en
Feedback
ቤተ ቅዱስ ሚካኤል

ቤተ ቅዱስ ሚካኤል

Open in Telegram

ለእኛ በ አባታችን ቤት መሆን መልካም ነው ለማንኛውም ሀሳብ እና አስተያየት @Natnael_E @NAWI21 ይላኩልን 👇👇የYoutube Channel ይቀላቀላሉ👇👇 https://youtube.com/channel/UCqIww_vrxOATvuc5K_EDf1A?sub_confirmation=1

Show more
3 570
Subscribers
+324 hours
+197 days
+10330 days
Posts Archive
የዓመታት ባለቤት ✨እነሆ አዲስ ዝማሬ✨ነገ ይጠብቁ ሰላም ውድ የቤተ ቅዱስ ሚካኤል ቻናል ቤተሰቦች እንኳን ለ2019 ዓ.ም የዘመን መለወጫ በዓል በሰላም አደረሳችሁ እያል ከሥር ያስቀመጥንላችሁን መስፈ
የዓመታት ባለቤት
✨እነሆ አዲስ ዝማሬ✨ነገ ይጠብቁ ሰላም ውድ የቤተ ቅዱስ ሚካኤል ቻናል ቤተሰቦች እንኳን ለ2019 ዓ.ም የዘመን መለወጫ በዓል በሰላም አደረሳችሁ እያል ከሥር ያስቀመጥንላችሁን መስፈንጠሪያ በመጫን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶን ዶግማ ፣ ቀኖና ትውፊት የጠበቁ አዳዲስ ዝማሬዎችንና የተለያዩ መንፈሳዊ አገልግሎቶችን የምታገኙበትን የዩቲብ ቻናል ሰብስክራይብ በማድረግ ከወዲሁ ቤተሰብ በመሆን አገልግሎቱን ይደግፉ ስንል በአክብሮት እንጠይቃለን። #Subscribe 👇👇👇👇👇 https://youtube.com/@zemariyosefkebede?si=E8eugBFlUf3jQ5dw

photo content
+2

❤ ይህ የከበረ አባ በርሱማ በዚህ የጽና ተጋድሎ ሠላሳ ዓመታትን በፈጸመ ጊዜ እግዚአብሔርንም አገልግሎ ከዚህ በኋላ ጳጒሜን አምስት በዚች ቀን በሺህ ሠላሳ ሦስት ዓመተ ሰማዕታት በሰላም በፍቅር አንድነት አረፈ። ❤ ከዚህ አስቀድሞ ደቀ መዝሙሩ ቀሲስ ዮሐንስ በልቡ እንዲህ አለ "ከአባታችን በርሱማ በኋላ እንግዲህ ስዎችን ማን ያጽናናቸዋል"። ደቀ መዝሙሩ ያሰበውን በመንፈስ ቅዱስ አውቆ በንጹሕ አንደበቱ እንዲህ ብሎ መለሰለት። "ልጄ ዮሐንስ ሆይ የቶባል ልጅ አባ በርሱማ ብሎ ስሜን የሚጠራኝን ሁሉ ከእሳቸው እንደማልርቅ ዕወቅ እኔ እነሆኝ ብዬ የክብር ባለቤት ከሆነ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ የሚሻውን ሁሉ እፈጽምለታለሁ"። ❤ ከዚህም በኋላ ወደ ግራው ተመልክቶ እነሆ ፈለጉብን ተመራመሩን ከክፋ ሥራ ምንም ምን በእኛ ላይ አላገኙም አለ። ከዚህም በኋላ ደግሞ ደቀ መዝሙሩ አብርሃምን "ቢላዋ ወይም መቊረጭት ስጠኝ" አለው መቁረጫውንም ተቀብሎ ምላሱን ቆርጦ ጣላትና እግዚአብሔር ብርሃኔና መድኃኒቴ ነው የሚያስፈራኝ ምንድነው የሚለውን መዝሙር እስከ መጨረሻው ይዘምር ጀመር። ❤ ከዚህም በኋላ አዳኝ በሆነ መስቀል ምልክት ፊቱን አማተበ ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ ብርሃናውያን መላእክትም የከበረች ንጽሕት ነፍሱን ተድላ ደስታ ወደ ሚገኝባት ገነት አሳረጓት። ❤ መነኰሳቱም ከበግ ጸጒር በተሠራ ንጽሕ በሆነ በነጭ ባና ገነዙት ተሸክመውም ወስደው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩት። ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሰማንያኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስ መጣ ከእርሱ ጋርም ኤጲስቆጶሳት ቀሳውስትና ዲያቆናት የምስር አገር ታላላቆችና ብዙ የክርስቲያን ወገኖች በአንድነት ሁነው በመዘመርና በማመስገን በታላቅ ክብር ሥጋውን ገንዘው ቀበሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ በርሱማ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #የምስር_አገር_ኤጲስቆጶስ_አባ_ያዕቆብ፦ ይህም ተጋዳይ የሆነ አባት ገና በታናሽነቱ የምንኵስናን ልብስ ይለብስ ዘንድ ነፍሱ ወደደች። ከሀገሩም ወጥቶ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔደና በአባ ዮሐንስ ሐጺር በዓት ውስጥ ኖረ በዚያም ጽኑዕ በሆነ ገድል ብዙ ዘመናት ተጠምዶ ኖረ። ❤ ከዚህም በኋላ በአባ ዮሐንስ ሐጺር ቤተ ክርስቲያን ላይ ሊቀ ዲያቆናት አድርገው ሾሙት የደግነቱ፣ የትሩፋቱና የቅድስናውም ዜና ተሰማ። በእግዚአብሔርም ፈቃድ በምስር አገር ላይ ኤጲስቆጶስነት ሾሙት። በሹመቱ ወንበርም በተቀመጠ ጊዜ ጾምን ጸሎትን ጨመረ ስለ ሹመቱም ተጋድሎውንና አገልግሎቱን ከቀድሞው አበዛ እንጂ ቸልል አላለም። ሕዝቡንም ሁልጊዜ ያስተምራቸዋል መጻሕፍትንም ያነብላቸዋል ከእነርሱ ሥውር የሆነውንም ይተረጒምላቸዋል። ❤ ኃጢአትን በመሥራት የሚኖሩትን ይገሥጻቸዋል፤ በንስሐ እስከሚመለሱም ሥጋውንና ደሙን ከመቀበል ያርቃቸዋል። በጎ ተጋድሎውንም በፈጸመ ጊዜ ጥቂት ታመመ መንጋዎቹንም ጠርቶ በቀናች ሃይማኖት እንዲጸኑ አዘዛቸው ደግሞ ካህናቱን ጠርቶ በጸሎትና በቅዳሴ ጊዜ ቸለል እንዳይሉ አዘዛቸው። ሁለተኛም "ሥጋውንና ደሙን ለማክበር በንጽሕና እግዚአብሔርን በመፍራት ሁናችሁ ካላገለገላችሁ ከደማችሁ ንጹሕ ነኝ" አላቸው። ❤ ከዚህም በኋላ ፊቱንና ደረቱን በመስቀል ምልክት አማተበ እጆቹንም ዘረጋ ዐይኖቹንም ራሱ ከደነና ጳጒሜን 5 ቀን በሰላም ዐረፈ በአማሩ ልብሶችም ገነዙት ታላቅ ልቅሶንም አልቅሰው በክብር በምስጋና በማወደስ ቀበሩት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ያዕቆብ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጳጒሜን 5 ስንክሳር።                            ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለበርሱማ_ትርሲተ_ዓለም_ዘገደፈ። እስከ ኢያጥረየ አሐደ ዐጽፈ። ወዲበ ዝኒ ወሰከ ፃማ ተጋድሎ ትሩፈ። ከመ ያጽምዕ አመ ደኃሪ ምስለ ቅዱሳን ምዕራፈ። ማዕከለ ሥጋሁ ወምድር ኢገብራ መንጸፈ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጳጒሜን_5።                            ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ላዕለ ተኵላ ወከይሲ ትፄዐን። ወትከይድ አንበሳ ወከይሴ። እስመ ብየ ተወከለ አድኅኖ"። መዝ 90፥13-14። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 11፥32-ፍ.ም፣ 2ኛ ጴጥ 1፥19-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 13፥1-12። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 5፥1-17 ወይም ማር16፥15-19። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የነቢዩ ቅዱስ አሞጽና የአባ በርሱማ የዕረፍት በዓልና የጾም ጊዜ  ለሁላችንም ይሁንልን።                    @Teamihokidusan

❤ "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤                 ❤ #ጳጒሜን ፭ (5) ቀን። ❤ እንኳን #ከዐሥራ_ሁለቱ_ደቂቀ_ነቢያት አንዱ ለሆነው ለታላቁ ነቢይ #ለቅዱስ_አሞጽ_ለዕረፍት በዓልና እናትና አባቱ የተውለትን ንብረት በመተው ከዓለም ለወጣ (ወደ ገዳም ለገባ) ከልብስ ተራቁቶ ለሚኖር በጸሎቱ ታላቁን አስፈሪ ዘንዶ ለማዳ እንስሳ ላደረገ ለታላቁ አባት ለብርቱ ልጅ #አባ_በርሱማ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በፍቅር አደረሰን፡፡ በተጨማሪ በዚች ቀንከሚታሰቡ፦ ከንጽሕ ከድግል አባት ከምስር አገር ኤጲስቆጶስ #ከአባ_ያዕቆብ_ዕረፍትና ከታላቁ አባት #ከአባ_መግደር_ዕረፍት እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ይደርብን።                            ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰአሉ_ለነ_ነቢያት ስኩራነ መንፈስ ምሉኣን ሞገስ አቅርንተ ሥሉስ ቅዱስ"። ትርጉም፦ የሥላሴ ነጋሪቶች (ዐዋጅ ነጋሪዎች) የምትኾኑ ክብርን የተመላችኊ በመንፈስ ቅዱስ የተቃኛችኊ ነቢያት ለምኑልን ለእኛ አማልዱን። #ሊቁ_አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ_በሰዓታቱ_ላይ።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #ነቢዩ_ቅዱስ_አሞጽ፦ ይህም ዕውነተኛ ነቢይ በእስራኤል ነገሥታት በኢዮአስና በኦዝያ ዘመን አስተማረ የእስራኤልንም ልጆች የእስራኤልንና የይሁዳንም ነገሥታት ይገሥጻቸው ነበር። ❤ ስለ ክብር ባለቤት ስለ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መከራ ስለመቀበሉ በዚያችም ቀን ስለ ፀሐይ መጨለም ከዚያም በኋላ እስራኤልን ስለሚደርስባቸው መከራ ኀዘን ልቅሶ ረድኤትም እንደሚአጡ የእግዚአብሔርንም ቃል መስማትን ከማጣት የተነሣ እንደሚራቡና እንደ ሚጠሙ። በሀገሩ ሁሉ በአሕዛብም መካከል እንደሚበተኑ አሕዛብም እንደ አጃ ሸክሽከው እንደሚአጓልቧቸው ትንቢትን ተናገረ ትንቢቱም በላያቸው ተፈጸመ። ❤ ስለኃጢአታቸውና ስለ ክፉ ሥራቸው ስለ ዘለፋቸው እነርሱ እንደ ገደሉት ተናገረ። የትንቢቱም ዘመን ከጌታችን ሥጋዌ በፊት በስምንት መቶ ዓመት ነው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጻድቅ ነቢይ በቅዱስ አሞጽ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #አባ_በርሱማ፦ የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ በምስር አገር እጅግ ባለጸጎች ነበሩ እነርሱም እግዚአብሔርን የሚፈሩ መጻተኞችንም በፍቅር የሚቀበሏቸው በእግዚአብሔርም በሕጉ ሁሉ ጸንተው የሚኖሩ ናቸው። ❤ ይህን ቡሩክ በርሱማን በወለዱት ጊዜ በፈሪሀ እግዚአብሔር የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትንም ሁሉ በማስተማር አሳደጉት። ከዚህም በኋላ ወላጆቹ አረፉ የእናቱም ወንድም ወላጆቹ የተውለትን ገንዘብ ሁሉንም ወሰደ አባ በርሱማም አባትና እናቱ የተውለትን ገንዘብ የእናቱ ወንድም እንደ ወሰደ አይቶ የዓለምን ኃላፊነት አሰበ። እንዲህም አለ "መድኃኒታችን "ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ይጣላት ስለእኔም ሰውነቱን የጣላት ያገኛታል" ብሏል"። "ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጠፋ ምን ይጠቅመዋል ወይስ ሰው ስለ ነፍሱ ቤዛ ምን በሰጠ ነበር። የሰው ልጅ በአባቱ ጌትነት ከመላእክቶቹ ጋር ይመጣ ዘንድ አለውና ያን ጊዜም ለሁሉ እንደ ሥራው ይከፍለዋል"። ❤ ይህንንም ብሎ ከዓለም ወጣ በበጋ ቃጠሎ፣ በክረምት ቅዝቃዜ ልብስ ሳይለብስ በአምስት ኮረብታዎች ላይ ኖረ። ወገቡንም በማቅ መታጠቂያ ይታጠቃል በልቡም እንዲህ ይላል "በርሱማ ሆይ በሚያስፈራ ዕውነተኛ ፈራጅ ፊት ትቆም ዘንድ አለህ እኮን"። ሁልጊዜም በጾም በጸሎት በስግደት በቀንና በሌሊት ይተጋ ነበር። በሚመገቡም ጊዜ በውኃ የራሰ ደረቅ ቂጣ ይመገባል ቆዳውም ከአጥንቱ ጋር ተጣበቀ። ❤ ከዚያም ቦታ ሊሸሽ ወደደ ከንቱ የሆነ የሰውን ምስጋና ፈርቷልና በምስር ወዳለት የቅዱስ መርቆሬዎስ ቤተ ክርስቲያን ደረሰ በዚያም በጾም በጸሎት በስጊድ እየተጋደለ ሃያ አምስት ዓመት ኖረ። በዚያችም ቤተ ክርስቲያን አካባቢ በዋሻ ውስጥ ታላቅ ዘንዶ አለ ዘንዶውንም ከመፍራት የተነሣ ሰው መብራትን ማብራት የማይችል ነው። እግዚአብሔርም የዚህን ቅዱስ የአባ በርሱማን ደግነቱን ሊገልጥና በእጆቹም ድንቆች ተአምራትን ለማድረግ በወደደ ጊዜ አባ በርሱማ ወደዚያች ዋሻ ገባ ወደ እግዚአብሔርም እንዲህ ብሎ ጸለየ "የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ እባቡን ጊንጡን እንረግጥ ዘንድ በጠላት ኃይል ላይ ሁሉ ሥልጣንን የሰጠኸን አንተ ነህ። አሁንም በዚች ዋሻ ውስጥ በሚኖር ከይሲ ላይ ታሠለጥነኝ ዘንድ እለምንሃለሁ ላንተም ምስጋና ይሁን ለዘላለሙ"። ❤ ከዚህም በኋላ ራሱን በመስቀል ምልክት አማተበ እንዲህም እያለ ዘመረ "በተኲላና በእባብ ላይ ትጫማለህ አንበሳውንና ዘንዶውን ትረግጣለህ"። ከዚህም በኋላ ያንን ዘንዶ በእጁ ይዞ እንዲህ አለው "ከእንግዲህ ገራም ሁን ታጠፋ ዘንድ ሥልጣን አይኑርህ ኃይልም ቢሆን በማንም ላይ ከሰው ወገን በአንዱ ላይ ክፉ ሥራ አታደርግ የሚሉህን ሰምተህ የምትታዘዝ ሁን እንጂ" በዚያን ጊዜም አንበሶች ለነቢዩ ዳንኤል እንደተገዙ ያ ዘንዶ ከአባ በርሱማ እግሮች በታች ተገዢ ሆነ። ❤ ከዚህም በኋላ አባ በርሱማ በመራብ በመጠማት ተጋድሎውን ጨመረ በየሁለት ቀን፣ በየሦስት ቀን፣ በየሰባት ቀን እያከፈለ ብርሃን በላዩ እስቲወጣ ያለ ማቋረጥ የሚጾም ሆነ። ለጸሎት በሚቆም ጊዜ ከይሲው ከርሱ ይርቃል በሚቀመጥም ጊዜ ሲጠራው ወደርሱ ይመጣል። ❤ በዚችም ቤተ ክርስቲያን አካባቢ የውኃ ጒድጓድ አለች ወደርሷ በመውረድ ሁል ጊዜ ከማታ እስከ ንጋት ከውስጧ ገብቶ ያድራል በክረምትም በበጋም እንደዚህ ያደርጋል መላዋን ሌሊትም በውስጥዋ እየጸለየ ያድራል። የሚመገበውም የደረቀና የሻገተ ቂጣ ሲሆን የሚጠጣውም የከረፋ ውኃ ነው። ❤ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትን አዘውትሮ ያነባል ይልቁንም የዳዊትን መዝሙር አባቶችም ሥጋቸውን ለማድከም ያደረጓቸውን ትኀርምቶች በማንበብ ስለዚህ ትኀርምትን ንጽሕናን ወደደ ለሰዎችም እንዲህ እያለ ጠቃሚ ሥራዎችን ያስተምራል "ያለ ልብ ንጽሕና በቀር አንዱ እንኳን የእግዚአብሔር መንግሥት ማየት አይችልም ኃጢአት ሁሉ ከንስሓ በኋላ ይሠረያልና"። ለክርስቲያን ወገኖችም እንዲህ ያስተምራቸዋል ከእግዚአብሔርም ተአምራት የማድረግ ሀብት ተሰጠው ከገድሉም ለሰው የገለጥነው ጥቂቱን ነው። ❤ የዚህም አባት አርአያው የሚያምር መልኩም በብርሃን ያሸበረቀ ገጽታው ደስ የሚል ነው። ጥሪት በማጣቱም ደስ ይልዋልና። ከዓለማዊ ልብስ የተራቆተ ዓለምን ከማግኘትም የራቀ ነው። ቀድሞ ከቤቱ ከወጣ ጀምሮ የቀይ ግምጃ ጨርቅ በማገልደም ሥጋውን ይሸፍናል በክረምትም በበጋም የቀን ሐሩርን የሌሊት ቊርን ይታገሣል በጐኑና በምድር መካከል ምንጣፍ አላደረገም ወደ ሕይወት አገር ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት የሚያደርስ ተጋድሎን እንደዚህ ተጋደለ። ❤ ከክፉዎች ሰዎችና ከክፉዎች አጋንንት ብዙ ጊዜ ኀዘን ፈተና አግኝቶታል ከዚህም ሁሉ ጋር በዚህ ጭንቅ በሆነ ሥራ የረዳው እግዘሐአብሔርን ፈጽሞ ያመሰግነዋል። ይህንን በጎ የገድል ጒዞ በተጓዘ ጊዜ ሰዎት ዜናውን ሰሙ ሽማግሎችም ጐልማሶችም ከእነርሱ በጽነት የተሰነካከለ ወይም ከጠላት ሰይጣን ፈተና ያገኘው ወይም የመንፈስ ደዌ ያገኘው ሁሉ መሪና አጽናኝ ይሆናቸው ዘንድ ተመኝተውት ፈለጉት ከእርሱ ፈውስ ያገኙ ዘንድ መጡ።

photo content
+1

❤ "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤                  ❤ #ጳጒሜን ፬ (4) ቀን። ❤ እንኳን ለታላቁ ለተጋዳይ አባት #ለአባ_ባይሞንና ለሮሜ ሊቀ ጳጳሳት አርዮሳውያንን በመቃወም በማውገዝ ብዙ ለደከመ ሃይማኖትን ለጠበቀ ላጸና ለታላቅ አባት #ለአባ_ሊባርዮስ_ለዕረፍታቸው_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታቡ፦ #ከአባ_ባይሞን_ከስድስቱ_ወንዱሞቹ_መነኰሳት ስማቸው #ከዮሐንስ_ከኢዮብ_ከዮሴፍ_ከላስልዮስ፣ #ከያዕቆብና_አብርሃም ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                              ✝ ✝ ✝ ❤ #አባ_ባይሞን፦ ይህም ቅዱስ ከምስር ሀገር ነው ስማቸው ዮሐንስ፣ ኢዮብ፣ ዮሴፍ፣ ላስልዮስ፣ ያዕቆብ፣ አብርሃም የሚባል ስድስት ወንድሞች አሉት ሁሉም መነኰሳት ሁነዋል። ከእሳቸውም ዮሐንስ ይልቃል ነገር ግን በእውቀትና በጥበብ ባይሞን ይበልጣል። ሁሉም ተስማምተው ከዓለም ወጡ ከሰውም ሩቅ በሆነ ቦታ የሚኖሩ ሆኑ የክብር ባለቤት የሆነ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ቀንበር ተሸክመው ከዘመድም ተለይተው በጠባብ መንገድ ተጓዙ። ❤ እናታቸውም ልታያቸው ወዳ ወደ በዓታቸውም ደርሳ በውጭ ቆመች ወደርሷም መጥተው እንድታያቸው ላከችባቸው እነርሱም ወደርሷ እንዲህ ሲሉ ላኩ "በዚህ በኃላፊው ዓለም ልታይን ከወደድሽ በወዲያኛው ልታይን አትችይም" እርሷም አስተዋለች አልመለሰችላቸውም መንገዷን ተጓዘች። ❤ ይህም አባት ባይሞን በአስቄጥስ ገዳም ለሽማግሌዎችም ለጐልማሶችም አረጋጊ ወደብ ሆነ። ከጠላት ሰይጣን ፈተና የሃይማኖት ጥርጥር ወይም ደዌ ያገኘው ሁሉ ወደርሱ ይመጣል ወዲያውኑ ያረጋጋዋል ከደዌውም ይፈውሰዋል። ይህም አባት በምንኲስና ሕግ ስለ መጋደል ስለ አምልኮም ብዙ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሰ። በትምህርቱም እንዲህ አለ "የተሰነካከለ ወንድምን ብታይ ስለርሱ ተስፋ አትቁረጥ ልቡን አንቃለት እንጂ ከወደቀበትም እንዲነሣ አጽናንተህ ሸክሙን አቃልለት። አፍህ የተናገረውን ይሠራ ዘንድ ልብህን አስተምረው" አለ። ❤ አንድ ወንድም እንዲህ አለው "ሥራው መልካም የሆነ ወንድም ያየሁ እንደሆነ ደስ ይለኛል ወደቤቴም አስገብቼ ባለኝ ነገር ደስ አሰኘዋለሁ። ግን ሥራው ብልሹ የሆነ ወንድም ያየሁ እንደሆነ አልፈቅደውም ወደ ቤቴም አላስገባውም"። አባ ባይሞንም እንዲህ ብሎ መለሰለት "ሥራው በጎ ለሆነው እንዳረግኸው ለዚህም ሥራው ብልሹ ለሆነው ዕጥፍ አድርገህ በመሥራት ደስ አሰኘው ለታመመ መድኃኒት ያደርጉለት ዘንድ ይገባልና"። ❤ ከዚህም በኋላ ለዚያ ከርሱ ጋር ለሚነጋገር ወንድም እንዲህ ብሎ ነገረው "በመነኰሳት ገዳም ስሙ ጢሞቴዎስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ በኃጢአትም ወድቆ "አቤቱ ይቅር በለኝ" እያለ የሚጮህና የሚያለቅስ ሆነ። ከሰማይም እንዲህ የሚል ቃል መጣ "አንተ ወንድምህን በመከራው ጊዜ ቸለል ያልከው ባትሆን እኔ ባልጣልኩህም ነበር"። ❤ ይህ አባት ደግሞ እንዲህ አለ "እኛ የወንድማችን በደል ብንሰውር እግዚአብሔርም በደላችንን ይሠውርልናል"። ይህም አባት ዕድሜውን በተጋድሎና በትሩፋት ሥራ ከፈጸመ በኋላ ወደ መልካም ዕርግና ደርሶ እግዚአብሔርን አገልግሎ ጳጒሜን 4 ቀን በሰላም አረፈ።                               ✝ ✝ ✝ ❤ #የሮሜ_ሊቀ_ጳጳሳት_አባ_ሊባርዮስ፦ ይህም አባት አርዮሳዊ በሆነ በሁለተኛው ቈስጠንጢኖስ ዘመን ተሾመ። የቈስጠንጢኖስም ወንድሙ ቊንስጣ በሮሜ ነግሦ ነበር። ❤ ሐዋርያዊ አትናቴዎስንና ጳውሎስን ከመንበረ ሢመታቸው በአሳደዳቸው ጊዜ እነርሱም ወደዚህ አባት ሊባርዮስ መጡ። ይረዳቸውም ዘንድ ለመኑት እርሱም ተቀበላቸው ከደብዳቤ ጋርም ወደ ንጉሥ ቊንስጣ ላካቸው ንጉሡም ደብዳቤያቸውን ተቀብሎ በጎ ነገር እንዲያደርግላቸው ወደ መንበረ ሢመታቸውም እንዲመልሳቸው ወደ ወንድሙ ቈስጠንጢኖስ ደብዳቤ ጻፈላቸው። እርሱም የወንድሙን ደብዳቤ በአነበበ ጊዜ አትናቴዎስን ወደ መንበረ ሢመቱ እስክንድርያ፣ ጳውሎስንም ወደ መንበረ ሢመቱ ቊስጥንጥንያ መለሳቸው። ❤ ከዚህም በኋላ ቊንስጣ ንጉሥ በዓመፀኞች በተገደለ ጊዜ ቈስጠንጢኖስ ወደዚህ አባት ሊባርዮስ መልእክት ላከ ሐዋርያዊ አትናቴዎስን ያሳድደው ዘንድ የአርዮስንም ወገን እንዲቀበላቸው ብዙ ቃል ኪዳናትንም ገባለት እርሱ ግን አልተቀበለውም በምክሩም ከእርሱ አልተስማማም። ስለዚህም ይህን አባት ሊባርዮስን ሩቅ አገር አጋዘው። ❤ ከዚህም በኋላ ወንዱሙ ቊንስጣን የገደለውን ጭፍራ ልኮ ገደለው። ከዚህም በኋላ ቈስጠንጢኖስ ወደ ሮሜ ከተማ ሔደ ስለዚህ አባት ሊባርዮስም የገዳማትና የአድባራት ሊቃውንት ካህናቱም ሁሉ ወደ መንበረ ሢመቱ ይመልሰው ዘንድ ንጉሡን ለመኑት እርሱም ምልጃቸውን ተቀብሎ ወደ መንበረ ሢመቱ መለሰው። ❤ ይህ አባት ወደ መንበሩ በተመለሰ ጊዜ በቀናች ሃይማኖት ይጸኑ ዘንድ ሁልጊዜ መንጋዎቹን ማስተማር ጀመረ ብዙ ድርሳናትንና ተግሣጻትንም ደረሰ የአርዮስ ወገኖችንም እየተቃረናቸው ኖረ ያወግዛቸውና ያሳድዳቸውም ነበር። ከስደት ከተመለሰ በኋላ በሰባት ዓመት በሰላም አረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ሊባርዮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጳጒሜን 4 ስንክሳር።                            ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ዕብል_በልሳንየ_መዋቲ። ፯ተ አኃወ ኅዱራነ በአት አሐቲ። ሶበ ፈቀደት እሞሙ ትርእዮሙ ይቤልዋ ላቲ። ኢትክሊ ትርአዪነ በዓለም ሰማይ እንታክቲ። ለእመ በዝየ ርኢክነ አንቲ"። #ሊቁ አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጳጉሜን_4።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ክላእ ልሳንከ እምእኩይ። ወከናፍሪከኒ ከመ ኢይንብባ ጒኅሉተ። ተገኃሥ እምእኩይ ወግበረ ሠናየ"። መዝ 33፥13-14። የሚነበቡት መልክዕታት 2ኛ ጢሞ 2፥11-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 5፥1-6 እና የሐዋ ሥራ 15፥19-25። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 18፥23-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም፣ የጸሎትና የምሕላ ጊዜና በዓል ለሁላችን ይሁንልን።                   @Teamihokidusan

photo content
+5

❤ #የጳጒሜን_3_የሊቀ_መላእክት_የቅዱስ_ሩፋኤል የሢመት ዓመታዊ በዓል ሙሉ ቃለ እግዚአብሔር የማኅሌት ሥርዓት።              @Teamihokidusan

photo content
+1

❤ "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤                  ❤ #ጳጒሜን ፫ (3) ቀን። ❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ ታላቁን #ቀብጽያ_ገዳምን_ለመሠረቱት፤ #መልአከ_ሞትን የማያሳይ ታላቅ ቃልኪዳን ላላቸው ለታላቁ ለአባት #ለአቡነ_ቀፀላ_ጊዮርጊስ_ለዕረፍታቸው በዓልና #ለኢትዮጵያ_ንጉሥ_መልካም_ስም አጠራር ላለው #ለአፄ_ዘርዐ_ያዕቆብ_ለዕረፍቱ ቀን መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #አቡነ_ቀፀላ_ጊዮርጊስ፦ ትውልዳቸው አገው ሲሆን ከብዙ ጽኑ ተጋድሎአቸው በኋላ እንደ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ስድስት ክንፍ የተሰጣቸው ታላቅ አባት ናቸው። አቡነ ቀፀላ ጊዮርጊስ በ16ኛው መ/ክ/ዘ የነበሩ ሲሆን ታላቁን ቀብጽያ አንድነት ገዳምን የመሠረቱት ናቸው። ጻድቁ በመጀመሪያ የአባ አሞኒን ገዳም ለመገደም ወደ ትግራይ ቀብጽያ ሲሄዱ በእግዚአብሔር ታዘው የአቡነ አሞፅን ገዳም በሰማዕቱ ቅዱስ ጊዮርጊስ ስም መሠረቱ። ገዳሙም "ቀብጽያ አሞፅ ወቀፀላ ጊዮርጊስ አንድነት ገዳም" ተባለ። ❤ አቡነ ቀፀላ ጊዮርጊስ 200 ተከታይ መነኰሳትን አስከትለው ሌሎች 6 አስደናቂ ገዳማትን ገድመዋል። ገዳማቱም ማይወኒ ቅዱስ ሚካኤል፣ ውጅግ ቅዱስ መርቆሬዎስ፣ ጅል ውኃ ቅዱስ ማርቆስ፣ ዶቅላኮ አርባእቱ እንስሳ፣ አንጓ ቅድስት ማርያም እና ድቁል ማርያም ይባላሉ። ❤ ጻድቁ ስድስት ክንፍ እስኪሰጣቸው ድረስ ብዙ ተጋድሎ ያደረጉት በቀብጽያ ገዳም ነው። ዕረፍታቸውም ጳጒሜን 3 ቀን ነው። በዘንዶዎች የሚጠበቀው ይህ አስደናቂ ገዳም በብዙ መልኩ ከሌሎች ገዳማት የተለየ ነው። የገዳሙን አፈር ቅዱሳን መላእክት ናቸው ከገነት ያመጡት። ጌታችን 12 እልፍ መላእክቱን ልኮ ከገነት አፈር አምጥተው በዝናብ አምሳል በቀብጽያ ገዳም ላይ እንዲነሰንሱት አዟቸዋል። ❤ ገዳሙን የተሳለመ ሰው ኢየሩሳሌም በጎልጎታን እንደተሳለመ የሚቆጠርለት ሲሆን በገዳሙ ውስጥ የተቀበረ ሰው ወቀሳ የለበትም። ከአካሉም ላይ ፀጉሩን ወይም ጥፍሩን ቆርጦ በገዳሙ ክልል ውስጥ የቀበረ ሰው ቢኖር መልአከ ሞትን ፈጽሞ እንደማያይና ገዳሙ የሚገኝበት አካባቢ በእግር ለመጓዝ አስቸጋሪ ቢሆንም ቦታውን የረገጠ እስከ 15 ትውልድ ምሕረትን እንደሚያገኝ ጌታችን በቃል ኪዳን አጽንቶታል። ❤ ቀብጽያ ገዳምን ለየት የሚያደርገው ነገር ቢኖር ፈዋሹ ጠበል ከጻድቁ አቡነ አሞፅ መቃነ መቃብር ሥር የሚፈልቅ መሆኑ ነው፡፡ ከዋሻው ሥር የተንጠባጠበው ጠበል ወደ ጠንካራ ዐለትነት የሚቀየር ሲሆን እርሱን ለእምነት የተጠቀሙበት ሰዎች ከተለያዩ በሽታዎች ተፈውሰዋል፡፡ በቅርቡም ከ6 ዓመት በፊት በዚህ እምነት የተሻሸች አንዲት ሴት ከዘመኑና መድኃኒት ካልተገኘለት ከHIV በሽታና ከመካንነቷ ተፈውሳ ልጅ ወልዳለች፡፡ ይህ አስደናቂ ቀብጽያ ገዳም ፍልፍል ዋሻ ቤተ መቅደስ ቢሆንም ከጊዜና ብዛት ጉዳት ስለደረሰበትና የሚያድሰው አካል ስላላገኘ በአሁኑ ወቅት ሌላ አዲስ ቤተ መቅደስ እየታነጸ ይገኛል፡፡ ❤ በቀብጽያ ገዳም ውስጥ 336 ዓመት የሆነው የወይራ ዛፍ የሚገኝ ሲሆን በቅርቡ ስውራን የሆኑ ቅዱሳን ሦስት ጊዜ ደወል ሲደውሉበት ተሰምቷል፡፡ ገዳሙን አቡነ ቀፀላ ጊዮርጊስ ይገድሙት እንጂ በቦታው ላይ አቡነ አሞፅ አስቀድመው መቶ ዓመት በታላቅ ተጋድሎ ኖረውበታል። አቡነ አሞፅ ትውልዳቸው ሸዋ ሲሆን የመነኰሱት ደብረ ሊባኖስ በአቡነ ዮሐንስ ከማ እጅ ነው፡፡ አቡነ ዮሐንስ ከማ በመልአክ ታዘው 10 መነኰሳት 500 ሕዝብ ተከትሏቸው ወደ ትግራይ ሲሄዱ ሳምረ ወረዳ ላይ ሲደርሱ ሕዝቡ ቢራብ ዋርካ ዕለቱን አብቅለው ባርከው መግበውታል፣ ውኃም አፍልቀው አጠጥተውታል፡፡ ከዚኽም በኋላ የበቁትንና ቅዱሳን የሆኑትን ዓሥሩን መነኰሳት ገዳም እንዲገድሙ ወደተለያዩ ቦታዎች ላኳቸው፡፡ ከእነዚኽም ዓሥር ቅዱሳን መነኰሳት መካከል አቡነ አሞፅ አንዱ ናቸው፡፡ እርሳቸውም ጽላተ ማርያምን ይዘው በቅዱሳን መላእክት ታጥራ ወደምትገኘው ምድረ ቀብጽያ መጥተው መቶ ዓመት በታላቅ ተጋድሎ ኖሩ። ❤ አቡነ አሞፅ ሰቆቃወ ድንግል የሚባለውን የእመቤታችን መከራ የሚተርከውን ድንቅ ድርሰት ሙሉውን ክፍል በብራና ላይ በሥዕል ገልጸው በክብር አስቀምጠውታል፡፡ ከሰማይ የወረደላቸው የወርቅ መስቀላቸውም በገዳሙ ይገኛል፡፡ ❤ አቡነ አሞፅ በ1592 ግንቦት 26 አርብ ቀን ሲያርፉ ጌታችን ከድንግል እናቱ ጋር ተገልጾላቸው ከላይ ያየናቸውን አስደናቂ ቃልኪዳኖች ከሰጣቸው በኋላ ነፍሳቸውን እመቤታችን አቅፋ አሳረገቻቸው፡፡ ዐፅማቸው ያረፈበትን መካነ መቃብር ታላላቅ ዘንዶዎች ይጠብቁታል፡፡ ጠበላቸውም የፈለቀው ከመቃብራቸው ሥር ነው፡፡ ቦታው በስውራን ስለሚገለገል የከበሮ ድምፅ የሚሰማ ሲሆን የእጣንም ሽታ ይሸታል፡፡ ከአባታች ከአቡነ ቀፀላ ጊዮርጊስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸውም ይማረን!። ምንጭ፦ከገዳሙ ካሳተመው ስዕል ጀርባ የተገኘ ታሪክና መዝገበ ቅዱሳን ከሚለው መጽሐፍ።                         ✝ ✝ ✝ ❤ #በዚች_ቀን_የኢትዮጵያ_ንጉሥ_መልካም_ስም አጠራር ያለው #ዘርዐ_ያዕቆብ ዐረፈ። እርሱም በመንግሥቱ ግዛቶች አገሮች ሁሉ ያማሩ ሥርዓቶችን የሠራ ሃይማኖትንም ያቀና ነው እግዚአብሔርንም አገልግሎ ደስ አሰኝቶ ጳጒሜን 3 ቀን በሰላም ዐረፈ። የአፄ ዘርዐ ያዕቆብ በረከቱ ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጳጒሜን 3 ስንክሳር።                   @Teamihokidusan

photo content
+1

                          ✝ ✝ ✝ ❤ #ለእግዚአብሔር_ልጅ_ምሳሌው_የሆነ #ካህኑ_ቅዱስ_መልከጼዴቅ፦ መልከጼዴቅም ዐሥራ አምስት ዓመት በሆነው ጊዜ ከአዳም ሥጋ ጋር እንዲልከውና በምድር መካከል እንዲያኖረው እግዚአብሔር ኖኅን አዘዘው እርሷም ቀራንዮ ናት። የዓለም መድኃኒት ክርስቶስም መጥቶ በዚያ እንደሚሠዋ አዳምንም ከልጆቹ ሁሉ ጋር እንደሚያድነው አመለከተው። ❤ ከዚህም በኋላ በአባቱ በኖኅ ትእዛዝ ሤም መልከጼዴቅን በሥውር ወሰደው የእግዚብሔርም መልአክ እየመራቸው ሔደው ወደ ቀራንዮ ተራራም አደረሳቸው መልከጼዴቅም ክህነትን ተሾመ። ዐሥራ ሁለት ደንጊያዎችንም ወስዶ መሠዊያ ሠራ ከሰማይ የወረደለትንም ኅብስትና ወይን መሠዊያ በሠራቸው ደንጊያዎች ላይ መሥዋዕትን አሳረገ። ❤ ምግቡንም መላእክት ያመጡለታል ልብሱም ዳባ ነው በአባታችን አዳም ሥጋ ዘንድ ሲያገለግል ኖረ። አብርሃምም ከጦርነት ነገሥታትን ድል አድርጎ በተመለሰ ጊዜ ኅብስትንና ወይንን አቀረበለት አብርሃምም ከገንዘቡ ሁሉ ከዐሥር አንድ ሰጠው እርሱ ካህንም ንጉሥም ሁኖ ተሹሟልና። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በካህኑ ቅዱስ መልከጼዴቅ በአማላጅነቱ ይማረን ለዘላለሙ አሜን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #ቅዱስ_ሰራጵዮን፦ ይህም ቅዱስ ሰንዱን ከሚባል አገር ነው። ከታናሽነቱ ጀምሮ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትን ትርጓሜያቸውንም ተማረ የዚህንም ዓለም ገንዘብ ሁሉ ትቶ ወደ አረሚ አገር ሔደ ራሱንም በሃያ ብር ሸጦ ማገልገል ጀመረ የሽያጩንም ዋጋ ጠበቀው። እንጀራ ሳይበላ ውኃ ሳይጠጣ ከስሕተታቸው ይመልሳቸው ዘንድ ሁል ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር። ❤ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት በሆነ በክርስቶስ አሳመናቸው ሕግንና ሥርዓትንም ሁሉ አስተማራቸው ከዚህም በኋላ ስለርሳቸው ራሱን ባሪያ አድርጎ እንደሸጠ እንጂ እርሱ ባሪያ እንዳልሆነ ነገራቸው ሽያጩንም ለድኆች እንዲሰጡት ሰጣቸው። ❤ ከዚህም በኋላ መንካያውያን ወደሚባሉ ሕዝቦች ሒዶ ለነርሱም ራሱን ሸጠ የክብር ባለቤት ወደሆነ ክርስቶስ እምነት እስከመለሳቸው ድረስ ተገዛላቸው። ከዚህም በኋላ ደግሞ ወደ ሮሜ አገር ሒዶ በሰላም እስከ አረፈ ድረስ በጾምና በጸሎት እየተጋደለ ኖረ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጳጒሜን 3 ስንክሳር።                                                          ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "መሐለ እግዚአብሔር ወኢይኔስሕ። አንተ ካህኑ ለዓለም በከመ ሢመቱ ለመልከጼዴቅ። እግዚአብሔር በየማንከ"። መዝ109፥4-5። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 17፥20-31።                               ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "እግዚአብሔር ገሃደይ መጽእ። ወአምላክነሂ ኢያረምም። እሳት ይነድድ ቅድሜሁ"። መዝ 49፥2-3። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 7፥1-7፣ ይሁ 1፥11-17 እና የሐዋ ሥራ 5፥16-26። የሚነበው ወንጌል ማቴ 25፥31­46። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ነው። መልካም የመልአኩ የቅዱስ ሩፋኤል በዓል ለሁላችን ይሁንልን።                 @Teamihokidusan

❤ "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤                  ❤ #ጳጒሜን ፫ (3) ቀን። ❤ እንኳን #ለሊቀ_መላእክት_ለቅዱስ_ሩፋኤል ለተሾመበት፣ #ቅዱስ_ጦቢትን_ዐይኑን_ለአበራለትና ልጁ #ቅዱስ_ጦብያን_ለረዳበት፣ የራጉኤልን ልጅ #ሣራን_ተቆራኝቷት_የነበረው_አስማንድዮስ_ጋኔን ላወጣላት በዓል (ታሪክ በጽሐፈ ጦብት ላይ ያንብቡ)ና #ለሊቀ_ካህን_ለኢየሱስ_ክርስቶስ ምሳሌ ለሆነ #ለካህኑ_ቅዱስ_መልከፄዴቅ ለመታሰቢያ በዓሉ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ ሰንዱን ከሚባል አገር #ከቅዱስ_ሰራጵዮን ዕረፍት እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                                                                     ✝ ✝ ✝ ❤ #ሊቀ_መላእክት_ቅዱስ_ሩፋኤል፦ እርሱም ከመላእክት አለቆች ሦስተኛ የሆነ ነው። ደግሞም ከእስክንድርያ ውጭ በደሴት የታነፀች ቤተ ክርስቲያኑ በከበረ ሊቀ ጳጳሳት ቴዎፍሎስ ዘመን በውስጧ ተአምር የተገለጸባት የከበረችበት ነው። ❤ ይህም እንዲህ ነው ሀብታም ሴት ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስ መጥታ ሳለ ከእርሷ ጋርም ብዙ ሰው ነበረ። ከባሏም የወረሰችው ብዙ ገንዘብ አላት በሊቀ ጳጳሳቱ ቤት አንጻር ያለውን ኮረብታ አስቆፈረችው በጥቅምት ወር ዐሥራ ስምንት ቀን እንደጻፍን የወርቅ መዝገብ ተገለጠ። በዚያም ወርቅ ብዙዎች አብያተ ክርስቲያናትን አነፀ ከእርሳቸውም አንዲቱ የመላእክት አለቃ በሆነ በከበረ መልአክ ሩፋኤል በስሙ የታነፀች ይህች ናት። ሥራዋንም በፈጸመ ጊዜ እንደዛሬው በዚች ቀን አከበራት። ❤ ብዙ ምእመናንም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈጽማ ተናወጸች ያቺ ደሴት በታላቅ አንበሪ ጀርባ ላይ የቆመች ናትና። የሰዎች ብዛትም በከበደው ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው። ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔርም በከበረ መልአክ ሩፋኤል ስም ጮኹ ያን ጊዜ ይህ የከበረ ሩፋኤል ያንን አንበሪ በጦሩ ወግቶ እንዲህ አለው "እግዚአብሔር አዞሃልና ከቦታህ ሳትናወጽ ጸጥ ብለህ ቁም"። አንበሪውም ጸጥ ብሎ ቆመ አልታወከም በውስጧም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆነ። ❤ ይቺም ቤተ ክርስቲያን እስላሞች እስከተነሡበት ዘመን ኖረች ከዚህም በኋላ ሁለተኛ ያ አንበሪ ተናወጸ ደሴቲቱም በላይዋ ከሚኖሩ ብዙ ሕዝብ ጋራ ሠጠመች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የመልአክ ቅዱስ ሩፋኤል በረከቱ ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #ዳግመኛም_የቊስጥንጥንያ_ሊቀ_ጳጳሳት #አባ_ዮሐንስ_ጻድቅ_ለሆነ_ንጉሥ_አኖሬዎስ_ተናገረው፦ እንዲህም አለው "ንጉሥ ሆይ እኛ ወዳንተ ልንመጣ በመርከብ እንደተሳፈርን ዕወቅ በጒዞ ላይ ሳለንም በቀዳሚት ሰንበት ቀን በደሴት ውስጥ ታናሽ ቤተ ክርስቲያን አየን ወደ ወደቡም ደርሰን በዕለተ እሑድ ሥጋውን ደሙን እንቀበል ዘንድ ወደርሷ ሔድን። ❤ ለዚያች ቤተ ክርስቲያንም በጐኗ ታናሽ ገዳም አገኘን በውስጧም ወንድሞች መነኰሳት አሉ በክብር ባለቤት ጌታችንም ፈቃድ ወደ ርሳቸው ደረስን። መነኰሳቱንም "በቀደሙ አባቶች ዘመን የተጻፈ አሮጌ መጽሐፍ በእናንተ ዘንድ እንዳለ እጽናናበት ዘንድ እርሱን ሰጡኝ" አልኳቸው። ❤ እንዲህም ብለው መለሱልኝ "እኛ ትርጓሜያቸውን የማናውቀው መጻሕፍቶች በዕቃ ቤት አሉ"። እኔም "አያቸው ዘንድ ወደዚህ አምጡልኝ" አልኳቸው። በአመጡአቸውም ጊዜ መረመርኳቸው ጌታችንም በደቀ መዛሙርቱ ፊት ያደረጋቸውን ኃይሎችና ድንቆች ተአምራቶችን ስለ ሰማይና ምድርም ጥንተ ተፈጥሮ አገኘሁ። ❤ ሁለተኛም ስመረምር ስለ ሰባቱ ሊቃነ መላእክት ሹመትና መዐርግ አባቶቻችን ንጹሐን ሐዋርያት የጻፉትን አገኘሁ ይኸውም ጌታችን በደብረ ዘይት ከእሳቸው ጋራ እያለ የመለኮቱን ምሥጢር በገለጠላቸው ጊዜ። ሐዋርያትም እንዲህ ብለው እንደለመኑት "ጌታችንና ፈጣሪያችን ሆይ የከበረ የሩፋኤልን ክብሩን ታስረዳን ዘንድ እንለምንሃለን በየትኛው ዕለት በየትኛው ወር ሾምከው"። ከባልንጀሮቹ የመላእክት አለቆችም ትክክል ነውን የበዓሉን መታሰቢያ ያደርጉ ዘንድ በዓለም ውስጥ ስለርሱ እንድናስተምር እርሱም በመከራቸው ጊዜ ይረዳቸው ዘንድ በአማላጅነቱም በአንተ ዘንድ ይቅርታን ያገኙ ዘንድ። ❤ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዘዘና ከሦስተኛው ሰማይ ሦስቱ የመላእክት አለቆች ሚካኤል፣ ገብርኤልና ሩፋኤል መጡ በታላቅ ደስታም ለክብር ባለቤት ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰገዱ። ጌታችንም ሩፋኤልን እንዲህ አለው "የክብርህን ገናናነት የባልንጀሮችህንም ልዕልናቸውን እንዲያውቁ ለሐዋርያት ንገራቸው"። ያን ጊዜም ለጌታችን ሰገደ ይነግራቸውም ዘንድ ጀመረ እንዲህም አላቸው "ደገኛው የመላእክት አለቃ ሚካኤል ለሁሉም መላእክት አለቃቸው ነው ስሙም ይቅር ባይ ይባላል"። ❤ "ሁለተኛም የመላእክት አለቃ ገብርኤል የስሙ ትርጓሜ አገልጋይም ጌታም የሆነ የዓለሙ ሁሉ እመቤት የሆነች አምላክን የወለደች ቅድስት ድንግል ማርያምን ያበሠራት ነው"። "የእኔም ስሜ ሩፋኤል ነው ይህም ደስ የሚያሰኝ ቸር መሐሪ ቅን የዋህ ማለት ነው እኔም ኃጢአተኞችን በእግዚአብሔር ዘንድ አልከሳቸውም ከኃጢአታቸው በንስሓ እስኪመለሱ ስለ ቅንነቴ በእነርሱ ላይ እታገሣለሁ እንጂ። በሃያ ሦስቱ የመላእክት ነገድ ሠራዊት ላይ እግዚአብሔር የሾመኝ እኔ ሩፋኤል ነኝ እግዚአብሔር አብን ይቅር ባይ ልጁን አጽናኝና አዳኝ የሆነ መንፈስ ቅዱስን እናመሰግነው ዘንድ። ❤ በደብረ ጽዮን በሚደረገው የሺህ ዓመት ተድላ ደስታ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የክብር ጽዋን በሚሰጣቸው ጊዜ ለቅዱሳኖቹ በጎ ነገርን እንድሰጣቸው እግዚአብሔር ያዘዘኝ ሩፋኤል እኔ ነኝ። ደግሞም በዚች ቀን ከዕፀ ሕይወት ዐጽቅ ወስጄ ለተመረጡ ክርስቲያኖች በእጄ እንድሰጣቸው እግዚአብሔር ያዘዘኝ ሩፋኤል እኔ ነኝ። የሰማያት መዛግብትም ከእጄ በታች ተጠብቀው የሚኖሩ እኔ ሩፋኤል ነኝ። እኔም እግዚአብሔር እንዳዘዘኝ እከፍታቸዋለሁ እዘጋቸዋለሁም። ❤ በምድር ሰው ለባልንጀራው ስለ ስሜ በጎ ነገር ቢያደርግ እኔ በመከራው በችግሩ ረዳዋለሁ ወይም የሹመቴን ነገር የሚጽፍ ወይም ከቅዱሳን ጋራ ስሜን የሚያስብ ወይም በስሜ ለቊርባን የሚሆነውን የሚሰጥ ወይም በበዓሌ ቀን ምጽዋትን የሚሰጥ ይኸውም እግዚአብሔር በሊቃነ መላእክት ክብር የሾመኝና ያከበረኝ ጳጕሚን ሦስት ቀን ነው። ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት እስከማስገባው በብርሃን ሠረገላ እኔ እሸከመዋለሁ በምድር ላይ ከቶ እንደርሱ ያለ የማይገኝ መዐዛው እጅግ ጣፋጭ በሆነ ሽቱ ነፍሶቻቸው እርሱን በማሽተት ደስ እንዲላቸው አደርጋለሁ። ❤ ሐዋርያት ሆይ በእግዚአብሔር ፊት እስከምትቆሙ እጠብቃችሁ ዘንድ ከእኔ ርዳታን ሹ። የዚህ የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሩፋኤል ተአምራቶቹ ብዙ ናቸው ስለእኛ ይማልድ ዘንድ የበዓሉን መታሰቢያ ልናደርግ ይገባናል። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በመልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል አማላጅነት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                         

❤ "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤                  ❤ #ጳጒሜን ፪ (2) ቀን። ❤ እንኳን #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት አንዱ ለሆነው ሐዋርያው #ቅዱስ_ጳውሎስ_መልእክት_ለጻፈለት ለከበረ #ለሐዋርያው_ለቅዱስ_ቲቶ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                           ✝ ✝ ✝ ❤ #ሐዋርያው_ቅዱስ_ቲቶ፦ የዚህም ቅዱስ ትውልዱ ቀርጤስ ከሚባል አገር ነው። እርሱም ለዮናናውያን ወገን ለሆነ ለአገረ ገዥው እኅት ልጅዋ ነው። ከታናሽነቱም የዮናናውያንን ትምህርትና ፍልስፍና ተምሮ እጅግ አዋቂ ሆነ በጠባዩም ቅን ሥራው ያማረ ለድኆችና ለችግረኞች መራራት የሚወድ ነው። ከሌሊቶችም በአንዲቱ "ቲቶ ሆይ ስለ ነፍስህ ድህነት ተጋደል ይህ ዓለም አይጠቅምህምና" የሚለውን በሕልሙ አየ። ከእንቅልፉም በነቃ ጊዜ ደነገጠ ምን እንደሚሠራም አላወቀም። ❤ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርት በተሰማ ጊዜ ብዙዎች ሰዎችም ተአምራቱን እርስበርሳቸው ተነጋገሩ የአክራጥስ መኰንንም ሰምቶ አደነቀ ዕውነት እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ወይም የሥራይ እንደሆነ ሊያውቅ ሽቶ የሚልከው ብልህ ሰው ፈለገ የእኅቱንም ልጅ ቲቶንን መረጠው ከእርሱ የሚሻል የለምና። ሲልከውም ታላቅና ጥልቅ የሆነ ምርመራ እንዲመረምር አዘዘው። ❤ ቲቶም ከይሁዳ ምድር በደረሰ ጊዜ የመድኃኒታችንን ድንቆች የሆኑ ተአምራቶቹን አየ ሕይወትነት ያላቸው ትምህርቶቹንም ሰማ። ከዮናናውያንም በትምህርታቸውና በሥራቸው መካከል ታላቅ የሆነ መራራቅን አግኝቶ የዮናናውያን ሃይማኖታቸው የቀናች እንዳልሆነች ለይቶ ዐወቀ። ❤ ከዚህም በኋላ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ አመነ፤ ደቀ መዝሙሩም ሁኖ ተከተለው። ወደ እናቱ ወንድም ወደ አገረ ገዥውም መልእክትን ላከ የክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያስተምረውና የሚሠራው ዕውነት እንደሆነ ነገረው። ❤ ጌታችንም ከሰባ ሁለቱ ደቀ መዛሙርቱ ውስጥ የተቆጠረ አደረገው ከዕርገቱም በኋላ ከሐዋርያት ጋር የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ተቀብሎ ከእሳቸው ጋር በሀገሮች ሁሉ ዙሮ አስተማረ። ጌታችንም ጳውሎስን ጠርቶ ሐዋርያው በአደረገው ጊዜ ያን ጊዜ ሐዋርያ ጳውሎስን ተከተለው በብዙ አገሮችም ወንጌልን ሰበከ። የከበረ ቅዱስ ጳውሎስም በሮሜ ከተማ ምስክር ሆኖ ከሞተ በኋላ ቅዱስ ቲቶ ወደ ሀገረ አክራጥስ ተመለሰ ቤተ ክርስቲያንም ሠርቶ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው በዙሪያቸው ላሉ አገሮችም እንዲሁ አደረገ። ❤ ከዚህም በኋላ ሐዋርያዊ አገልግሎቱን ፈጽሞ ወደ ወደደው እግዚአብሔር ጳጒሜን 2 ቀን ሔደ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                                              ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ቀዳሚሃ ለጥበብ ፈሪሃ እግዚአብሔር። ምክር ሠናይት ለኵሉ ዘይገብራ። ወስብሐቲሁኒ ይነብር ለዓለም"። መዝ 110፥10። የሚነበቡት መልዕክታት ቲቶ 1፥1-11፣ 2ኛ ጴጥ 3፥7-14 እና የሐዋ ሥራ 4፥31-36። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 10፥1-12። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ ነው። መልካም የሐዋርያው የቅዱስ ቲቶ የዕረፍት በዓልና የጾም፣ የጸሎትና የምሕላ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።                     @Teamihokidusan

photo content
+1

❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤                          ❤ እንኳን #ለጾመ_ዮዲት_ለጾመ፤ የኢትዮጵያ ንጉሥ #ዐፄ_ናኦድ_ስምንተኛው_ሺህ እንዳያዩት ለጾሙት  (የፈቃድ ጾም) እግዚአብሔር አምላከ በሰላምና በጤና አደረሰን።                          ✝ ✝ ✝ ❤  "ሰብአ ነነዌ #ጸዊሞሙ_ተማኅሊሎሙ ድኅኑ እሞቶሙ" ትርጉም፦ የነነዌ ሰዎች #ጾመውና_ምሕላ ይዘው ከሞት ዳኑ። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በጾመ_ድጓው_ላይ።                           ✝ ✝ ✝ ❤ አምላከ ቅዱሳን ልዑል እግዚአብሔር ጾሙን፣ ጸሎቱንና ምሕላውን ተቀብሎ በአዲሱ ዓመት በዘመነ ቅዱስ ሉቃሰሰ በአገራችን ኢትዮጵያዊ ያለውን የእርስ በእርስ ጦርነት አስወግዶ ሰላም፣ ፍቅርን፣ አድነትንና መተሳሰብን ይላክል፤ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት አማኞች ላይ እየሆነ ያለው ስደት እንግልት፣ መከራና ሞት አስወግድል። መልካም የጾም፣ የጸሎትና የምሕላ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።                @Teamihokidusan

photo content
+2

❤ "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤ ❤ እንኳን #የጌታችን_የአምላካች_የመድኃኒት #የኢየሱስ_ክርስቶስ_ዳግም_ምጽአት_ስለ_ዓለም_መጨረሻ፣ #ስለ_ምሥጢረ_ትንሣኤ ለሚነገርበት ለዓመቱ የመጨረሻ #ዕለተ_ሰንበት (እሑድ) እግዚአብሔር አምላክ በሰላም በጤና አደረሰን።                           ✝ ✝ ✝ ❤ #በዚህ_ሳምንት_መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ በ፪ "ከመ እንተ መብረቅ ዘይወጽእ እምጽባሕ ወያስተርኢ እስከ ዓረብ ከማሁ #ምጽአቱ_ለወልደ_እግዚአብሔር ምስለ ኃይል ሰማያት በንጥረ መባርቅት (ከማሁ) ምስለ አዕላፍ መላእክት ወኵሎሙ ሊቃነ መላክት (ከማሁ) አክሊለ አክሊላት ዲበ ርእሶሙ ለካህናት"። ትርጉም፦ መብረቅ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ እንዲታይ ከመላእክት አለቆች ሁሉ ጋር ከሰማያት ኃይል ጋር በመብረቆች ብልጭታ በካህናት ራስ ላይ አክሊልን የሚቀዳጅ #የወልደ_እጓለ_እመሕያው_የክርስቶስ ምጽአት እንዚሁ ነው። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ።                            ✝ ✝ ✝ ❤  #የኢትዮጵያ_ኦርቶዶክስ_ተዋሕዶ_ቤተ_ክርስቲያን #ስለ_ዳግም_ ምጽአትና_ስለ_ዓለም_መጨረሻ፣ ስለ ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንም ሁልጊዜ የምታስተምር ቢሆንም በተለይ በዐቢይ ጾም ውስጥ "ደብረ ዘይት" በሚለው ዕለት ሰንበትና በዓመቱ መጨረሻም በወርኃ ጳጒሜን ስለ ዳግም ምጽአትና ስለ ዓለም ፍጻሜ ከቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ነገረ ምጽአቱንና ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን የሚመለከቱ ጥቅሶችን እያነበበችና ምዕመናንን እያስጠነቀቀች በየጊዜም ትኵረት ሰጥታ ታስተምራለች። በእነዚህ ወቅቶች በቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው መዝሙር፣ ቅዳሴና ትምህርቱም ሁሉ ይህንኑ የተመለከተ ነው።                            ✝ ✝ ✝ ❤ #የዚህ_ሳምንት_የዕለቱ_ምስባክ፦ "እግዚአብሔር ገሃደይ መጽእ። ወአምላክነሂ ኢያረምም። እሳት ይነድድ ቅድሜሁ"። መዝ 49፥2-3። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ ፥1-10፣ 2ኛ ጴጥ 3፥10-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 9፥1-10። የሚነበው ወንጌል ሉቃ 17፥11­-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ነው። መልካም የጾምና የጸሎት ጊዜና የዓመቱ የመጫረሻ ዕለተ ሰንበት ለሁላችንንም ይሁንልን።                    @Teamihokidusan

photo content
+2