የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያን🙏
Open in Telegram
የኢ/ኦ/ተ/ቤተክርስቲያንን ዶግማና ቀኖና የጠበቁ የነፍስ ስንቅ የምናገኝበት፦ ✍️"ማንም አንዳች የሚያውቅ ቢመስለው ሊያውቅ እንደሚገባው ገና አላወቀም" ፩ኛ ቆሮ. ፰፥፪ #ለተጨማሪ፦👇✞👇 https://www.youtube.com/EOTC2921 https://www.facebook.com/eotc2921 https://www.tiktok.com/@eotc2921 https://www.instagram.com/eotc2921
Show more4 374
Subscribers
No data24 hours
No data7 days
No data30 days
Posts Archive
4 374
#ስርዓተ_ጸሎት_ወስግደት_ዘሰሙነ_ሕማማት
•••✞✞✞•••✞✞✞•••✞✞✞•••
ከሁሉም በፊት የሰዓቱ ተረኛ አገልጋይ ቃጭል እየመታ ሦስት ጊዜ ቤተ ክርስቲያኑን ይዞራል። የሰባት ቀን ውዳሴ ማርያም ፣ አንቀጸ ብርሃንና መዝሙረ ዳዊት በሙሉ ይጸለያል። የእለቱ ተረኛ መምህር (መሪጌታ) የእለቱን ድጓ ይቃኛል: ድጓው ከአራቱ ወንጌላት ምንባብ ጋር እንዲስማማ ሆኖ የተሰራ ነው። የተቀኘው ድጓ እየተቀባበለ እየተዜመ ይሰገዳል: ሶስት ጊዜ እየተመላለሰ ይባላል።
#የወንጌላቱ_ድጓ_እንደሚከተለው_ነው:-
📖 #በማቴዎስ ወንጌል:-
ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ስምዕዎኬ ለእግዚእነ ኲልክሙ አብያተ ከርስቲያናት ከመ ዘአክበሮሙ ከመ ዘአክበሮሙ ለኦሪት ወለነቢያት በወንጌለ መንግሥት እንዘ ይብል ክርስቶስ ወልደ ዳዊት አማን አማን እብለክሙ: እስከ አመ የኃልፍ ሰማይ ወምድር የውጣ እንተ አሐቲ ኅርመታ ወአሐቲ ቅርጸታ ኢተኃልፍ እምኦሪት ወእምነቢያት: እስከ ሶበ ኲሉ ይትገበር ወይከውን ይቤ እግዚእ ዘበዕብራይስጢ ልሳን በወንጌለ ማቴዎስ ብርሃን ዘእምብርሃን።
📖 #በማርቆስ ወንጌል:-
ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ስምዕዎኬ ለእግዚእነ ኲልክሙ አብያተ ከርስቲያናት ከመ ዘአክበሮሙ ለኦሪት ወለነቢያት በወንጌለ መንግሥት እንዘ ይብል ክርስቶስ ወልደ ዳዊት ኢይምሰልክሙ ዘመጻዕኩ እስዐሮሙ ለኦሪት ወለነቢያት ወኢከመ እንስቶሙ አላ ዳዕሙ ዘእንበለ ከመ ከመ እፈጽሞሙ ይቤ እግዚእ በወንጌለ ሰላሙ አማኑኤል ስሙ ማርያም እሙ።
📖 #በሉቃስ ወንጌል:-
ሃሌ ሉያ ይቤ እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዘ ይሜሕረነ በወንጌለ ሉቃስ ወባሕቱ ይቀልል ሰማይ ወምድር ይኅልፍ እምትደቅ አሐቲ ቃል እምኦሪት።
📖 #በዮሐንስ ወንጌል:-
ሃሌ ሉያ ስብሐት ለአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ በወንጌል ለዘመሐረነ በኦሪት ወበነቢያት ለዘናዘዘነ በከመ መሐረነ እግዚእነ ስብሐት ለእግዚአብሔር ከመ ናምልኮ ለዘፈጠረነ።
ይህ ሦስት ጊዜ ተመላልሶ ከተዘለቀ በኋላ "ለከ ኃይል" የሚለውን በመቀባበል ፲፪ ጊዜ ይበሉ : በመጨረሻም በ፲፫ኛው ከ "ለከ ኃይል" እስከ "እብል በአኮቴት" ድረስ አንድ ጊዜ በኅብረት ይበሉ:-
ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም፤
አማኑኤል አምላኪየ ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም፤
ኦ እግዚእየ ኢየሱስ ክርስቶስ ለከ ኃይል ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም፤
ኃይልየ ወፀወንየ ውእቱ እግዚእየ እስመ ኮንከኒ ረዳእየ እብል በአኮቴት፤
አቡነ ዘበሰማያት ይትቀደስ ስመከ ትምጻእ መንግሥትከ ወይኩን ፈቃድከ በከመ በሰማይ ከማሁ በምድር ሲሳየነ ዘለለዕለትነ ሀበነ ዮም ኅድግ ለነ አበሳነ ወጌጋየነ ከመ ንሕነኒ ንኅድግ ለዘአበሰ ለነ ኢታብአነ እግዚኦ ውስተ መንሱት አላ አድኅነነ ወባልሐነ እምኲሉ እኩይ እስመ ዚአከ ይእቲ መንግሥት ኃይል ወስብሐት ለዓለመ ዓለም።
ከዚህ በመቀጠል "ለአምላክ ይደሉ" የሚለውን መጀመሪያ በመሪ እየቀደሙ በአንሺ እየተከተሉ አንድ ጊዜ ይዝለቁ: በሁለተኛው ክፍል ደግሞ እያስተዛዘሉ አንድ ጊዜ ይበሉ:-
ለአምላክ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም:
ለሥሉስ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም:
ለማሕየዊ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም:
ለዕበዩ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም:
ለእዘዙ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም:
ለመንግሥቱ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም:
ለሥልጣኑ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም:
ለምኲናኑ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም:
ለኢየሱስ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም:
ለክርስቶስ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም:
ለሕማሙ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም:
ለመስቀሉ ይደሉ ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለም (በአርብ):
ለከ ይደሉ ኃይል:
ወለከ ይደሉ ስብሐት:
ወለከ ይደሉ አኮቴት:
ኦ እግዚእየ ኢየሱስ ክርስቶስ ለዓለመ ዓለም።
ከዚህ በመቀጠል የኦሪትና የነቢያት መፃህፍት ይነበባሉ: ቀጥሎም ከተአምረ ማርያም መቅድም እና ተአምር ጀምሮ ሎሎች ተአምራት ዘወትር በየጠዋቱ እንደተለመደው ይነበባሉ: መርገፋቸውን (የምንባባቱ የመግቢያ ጸሎታቸውና የመጨረሻ ጸሎታቸውን) ከሆሣዕና ሠርክ እስከ ዐርብ ሌሊት በአራራይ ዜማ ያድርሱ: ዐርብ ከጠዋት ጀምሮ ግን በዘወትር እንደተለመደው በዕዝል ዜማ ያድርሱ: ተአምረ ኢየሱስ ከተነበበ በኋላ ከወንጌል በፊት ዲያቆኑ ለሰዓቱ የተሰራውን ምስባክ መጀመሪያ በንባብ ቀጥሎም በዜማ ይበል: ሕዝቡም በአንድነት በዜማ ይቀበሉ።
ከዚያም ሁለተኛው ሥርዓተ ስግደት ይጀመራል: ዜማው የሚጀምረው አሁንም በቀኝና በግራ በመቀባበል ነው: አንዱ ይመራል ሌላው ይቀበላል:-
#በመሪ:- ክርስቶስ አምላክነ ዘመጽአ ወሐመ በእንቲአነ በሕማማቲሁ ቤዘወነ:
#በተመሪ:- ንሴብሖ ወናልዕል ስሞ እስመ ውእቱ ገብረ መድኃኒተ በዕበየ ሣህሉ:
ኪርያላሶን ኪርያላይሶን ኪርያላይሶን ኪርያላይሶን:
ኪርያላይሶን ኪርያላይሶን እብኖዲ ናይን ኪርያላይሶን:
ኪርያላይሶን ኪርያላይሶን ታኦስ ናይን ኪርያላይሶን:
ኪርያላይሶን ኪርያላይሶን ማስያስ ናይን ኪርያላይሶን:
ኪርያላይሶን ኪርያላይሶን ኢየሱስ ናይን ኪርያላይሶን:
ኪርያላይሶን ኪርያላይሶን ክርስቶስ ናይን ኪርያላይሶን:
ኪርያላይሶን ኪርያላይሶን አማኑኤል ናይን ኪርያላይሶን፡
ኪርያላይሶን ኪርያላይሶን ትስቡጣ ናይን ኪርያላይሶን።
ኪርያላይሶን የሚለውን ብቻ በመሪ ወገን ፳፩ ገዜ በተመሪ ወገን ፳ ጊዜ ይበሉ: ድምሩ ፵፩ ጊዜ ይሆናል።
✞ የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያንን አስተምሮና ስርዓት የጠበቁ የተለያዩ መርሃ ግብሮች በየቀኑ ወደ እርስዎ ይቀርባሉ፡፡ ለወዳጅዎ #Share በመድረግ የበረከት ተካፋይ ያድርጓቸው ✞
╭══•|❀:๑✞♡✞๑:❀|•══╮
https://t.me/EOTC2921
╰══•|❀:๑✞♡✞๑:❀|•══╯
4 374
Repost from የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያን🙏
✔ "በዚያም ቀን ፀሐይ በቀትር እንድትገባ አደርጋለኊ ይላል ጌታ እግዚአብሔር በብርሃንም ቀን ምድሩን አጨልማለኊ” (አሞ ፰፥፱) ተብሎ
🌾✞ በዕለተ ዐርብ በጌታችን ስቅለት ዕለት ስለተደረገው ስለዚኽ ታላቅ ተአምር ሊቃውንት እንዲኽ ይገልጹታል፡-
☞ “ጐየ ፀሓይ ወጸልመ ወርኅ ወከዋክብትኒ ተኀብኡ ከመ ኢያብርሁ ለምእመናን በጊዜ ስቅለቱ ቅዱስ እንዘ ፍጹም በገሃሁ ወርኅ ኢያብርሀ…” (ፀሓይ ብርሃኑን ነሣ ጨረቃም ጨለመ፤ ከዋክብትም በከበረ ስቅለቱ ጊዜ ለምእመናን እንዳያበሩ ብርሃናቸውን ነሡ፤ ጨረቃም በምልአቱ ሳለ አላበራም፤ ፀሓይ ብርሃኑን በነሣ ጊዜ ፍጡራን ኹሉ በጨለማ ተያዙ፤ የፈጠራቸው ፈጣሪያቸው እንደ ሌባ እንደ ወንበዴ በዕንጨት ላይ ተሰቅሎ እንዳያዩ ቀኑ ጨለመ፤ ባለሟሉ መልአክም ከሓድያንን ያጠፋቸው ዘንድ ሰይፉን በእጁ መዝዞ ይዞ ከመላእክት መኻከል ወጣ፤ የክርስቶስም ቸርነት በከለከለችው ጊዜ ያ መልአክ የቤተ መቅደሱን መጋረጃ በሰይፉ መታው ቀደደውም፤ ከላይ እስከ ታችም ወደ ኹለት አደረገው (ማቴ ፳፯፥፶፩፤ ማር ፲፭፥፴፰፤ ሉቃ ፳፫፥፵፭)፤ መላእክትም ኹሉ በሰማይ ኹነው ርሱን አይተው በአንድነት ሲቈጡ የአብ ምሕረቱ፣ የወልድ ትዕግሥቱ፣ የመንፈስ ቅዱስ ቸርነቱ ከለከለቻቸው፤ ፀሓይ ብርሃኑን ነሣ፤ በጨለማ ተይዞ ሲድበሰበስ ዓለምንም ተወው፤ ይኽ ኹሉ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነፍሱን ከሥጋው ከመለየቱ አስቀድሞ ተደረገ) (ቅዱስ አትናቴዎስ)
♥☞ “እስመ ሶበ ተሰቅለ ክርስቶስ ጸልመ ሰማይ አሜሃ ወፀሓይኒ ሰወረ ብርሃኖ ወወርኅኒ ደመ ኮነ…” (ክርስቶስ በተሰቀለ ጊዜ ያን ጊዜ ሰማይ ጨለማ ኾነ፤ ፀሓይም ብርሃኑን ነሣ፤ ጨረቃም ደም ኾነ፤ ምድርም ተነዋወጠች ደንጊያውም ተከፈለ፤ መቃብራትም ተከፈቱ፤ ስለዚኽም ለፍጡራን ከፈጣሪያቸው ጋር ሊታመሙ ተገባቸው (ማቴ ፳፯፥፵፭-፶፩) (ቅዱስ ሱኑትዩ)
♥ ☞ “ፀሓይ ጸልመ ወወርኅ ደመ ኮነ ወከዋክብት ወድቁ ፍጡነ ከመ ኢይርአዩ ዕርቃኖ ለዘአልበሶሙ ብርሃነ” (ፀሓይ ጨለመ፤ ጨረቃም ደም ኾነ፤ ከዋክብትም ፈጥነው ወደቁ፤ ብርሃንን ያጐናጸፋቸውን የጌታን ዕርቃን እንዳያሳዩ) (አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ)
🌾✞ ሊቁ አባ ጊዮርጊስም ምስጢሩን በመጠቅለል በሕማማት ሰላምታው ላይም፡-
“ፀሓይ ብሩህ አሜሃ ጊዜ ቀትር ጸልመ
ወወርኅኒ ጽዱል ተመሰለ ደመ
ትንቢት ከመ ቀደመ፤ ስብሐት ለከ”
(ብሩህ የኾነ ፀሓይ ያን ጊዜ በቀትር (በስድስት ሰዓት) ጨለመ፤ ጽዱል የኾነ ጨረቃም ደምን መሰለ፤ አስቀድሞ ትንቢት እንደተነገረ፤ ጌታ ሆይ ምስጋና ይገባኻል) በማለት ከትንቢተ ነቢያት በመነሣት በዚኽ በስድስት ሰዓት ምስጋናው ላይ በሰዓቱ ከተከናወነው ምስጢር በመነሣት አስተምሯል፡፡
🌾✞ በመስቀል የተሰቀለው የክብር ባለቤት ሰማይን የፈጠረ ነውና በሰማይ ከላይ የተጠቀሱት ተአምራት ሲደረጉ ምድርንም የፈጠረ ነውና በምድር ደግሞ አራት ተአምራት ማለት የቤተ መቅደሱ መጋረጃ ከላይ እስከ ታች ለኹለት ተቀደደ፤ ምድር ተናውጣ ዐለቶች ተሠንጥቀዋል፤ መቃብራት ተከፍተዋል፤ ከ፭፻ በላይ ሙታን ተነሥተዋል (ማቴ ፳፯፥፵፭፤ ፳፯፥፶፩፤ ፳፯፥፶፪-፶፫)፡፡
🌾✞ ከዚኽ በኋላ የተነገረው ትንቢት ኹሉ እንደተፈጸመ አይቶ የሕይወት ውሃ ምንጭ ጌታ ከእኛ ጽምዐ ነፍሳችንን ለማራቅ በፈቃዱ “ተጠማኊ” ባለ ጊዜ ነቢዩ ዳዊት አስቀድሞ በመዝ ፷፰፥፳፩ ላይ “ወወደዩ ሐሞተ ውስተ መብልዕየ ወአስተዩኒ ብሒአ ለጽምእየ” (በምግቤ ሐሞት ጨመሩበት፤ ለጥማቴም ኾምጣጤ አጠጡኝ) በማለት የተናገረው ትንቢት ሊደርስ ሊፈጸም አይሁድ በዚያም ኾምጣጤ የመላበት ዕቃ ተቀምጦ ነበርና እነርሱም ኾምጣጤውን በሰፍነግ መልተው በሁስጱም አድርገው በአፉ ውስጥ ጨምቀውለታል፡፡
✔ በመጠማቱም ከእኛ ጽምዐ ነፍስን አርቆልናልና፤ ✔ መራራ ሐሞትን በመቅመሱ ከሰው ልጆች ላይ መራራው ሞት ጠፍቷል፡፡
♥ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም በሰባቱ ጊዜያት የጸሎት መጽሐፉ ላይ፤ ጌታችን ሐሞትንና ከርቤን መጠጣቱ ስለምን እንደኾነ፡-
“ከመ ታስትየነ ለነ ደመ ገቦከ ነባቤ
እንተ አስተዩከ ሐሞተ ወከርቤ
ጸማእኩ በጊዜ ትቤ፤ ስብሐት ለከ”
(ነባቢ የሚኾን የጐንኽን ደም ታጠጣን ዘንድ ተጠማኊ ባልኽ ጊዜ ሐሞትን ከርቤን ያጠጡኽ ጌታ ምስጋና ለአንተ ይገባል) በማለት ገልጦታል፡፡
🌾✞ ቅዱሳን ደናግልም መራራ ሐሞትን ጌታችን በመቅመሱ ለ፭ሺሕ ፭፻ ዘመን የሠለጠነ መራራ ሞት ከሰዎች ስለመወገዱ፡-
“ወሰሪቦ እግዚእ ኢየሱስ ብኂዐ ይቤ ተፈጸመ ኲሉ…” (ጌታችን ኢየሱስ መጣጣውን ቀምሶ በመጽሐፍ የተጻፈው ኹሉ ደረሰ ተፈጸመ አለ፤ በጒረሮው መጠማትና በአንደበቱ መድረቅ ከሥጋና ከነፍስ መጠማት አዳነን፤ በቀትርም ጊዜ የዝኆን ሐሞትና ከርቤ የተቀላቀለበት መጻጻንና የበግ ሐሞትን በመጠጣቱ የጣፈጠ የበለስ ፍሬን ስለ በሉ ስለ አዳምና ስለ ሔዋን ከፈለ፤ ለእኛም መሪር የኾነ ሞትንና ርግማንን አጠፋልን) በማለት ተንትነው ጽፈዋል፡፡
ነገረ ክርስቶስ ክፍል አንድ ከሚለው 622 ገጽ ካለው መጽሐፌ በጥቂቱ የተወሰደ
በመስቀል ተሰቅለኽ ፈያታዊ ዘየማንን ያሰብከው አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በቸርነትኽ ዐስበን፡፡
✍በመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ
✞ የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያንን አስተምሮና ስርዓት የጠበቁ የተለያዩ መርሃ ግብሮች በየቀኑ ወደ እርስዎ ይቀርባሉ፡፡ ለወዳጅዎ #Share በመድረግ የበረከት ተካፋይ ያድርጓቸው ✞
╭══•|❀:๑✞♡✞๑:❀|•══╮
https://t.me/EOTC2921
╰══•|❀:๑✞♡✞๑:❀|•══╯
4 374
Repost from የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያን🙏
🌾⛪️ #የአምላካችን_የክርስቶስ_ጥንተ_ስቅለት 🌾⛪️
መጋቢት ፳፯
🌾✞ የነገሥታት ንጉሥ የሕይወት ራስ ኢየሱስ ክርስቶስን የአይሁድ ጭፍሮች በዕለተ ዐርብ የእሾኽ አክሊል ጐንጒነው በራሱ ላይ ደፍተውለታል፤ የእሾኽ አክሊል በመቀዳጀቱ በዘፍ ፫፥፲፰ ላይ አዳምን አስቀድሞ “ምድር እሾኽንና አሜከላን ታበቅልብኻለች” ብሎት ነበርና ያነን መርገም ደምስሶለት ለአዳም ክሷል፡፡
🌾✞ ዳግመኛም አዳምና ሔዋን ምክረ ከይሲን ሰምተው የድል ነሺዎች አክሊል ተለይቷቸው ነበርና ያነን ሰማያዊ አክሊል እንደመለሰልን ለማጠየቅ፡፡ ይኽ ለካሳ አምላካችን ስለፈጸመው የድኅነት ምስጢር ቅዱሳት ደናግል በጥልቀት እንዲኽ አብራርተዋል፡-
🌾✞ “አስተቀጸልዎ ከመዝ ለርእሰ ሕይወት አክሊለ ሦክ …” (የሕይወት መገኛ ርሱን የእሾኽ አክሊልን አቀዳጁት፤ መላእክትን የብርሃን ራስ ቁር የሚያቀዳጃቸው የነገሥታት ገዢ የሚኾን ርሱን የሾኽ አክሊል አቀዳጁት፤ በሾኽ አክሊልም ከራሱ ክፍል ያቆሰሉት ሺሕ ናቸው፤ ከራሱም ቊስሎች ደም እንደ ውሃ በዝቶ ፈሰሰ፤ ፊቱም ደምን ለበሰ ሰውነቱም በደም ተጠመቀ፤ የጽዮን ልጆች እናቱ ያቀዳጀችውን አክሊል ተቀዳጅቶ አዩት፤ ተድላ ደስታ የሚያደርግበትና የሙሽርነቱ ቀን ነውና (መሓ ፫፥፲፩) … ነገር ግን የሾኽ አክሊልን በመቀዳጀቱ በምድራችን ላይ የበቀሉትን አሜከላና እሾኽ ርግማንን አጠፋልን (ዘፍ ፫፥፲፰)፤ ራሱንም በዘንግ በመመታቱ የታላቁን እባብ ሰባቱን ራሶቹን ዐሥሩን ቀንዶቹን አጠፋልን (ራእ ፲፫፥፩)) ብለዋል፡፡
🌾✞ ሊቁ ቅዱስ ኤራቅሊስም ስለፈጸመው ካሳ እንዲኽ አስተምሯል፡-
♥☞ “እንዘ ይትቄጸል አክሊለ ሦክ አብጠለ ኲነኔሁ ለቀኖተ ሞት ወእንዘ ቅንው ዲበ ዕፀ መስቀል ኢተዐርቀ እምነ መንበሩ…” (የእሾኽ አክሊል ደፍቶ የሞትን ሥልጣን ፍርድ አጠፋ፤ በመስቀል ላይ ተቸንክሮ ሳለ ከዙፋኑ አልተለየም፤ ከባሕርይ አባቱ ከአብ፤ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ አልተለየም፤ በምድር አይሁድ እንደ በደለኛ ሲዘብቱበት፤ መላእክት በሰማይ የከበረ ጌትነቱን ይናገሩ ነበር) (ቅዱስ ኤራቅሊስ)
🌾✞ እጆቹና እግሮቹ ስለመቸንከሩ አስቀድሞ በነቢዩ ዳዊት ዐድሮ በመዝ ፳፩፥፲፮ ላይ “ብዙ ውሾች ከብበውኛልና የክፋተኞች ጉባኤም ያዙኝ እጆቼንና እግሮቼን ቸነከሩኝ፤ ዐጥንቶቼ ኹሉ ተቈጠሩ እነርሱም አዩኝ ተመለከቱኝም” በማለት ውሻ ከአፉ ያወጣውን መልሶ ለምግብነት እንዲፈልገው፤ አይሁድም ኦሪትን እለፊ ካላት በኋላ ሲሠሯት በመገኘታቸው በውሻ መስሎ ትንቢት ያናገረባቸው ሲኾን፤ ይኽም ሊፈጸም ንጹሓት እጆቹና እግሮቹ በምስማር ከዕፀ መስቀሉ ጋር አያይዘው ቸንክረውታል፡፡
🌾✞ የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ሔዋን በእግሮቿ ወደ ዕፀ በለስን በማምራቷ በድላ ነበርና ለርሷ ካሳ ሊኾን ንጹሓን እግሮቹ ሲቸነከሩ፤ በእጆቿም በለስን በመቊረጧ ንጹሐ ባሕርይ አምላክ እጆቹ በችንካር ተቸንክረዋል፡፡ በመቸንከሩም ለ፭ሺሕ ፭፻ ዘመን በሰው ልጆች ላይ የሠለጠነ የሞት ችንካር ጠፍቶልናል፡፡
🌾✞ ምስጋና ይግባውና ኢየሱስ ክርስቶስ በመቸንከሩ ስለፈጸመው ካሳ ደናግል ሲተነትኑ፡-
♥☞ “ወበቅንዋቲሁ ሠበረ ለነ ቀኖተ ሞት …” (በመቸንከሩም የሞት ችንካርን አጠፋልን፤ ሔዋን በእግሮቿ ወደ ዕፀ በለስ ስለ ተመላለሰች እጆቹንና እግሮቹን በመቸንከር ከፍሏልና፤ በእጆቿም የበለስን ፍሬ ስለቈረጠች ፈንታ በእውነት የእግዚአብሔር ቃል በሥጋው ከመስቀል ዕንጨት ጋራ ተቸነከረ) በማለት አስተምረዋል፡፡
🌾✞ መተርጒማን ሊቃውንት እንዳመሰጠሩት ጌታ በዕንጨት መስቀል ላይ መሰቀሉ ስለምን ነው ቢሉ?፤ እሾኽ በሾኽ ይነቀሳል ነገር በነገር ይወቀሳል እንዲሉ በዕፀ በለስ ምክንያት የገባውን ኀጢአት በዕፅ ለማውጣት በዕፀ መስቀል ላይ ተሰቅሏል፡፡
🌾✞ ጌታችን ከምድር ከፍ ከፍ ብሎ ስለምን ተሰቀለ? ቢሉ፦ “እምከመ ተለዐልኩ እምድር እስሕብ ኲሎ ኀቤየ” (ከምድር ከፍ ከፍ ባልኊ ጊዜ ኹሉን እስባለኊ) ብሎ ነበርና ይኽነን ሊፈጽም ነው (ዮሐ ፲፪፥፴፪)፡፡
ዳግመኛም ከምድር ከፍ ከሰማይ ዝቅ ብሎ መሰቀሉ “ኅሩይ ማእከለ እግዚአብሔር ወሰብእ” እንዲል አምላክ ወሰብእ ኾኖ እንዳስታረቀን ለማጠየቅ፡፡
በመጨረሻም ምድርን በኪደተ እግሩ እየተመላለሰ እንደ ቀደሳት፤ ዐየራትን ደግሞ ሥብ እያጤሱ አስተራኲሰውት ነበርና አየራትን ለመቀደስ ነው፡፡
🌾✞ ንጹሐ ባሕርይ ጌታችንን አይሁድ መስቀሉን አሸክመው ቀራንዮ ወደሚባል ቦታ ከወሰዱት በኋላ ኹለት ወንበዴዎችን በቀኝና በግራ አድርገው ጌታችንን በመኻከል ሰቅለውታል (ማቴ ፳፯፥፴፰፤ ማር ፲፭፥፳፯፤ ሉቃ ፳፪፥፴፫፤ ዮሐ ፲፱፥፲፰)፡፡
🌾✞ ክፉዎች አይሁድ ይኽነን ያደረጉበት ምክንያት በክፋት ነው፤ ይኸውም በቀኝ የሚመጡ ሰዎች በቀኝ የተሰቀለውን ወንበዴ አይተው “ይኽ ምንድነው?” ብለው ሲጠይቁ “ወንበዴ ነው” ይሏቸዋል፤ ከዚያም ጌታን “ይኽስ ምንድነው?” ብለው ሲጠይቁ “ይኽስ ከርሱ ልዩ ነውን አንድ ነው እንጂ” ብለው ሰዎችን ለማሳሳት፤ በግራ የሚመጡ ሰዎች በግራ የተሰቀለውን ወንበዴ አይተው “ይኽ ምንድነው?” ብለው ሲጠይቁ “ወንበዴ ነው” ይሏቸዋል፤ ከዚያም ጌታን “ይኽስ ምንድነው?” ብለው ሲጠይቁ “ይኽስ ከርሱ ልዩ ነውን አንድ ነው እንጂ” ብለው ሰዎችን ለማሳሳት ያደረጉት ነው፡፡
✔ዳግመኛም አነገሥንኽ ብለውታልና ቀኛዝማች ግራዝማች ሾምንልኽ ለማለት ለመዘበት፡-
በተጨማሪም ነቢዩ ኢሳይያስ በምዕ ፶፫፥፲፪ ላይ “ከዐመፀኞችም ጋር ተቈጥሯልና” የሚለው ትንቢቱን ሊፈጽም ሲኾን ምስጢሩ ግን እኛን ከጻድቃን ጋራ አንድ ያደርገን ዘንድ ርሱ ከበደለኞች ጋር ተቈጥሯል፤ ሌላውም በዕለተ ምጽአት እኛን ኃጥኣንን በግራ ጻድቃንን በቀኝ ታቆማለኽ ሲያሰኛቸው ነበር (ማቴ ፳፭፥፴፫፤ ራእ ፩፥፯)፡፡
🌾✞ በኹለት ወንበዴዎች መኻከል ከሰቀሉት በኋላ ጲላጦስም “የአይሁድ ንጉሥ የናዝሬቱ ኢየሱስ” የሚል ጽሕፈት በዕብራይስጥና በሮማይስጥ በግሪክም ጽፎ በመስቀሉ ላይ አኖረው፤ (ዮሐ ፲፱፥፲፰-፳፪)፤ የአይሁድ ካህናት አለቆች ጲላጦስን “ርሱ የአይሁድ ንጉሥ ነኝ እንዳለ እንጂ የአይሁድ ንጉሥ ብለኽ አትጻፍ” ሲሉት፤ ጲላጦስም “የጻፍኹትን ጽፌአለኊ” ብሎ መልሶላቸዋል፤ ይኽነንም በሕማማት ድርሳኑ ላይ ሲተረጒሙት፡- “ወዝ መጽሐፈ ጌጋይ ዘጸሐፎ ጲላጦስ ወአንበሮ መልዕልተ ርእሱ ይደምስስ ለነ በኲሉ ጊዜ መጽሐፈ ዕዳነ ዘጸሐፉ አጋንንት” (ጲላጦስ ጽፎ ከራሱ በላይ ያኖረው በደሉን የሚናገር ይኽ መጽሐፍ ኹልጊዜ አጋንንት የጻፉትን የዕዳችንን መጽሐፍ ያጠፋልን ዘንድ ነው) በማለት አራቅቀው ገልጠዋል፡፡
🌾✞ ጌታችን በሚሰቀልበት ጊዜ ብርሃን ያለበሳቸውን አምላክ ዕርቃኑን ለመሰወር ከስድስት ሰዓት እስከ ዘጠኝ ሰዓት ድረስ ፀሓይና ጨረቃ ብርሃናቸውን ነሥተዋል (ማቴ ፳፯፥፵፭፤ ማር ፲፭፥፴፫፤ ሉቃ ፳፫፥፵፬-፵፭)፡፡
❖ ይኽ በጌታ ስቅለት ዕለት እንደሚደረግ አስቀድሞ በነቢዩ አሞጽ ኹለት ጊዜ በትንቢት ተነግሯል፡- ይኸውም
✔“የእግዚአብሔር ቀን ብርሃን ሳይኾን ጨለማ አይደለምን? ጸዳል የሌለውም ድቅድቅ ጨለማ አይደለምን?” (አሞ ፭፥፳)
4 374
*ኒቆዲሞስ የዐብይ ጾም ፯ኛው ሳምንት*
*ኒቆዲሞስ*
🌾በቤተክርስቲያናችን 7ተኛው የዐብይ ጾም ሳምንት ኒቆዲሞስ ይባላል። ትርጓሜው የአይሁድ መምህር ወይም ደግሞ የጌታችን ደቀ መዝሙር የለሊት ተማሪ ማለት ነው።
🌾ኒቆዲሞስ ከፈረሲያዊያን ወገን ሲሆን በኢየሩሳሌም በሃብት ቢሉ በውቀት እንዲሁም በስልጣን የአይሁድ አለቃ ነበር።
🌾እርሱም በሌሊት ወደ ኢየሱስ መጥቶ መምህር ሆይ እግዚአብሔር እርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸው እነዚህን ታምራቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና መምህር ሆይ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን አለዉ። ዮሐ፡፫፥፪
🌾የለሊት ተማሪ ኒቆዲሞስ የለሊቱን ጊዜ ለትምህርት ለምን መረጠ አይሁድ ማንም ከእኛ ወገን የሆነ የክርስቶስ ደቀ መዝሙር ከሆነ ሀብቱ ንብረቱ ይወሰድበታል። በቤተመቅደስ አይገባም፤ መሰዋት አይወስድም ብለው ነበርና የአይሁድን ፈርቶ ሃብት ንብረቱን ወዶ እንዳይታወቅበት በለሊት ይመጣል ነበር።
*ውዳሴ ከንቱ ሽቶ፦* ኒቆዲሞስ መምህር ስለነበር ስማር ሰዎች ብያዩኝ ሊቅ ነኝ እያለ እስከዛሬ ትምህርት አልጨረሰም እንዳይሉት መምህር ምርባል ይቀርበኛል ብሎ በለሊት ይመጣ ነበር።
በሌላ በኩል ደግሞ የቀን ልብ ባከነ ነው አይን ብዙ ያያል ሃሳብ ይበታተናል በተሰበሰበ ልብ ለመማር በለሊት ይማር ነበር።
🌾ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለመማር የመጣውን ራሱን እየሄደ ያስተምር ነበርና
ኒቆዲሞስ ምንም በለሊት ቢመጣም ማወቅ ፈልጎ ነውና ስለ ዳግም መወለድ / ስለጥምቀት በእግዚአብሔር ልጅ ስለ ማመንና ስለጽድቅ ስራ በዝርዝር አስተምሮታል።
*የዮሐንስ ወንጌል*፫፡፩-፲፪ ከፈሪሳውያን ወገን የአይሁድ አለቃ የሆነ ኒቆዲሞስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ እርሱም በለሊት መጥቶ መምህር ሆይ እግዚአብሔር ከእሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸው እነዚህ ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና መምህር ሆይ በእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን አለው።
🌾ኢየሱስ መልሶ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግስት ሊያይ አይቻልም።
🌾 *ኒቆዲሞስ* "ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል? ሁለተኛ ወደ እናቱ ማህፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን?" አለው፤
🌾 *ኢየሱስም መለሰ*፦ እንዲህ ሲል እውነት እውነት እልሃለሁ ሰው ከሆነ ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግስት ሊገባ አይችልም። ከስጋ የተወለደ ስጋ ነው፤ ከመንፈስ የተወለደ መንፈስ ነው። ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል ስላለሁ አታድንቅ።
🌾በመጨረሻም ኒቆዲሞስ የአርማትያንስ ሰው ከሚሆን ከዮሴፍ ጋር በመሆን የጌታችን ቅዕዱስ ስጋ በንጹህ በፍታ ገንዞ በአዲስ መቃብር ቀብሯል።
🌾ወንጌላዊ ቅድስ ዮሐንስ ቀድሞ በለሊት ወደ ጌታችን ኢየሱስ ሄዶ የነበርው ኒቆዲሞስ መጣ ቀብተውም የሚቀበርበት መቶ ወቄት የከርቤና የእሬት ቅእልቅል ሽቶ አመጣ። ዮሐ፡፲፱፥፴፱ በዚህም ኒቆዲሞስ ከምክር አይሁድ ያልተቀላቀለ መሆኑ ይታወቃል።
🌾 *ትሁት* የሚያሰኘው ሳያውቁ አላወቅም ማለት ሳይሆን እያወቁ አላውቅም ማለት ነው።
🌾 *ሳይማሩ* ተምሬያለሁ ማለት ሳይሆን ተምረው ልክ እንደ ኒቆዲሞስ ለመማር ራስን ዝቅ ማድረግ ነው።
*መልካም ዕለተ ሠንበት ይሁንልን*🙏
4 374
🌾✞ #ይበራል_በክንፉ ✞🌾
ይበራል በክንፉ ምልጃውም ፈጣን ነው
የአምላክ ስም አለበት ስሙ ሚካኤል ነው
ያሳደገኝ መልአክ ዛሬም ከኔ ጋር ነው /፪/
ከፊቴ ቀደመ ደመናን ዘርግቶ
እንዳልደናቀፍ ጉድባዎቼን ሞልቶ
ዛሬ ላለሁበት ብሩቱ ጉልበት ሆነኝ
ሰው ለመባል በቃሁ ሚካኤል ደገፈኝ
#አዝ----▶✞◀---▶✞◀---
በእናቴ እቅፍ ገብቼ መቅደሱ
አለሁ እስከዛሬ አጥሮኝ በመንፈሱ
የህይወቴን ሰልፎች አለፍኩ ከርሱ ጋራ
ተፅፏል በልቤ የሚካኤል ስራ
#አዝ----▶✞◀---▶✞◀---
በዙሪያዬ ተክሎ የእሳት ምሰሶውን
ፅድቅ እየመገበ ኣሳደገኝ ልጁን
የአምላኬን ምስጋና ዘውትር እያስጠናኝ
እርሱ ነው ሚካኤል በመዝሙር የሞላኝ
#አዝ----▶✞◀---▶✞◀---
ፊት ለፊት ተተክሎ ከታናሿ መንደር
ይስማኝ ነበረ ቅኔው ሲደረደር
ይወስደኛል ደጁ እየቀሰቀሰ
ታላቁት በረከት በውስጤ አፈሰሰ
#አዝ----▶✞◀---▶✞◀---
ሴኬምን እንዳላይ ክንፎቹን ጋረደ
መራኝ ወደ ህይወት መዳኔን ወደደ
የሞአብን ቋንቋ ከአፌ ላይ አጥፍቶ
በፀጋው ቃል ቃኘኝ በበረከት ሞልቶ
4 374
🌾✞ በቅዱስ ያሬድ ጾመ ድጓ ዘወረደ እየተባለ የሚታወቀው፣ በጾመ ዐርባው ወቅት በተለይም በመጀመሪያው ሳምንት የሚገኘው ድርሰት በነግህ በሠለስት፣ በቀትርና በሠርክ እንደዚሁም ቅዳሜና እሑድ በሌሊት የሚዘመር ነው፡፡ በውስጡም የያዘው ፍሬ ሐሳብ የጾምን፣ የጸሎትን፣ የምጽዋትንና የፍቅርን ጠቃሚነት አጕልቶ የሚያስተምር ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በዘወረደ ጾመ ድጓው ‹‹አዘዞ እግዚአብሔር ለሙሴ ወይቤሎ ሰብእከ ወላህምከ ወኵሉ ቤትከ ያዕርፉ በሰንበት፤ እግዚአብሔር ሙሴን ሕዝብህ የከብትህ መንጋህ ቤተሰብህ ዅሉ በሰንበት ቀን ከድካማቸው ይረፉ በማለት አዘዘው፤›› በማለት ሰንበት ለሰው ልጆች ብቻ ሳይኾን፣ ሕይወት ላለው ነገር ዅሉ ጸጥታና ሰላም የሰፈነባት የዕረፍት ቀን ስለመኾኗ ተናግሯል /ዘፀ.፳፥፲፤ ፳፫፥፲፪/፡፡ በዚህም ወቅቱ ‹‹ዘመነ ጾም›› ወይም ‹‹ጾመ ሙሴ›› ይባላል፡፡
🌾✞ በአጠቃላይ ጾምን መጾም የፈቃድ ብቻ ሳይኾን የትእዛዝም ነው፡፡ ነቢዩ ኢዩኤል ‹‹ቀድሱ ጾመ ወስብኩ ምሕላ …፤ ጾምን ያዙ፤ አጽኑ፡፡ ምሕላንም ዐውጁ፡፡ ሸማግሌዎቹን ከፈጣሪያችን ቤት ሰብስባችሁ በአንድነት ኾናችሁ ወደ እግዚአብሔር ጩኹ (ለምኑ)፤›› ብሏል ኢዩ.፩፥፲፩፤ ፪፥፲፪፤ ፲፪፥፲፭-፲፮/፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹ወኩኑ ላእካነ ለእግዚአብሔር በጾም ወበንጽሕ፤ በጾም፣ በንጽሕና ተወስናችሁ እግዚአብሔርን አገልግሉ፤›› ብሏል /፪ቆሮ.፮፥፬-፮/፡፡ ጾም ባያስፈልግ ኖሮ ጌታችን ‹‹በምትጾሙበት ጊዜ እንደ ግብዞች አትኹኑ … ስለ ጽድቅ የሚራቡ የሚጠሙ ንዑዳን ክብራን ናቸው፤›› ባላለም ነበር /ማቴ.፭፥፮-፲፮/፡፡ ነቢዩ ዳዊትም ‹‹ጕልበቶቼ በጾም ደከሙ፤ ሥጋዬም ቅባት በማጣት ከሳ፤›› /መዝ.፻፰፥፳፬/ ማለቱ የጾምን አስፈላጊነት ያስረዳል /ዳን.፱፥፫-፬፤ ፲፬፥፭/፡፡ በቁራኝነት አብሮ የሚኖር መንፈስ ርኩስ (ሰይጣን) እንኳን በጾም የሚወገድ መኾኑን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተናግሮአል /ማቴ.፲፯፥፳፩፤ ማር.፱፥፪/።
🌾✞ ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹ሙሽራውን ከእነሱ ለይተው የሚወስዱበት ጊዜ ይመጣል፡፡ ያን ጊዜ ይጾማሉ፤›› ያለውን የጌታን ቃል መሠረት በማድረግ ጌታችን ሞቶ ከተነሣ እና ካረገ በኋላ ጾመዋል፤ የጾምንም ሕግ ሠርተዋል /ሐዋ.፲፫፥፫/፡፡ ሠለስቱ ምዕትም ‹‹ሐዋርያት የጾሙትንና እንዲጾም የወሰኑትን መጾም ይገባል›› ብለው አጽዋማትን እንድንጾም መወሰናቸው ይህን የጌታችንን ቃል መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሠራዔ ሕግ እንደመኾኑ ዐርባ ቀን ዐርባ ሌሊት ጾሞ እንጂ ዝም ብሎ ጾሙ አላለንም፡፡ ስለዚህ ጾም ትእዛዝ (ሕግ) መኾኑን ተገንዝበን ዅላችንም መጾም አለብን።
✍በሊቀ ጉባኤ ቀለመወርቅ ውብነህ
⛪️ መጪውን የዐቢይ ጾም የነቢያት፣ የሐዋርያት፣ የጻድቃንና የሰማዕታት አምላክ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ልጅ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይባርክልን፤ ተስፋ የምናደርጋትን መንግሥቱንም እንዲያወርሰን ዅላችንም በጾሙ በርትተን በጸሎትና በስግደት ታግዘን አምላካችን እግዚአብሔር መልካሙን ሁሉ ያደርግልን ዘንድ ልንማጸነው ይገባል፡፡
🙏✞ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር ✞🙏
4 374
🌾✞ ዐቢይ ጾም ✞🌾
🌾✞ ጾም ማለት መተው መከልከል ማለት ነው፡፡ ጾም በእግዚአብሐር የተቀደሰ ተግባር ስለኾነ ወደ ቅድስና ጎዳና የሚመራ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችንም ሥርዓት ሠርታ ጾመን ከአምላካችን ጋር ኅብረት እንዲኖረን፤ መንፈሳዊ ኃይል እንድናገኝ ታደርጋለች። በጾም ወራት ከመባልዕት መከልከል ብቻ ሳይኾን ዐይን ክፉ ከማየት፣ አንደበት ክፉ ከመናገር፣ ጆሮ ክፉ ከመስማት መቆጠብ እንደሚገባው በቅዱሳት መጻሕፍት ተጽፎአል፡፡ ‹‹ይጹም ዐይን ይጹም ልሳን እዝንኒ ይጹም እምሰሚዓ ኀሡም በተፋቅሮ›› እንዲል ቅዱስ ያሬድ /ጾመ ድጓ/፡፡ በጾም ወራት ላምሮት፣ ለቅንጦት የሚበሉ ወይም ለመንፈሳዊ ኃይል ተቃራኒ የኾኑ ሥጋዊ ፍትወትን የሚያበረታቱ፣ ሥጋንና የሚያሰክሩ መጠጦችን /ዳን.፲፥፪-፫/፣ ቅቤና ወተትን ከመጠቀም መታቀብ እንደሚገባ ታዟል መዝ.፻፰፥፳፬፣ ፩ቆሮ.፯፥፭፤ ፪ቆሮ.፮፥፮/፡፡
🌾✞ በብሉይ ኪዳን ጾም ከፍተኛ ቦታ ነበረው፡፡ የብሉይ ኪዳን ነቢያት ከእግዚአብሔር በሚገናኙበት ወራት እህልና ውኃ በአፋቸው አይገባም ነበር /ዘፀ.፴፬፥፳፰/፡፡ አስቴር አስቀድማ ሦስት ቀን ጾማ ጸልያ በእስራኤል ላይ የመጣውን መቅሠፍት እንዲመለስ አድርጋለች /አስቴር ፬፥፲፭-፲፮/፡፡ በዘመኑ በኃጢአት ብዛት የታዘዘው የእግዚአብሔር መዓት የሚመለሰውም ሕዝቡ በጾም ሲለምኑትና ሲማልዱት ነበር /ዮናስ ፪፥፯-፲/፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ጾም ሰው ሠራሽ ሕግ ሳይኾን ራሱ ክርስቶስ የሠራው ሕግ ነው /ማቴ.፬፥፪፤ ሉቃ.፬፥፪/፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም በየጊዜው ከመንፈስ ቅዱስ ትእዛዝ የሚቀበሉት በጾም በጸሎት ላይ እንዳሉ ነበር /ሐዋ.፲፫፥፪/፡፡ ለስብከተ ወንጌል የሚያገለግሉ ዲያቆናትና ቀሳውስትም የሚሾሙት በጾምና በጸሎት ነው ሐዋ.፲፫፥፫፤ ፲፬፥፳፫/፡፡ እንደ ቆርነሌዎስ ያሉ ምእመናን ያላሰቡትን ክብር ያዩና ያገኙ የነበረውም በጾምና በጸሎት ፈጣሪያቸውን በመማጸን ነው /ሐዋ.፲፥፴/፡፡
🌾✞ ዐቢይ ጾም ጌታችን ከተጠመቀ በኋላ ዐርባ ቀን የጾመው፤ እኛም እንድንጾማቸው በቤተ ክርስቲያናችን ከታዘዝናቸው ሰባቱ የአዋጅ አጽዋማት አንዱ ነው፡፡ ምእመናን ጌታችን ያደረገውን ምሳሌ ተከትለን ጾሙን በየዓመቱ እንጾመዋለን፡፡ ዐቢይ ጾም ስምንት ሳምንታት (፶፭ ቀኖች) አሉት፡፡ በውስጡ ስምንት ቅዳሜዎች፣ ሰባት እሑዶች ይገኛሉ፡፡ ይኸውም ዐሥራ አምስት ቀን ማለት ነው፡፡ እነዚህ ቀናት ከጥሉላት እንጂ ከእኽል ውኃ ስለማይጦሙ የጦሙ ወራት ዐርባ ቀን ብቻ ይኾናል፡፡
🌾✞ ጾሙ በተለያዩ ስሞች ይጠራል፤ አንደኛ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ የጾመው በመኾኑ፣ እንደዚሁም ‹‹ዐቢይ እግዚአብሔር ወዐቢይ ኀይሉ ዐቢይ እግዚአብሔር ወብዙኅ አኰቴቱ›› መዝ.፵፯፥፩፤ መዝ.፻፵፮፥፭/ የተባለ ጌታችን የጾመው ጾም ስለኾነ ‹‹ዐቢይ ጾም›› ይባላል፡፡ ሁለተኛ ‹‹ሁዳዴ ጾም›› ይባላል፡፡ ይህም የመንግሥት እርሻ ወይም ማንኛውም የሕዝብ ብዛት ያለበት ሥራ ሁዳድ ስለሚባል ሲኾን፣ ዐቢይ ጾምም ከአጽዋማት ዅሉ ብዙ ቀናት ስለሚጾምና ኃያሉ አምላካችን ስለጾመው ነው /አሞ.፯፥፩/፡፡ ሦስተኛ ‹‹በአተ ጾም›› ይባላል፡፡ የጾም መግቢያ፣ መባቻ ማለት ነው፡፡ አራተኛ ‹‹ጾመ ዐርባ›› ይባላል። ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው ፵ ቀን ስለኾነ /ማቴ.፬፥፩/፡፡ አምስተኛ ‹‹ጾመ ኢየሱስ›› ይባላል፡፡ ጌታችን እርሱ ጾሞ፣ ጹሙ ብሎ ስላዘዘን፡፡ ስድስተኛ ‹‹ጾመ ሙሴ›› ይባላል፡፡ ቅዱስ ያሬድ በዘወረደ ጾመ ድጓው ‹‹ከመዝ ይቤ ሙሴ እስመ ለዓለም ሙሴኒ ይቤ በውስተ ኦሪት›› እያለ ስለዘመረ /የሰኞ ዕዝል/፡፡
🌾✞ ከዐቢይ ጾም ሳምንታት መካከል የመጀመሪያው ሳምንት ‹‹ዘወረደ (ዘመነ አዳም)›› ይባላል፡፡ ዘወረደ ማለት ከላይ የመጣ፣ የወረደ ማለት ነው፡፡ ይህም አምላካችን አዳምንና ልጆቹን ከሞት ለማዳን ሲል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መኾኑንና የፈጸመውን የማዳን ሥራ ያመለክታል፡፡ ‹‹ከሰማይ ከወረደው በቀር ወደሰማይ የወጣ የለም›› ካለው ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ቃል በመነሣት ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ‹‹ዘወረደ እምላዕሉ አይሁድ ሰቀሉ ወሚመ ኢያእመሩ እግዚአ ኵሉ ዘየሐዩ በቃሉ›› በማለት በጾመ ድጓው መጀመሪያ ላይ ይህን ዕለት ገልጾታል፡፡ ትርጕሙም ‹‹አዳምን ለማዳን ከሰማይ የወረደውን አምላክ አይሁድ ሰቀሉት፤ የሰማይ ሥልጣን ያለው የዅሉ ጌታ እንደኾነም ምንም አላወቁም›› ማለት ነው፡፡ ይህም ድርሰት በቤተ ክርስቲያናችን የጾም መጀመሪያ የኾነው ዕለተ ሰንበት ዋዜማ፣ መግቢያ (መሐትው) ኾኖ ከዋዜማ በፊት ምንጊዜም በየዓመቱ ይቆማል፤ ይዘመራል፤ ይመሰገናል፡፡
🌾✞ በዚህ ሳምንት በተለይም እሑድና ሰኞ የሚነገሩት ውዳሴያት ከመጻሕፍተ ኦሪትና ነቢያት የተወሰዱ ናቸው፡፡ ሁለተኛም ሳምንቱ ‹‹ሙሴኒ›› በመባል ይታወቃል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ለማዳን ከሰማይ መውረዱንና በመስቀል መሰቀሉን ስለሚያወሳ ነው፡፡ በተጨማሪም ይህ የመጀመሪያው ሳምንት ‹‹ጾመ ሕርቃል›› ይባላል። ሕርቃል (ኤራቅሊየስ) የቤዛንታይን ንጉሥ ነበር፡፡ ይህ ሳምንት በስሙ የተጠራበት ምክንያት በዘመኑ ፋርሶች ኢየሩሳሌምን ወርረው፣ የጌታችንን መስቀል ማርከው ወስደውት ነበር፡፡ እርሱ ወደ ፋርስ ዘምቶ መስቀሉን ከእነርሱ ነጥቆ ይዞ ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሷል፡፡
🌾✞ ሕርቃል ከፋርሶች ጋር ከመዋጋቱ በፊት ሐዋርያት በሲኖዶሳቸው ‹‹ነፍስ የገደለ ሰው እስከ ዕድሜ ልኩ ይጹም›› ብለው ሥርዓት ሠርተዋልና ጾሙን ፈርቶ ስለነበር በኢየሩሳሌም የነበሩ ምእመናን አሳቡን ደግፈው ‹‹አንተ ጠላታችንን አጥፋልን፤ መስቀሉን አስመልስልን እንጂ የአንድ ሰው ዕድሜ ቢበዛ ሰባ፣ ሰማንያ ዓመት ነው፡፡ ጾሙን አምስት አምስት ቀን ተከፋፍለን እኛ እንጾምልሃለን›› ብለው ጾመውለታል፡፡ ይህንን መሠረት በማድረግ ያላወቁት አንድ ጊዜ ጾመው ትተውታል፡፡ ያወቁት ግን ቀድሞም ሐዋርያት ጾመውታል ብለው ሥርዓት አድርገው በዓመት በዐቢይ ጾም መጀመሪያ ላይ ጾመ ሕርቃል እያሉ የሚጾሙት ኾነዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ይህንን ሥርዓት መሠረት በማድረግ ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጾም የመጀመሪያውን ሳምንት ጾመ ሕርቃል በሚል ስም ሰይማ እንዲጾም አድርጋለች (የመጋቢት ፲ ቀን ስንክሳርን ይመልከቱ)፡፡
4 374
🌾 ✞ ጾመ ሰብአ ነነዌ ✞ 🌾
ሰኞ ጥር ፳፱/፳፻፲፭ ዓ/ም ይጀምራል።
✔‹‹ጾመ ሰብአ ነነዌ፤ የነነዌ ሰዎች ጾም›› የሦስት ቀን ጾም የጾሙት በነነዌ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች ናቸው፡፡ ከተማዋም (ነነዌ) በጤግሮስ ወንዝ ዳርቻ የምትገኝ ስትኾን መሥራቿም ናምሩድ ነው (ዘፍ.፲፥፲፩-፲፪)፡፡ ጥንታዊቷ የነነዌ ከተማ ለአሦር መነሻ የሆነች፤ እጅግ ሰፊና ያማረች፤ የቅጥሯ ርዝመትም ፲፪ ኪሎ ሜትር የሚሸፈን ነበር፡፡ በከተማዋ ንጉሡ ሰናክሬም ብዙ ሕንጻዎችን ገንብቶ ነበር (ዮናስ ፬፥፲፩)፡፡
✔በዚያ ዘመን የነበሩ የነነዌ ሰዎች ኃጢአታቸው በዝቶ እግዚአብሔር ሊያጠፋቸው ሲል ዮናስ የስሙ ትርጓሜ ‹ርግብ› የሆነ በዳግማዊ ኢዮርብዓም ዘመነ መንግሥት የነበረ ነቢይን ቸርነትና ምሕረቱ የማያልቅበት እግዚአብሔር መክሮ፣ ዘክሮ እንዲመልሳቸውና ንስሐ እንዲገቡ ነቢዩ ዮናስን ወደ ነነዌ ሕዝብ ላከው (ሉቃ.፲፩፥፴)፡፡ ይህ ነቢይ መኖሪያው በገሊላ በጋትሔፌር ድንበር ከተማ ነበረ፤ አባቱም አማቴ ይባላል፡፡ በዚያን ጊዜ ኢዮርብዓም ሶርያውያንን አባሮ የእስራኤልን ድንበር እንዲመልስ ነቢዩ ዮናስ ትንቢትን ተናገረ (፪ኛነገ.፲፬፥፳፭፤ ዮናስ ፩፥፩)፡፡
✔ነቢዩ ኤልያስ ያስነሣው የሰራጵታዋ መበለት ሕፃን ነቢዩ ዮናስ እንደ ሆነ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያስረዳል (፩ኛነገ.፲፯፥፲፱)፡፡ መድኃኒታችን ክርስቶስም የዮናስን ከዓሣ ሆድ መውጣት የራሱ ትንሣኤ ምሳሌ አድርጎ ነግሮናል (ማቴ.፲፪፥፲፱-፵፪፤ ሉቃ.፲፩፥፴-፴፪)፡፡
❖ እግዚአብሔር አምላክም ‹‹ሔደህ በነነዌ ላይ ስበክ›› ባለው ጊዜ ነቢዩ ዮናስ ‹‹አንተ መሐሪ ነህ፤ ልትጠፉ ነው ብዬ ተናግሬ ብትምራቸው ሐሰተኛ ነቢይ እባላለሁ›› ብሎ ላለመታዘዝ እስራኤልን ለቆ በመርከብ ወደ ተርሴስ ሸሸ።
❖ እግዚአብሔርም ታላቅ ነፋስን አስነሥቶ መርከቧ በማዕበል እንድትመታ አደረገ፡፡ ከዮናስ ጋር በመርከቧ ተሳፍረው የነበሩ ነጋድያንም ያላቸውን ሀብት ወደ ባሕሩ መጣል ሲጀምሩ ነቢዩ ዮናስ ጥፋቱን ተገንዝቦ ‹‹ማዕበሉ በእኔ ምክንያት የመጣ ስለሆነ ንብረታችሁን ሳይሆን እኔን ወደ ባሕር ጣሉኝ›› ብሎ ተማጸናቸው፡፡
❖ እነርሱም ‹‹ስለዚህ ሰው ነፍስ እንዳንጠፋ፣ ንጹሕም ደም በእኛ ላይ እንዳይደረግብን አይሆንም›› አሉ፡፡ ወደ ባሕሩ ለመጣል ዕጣ በተጣጣሉ ጊዜም ዕጣው በዮናስ ላይ ስለ ወጣ ነጋድያኑ ዮናስን ወደ ባሕሩ ጣሉት፡፡ ወዲያውኑ ከእግዚአብሔር ዘንድ የታዘዘ ታላቅ ዓሣ አንበሪ ዮናስን በአፉ ተቀብሎ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት አሳድሮ ወደ ነነዌ አደረሰው፡፡ እግዚአብሔር የቅል ተክልን ምሳሌ በማድረግ ቅጠሉ በመድረቁ ዮናስ ባዘነ ጊዜ ‹‹አንተ ላልደከምክበት እና በአንድ ቀን በቅሎ ላደገ ቅል ስታዝን እነሆ በታላቂቱ ነነዌ ከተማ ያሉ ከአንድ መቶ ሃያ ሺሕ በላይ ሕዝብና እንስሳቱ የእጄ ፍጥረቶች ስለ ሆኑ ያሳዝኑኛል›› በማለት ነቢዩ ዮናስም ውሸታም ላለመባል መኮብለሉ ስሕተት መሆኑን አስረድቶታል፡፡
✔ዮናስም ነነዌ መሬት ላይ መድረሱን ባወቀ ጊዜ ከእግዚአብሔር መሸሽ አለመቻሉን ተረዳ፤ የነነዌ ሰዎችንም ‹‹ንስሐ ግቡ›› እያለ መስበክ ጀመረ። የነነዌ ሰዎችም ንስሐ በገቡ ጊዜ እግዚአብሔር ይቅር ብሎ ከጥፋት አድኗቸዋል፡፡ ሐሰት እንዳይባልም እሳቱ እንደ ደመና ሆኖ ከላይ ታይቶአል፡፡ የታላላቁ ዛፍ ቅጠል እስኪጠወልግ ድረስ አድርቆ ለሕዝቡ አሳይቷቸዋል፡፡ ንስሐቸው በከንቱ እንዳልቀረ አስረድቷቸዋል (ትንቢተ ዮናስ)፡፡ ታኅሣሥ ፭ ቀን የሚነበበው የመጽሐፈ ስንክሳር ክፍል ‹‹ወበልዐ አሐደ ኀምለ›› በማለት ንስሐ ያልገቡ አንድ አገር ያህል ሰዎች በእሳቱ እንደ ጠፉ ይነግረናል፡፡
✔ጾመ ነነዌ የሦስት ቀን ሱባኤ ነው፤ በሦስት ቀናት ጾምና ጸሎት ንስሐ የገቡ የነነዌ ሰዎች ከጥፋት እንደ ዳኑ ሁሉ፣ በብሉይ ኪዳን አስቴር ሦስት ቀን ጾማ፣ ጸልያ በእስራኤል ላይ የመጣውን መቅሠፍት እንዲመለስ አድርጋለች (አስ.፬፥፲፭-፲፮)፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ከበዓል ስትመለስ ሕፃኑ ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ መንገድ ላይ ጠፍቶአት ከሦስት ቀን ፍለጋ በኋላ በቤተ መቅደስ አግኝታዋለች (ሉቃ.፪፥፵፮)።
❖ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ለሄሮድስ በሰጠው ምላሽ መልስ ሦስት ቀን የሱባኤ ፍጻሜ መሆኑን ገልጿል (ሉቃ.፲፫፥፴፪)፡፡
✔ጾመ ነነዌ የእግዚአብሔርን ቸርነትና መሐሪነት የምናስታውስበት ጾም ነው፡፡ ይኸውም እኛ ፍጡራኑ በበደልን ጊዜ ፈጽሞ ከማጥፋት ይልቅ ምክንያት ፈልጎ እንድንድን ያደርገናል፡፡ ዮናስ ለስብከት ፈቃደኛ ባይሆን እንኳን እግዚአብሔር በተለየ ጥበቡ እንዲሔድ አድርጎታል፡፡ በእርግጥ እግዚአብሔር ሌላ የሚልከው ነቢይ አጥቶም አይደለም፤ እርሱንም ጭምር ሊያስተምረው ስለ ፈለገ እንጂ፡፡ የነነዌ ሰዎች የተነሳሕያን ምሳሌ ናቸው፡፡ ይህም ማለት ሰው ጥፋቱን አምኖ ንስሐ ከገባ እግዚአብሔር ይቅር ማለቱን አይተውም፡፡ ለዚህም ነው ዮናስን ‹‹አንተ ላልደከምክበት እና በአንድ ቀን በቅሎ ላደገ ቅል ስታዝን እነሆ በታላቂቱ ነነዌ ከተማ ያሉ ከአንድ መቶ ሃያ ሺሕ በላይ ሕዝብና እንስሳቱ የእጄ ፍጥረቶች ስለ ሆኑ ያሳዝኑኛል›› ያለው፡፡ ቀደምት የቤተ ክርስቲያን አባቶቻችን ይህን እና ሌሎች አጽዋማትን እንድንጾም የወሰኑልን ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ ሕጉ የተዘጋጀልን እንደ ነነዌ ሰዎች እኛም ጾመን፣ ጸልየን ከኃጢአታችን እንነጻ ዘንድ ነው፡፡ ዛሬ ዓለማችን በኃጢአት ማዕበል እየተናወጠች ባለችበት ወቅት እኛም እንደ ነነዌ ሰዎች ከበደላችን ብንመለስ እና ንስሐ ብንገባ ቸሩ ፈጣሪያችን እግዚአብሔር ይቅርታና ምሕረት የባሕርይ ገንዘቡ ስለ ሆነ ‹‹ወደ እኔ ተመለሱ፤ እኔም ይቅር እላችኋለሁ፤›› ይለናል፡፡ ስለሆነም በነቢዩ ዮናስ ላይ የተደረጉ ተአምራትንና ካለመታዘዝ የሚመጣ ቅጣት ቀላል አለመሆኑን በማስተዋል፣ ለነነዌ ሰዎች የወረደውን ምሕረት በመገንዘብ ለእግዚአብሔርም ሆነ ለሃይማኖት አባቶች እና ለወላጆቻችን መታዘዝ ይገባናል፡፡
✔ስንጾምም እግዚአብሔር አምላካችን መዓቱን በምሕረት፣ ቍጣውን በትዕግሥት መልሶ በኃጢአት ለጠፋው ዓለም ይቅርታውን ይልካል፡፡ በመጾማችን ራሳችን ከመዓትና ከመቅሠፍት ከመዳናችን ባሻገር በእኛ በደል ምክንያት አገራችን፣ ዕፀዋቱና እንስሳቱም ሳይቀር ከድርቅና ከቸነፈር ይተርፋሉና፡፡
✍በርዕሰ ደብር ብርሃኑ አካል
🌾✞ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ✞🌾
4 374
"ፓትርያርክ መሆን አይገባኝም ስላሉ ብቻ መንበራቸውን ጥለው እንዳይሄዱ በወታደር ይጠበቁ የነበረት ከወላይታ የተገኙት ወላይተኛ ተናጋሪው ቅዱስ ፓትርያሪክ"
➥የቀደመው ስማቸው አባ መልአኩ ይባላሉ። ምንም እንኳን ውልደታቸው በጎንደር ጋዢን በምትባል ስፍራ ቢሆንም ረጅም ዕድሜያቸውን ያሳለፉት እና አብረው የኖሩት ማህበራዊ ስነልቦናቸው ያገኙት ወላይታ በሚባል ደቡባዊ ምድር ላይ ነው።
➥ከሀገሬው በላይ ወላይተኛ አቀላጥፈው ይናገራሉ። ከውልደት ስፍራቸው በቀር አኗኗር እና አዋዋላቸው ሙሉ በሙሉ ከአንድ የወላይታ ገበሬ የተለየ አልነበረም።
➥የመጽሐፍት ትርጓሜ በእዚሁ በወላይታ ምድር ባሉ ጉባኤ ቤቶች አጠኑ። ስርዓተ ገዳም ከተማሩ በኃላ በእዚያው ወላይታ በሚገኘው ደብረ መንክራት አቡነ ተክለሃይማኖት ገዳም መኖከሱ። የብህትህና ህይወታቸው በወላይታ ምድር ጀመሩ።
➥ከ1926-1968 ለ42 ዓመታት ወላይታ ላይ በወላይተኛ ቋንቋ ሐዋርያዊ አገልግሎት ፈጽመው ከ300,000 በላይ ኢ- አማንያንን እንዳስጠመቁ እና ከ65 በላይ አብያተክርስቲያናትን አሳንጸዋል። በእዛ ዘመን አስበኅዋል ወዳጄ?
➥የደርግ መምጣትን ተከትሎ የኢ/ኦ/ተ/ቤተክርስቲያን 2ኛው ቅዱስ ፓትርያሪክ የነበሩት ብጽኡ አቡነ ቴዎፍሎስን ተገደሉ። በመሆኑም ቅድስት ቤተክርስቲያን 3ኛው ቅዱስ ፓትርያሪክ ለመምረጥ 909 አከባቢያቸውን የሚወክሉ አባቶች በአዋጅ ሰበሰበች።
➥ከ565 ወረዳዎች ለማዕረገ ፕትርክና መንፈስ ቅዱስ የሚመርጠውን አባት ይገኝ ዘንድ ሁለት ሁለት ተወካይ ይላክ ዘንድ ታዘዘ። ገና ማዕረግ ጵጵስናን ያልተቀበሉት በቁምስና ያሉት መኖክሴው የወላይታው አባት የሆኑት አባ መላእኩ ከወላይታ "ተወካይ ሆኜ አልሄድም" ብሎ እንቢ ማለትን ከጅምሩ ቢያሳውቁም በገዳሙ አባቶች ትዕዛዝ እና ቃለ ውግዘት የወላይታ አውራጃን ወክለው ተላኩ። ገና ማዕረግ ጵጵስና ሳይቀበሉ በቁምስና ማዕረግ መሆናቸው ደግሞ ለዬት ያደርገዋል።
➥በስተመጨረሻም የመጨረሻው 5 ዕጩ ውስጥ ስማቸው ተካተተ። ከአንድ ቆሞስ እና ከሶስት ሊቃነ ጳጳሳት ጋር ለ3ተኛው የፕትርክና የአገልግሎት ሥልጣን ለውድድር ተቀመጡ። ከየወረዳው ለመጡት ለመራጩ ተወካዮችም ግን እንቢታቸውን እና ከውድድሩ እንዲያስወጧቸው እንዲህ ብለው ተናገሩ
➥<< "እኔ ባህታዊ ነኝ ..ጥዬው የመጣሁት ህዝብ አለኝ ፣ ኑሮዬ በጫካ ነው እና የከተማውን ህይወት ለምጄ መምራት አይቻለኝም ።የበቁ አባቶች አሉ እና እኔን በእዚህ ምርጫ ውስጥ አወዳድራችሁ መንፈስ ቅዱስን አታሳዝኑ፣ እኔን ከምርጫው ሰርዙኝ " >> ብለው ለጉባኤው በተደጋጋሚ እየጮኹ ቢነግሩም ሰሚ አጡ።
➥በስተመጨረሻም ከሊቃነ ጳጳሳት ጋር ተወዳድረው በአብላጫ ድምጽ መኖክሴው መናኝ የኢ/ኦ/ተ/ቤተክርስቲያን 3ኛው ቅዱስ ፓትርያሪክ ሆነው ተመረጡ። በ1968 ሐምሌ ወር ላይ መዓረገ ጽጽስና ተቀብለው ከወር በኃላ በጉባኤው ምርጫ መሰረት
"አባ ተክለሃይማኖት ሣልሳዊ የኢትዮጽያ ፓትርያሪክ" ተብለው ተሾሙ።
➥ከተሾሙ በኃላም በብህትህና ወደ ወላይታ ተመልሰው በገዳማቸው በዓት ለመዝጋት መንበራቸው ጥለው ሊሸሹ በተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርጉም የደርግ ወታደሮች እየያዟቸው መለሱ።
➥በስተመጨረሻም መንበራቸውን ጥለው እንዳይሄዱ በመኖርያ ቤታቸው ጥበቃ ተመደበ። መውጫ መግቢያቸው ከደርግ ወታደሮች እውቅና ውጪ እንዳይሆን ተደረገ።
➥ወዳጄ...መንፈስ ቅዱስ ሲመርጥ እንዲህ ነው። ዳዊትን ከእረኝነት ንጉስ ያደረገ አምላክ፣ ሳሙኤልን ከመካኒቷ ማህጸን አውጥቶ ነብይ ብሎ የሾመ ጌታ፣ ሙሴን ከውሐ ላይ ታድጎ ነጻ አውጭ አድርጎ የቀባ እግዚአብሔር ምርጫው ኮታ ሳይሆን ጸጋ ነው።
➥እኚኽ አባት ለጸጋ ፕትርክና የሚገቡ አባት መሆናቸውን ባገለገሉበት 12 የፕትርክና አገልግሎት ዓመታት ገለጡ።
➥ጫማን ለመንግስት ፕሮግራሞች ብቻ ይጫሙ እንደነበር ይነገራቸዋል።ከፆም ጸሎት በቀር ቅርባቸው የሚሆን ሰው አልነበረም።
ደምወዛቸውን ለነድያን እና ለወላይታ ደብረ መንክራት አቡነ ተክለሃይማኖት መኖኮሳት ቀለብ በቋሚነት ይልኩ ነበር።
➥ለቁመተ ሥጋ ብቻ ተመጋቢ የሆኑ ይህኝ አባት በስተመጨረሻ በሥጋ ድካም ሲያርፉ የከበረች ሥጋቸው 25 ኪግ ብቻ እንደነበር ይታወቃል።
ይህኝን አባት ዛሬም ድረስ የወላይታ ኦርቶዶክሳውያን ያለስስት በዓለ ረፍታቸውን አስበው በገዳማቸው ይዘክራሉ። የቅዱስነታቸው የከበረች በረከታቸው ትደርብን አሜን!!!
4 374
✞~ #ኢየሱስ_እናቱን_ተቆጥቷት_ይሆንን? ~✞
✅✞የቃና ሰርግ ቤት ታሪክ ለጊዜው እናቆየውና አንድ ልጅ በአደባባይ በሰዎች ፊት እናቱን በምንም ምክንያት ቢቆጣ እንኳን ከሃይማኖት አንጻር ከሥነ ምግባርም አንጻር የሚደገፍ ሥራ አይደለም፡፡ ክብር ይግባውና ጌታችን ‹እናቱን በቁጣ ተናገራት› የሚለው አስተሳሰብም እንዲሁ ብዙ የሚያመጣው ጣጣ አለ፡፡ ‹‹እናትና አባትህን አክብር››፣ ‹‹እናቱን የሰደበ ይሙት›› የሚለውን ሕግ የሠራ አምላክ ‹እኔን ምሰሉ› እያለ ለሰው ልጆች አርኣያ ሊሆን በመጣበት በዚህ ዓለም ራሱ እናቱን በአደባባይ በሰው ፊት ያቃልላታል ብሎ ማሰብ እጅግ ከባድና ለብዙ ሰዎች የኃጢአትን በር ወለል አድርጎ ከፍቶ መረን የሚለቅ ነው፡፡ (ዘጸ. ፳፥፲፪ ፣፳፩፥ )
✅✞ እመቤታችንን የጎዱ መስሏቸው ‹ጌታ እናቱን ተቆጣ› ብለው የሚሰብኩ ሰዎችም ሳያውቁት እየተናገሩ ያሉት በእመቤታችን ላይ ሳይሆን በራሱ በጌታችን ላይ ነው፡፡ ጌታችን ‹‹ከእናንተ ስለ ኃጢአት የሚወቅሰኝ ማን ነው?›› ብሎ የተናገረ ንጹሐ ባሕርይ ነው፡፡ (ዮሐ. ፰፥፵፮) ‹የሚጤስን የጧፍ ክር የማያጠፋ ፣የተቀጠቀጠ ሸንበቆን የማይሰብር› በአነጋገሩ ጭምት ነው፡፡ ስንክሳሩም ‹‹ወንድሜ ምእመን ሆይ ጌታችን ለንጽሕት እናቱ ለድንግል ማርያም ከአንቺ ጋር ምን አለኝ ጊዜዬ ገና አልደረሰም በማለቱ የክብርት እናቱን ቃል እንዳቃለለ አታስብ›› ይላል፡፡ (ስንክ. ጥር ፲፪ ቁ. ፵)
✅✞ በማስከተልም ‹‹ጌታችን የሰማያዊውና የመለኮታዊ አባቱን ክብር እንደጠበቀ ይታወቅ ዘንድ እንዲሁ ከእርስዋ ፍጹም ሥጋንና ፍጽምት ነፍስን ነሥቶ ከመለኮቱ ጋር ያዋሐደውን የእናቱን ክብር ጠበቀ፡፡ በወንጌል ይታዘዛትና ይላላካት ነበር ተብሎ እንደተጻፈ›› ይላል፡፡ (ስንክ.ጥር ፲፪ ቁ. ፵፪)
✅✞ በእርግጥም ጌታችን የባሕርይ አባቱን አብን ክብር እንደጠበቀ በራሱ አንደበት ‹‹አባቴን አከብራለሁ›› ሲል ተናግሯል፡፡ (ዮሐ. ፰፥፵፱) ለእመቤታችንና
ለአሳዳጊው ዮሴፍም እንዲሁ ‹‹ከእነርሱም ጋር ወርዶ ወደ ናዝሬት መጣ፥ ይታዘዝላቸውም ነበር። እናቱም ይህን ነገር ሁሉ በልብዋ ትጠብቀው ነበር።›› ተብሎ ተጽፎአል፡፡ (ሉቃ. ፪፥፶፩) እመቤታችን በቃና ዘገሊላ ስለ ወይኑ
የነገረችውም የልጅዋን መታዘዝ በልብዋ ትጠብቀው ስለነበር እና እንደሚታዘዛት
ታስብ ስለነበር ነው፡፡
✅✞ እስቲ ነገሩን ሌሎች ከሚያዩበት ማዕዘን ለመመልከት እንሞክር፡፡ እውነት ግን ጌታችን እናቱን ሊቆጣ የሚችልበት ምን ምክንያት ነበረው? ከላይ እንደተመለከትነው የለመነችው ስለ ራስዋ ጥቅም አይደለም፡፡ በዚያ ላይ ልመናዋ ከሚያስፈልግ ነገር ውጪ ይደረግ የተባለ አላስፈላጊ የቅንጦት ልመና አይደለም፡፡ በሰርግ ቤት ሙሽሮችን ለዕድሜ ልክ ውርደት ሊዳርግ የሚችል የወይን ጠጅ እጥረት በተከሰተበት ሰዓት ‹ወይን እኮ የላቸውም› ብሎ ማመልከት እንኳን በሩኅሩኁ አምላክ ፊት ይቅርና በእኛ በጨካኞቹ የሰው ልጆች ፊት እንኳን
ሊያስቆጣ የሚችል ነገር አይደለም፡፡
✅✞ የለመነችው እንደ አይሁድ ምልክት ለማየት ጓጉታ አይደለም፡፡ እንደ ፈሪሳዊያንና ሰዱቃውያን ‹አይተን እንድናምንህ ምን ምልክት ትሠራለህ?› ‹ከሰማይ ምልክት ልናይ እንወዳለን› የሚል የፈተና ጥያቄ አልጠየቀችም፡፡ (ማቴ. ፲፮፥፩ ፤ዮሐ. ፮፥፳) ተአምር የማየት ምኞት አድሮበት እንደጠየቀው እንደ ሄሮድስም በአጋጣሚው ልጠቀምና ተአምር ልይ ብላም አይደለም፡፡ (ሉቃ. ፳፫፥፰) ደግሞስ ያለ ወንድ ዘር በማኅጸንዋ አድሮ በታተመ ድንግልና ሲወለድ ያየች እናት ሌላ ምን ተአምር
ሊያስደንቃት ይችላል?
✅✞ የሰርጋቸው ቀን የኀዘናቸው ቀን ሊሆን ስለተቃረበ ሙሽሮች ተጨንቃ መለመንዋ እንዴት የሚያስቆጣ ሊሆን ይችላል? ያለጊዜው ስለለመነችውና ስለቸኮለች ተቆጣት እንዳንል ልመናዋን ትንሽ ብታዘገየው ኖሮ ነገሩ ይፋ እየሆነ ፣ ሙሽሮቹ መዋረዳቸው ነው፡፡ ስለዚህ የደረሰችው በሰዓቱ ነው፡፡
✅✞ የጌታችን አሠራር እንዲህ አልነበረም፡፡ የቅዱስ ጴጥሮስ አማት በንዳድ በታመመች ጊዜ እንዲፈውሳት ሲለምኑት እሺ ብሎ ንዳዱን ገሥፆ አላቀቃት፡፡ (ሉቃ.፬፥፴፱) የአንድ መቶ አለቃ ልጅ በታመመ ጊዜ የአይሁድ ሽማግሌዎች ሊያማልዱ በመቶ አለቃው ተልከው መጡ፡፡ ጌታችን ከይሁዳ ነገድ መሆኑን በማሰብም ‹‹ይህን ልታደርግለት ይገባዋል፤ ሕዝባችንን ይወዳልና ምኵራብም ራሱ ሠርቶልናል ብለው አጽንተው ለመኑት። ኢየሱስም ከእነርሱ ጋር ሄደ።›› የመቶ አለቃውንም ልጅ በመጨረሻ ፈወሰው፡፡ (ሉቃ. ፯፥፪-፮) እነዚህ ሰዎች ተአምር እንዲያደርግ ሲጠይቁት እሺ ያለ ጌታ እናቱ ስትለምነው ይቆጣል ብለን እንዴት እንቀበል? የአይሁድን ሽማግሌዎች እንኳን ያልተቆጣውን ጌታ በምን
አንደበታችን እናቱን ተቆጣ ልንለው ይቻለናል?
✅✞ ከሁሉ በላይ ቅዱስ ዳዊት ‹‹ጸሎቴን ያልከለከለኝ ምሕረቱንም ከእኔ ያላራቀ እግዚአብሔር ይመስገን›› እንዳለው በረከሰ አንደበታችን ፣ በሚወላውል ልባችን፣ በሚባክን ሃሳባችን ወደ እርሱ የምንጸልየውን የእኛን የኃጢአተኞቹን ጸሎት ለምን ጸለያችሁ ብሎ ያልከለከለ አምላክ ንጽሕት እናቱ በፍጹም ትሕትና ለለመነችው ልመና የቁጣ ምላሽ ሠጠ ማለት እንዴት እንደፍራለን? ዳዊት ‹‹በልቤስ በደልን አይቼ ብሆን ጌታ አይሰማኝም ነበር። ስለዚህ እግዚአብሔር ሰማኝ የልመናዬን ድምፅ አደመጠ›› ብሏል፡፡ እርሱ በልቡ በደል ስለሌለ ጌታ ከሰማው በሃሳብዋ ድንግል የሆነች እናቱን እንዴት አልሰማትም እንላለን? (መዝ.
፷፮፥፲፱-፳)
✅✞ እመቤታችን የጠየቀችው ይህን ያህል የማይጠየቅ ነገር ነው እንዴ?
የመንግሥትህን እኩሌታ ፣ የሥልጣንህን ፈንታ ሥጠኝ አላለችውም፡፡ የጠየቀችው ስለ ድሆቹ ሙሽሮች ነው፡፡ እኛ በረባ ባልረባው ስንዘበዝበው የምንውለውና የምናድረው ታጋሽ አምላክ ለእናቱ ለእኛ የሠጠውን ነገር ይነሣል ማለት ፈጽሞ አይታሰብም፡፡ ‹አብን አሳየንና ይበቃናል› ፤ ‹እሳት ከሰማይ ወርዶ ሕዝቡን ያጥፋቸው› ፤ ‹በግራ ቀኝህ አስቀምጠን› የሚሉ ደቀ መዛሙርትን ታግሶ ለሦስት ዓመት ከሦስት ወራት ያስከተለ ጌታ ቅድስት እናቱ ተገቢ ልመና በተገቢ ሰዓት ስትለምነው ሊቆጣ አይችልም፡፡
✅✞ እንደ ወንጌሉ ብቻ ከሔድን ደግሞ እመቤታችን ከዚህ በፊትና በኋላ ምንም ነገር ስትለምነው አልተጻፈም፡፡ በወንጌል ለተጻፈው ለዚህ ብቸኛ ልመናዋም መልሱ
ቁጣ ነው ብለን አምነን መቀመጥ ለእኛ ለኦርቶዶክሳውያን ፈጽሞ የሚዋጥልን
ሃሳብ አይደለም፡፡ በልጅነትዋ ወልዳው ለተሰደደችው ፣ በነፍስዋ የኀዘን ሰይፍ
ላለፈባት እናቱ አንዴ ብትለምነው ተቆጣ ብለን እንዴት እንናገራለን?
✅✞ ጌታችን በዚህ ሰርግ ቤት እንኳንስ እንዲህ መጽሐፍ ቅዱስ ራሱ የሚተረጉመው ‹ከአንቺ ጋር ምን ጠብ አለኝ› የሚል የአክብሮት ንግግር ተናግሮ ቀርቶ ፤ ለእናቱ የተናገረው በቀጥታና በግልፅ የቁጣ ንግግር ቢሆን ኖሮ እንኳን ጾመን ጸልየን ፣ ወድቀን ተነሥተን ምሥጢራዊ ትርጉሙን እንፈልጋለን እንጂ ሰማይና ምድር ቢነዋወጥ ‹ጌታ እናቱን ተቆጣ› ብለን አናምንም!!!
🌾ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ~ቃና ዘገሊላ ገጽ 81
4 374
🌾✞ #ጥምቀት ✞🌾
በአብ ስም በወልድ ስም በመንፈስ ቅዱስ ስም አንድ አምላክ አሜን፡፡
✔ጥር ፲፩ በዚች ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከአጥማቂው ዮሐንስ ዘንድ በዮርዳኖስ ወንዝ ውኃ ተጠመቀ፡፡
✔ይችም ዕለት በዮናኒ ቋንቋ ኤጲፋንያ ትባላለች። ትርጓሜው መለኮት የተገለጠበት ማለት ነው።
✔ልዩ የሆነች የሦስትነቱን ምሥጢር ገልጦባታልና አብ ከሰማይ ሁኖ የምወደው በርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት እያለ ሲመሰክር ወልድም በዮርዳኖስ ወንዝ ቁሞ ሳለ መንፈስ ቅዱስም በነጭ ርግብ አምሳል በወልድ ራስ ላይ ሲቀመጥ ታየ፡፡
✔ይህን አጥማቂው ዮሐንስ እንዲህ ሲል መሰከረ፡፡ "ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተጠምቆ ከውኃ በወጣ ጊዜ ወዲያውኑ ሰማይ ተከፈተ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ወርዶ በጌታችን ራስ ላይ ተቀመጠ ከሰማይ እንዲህ የሚል ቃል መጣ ይህ የምወደው በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ነው እርሱንም ስሙት፡፡" የሚል።
✔በዚች ዕለት ጌታችን ራሱን ገልጦአልና ከዚህ በፊት ሠላሳ ዓመት ያህል ራሱን አልገለጠም ነበር፡፡
✔በዚች ዕለት ለእስራኤል ልጆች ራሱን ገለጠ፡፡ እንሆ የእግዚአብሔር በግ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ ብሎ መጥምቁ ዮሐንስ እንደገለጠው የከበረ ወንጌል ምስክር ሆነ፡፡
✔እኔ አላውቅም ነበር ነገር ግን እስራኤል ያውቁት ዘንድ በውኃ ላጠምቅ ስለዚህ መጣሁ አለ፡፡
✔በዚህም በዓል የእግዚአብሔር ልጅ የክርስቶስ የጌትነቱ ክብር ተገልጧል እርሱም የዓለሙን ሁሉ ኃጢአት ለማስወገድ የሚሠዋ የእግዚአብሔር አማናዊ በግ ነው፡፡ ስለዚህም ይህ በዓል በክርስቲያን ወገኖች ሁሉ ዘንድ የከበረና ከፍ ከፍ ያለ ሆነ፡፡
✔በርሱም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ በአከበረው ውኃ ይነጹበታል፡፡
✔የተቀበሉትንም ንጽሕና ጠብቀው ቢኖሩ በውስጡ የኃጢአታቸውን ሥርየት ያገኛሉ፡፡
✔ስለዚህ ከክፉ ነገር ሁሉ ተጠብቀን የፈጣሪያችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የቸርነቱ ብዛት ልናመሰግን ይገባናል፡፡ እርሱ ስለ እኛ ሰው ሁኖ ከኃጢአታችን አድኖናልና።
☞ "እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ከውሃና ከመንፈስቅዱስ ያልተወለደ ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግስት ሊገባ አይችልም።" ዮሐ 3÷5
☞ "እንሆም፥ድምፅ፡ከሰማያት፡መጥቶ፦ በርሱ፡ደስ፡የሚለኝ፡የምወደ፟ው፡ልጄ፡ይህ፡ነው፡አለ።"ማቴ፡3፥17
እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላምና በጤና አደረሳቹ!!!🙏
4 374
☞♣❀✞ #ጥምቀት ✞❀♣☜
በአብ ስም በወልድ ስም በመንፈስ ቅዱስ ስም አንድ አምላክ አሜን፡፡
✔ጥር ፲፩ በዚች ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከአጥማቂው ዮሐንስ ዘንድ በዮርዳኖስ ወንዝ ውኃ ተጠመቀ፡፡
✔ይችም ዕለት በዮናኒ ቋንቋ ኤጲፋንያ ትባላለች። ትርጓሜው መለኮት የተገለጠበት ማለት ነው።
✔ልዩ የሆነች የሦስትነቱን ምሥጢር ገልጦባታልና አብ ከሰማይ ሁኖ የምወደው በርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት እያለ ሲመሰክር ወልድም በዮርዳኖስ ወንዝ ቁሞ ሳለ መንፈስ ቅዱስም በነጭ ርግብ አምሳል በወልድ ራስ ላይ ሲቀመጥ ታየ፡፡
✔ይህን አጥማቂው ዮሐንስ እንዲህ ሲል መሰከረ፡፡ "ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተጠምቆ ከውኃ በወጣ ጊዜ ወዲያውኑ ሰማይ ተከፈተ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ወርዶ በጌታችን ራስ ላይ ተቀመጠ ከሰማይ እንዲህ የሚል ቃል መጣ ይህ የምወደው በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ነው እርሱንም ስሙት፡፡" የሚል።
✔በዚች ዕለት ጌታችን ራሱን ገልጦአልና ከዚህ በፊት ሠላሳ ዓመት ያህል ራሱን አልገለጠም ነበር፡፡
✔በዚች ዕለት ለእስራኤል ልጆች ራሱን ገለጠ፡፡ እንሆ የእግዚአብሔር በግ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ ብሎ መጥምቁ ዮሐንስ እንደገለጠው የከበረ ወንጌል ምስክር ሆነ፡፡
✔እኔ አላውቅም ነበር ነገር ግን እስራኤል ያውቁት ዘንድ በውኃ ላጠምቅ ስለዚህ መጣሁ አለ፡፡
✔በዚህም በዓል የእግዚአብሔር ልጅ የክርስቶስ የጌትነቱ ክብር ተገልጧል እርሱም የዓለሙን ሁሉ ኃጢአት ለማስወገድ የሚሠዋ የእግዚአብሔር አማናዊ በግ ነው፡፡ ስለዚህም ይህ በዓል በክርስቲያን ወገኖች ሁሉ ዘንድ የከበረና ከፍ ከፍ ያለ ሆነ፡፡
✔በርሱም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ በአከበረው ውኃ ይነጹበታል፡፡
✔የተቀበሉትንም ንጽሕና ጠብቀው ቢኖሩ በውስጡ የኃጢአታቸውን ሥርየት ያገኛሉ፡፡
✔ስለዚህ ከክፉ ነገር ሁሉ ተጠብቀን የፈጣሪያችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የቸርነቱ ብዛት ልናመሰግን ይገባናል፡፡ እርሱ ስለ እኛ ሰው ሁኖ ከኃጢአታችን አድኖናልና።
☞ "እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ከውሃና ከመንፈስቅዱስ ያልተወለደ ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግስት ሊገባ አይችልም።" ዮሐ 3÷5
☞ "እንሆም፥ድምፅ፡ከሰማያት፡መጥቶ፦ በርሱ፡ደስ፡የሚለኝ፡የምወደ፟ው፡ልጄ፡ይህ፡ነው፡አለ።"ማቴ፡3፥17
እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላምና በጤና አደረሳቹ፡፡
4 374
🌾✞ #ከተራ_የጥምቀት_ዋዜማ ✞🌾
✔ #ከተራ ማለት "ከበበ" ከሚለው የግእዝ ግሥ የወጣ ሲሆን፡ ትርጕሙም ውሃን መከተር ወይም ውሃ መገደብ (መዝጋት፥ ማቆም፥ ማገድ፥ ማጠር፥ ዙሪያውን መያዝ፥ መክበብ፥ መከልከል) ማለት ነው፡፡
✔ #ከተራ_ለምን_ተባለ?
በጥምቀት በዓል ዋዜማ በጥር 10 ቀን ታቦተ ሕጉ ከቤተ መቅደስ ወጥቶ ውሃ ባለበት አካባቢ ስለሚያድር የየአጥቢያው ሕዝብ እየተሰበሰበ በወንዝ ዳር ወይም በምንጭ አካባቢ ወይም ጉድጓድ ተቆፍሮ፤ ድንኳን ይተክላል፥ ዳስ ሲጣል ይውላል (ምክንያቱም ጌታችን የተጠመቀበት ወርኀ ጥር በእስራኤላውያን ዘንድ የዝናምና የበረዶ ወራት ስለሆነ ቅዝቃዜውም በወንዞች አጠገብ ስለሚያይል በባሕረ ዮርዳኖስ፥ በዕደ ዮሐንስ ለመጠመቅ የሚሄዱ ሰዎች ድንኳን ተክለው፥ ዳስ ጥለው ያድሩ ስለነበረ ነው)፡፡ ነገር ግን በዚህ ወቅት የምንጮች ውሃ ደካማ በመሆኑ ውሃው እንዲጠራቀም ወንዶች ጉድጓድ እየቆፈሩ፥ ሴቶች ውኃ በእንስራ እየቀዱ ከወንዞችና ከምንጮች ውኃውን ይከትራሉ፥ ይገደባሉ (አሁን በከተሞች ሰው ሰራሽ ግድብ ይገደባል)፡፡ የምዕመናኑ አብዛኛው ስራ ውሃውን መከተርና መገደብ በመሆኑ ዕለቱ #ከተራ የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡
✔ አንድም በኢያሱ መሪነት እስራኤላውያን የዮርዳኖስን ባሕር ሲሻገሩ ታቦቱን ያከበሩ (የያዙ) ካህናት ሕዝቡ ተሻግሮ እስከሚያበቃ ከወንዙ መሃል ቆመው ነበር ውኃውም እንደ ባሕረ ኤርትራ ግራና ቀኝ ተከፍሎ እንደ ግድግዳ ቆሞ ነበርና ይህንንም ለማስታወስ ከተራ እየተባለ ይጠራል፡፡
✔ አንድም ጌታችን በዮርዳኖስ በተጠመቀ ጊዜ የላይኛው ሸሽቶ እንደ ክምር ተቆልሏል (ከአዳም ጀምሮ እስከ መድኅን መወለድ ድረስ በዘር ይወርድ የነበረው ፍዳ መርገም በክርስቶስ ተቋርጦ ለመቅረቱ፥ ከአበው ወደ ውሉድ ላለመተላለፉ ምሳሌ)፤ የታችኛውም ወደ ታች ሸሽቶ በመድረቁ (የአዳም ኀጢአት ከሥሩ እንደተነቀለ ዛፍ ሆና ለመውደቋ ምሳሌ) ከተራ እየተባለ ይጠራል፡፡
✔ውኃ የሚከተርበት ቦታ " #ባሕረ_ጥምቀት (ጥምቀተ ባሕር)" (የታቦት ማደሪያ) እየተባለ ይጠራል፡፡ ውኃው የሚከተረውም በማግስቱ ጥር 11 ቀን ለሚከበረው የጥምቀት በዓል መጠመቂያና የጥምቀትን በዓል ለማክበር እንዲሆን ነው፡፡ ሌሊት ማኅሌት ተቁሞ፥ ቅዳሴ ተቀድሶ፥ ጠዋት ጸሎት ተደርሶ የሚጠመቅ ሕፃን ካለ እዚያው ውስጥ ይጠመቃል፡፡ ጐበዛዝትም ለቡራኬ ይዋኙበታል ምዕመናንም እንዲሁ ለቡራኬ ይረጩታል፡፡ ያ ስፍራ በዘልማድ ጥምቀተ ባሕር ተብሎ ይጠራል፡፡
✔ #ሥርዐተ_ከተራ ታቦተ ሕግ ይዞ መጓዝና ወደ ወንዝ መውረድ የተጀመረው በአሮን ልጅ በአልዓዛር ጊዜ ነው፡፡ ነገር ግን ቀድሞ በሙሴ ኋላ በኢያሱ መሪነትም ታቦተ ሕጉን ይዘው የዮርዳኖስን ባሕር መሻገራቸውንም ልብ ይሏል፡፡ የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳን ታቦት ሌዋውያን ካህናት ተሸክመውት ባያችሁት ጊዜ ከስፍራችሁ ተነስታችሁ ተከተሉት፡፡ /ኢያ.3፥3/ እንዲል፡፡
✔ የከተራ ዕለት ድንኳኑ ተተክሎ፥ ዳሱ ተጥሎና ውሃው ተከትሮ ሁሉም ነገር ከተስተካከለ በኋላ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት አካባቢ የደወል ድምፅ እንደተሰማ ከልጅ እስከ አዋቂ በነቂስ ተወጥቶ በዐፀደ ቤተ ክርስቲያንና ታቦታቱ በሚያልፉባቸው መንገዶች ይሰበሰባሉ፤ የየአድባራቱና የገዳማቱ ታቦት በካህናት አማካይነት በወርቅና በብር በተንቈጠቆጠ መጐናጸፊያ እየተሸፈኑ በታቦት ጉዞ (በዝግታ) ወደ ጥምቀተ ባሕሩ ይጓዛሉ፡፡ በዚህም ጊዜ፤ ባለ መስቀል መፆር ሰንደቅ ዓለማና ዓርማ የያዘው ግን ከሁሉም ፊት ፊት እያለ ቀድሞ ይሄዳል፡፡ የወርቅ (ወርቀዘቦ) ካባና ላንቃ የለበሱና ጥላ የያዙት ቀሳውስትና መነኰሳት ከታቦቱ ጐን፤ መስቀልና ጽንሐሕ የያዙት ከታቦቱ በፊት ማዕጠንት እያጠኑ ይሄዳሉ፡፡ እንደ ቀሳውስቱ ተመሳሳይ ልብስ ተክህኖ የለበሱት ዲያቆናት ጥላ፣ ድባብ፣ መስቀልና ቃጭል ይዘው እያቃጨሉ ከቀሳውስቱ በፊት በመሆን ያጅቧቸዋል፡፡ ወደ ባሕረ ጥምቀቱም ሲወረድ ካባ ላንቃ፥ ጥንግ ድርብ በለበሱ፥ የብር፣ የነሐስ፣ የወርቅ መቋሚያና ጽናጽል በያዙ በማኅሌታውያን መዘምራን ደባትር ሃሌታ፣ በሰ/ት/ቤት ተማሪዎች ዝማሬና ሽብሸባ፣ በወጣት መዘምራን ደስታ፣ በወንዶች ሆታ፣ በሴቶች እልልታ ዲያቆናቱን ቀድመው እያጀቡ ይሄዳሉ፡፡ የደብር አለቆችና አበው ካህናት ታቦቱን ተከትለው ይጓዛሉ፡፡ ሕዝቡም "ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ" እንዲሉ እንደየ ችሎታው ያለውን ልብስ (ጃኖ፣ ለምድ፣ በርኖስና የመሳሰለውን) ለብሶና አጊጦ፥ ሽማግሌዎችና የጐበዝ አለቃዎችን በማስቀደም ታቦቱን በመከተል በስተኋላ ይሄዳሉ፡፡ ነገር ግን ሴቶችና ልጆች እንደፈለጋቸው ከፊትም ከኋላም ሆነው ይሄዳሉ፡፡
✔ ባሕረ ጥምቀትም እንደደረሱ ታቦቱ በድንኳን አጠገብ ቆሞ የዓመቱ #ተረኛ_ደብር (የምራት ባለተረኛ) “ወረደ ወልድ እምሰማያት ውስተ ምጥምቃት፤ በፍሥሓ ወበሰላም" (እግዚአብሔር ወልድ በሰላምና በደስታ በዮሐንስ እጅ ለመጠመቅ ከሰማያት ወደ መጠመቂያው ወረደ) የሚለው ሰላም ተመርቶ በአግባቡ ከተለዘበ በኋላ ጸሎት ተድርጐ ሲያልቅ ታቦቱ ወደ ድንኳኑ ይገባል፡፡ በክብረ በዓሉ ላይ ግሱን ለመቃኘትና ለማሸብሸብ፣ ማኅሌት ለመቆም፣ ቅዳሴ ለመቀደስና ሌላውንም ሥርዐት ለመፈጸም ኃላፊነት ያለባቸው ተረኛ ደብር (የምራት ባለተረኞች) ሲሆኑ ለቀጣዩ (ለከርሞ) ዓመት ተረኞች የሚሆኑና በአሁኑ ዓመት የምራት ባለተረኞችን የሚረዱት ገዳማትና አድባራት ደግሞ ‹‹አንሺዎች›› ይባላሉ፡፡
✔የከተራ ዕለት የየአጥቢያው ሕዝብ በየዓመቱ ተራ እየገባ ራት ከየአካባቢው ስለሚያመጣ ያ ሲበላና ሲጠጣ ከቆየ በኋላ ወዲያው የሌሊቱ ጸሎት(ስብሐተ ማኅሌቱ) በተረኛው ደብር ካህናት ተጀምሮ አገልግሎቱ መላ ሌሊቱን ሲካሄድ ያድራል (እንደ ቀጨኔ ባሉ ታላላቅና የሊቃውንት መፍለቂያ አድባራት ተረኛ ቢሆኑም /በጥምቀተ ባሕሩና በቤተ ክርስቲያናቸው ጭምር/ ባይሆኑም በቤተ ክርስቲያናቸው ማኅሌቱን ቆመውና ቅዳሴውን ቀድሰው ያድራሉ)፡፡ ቅዳሴው የሚቀደሰው ከሌሊቱ 7-9 ሰዓት ነው፡፡
✔ በከተራ ዕለት የሚከናወኑ ድርጊቶች ምሳሌነት አላቸው እነዚሁም፤
#ታቦቱ የጌታችን ምሳሌ
#ታቦቱን_አክብሮ_ይዞ_የሚሄደው_ካህን የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ምሳሌ
#ባሕረ_ጥምቀቱ የዮርዳኖስ ወንዝ ምሳሌ
#ታቦታቱን_አጅበው_የሚሄዱት_ምዕመናን ወደ ቅዱስ ዮሐንስ እየመጡ የንስሐ ጥምቀት ሲጠመቁ የነበሩ ሰዎች ምሳሌ
#ታቦታቱ_በከተራ_ዕለት_ከመንበራቸው_ወደ_ጥምቀተ_ባሕር_መውረዳቸው መድኀኔዓለም ክርስቶስ በእደ ዮሐንስ በፈለገ ዮርዳኖስ ለመጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ከማታው ጀምሮ መውረዱንና ተራውን ሲጠብቅ አድሮ መጠመቁን ያጠይቃል፡፡ ‹‹ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ ሊጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ፡፡››ማቴ፡ 3፥13
#ጥምቀቱ የሞቱ፤ አርአያ፤ የመቃብሩ አምሳል ነው፡፡
✔ በዓለ ጥምቀት ሰንበት (ቅዳሜና እሑድ ላይ) ካልዋለ የሚታረሰው መሬት ረድኤት በረከት ስለሚገኝበት ገበሬው አንድ ሁለት ፈር ያርሳል፡፡
✔ በዓለ ጥምቀት ዐቢይ በዓል ስለሆነ የጥሉላት (የፍስክ) ምግብም ጭምር ስለምንመገብበት ዘንድሮ ሰኞ ስለሚውል ዋይዜማውን እሑድን የጋድ ጾም (ከጥሉላት መባልዕት) እንጾማለን፡፡ የሚቈርብ ሰው ግን አክፍሎ ያድራል፡፡ ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 15
✞የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያንን አስተምሮና ስርዓት የጠበቁ የተለያዩ መርሃ ግብሮች በየቀኑ ወደናንተ ይቀርባሉ፡፡ለጓደኞቻችን #Share በመድረግ የበረከት ተካፋይ እናድርጋቸው✞
╭══•|❀:๑✞♡✞๑:❀|•══╮
@EOTC2921
╰══•|❀:๑✞♡✞๑:❀|•══╯
