cookie

We use cookies to improve your browsing experience. By clicking «Accept all», you agree to the use of cookies.

avatar

ጠበኛ እውነቶች😍

ምርጫ አልባ ምርጫ

Show more
Advertising posts
213
Subscribers
No data24 hours
No data7 days
No data30 days

Data loading in progress...

Subscriber growth rate

Data loading in progress...

ታውቃለህ ?? የተደገፍከው ያ እንዳንተ ስጋ ለባሽ ሰው የህይወትህን መንገድ ያካሂድህ (አብሮህ ይጏዝ) ይሆን ይሆናል እንጂ ... ያንተን ጉዞ አይጏዝልህም!! ልበ-ቀና ከሆነ መንገድህ ያዛለህ ጊዜ ያበረታሃል!! ... የወደቅህ ሰዓት ደግፎ ያነሳሃል!! .... የፍቅር ሰው ከሆነ በመንገድህ ስታነክስ ትከሻውን አስደግፎህ በምትጎትተው እግርህ ልክ የራሱን መንገድ ፍጥነት ገትቶ አብሮህ ይጏዛል:: በጣም ለፅድቅ የቀረበ ከሆነ እስከሚችለው ድረስ ያዝልህ ይሆናል:: .... (አንተ ጀርባው ላይ ሀሳብህንም ክብደትህንም ጥለህ ለሽ ብለህ እያንቀላፋህ ... ፈሱ እስኪያመልጠው አይሸከምህም!! ... 🤷🏽‍♀️🤷🏽‍♀️) በተረፈው ሁሉም ልክ እንዳንተው የራሱ ሩጫ.. የራሱ መውደቅ እና መነሳት ... የራሱ ጉድለት አለው እና የራሱን አቁሞ እንዲያቋቁምህ መጠበቅ የዋህነት ነው!!! ወደቅህም ተነሳህም .. ፈረጥክም ... ቀደምህም ... ዘገየህም ...ህይወቱኮ ያንተ ነው!! እገሌ እንዲህ አላደረገልኝም ... እገሊት ትታኝ አለፈች... ታምሜ ሳይጠይቁኝ ... ሞቼ ሳያለቅሱልኝ ... እያልክ የምታላዝነው ምን ሆነህ ነው?? ለራስህ ህይወት ሀላፊነቱን ራስህ ውሰድ እንጂ 🙄ምን ሆነህ ነው ቤተሰብ .. ጎደኛ .. ፍቅረኛ ... ደርበው ያንተን ስንክሳር እንዲኖሩልህ ቁጭ ብለህ የምትጠብቀው?? እንኳን ሰው አምላክ ራሱ ሲረዳህኮ የምትጏዝበትን ጉልበት እና ጥበብ እንጂ የሚሰጥህ በአስማት ነገር እንደንፋስ አያስወነጭፍህም!! እንዳልኩህ ነው!! ማንም ቢሆን አብሮህ ይሮጥ ይሆናል እንጂ ያንተን ሩጫ አይሮጥልህም!! ... ሰው እንዲረዳህ ከመጠበቅህ በፊት በራስህ የምትችለውን አድርግ !!! ሰው እንዲወድህ ከመጠበቅህ በፊት ራስህን ውደድ !! ሰው እንዲያከብርህ ከመጠበቅህ በፊት ራስህን አክብር!!) (ሄዋንዬ ለአዳም ነው ብለሽ አላለፍሽማ?? 🤣🤣🤣 ለኛም ነው እህትዬ❤️❤️❤️❤️ ) ውብ አርብ ውብኛ አዋዋል ዋሉልኝማ❤️❤️❤️
Show all...
ኦገኖቼ ባልተቤትየውኮ እንፋታ አለኝ 😭😭😭😭 እርግጥ እሱ "ወጋሁ!! እኔ አልወጣኝም!" ብሏል.... በቀጥታ አላለም እንጂ ብሏል.... 'ከኔጋ መዋል ከጀመረ ተንከሲስነት እየለመደ መጥቶ እንጂ ድሮ የዋህ ሰው ነበር' ብያችሁ የለ??? ይኸው የቀረው ቅኔ: አሽሙር: ሽሙጥ .... ነበር... እሱንም ጀምሯል:: ምንድነው የሆነው መሰላችሁ??? ባለትዳሮች ታውቁታላችሁ!! ልክ ተጋብተን መኖር ከጀመርን ቀን ጀምሮ ሳንማከር (አንዳንዱ ተነጋግሮ) መኝታችንን የባል ቦታና የሚስት ቦታ ብለን ርስታችንን እንመዳደብ የለ??? ... ( በድሮ ጊዜ እንደአሁኑ አልጋችንን እንደቀይወጥ ክፍሉ መሃል ላይ ጉሊጥ የምናደርገውን ስታይል ሳናመጣ በፊት አልጋው ግድግዳ ታክኮ በሚቆምበት ወቅት ... የሚስት ቦታ በግድግዳ በኩል... የባል ቦታ ወደበር ወይም ከግድግዳ ተቃራኒ ነበር የሚሆነው አሉ!! ምክንያቱም ድንገት የሆነ ነገር ቢፈጠር ለምሳሌ ሌባ ቢገባ... አባወራው መዥረጥ ብሎ የአባወራ ምከታ ተግባሩን እንዲከውን ነው አሉ:: እንደ ዘንድሮ በእግሩ ጥፍር አልጋው ላይ ቆሞ ሚስቱን እየተጣራ "አይጧ መጣችልሽ!!" የሚል ባል አልነበረም አሉ..... አሉ ነው እንግዲህ 🤪🤪🤪) እናላችሁማ ይኸው 5 ዓመት በትዳር ስንቆይ የመጀመሪያ ቀን ያስከበርናትን የአልጋ ርስት ተደፋፍረን የማናውቅ ሰዎች ... ትናንት ማታ እሱ በጊዜ ተኝቶ እኔ አርፍጄ ልተኛ ስሄድ እቦታዬ ላይ ለሽ ብሎ አላገኘሁትም??? ....... መቼም አንዳንዴ አንዳንዴም ቢሆን ጥሩ ሰው እሆን የለ??? ድምቅ አድርጎ ከተኛበት አልቀሰቅሰውም ብዬ በሱ ቦታ ተኛሁ!!! .... ገና ገልጬ ስገባ ቅዝቃዜው ተው.... (መኝታ ቤት ውስጥ heater አንለኩስም!! የዚህ ሀገር ሰዎች ማታ ንፁህ አየር እየተነፈስን ነው ማደር ያለብን ብለው ጭራሽ መስኮት የሚከፍቱት ታሪክ አላቸው!!.... ማለቴ በ -10 ዲግሪ ሴንቲግሬድ ነውኮ የምላችሁ🙄🙄 እህህህ ምን እያልኳችሁ ነውና?? .... እኔ ለራሴ እየበረደኝ እንቅልፍ ሊወስደኝ ይቅር እና ማሰብም ነው የማልችለው.... እሱ ደሞ ጭራሽ እንደሞላለት ሰው በቦክሰር ሁላ ነው የሚተኛው... ይሄን ለማስታረቅ የእኔ ቦታ ላይ ከአንሶላዬ ስር የምትነጠፍ እንደአንሶላ የሳሳች ማሞቂያ ገዝተን ... ተከባብረንና ... አንቺ ትብሽ አንተ ተባብለን ነበር የኖርነው .... ) እና ይሄ ከፍተኛ ሴራ አይደለም??? ቦታዬን ከነሙቀቱ ቀምቶኝ ለሽ ብሎ ደሞ አተኛኘቱ እንቅልፍ እንቢ ላለው ሰው ደም ሲያፈላ 🤷🏽‍♀️🤷🏽‍♀️🤷🏽‍♀️🤷🏽‍♀️ ታግዬ ታግዬ ሽልብ ቢያደርገኝ ሰው ቤት እንግድነት ሄጄ ለመጀመሪያ ጊዜ የማድር አይነት ስሜት እየተሰማኝ ብንን ማለት .... መባነኑ ሲቀር ... ከትንሽዬዋ የጉንዳን መንጋ ጀምሮ ያላባረረኝ እንስሳ የለም በህልሜ .... ቀጭኔዋ ፀጉሬ የደረቀ ሳር መስሏት ነው መሰለኝ ፀጉሬን ይዛ አንጠልጥላኝ መሬት እርቆኝ "ወይ መሬት ያለ ሰው" ስል ነቃሁ!!!..... ለሽ እሱ ምናለበት.... ሙሉ ለሊትማ ደግ አልሆንም ብዬ ቀስቅሼው "ምን እንደፈለግክ በግልፅ ተናገር!! ከዚህ ሁሉ ለምን እንፋታ አትልም!!" አልኩት.... "(አበስኩ ገበርኩ አይነት ነገር በኖርዌጅኛ አጉተምትሞ ሲያበቃ አይኑን ሳይገልጥ ) ማታኮ ቶሎ የምትተኚ መስሎኝ ላቅፍሽ ስጠብቅሽ እንቅልፍ ጥሎኝ ነው!! ( እንጣዬ ነው ያለው ... ጨዋ ሳደርገው ነው) " ብሎ ደገመውኮ ..... ደገመው ስላችሁ🙄🙄🙄🙄 ለሽ!!!! .... እሺ እኔ በዚህ ለሊት ንጋት 12 ሰዓት ለእናንተ ላቃጥር ነጠላዬን አቀብሉኝ ማለት ነበረብኝ??? እሱኮ እንደተኛ ነው በርስቴ..... እና ይሄ እንፋታ ከማለት ቢበዛ እንጂ ያንሳል???? 🤣🤣🤣🤣 ውብ ቀን ውብኛ አዋዋል ዋሉልኝማ❤️❤️❤️❤️
Show all...
ላንቺ ይሁንልኝ!! ያኔ በርረሽ የትም መድረስ የምትችዪ የሚመስልሽ ልጅነትሽ ውስጥ ብዙ ህልም የነበረሽ ፣ <ሳድግ የምሆናት> ብለሽ አርቀሽ የሰቀልሻት አንቺ የነበረችሽ ፣ እደምቅበታለው ያልሽው መክሊት እና ችሎታ የነበረሽ ……… ከዛ ግን ዓመታት ነጉደው ስትነቂ ክንፍሽ የተሰበረ ዓይነት ስሜት ያለው …….. ~ አግብተሽ ወልደሽ ….. በልጆችሽ ፍቅር ውስጥ ጠፍተሽ …. ምናልባትም ባልበሰለ ውሳኔሽ የተሳሳተ አጋር መርጠሽ ያዘመመ ትዳር እየመራሽ …… የእለት ተዕለት ኑሮን ለማስኬድ እጅሽ የደረሰበትን ስራ እየሰራሽ በኑሮ ትግል ደብዝዘሽ ……. ህልምሽ ተዘንግቶሽ ….. ሳድግ የምሆናት ካልሻት አንቺ የልጆችሽን ማደግ አስቀድመሽ …. ከራስሽ ጋር የምታወሪበት ፋታ ስታገኚ «በቃ?!! ህይወቴ ይሄ ነው በቃ?!! ህልሜ ፣ ምኞቴ ቅዠት ብቻ ነበር?!!» የምትይበት ዝቅታ ለሚሰማሽ ~ደግሞ ለቤተሰቦችሽ ወይም ለልጅሽ ቀን ላውጣላቸው ብለሽ ተሰደሽ በሰው ሀገር ስትለፊ ያንቺ ቀን ያለፈ ለሚመስልሽ ፣ በትከሻሽ ተሸክመሽ ባህር ያቋረጥሽውን ሀላፊነት ቀስ በቀስ ስትንጂ …. ወንድምሽ አግብቶ የራሱን ቤተሰብ መምራት ሲጀምር ፣ ለአባትሽ ቤት ከገዛሽ ኋላ ፣ እህትሽ ትምህርቷን ስትጨርስ ….. ለምትወጃቸው <ቆይ ይሄን አድርጌ> እያልሽ ዓመት ዓመትን ሲደርብ ….. <አሁን ለራሴ መኖር ልጀምር !> ስትዪ እድሜሽም ሄዶ ፣ ድሮ ያስቀመጥሽውን አንስተሽ መቀጠል እንዳትችዪ ሆኖ ተቀያይሮ … ከዚህ በኋላ ገና ተምሬ? ከዚህ በኋላ ገና ፍቅር ፈልጌ? ከዚህ በኋላ ምንስ ብጀምር እስክጨርሰው የትዬለሌ …… ብለሽ ቀኑ የሰጠሽን ተቀብለሽ «በቃ! አሁንማ አበቃ!! ድሮ ነበር!» የምትይበትን ዝቅታ ለነካሽ ~ ደግሞ ላንቺ …. በአደባባይ <እሷን ባደረገኝ> የሚባልልሽ ስኬታማ ፣ በመንገድሽ ላገኘሽው ሁሉ ብርታት እና ንቃትን የምታጋቢ ፣ ለልጆችሽ፣ ለጓደኞችሽ ፣ ለቤተሰቦችሽ እና በዙሪያሽ ላሉ ሁሉ በሳቅሽ ቀናቸውን የምታፈኪ ፣ በአደባባይ የዋጥሽው እንባ ብቻሽን ስትሆኚ የሚገነፍልብሽ ፣ እቤትሽ የምታነክሽበት ጉድለትሽ እንስ አድርጎ የሚያኮማትርሽ ….. <እስከመቼ ነው እንዲህ ባዶነት የሚፈረካክሰኝ? በቃ ህይወቴ እንዲህ ነው የሚቀጥለው? ያ ሁሉ የወጣሁ የወረድኩት ለዚህ ባዶነት ነው?> የምትይበትን ዝቅታ ለነካሽ ታውቂዋለሽኮ የመጨረሻ የዝቅታ ወለል ላይ ስትሆኚ ያለሽ ምርጫ ሁለት ብቻ ነው!! ወይ ወደላይ (ወደከፍታ) መሄድ ወይ ደግሞ እዛው መቆየት ነው። ምክንያቱም ከመጨረሻው ወለል ወደየትም ዝቅ አትይማ!! እዛው መቆየት ያንቺ ምርጫ አይሆንምኣ? <በቃ! አከተመ! > የሚባልበት እድሜም ሁኔታም የለምኮ!! ረስተሽው ወይ እየደቆሰሽ ባለፈ አስቸጋሪ ቀን የተሟጠጠ መስሎሽ እንጂ እንኳን አንድ ያንቺን የሌላውን ደርበሽ አቀበቱን የምትወጪበት ጉልበትኮ ነው ያለሽ!! ለምን አንድ ዓመት አይሆንም የቀረሽ የእድሜ ዘመን? እየሞከርሽ ፣ እያለምሽ ፣ መራመድ ባትችዪ እየተንከብለልሽ ዘመንሽ ይለቅ!! ምክንያቱም ስኬትኮ የተራራው ጫፍ አይደለም!! ጉዞውም የስኬትሽ አካል ነው!! መፍጨርጨር እና እየወደቁ መነሳቱምኮ ወደ ህልምሽ መቅረቢያ መንገዱ ነው!! የህልምሽ አካል ነው!! በቀንሽ መጨረሻ ምን ዓይነት ሴት ሆነሽ ማለፍ ነው የምትፈልጊው? ምን አይነት አሻራ ጥለሽ ነው ማለፍ የምትፈልጊው? ሁሉ ነገር ሲመቻች ብቻ አይደለም ያቺን ራስሽን የምትሰሪው ፤ አሁን ባለሽበት ዝቅታሽ ውስጥ ..... በኑሮ ውጣ ውረድ በደበዘዘ ነገሽ..... ምንም ተስፋ የሚሰጥ ጭላንጭል ብርሃን ባይታይሽም ራስሽን ስሪ ፣ ነገ የእኔ ቀን ሲመጣ የማጌጥበት ነው ብለሽ መክሊትሽን አዳብሪ!! አታስቀምጪው (አትደብቂው)!! እጅ አትስጪ እንጂ ያ ቀን ይመጣል!! አድካሚም ቢሆን ያ ያንቺ ቀን ይመጣል!! እየተዘጋጀሽ ፣ እያደግሽ ፣ እየተለማመድሽ ካልቆየሽኮ ግን ያ ቀንሽ ቢመጣም አትደምቂበትም! ምክንያቱም ተስፋ ቆርጠሽ ቀን እስኪመጣ የጣልሽው ህልም ነው ያለሽ እንጂ የምትሰጪው ወይ የምታሳዪው ነገር አይኖርሽም!! ደግሞ ከሁሉ በላይ የሰማዩ አምላክ አለ አይደል? ለእያንዳንዷ ለዘራሻት ፍቅር ፣ ለሞላሽው ጉድለት ፣ ላበስሽው እንባ ፣ ቀና ላደረግሽው አንገት …….. ይሄን ሁሉ ብድራትሽን ሊከፍልሽ ሳለ የምን እጅ መስጠት ነው? <አበርታኝ> በይው!! አንድ ለመራመድ የዘረጋሽው እግርሽ አስር ተራምዶ ታገኚዋለሽ!! እመኚኝ አልፎ ወደኋላሽ ዞረሽ ስታዪው እንዳለፈ ውሃ ነው!! ደሞ በተረፈው እኔ እወድሽ የለ? ❤️❤️ ውብ ቀን ውብኛ አዋዋል ዋሉልኝ!!! ❤️❤️❤️ (ወንዶች ካነበባችሁት ምናልባት ሊያስፈልጋት ስለሚችል ለሚስትህ አንብብላት ወይም ስደት ላለች እህትህ!! ቺኮችዬም አንብባችሁት!! ኸረ እኔ የለሁበትም! ያላችሁ እንተላለፍ !! )
Show all...
(ቤተሰብ ❤️❤️❤️❤️ከጥሩ ነው ባሻግር የእያንዳንዳችሁን አስተያየት detail እፈልጋለሁ። የተሰማችሁን! የጠበቃችሁትን! ፌስቡክ የምትጠቀሙ ልጆች እዛ ለኮመንት ስለሚመች የመጨረሻውን ክፍል ፖስት አደርገዋለሁ። እናካችሁ እዛ ኮመንት አድርጉልኝ እዛው እየተመላለስን እንድናወራ!! ፌስቡክ የማትጠቀሙ እዚሁ አስተያየታችሁን አስፍሩልኝ!! እንግዲህ ደግሞ በሌላ ፅሁፍ እስክንገናኝ ቸር ያቆየን!! 202 ገፅ መፅሐፍ ነው ያነበባችሁት እወቁት!! ) ነፍፍፍፍፍፍፍፍf ፍቅር ይኸው ❤️❤️❤️❤️
Show all...
«ከዚያስ!» «ከዚያማ ምን የማታውቂው ቀረ?» «ይቀራል እንጂ! መች ነው የወደድከኝ? የተመታሁ ቀንኮ ግን ትተኸኝ ልትሄድ ነበር ለነሱ ትተኸኝ!» «መች እንደወደድኩሽ ምኑን አውቄው? ስገቢ ስትወጭ ስትገለምጭ ስትሰድቢኝ!! አንዳንዴ ነገረ ስራሽ አፍሽ እንጅ የከፋ ልብሽ ደግ መሆኑን ሲነግረኝ አላውቅም!! እነርሱ የሚፈልጉትን መረጃ ሁላ አግኝቼ ለእነርሱ አሳልፌ ልሰጥሽ አቃተኝ!! ጥላሽን የማታምኝ ሴት እኔን ግን ከነጭርሱ አለመጠርጠርሽ አሳዘነኝ!! እንጃ ካስታወሽ የሆነ ቀን ለሊት ገብተሽ በር ስከፍትልሽ <አንተ ግን ደስተኛ ነህ?> አልሽኝ።» ብሎ ፈገግ አለ። አስታወስኩት። ትንሽም ቢሆን ደስታዬ የነበረው ከእሙጋ በማሳልፈው ጊዜ የነበረ ጊዜ እሷ የማያገባት ነገር የመቆስቆስ ሱሷ አላስቀምጥ ብሏት ለአምስተኛ ጊዜ የታሰረች ቀን ነው። (እኔ እስር ቤት ለ6 ዓመት እያለሁ እሷ ሁለቴ ገብታ ወጥታለች። ስትገባ አብረን ጊቢውን እናምሳለን። ከጋዜጠኝነቷ ባሻግር ታቱ መስራት በልምድ ተምራለች። እስር ቤት ውስጥ እንኳን ዘመናዊ ንቅሳት ልትነቀስ ፀጉሯን ከሁለት ጉንጉን የዘለለ የማትሰራ የገጠር ልጅ ሁላ ሳትቀር በጋዜጠኛ ምላሷ አዋክባ አሳምና ትነቅሳታለች። የጀርባዬን እና የቂጤን ንቅሳት ግማሹን መጀመሪያ የገባች ጊዜ የተቀረውን ቀለም ያልደረሰው ቦታ እየፈለገች ሁለተኛ ስትመለስ የነቀሰችኝ እሷ ናት።) የዛን ቀን መታሰሯን ሰምቼ የበረደው ልቤን ይዤ ስባዝን አምሽቼ ስገባ ጎንጥ ከእንቅልፉ ነቅቶ በር ከፈተልኝ። በረንዳው ጠርዝ ላይ ተቀምጬ እያየሁት በህይወቱ ምንም ግድ የሚሰጠው አይመስልም ነበር። «አንተ ግን ደስተኛ ነህ?» አልኩት በመገረም እያየሁት! እንደገመትኩትም ቁልል ብሎ «ፈጣሪ ይመስገን!!» አለኝ «ምን ማለት ነው ፈጣሪ ይመስገን? መልስኮ አልሰጠኸኝም!! ነህ አይደለህም? ነው ጥያቄው ! ነኝ ወይም አይደለሁም! ነው መልሱ» «ምን ለየው!! ፈጣሪ ይመስገን ማለቴ ደስተኛ በመሆኔም አይደል?» ብሎ አሁንም መልስ ያልሆነ መልስ ይመልስልኛል። «አንተ ግን መቼ ነው ቀጥተኛ ወሬ የምታወራው? ምናለ አሁን ነኝ ወይ አይደለሁም ብትል!! ምንህ ይቀነሳል?» «እሽ ካሻዎት! አዎን ደስተኛ ነኝ!! ምነው? እርሶ ደስተኛ አይደሉም እንዴ?» አለኝ መልሴ የጨነቀው አይመስልም። እኔ ግን ውስጤ መከፋቴ ሞልቶ ስለነበር መተንፈስ ለማልፈልገው ሰው ገነፈለብኝ። «ደስታ ምን እንደሚመስል ስለማላውቅ ደስ ቢለኝም ማወቄን እንጃ!! አላውቅም!! ደስታ ማለት መሳቅ ከሆነ ስቄኮ አውቃለሁ። በህይወት ውስጥ ምን ያህሉን ፐርሰንት ደስተኛ ስትሆን ነው ደስተኛ ነኝ የሚባለው? እኔእንጃ! አላውቅም ደስተኛ ሆኜ ማወቄን! ሰው የሚፈልገው ሁሉ ኖሮት እንዴት ደስታ አይኖረውም አይደል?» አልኩት እና ጎንጥ መሆኑን ሳስብ ትቼው ገባሁ!! «የዚህን ቀን አንጀቴን አላወስሽው!!» አለኝ አሁን ሳቅ ብሎ! «ከዛ ወዲህ ያለውን አላውቅም በጣም ብዙውን ቀን ታናድጅኛለሽ ለራሴ በቃ እተዋለሁ ይህን ስራ እላለሁ መልሼ ግን ያቅተኛል። የልጄ እናት በደንብ ስለምታውቀኝ ጠረጠረች። እየለገመ ነው እንጂ ይህን ያህል ጊዜ ምንም ፍንጭ ሳያገኝ ቀርቶ አይደለም ብላ ሰው ልትቀይር ነበር። ከዛ በላይ ምክንያት ደርድሬ ብቆይም አንች ፍቅሬን የምታይበት ልብ አልነበረሽም እና ደጅሽ መክረሜ ትርጉም አጣብኝ ለዛ ነው ልሄድ የነበር!! እንደው ጥሎብሽ ስታይኝ ትበሰጫለሽኮ!! ምን በድዬ ነው ግን እንዲያ የምትጠይኝ?» «ኸረ አልጠላህም!! አላውቅም!! እሙ ስለምትወጂው ነው እንደዛ የምትሆኝው ነው ያለችኝ!» ስለው አይኑን አፍጥጦ ሲያየኝ አብራራሁ «ከፀብ ውጪ የምታውቂው ፍቅር ስለሌለ ፍቅርሽን የምትገልጪበት መንገድ ነው የምትናደጂውና የምትቆጭው አለችኝ! እሷ ናት ያለችኝ!» አልኩኝ!! ሳቅ ብሎ ዝም ተባብለን እንደቆየን እህሉ ሳንነካው መቀዝቀዙን አየን!! ሁለታችንም የመብላት ፍላጎት አልነበረንም!! እኔ የምበላው መዓት ነገር አቀብሎኝ እንዴት ነው እህል የማስብ የነበረው። ልክ እንደቅድሙ አጠገቤ መጥቶ ተቀመጠ እና አገጬን ከፍ አድርጎ አይኖቼን እያየኝ። «መድሃንያለም ምስክሬ ነው! የደበቅኩሽ የለኝም!! ከፍቅርሽ ውጪ አንቺጋ ያኖረኝ ምንም ሰበብ የለም!! አሁን ሁሉን አውቀሻል!! አልሻህም እሄዳለሁ ካልሽኝም በግዴ የእኔ አላደርግሽም!! ብትተይኝም ከአፌ የሚወጣ ሚስጥር የለም!! በልጄ እምልልሻለሁ!! እ? ዓለሜ? ፍቅሬ ከጥላቻሽ ከበለጠ ንገሪኝ!! እሽ በይኝና የኔ ሁኝ በደልሽን በፍቅር እንድትረሽ አደርግሻለሁ!!» ሲለኝ ለተወሰነ ደቂቃ የእነሱ ወገን እንደሆነ ረስቼው እንደነበር አስታወስኩ። አባቴ ከወንድሙ ገዳዮች አንዱ ወይም አዛዡ እንደነበር አውቆ እንዴት ቻለበት ማፍቀሩን! «ስትጠፋብኝ ስላንተ መረጃ እንዲያቀብሉኝ አድርጌ ነበርኮ!!» አልኩት የተጠየቅኩት ሌላ የምመልሰው ሌላ እንደሆነ እየገባኝ « እየተከተሉሽ ነበር። ከኪዳን ጋር ከተማ ስትገቡ እንዴት እንደሆነ መረጃ ደርሷቸው ነበር። ኪዳን በሰላም እንዲወጣ እኔ ጣልቃ መግባት ነበረብኝ!! (ፍጥጥ ብዬ ሳየው) ምንም አልሆንኩም!! » አለኝ እጁን ከአገጬ አውርዶ «ምንድነው ያደረግከው?» አልኩት «ብዙም አይደል! ዋናው ኪዳን መውጣቱ ነበር ያንቺ እዳው ገብስ ነው!!» አለኝ «ይሁን ንገረኝ ምንድነው ያደረግከው?» ብዬ ጮህኩ «ከረፈደ ነው መኪና እንደተመደበባችሁ የሰማሁት!! ምንም ማድረግ የምችለው ስላልነበር መኪናውን ተጋጨሁት!! ምንም አልሆንኩም!! ማንም አልተጎዳም!! ትራፊክ መጥቶ ስንጨቃጨቅ እናንተ ተሰውራችኋል። እኔን ተከትለው ሊደርሱብሽ ስለሚችሉ ካንቺ አካባቢ መጥፋት ነበረብኝ! ለጊዜው የሚያቆሙ ይመስለኛል። ሌላ መላ እስኪያገኙ!! አንቺን መከተል ካላቆመች ለልጄ ማንነቷን እንደምነግራት ነግሪያታለሁ!! መረጃዎች እንዳሉኝ ስለምታውቅ ለጊዜው አትሞክረውም!! ስጋታቸው አሁን ለምርጫው የሆነ ነገር ታደርጊያለሽ ብለው ፈርተው ነው!! የምታደርጊውን እስክታስቢ ፋታ ይኖርሻል!! (ትንሽ ፋታ ወስዶ)መች ነው ግን አንቺ የምታምኝኝ? ምን ባደርግ ነው ትቶኝ ይሄዳል ወይ ይከዳኛል ብለሽ የምታስቢውን የምታቆሚው?» አለኝ «አላውቅም!! እኔ እንዲህ የምወደው ነገር ኖሮኝ አያውቅም! እንዲህ የተሸነፍኩለት ነገር ኖሮኝ አያውቅም!! እንዲህ የተንሰፈሰፍኩለት ሰው ኖሮኝ አያውቅም!! ባጣው የምሞት መስሎ የተሰማኝ ሰው ኖሮኝ አያውቅም!! የምወደውን ስጠብቅ የኖርኩት በመጠራጠር እና በጉልበት ነው!! ማመን እንዴት እንደሆነ አላውቅማ!!» አልኩት አስቤ የተናገርኩት አልነበረም!! ፈገግ ብሎ ፊቱን አዞረ እና መልሶ በተመስጦ ሲያየኝ ቆይቶ ሁለቱን እጆቹን በአንገቴ ዙሪያ ልኮ አንገቴን እንደመደገፍ ፣ ከአገጬ ቀና እንደማድረግ አድርጎ ከንፈሩን ከንፈሬ ላይ አሳረፈው። ስሞኝ እጆቹ እዛው እንዳሉ ከመልሴ በኋላ መልሶ እንደሚስመኝ ነገር «ያ ማለት ምን ማለት ነው? አለሽልኝ ማለት ነው? እ? ንገሪኛ?» ከንፈሩ ከንፈሬን ከነካው በኃላ እንኳን ዘሩን ያለሁበትን የማላስታውስበት ስካር ውስጥ ከቶኝ ነው የሚጠይቀኝ? በጭንቅላቴ ንቅናቄ አዎ!! አልኩት!! ከንፈሩን እቦታው መለሰው!! ......... አሁን ጨርሰናል!!..........
Show all...
«እሺ ታዲያ እንዴት ከእነርሱ ጋር መስራት ጀመርክ?» አልኩት የነገሩን ጅማሬ ውል እየፈለግኩ «ተዚያማ ትልቄ ሲሞት እምዬን ማስተዳደር በኔ ላይ ወደቀ። ያሸተ እህላችንን በእሳት ስላጋዩት ለከርሞ የሚቀመስ አልነበረም!! ቀዬው በጠኔ ደቀቀ። ይህኔ እምዬን ለወንድሟ አደራ ብዬ ወታደር ቤት ገባሁ!! ከዛ በምልክላቸው ፍራንክ እንደሆነው እንደሆነው አድርገው ከራረሙ።ወታደር ቤት ዓመታት ከቆየሁ ኋላ ወደቀዬ ተመልሼ መኖሪያዬን ቀለስኩ!! ምሽት አገባሁ ልጄን ወለድኩ!! ሚሽቴ ከ9 አቁማ የነበረውን የቀለም ትምህርት የመቀጠል እና በትምህርቷ ከፍ ያለ ቦታ የመድረስ ምኞቷ ትልቅ ስለነበር ከተጋባን ኋላ አስተምራት ነበር። የ12 ክፍል ትምህርቷን ስትጨርስ ሸጋ ውጤት አመጣች!! አዲስአበባ ዩንቨርስቲ ለትምህርት ተመደበች እና የ6 ዓመት ጨቅላ ልጃችንን ትታ መምጣት ግድ ሆነ!! ገና ከወራት ግን የልጇ ናፍቆት አቅቷት ተመልሳ መጣች። እሷ ከህልሟ አጓጉል ከምትሆን ምናባቱ ያገኘሁትን ሰርቼ እኖራለሁ ብዬ ልጄን ምሽቴን ይዤ አዲስአበባ ገባሁ!! ስራውንም ሳላማርጥ እየሰራሁ ባጀሁና ትንሽ ስደላደል እምዬንም አመጣኋት እኔጋ!! እንዳያልፍ የለም መቼም እንዴትም እንዴትም እሷ ተመረቀች። ይሄኔ እሷ ናት ይሄን ስራ በሰው አገኘሁልህ ብላ ደሳለኝጋ ያገናኘችኝ። እሷ ተመርቃ ከፍ ያለ ስራ ይዛ ከፍ ካሉ ሰዎች ጋር መዋል ስትጀምር ከእኔጋ መኖሩን እየተጠየፈችው መጣች። የምለብሰው አይጥማት ፣ አካሄዴ አይጥማት ፣ የማወራው አይጥማት …… ትምህርት ሚሽቴን ቀየራት ….. ትምህርት ሚሽቴን ነጠቀኝ!!» አለ ከደረቱ ቀና እንደማለት ብሎ በቁጭት ነገር የሆነ መፅሃፍ ትረካ ነገር በሬድዮ እየሰማሁ ያለሁ ነው እየመሰለኝ ያለው። «ኋላማ ትዳራችን እንደማይሆን ሆነ። አቶ ደሳለኝ ጋር በጥበቃ ሰርቼ የማገኛት ገንዘብ ለሚስቴ ከራሷ ደመወዝ ጋር ተደምሮላትም የሚበቃትን ኑሮ አላኖር አለኝ። ኋላ ላይ አቶ ደሳለኝ በሷ ጥቆማ የግሉ ጠባቂ አደረገኝ። መድሃንያለም በሚያውቀው የዚህን ጊዜ ሁለቱ የሆነ ነገር ይኑራቸው የማውቀው የለኝም!! አይኔ ስር የሚሰሩትን ቆሻሻ ስራ አያለሁ!! ንፁህ ሰው አግተው ሲዝናኑ አያለሁ!! ቤቴን አቆም ብዬ አንገቴን ደፋሁ። ሰውየው <ልዩ ጠባቂዎቼ > የሚላቸው አሉት!! ስራው ጥበቃ አይደለም! ቆሻሻ ስራዎችን መስራት ነው!! የሚፈልገውን ሰው ከመሰለል እስከማገት ፣ መረጃ መስረቅ ፣ …… እነርሱን ተቀላቀል ሲለኝ አሻፈረኝ አልኩ። ሚሽቴ ብዙ ብር የሚያስገኝልኝን ስራ እንቢ ማለቴን ደሳለኝ እንደነገራት ነግራኝ ስትቆጣ የዚያኔ እምነቴ ሙሉ ስለነበር አልጠረጠርኳትም!! ብሩ ቢያስፈልጋት ነው ብዬ ስራውን ተቀበልኩ!! እሷን ካስደሰተልኝ እና በሷ ፊት ሞገስ ከሆነኝ ምናባቱ ብዬ ገባሁ!! ብዙ ወዳጅ አፈራሁ!! ስለከተማ ሰው ብዙ አወቅኩ!! እንዲያ ህሊናዬን አቆሽሼ ብዙ ብር ባመጣላትም ሚሽቴን አላቆየልኝም!! ፍታኝ አለችኝ!! በግድ ይዤ ላቆያት አልችል ለቀቅኳት።» «ትወዳት ነበር!» «ሚሽቴ አይደለች እንዴ? ቤቴ እኮ ናት የልጄ እናት! እንዴት አልወዳት?» አለኝ እንደመቆጣት ብሎ «አይ እንዴት ሆነልህ ብዬ ነው! ባለፈው ሳያችሁ የሌላ ሴት ሚስት ሆና ምንም የመሰለህ አትመስልም ነበር።» «ያልፋልኮ! ያልፋል! ቅናቱም ፣ ህመሙም ፣ እህህ ማለቱም ያልፋል!» «እና ደሳለኝን ካገባችው በኋላ እሷን እያየህ ስራ እዛው እንዴት ቀጠልክ?» «እኔና እሷ ከተፋታን ኋላ ትንሽ ቆይቶ እምይ በጠና ታመመችብኝና ለህክምና 10 ዓመት ብሰራ የማላገኘው ፍራንክ ተጠየቅሁ!! አቶ ደሳለኝ ብሩን ሊያበድረኝ እና በምትኩ ለ3 ዓመት የታዘዝኩትን ልሰራ ያቀረበልኝን ሀሳብ ለማለፍ ምርጫዬ የእምዬ ህይወት ነበርና ፈርሜ ገባሁበት!! እምዬን አዳንኩበት እኔ የማልወጣው ሀጥያት ውስጥ በየቀኑ ሰመጥኩ እንጅ!! ከዚያማ የልጄ እናት የአለቃዬ ሚስት ሆና መጣች። ትቼ አልሄድ ቃሌ ፣ ፊርማዬ ….. አልቀመጥ ሽንፈት ፣ ቅናት ፣ መከዳት ፣ መታለል ፣ መዋረድ አንገበገበኝ። ያልፋል አልኩሽ አይደል? አለፈ። እሷን ወይ አብራኝ እያለች አላውቃት ይሆን ወይ ከትምህርቱ በኋላ ተቀይራ : ጭራሽ የማላውቃት ሰይጣን ሴት መሆኗን አለቃዬ ስትሆን አወቅኩ። ለእኔ እንዲያ ብትሆንም ለልጄ ወደር የሌላት እናት ናት!! ልጄ በቋሚነት እኔጋ ብትሆንም ከአርብ እስከእሁድ እሷጋ ትሆናለች። አብረሽኝ ሁኝ ብትላት ልጄ እኔን መረጠች» አለ ኮራ ብሎ በፈገግታ ቀጥሎ «አንቺጋ ስቀጠር ያገናኘን ሰውዬ ያንቺ ወዳጅ ቢሆንም በድብቅ የእነርሱ ወዳጅ ነው!! ያው ዘበኝነት ገብቼ የፈለጉትን መረጃ እንዳመጣ ነበር። ልጄ የታመመች ጊዜ » ብሎ ጊዜውን በማስታወስ ነገር ፍዝዝ አለ። «ልክ ያሁን ያህል አስታውሳለሁ። በረንዳው ላይ ተቀምጠሽ! «ቤተሰብ ነኝ ብዬ ከቀበሌ የሆነ ወረቀት እናሰራ እና የእኔ ከሆናት የኔን ኩላሊት እሰጣታለሁ!» ስትይ ነው ለመጀመሪያ ጊዜ እንደስራዬ ሳይሆን እንደሰው ያየሁሽ!! የዚያኔ ነው ለምን እንደሆን እንጃ ስላንች ማወቅ ናፈቅኩ። እናቷ ያንች ኩላሊት መስማማቱን ስነግራት አይሆንም አለች። ፈጣሪ ደግ ነው ሌላ ሰው ተገኘና ልጄ ዳነችልኝ! በሰው በሰው ሳጠራ ማን እንደሆንሽ ደረስኩበት። ስራዬን ልልቀቅ ካልኩሽ በኋላ ለእነርሱም ሄጄ ሌላ ስራ እንዲቀይሩልኝ ጠየቅኳቸው። በእኔ ምትክ እንዲገባ አናግረሽው የነበረውን ሰውዬ እነርሱ ናቸው የላኩልሽ!! የሰው ተፈጥሮ ያልፈጠረበት የሰይጣን ቁራጭ አረመኔ ነው!! ምንም እንኳን የምጠላው ጎሳ ፣የወንድሜ ገዳዮች ልጅ ብትሆኝም ለልጄ ስትይ አካልሽን ልትሰጭኝ ስስት አልነበረብሽም እና ለዚያ አውሬ አሳልፌ ልሰጥሽ አልሆነልኝም!! መልሼ ሀሳቤን አንስቻለሁ እሰራለሁ በቃ ብዬ ተመለስሁ!!» ብሎ ነግሮኝ እንደጨረሰ ነገር ዝም አለ።
Show all...
«አባቴንኮ የገደሉብኝ ያንተ ወገኖች ናቸው፤ ማን ያውቃል ወይ አጎትህ ወይ አባትህም ሊሆን ይችላል፤ እናቴን መሳሪያ ይዘው የደፈሩብኝኮ እነዛው ያንተ ወገኞች ናቸው፤ ልጅነቴን ፣ወጣትነቴን ፣ ጉልምስናዬን ያመሳቀሉብኝኮ ያንተ ወገኖች ናቸው ፤ አምርሬ ስጠላቸው እና ላጠፋቸው ስመኝኮ ነው የኖርኩት። በህይወቴ አንድ ጥሩ ነገር ቢከሰት ፣ አንዴ ፍቅርን ባገኝ ፣ አንዴ ብሸነፍ …… እሱም የእነሱ ወገን ይሁን?» እያልኩት ውስጤኮ ቁጭት ነው የሞላው ቃላቶቹ ከአፌ ሲወጡ ግን እንባዬን አስከትለው ሀዘን የተሸከሙ ነበሩ። «አንዴ ሁሉን ስሚና ፍረጅኝ!! ሰምተሽ አሻፈረኝ ከአሁን ፍቅሬ ያለፈ በደሌ ይበልጣል ካልሽ ምን ማድረግ ይቻለኛል? ልብሽ ያለሽን አድርጊ!! እ? እ ዓለሜ?» ከፊት ለፊቴ ተነስቶ አጠገቤ ወንበር አድርጎ ተቀመጠ። እንዳያቅፈኝም እንዳይነካኝም የቸገረው መሰለ። እንዳየው በዓይኖቼ ዓይኖቼን ያሳድዳል። «እሺ ንገረኝ! ሁሉንም ልስማህ!! የእነሱ ወገን መሆንህን ግን የትኛው ታሪክ ይቀይረዋል?» «ፍቅር! ፍቅር ይቀይረዋል! ፍቅር ጎሳ ብሄር ሀገር የለውምኮ ዓለሜ? እኔስ አስቤ እና አቅጄ በፍቅርሽ የወደቅኩ ይመስልሻል? ላንች እስከተንንበረከኩባት ሰዓት ድረስ እኔምኮ ያንቺን ጎሳ እንገሸገሸው ነበር። ሁሉም ቤትኮ እሳት አለ ዓለሜ!? ከጥላቻዬ አስበልጬ ወድጄሽ ነው! ከቂሜ አስበልጬ ወድጄሽ ነው፣ ፍቅርሽ ልቤ ሲሞላ መበደሌን ይቅር ብዬ ነውይ!» ብሎ ጀርባዬ ላይ አንድ እጁን ደገፍ አደረገ። «የአባትን ሞት ያህል በደል አልተበደልክማ! የእናትን መደፈር ያህል ቂም አልያዝክማ! እድሜህን ሁሉ የቀማህ ጥላቻ አልጠላህማ!!» አልኩት ማልቀሴን ሳላቆም! ከተቀመጠበት ተነስቶ እንደገና ወደነበረበት ተመልሶ «ህም!!» አለ እና በረዥሙ ተንፍሶ ቀጠለ። « እኮ የእኔ ህመም ይተናነስ እንደው ሰምተሽ ፍረጅኛ!! አብይ ህፃን ሳለሁ ነው የሞተው!! እንደመጎርመስ ብዬ ድምጤ የሻከረ ጊዜ እምይ ታማ ካልጋ ዋለች። ህመሟ እንዲህ ነው ሳይባል ወሰድ መለስ እያደረጋት እድሜ ቆጠርን!! እኔ እና ትልቅ ወንድሜ ነበርን እርሻውኑም ከብቱንም ብለን እምዬን የምናኖራት። ትልቄ እንደታላቅነቱ ሀላፊነት አለብኝ ብሎ ትምህርቱን ተወው!! እኔ በቀለሙ ትንሽ ፈጠን ያልኩ ስለነበርኩ እኔን ከትምህርት እንዳልጎድል አገደኝ። 10 ክፍል ስማር ሳለሁ አንድ እለት ተማሪ ቤት እየተማርን ሳለ ከተማው በጩኸት ሰከረ። በላይ በላያችን እየተረጋገጥን ብቅ ስንል ከተማው ይንቦለቦላል። ያልነደደ ቤት ያለ አይመስልም ነበር። ሁሉም የራሱን ቤተኞች ደህንነት ሊያጣራ ሲሮጥ መደሚጤሰው ከተማ ገባ። የምማርበትን ደብተር በትኜ ስበር ወደቤት ሄድኩ። በመንገዴ ከከተማው ግማሽ የሚያህለው ቤት እየነደደ መሆኑን ሳይ አልጋ ላይ የዋለች እምዬን እሳት በላብኝ ብዬ ነፍሴ ስትጨነቅ ደረስኩ። ቤታችን ሲነድ ደረስኩ። እምይ በደረቷ ስትሳብ ከበሩ ደርሳ ነበር።» ብሎኝ ፊቱ በሀዘን ተውጦ ከንፈሩን ነከሰ። « እሳት የጀመረው ቀሚሷን አፈር በትኜ አጥፍቼ እሷን በክንዴ ላይ አቅፌ ከጎረቤት የነበረ እሳት ያላገኘው የወንድሟ ቤት አስቀምጫት ለወንድሜ ሚስት ሀደራ ብዬ እንዲህ ካለ ግርግር መሃል አይጠፋም እና አንዳች ነገር እንዳይሆንብኝ ብዬ ወንድሜን ፍለጋ ወጣሁ። ሰፈርተኛው እሳቱ የባሰ እንዳይዛመት ሊያጠፋ ደፋ ቀና ይላል። ደመኞቻችን እጃቸው የደረሰውን ታህል ቤት አንድደው ፣ የደረሰው እህል ላይ እሳት ለቀውበት ወደገበያ መሃል መግባታቸውን ከመንገድ ስሰማ በአሳላጭ ቅያስ በርሬ ደረስኩ። (ክብድ ያለው ትንፋሽ ግንባሩን አኮሳትሮ ተነፈሰ እና ቀጠለ) ያንች ዘመዶች ገበያው ዳር የተፋለሟቸውን የከተሜውን ወንዶች ሬሳ አጋድመው ሲጨፍሩ ደረስኩ። ትልቄ ለስራ ከለበሰው ቡት ጫማውጋር በእጁ የአብዬን ጠብመንጃ እንደያዘ ተዘርግቷል።» ሲለኝ ሳላስበው «ሞተ?» አልኩኝ «እህ!! (ጭንቅላቱን ወደላይ እና ወደታች እየነቀነቀ) እንደዋዛ ድፍት ብሎ ሞተ። አድብተው እንደሌባ አጥቅተውን እንደጀግና እየጨፈሩ መሪያቸውን ትከሻቸው ላይ ተሸክመው በሽለላ እያወደሱት ያጋደሙትን ሬሳ ሲዞሩ ቆይተው ከተማውን ለቀው ወጡ!! ድምፃቸው ከጆሮዬ ብዙ ጊዜ ዋለ - የወንድ ዋርካ የጀግና አድባር የአምሳል አባት ባለዝናር …… » እሱ ድሮ በልጅነቴ ለአባቴ ሲገጠም የማውቀውን ግጥም በቃሉ ወረደልኝ። እኔ ግን የአምሳል አባት ከሚለው በኋላ ያለውን አልሰማሁትም!! ሰውነቴ ቀዘቀዘ። ሁሉም ቤት እሳት አለ ያለኝ ይሄን ነበር? ታዲያ ይሄን እረስቶ ወዶኝ ነው? ሊበቀለኝ ፈልጎ እንጂ!!! «እኔጋ መቀጠርህ ከቀዬህ ጋር የሚያያይዘው ነገር የለም አላልከኝም?» አልኩት ሳላስበው «የሚያያይዘው የለም!! ያ ሰው አባትሽ መሆኑን ያወቅሁት ራሱ አንቺጋ ከገባሁ ከወራት በኋላ ነው!!» አለኝ ረጋ እንዳለ። ዝም አልኩኝ!! «ታምኚኛለሽ? እንድዋሽሽ የሚያደርግ አንዳች ምክንያት የለኝም! አለመንገር እችል አልነበር? የምፈልገው በቀል ከነበር እጄ ላይ ነበርሽኮ ዓለሜ!! በብዙ መንገድ ላደርገው እችል ነበር። ለእነደሳለኝ መረጃውን እስኪያገኝ ነው ያልተበቀለኝ ብለሽ ታስቢ ከሆነ ልንገርሽ!! ሁሉንም አውቃለሁ!! ባንክ ያስቀመጥሽውን ኮፒ ፣ እሙጋ ያስቀመጥሽውን ፣ ሴትየዋጋ ያለውን!! እቤትሽ መታጠቢያ ቤት መስታወት ጀርባ ያለ ድብቅ ካዝናሽ ውስጥ ያሉ መረጃዎችሽን፣ ኮዱን ልነግርሽ እችላለሁ። የቀረኝ አለ? ሁሉን ደርሼበታለሁ!!! በቀል ከነበር ዓላማዬ እጄ ላይ ነበርሽ!! ታምኚኛለሽ? እርግጥ ነው ብዙ ጥላቻ እና ቂም ነበረኝ ግን የበቀል ሰው አልነበርኩም!!» ሲለኝ የማስበው ተምታቶብኝ የነገረኝን ትርጉም ልሰጠው እታገላለሁ!! ይሄን ሁሉ ካወቀ ምንድነበር የሚሰራው በሬ ላይ? ያሰብኩትን ያወቀ ይመስል «አላውቅም!! ለምን እንደቆየሁ አላውቅም!! መች በፍቅር እንዳየሁሽ አላውቅም!! ብቻ አንቺን መጠበቁን ወደድኩት!! የዚያን ቀን መሄዴ ነው ስልሽ ከልቤ ነበር!! ወረቀት አኑሬልሽ ልሄድ ነበር። እውነታውን ፅፌ አኑሬልሽ ልሄድ ነበር። እንደማይባል እንደማይባል ብለሽ ታች ላይ አድርሰሽ ሰድበሽኝ ወጣሽ!! ስዘገጃጅ ፖሊስ በሩን አንኳክቶ መመታትሽን ነገረኝ!! ልቤ ሁለት ሆነ። ከሆስፒታል እስክትወጪ ታግሼ እቤትሽ ስትገቢ ጠብቄ ልሂድ ብዬ ጠበቅኩ!! ስትመጭ ጭራሽ ሌላ ሰው ነበርሽና ትቼሽ መሄድ አልቻልኩም!!» (የዛን ቀን ያለውን ቀን እኔ እየከተለኝ የነበረ መኪና አስተውዬ <የሆነ ሰው እየተከተለኝ ነው!! የተለየ ነገር አስተውለሃል? በንቃት ተከታተልልኝ> ልለው ስወጣ ነበር ስራዬን መልቀቄ ነው ያለኝ። ምን እንደዛ እንዳናደደኝም አላውቅም!! እሱ ክብሩ ከሚነካ ሞቱ እንደሆነ አውቃለሁ ግን ተናገርኩት!! ስወጣ <ጥርግ በል! ያንተ ቢጤ 10 አመጣለሁ> ማለቴን አስታውሳለሁ።
Show all...
የመኖር አካፋይ የመሞት ሲሶ መንገድ መሃል........ ክፍል ሰላሳ (የመጨረሻ ክፍል) (ሜሪ ፈለቀ) ብዙ ጥያቄዎች ስለእርሱ እያብሰለሰልኩ አልነበር? ቅድም ተበሳጭቼበት ባገኘው የምጮህበት ሲመስለኝ አልነበር? ታዲያ ገና ሳየው እንኳን ልቆጣ የማወራውም የማስበውም ጠፍቶኝ አባን ጉልበት ስሜ እሱን እጁን ጨብጬ ተቀመጥኩ። እየመላለስኩ <ደህና ኖት> ስል ቆየሁ አባን!! «ተገናኛችሁም አይደል? እኔ የምፈፅማት ጉዳይ አለችኝ!» ብለው ተነሱ። እሳቸው ከአጠገባችን ከራቁ ከደቂቃዎች በኋላ እንኳን ዝም ተባብለናል። የሆነ በነዚህ ባልተገናኘንባቸው ቀናት በመሃከላችን መራራቅ የተፈጠረ ዓይነት ስሜት አለው። «ቸር ባጀሽ?» አለኝ እኔ ቀድሜ እንዳወራ ሲጠብቅ ቆይቶ! ቸር ነው የባጀሁት? እሱ ምን ሆኖ እንደዘጋኝ የሀሳብ ካብ ስከምር እና ስንድ እንቅልፍ እንቢ ብሎኝ የተሰቃየሁት ፣ እወድሻለሁ እያለ አንሶላ አብሮኝ ሲጋፈፍ የነበረው ሰው ከምድረገፅ ሊያጠፋኝ እስኪሻ አምርሮ የሚጠላኝ ሰው ሆኖ ማግኘቴ ፣ አሁን ወደዚህ እየመጣሁ በብዙ ባዶነት መዋጤ …… ይሄ ቸር ከተባለ አዎ ቸር ነው የባጀሁት!! «መሄድ ነበረብኝ!!» አለኝ እኔ ምንም ሳልጠይቀው! ዝም አልኩ! «አናግሪኝ እንጅ ዓለሜ?» ሲለኝ ኩርፊያዬን ትቼ <እቀፈኝ> ማለት ነበር ያሰኘኝ ደጀ ሰላም ሆንኩ እንጂ!! «ምን ልበል? መሄድ ኖሮብኝ ነው አልከኝ አይደል? <የት? ለምን ሄድክብኝ? > የማለት መብት አለኝ? ከመሄድህ በፊት ልታሳውቀኝ እንኳን ግድ ያልሰጠህ አያገባትም ብለህ አይደል? ያስኬደህ ነገር ከእኔ በላይ ያንተን ትኩረት የሚሻ ነገር ቢሆን አይደል ሀሳብ አሳቅፈኸኝ የጠፋኸው? ዝም ከማለት ውጪ ምን አቅም አለኝ?» ስለው በጣም ስፍስፍ ባለ አስተያየት አይቶኝ ከተቀመጠበት ተነሳ «ተነሽ እንሂድ?» አለኝ «የት?» «እኔእንጃ! ቁጭ ብለን የምናወጋበት ቦታ!!» ሲለኝ ለምንድነው ከተናገረው ዓረፍተ ነገር የተለየ የገባኝ? ማውጋቱንማ እያወጋን አይደል? እየነካሁሽ፣ እያቀፍኩሽ እየሳምኩሽ የማወጋሽ ቦታ እንዳለ ነው የሰማሁት። ተነሳሁ!! ደጁን ስመን ወጣን እና መኪናዬን ወዳቆምኩበት ልሄድ ስል ታክሲ ይዘን እንሂድ ሲል ለምን ብዬ አልጠየቅኩም!! «አባጋ እንደምመጣ በምን አወቅህ?» «ጭንቅ ጥብብ ሲልሽ የምትመጭ እዚሁ አይደል? ደሞ አርብ አይደል? አርብ አርብኮ ለወትሮም አባጋ ታዘወትሪ ነበር!» ከዋናው መንገድ ደርሰን ከቆሙት ላዳዎች አንዱን ወደሱሉልታ ይዞን እንዲሄድ አናግሮት ከኋላ ወንበር ገባን። መንገድ ስንጀምር እጁን በትከሻዬ አሳልፎ አመልጠው ይመስል ተሽቀዳድሞ ስብስብ አድርጎ ደረቱ ላይ አደረሰኝና ጭምቅ አድርጎ አቀፈኝ። «እኔ ላይ ሙሉ መብት አለሽ!! የልቤ አዛዡ አንቺ አይደለሽ? ያንቺን ያህል እኔ እንኳን መች በገዛ ልቤ አዝበታለሁ? አያገባሽም ብዬ አይደለም ሳልነግርሽ የጠፋሁ።» አለኝ። ካቀፈኝ በኋላ ምክንያቱን ቢነግረኝም ባይነግረኝም ግድ አልነበረኝም። ተናድጄ የነበረውን ፣ ከፍቶኝ የነበረውን ፣ ተቆጥቼ የነበረውን ፣ መጠየቅ እፈልግ የነበረውን ……… ሁሉንም ረሳሁት!! እጄን በሆዱ ላይ አሳልፌ ወገቡን አቀፍኩትና በቃ ዝም አልኩ!! እንደዚህ ታቅፌ አላውቅማ!! ደረት ከዝህች ዓለም ውጥንቅጥ መጠለያ ቤት መሆኑን አላውቅማ!! የሰው ልብ ማዘዝ እንደሚቻል አላውቅም ነበራ!! ብዙዙዙዙ ከፍቅር ጎድዬ ነበራ!! ሲጠፋብኝ ሳቄንም ሀሳቤንም ይዞብኝ የጠፋ ፣ ሲመጣልኝ ዓለምን ያስጨበጠኝ ሰው ኖሮኝ አያውቅማ!! በዚሁ ሱሉልታ አይደለም ከሀገር ይዞኝ ቢጠፋ ፣ እንዲሁ ደረቱ ላይ በክንዱ ታቅፌ ብቻ ብዙ ዓመት መሽቶ በነጋ!! ያለፈው ዘመኔ ፍቅር ያልጎበኘው ምነኛ ባዶ ነበር? ፀጉሬን ሳም አድርጎ «እየተከተሉሽ ነበር!! …… » ብሎ ሊቀጥል ሲል «ዝም ብለህ እቀፈኝ!! በኋላ ትነግረኛለህ!! አሁን ዝም በለኝ!!» አልኩት ከእርሱ ፍቅር ውጪ ቢያንስ ሱሉልታ እስክንደርስ መስማት የፈለግኩት ነገር የለም!! ክትትል ፣ ፀብ ፣ በቀል ፣ ሴራ ….. የት ይሄድብኛል ሲሆንብኝና ሳደርገው የኖርኩት አይደል? እንዲህ የታቀፍኩት ግን ዛሬ ብቻ ነው! እንዲህ ልቆይና የሱን የልብ ምት የእኔን የልብ ፈንጠዝያ ልስማ!! ከዛ በኋላ የሚከተሉኝ ሰዎች እንኳን አጊንተው ቢገድሉኝ ታቅፌ ነበር ፣ የእናትን ሞት በሚያስረሳ እቅፍ ታቅፌ ነበር፣ የበረደው ልብ በሚያሞቅ እቅፍ ታቅፌ ነበር፣ መኖር ጀምሬ ነበር። «እሽ» ብሎ ባላቀፈኝ እጁም ደርቦ አቅፎኝ አንዴ ጨመቅ አንዴ ላላ ሲያደርገኝ ፣ አሁንም አሁንም ፀጉሬን ሲስመኝ ደረስን። ልጁን መንገድ እንደሚያሻግር አባት እጄን ይዞኝ የገባው ሪዞርት ውስጥ ካሉት ትንንሽ ጎጆ ቤት መሳይ አንደኛው ጋር ገብተን ፊት ለፊት ለፊት ለፊት ተቀመጥን። ጎጆ ቤትዋ ውስጥ እኛ ከተቀመጥንበት ጠረጴዛ በተጨማሪ ሌላ አንድ ጠረጴዛ ቢኖርም ሰው የለውም ነበር እና እኔና እሱ ብቻ ነበርን። አስተናጋጁ የሚታዘዘውን ጨራርሶ እንዲሄድልን አጣድፈን አዘን ሸኘነው። መብት አለሽ ተብዬ የለ? ሁለቱንም እጄን ጠረጴዛው ላይ ዘርግቼ እንዲይዘኝ ሰጠሁት። በሁለቱም እጆቹ ያዘኝ። «እሺ አሁን ንገረኝ!!» አልኩት በስስት የሚያዩኝን አይኖቹን(መሰለኝ) እያየሁት «ከወየት ልጀምር?» «እኔ እንጃ!! ማነህ? ምንም ሳይቀር ስላንተ ማወቅ እፈልጋለሁ!» ስለው ዓይኖቹ ውስጥ መከፋት ነገር ያየሁ መሰለኝ ወይም ፍርሃት እኔንጃ «እሽ! ምንም ሳላስተርፍ አወጋሻለሁ!! ግና የቱ ነው ማን መሆኔን የሚገልጥልሽ? ያለፈ ህይወቴ? የመጣሁበት ብሄር ጎሳዬ? አባት አያት ቅድመአያቴ? እምነቴ? የእስከዛሬ በጎ ምግባሬ ወይስ ሀጥያቴ? ወይሳ አሁን የሆንኩት እኔ? በየትኛው ነው አንት ይህ ነህ ብለሽ ምትቀበይኝ?» አለኝ ያለፈው ህይወት አድካሚ እንደነበር በሚያሳብቅ መልኩ። «ሁሉም መሰለኝ!! የሁሉም ድምር መሰለኝ አንተን አንተ የሚያደርግህ!! ሁሉንም ልወቀው!!» «ደግ!! ከማን ጎሳ መገኘቴ ፍቅርሽን ያሳሳብኛል?» አለኝ ሲሆን አይቼው እንደማላውቅ ሽንፍ ብሎ በልምምጥ «የእነሱ ወገን አትሁን እንጂ ….. » ብዬ የአባቴን ገዳዮች ጎሳ ከመጥራቴ መልሱን ፊቱ ላይ አገኘሁት!! ማድረጌን ሳላውቀው እጄን ቀማሁት። ልቤ ድው ድው ማለቱን ያቆመ መሰለኝ። ከዛች የተረገመች ቀን ጀምሮ እድሜዬን ሙሉ ስጠላቸው ኖሪያለሁ። ያለፉትን ወራት ግን ልቤን የሞላው የሱ ፍቅር ጥላቻዬን ከድኖት ክፋትን እየሸሸሁ ፣ በቀልን እና ጥላቻን ከልቤ እያስወጣሁ ሌላ ሰው ልሆን እየሞከርኩ አልነበር? ለምን እንዲህ ተሰማኝ ታዲያ? የሱ ፍቅር ሌላው ላይ ያለኝን ጥላቻ እንጂ ማጥፋት የሚችለው እሱ የምጠላውን ሆኖ ሲመጣ ፍቅሩ አያሻግረኝ ይሆን? ዝም ብዬ መሬት መሬቱን ሳይ አስተናጋጁ የታዘዘውን ይዞ መጥቶ ጠረጴዛው ላይ መዋከብ ጀመረ። ቀና ብዬ አየሁት። እያየኝ ነው። ዓይኔን በዓይኑ ሲይዘው በሚለምን አስተያየት አየኝ!! «እሺ አንድ ነገር ንገረኝ? እኔጋ መስራት መጀመርህ የእነሱ ወገን ከመሆንህ ጋር ተያያዥነት አለው?» «የለውም ዓለሜ!!» አለኝ እንደተጨነቀ እያስታወቀበት።
Show all...
እኔ የምላችሁ?? .... ኮምፒውተሬ ጋርኮ ተፋጠን ብዙ ቆየን.... የመኖር አካፋይ የመሞት ሲሶ መንገድ መሃል ..... የመጨረሻ ክፍል .... ከአንድ አንቀፅ በላይ ንቅንቅ የለም!! እየተያየን ነው!!! ..... ምንም ዛሬ የመፃፍ ሙድ የለኝም!!! ሳስበው ለምንድነው የማልነግራችሁ እና ሙዱም ቃላቱም ፍስስስ ሲሉ የማልፅፈው??? አንድ ክፍል አይደል የሚቀረን?? ያውም የመጨረሻ ክፍል ለመጨረስ ያህል ብዬ አልፃፍ!! ... !!! ዛሬን እንዝለል ግድ የላችሁም!!! ... ❤️❤️❤️❤️
Show all...