"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"
Open in Telegram
1 134
Subscribers
No data24 hours
-27 days
-2330 days
Posts Archive
🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴
በእናንተ መካከል የክፉውን መንፈስ ትምህርት ይዘው በመካከላችሁ እንዳንድ ሰዎች ሰምቻለሁ፡፡ እናንተ እንዲህ ላሉት የክፋት ሠራተኞች እንክርዳዳቸውን እንዲዘሩ በር አትሰጧቸው ነገር ግን በእነርሱ የሚለፈፈው ስህተት እንዳይበክላችሁ ጆሯችሁን እንዲህ ያለውን ነገር ከመስማት ጠብቁ፡፡
✨ቅዱስ አግናጥዮስ ምጥው ለአንበሳ✨
🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴🌴
#ትንሿ_ቤተክርስቲያን_በኦርቶዶክሳዊ_ቤተሰብ
[ባለትዳሮች] በቤታቸው ውስጥ ማድረግ ያለባቸው ቤተ ክርስቲያን መጥተው ያዩትን ነው፡፡ ለምሳሌ፦
👉 ቤተክርስቲያን ውስጥ የጠዋትና የሰርክ ጸሎት እንዳለ ኹሉ እነዚህ ባለ ትዳሮችም የጠዋትና የሰርክ ጸሎት በቤታቸው ውስጥ ሊኖራቸው ይገባል፡፡
👉 በቤተክርስቲያን ያለው የኅብረትና የአንድነት ጸሎት እንደ ኾነ ኹሉ፥ ባልና ሚስት ልጆችም ሳይለያዩ አብረው መጸለይ አለባቸው፡፡
👉 በቤተክርስቲያን ውስጥ ከቅዳሴ በኋላ ትምህርተ ወንጌል እንዳለ ኹሉ፥ ባልና ሚስትም እራት ከበሉ በኋላ ቃለ እግዚአብሔር ሊማማሩ ይገባቸዋል፡፡
👉 በቤተክርስቲያን ውስጥ ራሳቸውን ገዝተው የሚኖሩ ትጉሃን መነኰሳት እንዳሉ ኹሉ፥ ባልና ሚስትም ይህን ትግሃትና ምስጋና ወደ ቤታቸው ይዘዉት ሊኼዱ ይገባቸዋል፡፡
👉 ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማታ ላይ ኅብስቱን አበርክቶ ሕዝቡን ከመገባቸው በኋላ ወዲያው ወደ መኝታ እንዲኼዱ እንዳላደረገ ኹሉ፥ ባልና ሚስትም ወደ መኝታቸው ከመኼዳቸው በፊት የቀን ውሎአቸውን መገምገም አለባቸው፡፡
👉 ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሌሊት ሌሊት ሲጸልይ ያድር እንደ ነበረ ኹሉ፥ ባልና ሚስትም ሌሊት ላይ ነቅተው መጸለይ ይገባቸዋል፡፡ ሕፃናት ካሉም አብረዋቸው እንዲነሡ ማድረግ ይገባቸዋል፡፡
👉 በቤተክርስቲያን ጾም እንደሚታወጅ ኹሉ፥ ባልና ሚስትም በቤተ ክርስቲያን ከሚታወጀው ጾም በተጨማሪ ከንስሐ አባቶቻቸው ጋር ተመካክረው በፈቃዳቸው ሊጾሙ ይገባቸዋል፡፡
👉 በቤተክርስቲያን ውስጥ እንዳለው፥ ባልና ሚስትም የቤታቸውን ግድግዳ፣ መስኮትና በር በመስቀል ሊያስጌጡት ይገባቸዋል፡፡ ማማተብ በማይችሉ ልጆቻቸው ግንባርም አድገው ራሳቸው ማማተብ እስኪችሉ ድረስ እነርሱ ያማትቡላቸው፡፡ ቅዱሳት ሥዕላትም በቤታቸው ውስጥ ሊኖሩ ይገባል፡፡
ቤታቸው ትንሿ ቤተ ክርስቲያን የምትኾነው በዚህ መንገድ ነው፡፡
#ኦርቶዶክሳዊ_ቤተሰብ
#በቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ መጽሐፍ፥ ገጽ 60 - 61
በገብረ እግዚአብሔር ኪደ
"አንድ ነዳይ አጥብቆ እየለመነህ በቸልታ ትተኸው ስትሔድ፤ እግዚአብሔርን አጥብቀህ በምትለምን ጊዜ ቢተውህ የሚሰማህን አስብ።"
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
"ወደ መሬት ወድቀን በሰገድን ጊዜ ኃጢአት እንዴት ወደ ታች ጎትታ እንደጣለችን እናስታውሳለን። ዳግመኛም ከወደቅንበት በተነሣን ጊዜ የእግዚአብሔር ጸጋ እና ምሕረት እንዴት ከመሬት እንዳነሣንና የሰማዩን ርስት እንደሰጠን እንመሰክራለን"
ቅዱስ ባስልዮስ
ሁል ጊዜ ሕሊናህን በመንፈሳዊ ነገሮች ሙላ !!
ይህን የምታደርግ ከሆነ ዲያብሎስ መጥፎ አሳብ ሊያስተዋውቅህ ሲመጣ እንኳን ደህና መጣህ የሚለው ሕሊና አያገኝም። እንደ መከላከያ መፍትሔ ይሆንህ ዘንድ ዘወትር ራስህን በሥራ ባተሌ አድርግ። ዲያብሎስ ወደ እርሱ ገብቶ የወደደውን ዘር እንዳይዘራበት ሕሊናህን ባዶ አታድርገው።
መንፈሳዊ ንባብ ሕሊናን በሥራ ለመጥመድና መጥፎ አሳቦችን ለማራቅ ብቻ ሳይሆን ሌላም ታላቅ ጥቅም አለው። ንባብ ሕሊናን በተመስጦ ሊሞላ የሚችል መንፈሳዊ ዘዴ ከመስጠቱም በላይ ተቃዋሚ አሳቦችን የሚያጠፋውንና እግዚአብሔርን መውደድ የሚያስችለውን ስሜት በልብ ውስጥ ያጎናጽፋል።
#አቡነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ
ንግሥት ወለተ ማርያም:-
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ግንቦት ሦስት በዚህች ቀን የተባረከች ንግሥት ወለተ ማርያም የዕረፍቷ መታሰቢያ ነው::
እግዚአብሔር የመረጣትና የባረካት ንግሥት ወለተ ማርያም የንጉሥ ወናግ ሰገድ እናቱ ናት::
አካሔዷን ሁሉ ከእግዚአብሔር ጋር አድርጋ በመንፈሳዊ ሕይወቷ ነውር ነቀፋ የሌለባት የፆምና የጸሎት እናት ናት::
የንጉሡ እናት በመሆኗ ያልተኩራራች ሀብት ዝና አለኝ ብላ ከእግዚአብሔር ያልራቀች ቅድስት እናት።
አሉባልታና ሐሜት የማታውቅ ለሁሉም ርሕሩ:: ሃይማኖቷን ለማወቅን ለመባረክ የምትተጋ፤ ወደ የትም ስፍራ ሂድ እግዚአብሔርን ከፊትህ አድርግ፣ ምንም ነገር አድርግ የመፅሐፍ ቅዱስን ምስክርነት ጠብቅ፣ በማንኛውም ቦታና ሥፍራ መንፈሳዊነትህን ጠብቅ የምትል ተጋዳይ እናት ናት::
በቅድስና በንጽሕና አባቶችን ማገልገል የምትወድ:: የምትሠራው ሥራ ሁሉ የሚያምርላት የሚጣፍጥላት በረከቷ ይደርብና ቅድስት እናት ናት።
ከቅዱሳን በረከት ለማግኘት ዘወትር ዝክራቸውን የምትዘክር ከጸሎት ከምጽዋት ከስግደት ያልተለየች ቅድስት እናት ናት::
በረከቷ ረድኤቷ ይደርብን እርሷን ያበረታና ያፀና አምላክ ያፅናን አሜን። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን ለዘላለሙ አሜን::
#ግንቦት_1
#ልደታ_ለማርያም
በግንቦት አንድ በዚህችም ቀን አምላክን የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደች እርሷም ለሰው ሁሉ ወገን ድኀነት የሆነባት ናት። ከወንዶች ወገን የከበረ አባቷም ስሙ ኢያቄም ከሴቶች ወገን የከበረች ሚስቱ ሐና ይባላሉ። ሁለቱም ልጅ በማጣት ሲያዝኑ ኖሩ በዚያ ወራት የመካኖችን መብዓ ካህናቱ አይቅበሉም ነበርና።
እነርሱም ከሰው የሚደርስባቸውን ሽሙጥና ኅዘናቸውን ያርቅላቸው ዘንድ በቀንና በሌሊት ወደ እግዚአብሔር ፈጽሞ ይማልዱ ነበር። ሰውን የሚወድ እግዚአብሔርም ከዘራቸው ለዓለሙ ሁሉ መድኃኒት ይሆን ዘንድ መልካም የሆነ ኀሳባቸውን ተመለከተ።
ክቡር እያቄምም አርባ ቀን እስኪፈጸም በተራራ ውስጥ ቁሞ ሲጸልይ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ተገለጸለትና ለዓለሙ ሁሉ ድኀነት የሚደረግባት ዘር እንደሚሰጠው አበሠረው።
በፍጹም ልብ አምኖ ከተራራው ወረደ ለተመሰገነች ሚስቱ ለሐናም ከእግዚአብሔር መልአክ የሰማውን ያንን ራእይ ነገራት ቃሉ እውነት እንደሆነ እርሷም አመነች ልዑል እግዚአብሔርንም አመሰገኑት።
የተመሰገነች ቅድስት ሐናም ከእርሷ የሚወለደውን በዘመኑ ሁሉ ለቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ ታደርገው ዘንድ ለእግዚአብሔር ስለትን ተሳለች። ከዚህም በኋላ ይቺን የከበረች ሕፃን ፀንሳ ወለደች ስሟንም ማርያም ብላ ሰየመቻት ትርጓሜውም እመቤት ነው ደግሞም ሀብትና ስጦታ ማለት ነው።
በእውነት የዓለሙ ሁሉ እመቤት ናት ሁላችን በእርሷ ሰማያዊ ሀብት ልጅነትን ያገኘንባት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን የሥጋና የነፍስ መድኃኒት የሆነች እርሷን እናቱን ለሰጠን በረከቷም ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋራ ለዘላለሙ ይኑር አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ግንቦት)
++ በሰንበት መፍረስ ++
የኢያሪኮ ሰዎች የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔርን ኃይል በመናቃቸው ምንኛ ተጎዱ?! እርሱ ዓለምን የፈጠረ መሆኑን ስላላመኑ እንዳልተፈጠሩ የሆኑት የኢያሪኮ ሰዎች መጨረሻ እጅግ አሳዛኝ ነበር፡፡
ቅጥራቸው ከመፍረሱ በፊት እስራኤል የእግዚአብሔርን ታቦት ይዘው ለስድስት ቀናት ያህል በዝምታ ኢያሪኮን ዞሯት፡፡ ዓለምን በስድስት ቀናት የፈጠረውን ጌታ እንዲያስተውሉ ስድስት የዝምታ ቀናት ተሠጧቸው፡፡ በሰባተኛው ቀን ግን ጮኹ የኢያሪኮም ቅጥር ፈረሰ፡፡
ሰባተኛ ቀን የዕረፍት ቀን ነው፡፡ ለኢያሪኮ ግን የመፍረስ ቀን ሆነባት፡፡ ሰባተኛ ቀን ፈጣሪን ለሚያምኑ የተቀደሰ ቀን ነበር ፤ ለኢያሪኮ ኝ የመረገም ቀን ሆነባት፡፡
እግዚአብሔር የፈጠረው ሁሉ መልካም እንደሆነ ባየበት ሰባተኛ ቀን ኢያሪኮ ግን ከፉ እንደሆነች ታየባት፡፡
እግዚአብሔር የሌለበት ሕይወት እንዲህ ነው፡፡ ወዳጄ እግዚአብሔር በሕይወትህ ውስጥ ከሌለ የሰንበት ቀን የነፍስህ ዕረፍት ቀን መሆኑ ይቀርና እንደ ኢያሪኮ የመፍረስ ቀን ይሆናል፡፡ በዚያ ቅዱስ ቀን ቅጥርህን በመጠጥ ፣ ብስካር ብዝሙት ስታፈርስ ትውልና ታድራለህ፡፡ ራስህን አንድደህ ትሞቃለህ ፤ እያራገብህ ትቃጠላለህ፡፡ ታቦት ይዘው ቢዞሩህም የኃጢአት ግንብን አጥረሃልና አትሰማም፡፡ በላይህ ላይ ቢቀደስብህም እንደ ኢያሪኮ ሰዎች ካህናቱን እያየህ ‘ዝም ብሎ መዞር ምንድር ነው?’ እያልክ ትስቃለህ፡፡ የካህናቱ የቅዳሴ ዜማ ለአንተ የሚያፈርስ ጩኸት ይሆንብሃል፡፡ የኢያሪኮ ሰው ከመሆን ፣ በሰንበት ፈራሽ ከመሆን ያድንህ!
ቅዳሴያችን መካከል ካህኑ ዕጣን እያጠኑ ዞረው ሲመለሱ የዚህች አጭር ጽሑፍ መነሻ ሃሳብ የሆነውን ይህንን ጸሎት ይጸልያሉ፦ አምላካችን እግዚአብሔር ሆይ አስቀድመህ በባሪያህ በነዌ ልጅ በኢያሱ እጅ የኢያሪኮን ግንብ እንዳፈረስከው የእኔንና የሕዝብህን የኃጢአታችንን ግንብ አፍርሰው፡፡
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ሰይጣን አንድን ኃጢአት ሊያሠራን ሲፈልግ ቀድሞ ስለ እግዚአብሔር መሐሪነት በሰፊው ይሰብከናል። ያን ኃጢአት ከፈጸምን በኋላ ደግሞ ስለ እውነተኛ ፈራጅነቱና ምንም ቢሆን ከቁጣው የማናመልጥ መሆኑን ከቀድሞው ይልቅ እየጮኸ ይነግረናል። በመጀመሪያው ስብከቱ ኃጢአትን እንዳንቃወም ሰነፎች ያደርገናል። በሁለተኛው ስብከቱ ደግሞ ንስሐ እንዳንገባ ተስፋ ያስቆርጠናል።
ይህ የተገለባበጠ ስብከት "የሰይጣን" ነው። ሰው በኃጢአት ከመውደቁ በፊት ሊያስብ የሚገባው የእግዚአብሔርን ፈታሒነት (ፈራጅነት) ሲሆን በኃጢአት ከወደቀ በኋላ ግን ማሰብ ያለበት የእግዚአብሔርን መሐሪነት ነው።
ፈታሒነቱ ኃጢአትን እንዳንሠራ ይጠብቀናል፤
መሐሪነቱ ንስሐ እንድንገባ ያቀርበናል፤
ዲያቆን አቤል ካሳሁን
#ቅዱስ_ጎርጎርዮስ_ዘእንዚናዙ ለንስሓ ልጁ #በሰርጓ ቀን መገኘት ባለመቻሉ የላከላት ደብዳቤ
“ልጄ! ለሰርግሽ የነፍስ አባትሽ እኔ ጐርጐርዮስ ይህን ግጥም ስጦታ አድርጌ ልኬልሻለሁ፡፡ አባት ለሚወዳት ልጁ ሊሰጣት የሚችለው የተሻለው ምክርም ይህ እንደ ኾነ አምናለሁ፡፡
“ኦሎምፒያታ ሆይ፥ እውነተኛ ክርስቲያን ለመኾን ያለሽን ፍላጎት ዐውቃለሁና በደንብ አድምጪኝ! እውነተኛ ክርስቲያን እንዲሁ መኾንን የሚመኝ ብቻ ሳይኾን እንደዚያ ለመኾን ሊጥር ይገባዋል፡፡
“ከኹሉም በላይ፥ እግዚአብሔርን ልታከብሪውና ልትወጂው ይገባሻል፡፡ ከእርሱ ቀጥሎም በቅዱስ ወንጌል እንደ ታዘዘው እንደ ጌታችንና መድኃኒታችን [ኢየሱስ ክርስቶስ] አድርገሽ ባልሽን ልታከብሪውና ልትወጂው ይገባሻል፡፡ ስለዚህ እጠይቅሻለሁ! ጌታዋንና ፈጣሪዋን [ኢየሱስ ክርስቶስን] የማታከብርና የማትወድ ሴት በዚህ መንገድ ባልዋን እንዴት አድርጋ ልታከብረውና ልትወደው ትችላለች?
“በጋብቻሽ ውስጥ የትዳር አጋርሽ ይኾን ዘንድ እግዚአብሔር መርጦ ለሰጠሽ ባል ያለሽ መውደድ፣ ስሜትና ፍቅር እጅግ ኃያል ሊኾን ይገባዋል፡፡ ይህ ሰው አሁን የሕይወትሽ ዓይን፣ የልብሽም ደስታ ነውና፡፡
“እግዚአብሔርን እንደምትወጂው፥ ባልሽንም ያለ ቅድመ ኹኔታ ልታከብሪውና ልትወጂው ይገባሻል፡፡ አንቺ ሴት እንደ ኾንሽና ታላቅ የኾነ ዓላማና ግብ እንዳለሽ፥ ኾኖም ዓላማሽና ግብሽ የቤትሽ ራስ ሊኾን ከሚገባው ባልሽ የተለየ እንደ ኾነ ዕወቂ፤ ተረጂም፡፡ ባንቺ ዕድሜ ላይ ያሉት አንዳንዶች ኹለቱም ፆታዎች እኩል [ራስ ናቸው] ብለው የሚሰብኩትን አትስሚ፤ የጋብቻንም ግዴታ [ወይም ዋና ዓላማ] አስቢ፡፡ እነዚህን ግዴታዎች [ወይም ዓላማዎች] ስታውቂ የቤተሰብሽን ተግባራት ለማከናወን እንደ ምን ያለ ትዕግሥትና ጽናት እንደሚያስፈልግሽ ታውቂያለሽና፡፡ እንደ ሚስት እጅግ ጥንካሬን ገንዘብ የምታደርጊውም በዚህ መንገድ ነው፡፡
“ወንዶች እንዴት በቀላሉ የሚቈጡ መኾናቸውን በርግጥ ልታውቂ ይገባሻል፡፡ አይችሉም፤ ብዙ ጊዜም እንደ በረኻ አንበሳ ይኾናሉ፡፡ እንግዲህ ሚስት ጸንታ ልትቆምና የነፍስ ልዕልናዋን ልታሳይ የሚገባት በዚህች ቅጽበት ነው፡፡ አንበሳን የማስለመድ ሥራ መሥራት አለብሽ፡፡ አንበሳን የሚያስለምድ ሰው አንበሳ ሲያገሳ የሚያደርገው ምንድን ነው? ከየትኛውም ጊዜ በላይ ዝም ጸጥ ይላል፡፡ በጸጥታውና በርጋታውም የአንበሳውን ቊጣ ይቈጣጠራል፡፡ በርጋታና በለሆሳስ ኾኖ ያናግረዋል፤ ይደባብሰዋል፤ በቀስታ ያሻሸዋል፤ በጥቂት በጥቂቱም አንበሳው ቊጣውን ይተዋል፡፡
“ባልሽ ስሕተት ሲሠራ በፍጹም ልትነቅፊው፣ ልትንቂው ወይም ልታስነውሪው አይገባም፡፡ በተመሳሳይ መንገድ አንድ መሥራት ያለበትን ነገር ባይሠራና ከዚሁ የተነሣም ውጤቱ ደስ የማያሰኝ ቢኾን፣ ወይም እጅግ የምትፈልጊውና አግባብ ነው ብለሽ የምታስቢውን ባያደርግ እንኳን ባልሽን መናቅ ከአንቺ ልታርቂ ይገባል፡፡ ክፉዎች አጋንንት ዘወትር ቤታችሁን ለማፍረስና የጥንዶች መንፈሳዊ አንድነትን ለመበተን እንደሚሞክሩ ዕወቂ፡፡”
(#ከገብረ_እግዚአብሔር_ኪደ ከትንሿ ቤተክርስቲያን መጽሐፍ የተወሰደ)
ተወዳጆች ሆይ! ትዘምራላችሁ፡፡ [ከጸሎታቱ ትሳተፋላችሁ፡፡ ቅዳሴውን አስቀድሳችሁ] እምነታችሁን ትመሰክራላችሁ፡፡ ይህን ኹሉ አድርጋችሁ ስታበቁ ግን አትቆርቡም፡፡ ለምን? ከሰማያዊው ማዕድ የማትሳተፉት ለምንድን ነው? አንዳንዶቻችሁ፡- “እኔ ኃጢአተኛ ስለ ኾንሁ ልቆርብ አይገባኝም” ብላችኋል፡፡ እንዴ! እንደዚህ’ማ ካላችሁ ከመዝሙሩም፣ ከጸሎታቱም፣ ከቅዳሴውም ልትሳተፉ አይገባችሁማ!
እስኪ ንገሩኝ! የንጉሥ ማዕድ በፊታችሁ አለ፡፡ መላእክት “ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ” እያሉ የሚያመሰግኑት የሚያገለግሉትም ማዕድ በፊታችሁ አለ፡፡ ንጉሡ በፊታችሁ አለ፡፡ ታዲያ እናንተ እንዲሁ ቁልጭልጭ እያላችሁ ትቆማላችሁን? ልብሳችሁ አድፎ ተዳድፎም ሳለ ምንም እንዳልተፈጠረ ኾናችሁ ወደ ቤታችሁ ትመለሳላችሁን?
ወደ መንግሥተ ሰማያት፣ ወደ ሰማያዊው ንጉሥ ማዕድ ራሱ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጠርቶን ሳለ ተዘጋጅተን እንደ መቅረብ ወደ ኋላ እንላለንን? እንደዚህ የምናደርግ ከኾነ ታዲያ ተስፋ ድኅነታችን ምንድን ነው?
“መቅረብ ያልቻልኩት’ኮ” ብለን ደካማ መኾናችንን እንደ ሰበብ ማቅረብ አንችልም፡፡ ተፈጥሮአችንን እንደ ምክንያት ማቅረብ አንችልም፡፡ እንዳንቀርብ የሚያደርገን ደካማ መኾናችን አይደለም፡፡ አዎን ከሰማያዊው ማዕድ እንዳንሳተፍ የሚያደርገን እንዲሁ ሳንዘጋጅ ልል ዘሊላን ኾነን መቅረባችን እንጂ ሌላ ምንም ምክንያት አይደለም፡፡
ስለዚህ እማልዳችኋለሁ! [ንስሐ ገብተን እንደ ቸርነቱም ተዘጋጅተን] በፍርሐትና በረዓድ ኾነን [በግድ] እንቅረብ እንጂ “ኃጢአተኛ ስለ ኾንሁ” ብለን አንራቅ፡፡ [ከኃጢአት ኹሉ የሚያነጻን የክርስቶስ ደም እንጂ ኃጢአተኛ ነኝና አይገባኝም ብለን መራቃችን አይደለምና፡፡] ክርስቶስ ዳግም ሲመጣ በድፍረት ወደ እርሱ መቅረብ ይቻለን ዘንድ ዛሬ በፍርሐትና በረዓድ ኾነን ወደ እርሱ እንቅረብ፡፡ ያኔ “ኑ እናንተ የአባቴ ብሩካን” ከሚላቸው ጋር ዕድል ፈንታችን ፅዋ ተርታችን በመንግሥተ ሰማያት ይኾን ዘንድ ዛሬ ወደ ሰማያዊው ማዕድ እንቅረብ፡፡
(በቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ገብረ እግዚአብሔር ኪደ እንደተረጎመው)
"ጸሎትን የምንጸልየው እግዚአብሔር የማያውቀው ነገር ኖሮ አይደለም፤ ወደ እርሱ እንድንቀርብ፣ ቀርበን ወዳጆቹ እንድንሆን፣ ዘወትር እንዲረዳን፣ ራሳችንን ዝቅ ለማድረግ፣ ኃጢአታችንንም እንድናሰብ ነው እንጂ።"
#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ
"ጋብቻ ለመመስረት ያሰበ አንድ ወጣት ከቤተሰብና ከጓደኞቹ ጋር ተማክሮ ከጨረሰ በኋላ የመንፈስ አባቱ ዘንድ በመሔድ ይህንን ውሳኔውን አስረዳቸው፡፡ ጥበበኛውም አባት ለማግባት ያለውን ጉጉት በልጁ ፊት ላይ እያስተዋሉ አሳቡ መልካም እንደሆነ ገልጸው ማስታወሻና ብዕራቸውን በማውጣት “ስለ ልጅቷ ትንሽ ነገር ንገረኝ” በማለት ጥያቄ አቀረቡለት፡፡ እርሱም እንዲህ አለ “ትውልዷ ከነገስታት ዘር እድገቷም በምቾት መሐል ነው” አለ፡፡ እኚህም አባት በሙሉ ልብ ሆነው በያዙት ማስታወሻ ላይ ዜሮ ጻፉ፡፡
ወጣቱም ስለ ልጅቷ ማብራራቱን ቀጠለ፡- “በጣም ውብ ናት” አለ፡፡ እርሳቸውም ሌላ ዜሮ ጻፉ፡፡ “በጣም ዝነኛ ናት” አለ፡፡ ደግመው ሌላ ዜሮ ጻፉ፡፡ “በጣም ሀብታም ናት” አለ፡፡ ጥበበኛውም ሌላ ዜሮ ጻፉ፡፡
“በጣም ምሁር ናት” አለ፡፡ አሁንም ሌላ ዜሮ ጻፉ፡፡
“በጣም ዘመናዊ ናት” አለ፡፡ ተጨማሪ ሌላ ዜሮ ጻፉ፡፡ በመጨረሻ ግን የረሳውን አንድ ነገር ነገራቸው “ልባም እንዲሁም ሕይወቷ ለእግዚአብሔር ክብርና ምስጋና የተሰጠ ነው” አላቸው፡፡ ጥበበኛውም አባት ፊታቸው ላይ ፈገግታ እየተነበበባቸው አስቀድሞ ከጻፉአቸው ስድስት ዜሮዎች ፊት አንድ ቁጥርን ጽፈው “በል ሂድና አግባት” አሉት፡፡ ወጣቱም በደስታ ከፊታቸው ሄደ፡፡
ጋብቻ ብዙ ጊዜም በሌላው ሰው አካላዊ ገጽታና ውጫዊ አቋም ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ ምንም እንኳን በአካላዊ ውበት መማረክ ወደ ፍቅር የሚመራ አንደኛው መንገድ ቢሆን እውነተኛ ፍቅር ግን በአካላዊ ውበት፣ በአፋዊ መስፈርት ከመሸነፍ ያለፈ ነው፡፡ አካላዊ ውበት የጊዜያዊ ጉጉት መገለጫ ሲሆን ፍቅር ግን በሌላው ውስጥ ያለውን መልካሙን ነገር በመሻት ትዕግስትን መሰረት የሚያደረግ ነው፡፡ይህም የትኛውንም ልብ የመንካት፣ በላቀና በጠለቀ መንገድ የመግዛት ጉልበት ነው፡፡ ማንኛውም ሰው በዘመኑ የሚያሳልፋቸው ትልልቅም ይሁን ትንን ውሳኔዎች አሉ፡፡ ሕይወትም በዚህ የዕለት ተዕለት ቋሚ የመምረጥና የመወሰን ተግባር ላይ የተመሰረተች ናት፡፡ ጋብቻ የእኛን ትልልቅ ውሳኔ ከሚፈልጉ ነገሮች አንዱ ነው፡፡ የምናመልከውን እንመርጣለን፣ የምንኖርበትን አካባቢ እንመርጣለን፣ የልባችንን የምናካፍለው ባልንጀራ እንመርጣለን፣ በትዳር አጋር የሚሆነንን እንመርጣለን፣ በአጠቃላይ መሆን የምንፈልገውን እንመርጣለን፡፡ በእርግጥ ምርጫችንን ከምንኖረው በላይ ተጽእኖ ወደ ኑሮአችን የሚያመጣውን መኖራችን ግልጽ ነው፡፡ ነገር ግን በዚህም ውስጥ ከእውነት ጋር ያለን ትስስር ሊደበዝዝ አይገባም፡፡ ምርጫችን ውስጥ ሞትም ሕይወትም፣ ደስታም ሀዘንም፣ ክብርም ውርደትም አለ፡፡ መርጠን ዘመናችንን የእንባ ልናደርገው መብቱ የእኛ ነው፡፡"
ፍቅር ሲመነምን ውጤቱ የበዙ ጥፋቶችን ማስከተል ይሆናል!!
የፍቅር እጦት ቂም እና ጥላቻን ይፈጥራል። ይህ ደግሞ በኃጢአት ሐሴት ማድረግን ያመጣል። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ "ጠላትህ ቢወድቅ ደስ አይበልህ በመሰናከሉም ልብህ ሐሴት አያድርግ" ምሳ 24፥17
ሌላው የፍቅር እጦት ውጤት ቁጣ እና ክፋት ነው። እንዲህ ያለው ሁኔታ ስድብን፣ ጠብን፣ ግድያን፣ ነቀፋን፣ ማዋረድንና ስም ማጥፋት ማስፋፋትን ያስከትላል። ከዚህ በተጨማሪ የፍቅር እጦት ወይም ጉድለት ወደ ቅንዓት፣ ወደ አላዋቂነት፣ ወደ ኩራት፣ ወደ ጽናትን ማጣትና ወደ ጭካኔ ይመራል።
ለእግዚአብሔር የሚሆን ፍቅርን ማጣት በብዙ ጉዳዮች ውስጥ ሊገለጥ ይችላል፤ ከእርሱም መካከል ጸሎትን፣ መጽሐፍ ቅዱስንና ቤተ ክርስቲያንን መርሳት ጥቂቶቹ ናቸው። በእግዚአብሔር ፊት መቆምን ማጣት እና በእግዚአብሔር መንግሥት ፈጽሞ ሐሴት አለማድረግ ሌሎቹ ጉድለቶች ናቸው።
#ብጹዕ_አቡነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ
ያለፈውን የሚያስንቅ ‹ቀድሞም የፍቅር ወይን አልነበረንም ፤ መናኛ ነበር የያዝነው!› የሚያሰኝ ነው፡፡ ይህን ስንል ግን ባልና ሚስት ራሳቸው ሊያስተካክሏቸው የሚገቡ ጉድለቶቻቸውንሳያስተካክሉ የእመቤታችንን ምልጃና ተአምር ብቻ ይጠባበቁ ማለታችን አይደለም፡፡
በቃና ምልጃዋ ችግር እንዲፈታ ለአገልጋዮቹ ‹የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ› ብላ ድርሻ ሠጥታ እንደነበር ባለትዳሮችም ሊያደርጉት የሚገባ ነገር አለ፡ትዳራቸው በፍቅር ወይን እንዲሞላ ‹የእኔስ ችግር ምንድር ነው?› ‹የእናቱን አማላጅነት ከጠየቅሁ ከእኔ ምን ማድረግ ይጠበቃል?› ብለው በትሕትና በመታዘዝና ድክመታቸውን በማስተካከል ትዳራቸውን መታደግ አለባቸው፡፡
መድኃኔዓለም ክርስቶስን ወደ ጋብቻ ሕይወት መጥራት የሚቻለው ሥጋና ደሙን በመቀበል ነው :: በደቀመዛሙርት የተመሰሉት ካህናትን በንስሓ አባትነት ይዞ ጋብቻን በሥጋ ወደሙ ወስኖ ዘወትር በመንፈሳዊ ሕይወት መንገድ በእግዚአብሔር ቃል ለሚጓዝ ሰው የወይን ጠጁ ዳግም ላያልቅ ይሞላል፡፡
በጋብቻ ሕይወት መንገድ ላይ ላላችሁ ሁሉ የቃናዋ እንግዳ እመቤታችን በአማላጅነቷ ፤ የተወደደ ልጅዋ ደግሞ በአምላካዊ ሥራው በቤታችሁ ተገኝቶ መንፈሳዊውን የፍቅር ወይን ይሙላላችሁ አሜን!
ቃና ዘገሊላ ገጽ 144-1247
በዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
✟#ትዳርና_የወይን_ጠጅ✟
ጌታችን በሰርጋቸው ላይ የተገኘላቸው የቃና ዘገሊላዎቹ ሙሽራና ሙሽሪት እንደማንኛውም ሙሽሮች ሁሉ አቅማቸው የፈቀደውን ያህል ለሰርጋቸው ሲዘጋጁ ሰንብተዋል፡፡ እንደባሕላቸው ስለሚለብሱት ልብስ ፣ ስለሚደግሱት ድግስ ፣ ስለሚጠሩአቸው እንግዶች ብዛት ፣ ስለሚቀርበው ምግብ ፣ ስለሚጠጣው የወይን ጠጅ ከዘመድ ወዳጆቻቸው ጋር ሲደክሙ ከርመዋል፡፡
በሰርግ ዕለት ግን የሚያጋጥም ነገር አይታወቅምና ብዙ እንግዳ ይሸኛል የተባለው የወይን ጠጅ ሳይታሰብ አለቀ… የማይሽር ቁስል የሚጥልባቸውን ፣ የሰው መተረቻ የሚያደርጋቸውን ይህን ክስተት ግን እነርሱ ሳይሰሙ በሰርጉ ቤት የነበረችው እመቤታችን በምልጃዋ ፈታችው፡፡
ለተወደደ ልጅዋ ነግራ የጎደለውን አስሞልታ ባማረ ሁኔታ ዳረቻቸው፡፡ የጠሩት የሰማይና የምድር ንጉሥ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ውኃን ወይን ጠጅ አድርጎ አከበራቸው፡፡
በመጽሐፍ ቅዱስ ውኃና የወይን ጠጅ ከጠብና ከፍቅር ጋር ተያይዘው ሲነገሩ እናገኛለን፡፡
ጠቢቡ ሰሎሞን ስለ ፍቅር ሲናገር ወይን ጠጅን በንጽጽር ያነሣል ‹‹ፍቅርህ ከወይን ጠጅ ይልቅ መልካም ነው!›› ‹‹ፍቅርሽ ከወይን ጠጅ ይልቅ እንዴት ይሻላል!›› ‹‹ከወይን ጠጅ ይልቅ ፍቅርህን እናስባለን›› ‹‹ወደ ወይን ጠጁም ቤት አገባኝ፥ በእኔ ላይ ያለው ዓላማውም ፍቅር ነው።›› እያለ ማለት ነው፡፡ (መኃ.፩፥፪፣፬፤፪፥፬፤፬፥፲) በአንጻሩ ስለ ጠብ ሲያነሣ ደግሞ ውኃን ያነሣል፡፡
‹‹ብዙ ውኃ ፍቅርን ያጠፋት ዘንድ አይችልም›› ‹‹የጠብ መጀመሪያ እንደ ውኃ አፈሳሰስ ነው›› ‹‹በዝናብ ቀን የሚያንጠባጥብ ቤትና ጠበኛ ሴት አንድ ናቸው›› ብሏል፡፡ (መኃ.፰፥፯፤ምሳ.፲፯፥፲፬፤፳፯፥፲፭) በአጠቃላይ በመጽሐፍ ቅዱሳዊ አተረጓጎም ውኃ የጠብ ምሳሌ ሲሆን ወይን ጠጅ ደግሞ የፍቅር ምሳሌ ነው፡፡
በቃና ዘገሊላ ሰርግ ቤት በመጀመሪያ የወይን ጠጅ ተጠምቆ ዝግጁ ሆኖ ነበረ፡፡ ይህ የወይን ጠጅ የጠማቂ ባለሙያ እጅ የተጠበበበት ነበር፡፡ ሙሽሮቹ ያላቸው ወይን ጠጅ ሰርጉን እንደሚያዘልቃቸው ተማምነው የነበረ ቢሆንም ወይኑ ግን ባልጠበቁት ፍጥነት አለቀ፡፡
ከዚያ በኋላ በዚያ ሰርግ ቤት ለሚመጣ እንግዳ ሊቀርብ የሚችለው ብቸኛ መጠጥ ውኃ ብቻ ነበር፡፡ ለሙሽሮቹ የተሻለ የሚሆንላቸው ከዚያች ደቂቃ ጀምሮ ሌላ እንግዳ ጨርሶ ባይመጣ ነው፡፡ ወይን ጠጅ በሚጠጣበት ሰርግ ቤት ውኃ ከሚጠጣ ለእንግዳውም ባይመጣ ይሻለዋል፡፡
በሁሉም የትዳር ሕይወት ውስጥ በወይን ጠጅ የተመሰለው ፍቅር መጀመሪያ ይኖራል፡፡ መጠኑ ይለያይ እንጂ ሁሉም ማለት ባይቻልም ባለትዳሮች በአመዛኙ ከጋብቻ በፊት ቢያንስ ወደ ጋብቻ እንዲያመሩ ምክንያት ሊሆን የቻለ ፍቅር ይኖራቸዋል፡፡ ብዙዎች የቃና ሙሽሮች በወይን ጠጃቸው እንደተማመኑ ሁሉ በፍቅራቸው ዘላቂነት እርግጠኞች ነበሩ፡፡
ከጋብቻ በፊት የነበራቸው ፍቅር ከጋብቻ በኋላ አብሯቸው እንደሚዘልቅ ተማምነው ነበር፡፡ አንዳንድ ጥንዶች እንደውም በፍቅራቸው ዘላቂነት ላይ ካላቸው እርግጠኝነት የተነሣ ሌሎች ባለትዳሮች ሲጣሉ ሲያዩና ሲሰሙ ‹ሰው እንዴት ይጣላል? እንደኛ ስላልተፋቀሩ ነው!› ብለው ይፈርዳሉ፡፡
‹የፈለገ ነገር ቢከሰት እኛ መቼም እንዲህ አንሆንም!› ብለው ይዝታሉ፡፡
በሰርግ ሰሞንና በመጀመሪያዎቹ የጋብቻ ወራት ባልና ሚስት በፍቅር ወይን የተሞሉ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ የጫጉላ እርከን (Honeymoon stage) ላይ እያሉ ሁሉም ነገር ደስታና ሰላምን የተሞላ ሊሆን ይችላል፡፡
እንደቃናው ሰርግ ቤትም ይህ የፍቅር ወይን በልበ ሙሉነት ሲቀዳ ይቆያል፡፡ ሆኖም ሰው የጠመቀው ወይን ማለቁ እንደማይቀር በጋብቻ ሕይወትም እንዲሁ በወይን የተመሰለው ፍቅር እያለቀ እያለቀ መምጣቱ አይቀርም፡፡
ከዚያ በኋላ በዚያ ጋብቻ ላይ ሊገኝ የሚችለው ውኃ ይሆናል፡፡ ባል ለሚስቱ ፍቅር የተባለውን ወይን ማቅረብ ሲሳነው ፣ ሚስትም እንዲሁ ወይን ማምጣት ሲያቅታት አንዳቸው በአንዳቸው ሁኔታ እየተበሳጩ ይሔዳሉ፡፡
ወይን ከሌለ ደግሞ እንደ መፍትሔ ቆጥረው አንዳቸው ለአንዳቸው የሚያቀርቡት ውኃን ይሆናል፡፡ ውኃ ደግሞ ከላይ በመጽሐፉ እንዳየነው የማያቋርጥ ጠብ ነው፡፡
ባል ለሚስቱ ሚስት ለባልዋ እንደ ውኃ የቀዘቀዙ ይሆናሉ፡፡ እርስዋ ‹‹እውነት ግን ይኼንን ሰው ነበር ባል ብዬ የተቀበልሁት?›› ብላ ትብከነከናለች፡፡ እርሱም ‹‹ምን ነክቶኝ ነበር?›› እያለ ይቆጫል፡፡ ወደ ቤታቸው የሚመጣ ሰውም ፊት ሊያቀርቡት የሚችሉት ወይን የላቸውም፡፡ የመጣ ሰው የሚያየው ጠባቸውን ብቻ ስለሚሆን የእንግዳ አለመምጣት ለሁለቱም የተሻለ ይሆናል፡፡
ያያቸው ሰው እርስ በእርሳቸው ያላቸውን ጥላቻ ሲመለከት ‹‹እነዚህ ሰዎች አስቀድሞስ እንዴት ተፋቅረው ሊጋቡ ቻሉ? የለም ቀድሞውኑም ፍቅር ባይኖራቸው ነው!›› ብሎ ይደመድማል፡፡ ልክ ነው ወይን አልቆ ውኃ ሲቀርብ በዚያ ቤት ወይን ኖሮ የሚያውቅ አይመስልም፡፡
በእንዲህ ዓይነት ኑሮ የሚሠቃዩ ብዙዎች ናቸው፡፡ ባልጠበቁት ሁኔታ የፍቅር ወይን አልቆባቸው የጠብ ውኃን መጋት የለመዱ ፣ የተጋቡበትን ቀን የሚራገሙ ፣ ጋብቻን ለማንም ሰው የማይመክሩ ፣ ባላገቡ ሰዎች ዕድል የሚቀኑ ፣ ፍቺ እንዳይፈጽሙ ፈርተው ልጆቻቸውን ላለመበተን ብለው አብረው የሚኖሩ ፣ ባልና ሚስት ሆነው አልጋ ለይተው የሚተኙ ፣ ሰላምታ እንኳን የማይሠጣጡ ወይን ጠጅ አልቆባቸው ቤታቸው በጠብ ውኃ ጎርፍ የተሞላባቸው እጅግ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡
ለዚህ ችግር መፍትሔ ፍለጋ ብዙዎች ይደክማሉ፡፡ ችግራቸውን ሊፈቱላቸው ለማይችሉ ለወዳጅ ዘመዶቻቸው የወይናቸውን ማለቅ ተናግረው መዘባበቻ ሆነው የቀሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ መፍትሔ ይሆናል ብለው በራሳቸው መንገድ ሔደው ሌላ ድጋሚ ሊያልቅ የሚችል በሰው ጥበብ የተጠመቀ የወይን ጠጅ ሊያመጡ ሞክረው ባጭር ጊዜ ያለቀባቸውም ብዙዎች ናቸው፡፡
መፍትሔው ግን በዚሁ በቃና ዘገሊላ ሰርግ ቤት ታሪክ ላይ ተቀምጧል፡፡ ችግሩ መፈታት የሚችለው በዚያ ሰርግ ቤት በተፈታበት መንገድ ብቻ ነው፡፡ የቃና ወይን ጠጅ ሲያልቅ አይታ ‹‹ወይን እኮ የላቸውም›› ብላ ለምና ያስሞላችው ወላዲተ አምላክ በባለ ትዳሮች መካከል ካለች ችግሩ ያለጥርጥር ይፈታል፡፡
ስም ለሚያጠፉ ለሰዎች በመንገር ጊዜ ማጥፋት አያስፈልግም፡፡ በቃና ዘገሊላ እንዳደረገችው ድንግል ማርያም በባለ ትዳሮችም ቤት ገብታ ‹‹ፍቅር እኮ የላቸውም›› ትላለች፡፡
አንዳንድ ባለ ትዳሮች በጋብቻቸው ውስጥ ወይን መጉደሉን እንደ ቃና ዘገሊላዎቹ ሙሸሮች ፈጽመው አያውቁም፡፡
በየጊዜው አስታራቂ ከመካከላቸው እየገባ ሊያስማማቸው ሲሞክር የጠባቸው መንሥኤ ከድሮም አብሯቸው የኖረ ተራ ምክንያት ይሆናል፡፡ የማያጣላው አጣልቷቸው በውኃ ቀጠነ ሲነታረኩ ይገኛሉ::፡በተደጋጋሚ ሽምግልና እየታረቁም እንኳን ሰላም አያገኙም፡፡
‹‹እስቲ ምን አዲስ ነገር ተገኘና ነው ዛሬ ተነሥተሽ እንዲህ የምትዪኝ›› ‹‹ዛሬ ነው ወይ ይኼ ነገር የታየህ›› እየተባባሉ በማያጠግብ ምክንያት መናቆራቸው ለሁለቱም ግራ ይገባቸዋል፡፡ ያልተረዱት ነገር ግን አለ፡፡ በየሰበቡ እንዲጣሉ የሚያደርጋቸው ፍቅራቸው ማለቁ ነው፡፡
የፍቅር ወይን እንዳለቀ ከእነርሱ ቀድማ የምታውቀው ድንግል ማርያም ግን ‹‹ፍቅርኬ አልቦሙ›› ‹‹ፍቅር እኮ የላቸውም›› ትላለች፡፡ ልጅዋ ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞ በጠብ ውኃ የተሞላውን ቤት ዳግመኛ በወይን ጠጅ ፍቅር ይሞላዋል፡፡ ይኼኛው የወይን ጠጅ ደግሞ እንደበፊቱ ሰው ሠራሽ ወይን የሚያልቅ አይደለም
"ባሎች ለሚስቶቻቸው ሊያሳዩአቸው የሚገባ ፍቅር"
(#በቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ)
ቤተ ክርስቲያን ለክርስቶስ እንደምትገዛ ሚስትህ ለአንተ ትገዛልህ ዘንድ ትሻለህን? ክርስቶስ ለቤተ ክርስቲያን እንዳደረገላት አንተም እንዲሁ ለሚስትህ አድርግላት፡፡ ሕይወትህን ስለ ርሷ አሳልፈህ መስጠት ካለብህ ስለርሷ ሕይወትህን አሳልፈህ ስጥ፤ መከራም መቀበል ካለብህ መከራን ለመቀበል አትሰቀቅ፡፡
አንተ ይህን ብትፈጽመው ስንኳ ክርስቶስ ለቤተ ክርስቲያን ካደረገላት ጋር ሲነጻጸር የሚወዳደር አይደለም፡፡ ምክንያቱም አንተ ይህን ያደረግኸው ከአንተ ጋር ፈጽማ ለተዛመደችህ ለአንዲት ሴት ነው፡፡ “እርሱ ግን ከእርሱ ለተመለሰችውና ለጠላቸው ራሱን አሳልፎ ሰጠ፡፡” ርሱ ከርሱ የተመለሰችውንና የጠላችውን እንዲሁም ያቃለለችውን ገንዘቡ ሲያደርጋት በማስፈራራት፣ በማስገደድ ወይም ይህን በመሳሰሉ ነገሮች አልነበረም፤ ነገር ግን ኀዘን ባልተቀላቀለበት ፍጹም በሆነ ፍቅር በመሆን ነበር፡፡ አንተም ለሚስትህ እንዲሁ አድርግላት አዎን! ምናልባት ሚስትህ አንተን ልታመናጭቅህ፣ ልትንቅህ፣ ልታፌዝብህም ትችላለች፤ ቢሆንም ግን አንተ ለርሷ ካለህ አርቆ አሳቢነት ንጹሕ ፍቅርና ኀዘኔታ የተነሣ ልትታገሣት ይገባሃል፡፡
ከሰው ሁሉ ጋር ተስማምቶ ለመኖርም ከእነዚህ የተሻሉ ነገሮች ፈጽሞ አናገኝም፡፡ በተለይም ለባልና ለሚስት፡፡ አንድ ሰው አገልጋይ ባሪያውን በማስፈራራት ለመግዛት ቢሞክር ለጥቂት ጊዜአት ሊገዛለት ይችላል፡፡ ሆኖም ይህ ባሪያ እንዲህ ዓይነት አገዛዝ ስለማይመቸው ከእርሱ ፈጥኖ ይሸሻል፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው የሕይወቱን አጋር፣ የልጆቹን እናት፣ የደስታው ሁሉ ምንጭ የሆነችውን ሚስቱን በፍቅርና በፍጹም አክብሮት እንጂ ልክ እንደ ባሪያ በፍርሃት ሰንሰለት በማሰር ወይም በማስጨነቅ ርሷን ሊገዛት መሞከር አይገባውም፤ ሚስት በባልዋ ምክንያት የምትሸበር ከሆነ አንድነታቸው ምን ዓይነት አንድነት ነው? ከባሪያ ጋር እንደ መኖር ከሚስት ጋር መቀመጥ ለባል የሚፈጥርለት ምን ዓይነት ደስታ ነው? አዎን ይልቁኑ አንተ ስለ ርሷ ስትል ብዙ መከራዎችን መቀበል ሲገባህ በተቃራኒው በቁጣ ርሷን በማስጨነቅና በማሸበር ታስፈራራታለህን? ክርስቶስ እንዲህ አላደረገም፡፡
“በውኃ መታጠብና ከቃሉ ጋር አንጽቶ አንዲቀድሳት ስለ ርሷ (ስለ ቤተ ክርስቲያን) ራሱን አሳልፎ ሰጠ ፡፡ ከቃሉ እንደምንረዳው ቤተ ክርስቲያን (እኛ) አስቀድማ ንጽሕት አልነበረችም፤ ጉድፍ ነበረባት፤ መልከ ጥፉም ነበረች፡፡ ስለዚህም ለእርሱ የተገባች አልነበረችም፡፡ አንተ እንደ ቤተ ክርስቲያን የሆነችውን ሴት ሚስትህ ትሆን ዘንድ አትመርጥም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ከክርስቶስ የተለየችውን ያህል ከአንተ ፈጽማ የማትስማማውን ሴት ሚስትህ ትሆን ዘንድ ወደ አንተ አታቀርባትም፡፡ እርሱ ግን እጅግ መልከ ጥፉ ብትሆንም አልጠላትም፣ አልተጸየፋትም፣ ስለ መልከ ጥፉነቷ የተጻፈውን መስማት ትፈልጋለህን? ቅዱስ ጳውሎስ ስለ ርሷ ምን እንደሚል ስማ “ቀድሞ ጨለማ ነበራችሁ” (ኤፌ.፭፡፰) አላት፤ የገጽታዋን መጥቆር ትመለከታለህን? ከጨለማስ የበረታ ጥቁረት ምን አለ? የአመሏን መክፋት ደግሞ ስማ “በክፋትና በምቀኝነት” ይልና “የምንኖር” ይላል፤ ስለ ነውሮቿ ደግሞ “የማንታዘዝና የምንስት ለልዩ ልዩ ተድላ እንደ ባሪያዎች የምንገዛ” ይላታል (ቲቶ.፫፡፫)፡፡
ነገር ግን ለርሷ ስለተደረገላት በጎነት ምን ማለት ይቻለኛል? እርሷ ስንፍናን የተሞላችና ክፉ አንደበት የነበራት እንዲሁም በነውሮቿ ሁሉ ያደፈች ብትሆንም እነዚህ ሁሉ ጠባዮቿ ከርሷ አላራቀውም፡፡ ነገር ግን ልክ የደስ ደስ እንዳላት ልጃገረድ በአፍቀሪም ዘንድ ለምትወደድ ውብ ሴት እንደሚደረገው ርሱ ስለ ርሷ ራሱን አሳልፎ የሰጠ አይደለምን? ይህንንም በማድነቅ ቅዱስ ጳውሎስ “ስለጽድቅ የሚሞት በጭንቅ ይገኛልና ስለ ቸር ሰው ግን ሊሞት ስንኳ የሚደፍር ምናልባት ይገኛል” ይልና “ነገር ግን ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቷልና”(ሮሜ.፭፡፯-፰) ብሎአል፡፡ በዚህ መልክ ርሷ ለርሱ ትሆን ዘንድ አቀረባት፤ በመንፈሳዊ ውበትም አስጌጣት፤ ንጽሕት አደረጋት፤ ስለ ርሷም ራሱን አሳልፎ ለመስጠት ስንኳ የጨከነ ሆነ፡፡
(የትዳር አንድምታ እንደ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አስተምህሮ ገጽ 17-19 - በመምህር ሽመልስ መርጊያ)
“ላገቡት” የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ምክር
ባልና ሚስት አንድ መኾናቸውን ብዙ ጊዜ ስለ ተማራችሁት እርሱን አልደግምላችሁም፡፡ ከዚህ ተነሥቼ ግን ጥያቄ ልጠይቃችሁ፦ ከሰውነታችሁ ውስጥ አንዱ ሕዋስ ቢታመም ቆርጣችሁ ትጥሉታላችሁን? ከሕመሙ ይፈወስ ዘንድ የምትጥሩ አይደላችሁምን? ለትዳር አጋራችሁም እንደዚህ መኾን አለባችሁ፡፡ እንደዉም'ኮ፥ ከሰውነታችሁ ሕዋስ ውስጥ ያለው በሽታ አንዳንዴ ላይድን ይችላል፡፡ የትዳር አጋራችሁ ግን፥ ምንም ክፉ ቢኾንም ሊለወጥ ይችላል፡፡
በሰውነታችን ላይ የሚኖረው አንዳንዱ ችግር ለምሳሌ ልምሾ እጅ ወይም እግር ሥራ መሥራትን ሊከለክለን፣ በሌላዉ የሰውነታችን ክፍል ላይ ጫና ሊያሳድርብን ይችላል፤ ነገር ግን ይበልጥ እንክብካቤ እናደርግለታለን እንጂ ቆርጠን አንጥለዉም፡፡
ታዲያ መዳን ለማይችለው ሰውነታችን ይህን ያህል እንብካቤ እያደረግንለት ሳለ፥ የመዳን (የመለወጥ) ዕድል ያለው አካላችንን (ባለ ትዳራችንን) መቁረጥ (መፍታት) እንደ አማራጭ ማስቀመጣችን እንዴት ብናብድ ነው?
የሕይወት አጋሬን እንዴት ልምረጥ
“ፍቅር ይዞኛል” “አፍቅሬአለሁ” ማለት በብዙ ወጣቶች ዘንድ የተለመደ ነገር ነው፡፡ ወጣትነትወንዶች ሴቶችን ሴቶችም ወንዶችን ለፍቅር የሚመርጡበት እድሜ ነው፡፡ በወጣትነት ዘመንበተቃራኒ ጾታ መሳብ፤ የራስን ሰው ለማግኘት ጊዜ ወስዶ ማሰብና መጨነቅ የተለመደ ክስተትነው፡፡ መፈላለግ ተፈጥሮአዊ ቢሆንም ሁሉም ለቁም ነገር ነው ለማለት ግን አያስደፍርም፡፡ በዚህየተነሣ ወጣቶች ተቃራኒ ጾታን ለጓደኝነት የሚመርጡባቸውን ምክንያቶች በሚገባ ማወቅ አስፈላጊ ያቸው ነው፡፡ የተወሰኑትን ምክንያቶች በዚህ ትምህርት ለማየት እንሞክራለን፡፡
1. ወጣቶች የተቃራኒ ጾታ ጓደኛ የሚይዙባቸው ምክንያቶች
ሀ. ጓደኛ የለውም (የላትም) እንዳይባሉ፤
ለ. ሌሎች ሲይዙ በማየት፤
ሐ. ለሩካቤ ሥጋ ፍላጎት (ለዝሙት) (2 ሳሙ 13፡11)፤
መ. በፍቅር ስለወደቁ (ዘፍ. 34፡3)፤
ሠ. የትዳር ጓደኛ ፈልገው (ዘፍ. 29፡18)፤
ረ. ለቁሳዊ ጥቅም ብለው (መሳ. 16፡5)
ሰ. በፉክክር ስሜት፣ ሌሎችም ለማናደድ ሲፈልጉ ወ.ዘ.ተ፡፡
2. የሕይወት አጋርን የምንመርጥባቸው ደረጃዎች፡-ወጣቶች የፍቅር ጓደኛ መፈለጋችሁ ኃጢአት ሳይሆን ተፈጥሮአዊ እና ጤናማ ስሜት ነው፡፡ነገር ግን ይህን የተቀደሰ ፍላጎት ያለ ጊዜው፣ በተሳሳተ ምርጫ እና ጤናማ ባልሆነ ፍላጎት እንዳናበላሸው ጥንቃቄ ማድረግ አለብን፡፡ስለዚህ የሚከተሉትን መመዘኛዎችና ደረጃዎችን ማጤን ትክክለኛ ውሳኔ እንድንወስን ያስችለናል፡፡ እንዲሁም ያለጊዜው ባደረግነው ያልተገባ ግንኙት ወይምበተሳሳተ ምርጫችን እንዳንጸጸት ያደርገናል፡፡
2.1. አካላዊ ብቃት፦
ወንዶች ለአቅመ አዳም ሴቶች ለአቅመ ሔዋን መድረሳችንን፤ ሰውነታችን ሌላ ሰውን ለመቀበል የተዘጋጀ መሆኑን ማወቅ አለብን፡፡
2.2. መንፈሳዊ ብስለት፡-
በመንፈሳዊ ሕይወት ጠንካራ መሆናችንን እንዲሁም ከአንድ ክርስቲያን የሚጠበቅ መንፈሳዊብስለት እንዳለን ለማረጋገጥ ራሳችንን ማየት ተገቢ ነው፡፡ በሕይወታችን ወይም በኑሮአችን ሁሉእግዚአብሔርን እንደምናስቀድም፣ የጸሎት ሕይወታችን ምን እንደሚመስል፣ መጽሐፍ ቅዱስንየማንበብና ለቃሉ ያለንን ፍቅር፣ የመንፈሳዊ ሕይወታችንን ጥንካሬ … ወ.ዘ.ተ ያጠቃልላል፡፡
2.3. የኢኮኖሚ ብቃት፦
ፍቅር ሓላፊነት እና ተጠያቂነት ያለበት ግንኙነት ነው፡፡ ገንዘብ ለዚህ ዓለም ኑሮ አስፈላጊ ነገርነው፡፡ ስለዚህ ከራሳችን አልፈን ሌላ ሰው ማኖር እንዲሁም መንከባከብ የሚያስችል አቅም አለኝ ወይብለን ራሳችንን መፈተሽ አለብን፡፡ ለመተዳደሪያ የሚሆን በቂ ገቢ የሚያስገኝ ሥራ አለን ወይ? የሚለውን ጥያቄ በአስተማማኝ ሁኔታ መመለስ ይገባናል፡፡
2.4. የሥነ ልቡና ዝግጅት ፦
አንድን ሰው ለማፍቀር ከመነሣታችን በፊት ሥነ ልቡናዊ ዝግጅት ማድረግ አለብን፡፡ ፍላጎታችንን መመርመር፣ ሌላ ሰውን ለመቀበል የመንፈስ ዝግጅት ማድረግ፣ በስሜት ሳይሆንበእርጋታና በሰከነ መንፈስ ምርጫችንን ማጤንን አስፈላጊ ነው፡፡
ወጣቶች የሕይወት አጋራችሁን ስትመርጡ እነዚህ ከላይ የተዘረዘሩትን መመዘኛዎች ማሟላታችሁን አረጋግጡ፡፡ ፍቅር የከበረ የእግዚአብሔር ስጦታ መሆኑን ተገንዝባችሁ በስሜታዊነትየፍቅር ጓደኛ ከመምረጥና በኋላ ከመጸጸት ራሳችሁን ጠብቁ፡፡ ከክፉ የጎልማሳነት (የወጣትነት) ምኞት በመራቅና በመሸሽ እያንዳንዱን ጉዞአችሁን በእግዚአብሔር ቃል እየመረመራችሁ እናፈቃዱን እየጠየቃችሁ በመንፈስ የምትመሩ ሁኑ፡፡
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ. አሜን
[ጥርጥር_እና_እምነት ]
(#ማክሰኞ-ቶማስ)
♧ጥርጥሮች በተለያየ መልክ ሊመጡ ይችላሉ ፥ አብዛኛዎቹ ቀድመን የያዝናቸው እውቀቶች ወይም አቅጣጫዎችን ሊመሠረቱ ይችላሉ፡፡ እነዚህ እውቀቶች አመጣጣቸው መነሻ ሊኖረው ይችላል ፤ አከባቢያችን ያሉ ሰዎች፣ የቀደመ ጉዳት፣ የምናነባቸው መጻሕፍት፣ የምናያቸው ቪዶዎች ...ወዘተ በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል ። እነዚህን እውቀቶች ይዘን የተቀረውን ነገር ሁሉ በእነዚህ መነጽርነት ለመመልከት እንሞክራለን፡፡ እምነት ደግሞ በተቃራኒው፤ ከእነዚህ አቅጣጫዎች ውጪ ወይም በላይ ሆኖ መመልከትን መጓዝ ይጠይቃል፡፡ ምንም እንኳን እነዚህ ቃላት ተቃራኒ ቢመስሉም መገናኛ ቦታ አላቸው፡፡
.
.
✞ጥርጥር ወደ እምነት ስንጓዝ መሸጋገርያ ምዕራፍ ነው፡፡ በዳግም ትንሣኤ በቤተክርስቲያን የሚነበበው ወንጌል (ዮሐ 20፡19-ፍጻሜ) ይህንን እንመለከት ዘንድ ይጋብዘናል :- በፋሲካው ዕለት ክርስቶስ ለደቀመዛሙርቱ በመጣ ጊዜ ቶማስ ከእነሱ ጋር አልነበረም፡፡ ሌሎቹ ደቀመዛሙርት ጌታችንን አየነው ብለው ሲነግሩት አለመናቸውም ይልቅም ይህን አለ "የችንካሩን ምልክት በእጆቹ ካላየሁ ጣቴንም በችንካሩ ምልክት ካላገባሁ እጄንም በጎኑ ካላገባሁ አላምንም" (ዮሐ 20፡25)፡፡
.
.
ይህንን ስንሰማ "ክርስቶስ ስለ ትንሣኤው አስተምሮት የለም እንዴ ?..ጌታ አላዓዛርን ከሞት ሲያስነሳ በእዛ አልነበረም እንዴ? .. ሌሎቹን ደቀመዛሙርት ለምን አላመናቸውም?.. ለምንስ ሊዋሹኝ ይችላሉ ብሎ ገመተ? " ልንል እንችላለን፡፡ እውነታው ግን ሁላችንም በሕይወታችን እንደዚህ አይነት አጋጣሚዎች አሉን፤ በውስጣችን ከምናውቀው እውነት ይልቅ ጥርጥራችን በልጦብን ያውቃል፡፡ የቶማስ ጥርጥር የቀደመ እውቀቱን/አስተሳሰቡን መሰረት ያደረገ ነው፡፡ እንደሚታወቀው ቶማስ በክርስቶስ ከመጠራቱ በፊት ሰዱቃዊ ነበር ፤ ሰዱቃውያን ደግሞ በትንሣኤ አያምኑም ነበር (ሐዋ 23፡8)፡፡ የጌታችንን ትንሣኤ የተጠራጠረው የቀደመ የሰዱቃዊ አስተሳሰቡ መሰረት ሆኖት ነው፡፡
.
.
በተመሳሳይ ሁኔታም የእኛ ጥርጥሮች በብዛት አጥብቀን ከያዝናቸው አቅጣጫዎች የሚመጡ ናቸው፡፡ በስምንተኛው ቀን (በዳግም ትንሣኤ ዕለት) ክርስቶስ ለደቀመዛሙርቱ በተገለጠላቸው ጊዜ ክርስቶስ ቶማስን ለምን አላመንክብኝም ብሎ አለጠየቀውም ይልቅም እንዲህ አለው "ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን" (ዮሐ 20፡27)፡፡ ጌታችንን ቶማስን እውቀቱን/አቅጣጫውን ይፈትን ዘንድ ጋበዘው፣ ከዛ ተሻግሮ ወደሚበልጠው ይጓዝ ዘንድ፡፡ የቶማስ ጥርጥር የቀደመ እውቀቱን ትቶ ወደሚበልጠው እምነት እንዲጓዝ ረዳው፤ ጥርጥር ብቻውን ሳይሆን ጥርጥሩን በጌታ ፊት ማቅረቡ ጭምር እንጂ፡፡
.
.
ቶማስም ወዲያው አመነ ክርስቶስም እንዲህ አለው "ሳያዩ የሚያምኑ ብፁዓን ናቸው" (ዮሐ 20፡29)፡፡ የዚህ ቃል አንደኛው አረዳድ የክርስቶስን ትንሣኤ በአይናቸው ሳያዩ የሚያምኑ (ክርስቲያኖች) ብፁዓናቸው የሚል ነው፡፡ ይህ ቃል ግን ከዚህ በላይ ነው፤ ካስቀመጡት አቅጣጫ ውጪ የሚመለከቱ፣ ከቀደመ እውቀታቸው በላይ የሚያዩ ማለት ነው፡፡ የቶማስ ጥርጥር ካስቀመጠው እውቀት በላይ እንዲያስብ፣ ከሚመለከተው አቅጣጫ ውጪ እንዲያይ ረድቶታል፤ በዚህም እምነት ትገኛለች፡፡
.
.
♡ሁላችንም ጥርጥር በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ ያጋጥመናል፤ የሚጠበቅብን ጥርጥራችን በተለያዩ ነገሮች አብዝተነው (በንባብ፣ በመስማት፣ በመጠየቅ) ወዴት እንደሚያመራን ማየት ሳይሆን፤ እንደ ቶማስ ጥርጥራችንን ወደ ጌታ ይዘን መቅረብ ነው፡፡ ጌታም በሕይወታችን ውስጥ የሚገኙትን መጠራጠሮች ወደ እምነት መሻገሪያ መንገድ ያደርጋቸዋል፡፡ እምነታችን ጥርጥር ባለማስተናገዳችን አይለካም ይልቅም እነዚህን ጥርጥሮች ወደ እግዚአብሔር በማቅረባችን እንጂ፡፡ የእምነት ሙሉ የለም፤ ሁላችንም ከዛሬ የተሻለ እምነት ይኖረን ዘንድ ተጓዦች ነን፤ ጥርጥር ደግሞ ወደዛ መሻገሪያ ድልድይ ነው፡፡ እግዚአብሔር እምነት ይሰጠን ዘንድ ስንለምነው ጥርጥር እንደሚመጣ ጠብቁ፤ የእምነት መንገድ መሻገሪያ ድልድይ ነውና፡፡ የጌታችን የትንሣኤው ብርሃን በእኛ ላይ ያብራልን፡፡ የቅድስት ማርያም እና የቅዱሳኑ ሁሉ በረከታቸው በእኛ ላይ ይደር፡፡ አሜን።
[ምንጭ :- ተወዳጅ ስለሺ ፥ እንስት ጸሀፊ ግለ ማህደር የተገኘ
< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >
