en
Feedback
የዘር ሐሳቦች/ Yezer Hasaboch

የዘር ሐሳቦች/ Yezer Hasaboch

Open in Telegram

እያንዳንዱ ሐሳብ ዘር ነው

Show more
996
Subscribers
No data24 hours
+17 days
+130 days
Posts Archive
የእልልታና የምስጋና፣ የደስታ ድምፅ የሚሰማበት አዲስ ዓመት ይሁንላችሁ። ያዘኑ የሚስቁበት፣ የወደቁ የሚነሱበት፣ ብዙዎች ወደ መንግስቱ የሚፈልሱት አዲስ ዓመት፣ የተነገራችሁ ትንቢት የሚፈጸምበት፣ ምርኮአችሁ የሚመለስበት፣ አዲስ ዓመት፣ ለአገራችን፣ ለቤተክርስቲያናችን፣ ለቤተሰብና ለግል ህይወታችን አዲስ ምዕራፍ የሚገለጥበት አመት ይሁንልን።

ራስህን ማክበር ስትችል ሌሎች ያከብሩሃል፣ ጥበበኞችንም ስታከብራቸው ያከብሩሃል፣ ሞኞች ግን ይንቁሃል። ለሞኞች አትገኝ።

#ስኬት_ማለት_ራስህ_ላይ_መስራት_ማለት_ነው ስኬት ሰው ሁሉ ሊደርስበት የሚፈልግበት ነገር ነው። የሐብት ስኬት፣ የኑሮ ስኬት፣ የትዳር ስኬት፣ ራዕይ አካል የማስያዝ ስኬት ወዘተ። ስኬታችን የሚለካው እኛ ስኬቴ ነው ወይም ማህበረሰቡ ስኬታማ የሚለው ጥግ ላይ መድረስ ነው። ብዙ ሰው ስኬት ይፈልጋል ግን ስኬት ጋር አይደርስም። የተለያየ ጥግ ያላቸው ስኬቶች አሉ። የስኬት መንገድ በሰው ልጆች ውስጥ እንዲሰሩት የተሰጠ ማንነት ነው። ማለትም ስኬት የሚጀምረው ራስ ላይ በመስራት ነው። #ራስህ_ላይ_ስራ የመጀመሪያ የስኬት መንገድ የሚጀምረው ራስህ ላይ በመስራት ነው። (Invest on You Personality) ስኬት በመንገድ ላይ የሚለቀም ጠጠር አይደለም። ራስህ ላይ በመስራት የሚመጣ ነው። ልትደርስት ለምትፈልገው ስኬት ራስህ ላይ ስራ። ቢዝነስ ለመጀመር ከፈለክና በዚያ ስኬታማ ለመሆን ከፈለክ ትክክለኛ የቢዝነስ ሰው ለመሆን የሚያስችል ማንነት እንዲኖርህ ራስህ ላይ ስራ። አንብብ፣ ከቀደሙህ ሰዎች ልምድ ተካፈል፣ አስተሳሰብህን በትክክለኛ እውቀት ላይ ገንባው፣ ራስህ ላይ መስራት የስኬት ትልቁ መንገድ ነው። በአገልግሎት ስኬታማ ለመሆን ትፈልጋለህ? ራስህ ላይ ስራ። ራስህ ላይ ያልሰራህው ነገር ወደ ስኬት አያመጣህም። አገልጋዮች የቃሉ አገልጋዮች ሆነው ከቃሉ ጋር ህብረት ከሌላቸው ከጌታ ጋር በፀሎት የማሳለፍ ጊዜ ከሌላቸው፣ የሚያገለግሉትን ህዝብ የመውዱድና የማገልገል ማንነት ከሌላቸው እንዴት በአገልግሎት ስኬት ይኖራቸዋል? ራስህ ላይ ስራ (Invest on your Personality) ይህ ትልቁ ወደ ስኬት የመድረስ መንገድ ነው። ራስህ ላይ በመስራት ስኬታማ ካልሆንክ በአደባባይ ስኬታማ ልትሆን አትችልም። ብዙ ታላላቅ መሪዎች አንባቢዎች ናቸው። ማለትም ብዙ ጊዜ ወስደው ራሳቸው ላይ የሰሩ ናቸው።

#መጋቢዎች_ሊጠነቀቋቸው_የሚገቡ_ምዕመናን! ©ዘሪሁን ግርማ ዳግም ስንወለድ የእግዚአብሔር ልጅ ብንሆንም በነፍስ መሰራት ግን የጊዜ ውጤት ነው። ስለዚህ ቤተክርስቲያን የፍጻማን ስብስብ አይደለችም ስለዚህም በባህሪ በመረዳት በማንነት ተሰርተው ያለቁ እንከን-አልባ የሆኑ ሰዎች መገኛ አይደለችም ወደ ክርስቶስ ሙላት ራሳቸውን ለማሳደግ የተዘጋጁ ሰዎች መገኛ እንጂ። ስለዚህ ሁላችንም ወደ ቤቱ ስንመጣ የራሳችን የሆነ አለመብቃት ይዘን ወደ መብቃት እንሄዳለን። ወደ ሐሳቤ ስመለስ ጤናማው አለማደግ አለመብቃትና መሳሳት እንዳለ ሆኖ መጋቢዎች ሊጠነቀቋቸው የሚገባውን ምዕመናን ባህሪያት ከማንሳት በፊት ሶስት አይነት የምዕመናን አይነቶችን ላንሳ ፨ ሳያውቁ የሚያጠፉ ፨ ባለመቻል ስለማይችሉ የሚያጠፉ ፨ አመጸኞች እያወቁ በግዴለሽነት የሚያጠፉ የመጀመሪያዎች የሚያጠፉት ስለማያውቁ ሲሆን ወደ ማወቅ ሲመጡ የሚያርሙ ናቸው። ሁለተኛዎቹ ደግሞ ያውቃሉ ጸጋ በማጣት ወይም ከተጽዕኖዎቹ መላቀቅ ባለመቻል የሚያጠፉ ናቸው እነዚህ እየተማሩ እየጸለዩ ሲመጡ የሚለወጡ ናቸው። ሶስተኞቹ እያወቁ በአመጻ በድፍረት የሚያጠፉ ናቸው። እነዚህ መመለስና ንስሃ ነው የሚያስተካክላቸው። ዛሬ አትኩሮቴ ከመጋቢዎች በአንድም በሌላም የሚገናኙ ግን ደግሞ ለመንጋውና ለመጋቢው ጭምር ወጥመድ የሚሆኑ ምዕመናን ባህሪያትን እናያለን። #የተለየ_ክብር_የሚፈልጉ_ምዕመናን እነዚህ ከመጋቢው ጋር በተለያየ መንገድ ቀረቤታ ይኖራቸዋል ወይም ደግሞ አገልግሎቱን በገንዘብ በተለያየ ነገር የሚደግፉ ይሆናሉ። እነዚህ አይነት ሰዎች በሁሉ ነገር ራሳቸውን ማሳየት ይፈልጋሉ ከዚያም አልፈው ቤተክርስቲያኒቱን የገዙ የሚመስላቸው፤ የሚወጣውና የሚገባውን በእነርሱ ፈቃድ እንዲሆን የሚሹ ከታች ባሉት ምዕመናን ላይ አለቃ አለቃ የሚጫወቱ፤ ለአገልግሎት ሁሉ አቃቂር የሚያወጡ አይነት ናቸው። ለቤተክርስቲያን ጤናማ እድገት እነዚህ አይነት ሰዎችን ቦታ ቦታ ማስያዝ ያስፈልጋል። እነዚህ አይነት ሰዎች ለአገልግሎቱ በሚያደርጉት ነገር ከጌታ ከመቀበል ይልቅ የተለየ ቦታ እንዲሰጣቸው የሚፈልጉ አይነት ናቸው። እውነት ነው ቤተክርስቲያንን በተለያየ መንገድ የሚያግዙ ሰዎች ያስፈልጋሉ ማድረግ ያለባቸው የተሰጣቸውን ብቻ ማድረግ ነው። #በቤተክርስቲያን_ውስጥ_ያሉ_ወረኛዎችና_ሐሜተኞች ቤተክርስቲያን መጽዳት ያለባት ከወረኛዎች ከሐሜተኞች ጭምር ነው። ወረኛ ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ጸር ነው። አንዳንድ መሪዎች የራሳቸው ጆሮ ጠቢ እንዳላቸው እውን ነው። መጋቢ ራሱንና ምዕመናኑን ከወረኛዎች መጠበቅ አለበት። ወረኞች ሁሌም ሲጀምሩ አሳቢ እና ለመጋቢና ለቤተክርስቲያን ተቆርቋሪ በመምሰል ሲሆን፤ የማይወዱን ሰው ከመጋቢው ጋር በማጋጨት፤ የሚፈልጉትን ሰው የተለየ ቦታ እንዲሰጠው ለማድረግ የሚራወጡ ናቸው። መጋቢ አካባቢውንና ቤተክርስቲያንኑን ከወረኛዎችና ከሐሜተኞች መጠበቅ አለበት። ብዙ ጊዜ የወሬና የሐሜት ሱስ የያዛቸው ሰዎች በመጋቢያቸው ፊት ሞገስ ለማግኘት ወሬን መለቃቀምና መፍጠር ይችሉበታል። መጋቢ ከእነዚህ ራሱንና መንጋውን ይጠብቅ። #የራሳቸውን_ቲፎዞ_የሚያሰባስቡ እነዚህኛ በተለያየ መንገድ የሚያዳምጧቸውን ከስራቸው ያከማቹና በቤተክርስቲያን ላይ በአገልጋዮች ላይ በምዕመናን ላይ ጭምር አመጻን የሚስነሱ አይነት ናቸው። እነዚህኞቹ ምን እንደሚፈልጉ በግልጽ አይታወቅም ግን ደግሞ በሁሉ ነገር ላይ ቤተ ክርስቲያን የምትሰጠውን አመራር እና አሰራር ከመቀበል ይልቅ የሚፈልጉትን ሐሳብ በአመጻ ያንቀሳቅሳሉ። ለመገሰጽ አይመቹም ለመታረምም የሚዘጋጁ አይደሉም። መጋቢዎች በቤተክርስቲያን የራሳቸውን ህብረት የሚያደራጁትን ከቤተክርስቲያን አመራር ውጪ የሚራመዱትን አጥርተው ማወቅ እና መንጋን መጠበቅ አለባቸው። .............. https://t.me/theideaofs

ውሸት ይፈጥን ይሆናል እንጂ አሸንፎ አያውቅም!!

እግዚአብሔር "በቃ" እስካላለ የሚያበቃ ነገር የለም!!

አንድ ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ብዙ ነው፣ ብዙ ሰው ያለ እግዚአብሔር ምንም ነው!!

የክፉ ሰው መጨረሻው ውድቀት ነው፣ ክፉ ዘር መልካም አዝመራ የለውምና። https://t.me/theideaofs

#እግዚአብሔር_የሚልህ_ያ_ይበልጣል ዳዊትን ታላቅ ወንድሙ እንዲህ አለው። " ታላቅ ወንድሙም ኤልያብ ከሰዎች ጋር ሲነጋገር ሰማ፤ የኤልያብም ቍጣ በዳዊት ላይ ነድዶ። ለምን ወደዚህ ወረድህ? እነዚያንስ ጥቂቶች በጎች በምድረ በዳ ለማን ተውሃቸው? እኔ ኵራትህንና የልብህን ክፋት አውቃለሁና ሰልፉን ለማየት መጥተሃል አለው። " (1ኛ ሳሙ 17:28) ታላላቆ ከተናገሩን የተሳሳተ ነገር፣ ማንኛውንም ሰው ስለ አንተ ከሚናገረው የተሳሳተ ነገር እግዚአብሔር ስለ አንተ የሚለው ይበልጣል። ዳዊት በዘመኑ ምንም የተሳሳተባቸው ነገሮች ቢኖሩም ዳዊት የሆነው ሁሉ በእግዚአብሔር ብቻ ነው። እግዚአብሔር ደግሞ ስለ ዳዊት እንዲህ አለ፦ " እርሱንም ከሻረው በኋላ ዳዊትን በእነርሱ ላይ እንዲነግሥ አስነሣው፥ ሲመሰክርለትም። እንደ ልቤ የሆነ ሰው ፈቃዴንም ሁሉ የሚያደርግ የእሴይን ልጅ ዳዊትን አገኘሁ አለ።" (የሐዋርያት ሥራ 13:22) እግዚአብሔር የሚልህ ነገር ሰዎች በከንቱ ወይም በተሳሳተ ወይም በጥላቻ ከሚሉህና ካሉህ ነገር ይበልጣል። #ጉዳዩ_ሰዎች_ምን_ብለውሃል_ሳይሆን_እግዚአብሔር_ስለ_አንተ_ምን_ብሏል_የሚለው_ ነው።

#የነገሮች_መልስ_ያለው_በጊዜ_ውስጥ_ነው!! ጊዜ አቅም ነው። ጊዜ መልስ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ "ለሁሉም ጊዜ አለው።" ይለናል። ጊዜ የሌለው ነገር የለም። ጊዜን መጠበቅ ከተቻለ። ታላቅ ነን ያሉ ታናሽ፤ ታናሽ የሆኑ ታላቅ የሚሆኑት በጊዜ ነው። እውነት የምትፈተነውና ጠርታ የምትታየው በጊዜ ውስጥ ነው። ውሸት የምትጠፋው በጊዜ ነው። ጊዜ መልስ ነው። ነገሮችን ለምን እንደምታደርግ ተፈትኖ የሚታየው፤ ያመንከው እምነትና የያዝከው ራዕይ የሚታየው በጊዜ ነው። ሰው ውጤትህን እንጂ መንገድህን አይረዳምና። ጊዜ ውበት ነው። ጊዜ ፈራጅ ጊዜ ዳኛ ነው። ሰዎች መንገድህን በማይረዱበት ጊዜ ሁሉ እውነተኛ ሁን ጊዜ ውጤቱን ይሰጥሀል። ጊዜ ነገር ሁሉ ጥርት ብሎ የሚገለጥበት ብርሀን ነው። ጊዜ መልስ ነው። የጊዜ ሁሉ ባለቤት ደግሞ #እግዚአብሔር ነው። መልካም የትንሳኤ መታሰቢያ በዓል ይሁንላችሁ Zerihun G. Girma https://t.me/theideaofs

#ሰው_በአለባበሱ_ሳይሆን_በማንነቱ_ተቀበለው!! (ፌስ ቡክ መንገር ያገኘኃት አስደናቂ ታሪክ!) ገጠሬ ባልና ሚስት ናቸው ።ቦስተን ባቡር ጣብያ ወረዱ። ከዩኒቨርሲቲ ከተማዋ የተገኙት ከሃርቫርድ ዩንቨርስቲ ፕሬዚደንት ጋር ባላሰለሰ ጥረት ባስያዙት ቀጠሮ ላይ ለመገኘት ነበር። ከፀሐፊዋ ቢሮ እንደ ደረሱ ቀጠሮ ማስያዛቸውን ተናገሩ። ፀሐፊዋ ንትብ አልባሳቶቻቸውን ገጠሬ የአነጋገር ዘዬአቸውን አስተውላ ፕሬዝዳንቱ እነዚህን ሰዎች የሚያናግርበትመክንያት ሊኖረው እንደማይችል ገመተች! እንደሚጠበቀው የተጣበበ ግዜ ነው ያለው!የሃርቫርድ ያውም የካምብሪጅ ፕሬዚደንት! "ስራ ላይ ሰለሆኑ ይቆዩባችኋል" ተባሉ እነርሱም "እስኪጨርሱ እንጠብቃለን ግድየለም" አሉ። በድጋሚ "ይቆያሉ" ተባሉ " ይሁን እንጠብቃለን" አለች ሚስት በርካታ ሰአታትን ጠበቁ። ፀሐፊዋ ተስፋ ይቆርጣሉ ብላ ብትጠብቅም ሰዎቹ የመሄድ አዝማምያ ስላላሳዩ አያያዛቸውን አጢና ቀስ ብላ ወደ ፕሬዝዳንቱ ቢሮ በመግባት ማናገር ነበረባት። "ለጥቂት ደቂቃ ቢያናግሯቸው ሊሄዱ ይችላሉ" ፕሬዝደንቱ በተስፋ መቁረጥና በንዴት እየተነጫነጩ መጡና አገኟቸው። በዛ ላይ ሲታዩ ለአይን እንኳን የማይሞሉ መጤ ባላገሮች! ምን እግር ጥሏቸው ይሆን? አለ ለራሱ። "አቤት ምን ነበር?" አለ ፕሬዝደንቱ ሴትየዋ ቀደም ብላ ራሳቸውን ካስተዋወቀች በኅላ "አንድ ብቸኛ ልጃችን እዚህ ዩንቨርስቲ ውስጥ ይማር ነበር። ዩንቨርስቲውንም ይወደው ነበር።ምን ዋጋ አለው! ከአንድ አመት ቆይታ በኋላ ልጃችን አረፈ እና አሁን የመጣነው ለልጃችን ማስታወሻ የሚሆን ነገር ተመካክረን ...." ፕሬዝደንቱ አላስጨረሷትም "እመቤት ይህ ዩንቨርስቲ ነው! ለእያንዳንዱ ለሞተ ተማሪ ሁሉ ሃውልት እናቁም ብንል ቀብር ወይ ሙዝየም መሆኑ ነው" አላቸው። "እኛም እኮ ሃውልት አልነበረም ያልነው።" "እና" አላቸው። "በልጃችን ስም የሚሰየም ለማስተማር ወይ ለምርምር የሚረዳ አንድ ህንፃ ብናሰራ ነበር ፍላጎታችን።" አሉት ፕሬዝደንቱ ትዕግስታቸው እየተሟጠጠ ነው! አንድ ያልገባቸው ነገር እንዳለም ገመቱ አይ የገጠር ሰው! "ሰዎች ግዜዬን ከምታባክኑ በቀላል ቋንቋ ልንገራችሁ ይህ ኮምፓውንድ ብቻሰባት ህንፃዎች ይዟል(በወቅቱ) የሁሉንም ወቅታዊ እሴት በአሁኑ ግምት ወስዳችሁ ብታሰሉት 7.5 ሚልዮን ዶላር አካባቢ ይገመታል!ገባችሁ?አሁን ስራ አለብኝ።" ይህንን ሲል ባልና ሚስት እርስ በእርስ ለረጅም ግዜ እንደተፋጠጡ በአግርሞት ሲተያዩ ቆዩ!ሚስትየውም "እኛኮ ያሰብነው አንዲት ህንፃ ለማቆም ነበር!ለካ ሙሉ ዩንቨርስቲም ማቋቋም እንዲህ ቀላል ነው።" አሉት ባልና ሚስቱ ወደሚኖሩበት የካሊፎርኒያ ግዛት ተመልሰው ፖውሎአልቶ ባለው ሰፊ እርሻቸው ላይ በልጃቸውም በነሱም ስም ታላቁን የስታንፈርድ ዩንቨርስቲ መሰረቱ! ** ስታንፈርድ በርካታ ተማሪዎችን በየደረጃው በማስመረቅ ከ83 በላይ የኖቤል ሎሬቶች ጋር በመስራት፣በግኝትም፣ በትምህርት ጥራት ሁነኛ ጥናቶችን በማሳተምም ጭምር በአሜሪካ የታወቀ ምንአልባትም ቀዳሚው ዩንቨርሲቲ ነው። Book for All

#የግለ_ታሪክ (Biography) ነገር!! ግለ-ታሪክ ማንበብ እወዳለሁ። የቤተክርስቲያን ታሪክን፤ የአገልጋዮች ታሪክ፣ በአገር ደረጃ ታላቅ ስራን የሰሩ ሰዎች ታሪክ ማንበብ እንዲሁም የቀደሙ ሰዎች ታሪክን ለጻፉልን ሰዎችም ታላቅ አክብሮት አለኝ። ግለ ታሪክ - Biography እጅግ አስፈላጊ ከመሆኑም በላይ ከቀደመው ታሪክ እንድንማር እና የቀደመውን ታሪክ እንድንረዳ ይረዳናል። በአንድ ወቅት የመጋቢ ታምራት ሐይሌ "የተአምራት አምላክ ታምረኛ" የሚለው መጽሐፍ በወጣበት ወቅት ታሪኩን ሳነብ ሰው በእግዚአብሔር ከተያዘ የማይወጣው ማንኛውም ተራራ እንደሌለ አስተምሮኛል። እምነትን ጨምሮልኛል። ከነበርኩበት አስቸጋሪ ሁኔታ እንዴት እንዳወጣኝ አስታውሳለሁ። በቤተክርስቲያን ውስጥ ረጅም አመታት ያገለገሉ አገልጋዮች ታሪካቸውን መጻፍ አለባቸው ወይም ታሪካቸው መጻፍ አለበት። ብዙ ከህይወታቸው፣ ከመውደቅና ከመነሳታቸው ልንማር የሚገቡ ጉምቱ የቤተክርስቲያን አባቶች አሉን። የእነርሱ ታሪክ መጻፉ ለቀጣይ ትውልድ ከፍተኛ ሚና አለው። በዚህ አቅጣጫ እኔ የገባኝን ጥቂት ምልከታ ላካፍል። በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ውስጥም እንደ አገርም ሁሉ ጥርት ያለ ታሪክን ለትውልድ ከማስቀመጥ አስፈላጊ ሆኖ ሳለ በዚያ አቅጣጫ ግን ክፍተት ይታይብናል። የሚጻፉት ግለ ታሪኮች በብዛት 'ሙሉ እውነታን' የማያስጨብጡ፤ የጸሐፊውን ወይም የሚጻፍለትን ግለሰብ በታሪኩ ውስጥ ያለውን ሚና 'የሚያጋንኑ' ሲሆኑ ከዚያም በተጨማሪ በአንድ ታሪክ ላይ ሁለት የተለያዩ ጸሐፊያን አንድን የታሪክ ክስተት በሁለት የተለያየ መንገድ ማቅረብን ሳይሆን የታሪክ ማዛባትን እና የዝግጅት እጥረትን ያየንባቸው መጽሐፍት አጋጥመውኛል። በምሳሌ ላስቀምጥ፦ በኢህአፓ ታሪክ ውስጥ ህይወት ተፈራ በ 'ማማ በሰማይ' መጽሐፏ የጌታቸው ማሩን ሚና ስታጎላ፤ አንባሳደር ታደለች ሐይለሚካኤል ደግሞ 'ዳኛው ማነው' በሚለው መጽሐፏ በኢህአፓ ታሪክ ውስጥ የብርሃነ መስቀል ረዳን ሚናን አጉልታ ታሳየናለች። የእነዚህ የሁለት ሰዎች ሚናም ቀላል አልነበረም። በኢህአፓ ዙሪያ ከተጻፉ መጽሐፍቶች በእኔ እይታ እነዚህ መጽሐፍቶች የመጀመሪያ ደረጃን ይይዛሉ። በታሪክ ውስጥ እንዲጎላ የተገባን አካል በተገቢው ደረጃ ማጉላት ችግር ባይኖረውም ነገር ግን የራስን ነገር ለማጉላት ታሪክን ማፋለስ፤ ሙሉ መረጃን አለመስጠት እና የተለያዩ ክፍተቶችን መፍጠር አግባብ አይደለም። የአንዳንድ ሰዎች ታሪክ ግለ ታሪክ ብቻ አይደለም የቤተክርስቲያን ታሪክም ነው። የእንደነዚህ አይነት ትልልቅ ሰዎች ታሪክ ሲጻፍ በብዙ አይነት መንገድ መታየቱ የግድ ነው። ይህ አይነት ነገር ቤተክርስቲያንን የመሩ፤ አብያተክርስቲያናትን የመሩ ለብዙ አመታት ያገለገሉ አገልጋዮች ታሪክ ሲጻፍ ሊተኩርባቸው ይገባል የምላቸውን ነገሮች በጥቂቱ ላስቀምጥ። ታሪክ እየቆየ ሲሔድ የመረሳት ነገሩም ከፍተኛ ነው። ይህ አይነት ችግር ደግሞ ሙሉ ታሪኩን እንዳናውቅ ይረዳናል። በአንድ ቦታ እግዚአብሔር ስላስነሳው መንፈሳዊ መነቃቃት ( Revival) ለመጻፍ ስንነሳ ምንም እንኳ የሚጻፈው የአንድ ግለሰብ ታሪክ ቢሆንም እንኳ በግራና በቀኝ የነበሩ ሰዎች ምስክርነትን መሰብሰብ አስፈላጊ ነው። እኔ በገባኝ ግለ-ታሪክ ሲጻፍ መሆን ከሌለባቸው ነገሮች በጥቂቱ ላክፍል። እነዚህ ሐሳቦች በተለያዩ ጊዜያት ከተለያዩ ወዳጆቼ ጋር እንደዚህ ቢሆን ብለን የምንወያይባቸውም ናቸው። ፨ ግለሰቦቹ ታሪካቸውን ሲጽፉ ወይም ሲያጽፉ ብርታታቸውንና እግዚአብሔር በእነርሱ የሰራውን ብርቱ ስራ ብቻ ሳይሆን ድካማቸውን ጭምር መጻፍ አለባቸው። የእግዚአብሔር ጀነራሎች መጽሐፍ ጸሐፊ ሮበርት ሊያርደን እንዲሁም መመሪያችን የሆነው መጽሐፍ ቅዱሱ የሰዎችም ጠንካራ ጎን ብቻ ሳይሆን በጊዜው የነበራቸውን ደካማ ጎን ጭምር መጻፍ አለበት። ጠንክረው ካለፉበት ብቻ ሳይሆን ወድቀው ከተነሱብት፤ ባለመቻል ካለፉበት መንገድም እንማራለን። ፨ መጽሐፉ ከግነት መጽዳት አለበት! የሚጻፍለት ግለሰብ ወይም ቤተክርስቲያንን የማጋነን እና በታሪክ ውስጥ የበላይ ለማስያዝ ከሚደረግ የታሪክ ሽሚያ ግብግብ ከአላስፈላጊ የታሪክ ባለቤትነት እሽቅድድም መጽዳት ያስፈልጋል። ግነት አንድን ታሪክ የውሸት ታሪክ ያደርገዋል። በተቻለ መጠን የግለሰቦቹ ታሪክ እንደነበረው መጻፍ መቻል አለብት። ፨ ፍጹምነትን ማስወገድ- አንዳንድ የህይወት ታሪክ መጽሐፍቶች ሰው ሰው የማይሸቱ፥ በመጽሐፉ ያሉ ታሪኮቹ ሰው በእውን ያለፈባቸው የማይመስሉ እና በሁሉም ነገር እንከን አልባ ተደርገው እንዳይጻፉ መጠንቀቅ ያስፈልጋል። ከእንደዚህ አይነት ታሪኮች ትውልድስ ምን ይማራል? ሰዋዊ የሆኑ የህይወት ታሪኮች አስፈላጊ ናቸው። ፨ በታሪክ ውስጥ የራስን የበላይነት ለማሳየት ከሚደረግ የታሪክ አጻጻፍ መቆጠብ ያስፈልጋል። እንትን የተባለውን ሪቫይቫል እኔ ወይም የእኛ ቤተክርስቲያን ነች የጀመረችው የሚሉ የተለያዩ ሰዎች ካጋጠሙን ችግሩ የታሪክ ሽሚያ ሊሆን ይችላል። ሁሉም ሰው በተሳካ ነገር ውስጥ ራሳችንን የማስቀመጥ አባዜ አለብን። ምን አልባት እነዚህ አይነት ግለሰቦች በታሪክ ውስጥ ጥቂት የራሳቸው አሻራ ሊኖራቸው ይችል ይሆናል። ነገር ግን ሙሉ ሙሉ የታሪኩ ባለቤት ላይሆኑ ይችላሉ። በታሪክ ውስጥ ያለን ተሳትፎ ብቻ መጻፍ አለበት። በታሪክ ጽህፈት ውስጥ አንድን ታሪክ የራስ ለማድረግ ከሚደረግ ሽሚያ ልንታረም ይገባል። ፨ ሐላፊነትን መውሰድ- ቀደምት አገልጋዮች ከሆኑ ታሪኩን የጻፉት ሙሉውን ታሪክ የመጻፍ እና በታሪክ ውስጥ ለተሳሳቱት ስህተት በመጽሐፋቸው ሐላፊነት ወሰድው ትውልዱን ይቅርታ መጠየቅ የ አለባቸው። ትናንት በአገልግሎት ዘመናቸው፥ በመሪነት ጊዜያቸው የተሳሳቷቸውን ስህተቶች መጽሐፉቸውን በሚጽፉ ጊዜ ስህተት የነበረውን ስህተት ነበር ብለው ሐላፊነት መውሰድ አለባቸው። ፨ ሙሉውን እውነት መስጠት- አንዳንድ ግለ ታሪኮች ላይ የምናየው ችግር ሙሉውን ታሪክ አለመናገር ነው። ማለትም በታሪክ ክስተት ውስጥ ያጋጠመን ነገር ሊሆን ይቻላል የተነሳበት ምክንያት ፤ በጊዜ የነበረን የእኛ አቆም፤ ያ ጉዳይ የጎዳቸውም ወይም የጠቀማቸው ነገሮች ካሉ በዝርዝር መጻፍ አለባቸው። በግለ-ታሪክ ውስጥ ማስቀመጥ ያለብን ሰዎች እኛ እንዲያውቁ የምንፈልገው ሳይሆን በጊዜው የነበረውን እውነተኛ ታሪኩን ነው። ለዛሬ አበቃሁ። ( በግለ-ታሪክ ዙሪያ በአገራችን ከተከወኑ እና በአገራችን ጸሐፍት ከተጻፉ መጽሐፍት እነዚህን እንድታነቡ እጋብዛለሁ) በ- ዘሪሁን ግርማ የቴሌግራም ቻናሌን ይቀላቀላሉ https://t.me/theideaofs

ሰዎች እንዲሰሙን እንፈልጋለን፣ እኛ ግን ሰዎችን እንሰማለንን?፣ ሰዎች እንዲወዱን እንፈልጋለን፣ እኛስ ሰዎችን እንወዳለን?፣ ሰዎች እንዲያከብሩን እንፈልጋለን፣ ሰዎችን ለማክበር ዝግጁ ነንን? የእኛ ነገር እንዲቀድም እንፈልጋለን፣ እኛስ ሰዎችን እናስቀድማለን?፣ ታናናሾቻችን እንዲታዘዙን እንጠብቃለን፣ እኛ ለታላላቆቻችን ታዛዥ ነን? ያልዘራነው ያጨደ፣ ያልተጋበትን የወረሰ፣ ያላሸነፈውን የገዛ ማነው? ያልዘራነውን የምንጠብቅ ሞኝ እንዳንሆን፣ እኛ እንዲደረግልን የምንፈልግ ለሌሎች እናድርግ። .. ዘሪሁን ግርማ

#የውሸት_ምላስ_ቀስቶች "የሰዎችን ህይወት 'በውሸት' ለማጥፋት አንሞክር፣ እኛ 'በእውነት' ሊጠፋ የሚችል ማንነት አለንና።" በሰዎች ላይ የሚዋሽ ውሸት መልኩ ብዙ አይነት ነው። ስለ ሰዎች መዋሸትና በሰዎች ላይ የምን ዋሸው ውሸቶች ምክንያታቸው ብዙ አይነትም ነው። የሰዎችን መልክ (Image) ማጠልሸት፣ ሙሉ እውነት ሳይኖረን የምንናገራቸው ግምታዊ ወሬዎች ጭምር ምንም ስለ እነዚያ ሰዎች ሙሉ እውቀት በሌላቸው ሰዎች ዘንድ የተሳሳተ እይታን ይፈጥራል። ስም መለጠፍ ቀላል በሆነበት በዚህ ጊዜ ደግሞ በማናውቀው ነገር ስለ ሰዎች የምንናገራቸው ውሸቶች ቀላል አይደሉም። አንዳንድ ሰዎች ስለ እናንተ በጥላቻ፣ ወይም በግምት ዋሽተውባቸው፣ ውሸትን አውርተውባችሁ ያውቃሉን? አዎ ያጋጥመናል ወይም እኛም በሰዎች ላይ ዋሽተን ይሆናል። ውሸት የሰዎችን መልክ ከማጠልሸት በላይ፣ የሰዎችን ስራ፣ አገልግሎት እና ትዳርና ግንኙነት ጭምር ያበላሻል። በጣም የሚገርመን በስህተት ተገኝተን ስለ እኛ ከሚነገር እውነት ይልቅ፣ በውሸት የሚዘራ ዘር ብዙ ነገራችንን ያበላሻል። 'ጆሮ ለባለቤቱ ባዳ ነው' እንደሚባለው አንዳንድ ውሸት ተወርቶ፣ ስር ሰዶ፣ ዞሮ ዞሮ፣ ተዘርቶ በቅሎ ፍሬን አፍርቶ ሲያበቃ የምንሰማቸው ብዙ ውሸቶች ይኖራሉ። ከጦር መሳሪያ በላይ የውሸት ወሬ ሰዎችን ከቤተ ክርስቲያን ያሳድዳል፣ ከአገልግሎት ያሰናክላል። ከህይወት ጭምር ያጎድላል። የስም ማጥፋት ትልቁ መሳሪያ ውሸት ነው። ስም ደግሞ የሰው መልክ ነው። አንዳንድ ሰዎች ገምተን፣ አስበውና፣ ውሸትን ጸንሰው ስለ እናንተ የሚዋሹትን ውሸት አምነው የሚኖሩ ብዙ ሰዎች ይኖራሉ። ውሸት ነገ በእኛ ህይወት ላይ በክፉ የሚበቅል ክፉ ዘር ነው። ውሸት በቤተ ክርስቲያን መካከል ትልቁ የሰይጣን መሳሪያ ነው፣ ጥይቱም ውሸተኛ ሰው ነው። ከላይ የጠቀስኩት አባባል ከቲክቶክ መንደር ስትዘዋወር ያገኘኃት ናት። "የሰዎችን ህይወት 'በውሸት' ለማጥፋት አትሞክሩ፣ እኛ 'በእውነት' ሊጠፋ የሚችል ማንነት አለንና።" ይላል ማለትም እኛ የእግዚአብሔር ምህረት የሸፈነው ቢገለጥ ሊያጠፋን የሚችል ብዙ እውነተኛ የሆነ ድካም አለብን። አደባባይ ላይ ቢገለጥ ማንም በእኛ ላይ ሳይዋሽብን ልንጠፋበት የምንችል እውነተኛ ድካም አለን። በሰዎች ላይ ዋሽተን የሰዎችን ህይወት በመኮነን የሚገኝ ራስን የማጽደቅ ስራን መስራትና የሰዎችን ስምና ማንነት ማጠልሸት መልሶ ክፋቱ ለእኛው ነው። ውሸት ውሸት ሆኖ አይቀርም መገለጡና ወደ ብርሃን መምጣቱም አይቀርም። ስለ ውሸት መልስ የሚሰጡ ሁለት ነገሮች አሉ እነርሱም፦ እግዚአብሔር እና ጊዜ ናቸው። እግዚአብሔር ውሸትን ወደ ብርሃን ማምጣት ብቻ ሳይሆን፣ በእውነት ጌጥ የተለበጡ ውሸቶችን ጭምር በእውነተኛው እውነት ይገልጣቸዋል። እግዚአብሔር ከሚጸየፋቸው ነገሮች መካከል "በውሸት ላይ ውሸት የሚጨምር ሐሰተኛ ምስክር፣ በወንድማማቾች መካከል ጠብን የሚጭር ሰው።" ምሳሌ 6፥19 በጥላቻ መዋሸት፣ በቅናት መዋሸት፣ ለማጣላት መዋሸት፣ ሰዎችን ለመጉዳት መዋሸት፣ ራስን የተለየ አድርጎ ለማሳየት ስለ ሌሎች መዋሸት፣ ሰዎች ባልተገኙበት ማስቀመጥ፣ የሌላቸውን ማናንነት በውሸት ማሰጠት፣ ስማቸውን ማጥፋት፣ በአገልግሎታቸውና በነገራቸው ላይ የውሸት ቃላትንና ዘርን መዝራት መልሱ ከእግዚአብሔር ዘንድ ሲመጣ አዝመራው ከባድ ነው። በሰዎች ላይ የምንዘራቸው ክፉ ዘሮች አዝመራው የሚታጨው በእኛ ቤት ነው። ሳናውቅ ተነድነተው፣ አውቀንም በክፉት፣ አልፈን በአመጻ ሰዎች ላይ ስለ ተናገርናቸው ውሸቶች ጌታ ይቅር ይበለኝ። በማናውቀው ነገር ገምተን፣ መዋሸት ሱስ ሆኖብንም ብንሆን ጌታ ይቅር ይበለን። እኛ በጀመርነው ውሸት ወይም ከሌሎች ውሸት ጋር ተባብረን ውሸትን ስላገነንን ይቅር ይበለን። ማናችንም በዚህ በደል ልንገኝ እንችላለን፣ ይህ ጽሑፍ ራሳችንን እንድናይ ማንቂያ ነው እግዚአብሔር ይቅር ይበለን። .. ዘሪሁን ግርማ https://t.me/theideaofs

ከሚመጡልኝ ጥያቄዎች መካከል “የመጻፍ ክህሎት እና ዲሲፕሊን” (Writing Skills and Discipline) አብዛኛውን ጊዜ ከምጠየቃቸው ጥያቄዎች መካከል ስንት መጽሐፍ እንደጻፍኩ እና ይህንን ያህል መጽሐፍ በስኬታማነት ለመጻፍ ምን አይነት መንገድ እንደምጠቀም ለማወቅ የሚጠየቁ ጥያቄዎች ይገኙበታል፡፡ በቀላሉ ለመመለስ ያህል፣ የሕይወትን ክህሎት በማሳደግ (self development) ዙሪያ 28 ማጻህፍቶችን ለአንባቢያን አድርሻለሁ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ብዙ ሰዎች የመጻፍን ክህሎት እና ዲሲፕሊን የማዳበርን ስልጠና መውሰድ እንደሚፈልጉ ይገልጹልኛል፡፡ በዚህ ርእስ ዙሪያ “የመጻፍ ክህሎት እና ዲሲፕሊን” (Writing Skills and Discipline) የተሰኘ ስልጠና ዝግ ለሆኑ ግሩፖች አልፎ አልፎ እሰጣለሁ፡፡ ይህንን ስልጠና በቂ የሆኑ ሰልጣኞችን ፍላጎታቸውን ሲገልጹልኝ ለማዘጋጀት ስለማስብ ፍላጎቱ ያላችሁ inbox ብታደርጉልኝ ወደፊት ስልጠናውን ለማቅረብ ስዘጋጅ ላሳውቃችሁ እችላለሁ፡፡ Dr. Eyob Mamo

#እግዚአብሔር_ያያል!! ፨ በማይመች የህይወት መንገድ ላይ እያለፋችሁ እንኳ ጸንታችሁ እያገለገላችሁ ላላችሁ፣ እግዚአብሔር ያያል። ጽኑ። ፨ ስለ ወንጌል ብላችሁ፣ ክብራችሁ እንደ ነውር የተቆጠረባችሁ እናንተ እግዚአብሔር ያላችሁበትን ያያል። ጽኑ። ፨ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የመፈጸም ታዛችሁ በመንገዳችሁ ወደ ኃላ የቀራችሁ የመሳላችሁ በማይመስል መንገድ ላላችሁ፣ መዘግየት ከእግዚአብሔር ጋር ሆኖ የለም፣ እግዚአብሔር የምታልፉበትን ያያል። ጽኑ። ፨ በቅንነት መንገድ እየሄዳችሁ ቅን ባልሆኑ ሰዎች ክፋት የተጎዳችሁ። እግዚአብሔር ያያል። ጽኑ። ፨ ነፍሳችሁ የእግዚአብሔር ፈቃድ በመፈጸም ጠባብ መንገድ ውስጥ እያለፈች፣ በሰፊው መንገድ ላይ በሚመላለሱ ስኬትና ተድላ በሚመስል ጎዳና በሚሯሯጡ ሰዎች አመጻ የተጨነቃችሁ እግዚአብሔር ያያል። ጽኑ። ፨ የፍሬያማነት ዘመናችሁ እስኪመጣ፣ በመካንነት ስድብ ውስጥ እያለፋችሁ ያላችሁ እግዚአብሔር ያያል። ጽኑ። እግዚአብሔር ያያል፣ የማያየን በሚመስለን ጊዜ ራሱ እያየን ነው። የምናደርጋቸው ነገሮች ሁሉ በፊቱ የተረሱ አይደሉም። ትግላችን ማብቂያ አለው፣ የተናገረን ቃል ፍጻሜ አለው። ይህ መልዕክት እግዚአብሔር በተናገራችሁ ነገር ላይ ቆማችሁ፣ በታማኝነት አሁንም ድረስ እግዚአብሔር በሰጣችሁ ቦታ ላይ እያገለገላ ችሁና እና እየተመላለሳችሁ ላላችሁ ለእናንተ ነው። እግዚአብሔር ያያል ጽኑ። ምላሽ አለው፣ በጊዜው ሁሉም ውብ ይሆናል። የስንፍና ቃል አትናገሩ፣ ለሁሉም ድልን የሚሰጥ እግዚአብሔር ነው። እግዚአብሔር ያያል። ዘሪሁን ግርማ https://t.me/theideaofs