሰነ::
✏እነርሱ እንደ መሪያቸው ፍጹማን ናቸውና በደስታ ሃሳቡን ተቀበሉት:: መጀመሪያ ትልቁ ልጅ ተሸጠ:: ገንዘቡ ግን አሁንም በምጽዋት አለቀ:: ቀጥሎ ትንሹ ልጅ ተሸጠ:: አሁንም በምጽዋት አለቀ:: 3ኛ ደግ ሚስት ተሸጠችና እርሱም ተመጸወተ::
✏በመጨረሻ ቅዱስ ዻውሎስ ራሱንም ሽጦ መጸወተና ይህ ድንቅ ሥራ ተጠናቀቀ:: ( ነገሩ ግራ እንዳያጋባን "ተሸጡ" ስንል ለአሕዛብ ወይም ለሌላ ሰው አይደለም:: 4ቱም የተሸጡት ለገዳማት ሲሆን ገዥዎቹ አበ ምኔቶቹ ናቸው:: ) ቅዱስ ዻውሎስ በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ መትቶ ምጽዋትንም : ገዳማዊ ሕይወትንም አትርፏል::
✏በሁዋላ ወደ ተሸጠበት ገዳም ገብቶ እንዲህ ብሎ ጮኸ:- "ጌታ ሆይ! የሰጠኸኝን ሁሉ ላንተ መልሼ ይሔው መጥቻለሁ::" ጌታም ከሰማይ መለሰለት:- "ወዳጄ ሆይ! ባንተ ደስ ብሎኛል:: ተቀብዬሃለሁ" አለው:: 4ቱም #ቅዱሳን በንጹሕ ተጋድሎ ኑረው በዚህች ቀን ዐርፈው የማታልፈውን ርስት ወርሰዋል::
✅ቅዱስ ሱርያል ሊቀ መላዕክት
✏ከታላላቅ ሊቃናት አንዱ የሆነው #ቅዱስ_ሱርያል ክብሩ ብዙ ቢሆንም ብዙ ምዕመናን አያውቁትም:: የመላእክት መዓርግ ሲነገር #ሚካኤል : #ገብርኤል : #ሩፋኤል ብሎ ቀጥሎ የሚመጣው ሱርያል ነው::
✏በ3ቱ ሰማያት ካሉት 9ኙ ዓለመ መላእክት የአንዱ (#የሥልጣናት) መሪ (አለቃ) ነው:: መልአኩ እጅግ ርሕሩሕ እና ተራዳኢ ነውና አንዘንጋው:: #ለኖኅ መርከብርን ያሳራው : ከጥፋት ውሃም ያዳነው ይህ ቅዱስ መልአክ ነው::
✏በገድለ ሰማዕታትም ላይ እንደተጠቀሰው የሰማዕታት ረዳትና አዳኝም ነው:: #ቅዱስ_ሱርያል በሌላ ስሙ "#እሥራልዩ" ይባላል:: "የእሥራኤል ረዳት" እንደ ማለት:: ዛሬ ደግሞ የሊቀ መልአኩ ቅዳሴ ቤቱ ነው::
✅ቅዱሳን መርቆሬዎስና ኤፍሬም
✏እነዚህ ወጣቶች በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን የነበሩ ሲሆን ከተወለዱባት #ገሊላ ወደ ግብጽ (#ገዳመ_አስቄጥስ) በምናኔ መጥተዋል:: ለ20 ዓመታትም በክህነት አገልግሎትና በተጋድሎ ኑረዋል::
✏አንድ ቀን መናፍቃን (አርዮሳውያን) በወታደር ተከበው መጥተው በገዳሙ እንቀድሳለን አሉ:: የራሳቸውን መስዋዕት መንበሩ ላይም አኖሩ:: ከዛ ያሉ አበው አዘኑ:: ወጣቶቹ መርቆሬዎስና ኤፍሬም ግን ለአምላካቸው ቀኑ::
✏ወደ ቤተ መቅደስ ገብተው መናፍቃኑን "በክርስቶስ አምላክነት የማያምን በዚህ መቅደስ ውስጥ አይሰዋም" ብለው በድፍረት የመናፍቃንን መስዋዕት ወደ ውጪ በተኑት:: በዚያች ሰዓት መናፍቃኑ 2ቱን ቅዱሳን ወደ መሬት ጥለው ደበደቧቸው:: ረገጧቸው:: የቅዱሳኑ አጥንቶችም ተሰባበሩ:: በመጨረሻ በስቃዩ ብዛት 2ቱም በአንድነት ዐረፉ::
✥የእነዚህ ሁሉ ቅዱሳን አምላክ ተረፈ ዘመኑን የንስሃ : የፍቅርና የአንድነት ያድርግልን:: ከወዳጆቹም በረከትን ያድለን::
✅ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ እንድርያስ ሐዋርያ
2.ቅዱስ ዻውሎስ መናኒ (ከቤተሰቡ ጋር)
3.ቅዱስ ሱርያል (እሥራልዩ) ሊቀ መላእክት
4.ቅዱሳን መርቆሬዎስና ኤፍሬም (ሰማዕታት)
5.ቅዱስ ጢሞቴዎስ ዘአልቦ ጥሪት (ፍልሠቱ)
6.እናታችን ማርያም ክብራ ኢትዮዽያዊት (የዐፄ ናዖድ ሚስት)
🚩ወርኀዊ በዓላት፦
1.ቅዱስ ማርቆስ ዘአንበሳ (ሐዋርያ)
2.አባ ሣሉሲ ክቡር
3.ቅዱስ ጐርጐርዮስ ነባቤ መለኮት
4.ቅድስት ሶፍያ ሰማዕት
5.ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት
397
✅ስንክሳር
🚩ሐምሌ 29
✅ቅዱስ ታዴዎስ ሐዋርያ
✏ቅዱሳን ሐዋርያት አባቶቻችን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በተከተሉበት ሰዓት እድሜአቸው በ3 ደረጃ የተከፈለ እንደ ነበር የቤተ ክርስቲያን ትውፊት ያሳያል:: እንደ ዮሐንስ ወንጌላዊ ያሉት በ20ዎቹ ውስጥ : ቅዱስ ታዴዎስን የመሰሉት ደግሞ በ30ና በ40ዎቹ
ውስጥ የነበሩ ሲሆን እነ ቅዱስ ዼጥሮስ ደግሞ በ50ዎቹ ውስጥ የሚገኙ ነበሩ::
✏ደቀ መዛሙርቱ ከወጣቶችም : ከጐልማሶችም : ከአረጋውያንም የተዋቀሩ ነበሩ ማለት ነው::
ቅዱስ ታዴዎስ በቀደመ ስሙ ልብድዮስ ይባል የነበረ ሲሆን በአንዳንድ መጻሕፍት ውስጥ
(በተለይ በምሥራቅ ኦርቶዶክሶች) ስምዖን እና ይሁዳ እየተባለም ተጠርቷል::
✏ቅዱሱ ጌታችን ተከትሎ : ከ12ቱ አንዱ ሆኖ በፈጣሪው ተመርጦ : 3 ዓመት ከ3 ወር ከጌታ
እግር ተምሮ : በዕርገቱ ተባርኮ : በበዓለ ሃምሳም 71 ልሳናትን ተቀብሎ : ሐዋርያት ዕጣ
ሲጣጣሉ የበኩሉን አሕጉረ ስብከት ተካፍሎ ዓለምን ዙሯል::
✏ቅዱስ ታዴዎስ እስከ እርጅናው ድረስ ለወንጌል ሲተጋ ኑሯል:: ጌታችንም በየጊዜው በአካል
እየተገለጸ አጽናንቶታል:: ከብዙ የድካምና የመከራ ዘመናት በሁዋላም ሐምሌ 2 ቀን ዐርፏል::
ቅዱሱ ሐዋርያ ያረፈው ሶርያ ውስጥ ሲሆን ከ250 ዓመታት በሁዋላ ቤተ ክርስቲያኑ ታንጾለት
በዚህች ቀን ወደ ቁስጥንጥንያ ፈልሷል:: ይህንን ያደረገው ደግሞ ታላቁ ንጉሥ ቅዱስ
ቆስጠንጢኖስ ነው:: ከሐዋርያው ዘንድም ብዙ ተአምራት ተደርገዋል::
✅ ቅዱስ ዋርስኖፋ ሰማዕት
✏ቅዱሱ በትውልድ ግብፃዊ ሲሆን ገና ከልጅነቱ ጣዕመ ክርስትና የገባው ነበር::
መጻሕፍትን በማንበብ: ክርስትናንም በመለማመድ ስላደገ በሰውና በእግዚአብሔር ፊት
የመወደድ ሞገስ ነበረው:: በእድሜው እየጐለመሰ ሲሔድ በተጋድሎውም እየበረታ ሔደ::
✏በወቅቱ እርሱ የነበረባት ሃገር ዻዻስ በማረፉ ሊቃውንቱና ሕዝቡ ተሰብስበው አምላክን
ጠየቁ:: እንደሚገባም መከሩ:: በደንብ አስተውለዋልና እንደ አንድ ልብ መካሪ: እንደ አንድ
ቃል ተናጋሪ ሁነው ሁሉም ቅዱስ ዋርስኖፋን መረጡ::
ዛሬን አያድርገውና በአባቶቻችን ዘመን ሕዝቡም ሆነ ሊቃውንቱ መሪ መምረጥን ያውቁ ነበር::
ተመራጮቹ ደግሞ እንኩዋን እንደ ዘመናችን "ሹሙኝ : ምረጡኝ" ሊሉ በአካባቢውም አይገኙም ነበር::
✏ቅዱስ ዋርስኖፋ ለዽዽስና እንደ መረጡት ሲያውቅ "ጐየ" እንዲል መጽሐፍ: ጨርቄን ማቄን
ሳይል በሌሊት ጠፍቶ በርሃ ገባ:: (እንዲህ ነበሩ አበው) በገባበት በርሃ ውስጥ በዓት ሠርቶ
በጾም: በጸሎትና በስግደት በርትቶ ዓመታትን አሳለፈ:: እርሱ በበርሃ እያለ ዘመነ ሰማዕታት
ጀምሮ ብዙ ክርስቲያኖች አልቀው ነበር::
እርሱ ግን ከዓለም ርቁዋልና ይህንን አላወቀም ነበር:: አንድ ቀን መልአከ እግዚአብሔር
መጥቶ "አንተ በስሙ ደማቸውን ለሚያፈሱ አክሊላት እየታደለ : ሰማያዊ ርስትም እየተካፈለ
ነውኮ! አልሰማህም?" አለው::
✏ቅዱስ ዋርስኖፋም "ለካም እንዲህ ያለ ክብር አምልጦኛል" ብሎ: በርሃውን ትቶ ወደ ከተማ
ወጣ:: መልአኩ እንዳለውም ክርስቲያኖች ሲሰቃዩ ደረሰ:: ቅዱሱም ሳያመነታ ስመ
ክርስቶስን ሰብኮ: ብዙ ተሰቃይቶ በዚህች ቀን አክሊለ ሰማዕትን በአክሊለ ጻድቃን ላይ
ደርቧል::
✅ እጨጌ አባ ዮሐንስ ዘጐንድ
✏ ጻድቁ ተወልደው ያደጉት በኢየሩሳሌም ሲሆን ነገዳቸውም እሥራኤላዊ ነው:: ነገር ግን
ተጋድሏቸውን የፈጸሙት በሃገራችን ኢትዮዽያ ውስጥ ነው:: እጨጌ አባ ዮሐንስ ከአቡነ
ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቀጥሎ ባለ ረዥም እድሜ ጻድቅ መሆናቸው ይነገራል::
✏አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ያረፉት በ562 ዓመታቸው ሲሆን እጨጌ አባ ዮሐንስ ደግሞ
በ500 ዓመታቸው ነው:: የሚገርመው ጻድቁ የታላላቁ ጻድቃን ገብረ መንፈስ ቅዱስ : ተክለ
ሃይማኖት: ሳሙኤል: ዜና ማርቆስ እና ሌሎችም ባልንጀራ ነበሩ::
✏በዛ ዘመን ዘረኝነት በቅዱሳኑ ዘንድ አልነበረምና ነጭ ሆነ ጥቁር : ከየትም ይምጣ የሰው ልጅ
መሆኑ ብቻ በቂ ነበር:: እጨጌ አባ ዮሐንስ በሃገራችን 5 በዓቶች የነበሯቸው ሲሆን በአንድ
በዓት የሚኖሩት ለ50 ዓመት ነበር::
በዚህም በኢየሩሳሌም ለ50 ዓመት : በኢትዮዽያ ደግሞ ለ450 ዓመታት ኑረዋል::
ከበዓቶቻቸው አንዱ ደብረ ሊባኖስ ሲሆን በገዳሙ ለ50 ዓመታት አበ ምኔት(እጨጌ) ሆነው
አገልግለዋል:: "እጨጌ" የሚባሉትም በዚህ ምክንያት ነው::
✏ጻድቁ የመጨረሻ ዘመናቸውን ያሳለፉት በጐንድ (ጉንድ) ተክለ ሃይማኖት ገዳም ነው::
ገዳሙ የሚገኘው በሰሜን ጐንደር ዞን : በለሳ ወረዳ ውስጥ ሲሆን የመሠረቱትም ራሳቸው
ናቸው:: ነገር ግን በራሳቸው እንዲጠራ አልፈለጉምና ገዳሙ የሚጠራው በወዳጃቸው
በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ስም ነው::ጐንድ እኛ ኃጥአን ሳይገባን ያየነው ገዳም ነው::
✏ዛሬም ድረስ ድንቅ የሆኑ አበው የሚኖሩበት
: ተአምራትም የማይቋረጥበት : ፈዋሽ ጠበል ያለው ደግ ገዳም ነው:: ጻድቁ እጨጌ አባ
ዮሐንስ ግን አስታዋሽ አጥተው እየተዘነጉ ካሉ ቅዱሳን አንዱ ናቸው:: ምንም ዛሬ አጽማቸው
ፈልሶ ወደ ደቡብ ኢትዮዽያ አካባቢ ቢሔድም እርሳቸው በ500 ዓመታቸው ያረፉት በዚህ
ገዳም ውስጥ ነው::
✥እግዚአብሔር ከሐዋርያው : ከሰማዕቱና ከጻድቁ ክብርን : በረከትን ያሳትፈን::
🚩 ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.ቅዱስ ታዴዎስ ሐዋርያ (ፍልሠቱ)
2.ቅዱስ ዋርስኖፋ ሰማዕት
3.እጨጌ አባ ዮሐንስ (ዘጐንድ)
🚩 ወርኀዊ በዓላት፦
1.የፈጣሪያችንና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት
2.ቅድስት አርሴማ ድንግል
3.ቅዱስ ዼጥሮስ ተፍጻሜተ ሰማዕት
4.ቅዱስ ማርቆስ ዘቶርማቅ
5.ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ኢትዮዽያዊት
6.ቅዱስ ዘርዐ ክርስቶስ (ጻድቅና ሰማዕት)
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
397
✅ ስንክሳር
🚩 ሐምሌ 28
✅ ጻድቃን እንድራኒቆስ ወአትናስያ
✏ሁለቱ ቅዱሳን ባል እና ሚስት (ባለትዳር) ናቸው:: የነበረበት ዘመን 4ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው:: እስኪ #እግዚአብሔር የቀደሰው ጋብቻ ምን እንደሚመስል እንመልከት::
✏#እንድራኒቆስና_አትናስያ በዘመናቸው ከልጅነት ጀምረው ቃለ እግዚአብሔርን የሚሰሙ : ለወላጆቻቸው የሚታዘዙ ነበሩ:: ዘመኑ ደርሶ በሚገባው የተክሊል ሥርዓት ጋብቻቸውን ፈጸሙ:: 40 ቀን ከተፈጸመ በሁዋላ ከምንም ነገር በፊት 2ቱ ቁጭ ብለው ተወያዩ::
✏የውይይታቸው ርዕስ ደግሞ "ፈጣሪያችን በምን እናስደስተው" የሚል ነበር:: ውይይታቸው የጠናቀቀው በእነዚህ ውሳኔዎች ነው::
1.ሁልጊዜም እንግዳ መቀበል አለብን::
2.ነዳያን ከቤታችን ሊጠፉ አይገባም::
3.ጸሎት : ጾምና ስግደት በቤት ውስጥ አይቁዋረጥም::
4.አብሮ ለመተኛት መቸኮል የለብንም::
✏እነርሱ መልካምን አስበዋልና አምላክ የሰጣቸውን ሃብት ሲመጸውቱ ኖሩ:: ከዘመናት የቅድስና ጉዞ በሁዋላ በፈቃደ እግዚአብሔር 2 ልጆችን አከታትለው ወለዱ:: ወንዱን "#ዮሐንስ" : ሴቷን ደግሞ "#ማርያም" አሏት::
✏እነርሱን ከወለዱ በሁዋላ እንደ ገና ሌላ ውሳኔ አሳለፉ:: "ይህንን ላደረገልን ጌታ ከዚህ በሁዋላ አልጋ እንለያለን" ብለው ለ12 ዓመታት በጾምና በጸሎት ተወሰኑ::
✏ሕጻናቱ ዮሐንስና ማርያም በቅንነት አድገው እድሜአቸው 12 ሲሆን 2ቱም በአንድ ቀን ታመው ሞቱ:: ይህ ለአንድ ወላጅ የመጨረሻው አሰቃቂ ፈተና ነው:: ሁሉቱም (እንድራኒቆስና ሚስቱ አትናስያ) ልጆቻቸውን ታቅፈው ወስደው ቀበሩ::
✏#እንድራኒቆስ ከቀብር በሁዋላ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ምርር ብሎ አለቀሰ:: ግን እንዲህ አለ:-
"አምላከ #ኢዮብ! አንተ ሰጠኸኝ:: አንተም ነሳኸኝ:: ስምህ ለዘለዓለም ይባረክ" ብሎ ሔደ:: እናት #አትናስያ ግን ከሐዘን ብዛት ልቡናዋ ሊሠወር ጥቂት ቀረው::
✏የልጆቿ መቃብር ላይ ተደፍታ ስታለቅስ ቅዱስ መልአክ ልቡናዋን ወደ ሰማይ አሳረገው:: ልጆቿ ዮሐንስና ማርያም በገነት ውስጥ ከቅዱሳን ጋር ሐሴትን ሲያደርጉም ተመለከተች:: ወዲያው ወደ ቤት ተመልሳ ለባሏ እንድራኒቆስ ያየችውን ነገረችውና ደስ አላቸው::
✏እዛው ላይ "ለዚህ ውለታው ከነፍሳችን ውጪ የምንሰጠው የለም" ብለው ሊመንኑ ተስማሙ:: እጅግ ሃብታሞች ነበሩና ነዳያንን ሰብስበው : ሃብት ንብረታቸውን : ቤት ርስታቸውን አካፍለው ወደ ገዳመ አስቄጥስ ሔዱ::
✏እርሷ ከሴቶች ገዳም : እርሱ ደግሞ ከወንዶቹ ገቡ:: ለ12 ዓመታት በፍጹም ተጋድሎ ለፈጣሪያቸው ተገዙ:: በእነዚህ ዘመናት ተያይተው : አንዱ ስለ ሌላው ሰምቶ አያውቅም:: በጸሎት ግን ያለማቁዋረጥ ይተሣሠቡ ነበር::
✏ከ12 ዓመታት በሁዋላ የፍቅር አምላክ በሁለቱም ልቡና በተመሳሳይ ሰዓት : ተመሳሳይ ሐሳብን አመጣ:: እርሱ ከአበ ምኔቱ (#ታላቁ_አባ_ዳንኤል) : እርሷም ከእመ ምኔቷ አስፈቅደው ወደ #ኢየሩሳሌም ከቅዱሳት መካናት ለመባረክ ጉዞ ጀመሩ:: በየፊናቸው ጥቂት እንደተጉዋዙ እርስ በርስ ተያዩ::
✏እርሷ ለየችው:: እርሱ ግን ጭራሽ ሊለያት አልቻለም:: ይህም ጥበበ እግዚአብሔር ነው:: 2ቱም እየተጫወቱ : እየጸለዩ በሰላም ተባርከው ወደ ግብጽ ተመለሱ:: በእነዚህ ጊዜያት ቅድስት አትናስያን የሚለያት አልነበረም:: አካሏ በገድል ከመለወጡ ባሻገር የለበሰችው እንደ ወንድ መነኮሳት ነበር::
✏ወደ #ገዳመ_አስቄጥስ ሲደርሱ ጸጋው ተሰጥቶታልና #አባ_ዳንኤል ባልና ሚስት መሆናቸውን አወቀ:: "ለምን አብራችሁ አትኖሩም?" አላቸው:: "እኛ ደስ ይለናል" አሉት:: ከዚያ እርሷ እያወቀችው: እርሱ ሳያውቃት ለ12 ዓመታት አብረው በቅድስና ኖሩ::
✏ከእነዚህ ዘመናት በሁዋላ ግን ሐምሌ 28 ቀን ቅድስት #አትናስያ ታመመች:: አባ ዳንኤል ሥጋውን ደሙን አቀብሏትም ዐረፈች:: ሊገንዟት ሲቀርቡ ቅዱስ #እንድራኒቆስ መልኩዋን ልብ ቢለው ሚስቱ ናት::
✏በአንድ ጊዜ ሚስቱንና የሚወደውን ባልንጀራ በማጣቱ አለቀሰ:: እርሷን ቀብረው ወደ በዓቱ ተመልሶ "ጌታ ሆይ! ውሰደኝ?" አለ:: እርሱም ተከትሏት ዐረፈ:: አባ ዳንኤል እርሱንም ቀብሮ ጥዑም ዜናቸውን ጻፈ::
✅ አባ ፊልዾስ ዘደብረ ሊባኖስ
✏ታላቁ ኢትዮዽያዊ ጻድቅ: ሐዋርያና ሰማዕት #አቡነ_ፊልዾስ የጻድቁ #አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት ደቀ መዝሙር ሲሆኑ የተወለዱት በምድረ ሽዋ በ1266 ዓ/ም ነው:: ከልጅነታቸው ጀምረው ምሥጢር ተመራማሪና መጻሕፍትን መርማሪ የነበሩት ጻድቁ የመነኑት ገና በ15 ዓመታቸው ነበር::
✏#በደብረ_ሊባኖስ በአሞክሮ ለ3 ዓመታት ቆይተው መንኩሰዋል:: ለ22 ዓመታትም የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ደቀ መዝሙር ሆነው አገልግለዋል:: አቡነ ተክለ ሃይማኖት በ1306 ዓ/ም ነሐሴ 24 ቀን ሲያርፉ የተተኩት አባ ኤልሳዕ ቢሆኑም ለ3 ወራት ቆይተው ዐርፈዋል::
✏በ1307 ዓ/ም አቡነ ፊልዾስ የደብረ ሊባኖስ አበ ምኔት (እጨጌ) ሁነዋል:: ገዳሙንም ለ28 ዓመታት መርተዋል:: ከዚያም በዘመነ አፄ ዓምደ ጽዮንና በአፄ ሰይፈ አርዕድ ብዙ ስደት: መከራ: እሥራትና ግርፋት ደርሶባቸዋል:: ምክንያቱ ደግሞ እውነትን መናገራቸውና ነገሥታቱን መገሰጻቸው ነበር:: በስደትም ለ6 ዓመታት ከ9 ወራት ቆይተዋል::
✏ሃገሪቱን በስብከተ ወንጌል ካበሩ #12ቱ_ንቡራነ_እድ አንዱ የሆኑት #እጨጌ አባ ፊልዾስ በተወለዱ በ74 ዓመት ከ9 ወራቸው በ1341 ዓ/ም ዐርፈዋል:: የተቀበሩት #በደብረ_ዕንቁ ሲሆን ካረፉ በ140 ዓመት #አቡነ_መርሐ_ክርስቶስ ዐጽማቸውን አፍልሰዋል::
✥ከቅዱሳኑ እንድራኒቆስ ወአትናስያ እና ከጻድቁ አቡነ ፊልዾስ በረከትን ይክፈለን::
🚩 ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.ቅዱሳን ጻድቃን እንድራኒቆስና አትናስያ
2.አቡነ ፊልዾስ ጻድቅ (ዘደብረ ሊባኖስ)
🚩ወርኀዊ በዓላት፦
1.አማኑኤል ቸር አምላካችን
2.ቅዱሳን አበው (አብርሃም : ይስሐቅና ያዕቆብ)
3.ቅድስት ዓመተ ክክርስቶስ
4.ቅዱስ ቴዎድሮስ ሮማዊ (ሰማዕት)
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
397
✅ስንክሳር
🚩ሐምሌ 27
✅ቅዱስ ሴት ነቢይ
✏አባታችን ሴት የመጀመሪያዎቹ ፍጥረቶች የአዳምና ሔዋን የተባረከ ልጅ ነው:: ቀደምተ ፍጥረት አዳም እና ሔዋን በዕጸ በለስ ምክንያት ከገነት ከተባረሩ በኋላ በመጀመሪያ ቃየን እና አቤልን ከነ መንትያዎቻቸው ወልደው ነበር::
✏ነገር ግን የልጅ ደስታቸው ቀጣይ ሊሆን አልቻለም:: ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ ቃየን ሲሆን ወንድሙን አቤልን በጾታዊ ፍላጐት ምክንያት በመግደሉ ነበር:: የአቤል ሞት ለአባታችን አዳም መራር ዜና ነበር:: ወላጅ እንኳን ደጉን ይቅርና ክፉ ልጁም እንዲለየው አይፈልግምና::
✏ቅዱስ አዳም ቅዱስ አቤልን ቀብሮ: ፈጽሞ አለቀሰ:: ልቅሶውም እንዲሁ የወርና የሁለት ወር አልነበረም:: አራት ኢዮቤልዩ (ሃያ ስምንት ዓመታት) ነበር እንጂ:: ይህንን ሐዘንና ልቅሶ የተመለከተ እግዚአብሔር ደግሞ ደግ ፍሬን በሔዋን ማኅጸን ውስጥ አሳደረ::
✏ይሕ ሕፃን በተወለደ ጊዜ "ሴት" ብለው ስም አወጡለት:: ትርጉሙም "የአቤል ምትክ" እንደ ማለት ነው:: ሴት ገና ከልጅነቱ ጀምሮ በብዙ ነገሩ አዳምን የሚመስል ነበረ:: ደም ግባቱ: ቅንነቱ: ታዛዥነቱ: ደግነቱ ሁሉ ልዩ ነበር:: በዚህም አዳምና ሔዋን ተጸናንተዋል::
✏ትልቁ ነገር ደግሞ ዓለም የሚድንባት እመቤት ድንግል ማርያም ከስልሳ በላይ የአዳም ልጆች ተመርጣ ለቅዱስ ሴት መሰጠቷ ነው:: ይሕንን ምሥጢርና የሴትን ማንነት ያስተዋለው ሊቁ አባ ሕርያቆስ እመ ብርሃንን እንዲህ ሲልም አመስግኗታል::
"ሒሩቱ ለሴት - የሴት ደግነቱ: በጐነቱ: ቅንነቱ አንቺ ነሽ" (ቅዳሴ ማርያም)
✏አባታችን ሴት በሚገባው ትዳር ተወስኖ ቅዱስ ሔኖስንና ሌሎች ብዙ ልጆችን ወልዷል::
አባታችን አዳም ባረፈ ጊዜ የዚህን ዓለም እረኝነት (በደብር ቅዱስ ላሉት) ተረክቧል:: አዳምም ልጆቹንና ወርቅ እጣን ከርቤውን አስረክቦታል:: ሴት እንባው እንደ ዥረት እየፈሰሰ አስቀድሞ አዳምን: አስከትሎም ሔዋንን ገንዞ በክብር ቀብሯቸዋል::
✏ወርቅ: እጣን: ከርቤውን ከሥጋቸው ጋራ በቤተ መዛግብት (በተቀደሰው ዋሻ) ውስጥ አኑሮታል:: የአገልግሎት ዘመኑ በተፈጸመ ጊዜ ደጉ ሴት ኃላፊነቱን ለልጁ ሔኖስ ሰጥቶ በዘጠኝ መቶ አሥራ ሁለት ዓመቱ ዐርፏል:: እርሱም ከወላጆቹ አዳምና ሔዋን ጋር ተቀላቅሏል::
✅ቅዱስ ሕዝቅኤል ነቢይ
✏ነቢዩ ቅዱስ ሕዝቅኤል የነበረው ቅ/ል/ክርስቶስ በ500 ዓመት አካባቢ ሲሆን የጼዋዌ (ምርኮ) አባልም ነበር:: እሥራኤልና ይሁዳ ወደ ባቢሎን በምርኮ ሲወርዱ አብሮ ወርዷል:: ቅዱሱ ከአራቱ ዐበይት ነቢያት አንዱ ሲሆን ሐረገ ትንቢቱም በአርባ ስምንት ምዕራፎች የተዋቀረ ነው::
✏በዘመኑ ሁሉ ቅድስናን ያዘወተረው ቅዱሱ ከደግነቱ የተነሳ በጸጋማይ (ግራ) ጐኑ ተኝቶ ቢጸልይ ስድስት መቶ ሙታንን አስነስቷል:: ወገኖቹ እሥራኤልንም ያለ መታከት አስተምሯል:: ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዚህች ዕለት ታላቁን ራዕይ እንዳየ ታስተምራለች:: ነቢዩ በፈለገ ኮቦር ካያቸው ምሥጢራት እነዚህን ያነሷል:-
1.እግዚአብሔርን በዘባነ ኪሩብ ተቀምጦ ሲሠለስና ሲቀደስ አይቶታል:: የኪሩቤልንም ገጸ መልክእ በጉልህ ተመልክቷል:: (ሕዝ. 1:1)
2.በመጨረሻው ቀን ትንሣኤ ሙታን : ትንሣኤ ዘጉባኤ እንደሚደረግም ተመልክቷል:: (ሕዝ. 31:1)
3.እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ኆኅት ኅትምት/ኆኅተ ምሥራቅ (የምሥራቅ ደጅ) ሁና አይቷታል::
✏ይሕ የምሥራቅ ደጅ (በር) ለዘላለም እንደታተመ ይኖራል:: የኃያላን ጌታ ሳይከፍት ገብቶ: ሳይከፍት ወጥቷልና:: (ሕዝ. 44:1)
በመጨረሻ ሕይወቱ እሥራኤል ለክፋት አይቦዝኑምና ነቢዩን አሰቃይተው ገድለውታል::
✅ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ
✏አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቅዱስ ወንጌሉ እንደነገረን በመንግስተ ሰማያት ታላቁ ሰው ወንጌላዊው ዮሐንስ ነው::
✏ቅዱሱ ሐዋርያ ከዘብዴዎስ እና ከማርያም ባውፍልያ ተወልዶ : በገሊላ አካባቢ አድጐ : ገና በወጣትነቱ መድኃኔ ዓለምን ተከትሎታል:: ቅዱስ ዮሐንስ ከሐዋርያት ቀድሞ ጌታን ከመከተሉ ባሻገር በምንም ምክንያት ከጐኑ አይጠፋም ነበር:: ስለ ንጽሕናውና በጐ የፍቅር ሕሊናው ሕፃን ሳለ በወንድሞቹ ሐዋርያት ዘንድ ሞገሱ ከፍ ያለ ነው::
✏ጌታችንን እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ በመከተሉ ድንግል እመቤታችንን ተቀብሏል:: ከእርሷ ጋር ለአሥራ አምስት ዓመታት ቢቀመጥ መዝገበ ምሥጢር ሆነ:: ስንኳን ከሰው ልጆች ይቅርና ከልዑላኑ መላእክትም ማዕረጉ ከፍ አለ:: ሰው ቢበቃ መላእክትን ሊያይ ይቻለዋል:: ቅዱስ ዮሐንስን ግን መላእክት ሊያዩት ይከብዳቸዋል:: ከፍጥረት ወገን ከእመ ብርሃን ቀጥሎ ክቡር እርሱ ነው::
✏በዚህ ቀንም ቅዱስ ዮሐንስ በታናሽ እስያ ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት መስበኩ ይታሰባል:: ቅዱሱ ከጌታችን ዕርገት በኋላ ለሰባ ዓመታት በዚህ ምድር ሲኖር አብዛኛውን ጊዜውን ያሳለፈው በኤፌሶን አካባቢ ነው:: ሕዝቡን ወደ ክርስትና ለማምጣት በአፍም : በመጽሐፍም ደክሟል::
✏ሦስት መልዕክታት : ራዕዩንና ወንጌልን ጽፎላቸዋል:: ሕይወትን ስለ ሰበከላቸው በፈንታው ብዙ አሰቃይተውታል:: ከእሳት እስከ ስለት : እስከ መጋዝም በስተእርጅና ደርሶበታል:: እርሱ ግን በትእግስቱ ገንዘብ አድርጓቸዋል:: ዳግመኛ ይሕች ዕለት ለሐዋርያው ቅዳሴ ቤቱ ናት::
✏እናት ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ዮሐንስን ስትጠራው እንዲሕ ነው:-
¤ወንጌላዊ
¤ሐዋርያ
¤ሰማዕት ዘእንበለ ደም
¤አቡቀለምሲስ(ምሥጢራትን ያየ)
¤ታኦሎጐስ (ነባቤ መለኮት)
¤ወልደ ነጐድጓድ
¤ደቀ መለኮት ወምሥጢር
¤ፍቁረ እግዚእ
¤ርዕሰ ደናግል (የደናግል አለቃ)
¤ቁጹረ ገጽ
¤ዘረፈቀ ውስተ ሕጽኑ ለኢየሱስ (ከጌታ ጎን የሚቀመጥ)
¤ንስር ሠራሪ
¤ልዑለ ስብከት
¤ምድራዊው መልዐክ
¤ዓምደ ብርሐን
¤ሐዋርያ ትንቢት
¤ቀርነ ቤተ ክርስቲያን
¤ኮከበ ከዋክብት
✥በቅዱስ ዮሐንስ ላይ ያደረ የእመቤታችን ድንግል ማርያምና የአንድ ልጇ ፍቅር በእኛም ላይ ይደር:: የሴት ደግነቱ : የሕዝቅኤልም በረከቱ ይደርብን::
🚩ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.ቅዱስ ሴት ነቢይ (ወልደ አዳም)
2.ቅዱስ ሕዝቅኤል ነቢይ
3.ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ (ቅዳሴ ቤቱ)
4.ቅዱስ አሞን ሰማዕት
🚩ወርኀዊ በዓላት፦
1.የጌታችንና አምላካችን መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ በዓለ ስቅለት
2.አቡነ መብዐ ጽዮን ጻድቅ
3.ቅዱስ መቃርስ (የመነኮሳት ሁሉ አለቃ)
4.ቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ
5.ቅዱስ ገላውዴዎስ ሰማዕት (ንጉሠ ኢትዮጵያ)
6.ቅዱስ ቢፋሞን ጻድቅና ሰማዕት
7.ማር ቅዱስ ፊቅጦር ሰማዕት
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
397
✅ስንክሳር
🚩ሐምሌ 26
✅አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን
✏ቅዱሱ በትውልዳቸው ግሪካዊ ቢሆኑም ሶርያ አካባቢ እንዳደጉ ይታመናል በቀደመ ስማቸው ፍሬምናጦስ የሚባሉት አቡነ ሰላማ ወደ ኢትዮዽያ የመጡት በአደጋ ምክንያት (በድንገት) ቢመስልም ውስጡ ግን ፈቃደ እግዚአብሔር ነበረበት::
✏በድንበር ጠባቂዎች (በአደጋ ጣዮች) ከባልንጀራቸው ኤዴስዮስ ጋር ተይዘው ወደ አክሱም የመጡት በንጉሥ ታዜር (አይዛና) እና በሚስቱ ሶፍያ (አሕየዋ) ዘመን ነው:: ጊዜው በውል ባይታወቅም በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው::
✏ፍሬምናጦስ ምንም የመጡበት ዓላማ ስብከተ ወንጌል ባይሆንም በአክሱም ቤተ መንግስት አካባቢ ይሰበኩ ነበር:: ያን ጊዜ በጃንደረባው ቅዱስ ባኮስ የተቀጣጠለው የክርስትና ችቦ ውስጥ ውስጡን በሃገሪቱ ነበረና ፍሬምናጦስ አልተቸገሩም:: በተለይ ሕጻናቱን (ኢዛናና ሳይዛናን) ገና ከልጅነት ስላስተማሯቸው ነገሮች የተሳኩ ሆኑ::
✏ልክ ንጉሥ ታዜር እንደ ሞተ ሁለቱ ሕጻናት በመንበሩ ተቀመጡ:: ፍሬምናጦስንም ወደ ግብፅ ዻዻስና ጥምቀት ከመጻሕፍት ጋር እንዲመጣላቸው ላኩ:: ሐዋርያዊ ቅዱስ አትናቴዎስም ፍሬምናጦስን "ሰላማ" ብሎ ሰይሞ : በዽዽስና : በንዋየ ቅድሳትና በመጻሕፍት ሸልሞ መለሳቸው::
✏አቡነ ሰላማ ወደ ኢትዮዽያ እንደተመለሱ ከነገሥታቱ ጀምረው ለሕዝቡ ጥምቀትን አደሉ:: ኢዛናና ሳይዛናም አብርሃ (አበራ) እና አጽብሃ (አነጋ) ተብለው ስማቸው ተደነገለ:: ከዚያ በሁዋላ ድንቅ በሚሆን አገልግሎት ነገሥታቱ : ዻዻሱ ሰላማና ሊቀ ካህናቱ እንበረም ለክርስትና መስፋፋት በጋራ ሠርተዋል::
✅የአቡነ ሰላማ ትሩፋቶች
1.ዽዽስናና ክህነትን ከእውነተኛ ምንጭ አምተዋል::
2.ክርስትናና ጥምቀትን በሃገራችን አስፋፍተዋል::
3.ቅዱሳት መጻሕፍትን ከውጭ ልሳኖች ተርጉመዋል::
4.ገዳማዊ ሕይወትን ጀምረዋል::
5.አብያተ ክርስቲያናትን አንጸዋል::
6.ግዕዝ ቋንቋን አሻሽለዋል::
ሀ.ከግራ ወደ ቀኝ እንዲፃፍ
ለ.እርባታ እንዲኖረው
ሐ.ከ"አበገደ" ወደ "ሀለሐመ" ቀይረዋል::
✏ባላቸው ንጹሕ የቅድስና ሕይወት ለሕዝቡ ምሳሌ ሆነዋ:: "ወበእንተዝ ተሰይመ ከሳቴ ብርሃን" እንዲል ገድላቸው በነዚህ ምክንያቶች "ከሣቴ ብርሃን" (ብርሃንን የገለጠ) ሲባሉ ይኖራሉ:: በመጨረሻም ከመልካሙ ገድል በሁዋላ በ352 ዓ/ም ዐርፈው ተቀብረዋል::
✅ ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ
✏ በሐዲስ ኪዳን መጀመሪያ አካባቢ ስም አጠራራቸው ከከበረ ደጋግ እሥራኤላውያን አንዱ የእመቤታችን ጠባቂ ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ ነው:: ትውልዱ ከነገደ ይሁዳ ሲሆን አባቱ ያዕቆብ ይሰኛል::
✏በጉብዝናው ወራት የእመቤታችንን አክስት ማርያምን አግብቶ ብዙ ልጆችን ወልዶ አርጅቷል:: ከልጆቹም ዮሳ: ያዕቆብ: ይሁዳ: ስምዖን እና ሰሎሜ በቅዱስ መጽሐፍ ተዘክረዋል:: ቅዱስ ዮሴፍ እድሜው 75 ሲሆን ሚስቱ ማርያም ሞተችበት::
✏ከጥቂት ወራት በሁዋላም በመንፈስ ቅዱስ ድንግል ማርያምን ሊያገለግል ተመረጠ:: "እጮኛ" የሚለውም ለዛ ነው:: (ለአገልግሎት ነው የታጨው) እመቤታችን ለአረጋዊ ዮሴፍ በ2 ወገን ልጁ (ዘመዱ) ናት::
1.የሚስቱ ማርያም የእህት (የሐና) ልጅ ናት::
2.የቅድመ አያቱ የአልዓዛር የልጅ ልጅ ናት::
✏ደጉ ሽማግሌ ቅዱስ ዮሴፍ ምን ቢያረጅ እመቤታችንን ለማገልገል አልደከመውም:: አብሯት ተሰደደ:: ረሃብ ጥማቷን: ጭንቅና መከራዋን: ሐዘንና ችግሯን ተካፍሏል:: ከእመ ብርሃንና አምላክ ልጇ ጋር ለ16 ዓመታት ኑሯል::
✏ከእነዚህ ዘመናት በሁዋላም በ16 ዓ/ም : በተወለደ በ91 ዓመቱ ሲያርፍ ጌታችን "ሥጋሕ አይፈርስም" ብሎ ቃል ኪዳን ገብቶለታል::
"ኢየሱስ ክርስቶስ በከመ አሠፈዎ ኪዳነ::
ኢበልየ በመቃብር ወኢሂ ማሰነ::
እስከ ዮም በድኑ ሐለወ ድኁነ::" እንዳለ መጽሐፈ ስንክሳር::
✅ ቅዱስ ጢሞቴዎስ ዘአልቦ ጥሪት
✏ይህ ቅዱስ አባት በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን የእስክንድርያ ፓትርያርክ የነበረ አባት ነው:: ዘመነ ሲመቱም ከ377 እስከ 387 ድረስ ለ10 ዓመታት ነው:: በእነዚህ ዘመናቱ "ዘአልቦ ጥሪት" (ገንዘብ የሌለው / ነዳዩ አባት) ነበር የሚባለው:: ገንዘብንና ዓለምን የናቀ አባት ነበር::
✏ቅዱስ ጢሞቴዎስ የቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ደቀ መዝሙር እንደ መሆኑ ከመንፈሳዊ አባቱ መልካም ሕይወትን ወርሷል:: ምሥጢራትንም አጥንቷል:: በዘመኑ የአርዮስ ውላጆች ቤተ ክርስቲያንን ያስቸግሩ ነበርና ከእነርሱ ጋር ተዋግቷል:: ምዕመኑንም ከተኩላዎች ይጠብቅ ዘንድ ተግቷል::
✏በ381 ዓ/ም በቁስጥንጥንያ ጉባዔ በተደረገ ጊዜ ማሕበሩን በሊቀ መንበርነት መርቷል:: ለመቅዶንዮስ : ለሰባልዮስና ለአቡሊናርዮስ ኑፋቄዎችም ተገቢውን ምላሽ ሰጥቶ አውግዟል:: ቅዱስ ጢሞቴዎስ ዘአልቦ ጥሪት በቅድስና ተመላልሶ በ387 ዓ/ም በዚህች ቀን ዐርፏል::
✥ ፈጣሪ ከአቡነ ሰላማ : ከአረጋዊ ዮሴፍና ከቅዱስ ጢሞቴዎስ በረከትን ያሳትፈን::
🚩ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.ቅዱስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን
2.ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ (የድንግል ማርያም ጠባቂ)
3.ቅዱስ አባ ጢሞቴዎስ (ዘአልቦ ጥሪት)
4.አባ ሮዲስ
🚩ወርሐዊ በዓላት፦
1.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ
2.አቡነ ሐብተ ማርያም ጻድቅ
3.አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ
4.ቅዱሳን ሰማዕታተ ናግራን
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
397
✅ስንክሳር
🚩ሐምሌ 25
✅ቅዱስ መርቆሬዎስ ሰማዕተ ሮሜ
✏ቅዱሱ ከቀደምት ሰማዕታት አንዱ ሲሆን በ200 ዓ/ም አካባቢ እንደ ተወለደ ይታመናል:: ወላጆቹ ከጣዖት አምልኮ ወደ ክርስትና የመጡት በተአምር ነው:: ስማቸውም #ታቦትና_ኖኅ ይባላሉ:: ቅዱሱ መጀመሪያ " #ፒሉፓዴር" ይባል ነበር:: ትርጉሙ "የአብ ወዳጅ" እንደ ማለት ነው::
✏ቀጥሎም " #መርቆሬዎስ" ተብሏል:: ይኸውም " #የኢየሱስ_ክርስቶስ_አገል ጋይ" እንደ ማለት ነው:: በጦርነት ኃይለኛ: በመልኩ ደመ ግቡና ተወዳጅ የነበረው ቅዱስ መርቆሬዎስ ስለ ክርስትናው መከራን የተቀበለው በ20 ዓመቱ ነው:: ዘመኑም በዳኬዎስ ቀዳማዊ ነው::
✏ስለ ሃይማኖቱም ለ5 ዓመታት መከራን ታግሦ በ25 ዓመቱ (ማለትም በ225 ዓ/ም) ሕዳር 25 ቀን አንገቱን ተከልሏል:: በዓለማቀፍ ደረጃም ቅዱስ መርቆሬዎስ ክብሩ ከሊቀ ሰማዕታት ቀጥሎ የሚገኝ ነው::
✏በተለይ ዛሬ ሐምሌ 25 ቀን ቅዳሴ ቤቱ ሲሆን ቤቱ በታነጸበት ሁሉ ተአምራትን ያደርጋል:: ስለዚህ ነገር ታሪክ ብቻ ሳይሆን እኛ ኃጥአንም ምስክሮች ነን:: ጋሹ አምባን ጨምሮ ዛሬም ቅዱሱ ድንቆችን ይሠራል::
✅ቅዱስ ኄኖክ ነቢይ
✏ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ኄኖክ ከአባታችን አዳም 7ኛው ደግ ሰው ሲሆን አባቱ #ያሬድ ይባላል:: በእርግጥ ቅዱሱ ሚስት አግብቶ #ማቱሳላና ሌሎች ልጆችን ወልዷል:: አካሔዱ ግን ከእግዚአብሔር ጋር ነበርና ሞትን አላየም::
✏#ነቢዩ_ኄኖክ በ1486 ዓ/ዓ የመጀመሪያውን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ( #መጽሐፈ_ኄኖክን) ጽፏል:: የዚሕ መጽሐፍ ባለቤት ደግሞ ሃገራችን ናት:: ቅዱሱ ብዙ ሰማያዊ ምሥጢሮችን ተመልክቷል::
✏የእርሱ ሞትን አለመቅመስ #በአቤል ሞት የፈሩትን #ውሉደ_አዳም በተስፋ አነቃቅቷቸዋል::
"በአቤል አፍርሆሙ:
ወበኄኖክ አንቅሆሙ" እንዳለው ሊቁ:: (ዘፍ. 5:24, ኄኖክ. 4:1)
✅ቅድስት ቴክላ ሐዋርያዊት
✏እናታችን ቅድስት ቴክላ በኒቆምድያ ተወልዳ ያደገች: ከአሕዛባዊ እምነት ወደ ክርስትና በሐዋርያው #ቅዱስ_ዻውሎስ አማካኝነት የመጣች እናት ናት:: እርሷ ክርስትናን ከልብ ለሚሹ ሴቶች ሁሉ መሪና ትልቅ ት/ቤት ናት:: ወንጌልን ከሐዋርያው ስትማር ምሥጢሩ እየመሰጣት አንዳንዴ ለ3 ቀናት ምግብ አትቀምስም ነበር::
✏እጅግ ቆንጆ ወጣትና የሃብታሞች ልጅ ብትሆንም ስለ ክርስቶስ ሁሉን ለመናቅና መስቀሉን ለመሸከም አልተቸገረችም:: ከኒቆምድያ እስከ አንጾኪያ ወንጌልን ሰብካለች:: ወላጆቿን ጨምሮ ብዙ ነፍሳትን አድናለች:: በፈንታውም ብዙ መከራን ተቀብላ በዚህ ቀን ዐርፋለች:: ቤተ ክርስትያን " #ሐዋርያዊት" ብላ ታከብራታለች::
✅ ቅዱስ አበከረዙን ጻድቅ ወሰማዕት
✏ስም አጠራሩ የከበረ ታላቁ #አባ_አበከረዙን ወደ ክርስትና የተጠራው ከሽፍታነት (ስርቆት) ሕይወት ነው:: ከአጋሮቹ ጋር ገዳም ለመዝረፍ ሒደው አንድ ባሕታዊ ከማታ 12:00 እስከ ጧት 12:00 ሲጸልይ አይተው ተጸጽተው ንስሃ ገብተዋል::
✏አበከረዙን ግን ዓለምን ንቆ በምናኔ ለ7 ዓመታት ተጋድሏል:: ነገር ግን ሰማዕት ለመሆን ከነበረው ፍቅር የተነሳ ከገዳም ወደ ከሃድያን ነገሥታት ሃገር ሔዶ ስመ ክርስቶስን ሰብኩዋል:: በእርሱ ላይ ከደረሱ ስቃዮች ብዛት የተነሳ ከሥጋው: ከአጥንቱና ከደሙ የተረፈለት የለም::
✏እንዲያውም አንዴ በዓየር ላይ ዘቅዝቀው ሰቅለው ደሙ በአፍና በአፍንጫው እየጐረፈ ለ10 ቀናት ቆይቷል:: በወቅቱ የመኮንኑ ሴት ልጅ እየመጣች ያለ ርሕሪሔ ታሰቃየው ነበርና እርሷን መልአክ ወርዶ ቀሥፎ ገደላት::
✏እርሱ በተሰቀለ በ22ኛው ቀን: እርሷ በተቀበረች በደግሞ በ12ኛው ቀን ከተሰቀለበት አውርደውት ከሞት አስነስቷታል:: ታላቁ አበከረዙንን በዚህች ቀን ብዙ አሰቃይተው: ወገቡን ሰብረው: አንገቱንም ሰይፈው ገድለውታል::
✅ቅዱስ ዱማድዮስ ሶርያዊ
✏ለቤተ ክርስቲያን በንጹሕ ሕይወታቸው ካበሩላት ዐበይት ቅዱሳን አንዱ #ቅዱስ_ዱማድዮስ ነው:: እርሱ ወደ ክርስትና የመጣው ከባዕድ አምልኮ ሲሆን መሪው #መንፈስ_ቅዱስ ነው:: ጣዕመ ሕይወቱን ሲሰሙት ዕዝነ ልቡናን ደስ ያሰኛል::
✏ገና በወጣትነቱ እንደ #ሐዋርያት ሰብኮ አሕዛብን አሳምኗል:: እንደ #ጻድቃን አካሉ አልቆ አጥንቶቹ እስኪታዩ ተጋድሏል:: እርሱ #ድንግል: #ንጹሕ: #መነኮስ: #ባሕታዊና #ካህን ነው:: ግን ውዳሴ ከንቱን አምርሮ ይጠላል:: በዚህ ምክንያት ካደረበት አይውልም: ከዋለበትም አያድርም::
✏እርሱ በጸሎቱ የተዘጉ ማሕጸኖችን ከፍቷል:: ዕውራንን አብርቷል:: ለምጻሞችን አንጽቷል:: አንካሶችን አርትቷል:: በፈጣሪው ኃይል ፈሳሽ ወንዝን አቁሟል:: እንደ ገናም እንደ ነበረው መልሶታል::
✏የቅዱስ ዱማድዮስ መጨረሻው ደግሞ #ሰማዕትነት ነው:: በበዓቱ ውስጥ ሳለ ከደቀ መዝሙሩ ጋር ክፉዎች በድንጋይ ወግረው ገድለውታል:: ድንጋዩም የኮረብታ ያህል ነበር:: ልክ በዓመቱ በዚህች ዕለት ምዕመናን ሥጋውን አፍልሠዋል::
✥ቸር አምላክ ከነቢያት: ሐዋርያት: ጻድቃንና ሰማዕታት ክብርን ያሳትፈን::
🚩ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፦
1.ቅዱስ መርቆሬዎስ ሰማዕት (ቅዳሴ ቤቱ)
2.ቅዱስ ኄኖክ ነቢይ (ዕርገቱ)
3.ቅድስት ቴክላ ሐዋርያዊት
4.ቅዱስ አበከረዙን ታላቁ (ጻድቅና ሰማዕት)
5.ቅዱስ ዱማድዮስ ሶርያዊ (ጻድቅና ሰማዕት)
6.ቅድስት ኢላርያ ሰማዕት
7.ቅዱሳት ቴክላ ወሙጊ ሰማዕታት
8.ቅዱስ እንዲኒና ሰማዕት
9.አባ ይስሐቅ ሰማዕት
10.አባ ሕጻን ሞዐ ዘደብረ ሊባኖስ
11."25,000" ሰማዕታት (የአትሪብ /ግብፅ/ ሰዎች)
🚩ወርሐዊ በዓላት፦
1.ቅዱስ ይሁዳ ሐዋርያ (ከ72ቱ አርድእት)
2.አቡነ አቢብ (አባ ቡላ)
3.ቅዱስ አባ አቡፋና ጻድቅ
✅ዘአቅረብኩ ማኅሌተ አዘኪርየ አእላፈ። እምእለ ተጸምዱከ ዘልፈ። ለለአነብብ ተወከፍ ዘንዴትየ መጽሐፈ። እንተ ረሰይከ እግዚኦ ጸሪቀሀ መበለት ውኩፈ። እምእለ አብኡ ብዑላን ዘተርፈ። ነቢያት ቅዱሳን ወሐዋርያት ሰባኪያን። ሰማዕት ወጻድቃን ወመላእክት ትጉሃን። ደናግል ዓዲ ወመነኰሳት ኄራን። ባርኩ ባርኮ ጉባኤ ዛቲ መካን። እስከ አረጋዊ ልሒቅ ወንኡስ ሕፃን። ለዘጸሐፎ በክርታስ ወለዘአጽሐፎ እንዘ ይደርስ። ለዘአንበቦ ወለዘተርጐሞ በልሳን ሐዲስ። ወለዘሰምዐ ቃሎ በዕዝነ መንፈስ። በጸሎተ እሙ ማርያም ዐራቂተ ኵሉ እምባእስ። ኅቡረ ይምሐረነ ኢየሱስ ክርስቶስ።
