en
Feedback
"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

Open in Telegram

@Dan12bot ለአስተያየትዎ ይህን ይጠቀሙ እናመሠግናለን

Show more
1 134
Subscribers
No data24 hours
-27 days
-2330 days
Posts Archive
+ የሚሸሹት ግብዣ + በሀገራችን ‘ወንድም ጋሻ ነው፥ ወንድም መከታ ነው’ ይባላል። ይህንን የማለት እድል ግን ለጻድቁ ዮሴፍ አልደረሰውም። እንዲያውም ወንድሞቹ በቅናት ተነሳስተው ሊገድሉት ዕቅድ አውጥተው ጨርሰው ነበር። ሆኖም ግን ሮቤል የተሰኘው ወንድሙ ‘ደም አታፍስሱ’ ብሎ መክሯቸው ከሞት አተረፈው። ከዚያም ታናሽ ወንድማቸውን አሳልፈው ለእስማኤላዊያን ነጋዴዎች ሸጡት፤ ጻድቁ ብላቴናም ከሞቀው የአባቱ ቤት ወጥቶ ሳያስበው ለባርነት ተሸጠ። ከዮሴፍ ጋር ግን እግዚአብሔር አብሮት ነበረና፤ በባርነት ሲሸጥም መልካም ሰው እጅ ላይ ወደቀ፤ ከነጋዴዎቹ ላይ የገዛው የግብጹ ባለሥልጣን ጲጥፋራ ነበረና። ዮሴፍን ከነጋዴዎቹ ላይ ሲገዛ የደረሰውን በረከት ጲጥፋራ ያወቀው ቀስ በቀስ ነበር። ዮሴፍ በጲጥፋራ ቤት የገባ ዕለት ከዮሴፍ ጋር አብሮ እግዚአብሔር ገባ። ዮሴፍ የሚሠራው ሁሉ መልካም እንደሚሆንለት የተመለከተው ጲጥፋራም የልቡን ሰው ስላገኘ “በቤቱ ላይ ሾመው፥ ያለውንም ሀብት ሁሉ በኃላፊነት ሰጠው” (ዘፍ 39፡4)። ይህ ከሆነ በኋላ ለዮሴፍ መልካም ለሆነለት ጲጥፋራ ደግሞ እግዚአብሔር መልካም ሆነለት፤ “በጲጥፋራ ቤትና ባለው ሀብት ሁሉ ላይ ከተሾመበት ጊዜ ጀምሮ እግዚአብሔር የግብጻዊውን ቤት ባረከ፥ የእግዚአብሔርም በረከት በግቢም በውጭም ባለው የጲጥፋራ ሀብት ንብረት ሁሉ ላይ ሆነ።” (ዘፍ 39፡5)። ዮሴፍ የሠራው ሁሉ ሲባረክለት፥ በሹመት ላይም ሹመት ሲሰጠው፥ የጲጥፋራ ሚስት ሁኔታውን ሁሉ ትከታተል ነበር። በተጨማሪ ደግሞ ዮሴፍ ታታሪ ከመሆኑ እና ሹመት ከማግኘቱ ባሻገር ‘ጥሩ ቁመና ያለውና መልከ መልካም’ (ዘፍ 39፡6) ነበረ። በዚህ ሁሉ ምክንያት እያደር የጲጥፋራ ሚስት ዓይኗን ጣለችበት። በዚህም አላበቃችም። አፍ አውጥታ ‘አብረኸኝ ተኛ’ አለችው። ጥበበኛው ሰለሞን ‘ስሜቱን የሚገዛ ከተማን በጉልበቱ ከሚይዝ ይበልጣል’ (ምሳ 16፡32) የሚለው በእርግጥም በዮሴፍ ይታያል። በጥንት ጊዜ የግብጽ ነገሥታት እና ባለሥልጣኖች እጅግ ውብ የተባሉ ሴቶችን ያገቡ አንደነበር የታሪክ ድርሳናት ያስረዱናል። መጽሐፍ ቅዱስ የዮሴፍን መልከ መልካምነት ብቻ ቢነግረንም፥ የባለሥልጣኑ ጲጥፋራ ሚስትም ውብ እንደነበረች መናገር ይቻላል። እንግዲህ ዮሴፍ በጲጥፋራ ቤት አገልጋይ ነው። በዚያ ላይ ወጣት ነው። የዝሙቱ ግብዣ የመጣው ደግሞ ከእርሱ ሳይሆን በቀጥታ ከጲጥፋራ ሚስት ነው። የእርሷን የዝሙት ግብዣ ተቀብሎ “እኔ ምን ማድረግ እችላለሁ? እርሷ ናት ተኛ ያለችኝ…” ወይም “የአለቃዬ ሚስት ስለሆነች ስትጣራ አቤት፥ ስትልከኝ ወዴት ብቻ ነው ማለት ያለብኝ።” የሚል አይነት የማይረባ ምክንያት መስጠት ይችል ነበር። እርሱ ግን ይህንን አላደረገም። ድንበሩን አስምሮ ለኃጢአት ግብዣዋ ‘አይሆንም’ የሚል መልስን ሰጣት። የዮሴፍ እርምጃ የጲጥፋራን ሚስት የዝሙት ግብዣ እምቢ በማለት ብቻ አላቆመም። ከከንቱ ምኞት እንድትላቀቅ በማለት ለፈተኟ ሴት ምክርን ጭምር አቀረበ። ይህ በሐዲስ ኪዳን ‘አንዳንዶችን ከእሳት ነጥቃችሁ አድኗቸው’ (ይሁ 1፡23) የተባለውን የሚያስታውሰን ነው። በእርሷ ላይ ከተቀጣጠለባት የዝሙት እሳት ሊያድናት “ጌታዬ ያለውን ሁሉ በኃላፊነት ስለ ሰጠኝ፥ በቤቱ ውስጥ ስላለው ሁሉ ምንም የሚያውቀው ነገር የለም። በዚህ ቤት ላይ ከእኔ የበለጠ ኃላፊነት ያለው ማንም የለም፤ እርሱ ያልሰጠኝ ነገር ቢኖር፥ አንቺን ብቻ ነው፤ ያውም ሚስቱ ስለሆንሽ ነው፤ ታዲያ እኔ ይህን ክፉ ድርጊት ፈጽሜ እንዴት በእግዚአብሔር ፊት ኃጢአትን እሠራለሁ?” (ዘፍ 39፡8-10) ብሎ መክሯት ነበር። እርሷ የፈለገችውን መፈጸም የአለቃውን እምነት መክዳት ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔርንም ማሳዘን መሆኑን ነገራት። ይህንን ኃጢአት መፈጸም እግዚአብሔርንም ሰውንም በአንዴ ማስቀየም እንደሆነ ሊያሳያት ሞከረ። እርሷ ግን ለምክር የምትመለስ ልትሆን አልቻለችም። የመካከለኛው ዘመን የአይሁድ ሊቃውንት በኦሪት ትርጓሜዎቻቸው ላይ እንደጻፉት ከሆነ የጲጥፋራ ሚስት ለአንድ ዓመት ያህል በየቀኑ ይህንን የኃጢአት ግብዣ ለዮሴፍ እያቀረበች ቆይታለች። ፈተናው እየበረታበት ሲሄድ ዮሴፍ ከእርሷ መራቅን መረጠ፤ መጽሐፍ ቅዱስም “ከእርሷ ጋር መተኛቱ ይቅርና አብሯትም መሆን አልፈቀደም” (ዘፍ 39፡10) የሚለን ለዚህ ነው። አንዳንድ ጊዜ ከሰው በኩል የሚገጥመን ፈተና ሲኖር እና ማስተካከሉ ከባድ ሲሆንብን ከዚያ ሰው መራቅን እንደ አንድ አማራጭ ልንጠቀመው እንችላለን። ይህ ግን ለዮሴፍ የሚሆን አልነበረም። ሁለቱም የሚኖሩት በአንድ ቦታ  ነውና፥ የጲጥፋራ ሚስት ሸሽቶ የሚሸሻት ልትሆን አልቻለችም። አንድ ቀን ዮሴፍ እንደተለመደው ሥራውን ለመሥራት ወደ ቤት ሲገባ ለብዙ ጊዜ ስትለማመጠው የነበረችው የጲጥፋራ ሚስት ልብሱን ጨምድዳ ያዘችው። ዮሴፍ እንደ ከዚህ ቀደሙ ሊመክራትም ስንኳ አልቆመም። ልብሱን ስትይዘውም ልብሱን ለማስለቀቅ አልታገላትም። ልብሱን በእጇ ላይ ጥሎ ሸሸ! መሸሽ የፍርሃት ምልክት በሆነበት ዓለም ላይ፥ የዮሴፍ መሸሽ ግን ሁሌም ሲወደስ ይኖራል። ወንድሜ፥ በሕይወትህ ውስጥ እንደ ጲጥፋራ ሚስት ለኃጢአት የሚጋብዙህ ሰዎች የሉም? አንቺስ እህቴ፥ ዘወትር በኃጢአት ግብዣቸው ወደ ውድቀትሽ ሊስቡሽ የሚፈልጉ ሰዎች የሉም? መዝሙረኛው ቅዱስ ዳዊት “በክፉዎች መንገድ የማይሄድ፥ በኃጢአተኞችም መንገድ የማይቆም፥ በፌዘኞችም ወንበር የማይቀመጥ ብፁዕ ነው” (መዝ 1፡1) የሚለውን ማስታወስ ይበጃል። ወንድሜ ሆይ፥ የሚፈትንህን መጋፈጥ ላትችል ትችላለህ። አንቺም እህቴ፥ ወደ ኃጢአት የሚስቡሽን እንደ ዮሴፍ መምከር ያቅትሽ ይሆናል። ሁሉም ቢቀር ግን መሸሽ ይቻላል። "ጠሪ አክባሪ ነው" የሚለው አባባል ለኃጢአት ግብዣ አይሠራም። በእግዚአብሔር አዳራሽ ለመገኘት ከፈለግን ወደ ኃጢአት አዳራሻቸው የሚጋብዙንን ሁሉ እንሽሻቸው። 🖋 Fresenbet G.Y Adhanom

እንደ ጥንቱ የሃገራችን ባህል አንድ ወንድና አንዲት ሴት ለመጋባት ሲስማሙ፥ ወንድዬው አስቀድሞ  ጥሎሽ ይሠጣታል፡፡ ጥሎሹ እንደ ሙሽራው ዓቅም ወርቅም፣ ልብስም፣ ወይፈንም ሊኾን ይችላል፡፡ ሙሽሪቱም እጮኛዋ በሰጣት ሥጦታ ኹለንታናዋን ታስውባለች፤ ታጌጣለች፤ ትሸላለማለች፡፡ ምንም ዓይነት እድፍ በሰውነቷ እንዳይኖር ትተጣጠባለች፤ ትጠነቀቃለች፤ ሽቶ ትቀባባለች፡፡ የሠርጓን ዕለትና የሙሽራዋን መምጣት በጕጕት ትጠባበቃለች እንጂ በሊጥ ወይም በጭቃ ተጨማልቃ አትጠብቅም፡፡ የአማናዊው ሙሽራ (የክርስቶስ) መምጣት የሚጠብቁ ልባም ክርስቲያኖችም እጮኛቸው በሰጣቸው ሰማያዊ ሥጦታ ኹለንተናቸውን ያስጌጣሉ፤ በምግባርና በትሩፋት ተውበውና ተሸላልመው ይጠብቃሉ፡፡ የተዳደፈ (የኀጢአት) ልብሳቸውን እያወለቁ አዲሱ (የጸጋ) ልብሳቸውን ይለብሳሉ፤ የከረፋ ሽታን እያራቁ በመለኮታዊ መዓዛ ራሳቸውን ያስውባሉ፡፡ የጸጋ ልብሳቸውን ከሚያሳድፍ ነገር እየተጠበቁ፣ ፈተናውን ኹሉ በክርስቶስ እየተሻገሩ የሙሽራዉን መምጣት ይናፍቃሉ /ማቴ.፳፪፡፲፩/፡፡ ሰነፎቹ ግን ቸል ብለው ወደ እርሻ ወይም ወደ ንግዳቸው ይኼዳሉ /ማቴ.፳፪፡፭/፡፡ የጸጋ ልብሳቸውን እያወለቁ የሞት ልብስን ለመልበስ፣ የኃጢአትንም መጐናጸፍያ ለመደረብ ሰሞኑ በመገናኛ ብዙሃን እንደምንሰማው አንድ ሺሕና ኹለት ሺሕ ብር ከፍለው ወደ ሄሮድያዳ ምሽት ይነጕዳሉ፡፡ በመዝናናት ስም ይዘናጋሉ፡፡ ሙሽራቸውን በሊጥ ቦክተው ይጠብቃሉ፡፡ በሠርጉ ዕለት ደስ ሊላቸው ሲገባ ያዝናሉ፡፡ ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ፡- “እናንተ ደግሞ ታገሡ፤ ልባችሁንም አጽኑ፤ የጌታ መምጣት ቀርቦአልና” በማለት ለሠርጉ ቀን የተዘጋጀን እንኾን ዘንድ ዛሬም ይጠራናል /ያዕ.፭፡፰/፡፡ ይኽን እንድናደርግ ሰውን በመውደዱ ሰው የኾነው ሙሽራው ይርዳን አሜን!!!

መልካሙ አምላካችን እግዚአብሔር የሰዎችን መልካም ሥራ ሁሉ አይዘነጋም ጥቂት ብትሆንም እንኳ። እርሱ በመልካም ምድር ላይ ከወደቀች በኋላ ሠለሳ ስድሳና መቶ እጥፍ ፍሬ ስለምታፈራው መልካም ፍሬ አስተምሯል። አምላካችን እዚህ ላይ ሠላሳ ፍሬ ያፈራችውን ዘር ከመልካም ዘር ነው የቆጠራት። እርሱ ሠርክ አሥራ አንድ ሰዓት ላይ መጥተው የተቀጠሩትን ሠራተኞች ተቀብሏል። (ማቴ 20፥9) ከእርሱ በስተቀኝ የተሰቀለውን ወንበዴ የተቀበለው በሕይወቱ የመጨረሻ ሰዓት ውስጥ ነበር። (ሉቃ 23፥43) እርሱ ታናናሾች ለተባሉት ሰዎች በደቀ መዝሙሩ ስም ቀዝቃዛ ውኃ ወይም ጽዋ ያጠጣ ዋጋውን እንደማያጣ እውነት እላችኋለሁ ብሎ በማሳሰብ ተናግሯል። (ማቴ 10፥42) የእርሱ መልካምነት ሦስት ዓመት ተመላልሶ ምንም ፍሬ ላላገኘባትን በለስ ሊያስቆርጣት ባዘዘ ጊዜ ጠባቂዋ በመካከል በአስታራቂነት ገብቶ "......ጌታ ሆይ ዙሪያዋን እስክኮተኩትላት ፋንድያ ስካፈስላት ድረስ በዚች ዓመት ደግሞ ተዋት ወደ ፊትም ብታፈራ ደኀና ነው ያለዚያ ግን ትቆርጣታለህ። (ሉቃ 13፥8-9) በማለት እንዲናገር ፈቅዶለታል። አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ!

#ነሐሴ_16 #ዕርገተ_ማርያም ነሐሴ ዐሥራ ስድስት በዚህች ቀን አምላክን የወለደች የእመቤታችን ድንግል ማርያም ሥጋዋ ወደ ሰማይ ያረገበት መታሰቢያዋ ሆነ። ከዕረፍቷም በኋላ ከእርሳቸው ስለመለየቷ ሐዋርያት ፈጽሞ እያዘኑ ነበር። ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ተገለጠላቸው እርሷን በሥጋ ያዩ ዘንድ እንዳላቸውም ተስፋ ሰጣቸው። ወንጌላዊ ዮሐንስም እስያ በሚባል አገር እያስተማረ ሳለ በነሐሴ ወር ዐሥራ ስድስተኛ ቀን ተድላ ደስታ ወደአለባት ገነት በመንፈስ ቅዱስ ተነጠቀ። የክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን የእመቤታችን ማርያም ሥጋዋ ካለበት ከዕፀ ሕይወት ሥር ተቀምጦ አየው። የንጽሕት እናቱንም ሥጋ ታወጣ ዘንድ ምድርን እንዲጠሩዋት ሰባቱን የመላእክት አለቆች አዘዛቸው። እነርሱም የንጽሕት እናቱን ሥጋ ታወጪ ዘንድ እግዚአብሔር አዞሻል አሏት። ያን ጊዜም ከዕፀ ሕይወት በታች ካለ መቃብር የእመቤታችን ማርያም ሥጋዋ ወጣ። የክብር ባለቤት ጌታችንም እንዲህ እያለ አረጋጋት የተወደድሽ የወለድሽኝ እናቴ ሆይ ዘላለማዊ ወደ ሆነ መንግሥተ ሰማያት አሳርግሽ ዘንድ ነዪ። ያን ጊዜም በገነት ያሉ ዕፀዋት ሁሉም አዘነበሉ መላእክት የመላእክት አለቆች ጻድቃን ሰማዕታትም እየሰገዱላትና ፈጽሞ እያመሰገኗት አሳረጓት። አባቷ ዳዊትም ንግሥት እመቤታችን ወርቀ ዘቦ ለብሳ ደርባ ደራርባ በቀኝህ ትቀመጣለች እያለ በበገና አመሰገናት። በኪሩቤል ሠረገላ ተቀምጣ ከዐረገች በኋላ በልጁዋና በፈጣሪዋ ቀኝ በታላቅ ክብር ተቀመጠች። ወንጌላዊ ዮሐንስም ከእርሷ በረከትን ተቀብሎ ሰግዶላት ተመልሶ ከሰማይ ወረደ ሐዋርያትን ተሰብስበው ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋ ፈጽሞ ሲያዝኑና ሲተክዙ አገኛቸው። እርሱም እንደ አየ እንደ ሰማ ሥጋዋንም በታላቅ ክብር በምስጋና እንደ አሳረጓት ነገራቸው። ሐዋርያትም በሰሙ ጊዜ ዮሐንስ እንዳየና እንደሰማ ባለማየታቸውና ባለመስማታቸው እጅግ አዘኑ። ከዚህም በኋላ እያዘኑ ሳሉ እነሆ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠላቸውና የፍቅር አንድነት ልጆች ሰላም ይሁንላችሁ ስለ እናቴ ማርያም ሥጋ ለምን ታዝናላችሁ። እነሆ እኔ እርሷን በሥጋ ላሳያችሁ ልባችሁም ደስ ሊለው ይገባዋል አላቸው ይህንንም ብሎ ከእርሳትው ዘንድ ወደ ሰማያት ዐረገ። ሐዋርያትም ዓመት ሙሉ ቆዩ የነሐሴም ወር በባተ ቀን ለሐዋርያት ዮሐንስ እንዲህ አላቸው አምላክን የወለደች የእመቤታችንን ሥጋዋን ለማየት የተዘጋጀን አድርጎ ያሰየን ዘንድ ኑ ይህን ሁለት ሱባዔ በመጾም የክብር ባለቤት ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን እንለምነው በልጅዋ በወዳጅዋ ቀኝ ተቀምጣ አይተን በእርሷ ደስ እንዲለን። በዚያን ጊዜም ዮሐንስ እንዳላቸው በጾም በጸሎት ሱባዔ ያዙ የነሐሴ ወር እንደ ዛሬ ዐሥራ ስድስተኛ ቀን በሆነ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉንም ሐዋርያት ወደ ሰማይ አወጣቸው። በታላቅ ክብር በተወደደ ልጅዋ ቀኝ ተቀምጣ ከሥጋዋ ተዋሕዳ ተነሥታ እመቤታችን ማርያምን አዩዋት። እጆቿንም ዘርግታ የከበሩ ሐዋርያትን እያንዳንዳቸውን ባረከቻቸው በልባቸውም እጅግ ደስ አላቸው። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በከበረ ሥጋውና ደሙ ላይ ሠራዒ ካህን ሆነ። እስጢፋኖስም አዘጋጀ ዮሐንስም በመፍራት ቁሙ አለ። ሁሉም ሐዋርያት በመሠዊያው ዙሪያ ቆሙ በዚያን ጊዜ ከቶ እንደርሱ ሆኖ የማያውቅ ታላቅ ደስታ ሆነ። ጌታችንም የቅዳሴውን ሥርዓት በፈጸመ ጊዜ ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው ። ከዚያም በኪሩቤልና በሱራፌል ሠረገላ ተቀምጣ በምታርግ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ እመቤታችን ማርያምን እንዲህ ብሎ ተናገራት። በዚች ቀን የሆነ የዕርገትሽን መታሰቢያ በዓለም ውስጥ እንዲሰብኩ ልጆችሽ ሐዋርያትን እዘዣቸው። መታሰቢያሽን የሚያደርገውን ሁሉ ተጠብቆም በዚች ቀን ቅዱስ ቁርባንን የሚቀበለውን ኃጢአቱን እደመስስለታለሁ። የእሳትን ሥቃይ ከቶ አያያትም መታሰቢያሽን ለሚያደርግ ሁሉ በዚች ቀን ለድኆች በስምሽ ለሚመጸውት ቸርነቴ ትገናኘዋለች ይህም ሥጋሽ ወደ ሰማይ ያረገበት ነው። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ክብር ይግባውና ጌታችንን እንዲህ አለችው ልጄ ሆይ እነሆ በዐይኖቻቸው አዩ በጆሮቻቸውም ሰሙ በእጆቻቸውም ያዙ ሌሎችም ታላላቅ ደንቆች ሥራዎችን አዩ። እመቤታችንም ይህን ስትናገር ጌታችን ሰላምታ ሰጥቷቸው በታላቅ ደስታ ወደ ደብረ ዘይት ተመለሱ። የተወደዳችሁ ወንድሞች ሆይ በፍጹም ደስታ መታሰቢያዋን እናደርግ ዘንድ ይገባናል እርሷ ስለእኛ ወደ ተወደደ ልጅዋ ሁልጊዜ ትማልዳለችና። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት ይማረን። በረከቷም ከርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ከአባ ማትያስ ከሁሉም ሊቃነ ጳጳሳትና ኤጲስቆጶሳት ጋራ ሐዋርያት ከሰበሰቧት ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች ከሁላችን ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ)

ነሐሴ 12-ቅዱስ ሚካኤል ንጉሥ ቆስጠንጢኖስን ረደቶ በድል ያነገሠበት ዕለት ንግስት ዕሌኒም በ272ዓ.ም ታላቁ ቆስጠንጢኖስን ወለደችለት፤ ቆስጠንጢኖስም ገና በወጣትነቱ የአባቱ እንደራሴ ሆኖ እንዳሠራ አባቱ ሞተ፡፡ የአባቱ ባለሟሎችና ህዝቡ ተስማምተው የ18 ዓመቱን ቆስጠንጢኖስን በአባቱ ቦታ ሐምሌ 25 ቀን 300ዓ.ም በሮም ምዕራብ ክፍል በገላትያ አነገሡት፡፡ በጦር ሜዳዎች ብዙ የጀግንነት ሥራዎች ስለሠራ በሠራዊቱ ዘንድ ይወደድ ነበር፡፡ ንግሥት ዕሌኒ ልጅዋን ቆስጠንጢኖስን ከልጅነቱ ጀምሮ ስለክርስትና ሃይማኖትና ስለክርስቲያኖች መከራ ታስተምረው ስለነበር በክርስቲያኖች ላይ የነበረው አመለካከት በሮም ከነገሡት ቄሣሮች ሁሉ የተሻለ ነበር፡፡ በተለይም በ312 ዓ.ም ከጠላቱ ከመክስምያኖስ ጋር ለመዋጋት "ምታ ነጋሪት ክተት ሠራዊት" ብሎ ለዘመቻ እንደተሰለፈ በራእይ በሰማይ ላይ "በዚህ የመስቀል ምልክት ጠላትህን ድል ታደርጋለህ; የሚል መስቀልና ጽሑፍ ስላየ ለሠራዊቱ ሁሉ የመስቀል ምልክት በመሣሪያቸውና በሰንደቅ ዓላማው ላይ እንዲያደርጉ አዘዘ፡፡ ወደያው ጦርነት ቢገጥም በቲቤር ወንዝ ድልድይ ላይ ጠላቱን ድል ነሥቶ በጠቅላላው የሮም መንግስት ግዛቶች ሁሉ ገዥ ሆነ፡፡ ይኸውም የሆነው በመላእክት አለቃ በቅዱስ ሚካኤል ረዳትነት ነው፡፡ ሚካኤል ማለት መኑ ከመ እግዚአብሔ "እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው?" ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ለፍጥረታት ሁሉ የሚራዳና የሚያዝን የምሕረትና የመዳኛ፤ የሰላም መልአክ ነው፡፡ ‹‹በዚያም ዘመን ስለ ሕዝብህ ልጆች የሚቆመው ታላቁ አለቃ ሚካኤል ይነሣል›› (ዳን.12፥1) በማለት በነቢዩ ዳንኤል የተነገረ ሲሆን በሌላ ቦታ ‹‹ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ›› (ዳን. 10፥13) በማለት ያስረዳል፡፡ በድርሳነ ሩፋኤል ላይ እንደተገለጸው ሰባት ሊቃነ መላእክት ቢኖሩም አለቃቸው ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል አርምሞ ትዕግሥትን የሚወድ መልአክ ነው፡፡ ‹‹የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ከዲያብሎስ ጋር በተከራከረ ጊዜ ስለ ሙሴ ሥጋ ሲነጋገር ጌታ ይገሥጽህ አለው እንጂ የስድብን ፍርድ ሊናገረው አልደፈረም፡፡›› ቅዱስ ሚካኤል ከእግዚአብሔር በተሰጠው ኃይል ዲያብሎስን ድል የነሣ መልአክ ነው፡፡ "በሰማይም ሰልፍ ሆነ፤ ሚካኤልና መላእክቱ ዘንዶውን ተዋጉ። ዘንዶውም ከመላእክቱ ጋር ተዋጋ፥ አልቻላቸውምም፥ ከዚያም ወዲያ በሰማይ ስፍራ አልተገኘላቸውም። ዓለሙንም ሁሉ የሚያስተው፥ ዲያብሎስና ሰይጣን የሚባለው ታላቁ ዘንዶ እርሱም የቀደመው እባብ ተጣለ፤ ወደ ምድር ተጣለ መላእክቱም ከእርሱ ጋር ተጣሉ፡፡" ራእ 12፥7-9፡፡ ታላቁ ቆስጠንጢኖስ በመላእክት አለቃ በቅዱስ ሚካኤል ረዳትነት ጠላቶቹን ሁሉ ድል ነሥቶ በጠቅላላው የሮም መንግሥት ግዛቶች ሁሉ ገዥ ከሆነ በኋላ በ300 ዓመታት ውስጥ ለመጀመርያ ጊዜ ለክርስቲያኖች የነጻነት ዐዋጅ ዐወጀ፡፡ ክርስትናም ብሔራዊ ሃይማኖት ተባለች፡፡ ንግሥት እሌኒም በተፈጠረላት አመች ሁኔታ በመጠቀም የጌታችን መስቀል ከተቀበረበት ለማውጣት በ327ዓ.ም ወደ ኢየሩሳሌም ሔደች፡፡ ዕሌኒ ልጅዋ ቆስጠንጢኖስ ክርስቲያን ከሆነላት ወደ ኢየሩሳሌም ሔዳ መስቀሉን ለመፈለግ እንዲሁም በኢየሩሳሌም ያሉ ቅዱሳት መካናትንና አብያተ ክርስቲያናትን ከማነጽ ለእግዚአብሔር ተሳለች፡፡ ከዚህ በኋላ ቆስጠንጢኖስ አምኖ በ337 ዓ.ም ተጠመቀ፡፡ ቅድስት ዕሌኒ ወደ ኢየሩሳሌም ሔደች ከእርሷም ጋር ብዙ ሠራዊት ነበር፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፡፡ እኛንም በጸሎቱ የምንታመን ሁላችንን የመልአክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤልን ረድኤት በረከቱን ያሳድርብን፡፡ በጸሎቱ ይማረን፡፡ (ምንጭ፡- የነሐሴ ወር ስንክሳር)

#እንኳን_አደረሳቹ_አደረሰን_የተዋህዶ_ልጆች_በሙሉ😘🙏 ✝️🌿👉 #ቡሄ_ጅራፍ_ማስጮህ ✝️🌿👉 #ችቦ_ማብራት ✝️🌿👉 #ሙልሙል_ዳቦ - ሐይማኖታዊ ምስጢራቸው ምንድነው⁉️ #ደብረ_ታቦር ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያዕቆብን ፣ ዮሐንስንና ጴጥሮስን ይዞ ወደ ታቦር ተራራ ከወሰዳቸው በኋላ በዚያ ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበትና ሙሴና ኤልያስን ጠርቶ የህያዋንና የሙታን አምላክነቱን ያሳየበት ከዘጠኙ የጌታ ዓበይት በዓለት ውስጥ አንዱ ነው። ✝️🌿💚💛❤ ቤተክርስቲያናችንም የተለያዩ ስርዓቶችን በመፈፀም አክብራው ታልፋለች፡፡ #በደብረ ታቦር በዓል የሚፈጸሙ ( #ቡሄ ፣ #ጅራፍ ማስጮህ ፣ #ችቦ ማብራትና #ሙልሙል_ዳቦ ) ትውፊታዊ የሃይማኖት ስርዓቶች ምሳሌዎች ምን እንደሆነ እናያለን፡፡ ✝️🌿💚💛❤ #ቡሄ ቡሄ ማለት ብራ ፣ ብርሃን፣ ደማቅ ማለት ነው፡፡ ከስሙ ትርጉም እንደምንረዳው ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት በዓል ስለሆነ ብራ፣  ብርሃን ደማቅ የሚል ፍቺ ያለው ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ አንድም ቡሄ ማለት ወቅቱ የክረምት ጨለማ አልፎ የብርሃን ወቅት ስለሚመጣ ሰማይም ከጭጋጋማነት ወደ ብሩህነት የሚለወጥበት የመሸጋገሪያ ወቀት ስለሆነ ብራ ተብሏል፡፡ ✝️🌿💚💛❤ " ቡሄ ከዋለ የለም ክረም ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት እንዲሉ " አንድም ቡሄ…..ቡኮ "/ሊጥ" ማለት ነው፡፡ በዚህ በዓል ቡኮ ተቦክቶ ዳቦ/ ሙልሙል / ተጋርሮ የሚታደልበት በዓል ስለሆነ ይህ ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ✝️🌿💚💛❤ ✝️🌿👉 #ሙልሙል_ዳቦ ሙልሙል ዳቦ አመጣጡ ጌታችን ብርሃናዊ መለኮቱን በገለጠበት በዚህ ዕለት በደብረታቦር አካባቢ የነበሩ ህፃናት እረኞች ቀኑ የመሸ ስላልመሰላቸው / ጌታችን በብርሃን አካባቢውን ሞልቶት ስለነበረ / በዛው ሆነው ከብትና በጎቻቸውን እየጠበቁ ሲቆዩባቸው የሰዓቱን መግፋት የተመለከቱ ወላጆች በችቦ ብርሃን ተጠቅመው ለልጆቻቸው የሚቀመስ ሙልሙል ዳቦ ይዘው ወዳሉበት መምጣታቸውን ያሳያልና ታሪኩን እየዘከርን በዓሉን እናከብራለን፡፡ ✝️🌿💚💛❤ #አንድም እንደ #ሐዋርያት_የምስራችሲነግሩን ወንጌል ሊሰብኩልን በየደጃፋችን መጥተው " ቢሄ በሉ " የሚሉትን ታዳጊዎችን ይበሉት ዘንድ ይሰጣቸዋል ይህም መጽሐፋዊ ነው ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን በደረሳችቡት ሁሉ ተመገቡ /ማቴ 10፥12/ ብሏልና ህፃናቱም የጌታን በዓል ሊያበስሩ ሲመጡ ዳቦ መስጠት ልማዳዊ ብቻ ሳይሆን ህፃናቱም የደቀመዛሙርት ምሳሌ ናቸው፡፡ ✝️🌿💚💛❤ #መዝሙራቸው ደግሞ የምስራች ወንጌል ይዘው የመምጣታቸው ምሳሌ ነው፡፡ ሐዋሪያት በገቡበት ሀገር ሁሉ አስተምረው አጥምቀው የፀጋ ልጅነትን አሰጥተው እንደሚቆዩ ሁሉ ልጆችም ዘምረው አመስግነው መርቀው ውለዱ ክበዱ የመንግስተ ሰማያት ወራሾች ያድርጋችሁ ብለው አመስገነው ይሄዳሉና በሐዋሪያት ህፃናቱ ይመሰላሉ፡፡ ✝️🌿💚💛❤ ✝️🌿👉 #ችቦ_ማብራት ችቦ የጌታችንን ብርሃነ መለኮት መገለጥን የሚያመለክት ነው፡፡ ጌታችን በደብረ ታቦር መለኮቱን ሲገልጥ ብርሃን አካባቢውን ሞልቶት ነበርና ያንን በዘመናችን ለመግለጥ የበዓሉ ዋዜማ ማታ ችቦ አብርተን አምላካችንን እናመሰግናለን፡፡ አንድም ደግሞ የችቦ ታሪክ ከላይ እንደገለፅነው የእረኞቹ ወላጆች ይዘውት የመጡት ብርሃን ነው፡፡ ✝️🌿👉 #ጅራፍ የጅራፍ ምሳሌነት በደብረ ታቦር በዓል በትውፊታዊ መልኩ የሚታየው ሚስጥር በእየሩሳሌም ስለሚሆነው የጌታችን ሞቱ ምሳሌ ነው፡፡ በዚህ በዓል ጅራፍ መገመዱ እና ማጮሁ ሁለት አይነት ምሳሌ አለው፡፡ ✝️🌿💚💛❤ ✝️🌿 #የመጀመሪያው_ምሳሌ - ጌታችን በዕለተ አርብ የደረሰበትን ግርፋትና ህማም እናስብበታለን፣ ✝️🌿 #ሁለተኛው_ምሳሌ -  ደግሞ ድምፁን ስንሰማ የባህሪ አባቱን የአብን የምስክርነት ቃልና በግርማው ሲገለጥ የተሰማውን ነጎድጓድ ያስታውሰናል፡፡ ✝️🌿💚💛❤ የጅራፍን ትውፊታዊ ውርስ መጽሐፋዊ ትምህርቱንና ምስጢሩን ከትውልድ ጠብቆ ማስተላለፉ ተገቢ ነው፡፡ ✝️🌿💚💛❤ በአጠቃላይ በዓለ ደብረ ታቦር ከነዚህ ሚስጢር ካላቸው ትምህርቶችና ትርጓሜያቱ ከትውልድ ወደ ትውልድ በቅብብል እንደመጣልን እኛም ሃይማኖታዊ ትውፊቱን ሳይለቅ ማስተላለፍ ይጠበቅብናል፡፡ የዚህ ነገር ባለ ድርሻ አካላት ደግሞ ወጣቶችና ወላጆች ናቸው፡፡ አንዳንድ ጊዜ በቡሄ ጨዋታ የሚሰሙ ግጥሞች ስድብ ፊዝና ሳቅ ይታይባቸዋል ተጫዋቾቹም ከሰጡን እንመርቃለን ካልሰጡን እንራገማለን አይነት መልዕክት ያስተላልፋሉ። የሚብሰው አሳባቢ ነገሩ ደግሞ ኃይማኖታዊ ስርዓቱን ወደ ገንዘብ ማግኛ መቀየሩ ነው፡፡ ✝️🌿💚💛❤ ስለሆነም ይህን ነገር በተለይ የነገ የሀገር ተረካቢና የቤተክርስቲያን ተተኪ የሆንን ወጣቶች ማስተካከል ይኖርብል፡፡ ወላጆችም ሕፃናት በየደጃፋችን ላይ በዓሉን ሊያበስሩ ሲመጡ አስደንግጦ ከማባረር በሚገባው መልኩ አስተምረን መርቀን ማስተናገድ ይጠበቅብናል ባህሉም እንዳይተው የበኩላችንን አደረግን ማለት ነው። ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን

🔮 ምክረ ቃል 🔮 🔅 የወጣትነት ውበት በዕድሜ ብዛት ይከስማል፡፡ እውነተኛው ውበት ግን አይከስምም ፣ አይሞትምም፡፡ የማይደበዝዝ ፣ የማይለወጥና በሞት የማይጠፋ ነው፡፡ ይህ እውነተኛ ውበት የሚገኘው በእግዚአብሔር አርአያ እና አምሳል በተፈጠረችው የማትሞት ነፍስ ውስጥ ብቻ ነው። ሌላ ውበት ይደበዝዛል ፤ ደም ግባትም ሁሉ ያልፋል፡፡ ነፍስ ስለ ውስጣዊ ውበቷ መጨነቅ ስትጀምር በዙሪያዋ ባለ ፍጡራን ላይ ያለውን ውበት ትንቃለች፡፡ በዙሪያህ ያሉትን ፍጥረታትና አስደናቂ ነገሮች ሁሉ ልታይ ትችላለህ ፤ ከአንተ ነፍስ በስተቀር በእግዚአብሓር አርአያና አምሳል የተፈጠረ አንድም የለም፡፡ 🔅 የተወደድኸው ሆይ እግዚአብሔር ለአንተ ከኅሊና በላይ የሆነውን የመጨረሻውን ውበት አጎናጽፎሃል!! እውነተኛውን ውበት የምትፈልግ ከሆነ ራስህን በበጎነትና በክርስቲያናዊ አኗኗር አስጊጠው፡፡ ክፉ ነገሮችን በማየትና በመጥፎ ጠባይ አትቆሽሽ፡፡ ምናልባት አንድን ሰው ውብና ማራኪ ሆኖ ታየው ይሆናል፡፡ ነፍሱ ግን በክፋት ውስጥ ሰጥማለች ፣ በውስጡ ግን በኃጢአት እየታወከ ነው ፤ በብዙ ጥፋቶች ጥላሸትም ጠቁሯል፡፡ በአንጻሩ የሚማርክ ገጽታ የሌለው ሰው ልታይ ትችላለህ ፤ ነፍሱ ግን በበጎነት እና በቅድስና አኗኗር የተዋበች ልትሆን ትችላለች፡፡ ስለዚህ እባክህን ሁሌጊዜ ውስጣዊ ማንነትን መርምር እንጂ ውጪያዊ ውበትን አትመልከት፡፡ ✨💧✨💧✨💧✨💧 ✍ ሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ ሀቢብ ጊዮርጊስ

✝ ቻይ እና ትዕግስተኛ የሆነ ሰው ይጸልያል ስለሚሰጠውም የእግዚአብሔር መልስ አይጨነቅም ። እግዚአብሔር ጸሎቱን እንደሚሰማው እርግጠኛ ነው ። ሁሉም ነገር በእግዚአብሔር ጥበብና ፈቃድ እንደሚሆን በተገቢው ጊዜና መንገድ መልስ እንደሚሰጠው በማመን ለእግዚአብሔር ፍቅር ይተዋል ። አንዳንድ ሰዎች ይህ መሰል ትዕግሥት የላቸውም ። እግዚአብሔርን መውቀስ እና ከእርሱ ስሕተት መፈለግ እንጂ መጠባበቅ አይችሉም ። እርሱን ይወነጅሉታል እርሱ  ግን እጅግ ይታገሳቸዋል ወቀሳቸውንም ይሸከማል ። እነዚህ ሰዎች እግዚአብሔር ለእነርሱ እንደሚሰራ ማመን አለባቸው ።

"ጌታ ሆይ ወርቅ ትሰጠኝ ዘንድ አልለምንህም ሀብት ንብረትም አልለምንህም እነርሱ ድኅነትን የሚያስገኙ አይደሉም። ይቅርታህን ማግኘት ግን ከወርቅ ይልቃል። የኃጢከት ሥርየትን ማግኘትም ከብር ይበልጣል።" ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ

እንኳን ለጾመ ፍልሰታ በሰላም በጤና አደረሰን አደረሳችሁ። ጾሙን የበረከት፣ የሰላም እና የይቅርታ ጾም ያድርግልን።
እንኳን ለጾመ ፍልሰታ በሰላም በጤና አደረሰን አደረሳችሁ። ጾሙን የበረከት፣ የሰላም እና የይቅርታ ጾም ያድርግልን።

🔮 ምክረ ቃል 🔮 🔅 በውጭው ካሉት ይልቅ በአንተ ውስጥ የሚገኙት ፍትወታት ጠንካራ ጠላቶችህ ናቸው። ልክ ያልተሠራለት ምኞት ከባቢሎን እሳት ይልቅ ያቃጥላል።  አልጠግብ ባይነትም ከጥፉት ውኃ ይልቅ ያሰጥማል። ያልተገራ ፍላጎት ማንነትን አስጥሎ የሰይጣን ባሪያ ያደርጋል። 🔅 ራስን መግዛት የሰው ልጆች ጌጥ ነው። ዮሴፍ ግብጽን ከፈርዖን ሁለተኛ ሆኖ ከገዛበት ታላቅ ሥልጣን ይልቅ፣ በጌታው ሚስት ፊት ያሳየው ራስን መግዛት ይበልጥ ይደነቃል። 🔅 ራስህን ነጻ ማውጣት ትፈልጋለህ? እንግዲያውስ ከውስጥህ ጀምር። ሁል ጊዜ ካልበላሁ የሚለው ሆድህ ስስት አስለምዶ በወንድምህ ላይ ጨካኝ እንዳያደርግህ ለሰውነትህ ጾም አስተምረው። ✨💧✨💧✨💧✨💧✨    ✍ ዲያቆን አቤል ካሳሁን    🍀⚜🍀⚜🍀⚜🍀⚜🍀 ✨መልካም የፍልሰታ ፃም ይሁንላችሁ 🙏

ጸሎት ለማድረግ አታቅማማ፤ ሥጋ ከምግብ በተከለከለ መጠን ደካማ እንደሚሆን ነፍስም ከጸሎት ስትከለከል ደካማ ትሆናለች፡፡ (አቡነ ማቴዎስ ግብፃዊ) ስለሁሉም ነገር ሳታቋርጥ ጸልይ፤ እንዲህ ካላደረግክ ምንም ነገር ያለ ልዑል እግዚአብሔር ፈቃድ የማታከናውን ትሆናለህ፡፡ ያለጸሎት ራሱን በማንኛውም  ዓለማዊ ጉዳዮች የሚያደክም ሰው በመጨረሻ  ውጤታማ ሊሆን አይችልም፡፡ ሰው ራሱን ኃጢአተኛ እንደሆነ እያሰበ ወደ እግዚአብሔር ካለየ ጸሎቱ ተቀባይነት አይኖረውም ፡፡ (አባ አጋቶን) እግዚአብሔር ለሰው ምሕረትን ሲያድል አንድ ሰው እንዲጸልይለት ያነሣሣዋል፡፡ በዚህ ጸሎት አማካኝነትም ይረዳዋል፡፡ በመከራ ጊዜ ያለማቋረጥ መሓሪውን አምላክ በጸሎት ጥራው፡፡ ባለማቋረጥ የእግዚአብሔርን  ስም መጥራት ለነፍስ ቁስል መድኃኒት ነው፡፡ ሰው በታመመ ጊዜ ዶክተሩ ፍቱን መድኃኒትን ፈልጎ ለበሽተኛው እንደሚሰጠው መድኃኒቱም ወደ ሰውነቱ ገብቶ ሥራ ሲሠራ እንጂ እንዴት እንደሚሰራ እንደማናውቀው በተመሳሳይ ሁኔታ የእግዚአብሔርን ስም አዘውትረን ስንጠራ እንዴት ጸሎታችን እንደሰራ ሳናውቅ የእግዚአብሔርን ፍቅር ምህረትና ርኅራኄ በእኛ ላይ ሲደረግ እንመለከታለን፡፡ (አቡነ ማቴዎስ ግብጻዊ)

ነሐሴ 1 ምንባባት፡ ፩ኛጢሞ. ም.፭ ቊ.—፲፩ ፩ኛ ዮሐ. ም.፭ ቊ. ፩—፮ ግብ.ሐዋ. ም.፭ ቊ.፳፯—፴፬ ምስባክ መሠረታቲሃ ውስተ አድባር ቅዱሳን፤ ያበድሮን እግዚአብሔር ለአናቅጸ ጽዮን፤ እምኩሉ ተዓይኒሁ ለያዕቆብ፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ዮሐንስ ም. ፲፱ ቊ. ፴፰—ፍጻሜ ም. ቅዳሴ፡ ዘዮሐንስ አፈወርቅ አው ዘእግዝእትነ ነሐሴ 2 ምንባባት፡ ፩ኛጢሞ. ም.፪ ቊ.፰—ፍጻሜ ም. ፩ኛ ጴጥ. ም.፫ ቊ. ፩—፮ ግብ.ሐዋ. ም.፲፮ ቊ.፲፫—፲፱ ምስባክ ወይወስዱ ለንጉሥ ደናግለ ድኅሬሃ፤ ወቢጻሂ ይወስዱ ለከ፤ ወይወስድዎን በትፍሥሕት ወበሐሤት፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ዮሐንስ ም. ፰ ቊ. ፱—፲፪ ቅዳሴ፡ ዘእግዝእትነ (ጐሥዓ) ነሐሴ 3 ምንባባት፡ ፩ኛተሰ. ም፩ ቊ.፩—ፍጻሜ ም. ፩ኛ ጴጥ. ም.፫ ቊ. ፲—፲፭ ግብ.ሐዋ. ም.፲፬ ቊ.፳—ፍጻሜ ም. ምስባክ ወይሰግዳ ሎቱ አዋልደ ጢሮስ በአምኃ፤ ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር፤ ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ሉቃስ ም. ፲፰ ቊ. ፱—፲፰ ቅዳሴ፡ ዘእግዝእትነ (ጐሥዓ) ነሐሴ 4 ምንባባት፡ ሮሜ. ም፲፪ ቊ.፲፰—ፍጻሜ ም. ፩ኛ ጴጥ. ም.፭ ቊ. ፲፪ ግብ.ሐዋ. ም.፲፯ ቊ.፳፫—፳፰ ምስባክ እግዚኦ በኃይልከ ይትፌሣሕ ንጉሥ፤ ወብዙኃ ይትሐሠይ በአድኅኖትከ፤ ፍትወተ ነፍሱ ወሀብኮ፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ሉቃስ ም. ፲፬ ቊ. ፴፩—ፍጻሜ ም. ቅዳሴ፡ ዘእግዝእትነ አው ዘቄርሎስ ነሐሴ 5 ምንባባት፡ ፪ኛቆሮ. ም፲፪ ቊ.፲—፲፯ ፍጻሜ ም. ፩ኛ ዮሐ. ም.፭ ቊ. ፲፬—ፍጻሜ ም. ግብ.ሐዋ. ም.፲፭ ቊ.፩—፲፫ ምስባክ ወትሰይመኒ ውስተ ርእሰ ሕዝብ፤ ሕዝብ ዘኢየአምር ተቀንየ ሊተ፤ ውስተ ምስማዐ ዕዝን ተሠጥዉኒ፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ሉቃስ ም. ፲፭ ቊ. ፩—፲፩ ቅዳሴ፡ ዘእግዝእትነ አው ግሩም ነሐሴ 6 ምንባባት፡ ፩ኛቆሮ. ም፫ ቊ.፲—፳፪ ፩ኛ ጴጥ. ም.፫ ቊ. ፯ ግብ.ሐዋ. ም.፲፮ ቊ.፲፫—፲፱ ምስባክ ወይሰግዳ ሎቱ አዋልደ ጢሮስ በአምኃ፤ ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር፤ ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ማርቆስ ም. ፲፮ ቊ. ፱—፲፱ ቅዳሴ፡ ዘእግዝእትነ አው ግሩም ነሐሴ 7 ምንባባት፡ ዕብ. ም፩ ቊ.፩—፲፯ ፩ኛ ጴጥ. ም.፪ ቊ. ፯—፲፰ ግብ.ሐዋ. ም.፲ ቊ.፩—፴ ምስባክ መሠረታቲሃ ውስተ አድባር ቅዱሳን፤ ያበድሮን እግዚአብሔር ለአናቅጸ ጽዮን፤ እምኩሉ ተዓይኒሁ ለያዕቆብ፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ማቴዎስ ም. ፩ ቊ. ፩—፲፯ ቅዳሴ፡ ዘእግዝእትነ ነሐሴ 8 ምንባባት፡ ሮሜ. ም፫ ቊ.፱—፳፬ ፩ኛ ጴጥ. ም.፬ ቊ. ፲፪—ፍጻሜ ም. ግብ.ሐዋ. ም.፲፯ ቊ.፴፩—ፍጻሜ ም. ምስባክ ወድቀት እሳት ወኢርኢክዋ ለፀሐይ፤ ዘእንበለ ይትዐወቅ ሦክክሙ ሕለተ ኮነ፤ ከመ ሕያዋን በመዓቱ ይውኅጠክሙ፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ማቴዎስ ም. ፯ ቊ. ፲፪—፳፮ ቅዳሴ፡ ዘእግዝእትነ (ጐሥዓ) ነሐሴ 9 ምንባባት፡ ፊልጵስ. ም፩ ቊ.፲፪—፳፬ ፪ኛ ዮሐ. ም.፩ ቊ. ፯—ፍጻሜ ም. ግብ.ሐዋ. ም.፲፭ ቊ.፲፱—፳፭ ምስባክ ወትቀውም ንግሥት በየማንከ፤ በአልባሰ ወርቅ ዑፅፍት ወሑብርት፤ ስምዒ ወለትየ ወአጽምኢ እዝነኪ፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ዮሐንስ ም. ፲ ቊ. ፩—፳፪ ቅዳሴ፡ ዘእግዝእትነ አው ዘባስልዮስ ነሐሴ 10 ምንባባት፡ ዕብ. ም፩ ቊ.፩—፳፪ ፩ኛ ጴጥ. ም.፩ ቊ. ፯—፲፫ ግብ.ሐዋ. ም.፬ ቊ.፴፩—፳፭ ምስባክ ተዘከር ማኅበረከ በትረ ርስትከ፤ ወአድኀንከ በትረ ርስትከ፤ ደብረ ጽዮን ዘኀደርከ ውስቴታ፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ሉቃስ ም. ፲፮ ቊ. ፱—፲፱ ቅዳሴ፡  ዘእግዝእትነ (ጐሥዓ) ነሐሴ 11 ምንባባት፡ ፩ ቆሮ. ም፳ ቊ.፲፩—ፍጻሜ ም. ፩ኛ ዮሐ. ም.፪ ቊ. ፲፬—፳ ግብ.ሐዋ. ም.፲፪ ቊ.፲፰—፳ ምስባክ ህየንተ አበውኪ ተወልዱ ለኪ ደቂቅ፤ ወትሠይሚዮሙ መላእክተ ለኵሉ ምድር፤ ወይዘክሩ ስመኪ በኵሉ ትውልደ ትውልድ፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ሉቃስ ም. ፮ ቊ. ፳—፳፬ ቅዳሴ፡  ዘእግዝእትነ (ጐሥዓ) ነሐሴ 12 ምንባባት፡ ፩ ቆሮ. ም፱ ቊ.፲፯—ፍጻሜ ም. ይሁዳ. ም.፩ ቊ. ፳ ግብ.ሐዋ. ም.፳፬ ቊ.፩—፳፪ ምስባክ እግዚኦ ኩነኔከ ሀቦ ለንጉሥ፤ ወጽድቀከኒ ለወልደ ንጉሥ፤ ከመ ይኰንኖሙ ለሕዝብከ በጽድቅ፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ማቴዎስ ም. ፳፪ ቊ. ፩—፲፭ ቅዳሴ፡ ዘእግዝእትነ አው ዘዮሐንስ አፈወርቅ ነሐሴ 13 ምንባባት፡ ዕብ. ም፲፩ ቊ.፳፫—፴ ፪ኛ ጴጥ. ም.፩ ቊ. ፲፩ ግብ.ሐዋ. ም.፯ ቊ.፵፬—ፍጻሜ ም. ምስባክ ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌሥሑ፤ ወይሴብሑ ለስምከ፤ መዝራዕትከ ምስለ ኃይል፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ሉቃስ ም. ፱ ቊ. ፳፰—፴፰ ቅዳሴ፡ ዘእግዝእትነ አው ዘዲዮስቆሮስ፡፡ ነሐሴ 14 ምንባባት፡ ፩ ቆሮ. ም.፩ ቊ.፲—፲፪ ያዕቆብ. ም.፩ ቊ. ፲፪ ግብ.ሐዋ. ም.፲ ቊ.፴—፵፬ ምስባክ ዘአዘዝከ መድኃኒቶ ለያዕቆብ፤ ብከ ንወግዖሙ ለኵሎሙ ፀርነ፤ ወበስምከ ናኃሥሮሙ ለእለ ቆሞ ላዕሌነ፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ማቴዎስ ም. ፲፯ ቊ. ፲፬—፳፬ ቅዳሴ፡ ዘእግዝእትነ አው ዘዮሐንስ አፈወርቅ፡፡ ነሐሴ 15 ምንባባት፡         ቆሮ. ፩ ም. ፲፪ ቊ. ፲፰—ፍጻሜ ም.  ይሁዳ. ፩ ቊ. ፲፯—ፍጻሜ ም. የሐዋ. ፩ ቊ. ፩—፲፪ ምስባክ፡ ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ፤ ወእስከ አጽናፈ ዓለም በጽሐ ነቢቦሙ፤ ወውስተ ፀሐይ ሤመ ጽላሎቶ፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ማቴዎስ ም. ፲ ቊ. ፩—፲፭ ቅዳሴ፡ ዘሐዋርያት (ዘበደኃሪ) ነሐሴ 16 ምንባባት፡ ሮሜ. ፰ ቊ. ፴፰—ፍጻሜ ም.  ዮሐ. ፪ ቊ. ፩—፯  የሐዋ. ፩ ቊ. ፲፪—፲፭ ምስባክ፡   ቀደሰ ማኅደሮ ልዑል፤ እግዚአብሔር ውስተ ማዕከላ ኢትትሐወክ፤ ወይረድኣ እግዚአብሔር ፍጽመ፤ ወንጌል፡ ወንጌለ ማቴዎስ. ፳፮  ቊ. ፳፮—፴፩ ቅዳሴ፡ ዘእግዚእነ (ነአኵተከ)

††† ✝✝እንኳን ለአበው ቅዱሳን ሴት : ሕዝቅኤል ነቢይ እና ዮሐንስ ወንጌላዊ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፣ አደረሰን። †††✝✝ ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††✝✝ ቅዱስ ሴት ነቢይ †††✝✝ ††† አባታችን ሴት የመጀመሪያዎቹ ፍጥረቶች የአዳምና ሔዋን የተባረከ ልጅ ነው:: ቀደምተ ፍጥረት አዳም እና ሔዋን በዕጸ በለስ ምክንያት ከገነት ከተባረሩ በኋላ በመጀመሪያ ቃየን እና አቤልን ከነ መንትያዎቻቸው ወልደው ነበር:: ነገር ግን የልጅ ደስታቸው ቀጣይ ሊሆን አልቻለም:: ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ ቃየን ሲሆን ወንድሙን አቤልን በጾታዊ ፍላጐት ምክንያት በመግደሉ ነበር:: የአቤል ሞት ለአባታችን አዳም መራር ዜና ነበር:: ወላጅ እንኳን ደጉን ይቅርና ክፉ ልጁም እንዲለየው አይፈልግምና:: ቅዱስ አዳም ቅዱስ አቤልን ቀብሮ: ፈጽሞ አለቀሰ:: ልቅሶውም እንዲሁ የወርና የሁለት ወር አልነበረም:: አራት ኢዮቤልዩ (ሃያ ስምንት ዓመታት) ነበር እንጂ:: ይህንን ሐዘንና ልቅሶ የተመለከተ እግዚአብሔር ደግሞ ደግ ፍሬን በሔዋን ማኅጸን ውስጥ አሳደረ:: ይሕ ሕፃን በተወለደ ጊዜ "ሴት" ብለው ስም አወጡለት:: ትርጉሙም "የአቤል ምትክ" እንደ ማለት ነው:: ሴት ገና ከልጅነቱ ጀምሮ በብዙ ነገሩ አዳምን የሚመስል ነበረ:: ደም ግባቱ: ቅንነቱ: ታዛዥነቱ: ደግነቱ ሁሉ ልዩ ነበር:: በዚህም አዳምና ሔዋን ተጸናንተዋል:: ትልቁ ነገር ደግሞ ዓለም የሚድንባት እመቤት ድንግል ማርያም ከስልሳ በላይ የአዳም ልጆች ተመርጣ ለቅዱስ ሴት መሰጠቷ ነው:: ይሕንን ምሥጢርና የሴትን ማንነት ያስተዋለው ሊቁ አባ ሕርያቆስ እመ ብርሃንን እንዲህ ሲልም አመስግኗታል:: "ሒሩቱ ለሴት - የሴት ደግነቱ: በጐነቱ: ቅንነቱ አንቺ ነሽ" (ቅዳሴ ማርያም) አባታችን ሴት በሚገባው ትዳር ተወስኖ ቅዱስ ሔኖስንና ሌሎች ብዙ ልጆችን ወልዷል:: አባታችን አዳም ባረፈ ጊዜ የዚህን ዓለም እረኝነት (በደብር ቅዱስ ላሉት) ተረክቧል:: አዳምም ልጆቹንና ወርቅ እጣን ከርቤውን አስረክቦታል:: ሴት እንባው እንደ ዥረት እየፈሰሰ አስቀድሞ አዳምን: አስከትሎም ሔዋንን ገንዞ በክብር ቀብሯቸዋል:: ወርቅ: እጣን: ከርቤውን ከሥጋቸው ጋራ በቤተ መዛግብት (በተቀደሰው ዋሻ) ውስጥ አኑሮታል:: የአገልግሎት ዘመኑ በተፈጸመ ጊዜ ደጉ ሴት ኃላፊነቱን ለልጁ ሔኖስ ሰጥቶ በዘጠኝ መቶ አሥራ ሁለት ዓመቱ ዐርፏል:: እርሱም ከወላጆቹ አዳምና ሔዋን ጋር ተቀላቅሏል:: ††† ✝✝ቅዱስ ሕዝቅኤል ነቢይ✝✝ ††† ††† ነቢዩ ቅዱስ ሕዝቅኤል የነበረው ቅ/ል/ክርስቶስ በ500 ዓመት አካባቢ ሲሆን የጼዋዌ (ምርኮ) አባልም ነበር:: እሥራኤልና ይሁዳ ወደ ባቢሎን በምርኮ ሲወርዱ አብሮ ወርዷል:: ቅዱሱ ከአራቱ ዐበይት ነቢያት አንዱ ሲሆን ሐረገ ትንቢቱም በአርባ ስምንት ምዕራፎች የተዋቀረ ነው:: በዘመኑ ሁሉ ቅድስናን ያዘወተረው ቅዱሱ ከደግነቱ የተነሳ በጸጋማይ (ግራ) ጐኑ ተኝቶ ቢጸልይ ስድስት መቶ ሙታንን አስነስቷል:: ወገኖቹ እሥራኤልንም ያለ መታከት አስተምሯል:: ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዚህች ዕለት ታላቁን ራዕይ እንዳየ ታስተምራለች:: ነቢዩ በፈለገ ኮቦር ካያቸው ምሥጢራት እነዚህን ያነሷል:- 1.እግዚአብሔርን በዘባነ ኪሩብ ተቀምጦ ሲሠለስና ሲቀደስ አይቶታል:: የኪሩቤልንም ገጸ መልክእ በጉልህ ተመልክቷል:: (ሕዝ. 1:1) 2.በመጨረሻው ቀን ትንሣኤ ሙታን : ትንሣኤ ዘጉባኤ እንደሚደረግም ተመልክቷል:: (ሕዝ. 31:1) 3.እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ኆኅት ኅትምት/ኆኅተ ምሥራቅ (የምሥራቅ ደጅ) ሁና አይቷታል:: ይሕ የምሥራቅ ደጅ (በር) ለዘላለም እንደታተመ ይኖራል:: የኃያላን ጌታ ሳይከፍት ገብቶ: ሳይከፍት ወጥቷልና:: (ሕዝ. 44:1) በመጨረሻ ሕይወቱ እሥራኤል ለክፋት አይቦዝኑምና ነቢዩን አሰቃይተው ገድለውታል:: †††✝✝ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ✝✝††† ††† አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቅዱስ ወንጌሉ እንደነገረን በመንግስተ ሰማያት ታላቁ ሰው ወንጌላዊው ዮሐንስ ነው:: ቅዱሱ ሐዋርያ ከዘብዴዎስ እና ከማርያም ባውፍልያ ተወልዶ : በገሊላ አካባቢ አድጐ : ገና በወጣትነቱ መድኃኔ ዓለምን ተከትሎታል:: ቅዱስ ዮሐንስ ከሐዋርያት ቀድሞ ጌታን ከመከተሉ ባሻገር በምንም ምክንያት ከጐኑ አይጠፋም ነበር:: ስለ ንጽሕናውና በጐ የፍቅር ሕሊናው ሕፃን ሳለ በወንድሞቹ ሐዋርያት ዘንድ ሞገሱ ከፍ ያለ ነው:: ጌታችንን እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ በመከተሉ ድንግል እመቤታችንን ተቀብሏል:: ከእርሷ ጋር ለአሥራ አምስት ዓመታት ቢቀመጥ መዝገበ ምሥጢር ሆነ:: ስንኳን ከሰው ልጆች ይቅርና ከልዑላኑ መላእክትም ማዕረጉ ከፍ አለ:: ሰው ቢበቃ መላእክትን ሊያይ ይቻለዋል:: ቅዱስ ዮሐንስን ግን መላእክት ሊያዩት ይከብዳቸዋል:: ከፍጥረት ወገን ከእመ ብርሃን ቀጥሎ ክቡር እርሱ ነው:: በዚህ ቀንም ቅዱስ ዮሐንስ በታናሽ እስያ ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት መስበኩ ይታሰባል:: ቅዱሱ ከጌታችን ዕርገት በኋላ ለሰባ ዓመታት በዚህ ምድር ሲኖር አብዛኛውን ጊዜውን ያሳለፈው በኤፌሶን አካባቢ ነው:: ሕዝቡን ወደ ክርስትና ለማምጣት በአፍም : በመጽሐፍም ደክሟል:: ሦስት መልዕክታት : ራዕዩንና ወንጌልን ጽፎላቸዋል:: ሕይወትን ስለ ሰበከላቸው በፈንታው ብዙ አሰቃይተውታል:: ከእሳት እስከ ስለት : እስከ መጋዝም በስተእርጅና ደርሶበታል:: እርሱ ግን በትእግስቱ ገንዘብ አድርጓቸዋል:: ዳግመኛ ይሕች ዕለት ለሐዋርያው ቅዳሴ ቤቱ ናት:: ††† እናት ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ዮሐንስን ስትጠራው እንዲሕ ነው:- ¤ወንጌላዊ ¤ሐዋርያ ¤ሰማዕት ዘእንበለ ደም ¤አቡቀለምሲስ(ምሥጢራትን ያየ) ¤ታኦሎጐስ (ነባቤ መለኮት) ¤ወልደ ነጐድጓድ ¤ደቀ መለኮት ወምሥጢር ¤ፍቁረ እግዚእ ¤ርዕሰ ደናግል (የደናግል አለቃ) ¤ቁጹረ ገጽ ¤ዘረፈቀ ውስተ ሕጽኑ ለኢየሱስ (ከጌታ ጎን የሚቀመጥ) ¤ንስር ሠራሪ ¤ልዑለ ስብከት ¤ምድራዊው መልዐክ ¤ዓምደ ብርሐን ¤ሐዋርያ ትንቢት ¤ቀርነ ቤተ ክርስቲያን ¤ኮከበ ከዋክብት ††† በቅዱስ ዮሐንስ ላይ ያደረ የእመቤታችን ድንግል ማርያምና የአንድ ልጇ ፍቅር በእኛም ላይ ይደር:: የሴት ደግነቱ : የሕዝቅኤልም በረከቱ ይደርብን:: ††† ሐምሌ 27 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ ሴት ነቢይ (ወልደ አዳም) 2.ቅዱስ ሕዝቅኤል ነቢይ 3.ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ (ቅዳሴ ቤቱ) 4.ቅዱስ አሞን ሰማዕት ††† ወርኀዊ በዓላት 1.የጌታችንና አምላካችን መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ በዓለ ስቅለት 2.አቡነ መብዐ ጽዮን ጻድቅ 3.ቅዱስ መቃርስ (የመነኮሳት ሁሉ አለቃ) 4.ቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ 5.ቅዱስ ገላውዴዎስ ሰማዕት (ንጉሠ ኢትዮጵያ) 6.ቅዱስ ቢፋሞን ጻድቅና ሰማዕት 7.ማር ቅዱስ ፊቅጦር ሰማዕት ††† ". . . "እኔ ሕያው ነኝና ኃጢአተኛው ከመንገዱ ተመልሶ በሕይወት ይኖር ዘንድ እንጂ ኃጢአተኛው ይሞት ዘንድ አልፈቅድም" ይላል ጌታ እግዚአብሔር:: "የእሥራኤል ቤት ሆይ! ተመለሱ:: ከክፉ መንገዳችሁ ተመለሱ:: ስለ ምንስ ትሞታላችሁ?" በላቸው::" ††† (ሕዝ. ፴፫፥፲፩) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

+++ "እኔ" ብቻ +++ ዕውቁ ሩስያዊው የልብ ወለድ ደራሲ ዶስቶየቩስኪ "Brothers Karamazov" በተሰኘው ድርሰቱ ስለ አንዲት ምናባዊት ንፉግ ሴት ታሪክ እንዲህ ይተርካል። በአንድ ዘመን በግብርና ሥራ እየተዳደረች የምትኖር ክፉ ሴት ነበረች። ታዲያ በሕይወት እያለች አንድ በጎ ነገር እንኳ ሳትሠራ ይህን ዓለም በሞት ተሰናበተች። ነፍሷም በወጣች ጊዜ ወዲያው አጋንንት እየተናጠቁ ይዘዋት ሄደው ወደ እሳት ባሕር ወረወሯት። ጠባቂ መልአኳም ይህን ባየ ጊዜ ከፈጣሪ ፊት ቆሞ የሚያዘክርላት ጥቂት በጎ ሥራ ሠርታ እንደ ሆነ ለማስታወስ ሞከረ። ወዲያውም "አንድ ጊዜ ከማሳዋ ላይ አንድ ራስ ሽንኩርት ነቅላ ለአንዲት ነዳይ መስጠቷን" ለአምላኩ አሳሰበላት። እግዚአብሔርም "በል ያን ሽኝኩርት ውሰድና ወደ እርሷ ሂድ። እርሱን ይዛ መውጣት ከቻለች ወደ ገነት ታስገባታለህ። ካልሆነ ግን እዚያው ሲኦል ትቀራለች" አለው። መልአኩም እንደ ተባለው ሴቲቱ የሽንኩርቱን ራስ እንድትይዝ አድርጎ በጥንቃቄ ወደ ውጭ ይስባት ጀመር። ነገር ግን ሌሎች በዚያ የእሳት ባሕር ውስጥ የነበሩ ኃጥአን ስትወጣ ሲመለከቱ አብረዋት ለመውጣት እርሷ ላይ ተንጠላጠሉ። ያቺ ጨካኝ ሴት ግን ክፉኛ በመወራጨት ከላይዋ ላይ እያራገፈቻቸው "እኔ ነው እየሳበኝ ያለው እናንተን አይደለም። ይህ ሽንኩርት የእኔ ነው። የእናንተ አይደለም።" አለች። ይህን እየተናገረች ሳለም የያዘችው የሽንኩርቱ ጫፍ ተበጥሶ  ወደ እሳቱ ተመልሳ ገባች። መልአኩም በሁኔታው እያዘነ ከእርሷ ተለይቶ ሄደ። ያን የሽንኩርት ጫፍ የበጠሰው ምን ይመስላችኋል? እርሷ ላይ የተንጠለጠሉት ነፍሳት ወይስ የእርሷ ጭካኔ እና ንፋግነት? ይህ የዶስቶቩስኪ ምናባዊ ትርክት በዚህ ዘመን ያለነውን የእያንዳንዳችንን ማንነት ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ይመስለኛል። ከመጠን በላይ ለራስ በመጨነቅና የራስን ምቾት ብቻ መፈለግ የእኛ ጊዜ መለያ ጠባይ ሆኗል። በንግግራችን ውስጥ "እኔ" "ለእኔ" "የእኔ" የሚሉት ቃላት እየረቡ "እኛ" የሚለው ቃል እየሳሳ መጥቷል። በብዙዎች የሚመለክ በየቤቱ የቆመ  የዘመኑ አዲስ ጣዖት ቢኖር "እኔ"ነት (ራስ) ነው። ጥቂት የማይባሉ ሰዎች የትኩረት ማዕከል ለመሆን የማይቆፍሩት ጉድጓድ የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለም። በተገኙበት ሁሉ ስለ እነርሱ እንዲወራ ይፈልጋሉ። ለቀብር እንኳን ሄደው ለሞተው ሰው ከሚሰጠው ትኩረት አንጻር በዚያች ቅጽበት ያን አስከሬን ቢሆኑ አይጠሉም። ስማቸውን በየሰው አፍ ለማስገባትና መነጋገሪያ ለመሆን የትኛውንም ዓይነት ዋጋ ይከፍላሉ። ይህን ጊዜ "ራስን መውደድ" በሽታ ይሆናል። በራስ ዓለም ውስጥ እንደ መጥፋት፣ ራስን በራስ እንደመዋጥ ያለ ሊታከም የሚገባው ጽኑ ደዌ! ሁልጊዜ በስግብግብነት እና ለእኔ ብቻ በማለት ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች መንፈሳቸው የተሰበረ ይሆናል። የገዙት አያስደስታቸውም፣ የሰበሰቡት አያረካቸውም። በሕይወታቸው ውስጥ ያስወጡት መልካም ነገር ስላለ መቼም የውስጥ ዕረፍት አያገኙም። ያ ከሕይወታቸው ያስወጡት መልካም ነገር ምንድር ነው? "ብቻ ያለ መሆን" መልካምነት ነዋ! "ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም" ዘፍ 2፥18 በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ግለኝነትና "ለእኔ ብቻ" ማለት ፈጽሞ የተወገዘ ነው። ምድር ላይ ባለችው ቤተ ክርስቲያን በኅብረት መንፈስ ካልኖርህ "በሰማያት ወደ ተጻፉት የበኩራት ማኅበር" ልትገባ አትችልም።(ዕብ 12፥23) በእግዚአብሔር ዙፋን ዙሪያ ቆመው የሚያመሰግኑት ሱራፌል ክንፎቻቸው እርስ በርስ የተያያዘ ነው። ይህንንም አንድ ሊቅ ሲተረጉም በአምላክ ዙፋን ፊት ለመቆምና ከእነዚህ አመስጋኝ  መላእክት ጋር አብሮ ለመቆጠር ሰዎች በአንዲት ኅብረት ሊኖሩ እንደሚገባቸው ያሳያል ሲል ተርጉሞታል። ክርስትና ራስን ማዕከል የማድረግ ሳይሆን ሌሎችን የማገልገልና ስለ ብዙዎችም በፍቅር መሥዋዕት የመሆን ሕይወት ነው። ዲያቆን አቤል ካሳሁን

+• የሕይወት ስንክሳር •+ የሕይወት ስንክሳር ሦስት ታላላቅ ክፍሎች አሏት:- ትላንት፥ ዛሬ እና ነገ:: ትላንት ስንል የምናወራው ታሪክን ነው:: ትላንትን ከትውስታ ወይም ከማኅደር እየመዘዝን "እንዲህ ሆኖ ነበር" እንላለን:: ከዚያ ባለፈ ግን ትላንት የተባለው የሕይወት ክፍል ላይ የተጻፈው አንዴ ሆኗልና ሊቀየር የማይችል ነው:: መለስ ብለን ልንፍቀው እና እንደ አዲስ ልንጽፈውም አይቻለንም:: ብልህ ከሆንን ተምረንበት ዛሬያችንን ያማረ፤ ነጋችንን የሠመረ እናድርግበታለን:: ዛሬ ደግሞ ከትላንት እና ከነገ መካከል ያለ እንቆቅልሽ ነው:: ዛሬን እንደ ትላንት ታሪክ ልንለው አንችልም:: አሁን ያለ ስጦታ ነው:: ዛሬን ጣፋጭ እንዳየ ሕጻን ልጅ ፈንድቀን መጠቀም ነው:: ዛሬያችን ነገ ላይ "ትላንት" ስለሚባል አሳምረን መጻፍ ነው:: ዛሬያችን የመዳን ቀን ነው:: ኃጢያታችንን አስፍቀን፥ ክርስቶስን እንደ ሸማ ለብሰን አጊጠን "ድሮ እንዲህ ነበሩ፤ ዛሬ ግን እንዲህ ሆኑ!" መባል የምንችልበት ገጸ በረከት ነው:: ነገ ግን ምስጢር ናት:: የነገው ገጾች ገና አልተጻፈባቸውም:: ነገን "እንዲህ ነው" ብለን በእርግጠኛነት አንናገረውም:: ምን እንደሚሆን ማን ያውቃል? ማን ሞቶ ማንስ ተወልዶ እንደሚያድር በእርግጠኛነት ሊናገር የሚችለው ማን ነው? የዓለም ታሪክ አይወድቁም የተባሉ ሲወድቁ፥ ብርቱ ናቸው የተባሉ ሲደቅቁ፥ ሺህ ዓመት ይንገሱ የተባሉ ሺህ ሰዓታት ሳይሞላቸው ከንግሥና ሲወርዱ፥ ይደልዎ ተብለው የተሾሙ ሲዋረዱ፥ ተወርውረው የተጣሉ ተፈልገው ሲከብሩ አሳይቷል:: ትላንት በታሪክ ልሳን ውስጥ ሕያው ናት፤ ዛሬ ደግሞ ስጦታችን ነች:: ነገ ግን ያለችው በፈጣሪ መዳፍ ብቻ ነው:: ትላንት በማለፏ ትነገራለች፥ ዛሬን እንኖራለን (ወይም እንሞታለን - ማን ያውቃል?) ነገ ግን ወደ ቀኝ ትታጠፍ ወደ ግራ ከፈጣሪ ውጪ የሚያውቅ ማንም የለም:: ይህ ሁሉ የጊዜ ግስጋሴ ግን ማብቃቱ አይቀርም:: ሊቃውንት "ጊዜ ሁሉን ያስረጃል፥ አምላክ ግን ጊዜን ያስረጃል" የሚሉት ለዚሁ ነው:: ትላንትን እያስቆጠረ፥ ዛሬን እያሳለፈ፥ ነገን ተስፋ እያስደረገ የሚነጉደው ጊዜም ተራው ሲደርስ በተራው ያረጃል:: ይህ ሲሆን የሕይወት ስንክሳራችንም ያበቃል፤ መጽሐፉም ይዘጋል:: ትላንታችን ላይ ምን ተጽፏል? ዛሬያችን ላይ ምን ለመጻፍ ተዘጋጅተናል? ነጋችንስ ምን ይል ይሆን? የሕይወታችን ስንክሳር ተጠናቅቆ በፈጣሪ ፊት ሲነበብ ምን ይናገር ይሆን? 🖋 Fresenbet G.Y Adhanom

"ጌታ ሆይ ወርቅ ትሰጠኝ ዘንድ አልለምንህም ሀብት ንብረትም አልለምንህም እነርሱ ድኅነትን የሚያስገኙ አይደሉም። ይቅርታህን ማግኘት ግን ከወርቅ ይልቃል። የኃጢአት ሥርየትን ማግኘትም ከብር ይበልጣል።" (ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ)

"በባልንጀራህ ላይ የምትቆጣ ከሆነ የአንተ ቁጣ በእግዚአብሔር ላይ ነው፡፡ በባልንጀራህ ላይ ቂምን በልብህ የያዝክ ከሆነ ቂምህ በጌታ ላይ ነው፡፡ ባልንጀራህን በከንቱ የምትቆጣው ከሆነ ኃጢአት በአንተ ላይ ይስለጠንብሃል፡፡ ልብህን የፍቅር ማደሪያ ካደረከው በምድር ላይ አንዳች ጠላት አይኖርህም፡፡" ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ

"በቤተ ክርስቲያን ውስጥ መለያየትን መፍጠር፣ በኑፋቄ ከመውደቅ ያነሰ ኃጢአት አይደለም። የመለያየት ኃጢአት በሰማዕትነት ደም እንኳን ሊነጻ አይችልም።" ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

+++ "ልጆቼ ከመሸ ተገናኘን" +++ ያኔ የገዳሙ መጋቢ የነበሩት አባ ተጠምቀ በጭንቀት ተውጠዋል። ከአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ እግር ስር ወድቀው "ግድ የልዎትም አባ የዛሬው ጉዞ ይቆይዎ። እኔ ጥሩ ሕልም አላየሁም። እባክዎ እግርዎን ከዚህ ቤት አያንሡ፤ እንደው እባክዎ" እያሉ ይለምኗቸዋል። አቡነ ጎርጎርዮስ ግን ወደ መቂ ጊዮርጊስ ለአገልግሎት ለመሄድ ቆርጠው ተነሥተው ነበርና ሳልሄድ አላድርም ብለው እምቢ አሉ። በእርግጥ በዚያች የጉዞ ቀን ምን ሊሆኑ እንደሚችሉ ቀድመው ሳይረዱት ቀርተው አይመስልም። ምክንያቱም "ዛሬ ጥሩ ሕልም አላየሁምና አይሂዱ" ላሏቸው አባ ተጠምቀ " እኔስ ብሆን አንዳች ምልክት ያላየሁ ይመስልሃል። ዛሬ ጠዋት ሱሬን ስታጠቅ ሰባት ጊዜ መልሶ ሲፈታብኝ ነበር" ሲሉ መልሰውላቸዋል። ይሁን እንጂ በመቂ የሚገኝ እጅግ ሕመም የጸናበት አንድ የሚያውቁት  ክርስቲያን ስለ ነበር ከራሳቸው ሕይወት ይልቅ ለዚያ ሰው ነፍስ ዋጋ ሰጥተው "ኸረ ሳላቆርበው እንዳይሞትብኝ" እያሉ አባ ጎርጎርዮስ ወደ መኪናው ፈጥነው ወጡ። ነገር ግን ከዚያ መኪና በሕይወት አልወረዱም። ከአዲስ አበባ ሕዝብ ጭኖ ከመጣ ተሽከርካሪ ጋር እርሳቸው ያሉበት መኪና ተጋጭቶ እሑድ ኃምሌ 22 ቀን ጠዋት አንድ ሰዓት ገደማ እኛ ደግ እና ባለ ብዙ ራእይ አባት አረፉ። ብፁዕነታቸው ከማረፋቸው ከ15 ቀናት በፊት በአላጌ ሕፃናት አምባ የልጆች ማሳደጊያ ተገኝተው በዚያ ቦታ ለሚሠራ ቤተ ክርስቲያን መሠረት ካኖሩ በኋላ "ሰው የሚፈልገውን ከሠራ የሚጠብቀው ሞቱን ነው" ብለው ተናግረው ነበር። በውስጣቸውም የነበረው የአገልግሎት እሳት ገና እየተቀጣጠለ ቢሆንም በዚህች ምድር የሚቀራቸው የእንግድነት ዘመን ግን ጥቂት መሆኑን ስለተረዱ በዚያ ለነበሩት መንፈሳዊ ልጆቻቸው እየደጋገሙ "ልጆቼ ከመሸ ተገናኘን" ይሏቸው ነበር። ከዚህች ክፋት ከነገሠባት ዓለም ጠልቀው ፈጣሪያቸው ካለበት መንፈሳዊ አገር የሚወጡበት ጊዜ መቃረቡን ቀድመው የተረዱ አባት ነበሩ። አቡነ ጎርጎርዮስ ከዘመናቸው ቀድመው የኖሩ፣ ትውልዱ ሃይማኖቱን ያቆዩለትን አባቶች እንዲያውቅና የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ እምነቱንም ታሪክ ከመሠረቱ ተረድቶ ቤተ ክርስቲያኑን እንዲያፈቅር በቃልም በመጽሐፍም የተጉ አባት ናቸው። ቅዱስ አባታችን የነበሩበትን ዘመን አልፎ በሚሄደው ተራማጅ አሳቢነታቸውና ለቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ ዕድገት ያሳዩት በነበረው ትጋት አሁን ላይ ላሉትና ወደ ፊትም ለሚነሡ በእውነት ለሚደክሙ ቅን አገልጋዮች ሁሉ ትልቅ አርአያ ይሆናሉ። የአገልግሎት ድካማቸው በረከት በሁላችን ላይ ይደርብን። እኛንም የአባቶቻችን ልጆች ያድርገን!!! (*የያኔው አባ ተጠምቀ የአሁኑ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሳይ የምሥራቅ ሸዋ አገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ናቸው።) ዲያቆን አቤል ካሳሁን ሐምሌ 22፣ 2014 ዓ.ም.