en
Feedback
"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

Open in Telegram

@Dan12bot ለአስተያየትዎ ይህን ይጠቀሙ እናመሠግናለን

Show more
1 134
Subscribers
No data24 hours
-27 days
-2330 days
Posts Archive
እንኳን አደረሳችሁ! ሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል ዑራኤል የሚለው ስም `ዑር' እና 'ኤል' ከሚሉ ሁለት ቃላት የተመሠረተ ስም ነው። ዑራኤል ማለት ትርጉሙ “የብርሃን ጌታ”፣ ”የአምላክ ብርሃን" ማለት ነው። ቅዱስ ዑራኤል ከ7ቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ሲሆን ከፍጥረተ ዓለም ጀምሮ በመብረቅና በነጎድጓድ ላይ የተሾመ መልአክ ነዉ። በመሆኑም መባርቅት ለጥጋብና ለበረከት እንዲበርቁ፣ ነጎድጓድም ለሰላም እንዲሆን ያሰማራል። መጽ/ሄኖክ 6÷2 ምሥጢረ ሰማይና እውቀትንም ሁሉ ለሄኖክ የገለጸለት የፀሀይን የጨረቃን የከዋክብትንና የሰማይ ሰራዊትን ብርሃንን የሚመራ እርሱ መሆኑን ለሄኖክ ነግሮታል። መጽ/ሄኖክ 28÷13 • ቅድስት ድንግል ማርያምን፣ ከልጇ ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ወደ ግብጽ ስትሰደድ መንገድ የመራ፤ • ክርስቶስ ለዓለም ቤዛ በተሰቀለ ጊዜ፣ ክቡር ደሙን በብርሃን ጽዋ ተቀብሎ፣ በብርሃነ መነሳንስ በዓለም ላይ የረጨ፤ •እውቀት ለተሰዎረባቸው ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል ጽዋ ጥበብን ያጠጣ፤ • አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በመልአኩ አማላጅነት ብዙ ድርሰት የደረሱት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ጽዋ ሕይወትን ስላጠጣቸው ነው፣ • በቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ የተመሰረቱ ገዳማት በቅዱስ ዑራኤል መሪነት ነው፤ የመልአኩ የቅዱስ ዑራኤል በዓላት በዓመት 3 ናቸው። • ጥር 22 በዓለ ሲመቱ፣ • መጋቢት 27 የጌታ ደሙን ለዓለም የረጨበት፣ • ሐምሌ 21 እና 22 ቅዳሴ ቤቱ የሚከበርበት። በጸሎቱ ለተማጸነ ከአምላኩ በረከትን ምህረትን የሚያሰጥ አዛኝ እሩህሩህ መልአክ ነው። የቅዱስ ዑራኤል አማላጂነት አይለየን፤ ሁላችንንም ይጠብቀን፡፡

እንኳን አደረሳችሁ! ሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል ዑራኤል የሚለው ስም `ዑር' እና 'ኤል' ከሚሉ ሁለት ቃላት የተመሠረተ ስም ነው። ዑራኤል ማለት ትርጉሙ “የብርሃን ጌታ”፣ ”የአምላክ ብርሃን" ማለት
+1
እንኳን አደረሳችሁ! ሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል ዑራኤል የሚለው ስም `ዑር' እና 'ኤል' ከሚሉ ሁለት ቃላት የተመሠረተ ስም ነው። ዑራኤል ማለት ትርጉሙ “የብርሃን ጌታ”፣ ”የአምላክ ብርሃን" ማለት ነው። ቅዱስ ዑራኤል ከ7ቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ሲሆን ከፍጥረተ ዓለም ጀምሮ በመብረቅና በነጎድጓድ ላይ የተሾመ መልአክ ነዉ። በመሆኑም መባርቅት ለጥጋብና ለበረከት እንዲበርቁ፣ ነጎድጓድም ለሰላም እንዲሆን ያሰማራል። መጽ/ሄኖክ 6÷2 ምሥጢረ ሰማይና እውቀትንም ሁሉ ለሄኖክ የገለጸለት የፀሀይን የጨረቃን የከዋክብትንና የሰማይ ሰራዊትን ብርሃንን የሚመራ እርሱ መሆኑን ለሄኖክ ነግሮታል። መጽ/ሄኖክ 28÷13 • ቅድስት ድንግል ማርያምን፣ ከልጇ ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ወደ ግብጽ ስትሰደድ መንገድ የመራ፤ • ክርስቶስ ለዓለም ቤዛ በተሰቀለ ጊዜ፣ ክቡር ደሙን በብርሃን ጽዋ ተቀብሎ፣ በብርሃነ መነሳንስ በዓለም ላይ የረጨ፤ •እውቀት ለተሰዎረባቸው ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል ጽዋ ጥበብን ያጠጣ፤ • አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በመልአኩ አማላጅነት ብዙ ድርሰት የደረሱት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ጽዋ ሕይወትን ስላጠጣቸው ነው፣ • በቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ የተመሰረቱ ገዳማት በቅዱስ ዑራኤል መሪነት ነው፤ የመልአኩ የቅዱስ ዑራኤል በዓላት በዓመት 3 ናቸው። • ጥር 22 በዓለ ሲመቱ፣ • መጋቢት 27 የጌታ ደሙን ለዓለም የረጨበት፣ • ሐምሌ 21 እና 22 ቅዳሴ ቤቱ የሚከበርበት። በጸሎቱ ለተማጸነ ከአምላኩ በረከትን ምህረትን የሚያሰጥ አዛኝ እሩህሩህ መልአክ ነው። የቅዱስ ዑራኤል አማላጂነት አይለየን፤ ሁላችንንም ይጠብቀን፡፡

እግዚአብሔር ሲቀጣን "[አንድ] ሐኪም አእምሯቸውን የሳቱ ሰዎች ቢሰድቡት፥ ስድባቸውን ከቁም ነገር አይቆጥረውም፡፡ እንዲህ አእምሯቸውን እንዲስቱ ያደረጋቸውን ምክንያት ያስወግድላቸው ዘንድ ይተጋል እንጂ፡፡ 'ሰድበውኛል' ብሎ የራሱን ጥቅም አያይም፤ የሕሙማኑን እንጂ፡፡ በጥቂቱም ቢኾን ሻል ካላቸውና ራሳቸውን መግዛት የሚችሉ ከኾነም እጅግ ደስ ይሰኝባቸዋል፡፡ ውስጡ በፍጹም ሐሴት ይሞላል፡፡ መድኃኒት መስጠቱን በፊት ከሚያደርግላቸው ይልቅ ተግቶ ይሰጣቸዋል፡፡ 'ከዚህ በፊት ሰድበውኛልና ልበቀላቸው' ብሎ በፍጹም አያስብም፡፡ ይበልጥ እንዲጠቀሙና ወደ ቀድሞ ጤናቸው ይመለሱ ዘንድ ተግቶ ይሠራል እንጂ፡፡ "እግዚአብሔርም እንደዚህ ነው፡፡ ምንም እንኳን እጅግ ጥልቅ በኾነ ኃጢአት ውስጥ ብንወድቅም፥ ኹሉንም ነገር የሚያደርገው እኛን ከመቅጣት አንጻር አይደለም፤ የሚቀጣን ስለ ሠራነው የኃጢአት ዓይነት አይደለም፡፡ ከዚህ ሕመማችን እንድንፈወስ ብሎ ነው እንጂ፤ በዚሁ መንገድ ሊመለሱ ይችላሉ ብሎ በማሰብ ነው እንጂ፡፡" (ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ፥ ወደ ቴዎድሮስ፥ ገጽ 36)

✍ ✝#በቀኖና_ቤተ ክርስቲያን መሰረት  የሐዋርያት ክህነታዊ መሥመር የሌለው፣ ያለ ቅዱስ ሲኖዶስና ያለ ቅዱስ ፓትሪያሪክ  የተከናወነ ሽመት ኦርቶዶክሳዊ ቅቡልነት የለውም፡የሊቃ ካህናት የኢየሱስ ክርስቶስ ክህነትም ፈጽሞ አይደለም።ከክርስቶስ የተገኘ በቅዱሳን ሐዋርያት የተገኘ  ሳይቋረጥ የመጣ  የሐዋርያት ክህነታዊ ቅብብል (apostolic succession) ይህ ይመስላል። #ኢየሱስ_ክርስቶስ 1.ማርቆስ 2. አንያኖስ 3.ሜልያስ 4.ክርዳኑ 5.አምብርዮስ 6. ዮስጦስ 7. አውማንዮስ 8. መርክያኖስ 9. ክላውያኖስ 10. አክርጵያኖስ 11. ዮልዮስ 12. ድሜጥሮስ 13.ያሮክላ(ሔራክልስ) 14.ዲዮናስዮስ 15. መክሲሞስ 16.ቴዎናስ 17. ጴጥሮስ (ተፍጻሜተ ሰማዕት) 18. አኪላስ 19.እለእስክንድሮስ 20. አትናቴዎስ 21. ጴጥሮስ 2ኛ 22. ጢሞቴዎስ 23. ቴዎፍሎስ 24. ቄርሎስ 25ዲዮስቆሮስ 26. ጢሞቴዎስ2ኛ 27.ጴጥሮስ 3ኛ 28.አትናቴዎስ 2ኛ 29. ዮሐንስ 30. ዮሐንስ 2ኛ 31.ዲዮስቆሮስ2ኛ 32.ጢሞቴዎስ3ኛ 33. ቴዎዶስዮስ 34. ጴጥሮስ 4ኛ 35. ድምያኖስ 36. አንስጣስዮስ 37. አንድራኒቆስ 38. ብንያሚን 39. ያቃቱ (አጋቶን) 40. ዮሐንስ 3ኛ 41. ይስሐቅ 42.ስምዖን 43.እለእስክንድሮስ 2ኛ 44. ቆዝሞስ 45. ቴዎድሮስ 46.ካኤል (ሚካኤል) 47. ሚናስ 48. ዮሐንስ 4ኛ 49. ማርቆስ 2ኛ 50. ያዕቆብ 1ኛ 51. ስምዖን 2ኛ 52. ዮሳብ 1ኛ (ዮሴፍ) 53.ካኤል(ሚካኤል) 2ኛ 54.ቆዝሞስ 2ኛ 55. ስንትዮ 1ኛ 56. ሚካኤል 1ኛ 57.ገብርኤል 1ኛ 58.ቆዝሞስ 3ኛ 59. መቃርዮስ 1ኛ 60. ታውፋኔዎስ 61. ሚናስ 2ኛ 62. አብርሃም 63. ፊላታዎስ 64. ዘካርያስ 65. ስንትዩ 2ኛ 66. ክርስቶዶሉ (ገብረ ክርስቶስ) 67. ቄርሎስ 2ኛ (ጌርሎስ) 68. ሚካኤል 2ኛ 69. መቃርዮስ 2ኛ (መቃርስ) 70. ገብርኤል 2ኛ 71. ሚካኤል 3ኛ 72. ዮሐንስ 5ኛ 73. ማርቆስ 3ኛ 74. ዮሐንስ 6ኛ 75. ቄርሎስ 3ኛ 76.አትናቴዎስ 3ኛ 77. ገብርኤል 3ኛ 78. ዮሐንስ 7ኛ 79. ታውዳስዮስ 2ኛ 80.ዮሐንስ 8ኛ 81. ዮሐንስ 9ኛ 82. ብንያሚን 2ኛ 83. ጴጥሮስ 5ኛ 84. ማርቆስ 4ኛ 85. ዮሐንስ 86. ገብርኤል4ኛ 87. ማቴዎስ 1ኛ 88. ዮሐንስ 5ኛ 89. ዮሐንስ 11ኛ 90. ማቴዎስ 2ኛ 91.ገብርኤል 6ኛ 92. ሚካኤል 4ኛ 93. ዮሐንስ 12ኛ 94. ዮሐንስ 13ኛ 95.ገብርኤል 7ኛ 96. ዮሐንስ 14ኛ 97.ገብርኤል 8ኛ 98. ማርቆስ 5ኛ 99. ዮሐንስ 15ኛ 100.ማቴዎስ 3ኛ 101ማርቆስ 6ኛ 102.ማቴዎስ 4ኛ 103ዮሐንስ 16ኛ 104. ጴጥሮስ 6ኛ 105. ዮሐንስ 17ኛ 106. ማርቆስ 7ኛ 107. ዮሐንስ 18ኛ 108. ማርቆስ 8ኛ 109. ጴጥሮስ 7ኛ 110. ቄርሎስ 4ኛ 111. ጴጥሮስ 8ኛ 112. ቄርሎስ 5ኛ 113. ዮሐንስ 19ኛ 114. መቃርዮስ 3ኛ 115.ዮሳብ (ዮሴፍ)2ኛ 116.ቄርሎስ 6ኛ 117. ባስልዮስ 118. ቴዎፍሎስ 119. ተክለሃይማኖት 120. መርቆሬዎስ 121. ጳውሎስ 122. ማትያስ Welday Meresa Ze Tewahdoo

#ክፉ_አሳብ ልጆቼ! ከመጀመሪያውኑ ክፉ አሳብ ባታስቡ መልካም ነው፡፡ ካሰባችሁ ግን ቢያንስ አትናገሩት፡፡ በዚያው በሕሊናችሁ ውስጥ እያለ ዝም አሰኙት፤ ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላም ወዳለመኖር ይኼዳል፡፡ እኛ ሰዎች ነን፡፡ በመኾኑም ብዙውን ጊዜ ክፉ፣ ያልተገቡና ጸያፍ ነገሮችን እናስባለን፡፡ ነገር ግን ቢያንስ እነዚህን አሳቦች አንናገራቸው፤ ቢያንስ ወደ ቃል አንለውጣቸው፡፡ ወደ ውጭ እንዳይወጡ አምቀን እንያዛቸው፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ እየከሰሙና እየደከሙ እየጠፉም ይኼዳሉ፡፡ አንድን እንስሳ ወደ ጉድጓድ ብትጥሉትና ጉድጓዱንም በመክደኛ ብትከድኑት ያ ወደ ጕድጓድ የጣላችሁት እንስሳ የሚተነፍሰውን አየር አጥቶ ይሞታል፡፡ ምናልባት ጥቂት ቀዳዳ ካገኘ ግን በዚያች ቀዳዳ በምትገባው አየር በሕይወት መቆየት ይችላል፡፡ ሲጨንቀውም እናንተን ክፉኛ ለመጉዳት ይዝታል፤ ከወጣም በኋላ ይጎዳችኋል፡፡ ልክ እንደዚሁ እናንተም በልቡናችሁ የተመላለሰውን ኩላሊታችሁ ያጤሰውን ክፉ አሳብ መውጫ ቀዳዳ እንዳይኖረው አድርጋችሁ ብትከድኑት (ብታፍኑት) ይሞታል፤ ከመኖር ወዳለመኖር ይለወጣል፡፡ በአንደበታችሁ በመናገር ጥቂት ቀዳዳ ከከፈታችሁለትና እንደ እንስሳው እንዲተነፍስ ከፈቀዳችሁለት ግን ክፉው አሳብ ክፉ ግብርን ይወልዳል፡፡ ያቆጠቁጣል፡፡ በአሳብ ሳለ ከጎዳችሁ በላይም በገቢር ተወልዶና ተለውጦ ክፉኛ ይጎዳችኋል፡፡ (#የክርስቲያኖች_መከራ #በቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ ገጽ 7➛በገብረ እግዚአብሔር ኪደ የተተረጎመ)

+• የሐዋርያው የመጨረሻ አደራ •+ በጥንቷ ቤተክርስቲያን ውስጥ ስለ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ የሚነገር አንድ ትውፊት አለ:: ይህንን ትውፊት ቅዱስ ሄሬኔዎስ በሥራዎች ውስጥ አካትቶት እናገኛለን :: በትውፊቱ መሠረት የተወደደው ሐዋርያ ሊለያቸው መሆኑን የተገነዘቡት ደቀ-መዛሙርቱ ተሰብስበው "ለእኛ ምን መልእክት ተተውልናለህ?" ብለው ጠየቁት:: እርሱም "ልጆቼ ሆይ፥  እርስ በእርሳችሁ ተዋደዱ" አላቸው:: ይህንንም እጅግ ብዙ ጊዜ ደጋገመው:: ደቀ-መዛሙርቱም "ከዚህ ሌላስ የምትለን አለ?" ብለው ጠየቁት:: እርሱም "ይህ ይበቃችኋል፤ የጌታ ትእዛዝ ይህ ነውና" ብሎ መለሰላቸው:: የክርስትና መነሻው፥  ማዕከሉም ሆነ መጨረሻው ፍቅር ነው:: ከክርስትና ውጪ "አምላክ ፍቅር ስቦት ኃጢአተኛ የሆነውን ሰውን ለማዳን እርሱ ራሱ ሰው ሆነ" የሚል ሃይማኖት የለም:: ክርስትና በአንድ ቃል ይገለጽ ቢባል "ፍቅር" የሚለው ቃል ይገልጸዋል:: የእውነተኛ ክርስቲያኖች መገለጫ ምንድር ነው ቢባል "ፍቅር" ተብሎ ሊጠቀለል ይችላል:: ጌታችንም ይህንን ሲያስረዳ "እርስ በርሳችሁ ፍቅር ቢኖራችሁ፥ ደቀ መዛሙርቴ እንደ ሆናችሁ ሰዎች ሁሉ በዚህ ያውቃሉ።" (ዮሐ 13:35) ብሎን ነበር:: ሰዎች ዛሬ ላይ አይተውን የክርስቶስ ደቀ-መዛሙርት ስለመሆናችን ቢጠረጥሩን አትደነቁ - እንደኛ ፍቅር ያጣ የለምና! አንዳንዴ እድሜ ልካችንን ክርስቲያን መሆናችንን እያወጅን እግዚአብሔርን ግን ላናውቅ እንችላለን:: 'ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል?' ልትሉኝ ትችላላችሁ:: ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ የዚህን መልስ ሲሰጠን:- "ፍቅር የሌለው እግዚአብሔርን አያውቅም፥ እግዚአብሔር ፍቅር ነውና።" (1 ዮሐ 4:8) ይለናል:: ክርስቲያን መሆናችንን ለዓለም ሁሉ ልናውጅ እንችላለን፤ ፍቅር ከሌለን ግን አዋጁ ሁሉ ከንቱ ነው:: ይህ ምን እንደሚያሳጣን ልብ በሉ:: ሐዋርያው "ለሚወጣ ሁሉ በክርስቶስም ትምህርት ለማይኖር ሰው አምላክ የለውም፤ በክርስቶስ ትምህርት ለሚኖር አብና ወልድ አሉት።" (2 ዮሐ 1:9) ይለናል:: እንግዲህ የክርስቶስ ትእዛዝ ፍቅር ከሆነ፤ እኛ ደግሞ ፍቅር ካጣን፤ ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል ብለን እየፎከርን ክርስቶስን አጣነው ማለት አይደለም? ክርስቶስን ካጣን ደግሞ አብም ሆነ መንፈስ ቅዱስ አጣን ማለት አይደለም? ለክርስቲያን ከዚህ በላይ ኪሳራ ምን ይኖር ይሆን? 🖋 Fresenbet G.Y Adhanom

ፍቅር ሲመነምን ውጤቱ የበዙ ጥፋቶችን ማስከተል ይኾናል!! የፍቅር እጦት ቂም እና ጥላቻን ይፈጥራል። ይኽ ደግሞ በኃጢአት ሐሴት ማድረግን ያመጣል። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲኽ ይላል፦ "ጠላትኽ ቢወድቅ ደስ አይበልኽ፥ በመሰናከሉም ልብኽ ሐሴት አያድርግ" ምሳ 24፥17 ሌላው የፍቅር እጦት ውጤት ቁጣ እና ክፋት ነው። እንዲህ ያለው ኹኔታ ስድብን፣ ጠብን፣ ግድያን፣ ነቀፋን፣ ማዋረድንና ስም ማጥፋት ማስፋፋትን ያስከትላል። ከዚኽ በተጨማሪ የፍቅር እጦት ወይም ጉድለት ወደ ቅንዓት፣ ወደ አላዋቂነት፣ ወደ ኩራት፣ ጽናትን ወደማጣትና ወደ ጭካኔ ይመራል። ለእግዚአብሔር የሚኾን ፍቅርን ማጣት በብዙ ጉዳዮች ውስጥ ሊገለጥ ይችላል፤ ከእርሱም መካከል ጸሎትን፣ መጽሐፍ ቅዱስንና ቤተ ክርስቲያንን መርሳት ጥቂቶቹ ናቸው። በእግዚአብሔር ፊት መቆምን ማጣት እና በእግዚአብሔር መንግሥት ፈጽሞ ሐሴት አለማድረግ ደግሞ ሌሎቹ ጉድለቶች ናቸው። ብጹዕ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ

ክርስቲያን እግዚአብሔርን በእምነት ይፈልገዋል። ከእእምሮ ይልቅ በልቡ ያምነዋል። በእምነት እግዚአብሔርን ያገኘ ክርስቲያን አካባቢውን ሳይሆን እግዚአብሔርን ያያል ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን በሌሊት በገሊላ
ክርስቲያን እግዚአብሔርን በእምነት ይፈልገዋል።  ከእእምሮ ይልቅ በልቡ ያምነዋል። በእምነት እግዚአብሔርን ያገኘ ክርስቲያን አካባቢውን ሳይሆን እግዚአብሔርን ያያል ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን በሌሊት በገሊላ ባህር በእግሩ ሲመጣ አየው "ጌታ ሆይ በባህር ላይ በእግሬ እንድመጣ እዘዘኝ" አለው ጌታችንም ፈቀደለት። ቅዱስ ጴጥሮስ በባህሩ ላይ በባዶ እግሩ ሄደ  ነገር ግን የባህሩን ኃይል አይቶ ፈራ ይሰጥምም ጀመረ። ማቴ 14፣22-33 ቅዱስ ጴጥሮስ የሰመጠው ጌታችንን ማየት ትቶ ባህሩን በመመልከት ስለፈራ ነው። ዓለምንና መከራዋን የምናይ ከሆነ እንፈራለን። የምንጠቀመው ስሌታዊ አእምሯችንን ከሆነ እንፈራለን። የምናምነው ከልብ ከሆነ ግን ክርስቶስን እያየን ባህር መከራውን እንሻገራለን።

እስኪ ንገረኝ! ምንስ ታስባለህ? በነፍሱ መከራ የሚቀበለው የትኛው ነው፡- የተሳደበ ሰው ወይስ የተሰደበ ሰው? የተሳደበ ሰው እንደ ኾነ ግልጽ ነው፡፡ ምክንያቱም አስቀድሜ እንደ ነገርኩህ አንድን ሰው ኃጠአተኛ የሚያሰኙት ከውስጥ ከሰውዬው የሚመነጩ ክፋቶች እንጂ ከአፍአ የሚመጡ አይደሉምና ከድርጊቱ ራሱ የታወቀ ነው - “ስሜት” መባሉም ለዚህ ነውና፡፡ ዳግመኛም በተሳዳቢው ላይ በሚፈጥሩት ነገር የታወቀ ነው፡፡ ተሳዳቢው ሲቈጣ ዓይነ ልቡናው ይታወራልና፤ አእምሮው ይታወካልና፤ [የጤና መታወክ ሳይቀር] ሌሎች ስፍር ቊጥር ጉዳትም ይደርስበታልና፡፡ ስለዚህ መከራ እየተቀበለ ያለው ተሰዳቢው ሳይኾን ተሳዳቢው መኾኑን መረዳት ይቻለናል፡፡ ምናልባት “እርሱ ልጄን ሞኝ ብሎ ተሳድቦአል” ልትለኝ ትችላለህ፡፡ እኔም እልሃለሁ፡- መሳደብ ራስን መጉዳት እንደ ኾነ ነግሬሃለሁ፤ ስለዚህ ሰውዬው ደካማ ኾኖ ስለ ተሳደበ አንተም እርሱን መስለህ ደካማ ኾነህ የስድብ አጸፌታ አትስጥ፡፡ እስኪ ልጠይቅህ! አንተም መልስልኝ! ይህ ሰው ልጅህን በመሳደቡ መልካም ነገር አደረገን? መቼስ “አዎ መልካም አድርጓል” አትለኝም፡፡ እንግዲያውስ አንተም እርሱ የፈጸመው መልካም ያልኾነን ግብር አታድርግ፡፡ ልጅህ በተሰደበ ጊዜ ወይም በእንደዚህ ዓይነት ሌሎች ኹኔታዎች ውስጥ በልብህ ሊፈጠር የሚችለውን ስሜት እረዳለሁ፡፡ ኾኖም እርሱን [ተሳዳቢውን] ባለመምሰል በራስህ ላይ መከራን ከማምጣት ተከልከል እልሃለሁ፡፡ ምናልባት “እንደዚህ በማድረጌ እንዳሸነፈኝ ቈጥሮ ቢንቀኝስ? ይህ ሳይበቃውና ከልጄም አልፎ እኔንም ጭምር ቢሰድበኝስ?” ብለህ ትጠይቀኝ ይኾናል፡፡ እኔም፡- “እንዲህ ያደረገውን ሰው በተሳሳተ መንገድ እየኼደ እንደ ኾነ በትሕትና ገሥጸው፣ ራሱን ከመጉዳት በቀር እርሱ አንተን በፍጹም ሊጎዳህ እንደማይችል ምከረው” ብዬ እመክርሃለሁ፡፡ በየውሃት፥ በልብ ውስጥ ያለውን የቊጣ ስሜት መፈረካከስ ይቻላልና፡፡ ስለዚህ በየውሃት ወደ ተሳዳቢው ኺድና ገሥጸው፡፡ ሰዎች እኛን ሲጎዱን ወደ እነርሱ የምንኼደው ግን እኛ እንደ ተጎዳን ለመናገር እንዳልኾነ በደንብ አስተውል፡፡ የምንኼደው ተጎጂዎቹ እነርሱ ራሳቸው ስለ ኾኑና ስለ እነርሱ መዳን ስንል ነው፡፡ ስለዚህ አንተም ወደ ተሳደበው ሰው ስትኼድ ልጅህ በመሰደቡ ምክንያት ወይም አንተ ራስህ እንደ ተሰደብክ በመቁጠር አይኹን፡፡ ተሳዳቢው ሰው አንተን ንቆህ አጥቅቶህ ሊኾን ይችላል፡፡ ነገር ግን ልጄ ተሰደበ ወይም እኔ ተናቅሁ ተጠቃሁ ብለህ አትኺድ፡፡ መኼድ ያለብህ ተሳዳቢው ሰው ራሱን እየጎዳ እንደ ኾነ አስበህና ስለ እርሱ መዳን ብለህ ነው፡፡ ስለዚህ እንደ ሰይፍ የሰላውን የቊጣ ሰይፍህን መልሰው፤ ወደ ሰገባውም ክተተው፡፡ (ነገረ መከራ - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው #በገብረ_እግዚአብሔር_ኪደ )

«ወዳጄ ሆይ! እግዚአብሔር ነዳያንን የሚልክልህ መስጠትን እንድትለማመድ ነው፡፡ ዛሬ በነዳያኑ አድሮ የሚለምንህ ለኋለኛይቱ ቀን ስንቅ እንዲያስቀምጥልህ ወድዶ ነው፡፡ ታድያ ንጉሥ ወደ ቤቱ መጥቶ የሚያባርር ሰው እንደምን ያለ ጎስቋላ ሰው ነው? እንግዲያውስ ነዳያንን ስታይ ወደ አንተ የመጣው ንጉሠ ሰማይ ወምድር ክርስቶስ እንጂ ሰው አይደለምና አትግፋው፡፡ በረከትህንም ከቤትህ አውጥተህ አትሸኘው፡፡» ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

#ቅዱስ_ጴጥሮስ_ወጳውሎስ (ሐምሌ 5) ሐምሌ አምስት በዚች ቀን የክቡራንና የዐበይት አባቶቻችን ሐዋርያት #የቅዱስ_ጴጥሮስ እና #የቅዱስ_ጳውሎስ የሰማዕትነታቸው መታሰቢያ ነው። #ቅዱስ_ጴጥሮስ ጴጥሮስ ማለት ዓለት ማለት ነው፡፡ ማቴ. 16፥18 በዕብራይስጥ ኬፋ ይለዋል፡፡ የመጀመሪያ ስሙ ስምዖን ነው፤ ትውልዱም ከነገደ ሮቤል ነው፡፡ አባቱ ዮና ይባላል፡፡ የተወለደው በገሊላ አውራጃ በቤተ ሳይዳ ነው፡፡ ጴርቴዋ የምትባል ሚስት ነበረችው የሚተዳደረው ዓሣ በማጥመድ ነበር፡፡ ከወንድሙ ከእንድርያስ ጋር ዓሣ ከሚያጠምድበት ተጠርቶ ሐዋርያ ሆኗል፡፡ ማቴ. 4፥19 ጴጥሮስ የዋህ፣ ፈጣን ቁጡ ነበር፡፡ የዋህነቱ ጌታ በባሕር ላይ ሲሄድ አይቶ ጌታ አንተስ ከሆንክ ወደ አንተ እንድመጣ አሰናብተኝ ብሎ በባሕር ላይ ሲሄድ በመሞከሩ ማቴ. 6፥45፣ ፈጣንነቱ ጌታ ደቀመዛሙርቱን በቂሣርያ ሰዎች ማን ይሉኛል ብሎ ጠይቋቸው ሙሴ ነው፣ ኤልያስ ነው ይሉሃል ባሉትና እርሱም መልሶ እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ ጴጥሮስ ፈጥኖ አንተ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ  ክርስቶስ ነህ ብሎ በመመለሱ ማቴ. 16፥16 ቁጡነቱም አይሁድ ጌታን በያዙት ጊዜ ተቶጥቶ የማልኮስን ጆሮ በሰይፍ በመቁረጡ ዮሐ. 18፥10 ላይ ያስረዳል፡፡ መዋዕለ ስብከቱ 50 ዓመት ነው፡፡ /ገድ ሐዋ፣ ዜና ሐዋ/ ንጉሡ ኔሮን ቄሣር መምለኬ ጣዖት ነበረና በሃይማኖት ምክንያት አስሮት ነበር፡፡ አካይያ ዘምቶ ጠላቱን ድል ነሥቶ ሲመለስ ለጣዖት ስገድ ቢለው አልሰግድም አለ፡፡ በችንካር ተቸንክሮ በመስቀል ተሰቅሎ ይሙት ብሎ ፈረደበት ከዚህ በፊት አሕዛብ ሊጣሉት ሲነሱ ወደ ጌታ ሲያመለክት እሳት ከሰማይ ወርዳ ታጠፋለት ነበር አሁንም እሳት ከሰማይ ወርዳ ትብላቸው ብሎ ወደ ጌታ ቢያመለክት ጌታ በመስቀል ተሰቅሎ ታየው ዳግመኛ በሮም ሰቀሉህን? አለ አንተ ብትፈራ እንጂ ነዋ አለው፡፡ ፈቃድህስ ከሆነ ብሎ እንደ ጌታዬ አቁማችሁ ሳይሆን ቁልቁል ዘቅዝቃችሁ ስቀሉኝ አላቸው በራሱ ዘቅዝቀው ሰቅለውታል፡፡ ዕረፍቱ በዚህች ሐምሌ 5 ቀን ይታሰባል፡፡ ሥጋውንም ደቀመዝሙሩ መርቄሎስ ከመስቀሉ አውርዶ በወተት በወይን አጥቦ ሽቶ ቀብቶ በነጭ ሐር ገንዞ እንዳይፈርስ በማር በተመላ ሣጥን አድርጎ ቀብሮታል፡፡ #ቅዱስ_ጳውሎስ ጳውሎስ ማለት ንዋይ ኅሩይ (የተመረጠ ዕቃ) ማለት ነው፡፡ ሐዋ.9፥15 አንድም ብርሃን ማለት ነው፡፡ አንድም መድቅሕ ማለት ነው፡፡ ደንጊያ በመዶሻ ተጠርቦ ለሕንፃ ሥራ እንዲውል አሕዛብም በእርሱ ትምህርት ታንፀው ለገቢረ ጽድቅ ይበቃሉና የመጀመሪያ ስሙ ሳውል ነው፤ ሳውልም ማለት ጸጋ እግዚአብሔር ማለት ነው፡፡ ትውልዱ ከነገደ ብንያም ማለት ነው፡፡ ፊል. 3፥5 አባቱ ዮስአል ይባላል፡፡ የተወለደው ጌታ በተወለደ በ5 ዓመት በጠርሴስ ነው፡፡ ከ15 ዓመቱ ጀምሮ ኢየሩሳሌም ከመምህር ገማልያል ሕገ ኦሪትን መጻሕፍተ ነቢያትን ሲማር አድጓል፡፡ ሐዋ. 22፥3 ለሕገ ኦሪት ቀናዒ ከመሆኑ የተነሣ ክርስቶስን ዕሩቅ ብእሲ ወንጌልን ዲቃላ ሕግ እያለ ሐዋርያትን ይቃወም ምእመናንን ያሳድድ ነበር፡፡ በወንጌል ያመነው ጌታ በዐረገ በ8ኛ ዓመት ነው፡፡ ምዕመናንን ለማሳደድ ከሊቀ ካህናት የሹመት ደብዳቤ ተቀብሎ ወደ ደማስቆ ሲሄድ መብረቅ ጣለበት፤ ደንግጦ ወደቀ ወዲያውም ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ የሚል ድምጽ ሰማ፡፡ አንተ ማነህ አለ ምእመናንን ከዋሉበት አላሳድር ካደሩበት አላውል የምትልብኝ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ፣ ሰይፍ ቢረግጡት የረገጠው ሰው እንጂ ሰይፉ ይጎዳልን፣ አንተስ እኔን ብትክድ ምእመናንን ብታሳድድ አንተ እንጂ እኔ እጎዳለሁን አለው፡፡ አሁን ምን ላድርግ አለው ተነሥተህ ወደ ከተማ ግባ የምታደርገውን ይነግሩሃል አለው፡፡ ከእርሱ ጋር የነበሩም ድምጹን ይሰማሉ መልኩን ግን አላዩም፤ ከወደቀበት ተነሥቶ ዓይኑ ጠፍቷልና ሰዎች እየመሩት ቤተ ይሁዳ አደረሱት እኅል ውኃ ሳይቀምስ 3 ቀን ውሎ አድሯል፡፡ ሐናንያ በደማስቆ ይኖር ነበርና ጌታ በራዕይ ታይቶት ጳውሎስን አጠመቀው፡፡ ሐዋ. 9፥1-19 በ69 ዓ.ም ሮም ገብቶ ሲያስተምር ንጉሡ ኔሮን ቄሣር አሥሮት ነበርና አካይያ ዘምቶ ጠላት ድል ነሥቶ ሲመለስ ጥሩት አለ፤ መስቀሉን በእጁ ይዞ ቀረበ፤ ተቆጥቶ በሰይፍ ቅጡት አለ፤ እንደ በግ እየነዱ ሲወስዱት የንጉሡ ልጅ አገኘቻቸው፤ አምና ነበርና መጎናጸፊያሽን ስጪኝ አላት ሰጠችው በዚያ ሸፋፍነው ሰይፈውታል፡፡ ደሙም ሰማየ ሰማያት ወጥቶ ቀተሉኒ በዓመጻ እያለ ተካሷቸዋል፡፡ እሱን ገድለው ሲመለሱ የንጉሥ ልጅ አገኘቻቸው ጳውሎስስ? አለቻቸው፡፡ በልብስሽ ሸፋፍነን በሰይፍ ገደልነው አሏት፡፡ ልብሴን መልሶልኝ ከጴጥሮስ ጋር አሁን በዚህ ሲያልፍ እያየሁት ገደልነው ትሉኛላችሁን አለቻቸው ልብሷን አይተው አምነዋል፡፡ ተቆርጦ የወደቀ ራሱንም ከአንገቱ ቢያጋጥሙት እንደ ቀድሞው ሆኖላቸው ቀብረውታል፡፡ ዕረፍቱ በዚች ሐምሌ 5 ይታሰባል፡፡ የቅዱሳን አባቶች ጸሎታቸው በረከታቸው በሁላችን ላይ ይደር፡፡ (ገድለ ሐዋርያት፣ ዜና ሐዋርያት፣ ስንክሳር ዘወርኀ ሐምሌ)

"እጅግ ምርጡ ጸሎት 'ጌታ ሆይ አንተ ሁሉን ታውቃለህ የፈቀድከውን አድርግልኝ።' ማለት ነው።" (ባሕታዊ ቴዎፋን)

በውጊያ ላይ የቆሰለ ወታደር ቁስሉ ይድንለት ዘንድ ለሐኪም ማሳየትን አያፍርም፡፡ ንጉሡም ቢሆን ከቁስሉ የዳነን ወታደር ወደ ሰራዊቱ መልሶ ይቆጥረዋል እንጂ አይተወውም፡፡ እንደዚሁ ሁሉ ጠላታችን ሰይጣን ያገኘው፣ በኃጢአት የጣለው ሰውም ኃጢአቱን በመናዘዝ የንስሐን መድኃኒት ተቀብሎ መዳንን ማፈር የለበትም፡፡ ቆስሎ ቁስሉን መናገር ያፈረና በቶሎ መድኃኒት ያልተደረገለት ወታደር ቁስሉ ወደ ካንሰር ይለወጥና አመርቅዞ መላ ሰውነቱን በመምታት ይጎዳዋል፡፡ ጉዳቱን ቶሎ የተናገረ ታማሚ ግን ታክሞ በመዳን ወደ ጦር ሜዳው ይመለሳል፡፡ ቁስሉን ባለመታከሙ ወደ ካንሰር የተለወጠበትና ያመረቀዘበት ሰው ግን ሊድን አይችልምና ወደ ጦር ሜዳው ሊመለስ አይችልም፡፡ እንደዚሁ ሁሉ በተጋድሎ ውስጥ ያለ ሰው እንደ ወታደር ነው። በተጋድሎ ውስጥ ያለ ሰው በኃጢአት ወድቆ "በኃጢአት ወድቄአለሁ" ብሎ የተናዘዘ የንስሓን መድኃኒት ያገኛል፡፡ ኃጢአቱን የደበቀ ግን ሊድን አይችልም፡፡ ምክንያቱም ታማሚው መድኃኒት አግኝቶ ከቍስሉ ሁሉ ይድን ዘንድ በሽታውን ሁለት ዲናር ወስዶ ለሚያክመው ባለ መድኃኒት አልተናገረምና።" (ቅዱስ አፍርሐት ዘሶርያ - በእንተ ንስሐ ገጽ 52)

"ትህትና" ✞ ትህትና መድኅን ነው ከሰይጣን አሽክላ ያድንሃል። / አባ እንጦንስ/ ✞ ትህትና የሰው ዘመድ ነው። / አባ አሞን / ✞ ትህትና የማይናድ ደልዳላ መሬት ነው። /አባ አርሳንዮስ / ✞ ትህትና ክርስቲያናዊ ምልክት ነው። /አባ መቃርስ/ ✞ ትህትና የሰው ሁሉ ጋሻ ጦር ነው። /አባ በሐይ/ ✞ ትህትና ግድግዳን የምታስጌጥ የአፈር ወይዘሮ ናት። /አባ አጋቶን/ ✞ ትህትና የመንግስተ ሰማያት መመላለሻ በር ነው። /አባ ሚልኪ/ ✞ ትህትና ሕፀጽን የሚያስታውቅ መስታወት ነው። /አባ ጰርዬ / ✞ ትህትና የነፍሳት ወደብ ነው። /አባ ዮሐንስ/ ✞ ትህትና የወንጌል ትእዘዝ መጀመሪያ ነው። /አባ ዮሐንስ ሐፂር/ ✞ ትህትና ወደ ንፁሐ ልቡና ሰገነት የሚወጡበት ነው ✞ ትህትና ዕፀ ሕይወት ናት።/አባ መቃርስ / @Ewnetgen

#መጥምቁ_ቅዱስ_ዮሐንስ (#ሰኔ_30) ሰኔ ሠላሳ በዚች ዕለት ነቢይ ሰማዕትና ሐዋርያ የሆነ መጥምቁ ዮሐንስ ተወለደ። ይህም በእናቱ ማኅፀን ውስጥ ሳለ ለእግዚአብሔር ልጅ የሰገደው ነው። ይህም በመድኅን ክርስቶስ ራስ ላይ እጁን ጭኖ በውኃ ያጠምቀው ዘንድ የተገባው ነው። በቅዱስ ወንጌል እንደ ተነገረ ወንድ ልጅን ትወልድ ዘንድ የኤልሳቤጥ የፅንሷ ወራት በተፈጸመ ጊዜ ወንድ ልጅን ወለደች። ዘመዶቿና ጐረቤቶቿ እግዚአብሔር ቸርነቱን እንዳበዛላት በሰሙ ጊዜ ስለርስዋ ደስ አላቸው። በስምንተኛውም ቀን ሊገዝሩት መጡ በአባቱ ስም ዘካርያስ ብለው ጠሩት። እናቱ ግን አይሆንም ዮሐንስ ይባል አለች። ከዘመዶችሽ ስሙ እንዲህ የሚባል የለም አሏት። አባቱንም ጠቅሰው ማን ሊባል ትወዳለህ አሉት። እርሱም ብራና ለምኖ ስሙ ዮሐንስ ይባል ብሎ ጻፈ። ሁሉም አደነቁ። ያን ጊዜም አንደበቱ ከድዳነት ተፈትቶለት ተናገረ እግዚአብሔርንም ፈጽሞ አመሰገነው። ስለ ልጁና ስለ መድኃኒታችን መምጣት ልጁ ዮሐንስም የልዑል ነቢይ እንደሚባልና በእግዚአብሔርም ፊት እንደሚሔድ ትንቢት ተናገረ። ሰብአ ሰገልም መጥተው ከሔዱ በኋላ ሄሮድስ ሕፃናትን በገደላቸው ጊዜ ስለ ሕፃኑ ዮሐንስ ለሄሮድስ ነገሩት እንዲገድሉትም ጭፍሮችን ላከ ጭፍሮችም ወደ አባቱ ዘካርያስ መጡ ሕፃኑንም ከእርሱ ፈለጉት አባቱም አንሥቶ በትከሻዎቹ ተሸክሞ ወደ ቤተ መቅደስ ከእርሱ ጋራ እንዲሔዱና ሕፃኑን ከዚያ እንዲወስዱት ወታደሮችን ለመናቸው። ከዚህም በኋላ ሕፃኑን በመሠዊያው ጠርዝ ላይ አኖረውና ከዚህ ራሳችሁ ተቀብላችሁ ውሰዱት አላቸው ወዲያውኑ የእግዚአብሔር መልአክ ነጥቆ ወደ በረሀ ወሰደው። ጭፍሮችም ባላገኙት ጊዜ አባቱ ዘካርያስን ገደሉት። ሕፃኑ ግን አድጎ ለእስራኤል እስከተገለጠበት ጊዜ ድረስ በበረሀ ውስጥ ኖረ። የእግዚአብሔርን መንገድ ጥረጉ ጥርጊያውንም አስተካክሉ እያለ በምድረ በዳ የሚጮህ የዐዋጅ ነጋሪ ድምፅ እነሆ ብሎ ኢሳይያስ የተናገረለት ይህ ነው። ሚልክያስም ስለሱ እንዲህ አለ። በፊትህ ጐዳናዬን አስተካክሎ የሚጠርግ መልእክተኛዬን እኔ እሰዳለሁ። ራሱ መድኃኒታችንም ስለርሱ ሲናገር ሴቶች ከወለዱአቸው መጥምቁ ዮሐንስን የሚበልጠው የለም ብሏል። ይህ የእግዚአብሔርን ልጅ በአጠመቀውና የማትዳሠሥ ራሱን በዳሠሠው ጊዜ የምወደው ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት የሚል የአብን ቃል ሰምቷልና። ዳግመኛም ክብር ይግባውና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ራስ ላይ መንፈስ ቅዱስ ወርዶ ሲቀመጥ አየ። እኛም መድኃኒታችን እንዲምረንና ይቅር እንዲለን በአማላጅነቱ እያመን መታሰቢያውን እናድርግ፡፡ በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘለዓለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_ሰኔ )

በሕይወት ውስጥ መጀመሪያ ከፊት የሚመጡት ሰዎች "ሔዋንህ" ወይም "አዳምሽ" ላይሆኑ ይችላሉ። ልክ አዳም ከተፈጠረ በኋላ መጀመሪያ በእርሱ ፊት እንስሳትን እንዳገኘ እና ለእነርሱም የሚገባቸውን ስም እየሰጠ እንዳሰናበታቸው፣ አንተም አንዳንዴ በኑሮህ ቀድመህ የምታገኛቸው አካላት "ጎረቤት፣ የሥራ ባልደረባ፣ ጓደኛ" እያልክ ስም የምታወጣላቸው ብቻ ይሆናሉ። ለምን? "እንደ አንተ ያሉ (የሚመቹ) ረዳቶች" አይደሉማ። አዳም ለእንስሳት፣ ለሰማይ ወፎችና ለምድር አራዊት ሁሉ ስም ካወጣላቸው በኋላ መጽሐፉ "ለአዳም እንደ እርሱ ያለ ረዳት አልተገኘለትም ነበር" ይላል።(ዘፍ 2፥20) አዳም እንደ እርሱ ያለ ረዳት ከእንስሳቱ መካከል ፈልጎ በማጣቱ "በቃ የምን መኩራት ነው? ያሉት እነዚህ ስለሆኑ እኔን ባትመስል እንኳ ትንሽ ለእኔ የቀረበችውን ብመርጥ ይሻላል" አላለም።  ከሌሎች ይልቅ በአካላዊ ቁመና ለእርሱ የምትቀርበውን ትልቅ ጦጣ (Chimpanzee) መርጦም ወደ ፈጣሪው በመውሰድ "እባክህ ጌታዬ፣ ለአንተ የሚሳንህ የለምና ትንሽ ጸጉሯን ብትቀንስ፣ ጅሯቷን ብታጠፋ እና ፊቷ አካባቢ ማስተካከያ ብታደርግላት እንደ እኔ ያለ ረዳት ትሆናለች" ብሎ ሲማጸን አናገኝም። ይህን ቢያደርግ ኖሮ አሁን የአዳምን ታሪክ የምናነብ ሰዎች ሁሉ በችኮላው እየተገረምን እንስቅበት ነበር። ምክንያቱም እግዚአብሔር ከጥቂት ቀን በኋላ አጥንቷ ከአጥንቱ፣ ሥጋዋ ከሥጋው የተፈጠረ ሔዋን የተባለች እጅግ ውብ ሚስት እንደሰጠው ስለምናውቅ።  ከአንተ ጋር በሃይማኖት፣ በአመለካከትና ይህን በመሳሰሉት ነገሮች ጨርሳ ልትገጥም የማትችል የማትመችህን ረዳት "ለአንተ ምን ይሳንሃል? አስተካክልልኝ" እያልክ ለምን ትታገላለህ። በፍጹም ስለማይሆንሽ ሰው ለምን የmodification ጥያቄ ታቀርቢያለሽ? ጥቂት ጊዜ ከታገስህ እግዚአብሔር ለአንተ የምትመችህን (compatible) ረዳት ያመጣልሃል። አሁን ግን ፊት ለፊት ያገኘሃት ጥሩ የሥራ ባልደረባ ወይም ጓደኛ እንጂ የምትመች ረዳትህ አይደለችም። በሕይወት ውስጥ ቀድሞ የመጣ ሁሉ ባል ወይም ሚስት አይሆንም። መጽሐፍ ቅዱስም "ቢቻላችሁስ... ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ" ይላል እንጂ "ከሁሉ ጋር ተጋቡ" አላለንም።(ሮሜ 12፥18) ዲያቆን አቤል ካሳሁን

🔮 ምክረ ቃል 🔮 🔅 አንድ አባት ልጆቹን ሲመክር እንዲህ አለ። "ክፉ ሀሳብና ስለ ጊዜያዊ ስኬቶች ወይም ኃላፊነቶች አብዝቶ የሚጨነቅ ሰው በነፍሱ ለስንፍና ይዳረጋል። ለነፍሱ የሚጠቅመውን ለማድረግ ቸልተኛ ይሆናል። ሥርዓተ አምልኮን በመከታተል ጠንካራ የሆኑ አማኞች ላይም ወደ ክርስቶስ ፍቅር ለመድረስ ወሳኝ በሆኑ የሕይወት ልምምዶች ላይ ሰንፈው ልታዩዋቸው ትችላላችሁ። ስንፍና በእግዚአብሔር ዘንድ እጅግ የተጠላ ነው፤ ኃጢአትም ነው። ከዚያም በላይ "ከዚህ በላይ ከእኔ ምን ይፈለጋል?" የሚል ትዕቢትም ነው:: ልጆቼ ከሰነፍ ኃጢአተኛ ይሻላል። ኃጢአተኛ የንስሐ ተስፋ አለው፡፡ ለሰነፍ ተሰፋው ምንድር ነው ?" ✨💧✨💧✨💧✨💧✨ ✍ አቡነ አትናስዮስ እስክንድር

ይቅር ስትል በትክክል መኖር ትጀምራለህ ይቅር ማለት የደካማዎች አይደለም። የበደሉህን ይቅር ማለት የመንፈስ ጥንካሬ እና በራስ የመተማመን ምልክት ነው። ይቅር ስትል ታድጋለህ። ይቅር ስትል ልብህ ይሽራል። ይቅር ስትል ቀጥ ብለህ ትቆማለህ። ይቅር ስትል አይኖችህ ንፁህ ይሆናሉ ከዚያም ፊት ለፊትህ ያለውን መንገድ በግልፅ ታየዋለህ። ብስጩነት የመንፈስ ህመም ነው። ይቅር ስትል በትክክል መኖር ትጀምራለህ! እግዚአብሔር ይቅርታ የሚጠይቅ አንደበትን ይቅር የሚል ልብን ያድለን።

#ዝምታ አንዳንድ ጊዜ ዝምታ ከቃላት ይልቅ ውጤታማ፣ ይበልጥ ተገቢና እጅግ ጠቃሚም ነው። ወይም ደግሞ ቢያንስ - ቢያንስ ተናግሮ ከሚመጣ ጉዳት ይልቅ ሳይናገሩ የሚመጣ ጉዳት ይሻላል። በዝምታ ውስጥ ጥበብና ጥንካሬ ከመኖራቸው በተጨማሪ ክብርና ሞገስም አሉ፡፡ አንዳንድ ጊዜ እግዚአብሔር ይናገር ዘንድ እኛ ዝም እንላለን፣እኛ ልንናገር ከምንወደው ከማንኛውም ነገር የበለጠ የእግዚአብሔር ቃል እጅግ ኃያል ነውና። መጽሐፍ ቅዱስ ይህን አስመልክቶ የተናገረው ቃል ምንኛ ድንቅ ነው! «እግዚአብሔር ስለ እናንተ ይዋጋል፤እናንተም ዝም ትላላችሁ. . » ዘጸ 14፥14። መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጲላጦስ ፊት በዝምታ ቆይቷል። በዚያን ጊዜ እርሱ  አፉን አልከፈተም ራሱንም አልተከላከለም። ጌታ ዝምታን በመረጠ ጊዜ ጲላጦስ «ይህን ጻድቅ ሰው የምወነጅልበት ምንም ዓይነት ምክንያት አላገኘሁም» በማለት ተናግሮ ነበር፡፡ ዝምታ ትርፍ አስገኚ ይሁን እንጂ የተወሰነ መመሪያ አይደለም፡፡ ወርቃማው መመሪያ፡- ሰው ሊናገር የሚገባው በትክክለኛው ጊዜ መሆኑና ዝም ማለት የሚገባውም ዝም ማለት በሚገባው ትክክለኛ ጊዜ መሆኑ ነው። ሰው ዝም ሲል ልቡ ከእግዚአብሔር ጋር እንዲነጋገር ስለሚፈቅድ በእርሱ ፈንታ ጌታው እንዲናገር ይጠይቃል ማለት ነው፡፡ (አቡነ ሽኖዳ ሣልሳዊ - የሕይወት ልምድ ገጽ 14 - በአያሌው ዘኢየሱስ የተተረጎመ)

ይቅር ስትል በትክክል መኖር ትጀምራለህ ይቅር ማለት የደካማዎች አይደለም። የበደሉህን ይቅር ማለት የመንፈስ ጥንካሬ እና በራስ የመተማመን ምልክት ነው። ይቅር ስትል ታድጋለህ። ይቅር ስትል ልብህ ይሽራል። ይቅር ስትል ቀጥ ብለህ ትቆማለህ። ይቅር ስትል አይኖችህ ንፁህ ይሆናሉ ከዚያም ፊት ለፊትህ ያለውን መንገድ በግልፅ ታየዋለህ። ብስጩነት የመንፈስ ህመም ነው። ይቅር ስትል በትክክል መኖር ትጀምራለህ! እግዚአብሔር ይቅርታ የሚጠይቅ አንደበትን ይቅር የሚል ልብን ያድለን።