en
Feedback
ህልምህን ኑረው_Live your dream

ህልምህን ኑረው_Live your dream

Open in Telegram

የቻናል አላማ ሰዎች ራዕያቸውንና አላማቸውን ለይተው በማወቅ ለተፈጠሩበት መልካም ስራ ማዋልን እና አስተሳሰባቸውን በመለወጥ የሚፈልጉትን ህልም እንዴት ማሳካት እንደሚችሉ ፣ የአሸናፊነት ልማድ፣የአእምሯችንን ሚስጥራዊ አሰራር የምናውቅበት እና የስኬታማ ሰዎች ተሞክሮም እናቀርባለን። ዩቱዩቭ: https://www.youtube.com/@Live_Your_Dream2112 https://t.me/Attitudeplc

Show more
499
Subscribers
No data24 hours
No data7 days
+3730 days
Posts Archive
መሱዓትነትህን ምረጥ! ለማን ማንነትህን አሳልፈህ መስጠት እንዳለብህ እወቅ፤ ለምን እስከመጨረሻው እንደምትፋለም ተገንዘብ፤ እንዴት ከመሱዓትነትህ ቦሃላ ለድል እንደምትበቃ አስቀድመህ መርምር። ትግልህ ለምንድነው? ለማነው? ከመሱዓትነትህ ጀርባ ያለውስ ትልቁ ምክንያት ምንድነው? በሰዎች ዘንድ ተወዳጅነትን ማግኘት? እራስን ብቁ አድርጎ የተሻለ ስፍራ መገኘት? ስኬትን ለሌሎች ማጋራት? ትክክለኛውን ማንነት ማሰየት? ምክንያትህ ምንም ቢሆን ኋላ ለማይቆጭህ ነገር መታገልህን እርግጠኛ ሁን። ስንት ዋጋ የከፈልንላቸው ሰዎች እንደ ቀልድ ጥለውን ሲሔዱ አይተናል፤ የተመቸንን ስራ ትተን የጀመርነው የግል ስራ አክስሮ አንገት ሲያስደፋን ተመልክተናል፤ ከወዳጅ ዘመድ የተለየንለት ሰው ብቻችንን ጥሎን የሔደበት አጋጣሚ አይረሳንም። አዎ! ጀግናዬ..! መሱዓትነትህን ምረጥ! "በእርግጥ ይህ ሰው የእኔ ውድ ጊዜና ውድ ስሜት ይገባዋል? የእውነት ሁሉን ትቼ ቀንና ሌሊት የምለፋበት ነገር ትርጉም የሚሰጠኝ ነውን? የምርም ዛሬ በሰዎች እየተተቸውና እየተሰደብኩ የምፈፅመው ተግባር ከህይወት አላማዬ ጋር ይገናኛልን? በእርግጥ ከቤተሰብ ርቄ ባዕድ አገር እድሜዬን የምፈጅበት ጉዳይ ዋጋ ያለው ነገር ነውን?" ብለህ እራስህን ጠይቅ። ከእያንዳንዱ ጥያቄህ ጀርባ አሳማኝ መልስ ጠብቅ። የሰው ልጅ በቅጡ ላልተረዳው አጀንዳ ጊዜውን፣ ንብረቱን ወይም ሴሜቱን አይደለም ህይወት እንኳን ሲሰዋ ቆይቷል። የትግልህን ምክንያት ካላወክ ባትታገል ይሻልሃል፤ ለምን እንደምትለፋ ግንዛቤው ከሌለህ እንዲሁ ቁጭ ብለህ በቂ ምክንያት ብታፈላልግ ይጠቅምሃል። አዎ! ህይወት አጭር ነች። እንዲሁ እንደዋዛ ማንም በፈለገው አጀንዳ እየነዳን የምናባክናት አይደለችም። እግዚአብሔር ሰውን የፈጠረበት ምክንያት አለው። አንድም በተሰጠው መክሊት ፍሬን አፍርቶ ለሌላው እንዲተርፍ፣ ሌላም ስሙን ቀድሶ ክብሩን እንዲወርስ። እያንዳንዱ ሰው እዳ አለበት። ላጠፋው ጥፋት፣ ለበደለው በደል፣ ላስለቀሰው እንባ፣ ለተሳደበው፣ ሰውን ላሸማቀቀው፣ በአጭሩ ላስቀረው ለእያንዳንዱ መጥፎ ተግባሩ ክፍያውን ይቀበላል። እናም ሁለቴ ዋጋ ከመክፈል እራስህን ጠብቅ። ውዱን የሰው ልጅ ለመበደል መሱዓትነት ባለመክፈል ከዳግም ቅጣት እራስህን አድን። ዛሬህን ነገ ስታስበው የማይቆጭህ ውድ ነገር ላይ አሳልፈው። ከእያንዳንዶቹ ተግባሮችህ ጀርባ ምክንያት ሲኖር ህይወትህ በሙሉ ትርጉም እንደሚኖረው ተገንዘብ። ═════════❁✿❁ ═════════

የብቸኝነትንና ብቻ የመሆንን ልዩነት እወቅ (ክፍል ሁለት) (“ራስን ማሸነፍ” ከተሰኘው የዶ/ር ኢዮብ ማሞ መጽሐፍ የተወሰደ) . . . ካለፈው የቀጠለ በትናንትናው “ፖስቴ” ለብቻ መሆን ማለት ብቸኝነት እንደሆነ የማሰብን ሁኔታ እና ስህተት ተመልክተናል፡፡ የዛሬው ሃሳብ የሚያተኩረው ይህንን አመለካከት እንድናዳብረ የሚያደርጉንን አመለካከቶች በመለየትና ሁኔታውን ካልቀረፍነው የሚያስከትለው መዘዝ ላይ ነው፡፡ መንስኤው 1.  ባህላዊ ተጽእኖ ከሃገራችን መልካም ባህሎች አንዱ ማሕበራዊ ግንኙነታችን መሆኑን ሁላችንም እናውቀዋለን፡፡ ከሰው ጋር ወጥተን፣ ከሰው ጋር እንገባለን፡፡ ስንበላ ከሰው ጋር ነን፣ ስንዝናና ከሰው ጋር ነን፣ በስራ መስክ ከሰው ጋር ነን፣ ከስራ ወጥተን ወደቤት ስንሄድ ከብዙ ሰው ጋር ነን፡፡ እቤትም ቢሆን ብዙ ሰው ነው የሚጠብቀን፡፡ ይህንን መልካም ባህል ተቀብሎ ያደገው ማንነታችን ሁኔታውን ሚዛናዊ ካላደረገው ለብቻ መሆንን እንደ ማሕበራዊ ቀውስ የማሰብ ዝንባሌ ሊኖረው ይችላል፡፡ በግርግር ውስጥ ተወልዶ በዚያው አይነት ግርግር ውስጥ ያደገ ሰው ከዚያ ውጪ ሌላ አለም እንዳለ ላያውቀውም ይችላል፡፡ ከዚያም በተጨማሪ ለብቻው ሲታይ፣ “ምነው ብቻህን?” የሚል ሃሳብ በሰዎች ሲነገረው ይህ ሰው የሚያዳብረውን አመለካከት መገመት አያዳግትም፡፡ 2.  ከህሊና ወቀሳ የመዳን ሙከራ ማንኛውንም በሕይወታችን የማንፈልገውን አጉል ስሜት ለማስወገድ የተለያዩ መንገዶችን የመጠቀም ምርጫው አለን፡፡ የህሊና ወቀሳም ሲኖርብን ከዚያ ወቀሳ ለመዳን በትክክለኛው መንገድ ስህተታችንን አስበንና ትክክለኛውን እርምጃ ከመውሰድ ይልቅ ከአንዱ ግርግር ወደሌላኛው በማለፍ “በመንጫጫት” ለመርሳት እንሞክራለን፡፡ እውነተኛው ችግር በውስጠኛው ማንነታችን ተንሰራፍቶ እየጮኸ፣ ከውጪ ያለውን የድምጽ መጠን በመጨመር ለጊዜው የውስጠኛውን ጩኸት የማንሰማበትን ሁኔታ እንፈጥራለን፡፡ ይህ ሙከራ ለጊዜው ልክ እንደማደንዘዣ መድኃኒት ቢሰራልንም ዘላቂ መፍትሄ ግን አይሰጠንም፡፡  3.  የራእይ አለመኖር ባለራእዮች ካላቸው አስገራሚ ባህሪይ አንዱ ለብቻቸው በመሆን ስለራእያቸው ማሰብ፣ ማቀድና ከራሳቸው ጋር መወያየት ዋነኛው ነው ብንል አንሳሳትም፡፡ አንድ ሰው በቅጡ ለማሰብና ለማቀድ ለብቻመሆንን የሚጠይቅ ራእይ ከሌለው በየእለቱ ብቅ ስላለው ክስተት ለማውራት ከዚህና ከዚያ ሲራወጥ ራሱን ያገኘዋል፡፡ አአምሮው ላይ የከበደ የወደፊት እቅድ ስለሌለው ያንን በራእይ ሊሞላ የሚገባውን ባዶ ቦታ የሚሞላ ሚዛነ-ቢስ ማህበራዊ ትርምስ ውስጥ ራሱን ያገኘዋል፡፡ እውነታው አጭርና ግልጽ ነው - ራእይ ያላቸው ሰዎች ለብቻቸውመሆን የሚናፍቃቸው ሰዎች ሲሆኑ፣ በተቃራኒው ራእየ-ቢሶች ደግሞ ብቻ መሆንን እንደብቸንነት የመቁጠር ዝንባሌ አላቸው፡፡ በግርግር ውስጥ ተወልዶ በዚያው አይነት ግርግር ውስጥ ያደገ ሰው ከዚያ ውጪ ሌላ አለም እንዳለ ላያውቀውም ይችላል፡፡ መዘዙ 1.  ውጤታማ አለመሆን ለብቻው የማይሆን ሰው ለማሰብ ጊዜ ያጣ ሰው ነው፡፡ ለማሰብ ጊዜ ያጣ ሰው ደግሞ በመጀመሪያ የትናንትናውን ጉዞ የመገምገሚያ ጊዜ ያጣል፡፡ ይህ የግምገማ ጊዜ የሌለው ሰው ከስህተቱ የማይታረም ሰው ነው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ለነገው የሚረዳውን የፈጠራ ብቃቱን የተነጠቀ ሰው ነው፡፡ ከፈጠራ ብቃት ውጪ ደግሞ የወደፊት ውጤታማነት የሕልም ጉዳይ ነው፡፡ለብቻ በመሆን የማሰብ እድል ከየት እንደመጣን፣ የት እንዳለን፣ ወደ የት መሄድ እንደምንፈልግና በምን መልኩ ወደዚያ መድረስ እንደምንችል ለማሰላሰል ጊዜ ይሰጠናል፡፡ ይህንን የግል ጊዜ ማጣት ማለት ለስኬታማነት ያለንን እድል መነጠቅ ማለት ነው፡፡ ከዚህ መሰረታዊ ልማድ ውጪ ወደተሻለ ቦታ ያደገ ሰው አለ ብሎ ለማሰብ አስቸጋሪ ነው፡፡ 2.  የአእምሮ መታወክ ቀኑን በጫጫታና በግርግር ጀምሮ በዚያው ሁኔታ የጨረሰ ሰው የሌሊት ሕልሙም ከዚያው የተለየ እንደማይሆን መገመት አያስቸግርም፡፡ ይህ ለአእምሮ እረፍት የሚያሳጣ ሁኔታ የሚፈጥረውን መታወክ የምናውቀው አረፍ ብለን ለማሰብ ጊዜ ስናገኝ ነው፡፡ ተቃራኒውን የተረጋጋ የሕይወት ዘይቤ ቀምሰነው ካላወቅን ከለመድነው የሁከት ዘይቤ ውጪ ያለ አይመስለንም፡፡ አንድን ጣፋጭ ጣእም ከዚህ በፊት ቀምሶ የሚያውቅ ሰው ብቻ ያንን ጣእም በድጋሚ ይፈልገዋል፡፡በጸጥታ ውስጥም የሚገኘውን የአእምሮ መረጋጋትና የትኩረት ብቃት የቀመሰ ሰው ብቻ ደግሞ ደጋግሞ ይፈልገዋል፡፡ 3.  የትክክለኛ ውሳኔ ችግር ሕይወት በውሳኔ የተሞላች ጉዞ ስለሆነች በየእለቱ የተለያዩ ውሳኔዎችን ከመወሰን አናመልጥም፡፡ ከእነዚህ ውሳኔዎች መካከል አንዳንዶቹ የኑሮአችንን አቅጣጫ ሊለውጥ የሚችል ተጽእኖ አላቸው፡፡ ለእነዚህ ውሳኔዎች ትክክለኛነት መዋጮ ከሚያደርጉ ልምምዶች አንዱ ለብቻ የመሆንና ሁኔታዎችን በተረጋጋ ሁኔታ የማሰብ ልምድ ነው፡፡ በዙሪያችን ካለው ግርግርና ጫጫታ መለስ ብለን የምናስብበትና ግራና ቀኙን የምናይበት የእረፍትና የብቻጊዜ ያስፈልገናል፡፡ ይህ አስፈላጊ ልምምድ ሲጎድለን አጥርተን ለማሰብና ትክክለኛ ውሳኔዎች ላይ ለመድረስ ያለን ብቃት ይደክማል፡፡ በአጭሩ፣ ለብቻቸው በመሆን የማያስቡ ሰዎች የውሳኔዎቻቸው ጥራት አናሳና ለስህተት የተጋለጠ ነው፡፡  በዙሪያችን ካለው ግርግርና ጫጫታ መለስ ብለን የምናስብበትና ግራና ቀኙን የምናይበት የእረፍትና የብቻ ጊዜ ያስፈልገናል፡፡ ነገ ይቀጥላል . . .

አንባቢ ሁሉ አዋቂ አይደለም፡፡ ብዙ መፅሐፍትን የገለጠ ሁሉ የማገናዘብ አቅሙ ያደገ ነው ማለት አይቻልም፡፡ መረጃ ያለው ሁሉ ዕውቀት አለው ለማለት አያስደፍርም፤ የመፅሐፍትን ታሪክ የሚተርክ ሁሉ ሕይወቱ የተለወጠ፤ አስተሳሰቡ የዘመነ፤ አኗኗሩ የረቀቀ ነው ማለት አይቻልም፡፡ አንባቢ ሁሉ ጥበበኛ ነው የሚል ድምዳሜ የለም፡፡ ማንበብ ወደጥበብ ጎዳና መሄጃ መስመር ሊሆን ይችላል፤ ነገር ግን በራሱ አያደርስም፡፡ አድራሹ የራስህ ሃሳብና አስተሳሰብህ፤ ምግባርህና ተግባርህ ብቻ ነው፡፡ ምንም ነገር ለማድረግ ብልሃት ወሳኝ ነው፡፡ ኑሮ ዘዴ ከሌለው የተሳካ አይሆንም፡፡ ማንበብም ብልሃት ከሌለው ማነብነብ ነው የሚሆነው፡፡ አዎ መፅሐፍ የምናነብበት መንገድ ወሳኝ ነው፡፡ የብዙዎች አንባቢ ችግር አንድም የአነባበብ ዘዴ ችግር ነው፡፡ አንድም ያነበቡትን የመርሳት፤ አንድም የጨበጡትን ቁምነገር በተግባር ወደሕይወት የማምጣትና ራስን የመለወጥ ችግር ነው፡፡ ሱሳን ሂል (Susan Hill) የተባለች ፀሐፊ ‹‹ፈጣን ንባብ የምናነበውን መፅሐፍ ቁምነገር አዕምሯችን ላይ ለማስቀመጥ አያስችለንም፡፡ ይዘቱን ተረድተን ራሳችንን እንድንገነባ አይፈቅድልንም፡፡›› ትለናለች፡፡ አሜሪካዊው ኢንቬስተርና የስራ-ፈጣሪ ናቫል ራቪካንት (Naval Ravikant) ደግሞ ‹‹ከምታነበው መፅሐፍ ምርጥ ቁምነገር የምትጨብጠው ረጋ ብለህ ስታነብ ነው (The smarter you get, the slower you read)›› ይለናል፡፡ አንድን መጽሐፍ ቶሎ አንብቦ መጨረስ ጀግና አያደርግም፤ ወይም ብዙ ጊዜ ፈጅቶ መጨረስም ቀርፋፋ አያስብልም፡፡ እንዲገባን የምናነበው መፅሐፍ ጊዜ ላይ ሳይሆን ይዘቱ ላይ ነው ጉዳዩ ያለው፡፡ ያነበብነውን መፅሐፍ ምን ያህል ፐርሰንት እናስታውሰዋለን?? አዎ ዋናው ጥያቄ ያነበብነውን መፅሐፍ ተረድተነዋል ወይ የሚለው ላይ ነው፡፡ እንደገናም የወደድነውንና ያሳመነንን ሃሳብ ወደሕይወታችን አምጥተን ተጠቅመንበታል ወይ የሚለው ሌላኛው ጥያቄ ነው፡፡ ሺ መፅሐፍ አንብበህ አንድ ጠብ የሚል ቁምነገር ሕይወትህ ላይ ካልጨመርክ ማንበብህ ምንም ፋይዳ የለውም፡፡ የብዙ አንባቢ ችግር ያነበባቸውን መፅሐፍት መርሳት ነው፡፡ ዛሬ ዛሬ ያነበቡትን ማስታወስ መቻል እንደብርቅ የሚታይ ክህሎት ሆኗል፡፡ ብዙ ሰው የመርሳት አባዜ ተጠናውቶታል፡፡ አብዛኞቻችን ያነበብናቸውን ብዛት ያላቸውን መፃሕፍት እንዘነጋለን፡፡ ርዕሳቸውን ብናስታውሰውም ቁምነገራቸውን ትዝ አይለንም፡፡ በመፅሐፍቱ ውስጥ ያሉት ገፀባህሪያት በአዕምሯችን ብልጭ-ድርግም ቢሉም መልዕክታቸውና ዋና ይዘታቸው ግን ብን ብሎ ይጠፋል፡፡ ያነበቡትን የመርሳት በሽታ የብዙ አንባቢዎች ህመም ነው፡፡ ጥቂቶቻችን ያነበብነውን ብናስታውስም፤ ቁምነገሩን ብንገነዘብም ሃሳቡን ወደሕይወት እልፍኛችን አንጋብዘውም፡፡ የምናነበውን መፅሐፍ ይዘት ወደአዕምሯን አስገብተን ፍሬና ገለባውን አንለይም፡፡ የሚስማማንን ሃሳብ ከራሳችን ሃሳብ ጋር አዋህደን አንጠቀምበትም፡፡ የማይጠቅመንን የማስወገድ፤ የሚስማማንን የመውሰድ ብልሃት ያንሰናል፡፡ እናግበሰብሳለን እንጂ እንደአግባቡ የመጠቀም ክህሎት አላዳበርንም፡፡ ሲኖረን በገፍ የማድፋፋት፤ ሲያንሰን በጭንቅ የማብቃቃት ልማድ ነው ያለን፡፡ መካከሉ ላይ የለንበትም፡፡ በአንዱ ጥግ ተውጠናል፡፡ አክራሪነት! ወግ አጥባቂነት! ጥጋዊነት፣ የእኔ-ብቻነት! አንድ-ጎንነት! ወዘተ መገለጫዎቻችን ሆነዋል፡፡ በዓመት ውስጥ መቶ መፃሕፍትን አንብበን በሕይወታችን ላይ ለውጥ የማናመጣ ከሆነ ማንበባችን ትርጉም የለውም፡፡ ‹‹ቄሱም ዝም፤ መፅሐፉም ዝም›› ከሆነ ካላነበበው የምንሻልበት ምንም ነገር የለም፡፡ በባህሪያችን ላይ፣ በአስተሳሰባችን ላይ፣ በአካሄዳችን ላይ፣ በዓላማችን ላይ፣ በስራችን ላይ፣ በአነጋገራችን ላይ፣ ወዘተ ላይ የሚታይ ለውጥ ከሌለ መፅሐፉን ገልጠን ጨረስን እንጂ አላነበብነውም፡፡ መፅሐፉን አንበብን የራሳችንን ሃሳብ ማንበብ ካልጀመርን፤ በሃሳብ የቱ ጋር እንደቆምን ካላወቅን፣ ምኑ ጋር አስተሳሰባችን እንደተዛነፈ ካልተረዳን ካነበብነው ያተረፍነው ነገር የለም ማለት ነው፡፡ የምናነበው ራሳችንን እንድናነብ ካልረዳን ባናነብ ይሻላል፡፡ ወዳጄ ሆይ.... የምታነበው ለመለወጥ ከሆነ እያነበብክ አስብ፤ እያሰብክ አንብብ፡፡ ረጋ ብለህ ማንበብን ተለማመድ፡፡ የምታነበው ለራስህ እስከሆነ ድረስ እስኪገባህ ድረስ አንብብ፡፡ ቶሎ ለመጨረስ ብለህ መፅሐፍ ማንበብ አትጀምር፡፡ ፈረንጆቹ ስኬታማ ንባብ “Metacognition” ይፈልጋል (Successful reading requires metacognition) ይላሉ፡፡ Metacognition ማለት ምን ማለት መሰለህ... ስታነብ የምታነበውን እያሰብክ፤ ሃሳቡ ላይ ያለህን ሃሳብ እየተነተንክና በማስታወሻ ደብተርህ እየከተብክ፤ የእያንዳንዱን ምዕራፍ ዋና ሃሳብና ማጠቃለያ ሃሳብ እያስቀመጥክ፤ የማትስማማበትን ሃሳብ እስከነምክንያትህ እየዘረዘርክ፣ ጥያቄ የፈጠረብህን ሃሳብ መላልሰህ እያሰብክ፣ ያገኘኸውን መልስም እየፃፍክ፤ ከማንበብህ በፊት ያለውን ሃሳብህንና መፅሐፉን ካነበብክ በኋላ ያገኘኸውን አዲሱን ሃሳብ እያነፃፀርክና እያዋሃድክ፤ የመፅሐፉን አጠቃላይ ግምገማህን ደካማና ጠንካራ ጎን እየገለፅክ አንብብ.. ማለት ነው፡፡ በዚህ መንገድ ካነበብክ ያነበብከውን ቁምነገር አትረሳም፤ ባነበብከው መፅሐፍም ትለወጥበታለህ፡፡ ያነበብካቸውን መፃሕፍት ብቻ ሳይሆን የጨበጥካቸውን ቁምነገሮችና የተለወጥክባቸውን ሃሳቦች ትቆጥርበታለህ፡፡ እያነበቡ ማሰብ፤ እያሰቡም ማንበብ! እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)

የብቸኝነትንና ብቻ የመሆንን ልዩነት እወቅ (ክፍል አንድ) (“ራስን ማሸነፍ” ከተሰኘው የዶ/ር ኢዮብ ማሞ መጽሐፍ የተወሰደ) በስነ-ልቦናው አለም፣ መረጃ-ተኮር ማሕበራዊ ተጽእኖ ተብሎ ሊተረጎም የሚችል፣ በእንግሊዝኛው “ሶሽያል ፕሩፍ” (Social Proof) የተሰኘ ሃሳብ አለ፡፡ ይህ ሁኔታ የሌሎችን ሰዎች ተግባር ተመልክተን እኛም ያንኑ ሰዎቹ የሚያደርጉትን ተግባር ብናደርግ ትክክለኛ እንደሆንን እንደማስረጃ የመጠቀም ዝንባሌ ነው፡፡ ይህንን ዝንባሌ በሌላ ስነ-ልቦናዊ አባባል ሲገልጹት በብዙሃኑ (በመንጋው ጋጋታ) የመነዳት ዝንባሌ (Herd Instinct) ይሉታል፡፡ ወደ አንድ የሙዚቃ ትርዒት (Concert) በመሄድ ላይ ነህ፡፡ መስቀለኛ መንገድ ላይ ስትደርስ፣ አንገታቸውን ቀና አድርገው ወደ ሰማይ የሚመለከቱ በርካታ ሰዎችን ታገኛለህ፡፡ ምንም ሳታስብበትና ሳታንገራግር አንተም ወደላይ መመልከት ትጀምራለህ፡፡ ለምን? ማሕበራዊ ተጽእኖ (Social Proof)፡፡ በሙዚቃው ትርዒት መካከል አርቲስቱ አስገራሚ ችሎታውን ሲያሳይ አንድ ሰው ማጨብጨብ ይጀምራል፣ በድንገት ተመልካቾች በሙሉ ያንን ሰው በመከተል ማጨብጨብ ይጀምራሉ፡፡ አንተም እንደዚያው ማድረግ ትጀምራለህ፡፡ ለምን? ማሕበራዊ ተጽእኖ (Social Proof)፡፡ ከሙዚቃው ትዕይንት በኋላ ካፖርትህን ወደሰቀልክበት አካባቢ ካፖርትህን ለመውሰድ ሄድክ፡፡ በፊትህ የቀደሙህ ሰዎች ካፖርታቸውን ሲወስዱ በዚያ በተቀመጠው ሳህን ላይ ሳንቲም ጣል እያደረጉ ሲሄዱ አየህ፡፡ ካፖርት እዚያ ሰቅሎ ለመግባት ምንም ክፍያ እንደማይጠይቅ በሚገባ ታውቃለህ፡፡ ምን ታደርጋለህ? ምናልባት አንተም ሳንቲም ጣል ታደረግ ይሆናል”፡፡ ይህ ሁኔታ ለብቻችን በመሆን የግል አመለካከትን ለማዳበር ከምናደርገው ጥረት ይልቅ ምን ያህል በሰዎች ሃሳብ እንደምንነዳ፣ ወጣ ብለን እንደ አፈንጋጭ ላለመታየትና ሰዎችን ለማስደሰት ምን ያህል ርቀት እንደምንሄድ ጠቋሚ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ብቻ መሆንን እንደብቸኝነት መቁጠር፤ የግል አመለካከትን እንደ ስህተት ማየት - የብዙዎቻችን ችግር! በብቸኝነትና ለብቻ በመሆን መካከል ትልቅ ልዩነት አለ፡፡ አንዳንድ ሰዎች እነዚህን ሁለት ሁኔታዎች ለያይተው አያስቧቸውም፡፡ ስለሆነም፣ ለብቻቸው መሆን ማለት ብቸኝነት ስለሚመስላቸው ካለማቋረጥ በዙሪያቸው ሰዎች ከሌሉ የስሜት ቀውስ ይጫጫናቸዋል፡፡ ለብቻቸው ሆነው በማሰብና በጸጥታ ሁኔታዎችን የመገምገም ጊዜ ስለሌላቸው ከአንዱ ግርግር ወደሌላኛው በመዘዋወር ቀናቶቻቸውን “እንደተንጫጩ” ያባክናሉ፡፡ ከብዙ ሁኔታዎችና ሰዎች ጋር አሳልፈህ፣ ከብዙ ሰዎች ጋር ተዋውቀህ፣ ብዙ ቦታዎች ተጉዘህና ባክነህ ለብቻህ በማሳለፍ ከራስህ ጋር ካልተነጋገርክና ካልተዋወክ ብዙ ሰርተህ ትንሽ የምታተርፍ ከመሆን አታመልጥም፡፡ በአለም ላይ ካሉ ሁሉ ወዳጆችህ ይልቅ የቅርብ የሆነው ወዳጅህ ማንነትህ ነው፡፡ ከዚህ ወዳጅ ጋር መተዋወቅ፣ መነጋገርና ማንም በሌለበት የብቻ ጊዜን ማሳለፍህ ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ ይህንን እውነታ የተገነዘቡ ሰዎች ከመባከንና ከመድከም የተረፉ ሰዎች ናቸው፡፡ ይቀጥላል . . . ዶ/ር እዮብ ማም

አትነጫነጭ! “በየሰበቡ ስትነጫነጭ ከሚሰሙህ ሰዎች መካከል 80 በመቶዎቹ ስለምትነጫነጭበት ነገር ግድም አይሰጣቸው፡፡ 20 በመቶዎቹ ደግሞ ከሰሙህ በኋላ፣ ይሄስ ይገባዋል ብለው ትተውህ ይሄዳሉ” (Unknown source)፡፡ ሰዎች ከአንተ ቀስ በቀስ እየራቁ እንዲሄዱ ከፈለክ፣ በሆነ ባልሆነው መነጫነጭ ቀላሉ መንገድ ነው፡፡ እንነጫነጭ ብንል ለመነጫነጭ ብዙ ምክንያቶች እናገኛለን፡፡ ሆኖም፣ ከመነጫነጭ ይልቅ አመስጋኝ መሆን ይመረጣል፡፡ ከመነጫነጭ ይልቅ አመስጋኝነት እንደሚልቅ የተገነዘቡ አንዳንድ ሰዎች ከተናገሩት . . . •  ከስራ ደክሜ እቤቴ ስገባ ልጆቹ በጣም በመጫወት ይንጫጫሉ፡፡ ለመነጫነጭ አሰብኩ፤ ነገር ግን ለካስ የሚጫወቱትና የሚንጫጩት ጤናማ ስለሆኑ ነው - ተመስገን! •  ባለቤቴ በየእለቱ የተለያዩ ስህተቶቼን በማንሳት እንዳርም ደጋግማ ትነግረኛለች፡፡ አንዳንድ ጊዜ ታበዛዋለች በሚል ሃሳብ መነጫነጭ ያምረኛል፤ ነገር ግን ሚስት ማግባት እየፈለጉ ሚስት ያላገኙ ስንት የግዳጅ ላጤዎች አሉ - ተመስገን! •  ባለቤቴ ስራ ውሎ እቤት ሲገባ ዝም ብሎኝ ይቀመጣል፡፡ ቢደክመውም ለምን አያጫውተኝም በማለት ለመነጫነጭ ይቃጣኝና፤ የስንቶች ባሎች የት እንደሚያመሹ ሳይናገሩ እኩለ ለሊት እንደሚገቡ ትዝ አለኝ - ተመስገን! •  አንዳንድ ጊዜ ወጥቤት ያለው ያልታጠበ እቃ ተከምሮ ሳየው ያለብኝን ስራ አስበውና መነጫነጭ ይጀማምረኛል፤ ነገር ግን ሳስበው እቃ የቆሸሸው እኮ ምግብ ኖሮን ስለበላን ነው፡፡ ስንቶች እንኳን እቃ የሚበላም የላቸውም - ተመስገን! •  አንድ ቀን ብዙ ጉዳዮችን ሳስፈጽም ውዬ ደክሞኝ እቤት ስደርስ ቤቱን ቆልፈውት ሄደው ስለነበረ መግቢያ አጣሁና የመነጫነጭ ስሜት መጣብኝ፡፡ ነገር ግን ሳስበው ስንቱ ጎረቤት ሲሰረቅ የእኛ ቤት ባዶ ሆኖ ውሎ ሳይሰረቅ መቆየቱን አስታወስኩ - ተመስገን! •  አንዳንድ ጊዜ መንግስት ማድረግ ሳይገባው ያደረገብንንና ማድረግ ሲገባው ያላደረገውን እያሰብኩ ሊያነጫንጨኝ ይሞክረኛል፡፡ ነገር ግን በአለም ላይ ካለመንግስት የሚኖሩ ሕዝቦች ትዝ አሉኝ - ተመስገን! •  አንዳንድ ጊዜ ቤተሰቦቼ በዚህ መልኩ ባያሳድጉኝ ኖሮ ስንት ደረጃ በደረስኩኝ እያልኩ በመነጫነጭ ስሜት ሳሰላስል ራሴን አገኘዋለሁ፡፡ ነገር ግን የእኔ ናቸው የሚሏቸው ቤተሰብ ሳይኖራቸው ደስተኛ ሆነው የሚኖሩ ሰዎች እንዳሉ አሰብኩ - ተመስገን! በሰዎች ስህተትም ሆነ ከጠማማ ገጠመኞች የተነሳ በሕይወታችን ላይ የሚደርሱ ተገቢ ያልሆኑ ሁኔታዎች መታረም እንደሚገባቸውና ለዚያም የመታገላችን ሂደት እንደተጠበቀ ሆኖ፣ ከምንነጫነጭባቸው ጊዜያት ይልቅ የአመስጋኝነታችን ጊዜ ቢበዛ ይመረጣል፡፡ ምንጭ:- ዶ/ር ኢዮብ

በአንድ ወቅት አንድ ገበሬ አህያው ጉድጉድ ውስጥ ትገባበታለች፡፡ ጉድጓዱ ሩቅ ከመሆኑ የተነሳ አህያዋ ለመውጣት በእጅጉ ተቸገረች፡፡ በጣም መጮህ ጀመረች፡፡ ባለቤቱም እሷን ለማውጣት ብርቱ ሙከራ አደረገ አልተሳካለትም ፤ አህያዋ አርጅታለችና እዚያው ጉድጓድ ውስጥ ሊቀብራት አሰበ። ጎረቤቶቹንም ጠራና ጉድጓዱን በአፈር መሙላት ጀመረ፡፡ አህያዋ ይህንን ስተመለከት እየቀበራት መሆኑን ተረዳችና እጅጉን አዘነች፡፡ ይሁን እንጂ አፈር በተደፋባት ቁጥር አህያዋ አንድ ነገር ታደርግ ነበር። አፈሩን እያራገፈች ከአፈሩ ውስጥ ብቅ ትል ነበር። በተደጋጋሚ በተደፋው አፈር ላይ መቆም ትጀምራለች። በሂደት በአፈሩ ላይ በቆመች ቁጥር ከነበረችበት ጉድጓድ ከፍ እያለች በመጨረሻም ከጉድጓዱ ውስጥ ሙሉ በሙሉ መውጣት ቻለች፡፡ በሚገርም ሁኔታ አህያዋን ሊቀብሯት የሞከሩት ስዎች ሁሉ በአህያዋ አወጣጥ በእጅጉ ተደነቁ፡፡ የአህያዋ ታሪክ ሁላችንንም ይመለከተናል። የሚጫንብን አፈር  በየጊዜው የሚያጋጥሙንና ዝም ብንላቸው በመጨረሻ ሊቀብሩን የሚችሉ ችግሮች ወይም መሠናክሎች ናቸው፡፡ አፈሩን የሚጭኑት ሰዎች በዙሪያችን ያሉ ሰዎች፣ ነገሮች፣ በህይወታችን ላይ ተፅዕኖ የሚፈጥሩብን አዳዲስ ለውጦች እንዲሁም የራሳችን አፍራሽ ስሜቶች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ጉድጓዱ ደግሞ አሁን ያለንበት ግራ የተጋባንበት! ተስፋ ቢስ የሆንበት፡ መላ ያጣንበት ህይወት ወይም ገጠመኝ ሊሆን ይችላል፡፡ በእርግጥም እኛ ሰዎች በጤናችን! በኢኮኖሚ ህይወታችን፤ በትዳርና ፍቅር ህይወታችን በተለያየ አጋጣሚ ልክ እንደ አህያዋ ጉድጓድ ውስጥ የመግባት ዕድላችን ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ ይሁን እንጂ ጠንካሮች እንደ ጠንካራዋ አህያ ከገቡበት ጉድጓድ ውስጥ መውጣት ሲችሉ አንዳንዶቹ በዚያው ተቀብረው ቀርተዋል፡፡ በህይወታችን ውስጥ ያለው አማራጭ! ወደ ላይ መውጣት አልያም ደግሞ ወደ ታች ወርዶ ከጥልቅ ጉዳጓድ ውስጥ ተቀብሮ መቅረት ብቻ ነው! ልክ እንደ አህያዋ (የሚጫንባትን አፈር እየረገጠች ወደ ላይ ከፍ እንዳለችው) ሁሉ እኛም በየጊዜው የሚያጋጥሙንን ችግሮች እንደ ድጋፍ እየተጠቀምን በጥንካሬ ወደ ላይ መነሳት ያስፈልገናል። ከጥልቁ ጉድጓድ ውስጥ ለመውጣት የምንችለው ለመውጣት የምናደርገውን ጥረት ባለማቆም ብቻ ነው! ምንጊዜም በጠንካራ ውስጣዊ ቁርጠኝነትና እምነት ችግሮችን እንደ መወጣጫ ደረጃ በመጠቀም ከታች ወደ ላይ እንጓዝ!!!

ለአዕምሮህ ተጠንቀቅ! ሁሉም ነገር ሲጀመር ከባድና ነውር ነበር፣ አዕምሯችን ውስጥ ከገባና ደጋግመመን ስለእርሱ ማሰብ ከጀመርን ጊዜ አንስቶ ግን አዲስነቱ ያበቃል፤ ነውርነቱ ይቀራል፣ አሳፋሪና የሚጠላ መሆኑ ተረስቶ የተለመደ፣ የሚያኮራና አስደሳች ሆኖ እንመለከታለን። ደጋግመህ በምታየው፣ ደጋግመህ በምትሰማው፣ አብዝተህ ትኩረት በምትሰጠው አስነዋሪና የወረደ ነገር አዕምሮህን እያጠለሸሀው፣ ስብዕናህን እየመረዝከው፣ ነውርንም እየተለማመድክ እንደሆነ እወቅ። ደጋግመን የጦርነት፣ የመጠፋፋትና የሞት ዜና በሰማን ቁጥር አዕምሯችን ይለምደዋል በመቀጠልም መደንገጥ እናቆማለን፣ እንዲሁ ደንዝዘን አንዳች ሰብዓዊነት ሳይሰማን የሞተን ሰው እየቆጠርን እንኖራለን። በሃይማኖትም በባህልም እጅግ የሚወገዘውና በነውርነቱ ብዛት የሰውን ልጅ በመቅሰፍት ያስመታው ግብረሰዶማዊነትም እንዲሁ እንደ ቀላል አዕምሯችንን ወደመቆጣጠር እየተሸጋገረ ነው። አዎ! ጀግናዬ..! ለውድ ንብረትህ ለአዕምሮህ ተጠንቀቅ! አዕምሮህ ውስጥ የገባን ነገር ወይ ታጥበህ አታፀዳውም ወይም ቆርጠህ አትጥለውም። ዛሬ ላይ በሞት መደንገጥ ቀርቷል፣ እዚም እዛም አስነዋሪ ተግባራትን መመልከቱ ተለምዷል። አለም አዕምሯችንን እያጠበ (Brain Wash) ቀስ በቀስ ነውሩን Normalize እንድናደርግ፣ እግዚአብሔርን እየሸሸን የሰይጣን መሳሪያ እንድንሆን በየእለቱ ይተጋል። ህፃናት የሚያዩት ፊልም አብሯቸው ያድጋል፣ ወጣቶች የተጠመዱበት የፖርን፣ የአደንዛዥ እፅና የአስነዋሪ ንግግር ሱስ እያደር በእራስመተማመናቸውን እየሸረሸረ፣ አዕምሯቸውን እየመረዘ፣ የአምላክን ህግ የሚጥሱ፣ ለሞራላቸው የማይጠነቀቁና በሃይማኖት አልባነት እንዲኖሩ ያደርጋቸዋል። አዎ! የሚሆነውን ፀያፍ ነገር ደጋግመህ በመስማት ነውርነቱን እንዳትረሳ ጆሮህን ይህን ከመስማት፣ አይንህንም ይህን ከመመልከት ጠብቀው። ብትሰማው ብትሰማው አንዳች ጠብ የማያደርግልህ፣ ብታየው ብታየው አንዳች ዋጋህን የማይጨምር ይልቁንም በክፉ ሃሳብ እየመረዘህ፣ አዕምሮህን እያጠለሸ፣ ውስጥህን እየረበሸ፣ በስጋት እያጠረ ተስፋ ቢስ ከሚያደርግህ የትኛውም ነገር ተቆጠብ። አዕምሮህ ሰላም ሲያጣ ምንምህም ሰላም ሊያገኝና ሊረጋጋ አይችልም። ከሁሉም ከሁሉም ለአዕምሮህ ተጠንቀቅ፣ መርጠህ መግበው፣ የሚሰማውን ምረጥለት፣ ማተኮር ያለበትን ጉዳይ ምረጥለት። እንደነዱህ መነዳት አቁም፤ በፈሰሱበትም መፍሰስ አቁም። አንተ ያልጠበከውን አዕምሮህን ማንም አይጠብቅልህም። በአዎንታዊ፣ ተስፋ በሚሰጡ፣ ውስጣዊ ሰላምን በሚያረጋግጡ በፈጣሪ ቃልና በሰው ልጆች መልካም ትሩፋቶች አጥረህ ከጥፋትና ከውድቀት ጠብቀው።

የስሜት ብልህነት ማለት 1. ስሜቶቻችንን የሚያካትቱት ችግሮችንለመፍታት እንዲሁም ባህርይን ለመቆጣጠር የሚያግዙንን ስሜቶችን የመረዳት፣ የመጠቀምና የማስተዳደር ችሎታ ማለት ነው። 2. የስሜት ብልህነት የግላችንንና የሌሎች ሰዎችን ስሜት የማወቅና የመቆጣጠር እንዲሁም ለራሳችንና ለሌሎች ሰዎች ስሜት ልንሰጥ የሚገባንን ትክክለኛ ምላሽ ለይተን የምናውቅበት ማህበራዊ ምላሽ ነው። ስለዚህ የስሜት ብልህነት 3. ከግላችንና ከሌሎች ሰዎች ስሜት መረጃን በመሰብሰብ ስለማንነታችንና ስለሌሎች ሰዎች ማንነት መረዳት ማለት ነው። 4. ጭንቀትን ለማርገብ፣ ለመልካምና የተሳካ ግንኙነት፣ ከሌሎች ጋር በትብብር ለመኖር፣ ችግርን ለመፍታት፣ ግጭትን ለማራቅ የምንችልበት ጥበብ ነው። 5. ሰዎች የራሳቸውን ውስጣዊ ባህርይና ስሜት በመቆጣጠር ከሌሎች ጋር እንዴት አብሮ መስራት እንደሚኖርባቸው የሚገነዘቡበት ስልት ነው። 6. ስሜታዊ ብልህነት በትምህርት ከሚገኘው እውቀት በተለየ ሰዎችን ውጤታማ የማድረግ አቅም ያለው ጥበብ ነው። ይህ ብቃት በተለይም መሪዎች ከሚያስፈልጋቸውና ሌኖራቸውከሚገባው አቅም ሲታይ ዋነኛው ነው።

የተሻለ ሰው ሆነህ ለመገኘት ✍️ 👇👀 👉 በህይወትህ ሊጠቅሙህ የሚችሉ ነገሮችን ብቻ አንብብ፡፡ ንባብን በቻልከዉ ቦታና ጊዜ ልማድ በማድረግ አእምሮህን መግበዉ፡፡ 👉 ካንተ ከተሻሉ ሰዎች ጋር አብረህ አሳልፍ፤ አስታዉስ! የአእምሮህ ብስለት የሚለካዉ አብረህ ብዙ ጊዜ ከምታሳልፋቸዉ አምስት ሰዎች የአስተሳሰብ ዉጤት ተደምሮ ነዉ። 👉 የምትወደዉን ስራ ስራ።  ሁሌም ለማሻሻል ጣር፤ ጎበዝ በሆንክበት ሙያ ከማንም የተሻልክ ሆነህ እንድትገኝ በየቀኑ አዳብረዉ። 👉 አዳዲስ ክህሎቶችን ለመማር እራስህን አዘጋጅ፤ ዉስጥህን ደስ ሊያሰኝ የሚችል ጊዜ ማሳለፊያ ወይንም ትርፍ ሙያ ለመማር ፍቃደኛ ሁን። 👉 ከሰዎች ጋር ያለህን ግንኙነት አዳብር፤ አዳዲስ ሰዎችን ለማወቅ ፈቃደኛ ሆነህ የህይወት ልምድ ተለዋወጥ። 👉 ለራስህ ህይወት ሃላፊነት ውሰድ! የምትነሳው በእራስህ ነው ፤ የምትወድቀው በእራስህ ነው ፤ የምታድገው በእራስህ ነው ፤ የኋሊት የምትጓዘው በእራስህ ነው። ለውድቀትህ የሚጠየቅ ሌላ አካል የለም።  የትም ብትሆን ፣ ምንም ብትሰራ ያንተ ህይወት ሃላፊነት የእራስህ ብቻ ነው ። ላለማደግህ ፣ ላለመቀየርህ ፣ ላለማወቅህ ...ካንተ ውጪ ሌላ ተጠያቂ አካል የለም። 👉 በእራስህ ታገል ፤ በእራስህ ተጣጣር ፤ ተፋለም ። በእራስህ ተማመን ፤ የሚመጣውን ተቀበል ፤ ያለፈው አልፏልና መጪውን ለማስተካከል ዛሬን በሚገባ ኑር። ቀጣዩን የህይወት ምዕራፍህን አስተካክለህ ፃፈው ፤ እርሱንም እመነው ፤ በነፃነት ፣ በልበሙሉነትም ተግብረው። 👉 በልዩነት አስብ! በተሻለ መንገድ አስብ ፤ የተሻለ ሃሳብ ሲኖርህ ብቻ ተመራጭ ትሆናለህ። በተለየ መንገድ አልም፣ በተለየ ሁኔታ ማለም ስትጀምር ብቻ የተለየ ነገር መፍጠር ትችላለህ ።ያለመከውን በተሻለ መንገድ አድርገው። 👉 በአምላክህ ተማመን! ከፈጣሪህ ጋር የማትችለው ፣ የማታልፈው ፣ የማትቋቋመው ምድራዊ ፈተና ፣ የማታሳካው ፣ የማታገኘው ፣ የማትኖረው ህልም የለም። 👉 ትኩረትህን ሙሉ ለሙሉ መድረስ የምትፈልግበት፣ መገኘት የምትመኘው ቦታ ላይ አድርገው ምንም ሳትሰስት የሚፈለግብህን ሙሉ ለሙሉ አድርግ ወደ ሌላ ቦታ በፍፁም እንዳታይ። የምትፈልገውን እስክታሳካ አትተኛ። 👉 ፉክክርህን ከሌሎች ጋር ሳይሆን ከትላንቱ ማንነትህ ጋር አድርግ! 👉 ሂደት በሚጠይቅ የረጅም ጊዜ ለውጥ ማመን አለብህ። እውነተኛ እርካታ እና ደስታ ያለው በመልፋትና በፅናት በሚገኝ ስኬት ውስጥ ነው። አቋራጭና ጥድፊያ የበዛበት ሰላም የሚነሳውን ህይወት ለሰነፎች ተውላቸው፤ የተሻለ ሰው የሚያደርግህ፣ የሚያስከብርህ የማይቆም ጥረትህ ነው! 👉 አስተውል! ዛሬህን ልክ እንደትላንትናህ ካሳለፈከው... የሚለወጡት አንተ ልትለውጣቸው የማትችላቸው ነገሮች ብቻ ናቸው! 👉 አስተውል! ባንተ ቁጥጥር ስር ያሉትን እውቀትህን፣ ልምድህን፣ የማኅበራዊ ህይወት ክህሎትህን፣ የገንዘብ ምንጭህን፣ የቤተሰብህን ሠላምና ደህንነት... የመሳሰሉትን ነገሮች ለመለወጥ አንዲት እንኳን እርምጃ የማትራመድ ከሆነ... መልክህ የዛሬ፣ ማንነትህ ግን የትላንት ሆኖ ነው የምትኖረው! 👉 ክቡርና ድንቅ አድርጎ የፈጠረህ አምላክም የልብህን መሻት አይቶ ከጎንህ እንደሚቆም እመን። የምትፈልገውን ጠይቀው፣ ላደረገልህ ነገር ሁሉ አመስግነው! 👉 ማደግህን አታቁም! አጋጣሚዎችን መፍጠር ፣ የተለያዩ አማራጮችን መሞከር ፣ እራስን ማብቃት ፣ እራስን ማሳደግ ፣ ከፍ ማለት የየለት  ተግባሩ የሆነ ሰው ሁሌም እድገቱ ይቀጥላል ፤ ነገዎቹ በሙሉ ከዛሬ የተሻሉ ይሆናሉ። 👉 ተደላድሎ የተቀመጠን ማንም አይረዳውም ፤ ተመቻችቶ የተኛውን ማንም አይቀሰቅሰውም ፤ እንዳልደላህ በመልፋት አሳይ ፤ እንዳልተመቸህም በመንቃት አሳይ የሚያግዝህ የሚረዳህም ፈጣሪ የእራሱን ድርሻ እንዲወጣ አግዘው!!!

አንድ ቀን መምህሩ ወደ ማስተማሪያ ክፍሉ ከገባ በሁዋላ ተማሪዎቹን ለድንገተኛ ፈተና እንዲዘጋጁ ይነግራቸዋል። ተማሪዎቹ ያልጠበቁት ፈተና ስለሆነ በጭንቀት ጥያቄውን ይጠባበቁ ጀመር። መምህሩ፣ ጥያቄ የሰፈረባቸውን ወረቀቶች ለተማሪዎቹ በጠረጴዛ በጠረጴዛቸው ላይ አስቀመጠላቸው። ከዚያ ወረቀቱን ለሁሉም ተማሪዎች ካዳረሰ በሁዋላ፤ ‹‹አሁን መጀመር ትችላላችሁ›› አላቸው። ሁሉም እየተጣደፉ ወረቀቱን ገልብጠው ሲያዩት አንድም ጥያቄ የለም። ደነገጡ። ከዚያ ልብ ብለው ሲያጤኑ ወረቀቱ መሐል ላይ አንዲት ጥቁር ነጥብ አለች… ከእሷ ውጭ ሌላ ነገር የለም። ዞር ዞር እያሉ እርስ በእርስ ተያዩ። መምህሩ ይሄን ግዜ እንዲህ አላቸው። ‹‹ወረቀቱን ስታዩ እንደተደነቃችሁ እያስተዋልኩ ነው። በሉ ያያችሁትን ጻፉ… ፈተናው ምን እንዳያችሁ በትክክሉ መጻፍ ነው።›› ተማሪዎቹ በድጋሚ ተያዩና ወደ ወረቀቱ አቀርቅረው የመሰላቸውን መሞነጫጨር ጀመሩ። ለፈተናው የተመደበው ጊዜ አለቀና ወረቀቱ ሁሉ ተሰበሰበ። ከዚያ መምህሩ እያንዳንዱን ወረቀት እያነሳ ተማሪዎች የሰጡትን መልስ ጮክ ብሎ ያነብላቸው ጀመር። የሚደንቀው ነገር ሁሉም ተማሪዎች ለማብራራት ሲጣጣሩ የነበረው ስለዚያች ጥቁር ነጥብ እንጂ ስለሌላ ነገር አልነበረም። ነጥቧን በተመለከተ እያንዳንዳቸው፥ ስለ ጥቁረቷ፣ ስላለችበት ቦታ፣ ስለ ግዝፈቷ፣ ስለሌላም ሌላም ጥቁሯን ነጥብ ስለተመለከቱ ጉዳዮች ትንታኔዎችን አቅርበዋል። መምህሩ አንብቦ ሲጨርስ ዐይኑን መለስ ቀለስ እያደረገ የተማሪዎቹን ፊት ሲያስተውል ቆየ። ከዚያም ‹‹ተማሪዎች አንዳችሁም ትክክለኛ መልስ አልሰጣችሁም። ስለዚህ ይሄን ፈተና ውጤት አልሰጥበትም። ነገር ግን አንድ ነገር ላስተምራችሁ እፈልጋለሁ›› አላቸው። ሁሉም ተማሪ መምህሩ የሚናገረውን ለመስማት ጓጉተው መጠበቅ ጀመሩ። መምህሩም ንግግሩ ቀጠለ። ‹‹ከመካከላችሁ አንዳችሁም ስለነጩ ወረቀት አልጻፋችሁም። ሁላችሁም ትንሽዬዋን ነጥብ ዐይታችሁ፥ ትልቁንና ሰፊውን ወረቀት እስከናካቴው ረሳችሁት። በሕይወታችሁም ላይ አንዲት እንከን ስታገኙ በዚህ መልኩ ያላችሁን ጸጋ ሁሉ ጠቅልላችሁ የምትረሱ ከሆነ በጣም ትጎዳላችሁ። በሚሊዮን የሚቆጠሩ መልካም ስጦታዎች እያላችሁ ስለ አንዲቷ እንከን አብዝታችሁ የምታስቡ ከሆነ እውነቴን ነው የትም አትደርሱም፤ ቆሻሻ ውስጥ ትቀራላችሁ። የገንዘብ ማጣቱ አስጨንቋችሁ ታማርሩ ይሆናል፤ ነገር ግን ከገንዘብ የበለጠ ጥሩ ፍቅር፣ ጥሩ ጤና፣ ጥሩ ሰላም፣ ጥሩ ቤተሰብ ወዘተ ካላችሁ ዓለም ላይ ተዓምር መሥራት ትችላላሁ። ስኬታማ ሕይወት ለመምራት ዋናው ነገር ያላችሁ ዐቅም ስፋት ላይ ማተኮር ስትችሉ እንጂ የጎደላችሁ ኢምንት ነገር ላይ ስታተኩሩ አይደለም። እንዲህ ማሰብ ከጀመራችሁ ያለጥርጥር እንደ እናንተ ደስተኛ ሰው አይኖርም። በተቃራኒው ጉድለት ብቻ ተመልካች ከሆናችሁ ምንም ብታገኙ እርካታ የሚባል አይኖራችሁ።›› የእኛው ድንቅ ደራሲ ጋሽ ስብሐት ገብረ እግዚአብሄርም በአንድ ወቅት ‹‹ጸጋህን ቁጠር›› የምትል ምክር ነበረችው። ‹‹… ጠዋት ከእንቅልፍ ስትነሳ ተመስገን በል! አንገትህ ተቆልምሞ ሞተህ ልታድር ትችል ነበራ! እየተንጠራራህም ተመስገን በል! መንጠራራት ደስ ይላል። ይሄን ማድረግ የማይችሉ ስንቶች አሉ መሰለህ! አንተም ሽባ ሆነህ ብታድር ኖሮ መንጠራራት ባልቻልክ ነበር።…›› እያለ ስብሃት፣ እኛ ሰዎች ያለን ጸጋ ምን ያህል ብዙ እንደሆነና በዚያም ደስተኛ መሆን እንዳለብን በሚደንቅ መልኩ ያስረዳናል። ላወቀበት ይሄ ትልቅ ትምህርት ነው፡፡ ወዳጆቼ ባላችሁ ነገር ደስተኛ መሆን ስትጀምሩ ነው ባናቱ ሌላ ደስ የሚያሰኝ ነገር የሚጨመርላችሁ… 😁😁 (በመሳፍንት ተ.)

ህይወትህን ቃኘው! ፨፨፨፨///////፨፨፨፨ ሩጫ በበዛበት አለም ፋታ ወስዶ የእራስን ህይወትና የአኗኗር ዘይቤ ቆም ብሎ የሚገመግም ሰው ጠንካራና ብርቱ ሰው ነው። በህይወትህ ውስጥ ምን እየተከናወነ ነው? የት ሆነህ ስለምን እያሰብክ ነው? የወደፊት እቅድህ ምንድነው? እንዲሁ በጭፍኑ እየተነዳህ ነው ወይስ በአላማህ አቅጣጫ ግብህን ለመምታት እየተንቀሳቀስክ ነው? ደስታህ የህይወት መርህህ ውስጥ ነው፤ ሃሴት መንፈሳዊ ልዕልናህ ውስጥ ነው፤ እረፍትና እርጋታህ የደጉ አባትህ የአምላክህ እቅፍ ውስጥ ነው። በዘፈቀደ የሚኖር፣ እንዲሁ እንደዋዛ በብክነት፣ በስንፍናና በአሉታዊነት የሚከስም ህይወት እንደሌለህ አስታውስ። መኖር መሰንበት የእግዚአብሔር ስጦታ ነው፤ ለዘመናት ሲመሽ ሲነጋ መመልከት፣ ብዙዎች ሲመጡ ሲሔዱ፣ ሲሾሙ ሲወርዱ መመልከት በእርግጥም በበረከት መሞላት፣ በፀጋ መመረጥ፣ በይቅርታም መጎብኘት ነው። አዎ! ጀግናዬ..! ህይወትህን ቃኘው፤ ፈትሸው። ክራር የተፈለገውን ድምፅ ያመጣ ዘንድ ይቃኛል፣ ያንተንም ህይወት በፈለከው መንገድ ትኖረው ዘንድ፣ በመኖርህ ታተርፍበትና ትተርፍበት ዘንድ፣ ካንተም በላይ ለተፈጠርክለት አላማ ትኖርለት ዘንድ ዘወትር ህይወትህን መቃኘት፣ እራስህን መመልከት፣ ውስጥህን ማዳመጥ፣ ለነፍስህ ቦታ መስጠትና በጥልቀት መመሰጥን እንዳትረሳ። ለእራስህ ህይወት ግድ ከሌለህ ማንም ላንተ ህይወት ግድ አይኖረውም፤ እራስህን በየጊዜው እያሳደክና ብቁ እያደረክ ካልሔድክ ማንም ሰው አንተን ብቁ ሊያደርግህ የሚተጋ የለም። እያንዳንዳችን ለእየራሳችን ህይወት ጠዓም የመስጠት ግዴታ አለብን። አምላካችንን ለማማር የሚያበቁን ስፍራ በመገኘታችን ፈጣሪያችንን ተጠያቂ እናደርጋለን፣ በገዛ ጥፋታችን እርሱን እንወቅሳለን። በምርጫ በሚኖር ህይወት ለእኛ አዳልቶ የተሻለ ነገር እንዲሁ በዋዛ እንዲሰጠን እንመኛለን። አዎ! ምሬትን ከፈለክ እልፍ ምክንያቶች ተደርድረውልሃል፤ ምስጋናንም ከፈለክ እንዲሁ በቂ ምክንያቶች አሉልህ። ትልቁ ጥያቄ "የህይወቴን ዝግ በር የሚከፍተው የትኛው ቁልፍ ነው?" የሚለው ነው። ሁላችንም አንድ ቀን ምድርን ጥለን ማለፋችን ግድ ነው። ነገር ግን አሁንም በህይወት ስለመኖራችን፣ የተሰጠንን ኑሮ ስለማጣጣማችን፣ ዘወትር ስለስጦታችን በምስጋና መትጋታችንን፣ በረከቶቻችንን ከእርግማናችን በላይ አጥብቀን ስለመያዛችን፣ ለህይወታችን ትርጉምና ጠዓም ስለመስጠታችን ስንቶቻችን እርግጠኞች ነን? ነገ ጥለሀው ለምትሔደው ወዳጅህ በፍፁም ክፉ አትመኝ፤ ለውድቀቱ አትትጋ። ብትችል ከለላ ሁነው፣ ደግፈው፣ ወግንለት፣ ካልቻልክ ግን በፍፁም የስብራቱ መንስኤ፣ ፈጣሪውን የማማረሩ ምክንያት አትሁን። ውዷን ህይወትህን በእራስህ ምርጫ ጠዓም ስጣት፣ በአምላክህ በረከትም አስጎብኛት። ═════════❁✿❁ ═════════ 💪💯 ሶሻል ሚዲያ ያገኘነውን እውቀት ለሌላውም የምናደርስበት የመረጃ ቋጥ ነውና ይህን ጹሁፍ ካነበባችሁት በኋላ ለሌላውም እንዲደርስ #ሼር ማድረጋችሁን አትርሱ!!!👌የቴሌግራም ቻናላችንን ግቡና JAttitudeplc https://t.me/Attitudeplc

ትወድቃለህ እንጂ ውዳቂ አይደለህም! ፨፨፨፨፨፨፨፨////////////////፨፨፨፨፨፨፨ እራስህን መዝነው! 1. የተሳሳቱ ሰዎችን (ራስህን ጨምሮ) የመውቀስ ልማድ አለብህ? 2. በሌሎች ሰዎች እንዳልተሳካለት ሰው ሆኜ እታያለሁ የሚል ስጋት አለብህ? 3. እንደሚሳካልህ እርግጠኛ የሆንክባቸውን ነገሮች ብቻ እየመረጥክ ማድረግ ትወዳለህ? 4. አንድን ነገር አንድ ጊዜ ሞክረኸው ካልተሳካ ደግሞ የመሞከር ፍላጎት የለህም? 5. ስኬታማ ሰዎች የስኬታማነትን ብቃት በጥረት ሳይሆን በውርስ ወይም በእድል እንዳገኙት ታስባለህ? 6. ምንም ያህል ብትሞክር እንኳ ማድረግ የማትችላቸው ብዙ ነገሮች እንዳሉ ታስባለህ? 7. የማንነትህ ዋጋ ከተሳካልህና ካልተሳካልህ ነገር አንጻር የተያያዘ እንደሆነ ታስባለህ? 8. ያለመሳካትን ሃሳብ ስታስብ የተስፋ መቁረጥ ስሜት ይጫጫንሃል? 9. ስላልተሳኩልህ ሁኔታዎች ሙሉ ሃላፊነትን ከመውሰድ ይልቅ ምክንያት ማብዛት ትወዳለህ? 10. አዳዲስ ችሎታዎችን ከማዳበር ይልቅ ያለህን ችሎታ ማሳየትና ስለእሱ ማውራት ይቀናሃል? ከላይ ለተጠየቁት አስር ጥያቄዎች ከግማሽ በላይ ለሆኑት “አዎ” የሚል መልስ ከሰጠህ ከዚህ በታች ላሉት ነጥቦች አስፈላጊ ትኩረት በመስጠት ለውጥን ለማስተናገድ ጥረት አድርግ፡፡  አመለካከትህን ለውጥ ውድቀት ምንድን ነው? ለወደፊቱ ደግመን እንዳንወድቅ እንቅፋትን ለይቶ የማወቂያ ሂደት ወይስ እንዳከተመልን ጠቋሚ ነገር? አለመሳካት ምንድን ነው? የመሞከራችንና ወደፊትም ከመሞከር እንደማናቆም አመልካች ነገር ወይስ ያለመቻል ምልክት? ስህተትስ ምንድን ነው? ሁሉም ሰው የሚያልፍበት ጤናማ የሕይወት ሂደት ወይስ የማንነት ቀውስ? የመውደቅ ፍርሃትህን ተጋፈጠው በጥቅሉ ሲታይ በአንድ ጉዳይ ላይ የመውደቅና የመሳሳት ስሜት ሲጋፋን ያንን ፍርሃታችንን የመጋፈጡ ምርጫ ውጤታማ ነው፡፡ ይህም ማለት የምንፈራቸውን ነገሮች ቀስ በቀስ በመዳፈር መነካካትና ማድረግ ማለት ነው፡፡   ስትወድቅ እንደገና ተነሳ ራሳቸውን ላሸነፉ ጎበዞች መውደቅን እንደመጨረሻ ክስተት መቀበል የማይታሰብ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ከአንድ ውድቀትና ስህተት በኋላ የመነሳትን ሁኔታ ሳያስመዘግቡ በፍጹም አያርፉም፡፡ አንተም ይህንን አመለካከት እንደ ራስህ አድርገህ ልትወስደውና ከውድቀት ባሻገር ዘልቀህ ልትጠቀምበት ትችላለህ፡፡ መውደቅና መነሳት የሕይወትህ አንዱ አካል እንደሆነ በመቀበል በወደክ ጊዜ ሁሉ በመነሳት ወደፊት መገስገስ ትችላለህ፡፡ ከውድቀታችን አጉል ተጽእኖ ማምለጥ እንችላለን እንጂ መውደቅ እንዳይከሰት ማድረግ አንችልም፡፡ ═════════❁✿❁ ═════════ 💪💯 ሶሻል ሚዲያ ያገኘነውን እውቀት ለሌላውም የምናደርስበት የመረጃ ቋጥ ነውና ይህን ጹሁፍ ካነበባችሁት በኋላ ለሌላውም እንዲደርስ #ሼር ማድረጋችሁን አትርሱ!!!