የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)
Open in Telegram
ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።
Show more2 639
Subscribers
-224 hours
+37 days
+5630 days
Posts Archive
ከዚህም በኋላ የክርስትና ጥምቀትን ወደ ተጠመቀባት ወደ ቅዱስ ቴዎድሮስ ቤተ ክርስቲያን ሒዶ በሥዕሉ ፊት ቁሞ ጸለየ። በርሱም ዘንድ ሰውነቱን አደራ አስጠበቀ ወደ መኰንኑም ወጥቶ ክርስቲያን እንደ ሆነ ታመነ። ያንጊዜም ከከባዶች እንጨቶች ጋራ የኋሊት አሥረው ከረኃብና ከጽምዕ ጋራ ከፀሐይ ውስጥ ጣሉት። መንፈቀ ሌሊትም በሆነ ጊዜ ጌታችን ተገለጠለት። ሰላምታም ሰጠው ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያውን ለሚያደርግም ቃል ኪዳን ሰጠው።
ከዚህ በኋላም መኰንኑ ራሱን እንዲቆርጡት አዘዘ በቆረጡትም ጊዜ ራሱ እኔ ክርስቲያን ነኝ እያለች ሦስት ጊዜ በተራራው ላይ በረረች ሃምሳ ምዕራፍ ያህልም ሒዳ ከባሕር ወደቀች ።
ከዚህም በኋላ ሆዱን ሰንጥቀው ባሩድና ሙጫ ዘይትን መልተው ከእሳት ውስጥ ጣሉት። እሳቱ ግን ምንም አልነካውም ከዚህም በኋላ በየጥቂቱ ከትፈው በእንቅብ አድርገው ከባሕር ውስጥ ጣሉት። በእግዚአብሔርም ፈቃድ ከራሱ ጋራ አንድ ሆኖ እንደ ቀድሞው እስና በሚባል አገር በባሕሩ ወደብ ታየ ምእመናንም ወስደው በታላቅ ክብር ቀበሩት።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ሚካኤል_ገዳማዊ
በዚህችም ዕለት የአባ ሚካኤል መታሰቢያውና ቤተ ክርስቲያኑ የከበረችበት ሆነ። የዚህ ቅዱስ ወላጆቹ ክርስቲያን ባለጸጎች ናቸው ልጅ ባጡ ጊዜም የክብር ባለቤት ወደ ሆነ እግዚአብሔር ለመኑ እርሱም ይህን የተቀደሰ ልጅ ሰጣቸው የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርት አስተማሩት።
ወላጆቹም በሞቱ ጊዜ የዚያች አገር ኤጲስቆጶስ ገንዘቡን አስጠበቀለት ዐሥራ ሁለት ዓመትም ሲሆነው የዚህን ዓለም ኃላፊነት አስቦ ወደ አባ ይስሐቅ ገዳም ሒዶ የምንኲስና ልብስ እንዲያለብሰው ፈለገ። እርሱም ከፈተነውና ብርታቱን ከአየ በኋላ አለበሰው የእግዚአብሔርም ጸጋ አደረበት የፊቱ መልክ ተለውጦ እንደ ደረቅ እንጨት እስኪሆን በጾምና በጸሎት ሰውነቱን አስጨነቀ።
በአንዲት ዕለትም አባቱ አባ ይስሐቅ ወደ አባ ሚካኤል በዓት ሔደ መልኩ እንደ ሞተ ሰው ሆኖ አይቶት አለቀሰ። ልጄ ሆይ እንዴት እንዲህ ሥጋህ ተጎዳ አለው እርሱም አባቴ ሆይ አታልቅስ እግዚአብሔር አልተወኝምና ለመቆምም ኃይሌ አልደከመምና ነገር ግን በሕልሜ ያየሁትን ልንገርህ እኔን የሚፈልጉ የንጉሥ መልእክተኞች ከእስክንድርያ ወደ አንተ ሲመጡ እኔን አትከልክላቸው አንተን እንዳይወቅሱ። በሁለተኛውም ዓመት ታላቅ ረኃብ ይመጣል ምድርንም ያጠፋታልና ለልጆችህ ምግባቸውን አዘጋጅ ብሎ መለሰለት።
ከወራትም በኋላ በንጉሥ ጭፍራ አምሳል ሰዎች አባ ሚካኤልን እየፈለጉ መጥተው አባ ይስሐቅን ያዙት ሚካኤልንም በአገኙትና በአወቁት ጊዜ ከእሳቸው ጋራ ወሰዱት መነኰሳቱም እያዘኑ ቀሩ።
ረኃብም በሆነ ጊዜ አገረ ገዥው በዚያ ገዳም እህል እንዳለ ሰምቶ ሊከባቸው ፈለገ። አባ ይስሐቅም ሊማልድ ወደ መኰንኑ መጣ ያንጊዜም ብዙ ጭፍሮች ከሰይፎች ጋራ ከዚያ ገዳም ወጥተው መኰንኑ እያደነቀ አባ ይስሐቅን ወሰዱት።
ከዚህም በኋላ አባ ሚካኤል መጥቶ ራሱን ገለጠለት እነዚያ የወሰዱት ሰዎች የሰማይ ሰራዊት እርሱን የወሰዱበት አገርም ኢየሩሳሌም ሰማያዊት እንደሆነች ነገረው።
ከዚህም በኋላ ኤጲስቆጶሱ በአስጠበቀለት ገንዘቡ ቤተ ክርስቲያን እንዲሠራለት አዘዘው በዚያች በበዓቱ ላይ ሠራለትና በዚች ዕለት አከበሩዋት። ደግሞም አባ ሚካኤል ለአባ ይስሐቅ ተገልጾ በመጪው ዓመት እንደሚሞት ነገረው እንደቃሉም ሆነ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎትና ምልጃ ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ግንቦት_10
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ግንቦት ዐሥር በዚች ቀን የከበሩ #ጻድቃን_ሠለስቱ_ደቂቅ አናንያ አዛርያ ሚሳኤል የዕረፍታቸው መታሰቢያ ነው፣ የከበረ አባት #ቅዱስ_አብርሃም_ ፀራቢ በሰማዕትነት አረፈ፣ #የአባ_ሚካኤል መታሰቢያውና ቤተ ክርስቲያኑ የከበረችበት ሆነ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ሠለስቱ_ደቂቅ_ቅዱሳን
ግንቦት ዐሥር በዚች ቀን የከበሩ ጻድቃን ሠለስቱ ደቂቅ አናንያ አዛርያ ሚሳኤል የዕረፍታቸው መታሰቢያ ነው። እሊህም ለይሁዳ ንጉሥ ለኢዮአቄም ልጆቹ ናቸው ዳንኤልም የእኅታቸው ልጅ ነው በምርኮ ጊዜም ከእስራኤል ልጆች ጋራ ተማርከው ወደ ባቢሎን ወረዱ።
ከእስራኤል ልጆች ምርኮ ውስጥ በመብልና በመጠጥ እያስተማረ አሳድጎ በሠራዊቱ መካከል ጭፍሮቹ ያደርጋቸው ዘንድ ነውር ነቀፋ የሌለባቸውን ወጣቶች ንጉሥ መረጠ። እሊህም ከተመረጡት ውስጥ የተቆጠሩ ሆኑ የእኅታቸው ልጅ ዳንኤልም። ምግባቸውን በሚሰጡአቸው ጊዜ አረማውያን ከአረዱአቸው ውስጥ መብላትን አልወደዱም ከንጉሥ ማዕድም ከሚመጣ ከሥጋው እንዳያበላቸውና እንዳያጠጣቸው አለቃውን ለመኑት።
እግዚአብሔርም በባለሟሎች አለቃ ፊት ቸርነቱን አደረገላቸው። የባለሟሎች አለቃም ንጉሡ ጌታዬን እፈራዋለሁ የምትበሉትንና የምትጠጡትን ምግባችሁን ስለ አዘዘ ከባልንጀሮቻችሁ እናንተን ከስታችሁ ቢያያችሁ ንጉሥ ራሴን ይቀጣኛል አላቸው።
በእነርሱ ላይ የተሾመ አሚሳድን እንዲህ አሉት እኛን ባሮችህን ዐሥር ቀን ፈትነን ከምድር ዘር ሽምብራን ይስጡን እንበላ ዘንድ ውኃንም እንጠጣ ዘንድ። ቃላቸውንም ሰምቶ ዐሥር ቀን ፈተናቸው ዐሥር ቀንም ከአለፈ በኋላ የንጉሡን ማዕድ ከሚመገቡ ከእነዚያ ልጆች ይልቅ ሰውነታቸው ወፍሮ መልካቸውም አምሮ ታየ።
ከዚህ በኋላ አሚሳድ የሚበሉትን ምግብ የሚጠጡትን ወይን እየወሰደ ለአራቱ ሁሉ ልጆች ሽምብራ ይሰጣቸው ነበር። እግዚአብሔርም ዕውቀትንና ጥበብን መጻሕፍትን በማንበብ ሁሉ ማስተዋልን ሰጣቸው። ከዚህ በኋላ ንጉሥ ያዘዘው ቀን በተፈጸመ ጊዜ ወደርሱ አመጡአቸው የባለሟሎችም አለቃ ወደ ንጉሡ ወደ ናቡከደነፆር አገባቸው።
ንጉሡም ጠየቃቸው በሰው ሁሉ ዘንድ እንደ አናንያና እንደ ዳንኤል እንደ ሚሳኤልና እንደ አዛርያ ያለ አልተገኘም በንጉሡም ፊት ቆሙ። ንጉሡም የፈለገውን የምክርና የጥበብን ነገር ሁሉ በግዛቱ ካሉ ጠንቋዮችና አስማተኞች ሰዎች ሁሉ ይልቅ በነሳቸው ዘንድ ዐሥር እጥፍ አገኘ። ንጉሡም እጅግ ወደዳቸው በባቢሎን አገር ሁሉ ላይ ገዢዎች አድርጎ ሾማቸው።
ንጉሥም ጣዖትን ከወርቅ ባሠራ ጊዜ ሰዎችን ሁሉ እንዲሰግዱለት አዘዛቸው። ሦስቱ ልጆችም ለዚያ ጣዖት ባልሰገዱ ጊዜ የሚቀኑባቸው ወደ ንጉሥ ነገር ሠርተው በንጉሥ ፊት አቀረቧቸው ስለ አልሰገዱለትም ጠየቃቸው እነርሱም እኛስ ለሠራኸው ለወርቅ ምስል አንሰግድም አሉት። ንጉሥም ተቆጥቶ ከምትነድ የእሳት ምድጃ ውስጥ ይጨምሩአቸው ዘንድ አዘዘ።
እግዚአብሔርም መልአኩን ልኮ የእሳቱን ነበልባል አጠፋው በጥዋት ጊዜ እንደሚቀዘቅዝ በእሊህ በሦስቱ ልጆች ዘንድ እንደ ጥዋት ውኃ ቀዝቃዛ አደረገው። ከዚያም የእሳቱ ነበልባል አርባ ዘጠኝ ክንድ ያህል ከፍ ከፍ ብሎ በውጪ ያሉትን አቃጠላቸው እሊህን ሠለስቱ ደቂቅን ግን ምንም አልነካቸውም።
ንጉሥም ይህን ድንቅ ሥራ አይቶ በፊታቸው ሰገደ። የሰማይና የምድር ፈጣሪ እግዚአብሔርንም አመነ ለእሊህም ልጆች ሹመታቸውን ከፍ ከፍ አድርጎ ክብርን ጨመረላቸው። ከዚህም ዓለም የሚወጡበት ጊዜ ሲደርስ በበዐታቸው እየጸለዩ ሳሉ ሰግደው ነፍሳቸውን በእግዚአብሔር እጅ ሰጡ።
ወዲያውኑ ታላቅ ንውጽውጽታ በባቢሎን አገር ሆነ። ንጉሡም ፈርቶ ስለ ምን ይህ ታላቅ ንውጽውጽታ ሆነ ብሎ ዳንኤልን ጠየቀው ነቢይ ዳንኤልም ይህ ሦስቱ ልጆች ስለ አረፉ ከዓለም ለመውጣታቸው ምልክት ነው ብሎ ነገረው። ንጉሡም ወደርሳቸው ደርሶ ታላቅ ኀዘንን አዘነ ከዝሆን ጥርስም ሦስት ሣጥኖችን እንዲሠሩላቸው በሐር በግምጃ ልብሶች ገንዘው ቅዱሳኑን በሣጥኑ ውስጥ እንዲያኖሩአቸው አዘዘ ንጉሡ እንዳዘዛቸውም አደረጉ።
ሁለተኛም የወርቅ ሣጥን ሠርተው እርሱ በሚሞት ጊዜ ሥጋውን በውስጡ አድርገው በከበሩ ሠለስቱ ደቂቅ መካከል እንዲያኖሩት አዘዘ እንዲሁም አደረጉለት።
ከዚህ በኋላ የከበረ አባት አባ ቴዎፍሎስ በእስክንድርያ ሊቀ ጵጵስና በተሾመበት ወራት በስማቸው ቤተ ክርስቲያን ሠራ ሥጋቸውን ወደዚያች ቤተ ክርስቲያን ሊያመጣ ወዶ ሥጋቸውን እንዲያመጣለት አባ ዮሐንስ ሐፂርን ወደ እርሳቸው ሀገረ ባቢሎን ላከው።
ወደ ባቢሎን ሀገርም በደረሰ ጊዜ ወንዞቿን አየ በውስጧ ከቶ ሰው አልነበረም የወርቁ ምስልም በዚያ አለ። ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክም የቅዱሳን ሥጋ ወደአለበት አደረሰው የንጉሡም ሥጋ በመካከላቸው ነበረ። ሥጋቸው በአለበትም ቦታ ሰገደ። እንዲህም ብሎ በማልቀስ ጸለየ የከበራችሁ አባቶቼ ሆይ የከበረ አባት ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስ በስማችሁ ቤተ ክርስቲያን ሠርቶ ሥጋችሁን በውስጧ ሊያኖር እኔን ልኮኛልና ከእኔ ጋራ ትሔዱ ዘንድ ፈቃዳችሁ ይሁን።
በዚያን ጊዜ እንዲህ የሚል ቃል ከሥጋቸው ወጣ ለሃይማኖት አባት ለአባ ቴዎፍሎስ እንዲህ በለው የድካምህን ዋጋ እግዚአብሔር ይስጥህ ነገር ግን እኛን እስከ ፍርድ ቀን ድረስ ሥጋዎቻችን ከንጉሡ ሥጋ እንዳይለዩ እግዚአብሔር ስለአዘዘን ከዚህ አንወጣም ድካሙንም ከንቱ አናደርግም። ቤተ ክርስቲያኒቱ በምትከብርበት ዕለት በሌሊት መብራቶችን ይሰቅሉ ዘንድ እንዲአዝ በውስጣቸውም ዘይትና ፈትል እንዲያደርጉ በእሳት ግን አይለኩሱአቸው። እኛም ከዚያ ደርሰን በእኛ የእግዚአብሔር ኃይል በዚያ ይገለጣል ብለህ ንገረው አሉት።
አባ ዮሐንስ ሐፂርም ተመልሶ እንደነገሩት እንዴትም እንዳዘዙት ሁሉንም ለአባ ቴዎፍሎስ ነገረው እርሱም ሠለስቱ ደቂቅ እንዳዘዙ አደረገ። በዚችም በግንቦት ወር በዐሥር ቀን ቤተ ክርስቲያኒቱ በምትከብርበት ሌሊት የከበሩ ሠለስቱ ደቂቅ ተገለጡ ያለ እሳትም መብራቶችን አበሩ ሊቀ ጳጳሳቱና ለዚህ ጸጋ የታደሉ ሁሉ በቤተ ክርስቲያኒቱ እርከን ላይ ሲዞሩ ሠለስቱ ደቂቅን አዩአቸው በየአይነቱ በሆነ ደዌ የታመሙ ብዙ በሽተኞችም ከቅዱሳን ሠለስቱ ደቂቅ መገለጥ የተነሣ ያን ጊዜ ተፈወሱ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አብርሃም_ጸራቢ
በዚህችም ቀን አብርሃም ፀራቢ በሰማዕትነት አረፈ፡፡ ይህም ቅዱስ የሰማዕት ቴዎድሮስ ገዳም ተብላ ከምትጠራ ከመርቅያስ አገር ሰዎች ነው።
ወላጅ እናቱም የክብር ባለቤት የሆነ የክርስቶስን ሃይማኖት እንዲማር ለመምህር ሰጠችው። ጌታችንም ዐይነ ልቡናውን ገልጦለት ትምህርቱን ሁሉ የቤተ ክርስቲያንንም ሕግ ተማረ።
ከዚህም በኋላ መጾም መጸለይና መስገድ ጀመረ ዘጠኝ ዓመትም በሆነው ጊዜ ከደንጊያ የሚሠራ የውኃ መሔጃ መጥረብን ተማረ በዚህም ብዙ ገንዘብ አከማቸ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች የሚመጸውት ሆነ። በአንዲት ዕለትም በሌሊት ሲጸልይ የዚችን ዓለምና በውስጧ ያለው ሁሉ ኃላፊ መሆኑን አሰበ። የክብር ባለቤት በሆነ በክርስቶስ ስም ምስክር ሆኖ መሞትን ወደደ።
በዚያንም ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለት ሰላምታም ሰጥቶት ጽና አትፍራ አንተ ጠላቶችህን ድል አድርገህ የሰማዕትነትን አክሊል ትቀበላለህና አለው።
🔴#ስንክሳር ግንቦት_9
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ግንቦት ዘጠኝ በዚች ቀን የጻድቅ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ እናት #ቅድስት_ዕሌኒ አረፈች፣ ታላቁ አባት #አቡነ_ብፁዕ_አምላክ ዕረፍታቸው ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_ዕሌኒ_ንግሥት
ግንቦት ዘጠኝ በዚች ቀን የጻድቅ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ እናት ቅድስት ዕሌኒ አረፈች። ይቺም ቅድስት በፊት የአንድ ነጋዴ ሰው ሚስት ነበረች እርሱም በነገረ ሠሪ ንጽሕት ሁና ሳለች ወደ ባሕር ጣላት። የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ፈቃድም ሮሐ ከሚባል አገር ደርሳ የበራንጥያ ንጉሥ ቊንስጣ አገኛት። ውበቷንና ደም ግባቷንም አይቶ አገባት። ለክርስቲያን ነገሥታት መጀመሪያቸው የሆነውን ቈስጠንጢኖስን ወለደችው ምግባርንና ሃይማኖትን በማስተማር በመልካም አሳደገችው።
ልጇም በነገሠ ጊዜ ወደ ኢየሩሳሌም ሒደሽ የክብር ባለቤት የሆነ የክርስቶስን መስቀል ግለጪ የከበሩ ቦታዎችንም ሥሪ የሚላትን በሕልሟ አይታ እንዴት እንዳየች ይህን ለልጇ ነገረችው እርሱም ከብዙ ሠራዊት ጋራ ሰደዳት። በደረሰችም ጊዜ የክብር ባለቤት ስለሆነ ስለ ጌታችን መስቀል መረመረች አዳኝ የሆነ መስቀሉንም ሁለቱ ወንበዴዎች ከተሰቀሉባቸው መስቀሎች ጋራ አገኘችው። የክብር ባለቤት የክርስቶስ መስቀል የትኛው እንደሆነ ታውቅ ዘንድ በወደደች ጊዜ ከራሱ በላይ ይህ የናዝሬቱ ኢየሱስ የአይሁድ ንጉሥ ነው የሚል በእንጨት የተቀረጸበት ጽሑፍ ያለው እንደሆነ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ ቅዱስ መቃርስ ነገራት።
ከዚህ በኋላ ከእርሱ ምልክት ታይ ዘንድ ፈለገች የሞተ ሰውም አግኝታ መስቀሎችን በበድኑ ላይ አኖረች አልተነሣም። ከዚህ በኋላ ሦስተኛውን መስቀል በላዩ አኖረች። ያን ጊዜ ምውት ተነሣ ሃይማኖቷም ጸና ደስታዋም በዛ።
ከዚህ በኋላም ዜናቸው በመስከረም ወር በዐሥራ ሰባት የተጻፈ በከበሩ ቦታዎች ውስጥ አብያተ ክርስቲያናትን ትሠራ ዘንድ ጀመረች። ለአባ መቃርስም በከበሩ ቦታዎች ሁሉ አብያተ ክርስቲያናትን እንዲሠራ ብዙ ገንዘብ ሰጠችው።
ከዚህ በኋላ ወደ ልጇ ተመልሳ የሆነውን ሁሉ ነገረችው የከበረ መስቀል በመገኘቱ እጅግ ደስ አለው።
ይቺም ቅድስት በጎ ገድሏን ከፈጸመችና እግዚአብሔርንም ከአገለገለች በኋላ ስለ ካህናትም ልብስና ቀለብ ለአብያተ ክርስቲያናትና ለገዳማት ብዙ ጉልቶችና ርስቶችን ለድኆችና ለምስኪኖችም እንዲሁ ከሠራችና ከተከለች በኋላ በሰላም አረፈች መላ ዕድሜዋም ሰማንያ ሆነ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_ብፁዕ_አምላክ
በዚህች ቀን ታላቁ አባት አቡነ ብፁዕ አምላክ ዕረፍታቸው ነው፡፡ እኚህ ጻድቅ የአባታቸው ስም ቅዱስ አፍቅረነ እግዚእ ሲሆን የእናታቸው ስም ደግሞ ቅድስት ማርያም ዘመዳ ሲባሉ በ1425 ዓ.ም መስከረም አንድ ትግራይ ክልል ልዩ ስሙ መከዳ በተባለ ቦታ ተወለዱ። እስከ ሰባት ዓመታቸው በእናትና አባታቸው ቤት ከኖሩ በኋላ በስምንት ዓመታቸው ወደ ደብረ ቢዘን ገብተው የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ሲማሩ በገዳማዊ ኑሮ ሲያገለግሩ ቆይ እስከ 25 ዓመታቸው ከቆዩ በኋላ በዛው በደብረ ቢዘን በ25 ዓመታቸው መነኵሰዋል።
ከዚያም ወደ ደብረ ዳሞ ገዳም ገብተው ለአምስት ዓመታት ካገለገሉ በኋላ በድጋሚ በእግዚአብሔር ፈቃድ ወደ ኤርትራ አገር ወደ መጀመርያ ወደ መሰረቱ ገዳም ደብረ ኰዳዱ ሔደው በአንድ ዋሻ ውስጥ ገብተው ሕማማተ መስቀልን በማሰብ በአንድ ሺህ ችንካሮች እራሳቸው ቸክረው ለ30 ዓመታት ሲጋደዱ ኖሩ። በዛው አጋዕዝተ ዓለም ሥላሴ ለአብሃም እንደተገጹ ለእርሳቸውም በአንድነትና በሦስትነት ታኅሣሥ አንድ ቀን ተገለጡላቸው። እርሳቸው ሥላሴ መሆናቸው ለማረጋገጥ የቆሙበት ድንጋይ ለሦስት ቦታ ተከፈለ፤ እንደ ገና ደግሞ ተመልሶ ወደ አንድ ተለወጠ። በዚህ የተገለጡላቸው ሥላሴ እንደሆኑ አረጋገጡ ቃል ኪዳን ከገቡላቸው በኋላ መጨረሻ የሚያርፉበት ቦታ ነግረዋቸው ተሰወሩ ከዚያም ወደ ሁለተኛ ወደ መሰረቱት ገዳም ደብረ ምዕዋን ገብተው ብዙ ከተጋደሉ በኋላ ግንቦት 9 ቀን 1501 ዓ.ም በ76 ዓመታቸው ከእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ተቀብለው ዐርፈዋል። አጽማቸውም እስካሁን በዛው በደብረ ምዕዋን ይገኛል።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎትና ምልጃ ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
https://t.me/finotebirhan12
ወንበዴውም አይቶ ደነገጠ ሥራውንም ገለጠ ንስሓ ገብቶም መነኰሰ በበጎ ገድል ሁሉ ተጠምዶ እግዚአብሔርን አገለገለው። ጌታችንም ከዚህ ዓለም ድካም ሊአሳርፈው በወደደ ጊዜ መልአኩን ልኮለት ከዓለም የሚወጣበትን ጊዜ አስረዳው። መነኰሳቱንም ሰብስቦ በበጎ ሥራ እንዲጸኑ አዘዛቸው አጽናናቸው አረጋጋቸውም ከዚህም በሰላም አረፈ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎትና ምልጃ ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ግንቦት_8
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ግንቦት ስምንት በዚህች ዕለት የክብር ባለቤት #የጌታችንና_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ #በዓለ_ዕርገት ሆነ፣ ስንሑት ከሚባል አገር #ቅዱስ_ዮሐንስ በምስክርነት አረፈ፣ የአስቄጥስ ገዳም አበምኔት #አባ_ዳንኤል አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ዕርገተ_እግዚእ
ግንቦት ስምንት በዚህች ዕለት የክብር ባለቤት ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእኛ በነሣው ሥጋ ከአባቱና ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ ወደአለው የአንድነት አኗኗሩ ከሰማያት በላይ ያረገበት ሆነ።
እርሱም በረቀቀ ጥበቡ በመከራው በሞቱና በመነሣቱ ሥራውን ከፈጸመ በኋላ አርባው ቀን ሲፈጸም በነፋሳት ክንፍ ላይ ሆኖ ዐረገ።
ያን ጊዜ በኪሩቤል ላይ ተቀምጦ ወጣ በነፋሳትም ክንፎች ላይ ሁኖ ወጣ ያለው የዳዊት ትንቢት ተፈጸመ። በዚህም ዕርገቱ ለሚያምኑበት በልዕልና ወደሚኖሩበት የሚዐርጉ መሆናቸው ተረዳ ተረጋገጠ ራስ በአለበት ሕዋሳት ሊኖሩ ይገባልና ።
አዳም አስቀድሞ በምድራዊ ርስቶች በሲኦልም እንደኖረ መኖርንም እንደ ቀደመ እንዲሁ ዳግማዊ አዳም ጌታ በመንግሥተ ሰማያት ርስት መኖርን ቀደመ። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ዕርገቱን ከትንሣኤው አከታትሎ ወዲያውኑ አላደረገም መናፍቃን ዕርገቱ ምትሐት ናት ብለው እንዳያስቡ።
ጌታችንም በረቀቀ ጥበቡ የደቀ መዛሙርቱን ተሸብሮ የነበረ ልቡናቸውን እያጽናና መነሣቱንም እያስረዳቸው ከትንሣኤው በኋላ አርባ ቀን ኖረ። በጌታችንም ዕርገት የዳንኤል ትንቢት ተፈጸመ እንዲህ የሚል ሌሊት በራእይ አየሁ እነሆ ታላቅ እንደ ሰው ልጅ የሆነ መጣ ዘመናትን ወደሚያስረጃቸው ደረሰ ከፊቱም አቀረቡት።
የዘላለም አገዛዝ ጌትነት መንግሥት የዘላለም ሥልጣን ተሰጠው ሕዝቡና አሕዛቡ ሁሉ መንደር መንድረው የሚኖሩትና ነገዱም ነገሥታቱም ሁሉ ይገዙለታል አገዛዙም የዘላለም አገዛዝ ነው መንግሥቱም የማያልፍ የማይጠፋ ነዋሪ ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ዮሐንስ_ሰማዕት
በዚህች ቀን ስንሑት ከሚባል አገር ቅዱስ ዮሐንስ በምስክርነት አረፈ። የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም መቃርስ የእናቱም ስም ሐና ነው። እርሱም የአባቱን በጎች ሲጠብቅ የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦ የብርሃን አክሊልን አሳየው። እነሆ ተጋድሎ ተዘርግቶ በክርስቶስ ስም ለሚጋደል አክሊላት ተዘጋጅተው ሳሉ አንተ ለምን ከዚህ ተቀመጥክ። አሁንም ወደ ሀገረ አትሪብ ሒድ የክብር ባለቤት ስለሆነ ስለ ክርስቶስ ስም ተጋደል አለው። ከዚያም ሰላምታ ሰጥቶት ከእርሱ ዘንድ ሔደ።
በዚያም ወቅት ቅዱስ ዮሐንስ ተነሣ እናቱንና አባቱንም ተሰናብቶ ወደ አትሪብ ከተማ ሔደ መኰንኑንም በውሽባ ቤት አገኘውና በወጣ ጊዜ በፊቱ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ። መኰንኑም ለአንድ ወታደር ሰጥቶት ምናልባት ከምክሩ ተመልሶ ቢታዘዝለት አስቦ እንዲአባብለው ወታደሩን አዘዘው።
ከዚህ በኋላ መኰንኑ ወደ ሥራው ሔደ ወታደሩም ቅዱስ ዮሐንስን ወደ ቤቱ ወሰደው። ቅዱሱም ተአምራትን አደረገ ያ ወታደርም በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ። መኰንኑም በተመለሰ ጊዜ ያ ወታደር በክብር ባለቤት በጌታችን በመኰንኑ ፊት ታመነ የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበለ።
ከዚህ በኋላም ቅዱስ ዮሐንስን እንዲአሠቃዮት መኰንኑ አዘዘ በየአይነቱ በሆነ ሥቃይም አሠቃዩት። እግዚአብሔርም ያጸናውና ያስታግሠው መልአኩንም ልኮ ቊስሎቹን አድኖ ያለ ጉዳት በደኀና ያነሣው ነበር።
ከዚህም በኋላ ወደ እንዴናው ከተማ ላከው በዚያም ታላቅ ሥቃይን አሠቃዩት። መኰንኑም ማሠቃየቱን በሰለቸ ጊዜ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበለ።
የአቅፍሐሲ ዮልዮስም ሥጋውን ወስዶ ገነዘው ወደ ሀገሩ ስንሑትም ላከው። የሀገሩ ሰዎች ሁሉም ወጥተው በፍጹም ደስታ ተቀበሉት ከማዕጠንት ጋራ እየዘመሩና እያመሰገኑ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩት ከሥጋውም ብዙዎች ድንቆች ተአምራት ተገለጡ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አባ_ዳንኤል_ጻድቅ
በዚህችም ዕለት የአስቄጥስ ገዳም አበምኔት አባ ዳንኤል አረፈ። ይህም ቅዱስ ዕውነተኛ ንጹሕ ፍጹም ነው ዜናው በሁሉ ቦታ በተሰማ ጊዜ ሹመት ያላት አንስጣስያ የመኳንንቶችን ልብስ ለብሳ ወደርሱ መጥታ ከእርሱ መነኰሰች። በእርሱ አቅራቢያም ሃያ ስምንት ዓመት በበዓት ውስጥ ኖረች እርሷ ሴት እንደሆነችም ማንም አላወቀም።
ይህም ቅዱስ ስሙ አውሎጊስ የሚባለውን ሰው አየው ይህም አውሎጊስ የወፍጮ ድንጋይ እየወቀረ ለግርሽ እየሸጠ ሁል ጊዜ በመጠኑ እየተመገበ ድኆችንና ጦም አዳሪዎችን ይመግባቸዋል የተረፈውንም ፍርፋሪ ለውሾች ይጥላል ለነገ ብሎ ምንም አያሳድርም።
አባ ዳንኤልም ይህን መልካም ሥራውን አይቶ በርሱ ደስ አለው እጅግም አማረው ለአውሎጊስም የዚህን ዓለም ብልጽግና እንዲሰጠውና ለድኆች የሚመጸውተው እንዲጨመርለት ወደ እግዚአብሔር ለመነ።
ለአውሎጊስም ዋስ ሆነው የሚወቅረውንም ደንጊያ ሲፈነቅል በሸክላ ዕቃ የተደፈነ ወርቅን አገኘ ወደ ቊስጥንጥንያ ከተማ ሒዶ የንጉሥ የሠራዊት አለቃ ሆኖ ተሾመበት የሚሠራውንም የቀደመ በጎ ሥራውን ተወ። አባ ዳንኤልም ስለርሱ ሰምቶ ወደርሱ በሔደ ጊዜ የንጉሥ ሠራዊት አለቃ ሆኖ በፈረስ ላይም ተቀምጦ ብዙ ሠራዊት አጅቦት እርሱም በትዕቢት ተመልቶ የቀድሞ በጎ ሥራውንና ለድኃ መመጽወቱንም ትቶ አገኘው።
አባ ዳንኤልም አይቶ አዘነ ስለርሱ በመለመኑም ተጸጸተ። ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ለፍርድ እንደ መጣ አባ ዳንኤልንም እንዲሰቅሉት ሲያዝ የአውሎጊስንም ነፍስ ከእርሱ እንዲሹ በእርሱ ምክንያት ጠፍቷልና የከበረች ድንግል እመቤታችን ማርያምም የክብር ባለቤት ጌታችንን ልጅዋ ኢየሱስ ክርስቶስን ስለ አባ ዳንኤል እንደ ለመነችው በሌሊት ራእይ አባ ዳንኤል ራሱ አየ።
በነቃም ጊዜ ደነገጠ አውሎጊስንም ወደ ቀድሞ ሥራው ይመልሰው ዘንድ በጸሎትና በምሕላ በመትጋት ወደ እግዚአብሔር እየለመነ ግብር ገባ ሱባኤ ያዘ።
ከዚህ በኋላም ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ተገለጸለት በፍጥረቱ ላይ በሚያደርገው በእግዚአብሔር ፍርድ ውስጥ ለመግባት በመድፈሩ ገሠጸው። በዚያንም ወቅት አውሎጊስን የሾመው ንጉሥ ሞተ ሌላ ንጉሥም ነገሠ በአውሎጊስም ላይ ተነሥቶ ገንዘቡን ሁሉ ወረሰ። ደግሞም ሊገድለው ፈለገው አውሎጊስም ነፍሱን ለማዳን ከንጉሡ ሸሽቶ ወደ አገሩ ደረሰ እንደ ቀድሞውም ደንጊያ ይወቅር ጀመረ አባ ዳንኤልም ወደርሱ ተመልሶ ስለርሱ ያየውን ሁሉ ስለ ርሱም እንደሰቀሉትና ነፍሱንም ከእርሱ እንደፈለጉ ነገረው።
በዚህ በአባ ዳንኤልም የትንቢት መንፈስ አድሮበት ነበር ከእርሱም ብዙዎች ታላላቅ ታአምራት ተገለጡ። መናፍቃን አርዮሳውያንም ከቀናች ሃይማኖት ሊአወጡት በፈለጉ ጊዜ እንቢ አለ። ያቺንም የክህደት ደብዳቤ ተቀብሎ ቆራረጣት የአርዮሳዊ ንጉሥ ወታደርም ይዞ ብዙ ሥቃይን አሠቃየው። በአንዲት ዕለትም ቅዱሳት ደናግል ወደ ሚኖሩበት ወደ ሲሐት ገዳም አባ ዳንኤልን ተመስሎ ሽፍታ ገባ። ደናግሉም በደስታ ተቀብለው እግሮቹን አጠቡ። እነርሱም አባ ዳንኤል እንደሆነ አምነው የወንበዴውን የእግር እጣቢ ውኃ በረከቱን ለማግኘት በላያቸው ረጩት። በዚያም አንድ ዐይኗ የታወረ ነበረች ውኃው በነካት ጊዜ ዐይኗ በርቶላት አየች።
ወደ ገዳሙም ደርሶ ከልጆቹ መነኰሳት ጋራ የመንፈቀ ሌሊትን ጸሎት አደረገ። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ብዙ ጊዜ ወደርሱ እየመጣ ያነጋግረው ነበር። እርሱም የመድኃኒታችንን እግሩን ያጥበው ነበር እጣቢውንም ይጠጣ ነበር ጌታችንም ብዙ ምሥጢራትን ገለጠለት ትንቢቶችንም ተናገረ።
ከዚህም በኋላ ፈጽሞ በአረጀ ጊዜ ሐምሌ ሰባት ቀን ተኛ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መጥቶ እያረጋጋው በእርሱ ዘንድ ተቀመጠ። ብፁዕ አባ ሲኖዳም ጌታችንን እንዲህ አለው ጌታዬ ፈጣሪዬ ልዩ ሦስትነትህንና ጌትነትህን ስለሚነቅፉ ከሀድያን ወደ ጉባኤው እሔድ ዘንድ እንዲጠሩኝ ሊቀ ጳጳሳቱ ወደ እኔ ልኳልና እንደቀድሞው ታጸናኛለህን።
ጌታችንም በጸጋና በጥዑም ቃል እንዲህ ብሎ መለሰለት ወዳጄ ሲኖዳ ሆይ ሌላ ዕድሜ ትሻለህን። እነሆ ዕድሜህ ሁሉ መቶ ሃያ ዓመት ከሁለት ወር ሁኖሃል ዕድሜህ ዘጠኝ ዓመት ሲሆን አስኬማን ለበስኽ ከዚያ በኋላ መቶ ዐሥራ አንድ ዓመት ከሁለት ወር ኖርኽ አሁንስ ድካምህ ይብቃህ ይህንንም ብሎ ጌታችን በክብር ዐረገ።
በዚያንም ጊዜም የቅዱሳን አንድነት ማኅበር ወደርሱ መጡ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ዳግመኛ አየው ልጆቹንም ክብር ይግባውና ለጌታዬ ለኢየሱስ ክርስቶስ እሰግድ ዘንድ አንሱኝ አላቸው አንሥተውትም ሰገደለት። ከዚህም በኋላ ዳግመኛ እንዲህ አላቸው ወደ እግዚአብሔር አደራ አስጠብቅኋችሁ ነፍሴም ከዚህ ከደካማው ሥጋዬ የምትለይበት ጊዜ ደርሷል እኔም ለአባታችሁ ለዊዳ እንድትታዘዙ አዝዛችኋለሁ ከእኔ በኋላ ጠባቂያችሁ እርሱ ነውና አላቸው።
ለልጆቹም ይህን በተናገረ ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመረጥሁህ ሲኖዳ ሆይ ብፁዕ ነህ ቸርነቴም ይደረግልሃል በሕይወትህ ዘመን ሁሉ አንተ የምወደውን ሥራ ሠርተሃልና እንግዲህ ወደ ዘለዓለም ተድላ ታርፍ ዘንድ ወደእኔ ና አለው። ሐምሌ 7 ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎትና ምልጃ ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ግንቦት_7
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ግንቦት ሰባት በዚች ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃያኛ የሆነ የከበረ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_አትናቴዎስ_ሐዋርያው አረፈ፣ ቅዱስ አባት የባሕታውያን አለቃ የሆነ መስተጋድል #አባ_ሲኖዳ ልደቱ ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አትናቴዎስ_ሐዋርያዊ
ግንቦት ሰባት በዚች ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃያኛ የሆነ የከበረ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ሐዋርያዊ አትናቴዎስ አረፈ።
ይህም ቅዱስ ሐናፊ ከሚባል የእስ*ላም ነገድና ከአረማ*ውያን ተወላጅ ነው ይባላል። እርሱም ከመምህር ከሚማሩ ሕፃናት ጋራ እያለ እርስ በርሳቸው በመጫወት ሥርዓተ ቤተክርስቲያን እየሠሩ ከእነርሱ ውስጥ ዲያቆናትን ኤጲስቆጶሳትንም ሲያደርጉ እሊያን የክርስቲያንን ልጆች አይቶ ጨዋታቸው ደስ ስለአለው ከእሳቸው ጋራ በጨዋታቸው አንድ ይሆን ዘንድ የክርስቲያንን ልጆች ለመናቸው። እነርሱም አንተ አረ*ማዊ ነህና ከእኛ ጋራ አትደመርም ብለው ከለከሉት እርሱም ክርስቲያን እሆናለሁ አላቸው እነርሱም ደስ ተሰኙበት።
ያን ጊዜም ወስደው በሊቀ ጳጳሳት አምሳል አደረጉት ከበታቹም ወንበር አድርገው ይሰግዱለት ጀመር። በዚያን ጊዜም ሊቀ ጳጳሳት አባ እለእስክንድሮስ በዚያ አለፈ የክርስቲያን ልጆች ሲጫወቱ በአያቸው ጊዜ አብረውት ላሉ ይህ ሕፃን ከፍ ከፍ ያለችና የከበረች ሹመትን ይሾም ዘንድ አለው አላቸው።
አባቱም በሞተ ጊዜ ወደ አባ እለእስክንድሮስ መጣ የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቀው። ከዚህም በኋላ የአባቱን ገንዘብ ሁሉ ወስዶ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ሰጥቶ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርትና ሕግ ሥርዓትንም ከአባ እለእስክንድሮስ ዘንድ እየተማረ ኖረ እርሱም ተወዳጅ ልጅ አደረገው።
ከዚህም በኋላ ዲቁና ሾመው የመንፈስ ቅዱስንም ጸጋ የተመላ ሆነ። የከበረ አባት እለእስክንድሮስም በአረፈ ጊዜ ይህን አባት አትናቴዎስን በእስክንድርያ አገር ላይ ሊቀ ጳጳሳት አድርገው ሾሙት። ከዚህ አስቀድሞ ግን የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ኤጲስቆጶሳት ስብሰባ በተደረገ ጊዜ አባ እለእስክንድሮስ ከዚህ ዓለም ሳይለይ ይህም አትናቴዎስ ከእሳቸው ጋራ ተሰብስቧል። የጉባኤውም ጸሐፊ አድርገውት በኒቅያ ከተማ ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን ከእሳቸው ጋራ ሠራ።
ጻድቁ ቈስጠንጢኖስ በሞተ ጊዜ አርዮ*ሳዊ ልጁ ሁለተኛው ቈስጠንጢኖስ ነገሠ አርዮ*ሳውያንም በዙ ይህንንም አባት አርዮ*ሳዊው ንጉሥ ከመንበረ ሢመቱ አሳደደው በእርሱም ፈንታ ጊዮርጊስ የተባለ ከሀዲ ሰው ሾመ።
ከዚህም በኋላ ብዙ ጊዜ ሲአሳድዱትና ሲመልሱት ኖረ። በስደቱም በአንዲት ምዕራባዊት አገር በአለ ጊዜ በዚያ የጣዖት ቤት አለች። በዚያችም የጣዖት ቤት ብዙ ሕዝቦች በውስጧ ይሰበሰባሉ። ለዚያችም የጣዖት ቤት በውስጧ የሚሠሩ ብዙ የሰይጣን ሥራዎች አሏት። እርሱም የክብር ባለቤት የሆነ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመነው ያቺንም የጣዖት ቤት አፍርሶ የአገር ሰዎችን ሁሉ እግዚአብሔርን ወደማወቅ መለሳቸው።
ይህንንም አባት አምስት ጊዜ አሳደዱት የሹመቱም ዘመን አርባ ሰባት ሲሆን ዐሥራ አምስቱን ዓመት በስደትና በእሥራት ነው ያሳለፈው። ይህንንም አባት ብዙ መከራና ድካም መሰደድም ስለደረሰበት ሐዋርያዊ ተብሎ ተጠራ።
በሚሞትበትም ጊዜ በእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነትን ባገኝ ይህን የጣዖት ቤት ያፈርስ ዘንድ በፊቱ እኔ እየሰገድኩ እለምነዋለሁ። ይህም አባት ከአረፈ በኋላ ንጉሥ ልኮ ያንን የጣዖት ቤት አስፈረሰው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ታላቁ_አባ_ሲኖዳ (የባሕታውያን አለቃ)
ዳግመኛም በዚህች ቀን ቅዱስ አባት የባሕታውያን አለቃ የሆነ መስተጋድል አባ ሲኖዳ ልደቱ ነው።
ይህም ቅዱስ በግብጽና በአክሚም አውራጃ ስሟ ስንላል ከምትባል ሀገር ከላይኛው ግብጽ ነበር። ስለእርሱም የመላእክት አምሳል የሆነ አባ ሐርስዮስ ትንቢት ተናገረለት። እርሱም ስለ ገዳም አገልግሎት ከመነኰሳት ጋር ሲሔድ የዚህን የቅዱስ ሲኖዳን እናት ውኃ ለመቅዳት ወጥታ አገኛት: ወደርሷ ሒዶ ሦስት ጊዜ ራሷን ሳማትና እንዲህ አላት ዜናው በዓለሙ ሁሉ የሚሰማ የስሙ መዓዛ ከሽቱ የሚጥም የሆነ የሆድሽን ፍሬ እግዚአብሔር ይባርክ።
እነዚያ መነኰሳትም በአዩት ጊዜ አድንቀው አባታችን አንተ የሴት ፊት ማየት ከቶ አትሻም ነበር ዛሬ ግን ከሴት ጋራ ትነጋገራለህ አሉት። ልጆቼ ሆይ ሕያው እግዚአብሔርን የእግዚአብሔርን ምሕረት ተስፋ የሚያደርግ ዓለሙ ሁሉ የሚጣፍጥበት ከዚች ሴት የሚወጣ የጨው ቅንጣት አለ አላቸው።
አንድ በገድል የጸና ጻድቅ ሰው መነኰስ ነበረ እርሱም መልሶ አባ ሐርስዮስን እንዲህ አለው እግዚአብሔር ሕያው ነው አንተ ራሷን ትስም ዘንድ ወደዚያች ሴት በቀረብክ ጊዜ በእጁ የእሳት ሰይፍ የያዘ የእግዚአብሔርን መልአክ በዙሪያዋ አየሁት፡፡ ራሷንም በሳምካት ጊዜ ክብር ይግባውና የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ወዳጁ ሆይ ሰላምታ ይገባሃል ሲልህ ደግሞም ከዚች ሴት የሚወለደው የተመረጡ ቅዱሳንን ሁሉ ልባቸውን ደስ ያሰኛል ወልደ እግዚአብሔርም ከርሱ ጋር ብዙ ጊዜ ይነጋገር ነበር ሲል ሰማሁት አለ።
በግንቦት ሰባት ቀን ይህ ቅዱስ አባ ሲኖዳ ተወለደ በአደገም ጊዜ አባቱ በጎች ስለነበሩት ለልጁ ለሲኖዳ እንዲጠብቃቸው ሰጠው ይህ ሲኖዳም ምሳውን ለእረኞች ሰጥቶ እስከ ማታ ድረስ ይጾም ነበር። በሌሊትም ከውኃ ዐዘቅት ውስጥ ወርዶ በዚያ ቁሞ እስቲነጋ ድረስ ሲጸልይ ያድር ነበር። በክረምትም ሆነ በቊር ሰዓት እንዲሁ ያደርግ ነበር።
አባቱም የሲኖዳ እናት ወንድም ወደ ሆነው ወደ አባ አብጎል እጁን በላዩ ጭኖ ይባርከው ዘንድ ወሰደው። አባ አብጎልም በአየው ጊዜ የሕፃኑን እጅ አንሥቶ በራሱ ላይ አድርጎ ሲኖዳ ሆይ ባርከኝ ለብዙ ሕዝብ ታላቅ አባት ትሆን ዘንድ የሚገባህ ሁነሃልና አለው: አባቱም በአባ አብጎል ዘንድ ተወው።
ከዕለታትም በአንዲቱ ቀን አባ አብጎል እንዲህ የሚል ቃል ከሰማይ ሰማ እነሆ ሲኖዳ ለዓለሙ ሁሉ አርሲመትሪዳ የባሕታውያን አለቃ ሁኖ ተሾመ። ይህም ሲኖዳ ለዓለሙ ሁሉ ብርሃን እስከሚሆን በበጎ አምልኮ ያለ ማቋረጥ በጾምና በጸሎት በስግደትና በመትጋት ታላቅ ተጋድሎ መጋደልን ጀመረ።
ከዚህም በኋላ በአንዲት ቀን ለአባ አብጎል የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለትና የኤልያስን አስኬማ የሠለስቱ ደቂቅን ቆብና የመጥምቁ ዮሐንስን ቅናት አመጣለት። እንዲህም አለው እንድትጸልይና የምንኵስና ልብስ ለሲኖዳ እንድታለብሰው እማዚአብሔር አዝዞሃል። ያን ጊዜም አባ አብጎል ተነሥቶ ጸለየ የምንኵስና ልብስንም አለበሰው።
ከዚህም በኋላ ተጋድሎውን አበዛ፡፡ ለመነኰሳት፣ ለመኳንንት፣ ለሕዝባውያንና ለሴቶች ለሰዎች ሁሉ መመሪያ የሚሆን ሥራትን ሠራ። በኤፌሶንም የሁለት መቶ ኤጲስቆጶሳት ጉባኤ ስለ ከሀዲው ንስጥሮስ በተደረገ ጊዜ ከማኅበሩ አባት ከሊቀ ጳጳሳት ቄርሎስ ጋራ ወደ ጉባኤው ሔደ ንስጥሮስም ከክህደቱ ባልተመለሰ ጊዜ አውግዘው ለይተው አሳደዱት።
ከዚህ በኋላም ወደ ሀገራቸው በመመለሻቸው ጊዜ መርከበኞች ከሊቀ ጳጳሳቱ ጋራ አትሳፈርም ብለው አባ ሲኖዳን ከለከሉት እርሱም ወደ እግዚአብሔር በጸሎት ማለደ። ወዲያውኑም ደመና መጥታ ተሸከመችውና አባ ቄርሎስ በመርከቡ ውስጥ እያለ በበላዩ በአንጻሩ አደረሰችው። አባቴ ሆይ ሰላም ለአንተ ከአንተ ጋራ ላሉትም ይሁን ብሎ ሰላምታ አቀረበ፡፡ በመርከብ ያሉት ሁሉም ላንተም ሰላም ይሁን በጸሎትህም አትርሳን አሉት። እጅግም አደነቁ ለሚፈሩት ይህን ይህል ጸጋ የሚሰጥ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት።
በዚህችም ቀን ቅድስት ዲላጊ ከአራት ልጆቿ ጋራ ምስክር ሆና አረፈች፡፡ እነርሱም ሱርስ ኀርማን ያአፋ ናቸው። ይችም ቅድስት በክብር ባለቤት ክርስቶስ ሃይማኖት የጸናች ናት።
መኰንኑ አርያኖስም ሀገረ አስና በደረሰ ጊዜ ልጆቿን እየነዳች ተቀበለችው በፊቱም ቁማ አርያኖስ ሆይ ሰማይንና ምድርን በውስጣቸው ያለውን በፈጠረ በክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ የማምን ክርስቲያን ነኝ አለችው።
ልጆቿም እንደርሷ እኛ ክርስቲያን ነን እያሉ በግልጽ ጮኹ። መኰንኑም ሰምቶ ቁጣን ተመላ ራሳቸውንም በሰይፍ ቆረጠ ምስክርነታቸውንም ፈጽመው ነፍሶቻቸውን ወደ ክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ መላእክት ወሰዱ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#እናታችን_ቅድስት_ሰሎሜ_ዘወረብ
በዚህችም ዕለት ደግሞ ንጽሕናን ቅድስናን ድንግልናን ገንዘብ ያደረገች ተሐራሚት ሰሎሜ አረፈች። ይችም ቅድስት ወረብ ከሚባል አገር ናት ወላጆቿም እግዚአብሔርን የሚፈሩ ናቸው በበጎ አስተዳደግም አሳደጉዋት። በአደገችም ጊዜ እርሷ ሳትፈቅድ አንድ መኰንን አጭቶ በሠርግ አገባት። ያን ጊዜም አምላካዊ ኃይል ከልክሎት ወደርሷ መቅረብ አልቻለም አባለ ዘሩ ተቀሥፎአልና።
በእንደዚህም እያለች ራሷን ሠውራ በሌሊት ሔደች በእግዚአብሔር ኃይል አመለጠች። ቅዱሳን በአሉበት ሁሉ በመዞር በጾም በጸሎት ተወስና ዕውነተኛ መንገድን ጌታ ይመራት ዘንድ በቀንና በሌሊት ስትማልድ ኖረች።
ጌታችንም ልመናዋን ሰምቶ ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም አደረሳት የመላእክት የሆነ አልባሰ ምንኲስናን በአባ ዮሐንስ ከማ እጅ ለብሳ የሰውን ልብ የሚያስደነግጥ ጽኑ ገድልን ተጋደለች።
በጾም በጸሎት በተመሰገነ ገድል ሁሉ የፍጹማን አባቶችን ጐዳና ተጓዘች። በመጽሐፈ ገድሏ እንደ ተጻፈ ብዙዎች ድንቆች ተአምራትንም እስከ ማድረግ ደርሳ ከዚህ በኋላ በሰላም አረፈች።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ግንቦት_6
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ግንቦት ስድስት በዚህች ቀን የእስክንድርያ ቄስ የከበረ አባት #አባ_መቃርስ አረፈ፣ ከግብጽ ደቡብ ዳፍራ ከሚባል አገር የከበረ #አባ_ይስሐቅ ምስክር ሆኖ አረፈ፣ #ቅድስት_ዲላጊ ከአራት ልጆቿ ጋራ ምስክር ሆና አረፈች፣ ንጽሕናን ቅድስናን ድንግልናን ገንዘብ ያደረገች #ተሐራሚት_ሰሎሜ አረፈች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_መቃርስ
ግንቦት ስድስት በዚህች ቀን የእስክንድርያ ቄስ የከበረ አባት አባ መቃርስ አረፈ። ይህም ቅዱስ በአባቱ በሚቀድመው በታላቁ በክቡር አባ መቃርስ ዘመን ለአስቄጥስ ገዳም አባት ሁኖ ብዙ ትሩፋትን ሠራ።
ስለእርሱም እንዲህ ተባለ አንዲት ዘመሚት ነክሳው ገደላት ከዚህም በኋላ ተጸጽቶ ነፍሱን ገሠጻት ስለ ዘመሚቷም ሞት በበረሀ ወደአለ ወንዝ ወርዶ ሥጋውንም ለዘመሚት ገልጦ እንደዝልጉስ እስኪሆን በዚያ ስድስት ወር ኖረ። ከዚህ በኋላ ወደበዓቱ ተመለሰ መቃርስ እንደሆነም ማንም አላወቀውም።
አንድ ጊዜም እየጸለየ አምስት ቀን አምስት ሌሊት ቆመ ልቡም ወደ ሰማይ ተመስጦአል ሰይጣናትም እስከ ተቃጠሉ ድረስ ይቺ ትጋትና ተጋድሎ ከሠራው ትሩፋት ሁሉ ትልቃለች አሉ። አንድ ጊዜም የረዓይትን ቦታዎች ሊያይ ወዶ ወደ በረሀ ውስጥ ገባ ዐሥር ቀኖችም እየተጓዘ ኖረ። በሚመለስም ጊዜ ምልክት ሊሆኑት መንገዱን እንዳይስት ለምልክት የሚያኖራቸው ሸንበቆዎች ከእርሱ ጋራ ነበሩና በየመንገዱ ተከላቸው።
በደከመም ጊዜ ጥቂት ሊያርፍ በምድር ላይ ተኛ። ተኝቶ ሳለም እነዚያን ሸንበቆዎች ሰይጣን ነቀላቸው አሥሮም በቅዱስ መቃርስ ራስጌ አኖራቸው። በነቃም ጊዜ አያቸውና ወዲያውኑ አጣቸው አደነቀ እንዲህ የሚልም ቃልን ሰማ።
መቃርስ ሆይ ሃይማኖት ካለህ አታወላውል በሸንበቆዎችም አትታመን የእስራኤልን ልጆች በበረሀ ሲመራቸው የነበረ የብርሃን ምሰሶ እርሱ እንደሚመራህ እመን እንጂ አትጠራጠር። ወዲያውኑ የብርሃን ምሰሶ አይቶ ተመለሰ።
ከዚህም በኋላ በጎዳና ሳለ ተጠማ እግዚአብሔርም ከበረሀ ላሞች አንዲቷን ልኮለት ወተቷን ጠጥቶ ረካ ወደ በዓቱም ተመለሰ።
በአንዲት ቀንም ጅብ ወደርሱ መጥታ ልብሱን ይዛ ትስብ ጀመር እርሱም እስከ ዋሻዋ ተከተላት። ሦስት ልጆቿን አወጣችለት በአያቸውም ጊዜ ዕውሮች ሁነው አገኛቸው ከልቡናዋም አሳብ የተነሣ ያቺን ጅብ አደነቃት። ግልገሎቿንም ይዞ በዐይኖቻቸው ውስጥ ምራቁን ተፋ፡፡ አዳኝ በሆነ በመስቀል ምልክትም አማተበባቸው ያን ጊዜ ድነው ከእናታቸው ኋላ ሮጡ ጡቷንም ጠቡ ከዚህ በኋላም ወደ በዓቱ ተመለሰ እርሷም የበግ አጐዛ አመጣችለት እርሱም ተቀብሎ በላዩ እየተኛ እስከሚአርፍበት ጊዜ በእርሱ ዘንድ አኖረው።
በአንዲት ጊዜም ደግሞ ልብሱን ለውጦ በሕዝባዊ አምሳል ሆኖ ወደ አባ ጳኵሚስ ገዳም ሔደ በታላቁም ጾም ሳይበላ ሳይጠጣ አርባ መዓልት አርባ ሌሊት ቆመ። የሚሠራውንም እንደቆመ ይታታ ነበር እንጂ አይቀመጥም። መነኰሳቱም አባ ጳኩሚስን ይህን ሰው ከእኛ ዘንድ አውጣው ሥጋ የለውምና አሉት አባ ጳኵሚስም ሥራውን ይገልጥልኝ ዘንድ እግዚአብሔርን እስከምለምነው ታገሡኝ አላቸው። በለመነውም ጊዜ የእስክንድርያው መቃርስ እንደሆነ እግዚአብሔር አስረዳው።
በዚያን ጊዜም አባ ጳኵሚስና መነኰሳቱ ሁሉ ወደርሱ ሒደው እጅ ነሱት ከእርሱም ቡራኬ ተቀብለው ደስ ተሰኙበት ወደቤተ መቅደስም ከእሳቸው ጋራ አስገቡት። በገዳሙ ውስጥም በሥራቸው በመመካት በባልንጀሮቻቸው ላይ የሚታበዩ የዚህን ቅዱስ አባት የአባ መቃርስን ጸጋውን አይተው ትሑታኖች ሆኑ። ከዚህ በኋላም ወደ በዓቱ ወደ አስቄጥስ ገዳም ተመለሰ።
በእስክንድርያ አገርም ዝናብ በተከለከለ ጊዜ ዝናብን እንዲያወርድ አንበጣንም እንዲአጠፋ ወደ እግዚአብሔር አብሮት ለመጸለይ ወደርሱ ይመጣ ዘንድ ሊቀ ጳጳሳት አባ ጢሞቴዎስ እየማለደ ላከበት። ያንጊዜም ተነሥቶ ወደ እስክንድርያ አገር ሔደ ሕዝቡም በታላቅ ደስታ ተቀበሉት በልቡም ጸለየ ብዙ ዝናብም ዘነበ ከዝናብ ብዛት የተነሣ ምድሪቱ ትጠፋለች ብለው እስቲአስቡ ድረስ ሁለት መዓልት ሁለት ሌሊት እየዘነበ ኖረ። እጅግም ፈርተው አባታችን ሆይ ዝናቡን አስወግዶ በልክ ይሆን ዘንድ እንዳንጠፋ ስለ እኛ ወደ እግዚአብሔር ጸልይ ብለው ለመኑት ያንጊዜም ጸለየ ዝናቡም በርቶ በእግዚአብሔር ቸርነት ፀሐይ ወጣላቸው።
ይህም አባት ብዙ ታላላቅ ትሩፋቶችን ሠርቷል እግዚአብሔርም በእጆቹ ድንቆች ተአምራትን ገለጠ ርኵሳን አጋንንት ያደሩባቸውንና ብዙዎች በሽተኞችን አዳናቸው። ይህ አባትም የሠራቸውን በጎ ሥራዎች ሊቆጥራቸው የሚችል የለም አንድ ሰው በጎ ሥራ እንደሠራ የሰማ እንደሆነ ሰውዬው እንደሠራው እስከሚሠራ አይተኛም።
የክብር ባለቤት ስለሆነ ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም ክብር ምራቁን ሳይተፋ ስልሳ ዓመት ኖረ። መቶ ዓመት ከሆነውና ተጋድሎውን ከፈጸመ በኋላ በበጎ ሽምግልና አረፈ፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ይስሐቅ_ጻድቅ
በዚህች ቀን ከግብጽ ደቡብ ዳፍራ ከሚባል አገር የከበረ አባ ይስሐቅ ምስክር ሁኖ አረፈ። ለዚህም ቅዱስ በሌሊት ራእይ የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጾለት የሰማዕትነትን አክሊል ትቀበል ዘንድ ጣዋ ወደሚባል አገር ሒድ አለው።
ከዚያም በነጋ ጊዜ ከመሔዱ በፊት አባትና እናቱን ሊሰናበታቸው ተነሣ። ሁለተኛም የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ ከአገሩ እስከ አወጣውና ሀገረ ጣዋ እስካደረሰው ድረስ እነርሱ በላዩ እያለቀሱ አልለቀቁትም።
በደረሰም ጊዜ መኰንኑን በዚያ ከውሽባ ቤት አገኘው ከዚያም በወጣ ጊዜ በክብር ባለቤት በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ የማምን እኔ ክርስቲያን ነኝ ብሎ በመኰንኑ ፊት በግልጽ ጮኸ።
ከኒቅዩስ ሀገርም እስኪመለስ ቅዱሱን ወስዶ እንዲጠብቀው ከወታደሮች አንዱን አዘዘው ከዚያ ወታደርም ጋራ ቅዱስ ይስሐቅ አልፎ ሲሔድ በመንገድ ዳር የተቀመጠ አንድ ዕውር የእግዚአብሔር ቅዱስ ሆይ ይቅር በለኝ ዐይኖቼንም አድንልኝ ብሎ ለመነው። አባ ይስሐቅም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ስለዚያ ዕውር ለመነው ያን ጊዜም ዐይኖቹ ተገለጡ። ይህንንም ድንቅ ተአምር ወታደሩ አይቶ የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምኖ የክርስቲያን ወገን ሆነ።
መኰንኑም በተመለሰ ጊዜ ያ ወታደር በመኰንኑ ፊት የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ በመታመን ሰማዕት ሁኖ አክሊል ተቀበለ።
ከዚህም በኋላ መኰንኑ ቅዱስ ይስሐቅን ጽኑ ሥቃይን አሠቃይቶ ወደ ሀገረ ብህንሳ ሰደደው በዚያም አሠቃዩት። በመርከብም ሲወስዱት የጽዋ ወኃን ለመናቸው ከቀዛፊዎችም አንዱ አንድ ዐይኑ የታወረ ውኃን በጽዋ ሰጠው የከበረ ይስሐቅም ያን ውኃ በላዩ ረጨ ዐይኑም ድና እንደ ሌላዪቱ ሆነች።
ጽኑ ሥቃይን የሚአሠቃዩት የብህንሳ ሀገር ሰዎችም ይህን ድንቅ ሥራ በአዩ ጊዜ ወደ መኰንኑ ወሰዱትና ብትገድለውም ብትተወውም አንተ ታውቃለህ አሉት። መኰንኑ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ ወዲያውኑ አዘዘ የከበረች ራሱንም ቆረጡት የምስክርነት አክሊልንም ተቀበለ።
በዚያም ምእመናን ሰዎች ነበሩ የአባ ይስሐቅንም ሥጋ በሠረገላ ጭነው በበሮች እያሳቡ ዳፍራ ወደተባለ አገሩ አደረሱት ያሻግሩትም ዘንድ መርከብ ባላገኙ ጊዜ ተሸክመው አሻግረው ወደ ቤቱ አደረሱት። ቤቱንም አፍርሰው በስሙ ቤተ ክርስቲያን አድርገው ሠሩዋት ሥጋውንም በውስጥዋ አኖሩ ከእርሱም የሚያስደንቁ ብዙዎች ተአምራት ተገለጡ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_ዲላጊና_አራት_ሴት_ልጆቿ
🔴#ስንክሳር ግንቦት_5
#ቅዱስ_ኤርምያስ_ነቢይ
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ግንቦት አምስት በዚች ቀን የካህኑ ኬልቅዩ ልጅ ታላቅ ነቢይ ኤርምያስ አረፈ። ይህም እውነተኛ ነቢይ የአሞጽ ልጅ የይሁዳ ንጉሥ ኢዮስያስ በነገሠ በዐሥራ ሦስት ዓመቱ ማስተማር ጀመረ።
ከዚያም በይሁዳ ንጉሥ በኢዮስያስ ልጅ በኢዮአቄም ዘመን ዐሠራ አንዱ የሴዴቅያስ ዘመነ መንግሥቱ እስከሚፈጸም በአምስተኛው ወር ኢየሩሳሌም እስከ ተማረከችበት ጊዜ ያስተምር ነበር።
ስለ ራሱ እንዲህ ሲል ራሱ ተናገረ የእግዚአብሔር ቃል ወደኔ መጣ እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ "በእናትህ ማሕፀን ሳልፈጥርህ ወደድኩህ ከእናትህም ማሕፀን ሳትወጣ መረጥኩህ ለአሕዛብም መምህር አደረግሁህ አለኝ።" ይህም ነቢይ የእግዚአብሔርን አምልኮና ሕጉን በመተዋቸው እንዲህ ሲል የእስራኤልን ልጆች ገሠጻቸው። ተጠበቁ ንስሐም ግቡ የእግዚአብሔር ቁጣው በላያችሁ እንዳይመጣ።
ሁለተኛም እንዲህ ብሎ አስረዳቸው ወደ ፈጣሪያችሁ እግዚአብሔር ካልተመለሳችሁ ያለዚያ የከላውዴዎንን ንጉሥ ናቡከደነጾርን በላያችሁ እርሱ ያሥነሣዋል ይማርካችኋልም እንደቃሉም ሆነ። ሁለተኛም ሕዝቡ ተማርከው ሰባ ዘመን እንደሚኖሩ ትንቢት ተናገረ።
ደግሞ የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ለኩነተ ሥጋ እንደሚመጣና መከራ እንደሚቀበል የአስቆሮቱ ይሁዳ እንደሚሸጠውና ሠላሳ ብር እንደሚወስድ ተናገረ። ስለ ብዙ ሥራዎችም ተናገረ አይሁድ ግን ሊገድሉት ወደው ገርፈው አሥረው በጒድጓድ ውሰጥ ጣሉት እግዚአብሔርም አዳነው። እርሱ ግን ስለእነርሱ ይለምንና ይማልድ ነበር እግዚአብሔርም ስለ እርሳቸው ወደእኔ አትማልድ እነርሱ ከክፋታቸው አይመለሱምና አለው።
ናቡከደነጾርም የኢየሩሳሌምን ሕዝብ በማረከ ጊዜ ከእሳቸው ጋራ አልማረከውም። ነገር ግን ከምርኮ የቀሩት ወደ ግብጽ አገር ወሰዱት የግብጽን ሰዎች ሲያጠፉአቸው የነበሩ በግብጽ ወንዞች የሚኖሩ አራዊትን በእርሱ ጸሎት እግዚአብሔር አጠፋቸው።
ከዚያም ወደ ባቢሎን አገር ወሰዱት በዚያም የእስራኤል ልጆች ከምርኮ እስኪመለሱ ትንቢት እየተናገረ ሕዝቡን ሲአስተምር ኖረ። የትንቢቱ ወራትም በተፈጸመ ጊዜ አይሁድ በደንጊያዎች ወገሩት ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በነቢዩ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። https://t.me/finotebirhan12
ነው፡፡
ከዚህ በኋላም አባታችን ተክለ ሃይማኖት ሦስት የብርሃን አክሊሎችና የወርቅ ዘውድ ተቀዳጅቶ ተገለጠለት፡፡ የብርሃን ልብሶችን ለብሶ የመስቀል ምልክት ያለው በትርም ተመርኩዞ ፊቱም እንደ እግዚአብሔር መልአክ እያበራ መጣና ወደ አባታችን መልከ ጼዴቅ ቀርቦም "ልጄ ሆይ ሰላም ለአንተ ይሁን" አለው፡፡ አባታችን መልከ ጼዴቅም መልሶ "የእግዚአብሔር ሰላም ከአንተ ጋር ይሁን አንተ ማነህ አለው፡፡ "እኔ ከእናቴ ማኀፀን ጀምሮ መድኃኒዓለም የመረጠኝ ተክለ ሃይማኖት ብሎም የሰየመኝ ፍሰሐ ጽዮን ነኝ" አለው፡፡ ያንጊዜም ከእግሩ በታች ወደቅሁ ከኔ ጋር የነበረው የእግዚአብሔር መልአክ አነሣኝ አቡነ ተክለ ሃይማኖት "የዳሞት ንጉሥ ሞተለሚ እንዴት እንዳደረገው የጣዖት ማምለኪያዎችን እንዴት እንዳጠፋ ብዙ ሰዎችን በክርስቶስ እንዴት እንደአሳመነ" ያን ጊዜ ነገረኝ፡፡
ስለዚህም "እግዚአብሔር አከበረኝ ከፍ ከፍ አደረገኝ፤ የብዙዎችም አባት አደረገኝ፤ ልጄ ሆይ አንተም ጸንተህ ተጋደል የብዙዎች አባት ትሆናለህ፤ እግዚአብሔር ለመጋደል ያበርታህ ሰላምንም ይስጥህ"፡፡ ይህንም ብሎ ከእርሱ ተሠወረ፡፡ ከርሱ በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ አባታችን መልከ ጼዴቅ መጣና ወዳጄ ሆይ ሰላም ለአንተ ይሁን" አለው፡፡ መልከ ጼዴቅም "አንተ ማነህ" አለው፡፡ "እኔ የድንግል ማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነኝ" አለው፡፡ ያን ጊዜም ከእግሩ በታች ወደቀ፡፡ ጌታችንም እጁን ይዞ፡፡ አነሣውና "ጽና አትፍራ" አለው፡፡ ያን ጊዜም እናቱ ድንግል ማርያም፣ ከቅዱስ ሚካኤልና ከቅዱስ ገብርኤል፣ ከሱራፌልና ከኪሩቤል ጋር ከነቢያት፣ ከሐዋርያት ጋር፣ ከጻድቃንና ከሰማዕታት ጋር መጣች መድኃኔዓለምም አባታችን መልከ ጼዴቅን "ከእናትህ ማኀፀን ጀምሮ በምስክር ሁሉ ፊት መረጥሁህ ካህንም አደረግሁህ ዛሬም የብዙዎቹ አባት አደርግሃለሁ፡፡ ኃጢአተኞችንም የምትመልስ ትሆናለህ፡፡ ያልጠቆረ ብሩህ አክሊልና በሰው እጅ ያልተሠሩ የብርሃን ልብሶችን እሰጥሃለሁ፡፡ ርስትህ ከአጥማቂዬ ከቅዱስ ዮሐንስ ጋር ይሁን፤ ሹመትህም ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይና ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ጋር ይሁን፣ ስምህም የኔ ምሳሌ በሆነው መልከ ጼዴቅ ይሁን" አለው፡፡
የመጀመሪያው በጥምቀት የተሰጠው ስሙ ኀሩየ ወልድ (በወልድ የተመረ) የሚል ነበርና ያን ጊዜም ቁመታቸው እስከ ሰማይ የሚደርስ ብርሃናቸው እንደ ፀሐይ የሚያበራ፤ ሦስት የወርቅ መስቀሎችን ሰጠው" በላያቸው ላይ ውጣ" አለኝ፤ እኔም በእያንዳንዳቸው ላይ ሦስት ጊዜ ወጣሁ እስከ አርያምም አገቡኝ፡፡ በዚያም የእግዚአብሔርን መንበር አየሁ፡፡ በአንድነት በሦስትነት የሚኖር የዘመናት ጌታም በላይ ተቀምጧል፡፡ ይህም ነገር እጅግ ድንቅ ነው ወልድ በምድር ላይ ከእርሱ ጋራ እየተነጋገረ ሳለ በአርያም ደግሞ በሦስትነቱ ተቀምጦ አየሁ፡፡ ጌታም ሥርዓትህ እንዲሁ እንዳየኸው ይሁን፤ እስከ ዕለት ዕረፍትህም ድረስ ስለ ገድልህ ጽናት የሚሆን ሰጥቼሃለሁ" አለው፡፡ በጸሎቱ የተማጸነውን እንደሚምርለትና ሌላም ብዙ ቃል ኪዳን ሰጠው፡፡ "እኔም ከአንተ አልለይም፣ መላአክቶቼም ይጠብቁሃል" አለው፡፡ መልከ ጼዴቅም ይህንን በሰማ ጊዜ በፊቱ ሰገደ፡፡ "አቤቱ ለእኔ ለኃጢአተኛው አገልጋይህ ይህን ሁሉ ክብር የሰጠኸኝ ጌታ ሆይ መንግሥትህ ይባረክ" አለው፡፡ ጌታችንም ባርኮት በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ፡፡
አባታች መልከ ጼዴቅ እንደዝህ በብዙ ተጋድሎ ሲኖሩ ዕረፍታቸው ሲደርስ ትንሽ በተቅማጥ በሽታ ታመሙ ያንጊዜም ጌታችን እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ከቅዱሳን መላእክቶች ጋር መጣች፡፡ መላእክትንና ቀደምት አባቶችን፣ ነቢያትንና ሐዋርያትን፣ ጻደቃን ሰማዕታትን፣ ቀሳውስትና ዲያቆናትን፣ ደናግልና መነኮሳትን፣ ወንዶችንና ሴቶችን ሕፃናትንም ምስክሮች አድርጎ አቆመ፡፡ ሄሮድስ ያስገደላቸው 144,000 ሕፃናት ከአለቃቸው ከቅዱስ ቂርቆስ ጋር መጡ፡፡ "በእኔና በአንተ መካከል እነዚህ ሁሉ ምስክሮች ይሁኑ፤ ስምህን የጠራ፣ መታሰቢያህን ያደረገ፣ በእጅህ የተጠመቀ፣ በቃልህ የተናዘዘና በእጅህ የተሳለመ ምሬልሃለሁ፤ የገድልህን መጽሐፍ የጻፈውና ያጻፈውን ምሬልሃለሁ ከአንተም ጋር ርስት እሰጠዋለሁ፤ የቤትህ ልጆች መንግሥተ ሰማያትን ከአንተ ጋር ይውረሱ" አለው፡፡ ዳግመኛም "ለምህረት ያልጠራኋትን ነፍስ ለመሳለምም ሆነ ለመባረክ ወይም ለመናዘዝ ወደ አንተ አላቀርብም፤ ከኃጥአንም ወገን አንተ ስለ እነርሱ ከለመንኸኝ እምርልሃለሁ" ብሎ ቃል ኪዳን ገባላቸው። አባታችንም በዚህች ቀን ነፍሳቸው ከስጋቸው ተለየች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ዮሐንስ_ሊቀ_ጳጳሳት
በዚህች ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሀያ ዘጠነኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስ አረፈ። እርሱም ከእስክንድርያ አገር ነው ከታናሽነቱም በአስቄጥስ በአባ መቃርስ ገዳም መንኲሶ በተጋድሎ ኖረ።
ከእርሱ አስቀድሞ የነበረ አባ አትናቴዎስም በአረፈ ጊዜ አዋቂዎች ኤጲስቆጶሳት ሕዝቡም ሁሉ መረጡት። ወስደውም በግድ ተሾም አሉት እርሱ ግን አልፈለገም የክርስቶስን መንጋ እንዳይተው ሌላ ተሹሞ በክርስቶስ መንጋዎች ላይ ጥፋት እንዳያመጣ ብዙ ልመናዎችን ለመኑት አዋቂዎች ኤጲስቆጶሳትና መምህራን ሁሉ አጽንተው ሲለምኑት በአየ ጊዜ ፈራ ይህ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፈቃድ ይሆን ብሎ አሰበ።
ከዚህም በኋላ ሊቀ ጵጵስና ሾሙትና በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበር ላይ ተቀመጠ። ስለ መንጋዎቹም ጥበቃ አሰበ ደግሞ ስለ ትምህርት መጻሕፍትንም ስለ ማንብበ በቀናች ሃይማኖትም የሚያጸናቸው ሆነ ምሁራን ካህናትንም ኤጲስቆጶሳትን አድርጎ ሾማቸው።
በዚያ ወራትም ስሙ ዘይኑን የሚባል እግዚአብሔርን የሚፈራ ደግ ንጉሥ ነበረ። ይህንንም ቅዱስ ስለረዳው ሥልጣኑ በሀገሮች ላይ ተዳረሰ የቀናች ሃይማኖትም በግብጽ አገሮች ሁሉ ላይ ተዘረጋች።
በዚያም ወራት ስንዴና ወይን ዘይትም የተመሉ ብዙ እንቅቦችን ለአብያተ ክርስቲያናትና ለገዳማት ለፍላጎታቸው ንጉሥ ዘይኑን ላከ። ለዚህም አባት ዘመኑ ሁሉ ጸጥታና ሰላም ሆነ። ጌታችንም በሥራው ሁሉ ተደሰተለት ከዚህም በኋላ በቸርነቱ ጐበኘውና ጥቂት ታመመ በሹመቱም ስምንት ዓመት ከኖረ በኋላ በሰላም አረፈ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ግንቦት_4
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ግንቦት አራት በዚህች ቀን ኢትዮዽያዊ ጻድቅ #አቡነ_መልከ_ጼዴቅ_ዘሚዳ ዕረፍታቸው ነው፣ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_ዮሐንስ አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_መልከ_ጼዴቅ_ዘሚዳ
ግንቦት አራት በዚህች ቀን ኢትዮዽያዊ ጻድቅ አቡነ መልከ ጼዴቅ ዘሚዳ ዕረፍታቸው ነው፡፡ እኚህ ጻድቅ ከከበሩና ነገሥታት ከሆኑት ወገን በአገረ ጐጃም ኢናይ በምትባል ቦታ የካቲት አሥራ ስድስት ቀን ተወለዱ፡፡ ልደታቸውም እንዲህ ነበር፡፡
ንጉሥ አምደ ጽዮን ምስረነዓዳን ወለዱ፣ ምስረነዓዳም በዝራምበሳን ወለደች፣ በዝራምበሳም ፍሬጽዮንን ወለደ፣ ፍሬጽዮንም መልከ ጼዴቅን ወለደ የእናታቸውም ስም ቅድስት ዓመተ ማርያም ነው፡፡ በተወለዱም ጊዜም በአባትና በእናታቸው ቤት ታላቅ ደስታ ሆነ እግዚአብሔር ለብዙዎች አባት አድርጎ መርጦአቸዋልና፡፡
ለትምህርት በደረሱም ጊዜ መዝሙረ ዳዊት ይማሩ ዘንድ አባትና እናታቸው ለመምህር ሰጧቸው ፡፡ እርሳቸውም አምቢ ብለው ወደ አባትና እናታቸው ቤት ተመለሱ ፡፡ ፈረስ ጋላቢም ሆኑ፡፡ ደግሞ እኚህ ጻድቅ በጐለመሱ ጊዜ አባትና እናታቸው መልኳ የምታምር ሚስት አጩላቸው፡፡ የአባታቸውንም ሹመት የንጉሥ ሠራዊት አለቃ ሆነው ተሾሙ፡፡ በልባቸውም ሰሎሞን እንደተናገረው "ከፀሐይ በታች ያለው ሁሉ ከንቱ እንደሆነ አሰቡ" "በምድር ላይ ቋሚ የፀና ሕይወት የለምና" ይህንም ብለው ከአባትና ከእናታቸው ቤት ተሰደዱ፡፡ የእግዚአብሔርም መልአክ እየመራቸው ቅጽሮ ወደሚባል አገር ደረሱ የበሩም ጠባቂዎች አባታችን መልከ ጼዴቅን ከተሸከሟቸው ሁለት የወርቅ ልብሶች ጋር አቆሙአቸው "አትሻገር ተመለስ" አሏቸው፡፡ ያ የበር ጠባቂ የሆነ ሰውም "ለሌላው እስከምመለስ ጠብቀው" አላቸው ይህን ብሎም ይረዷቸው ዘንድ ጓደኞቹን ሊጠራ ሄደ የሚመራው መልአክም መልከ ጼዴቅ "ከወርቅህ ጋር ከዚህ ሂድ" አላቸው ልብሶቻቸውንም ተሸክመው ሄዱ፡፡ ይመራቸው የነበረ የእግዚአብሔር መልአክም እነዚህን የበርሃ ጠባቂዎች እንደ ድንጋይ የፈዘዙ እንደበድን የደነዘዙ አደረጋቸው፡፡ መናገርም ተሳናቸው፡፡
ከዚህ በኋላም የኢዮስያስ ቦታ ወደ ሆነችው ደጋዳሞት ደብረ ምዕራፍ ደረሱ፡፡ ከአባታችን ኢዮስያስ ቀጥሎ (በኋላ) በተሾሙት በአባታችን በአቡነ አሮን እጅ በዚያ መነኰሱ እርሳቸው አስቀድመው በስውር መንኩሰው ነበርና፡፡ አባታችን አቡነ አሮን ንዑድ ክቡር ለሚሆን መልከ ጼዴቅ የምንኩስናን ልብስ አለበሳቸው፡፡
ከዚህም በኋላ አባትና ወንድሞቹ ዘመዶቹም ኤናይ ከምትባል አገሩ እየፈለጉ መጡ፡፡ በመንፈስ ቅዱስም ፈቃድ ተሰወራቸው አላገኙትም አባታችን አሮንንም ይዘው "ልጃችን አባት እናቱን እጮኛውንና ሹመቱን ትቶ ወደ አንተ መጥቷልና ስጠን" አሉት፡፡ አባታችን አሮንም ቅዱስ መልከ ጼዴቅ እንደመነኰሰ ነገራቸው፡፡ ያን ጊዜም አባትና እናቱ ወንድሞቹና ዘመዶቹ ታላቅ ለቅሶን አለቀሱ አዘኑ "ወዮልን ወዮልን ክብራችን ፈርሶአልና ኃይላችንም ተሽሮአልና ወልደን እንደ አልወለድንም ሆነናልና" አሉ፡፡ ከአባታችን ከአቡነ አሮን ጋር አስታረቋቸው አባቱም ያን ጊዜ "የእግዚአብሔር ፈቃድ ይሁን" አለ አስቀድሞ ቅዱሳንን ሲጎበኝና ለነዳያን ሲራራላቸው ባየሁ ጊዜ ይህ ልጅ መነኩሴ እንደሚሆን በልቤ አስብ ነበር፡፡ ትተውትም ወደ አገራቸው ሄዱ፡፡ ከዚህ በኋላም የእግዚአብሔር መልአክ ክቡር መልከ ጼድቅን በዚያ ወስዶ ደብረ መድኃኒት አደረሳቸው፡፡ በዚያም ከቀሲስ አስጢፋኖስ የዳዊትን መዝሙርና የመጻሕፍትን ቃል እየተማሩ ተቀመጡ፡፡ ፈጥነውም ጨረሱ መንፈስ ቅዱስ በእርሳቸው ላይ ይናገራልና፡፡
ከዚህ በኋላ ከትንሽ ዋሻ ገቡ የአምላካቸውን የክርስቶስን መከራ በማሰብ በዚያ ገብተው ቀንና ሌሊት ዘግተው በረደኝ ፀሐይ ልሙቅ፣ ጨለመኝ ብርሃን ልይ ሳይሉ በጸሎት ብቻ ዘግተው በመኖር ራሳቸውን በችንካር እያቆሰሉና ጭንቅላታቸውን እያተሉ ትሉን ለሰማይ አእዋፍ ይመግቡ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ወልድ የተገረፈውን ግርፋት እያሰቡ በየቀኑ እስከ ሦስት ሺህ ድረስ ይሰግዳሉ፡፡ ሰውነታቸውንም እንዲሁ ይገርፋሉ፡፡ የክርስቶስን መቸንከር እያሰቡ እጅና እግራቸውን፣ ወገብና ደረታቸውን በብረት ቸንክረው መከራውን ያስባሉ፡፡
ጎኑ በጦር መወጋቱን አስበው አጥንታቸው እስኪሰበር ድረስ ጎናቸውን ወጉ፤ ሐሞትና ከርቤ መጠጣቱን አስበው እርሳቸውም መራራ ይጠጡና እንክርዳድን ይመገባሉ፤ ሞቱን አስበው ደም እንባን ያነባሉ፤ ብፁዕ መልከ ጼዴቅ በቀንና በሌሊት በጾምና በጸሎት ይጋደሉ ዘንድ ጀመሩ፡፡ የዳዊትን መዝሙር በየቀኑ ሦስት ጊዜ ይጸልዩ፣ እየተጋደሉም አርባ መዓልትን ቆዩ፤ ሌሊትም ራቁታቸውን ማቅ ብቻ ለብሰው ከባህር ውስጥ ይቆማሉ፡፡ በነጋም ጊዜ ወደ በዓታቸው ይመለሳሉ፡፡ በየዓመቱም አራት ጊዜ እንዲህ ያደርጋሉ፡፡ በየዓመቱም አርባ ቀን እህል ሳይበሉ ወይን ሳይጠጡ፣ ከቅጠልና ከእንጨት ፍሬ ከሣርም ፍሬ የፅዋው ቁመት በትንሽ ጣት ልክ ከተሰፈረ ጥቂት ውኃ በስተቀር እንደዚህ እየተጋደሉ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል በደብረ መድኃኒት ሰባት ዓመት ኖሩ፡፡ የእግዚአብሔርም መልአክ ይጠብቃቸው ነበር፡፡ በእንደዚህ ዓይነቱ ተጋድሎ የክርስቶስን መከራ እያሰቡ ነቢያትን፣ ሐዋርያትን፣ ሰማዕታትን ደናግል መነኰሳትን መስለው ሁሉን እያከናወኑ እያለ የወዳጆቹን መከራ የማይዘነጋ፣ የሰውን የድካሙን ዋጋ ፈጽሞ የማያስቀር አምላክ ሠራዊተ መላእክትን አስከትሎ መጥቶ "መገረፍህ ስለ እኔ መገረፍ ይሁንልህ፤ የደምህ መፍሰስ ስለ እኔ ደም መፍሰስ ይሁንልህ፤ መቸንከርህም ስለ እኔ መቸንከር ይሁንልህ፤ ሞትህም ስለ እኔ ሞት ይሁንልህ" ብሎ ቃል ኪዳን ገባላቸው፡፡ "ከዚህ ቦታ መጥቶ የተሳለመውን እምርልሃለሁ ነፍሱ በአንተ ቃል ኪዳን የማይማር በአንተ ቦታ ለመሳለምም፣ ንሰሐ ለመግባትም ሆነ ለመቀበር አላቀርብብህም፣ መጥቶም የተቀበረውን ሥጋውን አፈር አይበላውም" የሚል እጅግ ድንቅ ቃል ኪዳን መድኃኒዓለም ሰጣቸው እስከ ዕለተ ምጽዓትም ሲታይ ይኖራል፡፡ በደጃቸው የተቀበረ ሰው አይበሰብስም፡፡
የእግዚአብሔር መልአክ አባታችን መልከ ጼጼቅን "በግራሪያ አገር ወደምትገኝ የቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ደብር ወደሆነች ወደ ደብረ ሊባኖስ ሂድ" አለው፡፡ አባታችን መልከ ጼዴቅም በዚህ መልአክ ትዕዛዝ ሄዱ ደብረ ሊባኖስ ደረሱና በዚያ እያሉ ቅዱሳንን እጅ ነሷቸው ከንቡረ ዕድ እንድርያስ ጋርም ተቀመጡ፡፡ ትንሽ ዋሻ በዓትን ሰጡዋቸውና "ትዕዛዛቱን ለመጠበቅ እግዚአብሔር ያጽናህ የገድልህንም ፍጻሜ ይሰጥህ" አላቸው፡፡ አባታችን እንድርያስ በእሱ ላይ በባረከ ጊዜም አባታችን መልከ ጼዴቅ ወደ በዓቱ ገብቶ ምስጋና ጸሎትና ስግደት ተግቶ ያዘ፡፡ እንደ መጀመሪያውም ታስሮ እያለ በየለቱ እስከ ሦስት ሺህ ስግደት ይሰግድ ነበር፡፡ ደሙም በምድር ላይ እስከሚፈስ ድረስ መንታ በሆነ የገመድ ጅራፍ ሰውነቱን ይገርፍ ነበር፡፡ እንባውም እንደክረምት ነጠብጣብ ይፈስ ነበር፤ የዓይኑ ብሌን እስኪገለበጥ ድረስ ያነባ ነበር፡፡ የሥጋውንም ቁስል እንደ መርፌ ሰርስሮ ወደ ውስጥ አካሉ እስኪገባ ድረስ በማቅ ፀጉር ይሰቀስቅና ይደመድም ነበር፡፡ እንዲህ ሆኖ መከራ ሲቀበልም ከእግዚአብሔር ምሥጋና ዝም አይልም ሥራውንም ፈጽሞ ያደንቅ ነበር፡፡ "ጌታ ሆይ የተኛሁትን አንቃኝ የደከምሁትን አበርታኝ የጨለምሁትን እኔን አብራልኝ" ይል ነበር፡፡ ይህንንም የሚለው ለራሱ ብቻ አይደለም ስለዓለም ሁሉ ነበር እንጅ እሱስ በኢየሩሳሌም ከሐዋርያት ጋርና በዓርያም ካሉ ከሱራፌል ጋር በክህነት የሚያገለግል ፍጹም ንጹሕና ጻድቅ ሰው
🔴#ስንክሳር ግንቦት_3
#ቅዱስ_ያሶን_ሐዋርያ
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ግንቦት ሦስት በዚች ቀን ጌታ ከመረጣቸው ከሰባ ሁለቱ አርድእት ውስጥ የሆነ ሐዋርያው ቅዱስ ያሶን አረፈ። ይህም ቅዱስ ከሐዋርያት ጋራ ወንጌልን በሰበከ ጊዜ ብዙ መከራዎችን በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተቀበለ ድንቆች ተአምራትንም አደረገ በሃምሳኛው ቀን ከሐዋርያት ጋራ አጽናኝ መንፈስ ቅዱስን ተቀብሏልና።
ትውልዱም ከጠርሴስ አገር ነው ከጠርሴስም ሰዎች አስቀድሞ አመነ ሐዋርያ ጳውሎስም ከተጠራና ከአመነ በኋላ በብዙ አገሮች ተከትሎ በወንጌል ትምህርት አገለገለው በተሰሎንቄ ከተማም ከጳውሎስ ጋራ ይዘው በመጐተት ከተሰሎንቄ ገዢ ዘንድ አቀረቡአቸው።
ከዚህም በኋላ በጠርሴስ አገር ቅዱስ ጳውሎስ ኤጲስቆጶስነት ሾመው የወልደ እግዚአብሔርንም ቤተ ክርስቲያን በመልካም አጠባበቅ በቅንነት ጠበቀ። ምእመናንን በቀናች ሃይማኖት ከአጸናቸውና በጎ ምግባርን ከአስተማራቸው በኋላ ከዚያ ወደ ምዕራብ አገር ሒዶ በውስጥዋ የከበረ ወንጌልን አስተማረ። ስሟ ኮራኮራስ ወደምትባል ደሴትም ደርሶ በውስጧ ወንጌልን ሰበከ እግዚአብሔርንም ወደማወቅ መለሳቸው በዲያቆናት አለቃ በሰማዕታትም መጀመሪያ በከበረ ሐዋርያ እስጢፋኖስ ስም በውስጧ ቤተ ክርስቲያን ሠራላቸው።
የዚያች አገር ገዥም በአወቀ ጊዜ ይዞ ከእሥር ቤት አስገባው በዚያም ሰባት ወንበዴዎችን አግኝቶ ሃይማኖትን አስተማራቸው በክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው። ከዚያም በኋላ በመኮንኑ ፊት ቁመው እኛ ክርስቲያን ነን በክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን ብለው ጮኹ። መኰንኑም ዝፍትና ዲን በተመላ ምጣድ ውስጥ አግብቶ አቃጠላቸው የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበሉ።
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ያሶንን ከእሥር ቤት አውጥቶ ብዙ አሠቃየው ነገር ግን ምንም ምን ጉዳት አልደረሰበትም። የንጉሡም ልጅ ከቤቷ መስኮት ሁና አይታ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነች ልብሶቿንና ጌጦቿን አውጥታ ለድኆችና ለምስኪኖች ሰጠችና ከዚያም በሐዋርያው በያሶን አምላክ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ታመነች አባቷም ሰምቶ እንዲአሥሩዋት አዘዘ እንዳዘዛቸውም አደረጉ። በጢስም አፍነው አሠቃዩዋት ደግመውም አራቈቷትና አባቷ በፍላፃ ነደፋት ነፍሷንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠች።
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ያሶንን ወደ ደሴት ሰደደው በደሴትም ውስጥ ያሠቃየው ዘንድ መኰንኑ ከሠራዊቱ ጋራ አብሮ በመርከብ ተሳፈረ እግዚአብሔርም ከሠራዊቱ ጋራ በባሕር አሠጠመው።
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ያሶን ወንጌልን እያስተማረ ብዙ ዘመናት ኖረ። ሁለተኛም ሌላ መኰንን ተሾመ ቅዱስ ያሶንንም ይዞ በምጣድም ውስጥ ድኝና ዝፍት ሰም መልቶ ነበልባሉ ወደ ላይ እስቲወጣ ድረስ ከበታቹ አነደደ ቅዱስ ያሶንንም በውስጡ ጨመረው። የክብር ባለቤት ጌታችንም አዳነው ምንም ምን ጉዳት አልደረሰበትም መኰንኑም ይህን ድንቅ ሥራ አይቶ በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቤተሰቡ ሁሉ ከሀገር ሰዎች ሁሉ ጋራ አመነ። ሁሉንም አጥምቆ የከበረ የወንጌልን ሕግና ትእዛዝ አስተማራቸው አብያተ ክርስቲያንም ሠራላቸው በውስጣቸውም ብዙ ድንቆች ተአምራትን አደረገ ብሩህ በሆነ ገድሉ ጌታችንን ደስ ካሰኘውና ካገለገለው በኋላ በበጎ ሽምግልና አረፈ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ሐዋርያ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ግንቦት 2
❖ ግንቦት 2 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
+"+ ቅዱስ ኢዮብ +"+
+የትዕግስት አባት ቅዱስ ኢዮብ በቅዱስ መጽሐፍ ላይ
እንደተመለከትነው ያልተፈተነበት ነገር የለም:: ሐረገ
ትውልዱም
ከአባታችን አብርሃም ይመዘዛል::
*አብርሃም ይስሐቅን
*ይስሐቅ ኤሳውን
*ኤሳው ራጉኤልን
*ራጉኤል ዛራን
*ዛራ ኢዮብን ይወልዳሉ::
+ቅዱስ ኢዮብ የነበረው እሥራኤል በግብፅ በባርነት ሳሉ
ነበር:: ኢዮብ ይሕ ቀረህ የማይሉት ባለጠጋ: ደግና
እግዚአብሔርን
አምላኪ ነበር:: የኢዮብ ደግነት የተመሰከረው በሰው
(በፍጡር) አንደበት አልነበረም:: በራሱ በፈጣሪ አንደበት
እንጂ::
+በዚህ የቀና ጠላት ዲያብሎስ ግን ኢዮብን ይፈትነው
ዘንድ ከአምላክ አስፈቀደ:: ጌታችን የጻድቁን የትዕግስት
መጠን
ሊገልጥ ወዷልና ሰይጣን ኢዮብን በሐብቱ መጣበት::
በአንድ ጀምበርም ድሃ ሆነ:: እርሱ ግን ፈጣሪውን ባረከ::
+ሰይጣን ቀጠለ:- የአብራኩን ክፋዮች (ልጆቹን)
አሳጣው:: ኢዮብ አሁንም አመሰገነ::
+በሦስተኛው ግን ሰውነቱን በቁስል መታው:: ቁስል ሲባል
በዘመኑ እንደምታዩት ዓይነት አልነበረም:: ከሰው ሕሊና
በላይ
የሆነ አሰጨናቂ ደዌ ነበር እንጂ:: ጻድቁ የአንድ ወጣት
እድሜ ያሕል በመከራው ጽናት እየተሰቃየ ገላውን በገል
ያከው
ነበር::ከአፉ ግን ተመስገን ማለትን አላቁዋረጠም::
+በመጨረሻም ሰይጣን በሚስቱ መጣበት::
"እግዚአብሔርን ተሳደብ" አለችው:: እርሱ ግን መለሰ:-
"እግዚአብሔር ሰጠ:
እግዚአብሔርም ነሣ: ስሙ የተባረከ ይሁን::"
+ከዚሕ ሁሉ ነገር በኋላ እግዚአብሔር ሰይጣንን ከጎዳናው
አስወገደው:: ጤናውን: ሐብቱን: ልጆቹን ለኢዮብ
መለሰለት::
ካለው እድሜ ላይ 140 ዓመት ጨመረለት:: ጻድቅና
የትዕግስት ሰው ቅዱስ ኢዮብ በ248 ዓመቱ በዚሕች ቀን
ዐረፈ::
=>እግዚአብሔር አምላክ ከጻድቁ ትዕግስትና በረከት
አይለየን::
❖ግንቦት 2 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ኢዮብ ጻድቅ (የትእግስት አባት)
2.አባ ቴዎድሮስ ሊቀ ምኔት (የታላቁ ቅዱስ ዻኩሚስ ደቀ
መዝሙርና የአቡነ አረጋዊ ጉዋደኛ)
3."22" ሰማዕታት (የአባ ኤሲ ማሕበር)
❖ወርኃዊ በዓላት
1፡ ቅዱስ ታዴዎስ ሐዋርያ
2፡ ቅዱስ ሳዊሮስ ዘአንጾኪያ
3፡ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ
4፡ ቅዱስ አቤል ጻድቅ
5፡ አባ ጳውሊ ገዳማዊ
6፡ አባ ሕርያቆስ ዘብሕንሳ
++"+ ወንድሞች ሆይ! የመከራና የትዕግስት ምሳሌ
የሆኑትን በጌታ ስም የተናገሩትን ነቢያትን ተመልከቱ::
እነሆ
በትዕግስት የጸኑትን ብጹዓን እንላቸዋለን:: ኢዮብ እንደ
ታገሠ ሰምታቹሃል:: ጌታም እንደፈጸመለት አይታቹሃል::
ጌታ እጅግ የሚምር: የሚራራም ነውና:: +"+ (ያዕ.
5:10)
<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>https://t.me/finotebirhan12
የሚንቁትና የሚጠሉት ‹‹ይህ የነገሩትን ቀለም እንኳን አከናውኖ መናገር የማይችል ዛሬስ እንግዳ ድርሰት እደርሳለው ብሎ አገኝ አጣውን የቆጥ የባጡን ይቀባጥራል›› ብለው ተደነቁበት፡፡ የሚወዱትና የሚያከብሩት ግን ‹‹ከመንፈስ ቅዱስ ነው እንጂ እንዲህ ያለ ምሥጢር ከእሩቅ ብዕሲ ይገኛልን!›› ብለው አደነቁለት፡፡ ወዲያው የሚወዱት የሚያከብሩት ‹‹ጽፈን ደጉሰን አንይዘውምን!?›› አሉ፡፡ የሚንቁት የሚጠሉት ደግሞ ‹‹ማን ተናገረው ብለን እንይዘዋለን?›› አሉ፡፡ እንደ ልማዱ አድርገን አንይዘውም አሉ፡፡ ለሃገራቸው እንግዳ ድርሰት የተደረሰ እንደሆነ ጽፈው ደጉሰው ከእሳት ይጥሉታል፡፡ ከእሳት ደህና ሆኖ የወጣ እንደሆነ ከውሃ ይጥሉታል፡፡ ከውኃም ደህና ሆኖ የወጣ እንደሆነ ከድውይ ሰው ላይ ይጥሉታል፡፡ ከእሳት ገብቶ ባይቃጠል፣ ከውኃ ገብቶ ባይርስ በመጨረሻም ድውይ የፈወሰ እንደሆነ ‹‹ደገኛ ድርሰት ነው›› ብለው ይይዙታል፡፡ ይህንንም ቅዳሴ ማርያምን ጽፈው ደጉሰው ከእሳት ላይ ጣሉት፣ ከእሳት ደህና ወጣ፡፡ ከውኃ ላይ ጣሉት-ከውኃ ደህና ሆኖ ወጣ፡፡ ከደውያን ላይ ጣሉት-ድውይ ፈወሰ፡፡ ይልቁንም ሙት አስነሣ፡፡ ከዚህም በኋላ ‹‹ደገኛ ድርሰት ነው›› ብለው ጽፈው ደጉሰው ይዘውታል፡፡ በጥራዝም 14ኛ አድርገው ጠርዘውታል፡፡ ቅዳሴ ከዚያ በፊት 13 ነበርና አሁን ግን 14ኛ አድርገው ጽፈውታል፡፡ በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ከ14ቱም ቅዳሴ ተአምራት ያልተደረገበት የለም፡፡
ይህም ቅዳሴ ማርያም ስለ እመቤታችን እጅግ በጠለቀ ሁኔታ የሚያመሰጥር በመሆኑ በሰሙነ ፍልሰታ ይተረጎማል፡፡ ዕለቱን የሚመለከቱ ምሥጢራትም በዕለቱ ይተረጎማሉ፡፡ ምሳሌ ነሐሴ ሦስት የበዓታና፣ ነሐሴ ሰባት የፅንሰታ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ የበዓታ ‹‹ድንግል ሆይ! አንገታቸውን እንደሚያገዝፉ እንደ ዕብራውያን ልጆች በጨዋታ ያደግሽ አይደለሽም፡፡ በቅድስና፣ በንጽሕና በቤተ መቅደስ ኖርሽ እንጂ…›› የሚለውን ይመለከቷል፡፡ ነሐሴ ሰባትም ‹‹ድንግል ሆይ! ኃጢአት በሆነ ሩካቤ የተፀነስሽ አይደለሽም….›› የሚለውን ይመለከቷል፡፡
አባ ሕርያቆስ የእመቤታችንን ቅዳሴ እጅግ ድንቅ አድርጎ ለመጀመሪያ ጊዜ የቀደሰው በልደቷ ቀን ነው፡፡ ይኸውስ እንዴት ታወቀ ቢሉ አንድ ምግባር ሃይማኖቱ የቀና በትሩፋት የበለጸገ ደገኛ ባሕታዊ ነበርና ከተጋድሎውና ለእመቤታችን ካለው ፍቅር የተነሣሳ እመቤታችን ተገለጠችለት፡፡ እርሱም ‹‹ከ33ቱ በዓላት ማንን ትወጃለሽ?›› ብሎ ጠየቃት፡፡ እመቤታችንም ‹‹ኪዳነ ምሕረትን፣ ልደታን፣ አስተርአዮን፣ ፍልሰታን›› አለችው፡፡ እርሱም ‹‹ከእነዚ ከ4ቱስ ማንን ትወጃለሽ?›› ቢላት እመቤታችን ‹‹ከጠባብ ወደ ሰፊ፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን የወጣሁበት ነውና ልደቴን እወዳለው›› አለችው፡፡ ‹‹ቀድሞ እኔ ሳልወለድ እናትና አባቴን መባችሁን አንቀበልም ብለው አዝነው ተክዘው ነበር፡፡ የእነርሱ ሃዘን ሃዘኔ ነውና እኔን ከወለዱ በኋላ መባቸውን ተቀብለዋቸው ደስ ብሎዋቸዋል፡፡ የእነርሱ ደስታ ደስታዬ ነውና›› ብላዋለች፡፡
ይህንን ድንቅ የሆነውን የአባ ሕርያቆስን ቅዳሴ እመቤታችን ለሌላኛው ወዳጇ ለኢትዮጵያዊው ማኅሌታይ ቅዱስ ያሬድ ገልጣለታለች፡፡ እመቤታችን ቅዱስ ኤፍሬምን ከሶርያ፣ አባ ሕርያቆስን ከብሕንሳ በደመና ጠቅሳ ቅዱስ ያሬድ ካለበት አድርሳ ‹‹አንተ ውዳሴዬን፣ አንተ ቅዳሴዬን ነግራችሁት በዜማ ያድርስ›› ብላቸው እነርሱም ለቅዱስ ያሬድ ነግረውት በዜማ አድርሶታል፡፡ ከዚሁም ጋር አያይዞ 13ቱንም ቅዳሴ በዜማ ደርሷል፡፡
በእመቤታችን በዓሏ ዕለት ጌታችን ተገልጦላቸው ቅዳሴዋን እንዲቀድሱ ነግሯቸው ለዚህም የሚሆን ከሰማይ ኅብስትና ጽዋ አውርዶላቸዋል፡፡ በዕለቱም ቅዳሴዋን ሲቀድሱ የከበሩ ሐዋርያት በቀኝ በግራ እየተራዷቸው ሲቀድሱ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ወርዶ ኅብስቱንና ጽዋውን ጋርዶታል፡፡ በሌላ ጊዜም አቡነ ሳሙኤል ጊዜአቸው ደርሶ ከማረፉ በፊት ቅዱስ ሚካኤል ነሐሴ 16 ቀን ወደ ገነት ነጥቆ ወስዶ ከእመቤታችን ፊት አቁሞ አስባርኳቸዋል፡፡
ቅዱሳን አባቶቻችን የእመቤታችንን ቅዳሴዋን ሲቀድሱ ከምድር ከፍ ብለው ይታዩ ነበር፡፡ የዋልድባው አቡነ ሳሙኤል ቅዳሴ ማርያምን እየደገሙ ሲሄዱ ክንድ ከስንዝር ከመሬት ከፍ ይሉ ብለው ይሄዱ ነበር፡፡ ከዕለታትም በአንደኛው ዕለት ውኃውን ቢባርኩት ውኃው ኅብስት ሆኖላቸው ተመግበው ምእመናንንም መግበዋቸዋል፡፡ እመቤታችንም የፍቅር ምልክት ሁለት ንዋያት ከጠቻቸው በኋላ ‹‹ውዳሴዬን ከቅዳሴዬ ጋራ አንድ አድርጎ የሚደግመውን ሰው አንተ ከገባህበት ውሳጤ መንጦላዕት አገባዋለው›› ብላ ተስፋቸውን ነግራዋለች፡፡ ይህንንም መሠረት ነማድረግ ልጆቻው ዛሬ በዋልድባ ያጠና በቃሉ፣ ያላጠና በመጽሃፍ ውዳሴዋንና ቅዳሴዋን ሳይደግም የሚውል የለም፡፡ ይህም ተስፋ ውዳሴዋን ከቅዳሴዋ ጋር አንድ አድርጎ ለሚደግም ሰው ሁሉ ነው እንጂ ለእነርሱ ብቻ አይደለም፡፡ ዳግመኛም ሃይማኖት ምግባሩ የቀና ያ ደገኛ ባሕታዊ እመቤታችንን ‹‹ከምስጋናሽ ሁሉ ማንን ትወጃለሽ?›› ብሎ ቢጠይቃት እርሷም ‹‹ልጄ ዳዊትን፣ አቡነ ዘበሰማያትን ቢደግሙለት እንዲወድ እኔም ውዳሴዬን ቅዳሴዬን ቢደግሙልኝ ወዳለሁ›› ብላዋለች፡፡
አባ ሕርያቆስ የብርሃን እናቱ እመቤታችን ድንቅ ምሥጢርን ከገለጠችለትና ከባረከችው በኋላ በዘመኑ ቁጥር አንድ ሊቅ ሆኖ እጅግ ብዙ ድርሳናትን ደርሷል፡፡ ቁጥራቸው እጅግ የበዙ ተግሣጻትን ጽፏል፡፡ አጠቃላይ ድርሰቶቹ ከ10 ሺህ በላይ ናቸው፡፡ በእንዲህ ያለ ንጽሕናና ቅድስና ሲያገለግል ኖሮ ጥቅምት 2 በሰላም ዐርፏል፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፤ የእመቤታችን ድንግል ማርያም ጣዕሟ: ፍቅሯ: ጸጋዋና በረከቷ ይደርብን::https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ግንቦት_1
በግንቦት አንድ በዚህችም ቀን አምላክን የወለደች #እመቤታችን_ቅድስት_ድንግል_ማርያም ተወለደች፣ የከበረ #አባ_ሕርያቆስ ዘሃገረ ብሕንሳ የእመቤታችንን ቅዳሴ የደረሰበት ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ልደታ_ለማርያም
በግንቦት አንድ በዚህችም ቀን አምላክን የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደች እርሷም ለሰው ሁሉ ወገን ድኀነት የሆነባት ናት። ከወንዶች ወገን የከበረ አባቷም ስሙ ኢያቄም ከሴቶች ወገን የከበረች ሚስቱ ሐና ይባላሉ። ሁለቱም ልጅ በማጣት ሲያዝኑ ኖሩ በዚያ ወራት የመካኖችን መብዓ ካህናቱ አይቅበሉም ነበርና።
እነርሱም ከሰው የሚደርስባቸውን ሽሙጥና ኅዘናቸውን ያርቅላቸው ዘንድ በቀንና በሌሊት ወደ እግዚአብሔር ፈጽሞ ይማልዱ ነበር። ሰውን የሚወድ እግዚአብሔርም ከዘራቸው ለዓለሙ ሁሉ መድኃኒት ይሆን ዘንድ መልካም የሆነ ኀሳባቸውን ተመለከተ።
ክቡር እያቄምም አርባ ቀን እስኪፈጸም በተራራ ውስጥ ቁሞ ሲጸልይ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ተገለጸለትና ለዓለሙ ሁሉ ድኀነት የሚደረግባት ዘር እንደሚሰጠው አበሠረው።
በፍጹም ልብ አምኖ ከተራራው ወረደ ለተመሰገነች ሚስቱ ለሐናም ከእግዚአብሔር መልአክ የሰማውን ያንን ራእይ ነገራት ቃሉ እውነት እንደሆነ እርሷም አመነች ልዑል እግዚአብሔርንም አመሰገኑት።
የተመሰገነች ቅድስት ሐናም ከእርሷ የሚወለደውን በዘመኑ ሁሉ ለቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ ታደርገው ዘንድ ለእግዚአብሔር ስለትን ተሳለች። ከዚህም በኋላ ይቺን የከበረች ሕፃን ፀንሳ ወለደች ስሟንም ማርያም ብላ ሰየመቻት ትርጓሜውም እመቤት ነው ደግሞም ሀብትና ስጦታ ማለት ነው።
በእውነት የዓለሙ ሁሉ እመቤት ናት ሁላችን በእርሷ ሰማያዊ ሀብት ልጅነትን ያገኘንባት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን የሥጋና የነፍስ መድኃኒት የሆነች እርሷን እናቱን ለሰጠን በረከቷም ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋራ ለዘላለሙ ይኑር አሜን።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_ሕርያቆስ_ዘብሕንሳ
በዚህች ቀን የከበረ አቡነ ሕርያቆስ ዘሃገረ ብሕንሳ የእመቤታችንን ቅዳሴ የደረሰበት ነው፡፡ ሕርያቆስ ማለት ‹‹ኅሩይ-የተመረጠ›› ማለት ነው፡፡ እንዲሁም ደግሞ ምሥጢረ ሥላሴን ከሁሉ ይልቅ አራቆ ይናገራልና አባቶቻን ሕርያቆስ ማለት ‹‹ረቂቅ›› ማለት ነው ይሉታል፡፡ ‹‹አብ ፀሐይ ወልድ ፀሐይ መንፈስ ቅዱስ ፀሐይ›› ብሎ አመስግኗልና አሁንም ሕርያቆስ ማለት ‹‹ፀሐይ›› ማለት ነው ይሉታል፡፡ ደግሞም የምእመናንን ልቡና በትምህርቱ ብሩህ አድርጓልና ሕርያቆስ ማለት ‹‹ብርሃን›› ማለት ነው፡፡ አንድም ደግሞ ሕርያቆስ ማለት ‹ንብ› ማለት ነው፡፡ ንብ የማትቀምሰው አበባ እንደሌለ ሁሉ ሕርያቆስም ያልቀሰመው ሰማያዊ ዕውቀት የለምና እርሱን የማይጠቅሰው ሊቅ የለም፡፡
አባ ሕርያቆስ ስለ ምሥጢረ ሥላሴ እና ስለ ምሥጢረ ሥጋዌ የሚያመሰጥረውን እመቤታችንን በተለያዩ ምሳሌያት እየመሰለ የሚያመሰግንበትን ድንቅ የሆነውን ድርሰቱን ‹‹ቅዳሴ ማርያምን›› ሰማያዊ ምሥጢር ወለል ብሎ ተከፍቶለት ደርሶታል፡፡ የብሕንሳው ኤዺስቆዾስ ስላረፉ በእሳቸው ምትክ የሚሾሙትን ሲያፈላልጉ መንፈስ ቅዱስ አባ ሕርያቆስን መረጣቸው፡፡ የከበሩ ሐዋርያት ‹‹የተማረና ግብረ ገብ የሆነ ይሾም›› ብለው ሥርዓት ሠርተዋል፡፡ ደግሞም ‹‹ሁለቱን አስተባብሮ የያዘ ባይገኝ የተማረ ከሆነ ይሾም›› ብለዋል፡፡ ምክንያቱም በትምህርቱ መናፍቃንን ተከራክሮ ይመልሳልና ነው፡፡ ደግሞም ‹‹ግብረ ገብም ከሆነ ይሾም›› ብለዋል፡፡ ምክንያቱም በጸሎቱ ይጠብቃል በትሩፋቱ ያጸድቃልና ነው፡፡ በዚህም መሠረት አባ ሕርያቆስ ያልተማረ ነገር ግን ግብረ ገብ ነውና ‹‹ትምህርቱን ውሎ አድሮ ያደርገዋል›› ብለው ሾሙት፡፡ አባ ሕርያቆስም የተማረው ለጸሎት ለቅዳሴ ያህል ትንሽ ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ ይህ ቅዱስ አባት በብሕንሳ ገዳም በ10000 መነኮሳት እና በ10000 መነኮሳይያት ላይ ተሹሞ የገዳሙ አስተዳዳሪ ሆነ፡፡
አባ ሕርያቆስ እመቤታችንን እጅግ ከመውደዱ የተነሣ ስሟን እንኳን ሲጠራ በመስጦ ልቡናው ይሰወርበት ነበር፡፡ ዘወትር ፍቅሯ ከማሰብ በቀር ሌላም አያስብም ነበር፡፡ እርሱ የነበረበት ዘመን የሊቃውንት ዘመን ስለነበር ሁሉም ለትምህርት ሲተጉ አባ ሕርያቆስ ግን ለጸሎትና ለደግነት ብቻ ይተጋ ነበር፡፡ የአባ ሕርያቆስ የሌት ተቀን ሞኞቱ ‹‹እንደ ቅዱስ ኤፍሬም የእመቤታችን ምስጋና እንደ ባሕር አሸዋ እንደ ሰማይ ኮከብ በዝቶልኝ እንደልብስ ለብሼም እንደ ምግብ ተመግቤው›› የሚል ነበር፡፡ ከልጅነቱ ጀምሮም እጅግ ስለሚወዳት እመቤታችንም ትጠብቀው ነበር፡፡ ከዕለታት በአንደኛው ቀን አባ ሕርያቆስ በበረኃ ብቻውን እየተጓዘ ሳለ የእመቤታችንን ፍቅር በልቡ ሲያመላልስ ስሟን እያነሣ ሲዘምር በተመሥጦ ውስጥ ሆኖ መንገድ ሳተና ከታላቅ ገደል ጫፍ ደርሶ ሳያስበው ወደቀ፡፡ ከገደሉም ጫፍ ደርሶ ከወደቀ በኋላ እጅግ ደንግጦ ራሱን ቢመለከት አካሉ ሳይጎድል ልብሱ ሳይቆሽሽ አገኘው፡፡ በዚህም ተገርሞ ያለበትን አካባቢውን ቢያማትር ራሱን ብርሃንን በተሞላ የልብስ ዘርፍ ላይ አገኘው፡፡ ያም ብርሃንን የተሞላ የልብስ ዘርፍ የእመቤታችን የቀሚሷ ዘርፍ ነው፡፡ በዚህም እጅግ ደንግጦ ‹‹እመ ብርሃን›› ብሎ ጮኸ፡፡ እመቤታችንም ከፊቱ ቁማ ተገለጠችለት፡፡ እርሱም የብርሃን እናቱ ድንግል ወላዲተ አምላክን በገሃድ በዐይኑ አጠገቡ ቆማ ቢያያት በደስታ ዘለለ፡፡ እመቤታችንም በቃሏ አነጋግራው ባርካው ተሰወረችው፡፡ እርሱም ፍቅሯ ጣዕሟ ቢመስጠው ከሰው ሳይገናኝ ምግብም ሳይበላ እዚያው እገደሉ ውስጥ አንድ ዓመት በምስጋና ብቻ በተመስጦ ኖሯል፡፡ በኋላም እመቤታችን ድጋሚ ተገልጣለት ከገደሉ አውጥታ ወደ ሀገሩ አድርሳዋለች፡፡
ከዚህም በኋላ አባ ሕርያቆስ እርሱ በተሾመባ በብሕንሳ ገዳም ሴትና ወንድ ያልተለየባት ገዳም ነበረችና በዚህች ገዳም የተሾመው አባ ሕርያቆስ ብዙም ትምህርት ስላልነበረው ይንቁት ነበር፡፡ ‹‹ከመጠምጠም መማር ይቅደም›› እንዲሉ ‹‹ከመሾም በፊት መማር አይቀድምም›› እያሉም ይዘብቱበት ነበር፡፡ እርሱ ግን እንደጠሉኝ ልጥላቸው ሳይል በፍቅር በትሕትና ይመክራቸው ነበር፡፡ እነርሱ ግን ‹‹በምን ምክንያት እንሻረው›› እያሉ ይመክሩ ነበር፡፡ ከዕለታት በአንድ ቀን ‹‹ቀድሰህ አቁርበን እንበለውና አይሆንም ካለን በዚህ ምክንያት እንሻረው?›› ብለው መከሩ፡፡ እርሱም ሥርዓተ ቅዳሴውን ፈጽሞ ወደፍሬ ቅዳሴው ሲደርስ የትኛውን ከባድ ቅዳሴ ቀድስ እንበለው?›› እያሉ ይመካከሩ ጀመር፡፡ እርሱ ግን ከቅዳሴ ሐዋርያት በቀር የሚያውቀው አልነበረም፡፡ አባ ሕርያቆስ እያዘነ ወደ መንበሩ ዞሮ ‹‹እመቤቴ ሆይ! መናቄን መገፋቴን ተመልከች›› ሲል ወዲያው እመቤታችን ወርዳ ጠራችውና በዘርፋፋው ቀሚሷ ላይ ረቂቅ የሆነ ቅዳሴን አሳየችው፡፡ የለመኗትን የማትነሣ፣ የነገሯትን የማትረሣ የብርሃን እናቱ እመቤታችንም የልቡን መሻት ተመልክታ ‹‹ጎስዐ ልብየ ቃለ ሠናየ ልቡናዬ በጎ ነገርን አወጣ›› በማለት ጀምሮ ‹‹ዛሬም አብን ወልድንና መንፈስ ቅዱስን እናመስግን›› እስከሚለው ድረስ ሰተት አድርጋ አስደርሳዋለች፡፡ እነርሱም ይህንን ግሩም የሆነውን ቅዳሴውን አደነቁ፡፡
🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_30
#ቅዱስ_ማርቆስ_ሐዋርያ
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሚያዝያ ሠላሳ በዚች ቀን ለእስክንድርያ ሊቃነ ጳጳሳት አለቃ የሆነ ወንጌልን የጻፈ ሐዋርያው ቅዱስ ማርቆስ በሰማዕትነት አረፈ።
የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም አርስጦቡሎስ ነው እርሱም ከአምስቱ አገሮች የሆነ የእናቱም ስም ማርያም ነው እርሷም በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ተጽፋለች እርሱም አስቀድሞ ስሙ ዮሐንስ ነው። በግብረ ሐዋርያት ማርቆስ በተባለ በዮሐንስ እናት ቤት ሐዋርያት ይጸልዩ ነበር ተብሎ እንደ ተጻፈ። እርሷም ባለጸጋ ነበረችና የዮናናውያንን የሮማይስጥን የዕብራይስጥን ትምህርት ለልጅዋ ለማርቆስ አስተማረችው።
በአደገም ጊዜ በርናባስ ወንጌልን ለመስበክ ከጳውሎስ ጋራ ሲሔድ ይዞት ሔደ በእነርሱም ላይ የሚደርስባቸውን መከራ አይቶ በጵንፍልያ ከተማ ሳሉ ትቷቸው ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሰ።
ሐዋርያትም በተመለሱ ጊዜ የክብር ባለቤት የሆነ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደ ማመን አሕዛብ እንደ ተመለሱ እግዚአብሔርም በእጆቻቸው ላይ ድንቅ ተአምራትን እንዳደረገ ተናገሩ። ይህ ብላቴና ማርቆስም ከእርሳቸው ስለ መለየቱ አዘነ ተጸጸተ።
ከዚያም አብሮአቸው ሊሔድ ፈለገ አስቀድሞ ትቷቸው ስለተመለሰ ጳውሎስ ሊአስከትለው አልወደደም በርናባስ ግን ወሰደው አጎቱ ነውና። በርናባስም ከአረፈ በኋላ ወደ ሮሜ አገር ወደ ቅዱስ ጴጥሮስ ሒዶ ለእርሱ ደቀ መዝሙሩ ሆነ በዚያም ቅዱስ ጴጥሮስ የተረጐመለትን ወንጌልን ጻፈ በሮሜ አገርም አስተማረበት። ከዚያም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትእዛዝና በሐዋርያትም ትእዛዝ ወደ እስክንድርያ አገር ሔደ። በውስጥዋም የከበረ ወንጌልን አስተማረ ደግሞም በአፍራቅያና በአምስቱ አገሮች በርቃ በሚባልም አገር ወደ እስክንድርያ ከተማ በገባ ጊዜ ጫማው ተቆረጠ።
በዚያም በከተማው መግቢያ ጫማ ሰፊ ነበረ። ቅዱስ ማርቆስም እንዲሰፋለት ለርሱ ሰጠው ሲሰፋም ጣቱን ወግቶ ሰነጠቀው ከእርሱም ደም ፈሰሰ በዮናኒም ቋንቋ ኢታስታዖስ አለ ትርጓሜውም አንድ እግዚአብሔር ማለት ነው። ቅዱስ ማርቆስም ስሙን የምትጠራው አውቀኸው ነውን አለው እንጠራዋለን እንጂ አናውቀውም አለ።
እግዚአብሔር ሰማይና ምድርን ከፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ አባታችን አዳም ትእዛዙን እንደተላለፈ የጥፋት ውኃም እንደ መጣ ሙሴንም እንደላከውና እስራኤልን ከግብጽ እንዳወጣቸው ሕግንም እንደ ሠራላቸው ናቡከደነጾርም ወደ ባቢሎን ማርኮ እንደወሰዳቸውና ከሰባ ዓመት በኋላ ወደ አገራቸው ኢየሩሳሌም እንደ ተመለሱ ክርስቶስ ሥጋ በመልበስ ወደ ዓለም ስለ መምጣቱ ነቢያት ትንቢት እንደ ተናገሩ ያስተምረው ዘንድ ጀመረ።
ከዚያም በኋላ ወደ ምድር ምራቁን ትፍ ብሎ ጭቃ አድርጎ ጣቱን ቀባው ወዲያው ዳነ በጌታችንም አመነ። ያም ሰፊ ስሙ አንያኖስ ነው። ቅዱስ ማርቆስንም ወደ ቤቱ ወስዶ ልጆቹን ዘመዶቹንም ወደ ርሱ አቀረበ እርሱም አስተምሮ አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው።
በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያመኑ ሰዎች በበዙ ጊዜ የቅዱስ ማርቆስን ዜና ሰምተው የአገር ሰዎች ሊገድሉት ተሰበሰቡ እርሱም አንያኖስን ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሹሞ ልጆቹን ቄሶችና ዲያቆኖች አድርጎ ከዚያም ወደ በርቃ ወደ አምስቱ አገሮችም ወጥቶ አስተማረ። በቀናች ሃይማኖትም አጸናቸው በእርሳቸውም ዘንድ ሁለት ዓመት ኖረ ኤጲስቆጶሳትን ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው።
ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ ተመለሰ ምእመናንም ተጨምረው በዝተው በታወቁ ቦታዎች ሁሉ በባሕሩም ዳር በላሞች መካበቢያ በሚባለውም አብያተ ክርስቲያን ሠርተው አገኛቸው።
ከሀድያንም የከበረ ሐዋርያን ይገድሉት ዘንድ በብዙ ድካም ፈለጉት እርሱም አምስቱን አገሮች ሲጐበኝ በሥውር ወደ እስክንድርያ ከተማ ይገባ ይወጣ ነበር። በአንዲትም ዓመትም ከአምስቱ አገሮች ተመልሶ ሚያዝያ ዐሥራ ሰባት ቀን በመድኃኒታችን የትንሣኤ በዓል ወደ ቤተክርስቲያን ገባ ሕዝቡም ሁሉ በዙሪያው አሉ። ከሀድያንም ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተው በአንገቱ ውስጥ ገመዶችን አድርገው በከተማው ሁሉ ጎተቱት። እነርሱም ገና እንደፍየል ሙክት እንጎትተዋለን እያሉ ይጮኹ ነበር። በላሞች መካበቢያና በሀገሪቱ አደባባይ በከተማውም ዙሪያ በየቀኑ ሲጎትቱት ኖሩ።
ሌሊትም በሆነ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሐዋርያት ጋራ በነበረበት አርአያ ሁኖ ተገለጠለት ሰላምታም ሰጥቶ አጽናናው ቃል ኪዳንም ሰጠው። እነሆ አንተ ከወንድሞችህ ሐዋርያት ጋር ተካከልህ አለው። እርሱም በልቡናው ፈጽሞ ደስ አለው። በማግሥቱም ሁለተኛ ገመዶችን በአንገቱ አድርገው በአገሮች ሁሉ ጎተቱት በቀኑም መጨረሻ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ።
ከሀዲዎችም ታላቅ እሳትን አንድደው የቅዱስ ማርቆስን ሥጋ ከውስጡ ጨመሩ። በክብር ባለቤት ጌታችን ፈቃድም ንውጽውጽታ ጨለማ ቀዝቃዛ ነፋስ መብረቅና ነጐድጓድ ሆነ። ፀሐይም ጨለመ ከሀዲዎችም ሸሹ ምእመናንም መጥተው የሐዋርያ ቅዱስ ማርቆስን ሥጋ ወሰዱ ምንም ጥፋት ሳይደርስበት ደኀና ሆኖ አገኙት በመልካም ልብስም ገንዘው በጥሩ ቦታ አኖሩት መታሰቢያውንም አደረጉ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ማርቆስ ጸሎት ይማረን በረከቱ ከእኛ ጋር ለዘላለሙ ትኑር አሜን።https://t.me/finotebirhan12
Available now! Telegram Research 2025 — the year's key insights 
