en
Feedback
"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

Open in Telegram

@Dan12bot ለአስተያየትዎ ይህን ይጠቀሙ እናመሠግናለን

Show more
1 134
Subscribers
No data24 hours
-27 days
-2330 days
Posts Archive
በሕይወት ውስጥ መጀመሪያ ከፊት የሚመጡት ሰዎች "ሔዋንህ" ወይም "አዳምሽ" ላይሆኑ ይችላሉ። ልክ አዳም ከተፈጠረ በኋላ መጀመሪያ በእርሱ ፊት እንስሳትን እንዳገኘ እና ለእነርሱም የሚገባቸውን ስም እየሰጠ እንዳሰናበታቸው፣ አንተም አንዳንዴ በኑሮህ ቀድመህ የምታገኛቸው አካላት "ጎረቤት፣ የሥራ ባልደረባ፣ ጓደኛ" እያልክ ስም የምታወጣላቸው ብቻ ይሆናሉ። ለምን? "እንደ አንተ ያሉ (የሚመቹ) ረዳቶች" አይደሉማ። አዳም ለእንስሳት፣ ለሰማይ ወፎችና ለምድር አራዊት ሁሉ ስም ካወጣላቸው በኋላ መጽሐፉ "ለአዳም እንደ እርሱ ያለ ረዳት አልተገኘለትም ነበር" ይላል።(ዘፍ 2፥20) አዳም እንደ እርሱ ያለ ረዳት ከእንስሳቱ መካከል ፈልጎ በማጣቱ "በቃ የምን መኩራት ነው? ያሉት እነዚህ ስለሆኑ እኔን ባትመስል እንኳ ትንሽ ለእኔ የቀረበችውን ብመርጥ ይሻላል" አላለም።  ከሌሎች ይልቅ በአካላዊ ቁመና ለእርሱ የምትቀርበውን ትልቅ ጦጣ (Chimpanzee) መርጦም ወደ ፈጣሪው በመውሰድ "እባክህ ጌታዬ፣ ለአንተ የሚሳንህ የለምና ትንሽ ጸጉሯን ብትቀንስ፣ ጅሯቷን ብታጠፋ እና ፊቷ አካባቢ ማስተካከያ ብታደርግላት እንደ እኔ ያለ ረዳት ትሆናለች" ብሎ ሲማጸን አናገኝም። ይህን ቢያደርግ ኖሮ አሁን የአዳምን ታሪክ የምናነብ ሰዎች ሁሉ በችኮላው እየተገረምን እንስቅበት ነበር። ምክንያቱም እግዚአብሔር ከጥቂት ቀን በኋላ አጥንቷ ከአጥንቱ፣ ሥጋዋ ከሥጋው የተፈጠረ ሔዋን የተባለች እጅግ ውብ ሚስት እንደሰጠው ስለምናውቅ።  ከአንተ ጋር በሃይማኖት፣ በአመለካከትና ይህን በመሳሰሉት ነገሮች ጨርሳ ልትገጥም የማትችል የማትመችህን ረዳት "ለአንተ ምን ይሳንሃል? አስተካክልልኝ" እያልክ ለምን ትታገላለህ። በፍጹም ስለማይሆንሽ ሰው ለምን የmodification ጥያቄ ታቀርቢያለሽ? ጥቂት ጊዜ ከታገስህ እግዚአብሔር ለአንተ የምትመችህን (compatible) ረዳት ያመጣልሃል። አሁን ግን ፊት ለፊት ያገኘሃት ጥሩ የሥራ ባልደረባ ወይም ጓደኛ እንጂ የምትመች ረዳትህ አይደለችም። በሕይወት ውስጥ ቀድሞ የመጣ ሁሉ ባል ወይም ሚስት አይሆንም። መጽሐፍ ቅዱስም "ቢቻላችሁስ... ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ" ይላል እንጂ "ከሁሉ ጋር ተጋቡ" አላለንም።(ሮሜ 12፥18) ዲያቆን አቤል ካሳሁን

#ኅዳር_6 #ደብረ_ቁስቋም ኅዳር ስድስት በዚህች ዕለት ክብርት እመቤታችን ከተወደደ ልጇ ጋር ከስደት በሚመለሱበት ጊዜ ደብረ ቁስቋም ገብተው ካገኛቸው ድካም ዐረፉ፡፡ አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ከስደት በተመለሰች ጊዜ እንዲህ ሆነ፡- የብርሃን እናቱ ክብርት እመቤታችን ልጇን ይዛ ከእነ ዮሴፍ ጋር ወደ ምድረ ግብፅ ስትሰደድ ግብፅ ደርሰው በዚያ ቢቀመጡም ነገርን ግብፅ አልተመቸቻውም፡፡ ሕዝቡም በሰላም አልተቀበላቸውም፡፡ እንዲያውም በምድረ ግብፅ ብዙ ተሠቃይተዋል፡፡ ከግብፅም ተነሥተው ወደ ኢትዮጵያ በመጡ ጊዜ ግን ኢትዮጵያ ሕዝብ ሁሉ በሰላምና በፍቅር ተቀበላቸው፡፡ ከመንገዱና ከርሃብ ጥሙ ጽናት የተነሣ እጅግ ደክማለችና የኢትዮጵያ ሰዎች እመቤታችንን አይተው እጅግ አዘኑላት፡፡ ‹‹ይህችስ የነገሥታት ዘር ትመሥላለች ነገር ግን አንዳች ችግር አጋጥሟት ተሰዳ ወደ ሀገራችን መጥታለች..›› ብለው እንክብካቤን አደረጉላት፡፡ እግራቸውን አጥበው በክብር ማረፊያዎች ላይ አሳረፏቸው፡፡ መልካም መስተንግዶም አደረጉላቸው፡፡ እመቤታችንም ከድካሟ ካረፈች በኋላ ሀገሪቱን በእጅጉ ወደደቻትና የተወደደ ልጇን ‹‹ይህን ሀገርና ሕዝቧን በመላ ወድጃቸዋልሁና በዚህ እስከ መጨረሻው እንኑር›› አለችው፡፡ ጌታችንም ክብርት እናቱን ‹‹ይህች ቅድስት ሀገር ናት፣ በኋለኛው ዘመን የቅዱሳን መነኮሳት ቦታ ትሆናለች፡፡ በውስጧም እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ እመሰገንባታለሁ፤ የአንቺም ስም ሳይጠራ አይውልባትም›› አላት፡፡ ከዚህም በኋላ ጌታችን ደመና ጠቅሶ በእርሷ ላይ ተቀመጡ፡፡ መልአኩ ቅዱስ ዑራኤልም መጣና እየመራቸው መላ ኢትዮጵያን ጎበኟት፡፡ እመቤታችንም ሀገሪቱንና ሕዝቦቿን ወዳቸዋለች ደስም ተሰኝታባቸዋለችና ጌታችን ለክብርት እናቱ ‹‹ይህችን ቅድስት ሀገር አሥራት አድርጌ ሰጠሁሽ›› አላት፡፡ እመቤታችንም እጅግ ተደስታ ‹‹ልጄ አምላኬ›› ብላ አመሰገነችው፡፡ ከዚህም በኋላ ከአንዱ ቦታ ወደ አንዱ ቦታ እየተዘዋወሩ መላዋ ኢትዮጵያን በኪደተ እግራቸው ባረኳት፡፡ ጌታችንም ‹‹በዚህ ቦታ እንዲህ ዓይነት ቤተ ክርስቲያን ይታነጻል፤ እከሌ የሚባል እንዲህ ዓይነት ቅዱስ ይነሣል…›› እያለ ብዙ ምሥጢራትን ለክብርት እናቱ ነገራት፡፡ ከዚህም በኋላ የስደቱ ዘመን ሲያልፍ ሄሮድስም በመጨረሻ ክፉ አሟሟትን ሲሞት መልአኩ ወደ ገሊላ አውራጃ እንዲመለሱ ነገራቸው፡፡ እመቤታችንም ‹‹ከዚህች ሀገርስ ባንሄድ እመርጣለሁ›› ስትለው የተወደደ ልጇ ግን ‹‹እናቴ ሆይ ጽድቅንና ፈቃድን ሁሉ ልንፈጽም ይገባናል›› ብሎ አጽናናትና ወደ ሀገራቸው ተመልሰው ሄዱ፡፡ ተመልሰውም ሊሄዱ ሲነሡ የኢትዮጵያ ሰዎች ልዩ ልዩ አምሐ እጅ መንሻ ሰጧቸው፡፡ ልዩ ልዩ ልብሶች፣ ወርቅ፣ ዕጣን፣ ከርቤ፣ ሽቱ እና ሥንቀቸውን በግመሎች ላይ ጭነው እመቤታችንንና የተወደደ ልጇንም በበቅሎ ላይ አስቀምጠው በክብር ሸኟቸው፡፡ እመቤታችንም ልጇን ታቅፋ በበቅሎ ተቀምጣ በበረሃው በመጓዝ ወደ መጣችበት አገር ሄደች፡፡ ኢትዮጵያንም የሰጧትን ብዙ እጅ መንሻዎች በግመሎች ጭና ይዛ ወደ አገሯ በተመለሰች ጊዜ ከአንድ ባሕር ዳር ደረሰች፡፡ ከዚያም የጀልባውን ባለቤት ‹‹እግዚአብሔርን ስለመውደድ አሻግረኝ›› ብላ ለመነችው፡፡ ባለጀልባውም ‹‹እነሆ ዕቃ የተጫኑ አምስት ግመሎችና ከአንቺ ጋር ከዚህም ሕፃን ጭምር አምስት ሰዎች እመለከታለሁ፣ አንቺ የተቀመጥሽባት በቅሎም አለች፡፡ ጀልባዋም ታናሽ ናት፣ የመቀመጫ ክፍሏም በውስጧ የተሳፈሩት ሰዎችም ተጨናንቀው ነው ያሉት፡፡ ስለዚህ እንዴት ላሻግርሽ እችላለሁ? ነገር ግን እመቤቴ ሆይ! ይቅርታ አድርጊልኝ ይህን በክፋት አላደረግሁትምና›› አላት፡፡ ክብርት እመቤታችንም የጀልባው ባለቤት ሊያሻግራት እንዳልቻለ በተረዳች ጊዜ ‹‹ልጄ ሆይ የእግዚአብሔር ልጅ እንደመሆንህ ይህን ትልቅ ወንዝ ለመሻገር የአምላክነትህን ሥራ ትሠራ ዘንድ እለምንሃለሁ›› ስትል ማለደችው፡፡ ያንጊዜም ጌታችን ክብርት እናቱን ‹‹የወለደሽኝ እናቴ ሆይ! አትዘኝ›› ብሎ አረጋጋት፡፡ ዳግመኛም ‹‹በእኔ ፈቃድ በአባቴ ፈቃድ በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ካንቺ ሰው ሆኛለሁና ሰው መሆኔንም ከአባቴ በቀር መስተፍሥሒ ከሚሆን ከመንፈስ ቅዱስም በቀር ያወቀ የለም፡፡ ዳግመኛም በሕያዋንና በሙታን ለመፍረድ ለሁሉም እንደየሥራው እከፍለው ዘንድ እመጣለሁ፡፡ ያችንም ሰዓት የሰማይ መላእክትም ቢሆኑ የአዳም ልጆችም ቢሆኑም ከእኔና ከአባቴ ከመንፈስ ቅዱስም በቀር የሚያውቃት የለም፡፡ ያንጊዜ ‹ዐመፅን የሚናገር አንደበት ሁሉ ይዘጋል› ብሎ አባትሽ ዳዊት እንደተናገረ እከራከራለሁ የሚል አንደበት እንደድዳ ምላሽ ያጣል›› አላት፡፡ ክብርት እመቤታችን ማርያምም ይህንን ሁሉ ምሥጢር የተወደደ ልጇ የነገራትን ታስተውለው በልቧም ትጠብቀው ነበር፡፡ ጌታችንም አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ለክብርት እናቱ ይህንን ከነገራት በኋላ ቀኝ እጁን ዘርግቶ ከወንዙ ማዶ ጢር በሚባል ተራራ ያሉትን ድንጋዮች ጠቀሳቸው፡፡ ያንጊዜም እነዚህ ድንጋዮች እየተገለባበጡ መጥተው እንደ ጀልባ ሆነው በወራጁ ወንዝ ላይ ተንሳፈፉ፡፡ ከዚያም እመቤታችንን ከሕፃኑ ጋር ከነቤተሰቧና ከነጓዟ አሻገረሯት፡፡ እነዚህንም ድንጋዮች ያዩ ሰዎች ሁሉ እጅግ አድንቀው ‹‹ብቻውን ድንቅ ተአምራት ያደረገ፣ እስራኤልን የፈጠረ እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን የጌትነቱም ስም የተመሰገነ ነው›› እያሉ አመሰገኑ፡፡ እነዚህም የተባረኩ ሰዎች ወንዙን ከተሻገሩ በኋላ በዚህች አገር ለስምንት ቀን ተቀመጡ፡፡ ከዚህም በኋላ አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ስለደረገላት መልካም ሥራ ሁሉ እግዚአብሔርን ፈጽማ እያመሰገነች ወደ አባቷ ወደ ዳዊት አገር ተመለሰች፡፡ ዳግመኛም በኋለኛው ዘመን ጌታችን በዚህ በደብረ ቍስቋም ቅዱሳን ሐዋርያቶቹን ሰበሰባቸውና ታቦትንና ቤተ ክርስቲያንን አክብሮ የቍርባን መሥዋዕትንም ሠርቶ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለወገኖቹ ሰጣቸው፡፡ ለዚህም ነገር የእስክንድርያ አገር ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱሳን አባቶቻችን ቄርሎስና ቴዎፍሎስ ምስክሮቹ ሆኑ፡፡ ( ስንክሳር ዘተዋሕዶ እና #ገድላት_አንደበት)

#ለወርኃ_ኅዳር_እንኳን_አደረሰን_አደረሳችሁ።       እነሆ የዓመቱን ሦስተኛ ወር ጀመርነው። ለዚህ ያደረሰን እግዚአብሔር አምላክ ይክበር ይመስገን። " ኅዳር "  ማለት " ኅደረ " ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ቃል ሲሆን በክረምቱ ጊዜና ቀደም ባሉት ወራት የተዘሩት አዝርዕት አፍርተው ሰብሉ ፍሬ ይዞ ለመሰብሰብ የሚደርስበት ወቅት ስለሆነ በዚህ ወር እረኞች ሰብላቸውን ቀን ከአእዋፍ ሌሊት ከአጥፊ እንስሳት ለመጠብቅ በየእርሻው መሀል ጎጆ ሠርተው ስለሚያድሩ ያን ለመግለጥ የወሩ ስያሜ ኅዳር ተባለ።     በዚህ ወር ከዛሬዋ ዕለት ጀምሮ በቤተ ክርስቲያናችን በርካታ ቅዱሳን አበውና ቅዱሳት እናቶች ይዘከራሉ። የቅዱሳን መላእክት መታሰቢያም ይከበርበታል። እንዲሁም ታቦተ ጽዮንም በዓለ ንግሧ የሚውለው በዚህ ወር ነው። የሌሎችም የጻድቃንና የሰማእታት በዓላት ሀገራዊ ታሪካዊ ኹነቶችንም ጨምሮ የያዘ ወር ነው ኅዳር።           እነሆ ዛሬ በእናታችን በቅድስተ ቅዱሳን በንጽሕተ ንጹሐን በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወርኃዊ የበዓለ ልደት መታሰቢያዋ ጀምረነዋል። በድጋሚ እንኳን አደረሳችሁ። እግዚአብሔር አምላካችን ወሩን ባርኮ እንደሰጠን እርሱን እያስደሰትን እናሳልፈውም ዘንድ ጠብቆቱ አይለየን። አሜን🙏

ጥቅምት 27 "በዓለ ስቅለት" ጥቅምት 27 በዚህች ዕለት የአምላካችን የመድኃኔዓለም የስቅለቱ መታሰቢያ ነው። መድኃኒታችን ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና በቸርነቱ ስለኹላችን ድኅነት ሲል ራሱን ወድዶ ፈቅዶ ለሞት አሳልፎ በመስጠት ፍጹም ፍቅሩን አሳይቶናል። በቅዱስ ወንጌልም እርሱም መድኃኒታችን " ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም" ብሎ ነግሮናል። እውነት ነው፣ ራስን ነፍስን ስለጠላት ነፍስ አሳልፎ ከመስጠት በላይ ምን ድንቅ ነገርና ምን ድንቅ ፍቅር አለ? ቸሩ አምላካችንን የአስቆሮቱ ይሁዳ ሊያስይዘው የሊቃነ ካህናቱን አገልጋዮች እየመራ አመጣቸው። እነርሱንም ማንን ትፈልጋላችሁ ሲላቸው የናዝሬቱ ኢየሱስን አሉት፣ እኔ ነኝ ቢላቸው የቸሩን አምላክ ድምጽ ሰምቶ አይደለም መቆም በሕይወት መጽናት የሚቻለው የለምና ወደ ኋላቸው ተስፈንጥረው ወደቁ። ደጋግሞም እንዲህ ኾነ። በኋላ ግን እኔ ነኝ ብሎ በፈቃዱ ይሁዳ ስሞ አሳልፎ ሰጣቸው። ከያዙት በኋላ እያዳፉና እየጎተቱ በሰንሰለት አስረው ወደ ቀያፋና ሐና ግቢ ወሰዱት፣ እስከ ሦስት ሰዓትም አላሳረፉትም ሲያሰቃዩት አድረዋል፣ በራሱም ላይ ሰባ ሦስት ስቊረት ያለው ወደ ሦስት መቶ እሾኾችን የያዘ የእሾህ አክሊል ጎንጉነው ቢያደርጉበት የራስ ቅሉን ቀዶ ገብቶ እስከ ልቡ ዘልቋል። እንደምን ጭንቅ ነው? እንዲህም አድርገው ደግሞ እያፌዙ ርኲስ ምራቃቸውን ይተፉበትና በዘንግም ደጋግመው ይመቱት ነበር። እየተፈራረቁ ያለ ምንም ርኅራኄ ቸሩን አምላክ ሥጋው እየተቆረጠ እስኪወድቅ ድረስ ስድስት ሺህ ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ጽኑዕ ግርፋትን ገርፈውታል። የገረፉበትም ጅራፍ በላዩ ላይ ሥጋን እየጎመደ የሚጥል፣ ሕመሙ አንጀት ሰርሥሮ የሚገባ በስለት የተያያዘበት ነበር። በኋላም አላሳረፉትም እንዲህ አድርገውትም በሊቶስጥራ አደባባይ ያንን ዕርጥብ መስቀል አሸክመው ወደ ቀራንዮ ወሰዱት። እርሱ ግን ይህን ኹሉ ግፍ ሲያደርሱበት አንድም አልተናገረም ነበር። በቀራንዮም በአምስት ጽኑዕ ቅንዋት (ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ እና ሮዳስ) ቸንክረው ዕርቃኑን ሰቀሉት። በዚህች ቀን ድንግል ማርያም ልቧ በሐዘን ተሰበረ መጽናናትንም አልፈለገች ነበር፤ ወዳጁ ቅዱስ ዮሐንስም ፍፁም ለቅሶን አለቀሰ እናቱንም እናት ትሆነው ዘንድ በእግረ መስቀሉ አደራን ተቀበለ። ቅዱሳት አንስት በፍጹም ሀዘንና በዋይታ ዋሉ። በስልጣኑም ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው ለየ። ሰባት ድንቅ የኾኑ ተአምራትንም አድርጎ አምላክ መኾኑን ገለጠ። ይህም ጽኑዕ የኾነ ለሰማይ ለምድር የከበደ ነገር ሲከሰት ፀሐይ አምላኬን ዕርቃኑ እንዴት አያለሁ ብላ ጨለመች። ጨረቃ ደም ኾነች፣ ከዋክብቱም ረገፉ፣ ንዑዳን ክቡራን ንጹሐን መላእክትም ትዕግስቱን እያደነቁ በጽኑዕ ሐዘንና መደነቅ ከቅዱስ ዕፀ መስቀሉ ፊት እንደሻሽ ተነጠፉ። አስራ አንድ ሰዓት በሆነም ጊዜ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ከታላቅ ክብርና ሐዘን ጋር ቅድስት ሥጋውን ከመስቀሉ አውርደው በክብር ገንዘው በአዲስ መቃብር ቀበሩት። በሦስተኛውም ቀን እንደተናገረ ተነሳ። በዛሬዋ ቀን ቤተ ክርስቲያን የመድኃኔለምን የስቅለት በዓል በደማቁ ታከብራለች፤ ይህም የለውጥ በዓል ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን እየሱስ ክርስቶስ ደሙን ያፈሰሰው ስጋውን የቆረሰው መጋቢት 27 ቀን ነው፤ ይህ በዓል ግን በዐቢይ ጾም ስለሚውል በዐቢይ ጾም ሀዘን እንጂ ደስታ ስለሌለና በዓል ማክበር ስለማይፈቀድ፤ ወደ ጥቅምት 27 ተዛውሮ ደስ ብሎን እንድናከብረው ቤተ ክርስቲያን ስርዓት ሰርታልናለች፡፡ ከበዓሉ ረድኤት በረከት ይክፈለን (#በዲያቆን_መላኩ_ይፍሩ)

ከምን ዓይነት ነገር መላቀቅ እንዳለብህ ታዉቃለህ ?? ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ሳልሳዊ ምድራዊ ምኞት ምን ያህል አስከፊ እንደሆነና እንዴት ከዚህ ነገር ነፃ መውጣት እንዳለብን እንዲህ በማለት ይመክሩናል፦ "ወዳጄ ከምድራዊ ምኞትህ ተላቀቅ ከምን አይነት ነገር መራቅ እንዳለብህ ታውቃለህ? ከምድራዊ ፍላጎት ከመሳሰሉት ራቅ ፍፁም የመንፈስ ነፃነት እንዲኖርህ ከፈለክ ከምድራዊ ምኞቶችህ ተላቀቅ። በእርጋታና በግልጽነት ላውጋህ እጅግ አብዝተህ የምትጨነቅባቸው ልብህን የተቆጣጠሩት ታላላቅ ምድራዊ ተስፋዎች አሉህ። እነኚህም ሃሳብህን ሁሉ ይቆጣጠሩታል ብቻህን በምቶንበት ጊዜ በምናብ ይመጡብሃል በምትተኛ ጊዜ ህልምህ ሁሉ ይህ ይሆናል ልትክዳቸው የማትችለው ነገር ግን የምታውቃቸው ምድራዊ አላማዎች አሉህ። ተፈላጊነት እንዲኖርህ ትመኛለህ፣ ስልጣን እንዲኖርህና፣ ኃያል እንድትሆን፣ ዕውቅና እንዲኖርህና ስምህ ከጽንፍ እስከ አጽናፍ እንዲናኝ ትፈልጋለህ። በሀብት፣ በምድራዊ ስልጣን፣ በዕውቀት በማዕረግና በመልክ ዝነኛ የመሆን ተስፋ አለህ ፣ በመኖሪያ ቤት፣ በምግብ፣ በልብስና በሰውነት ደስታን በሚሰጡ ነገሮችም ተስፋ አለህ። ዓለም በአንተ እንጂ አንተ በዓለም እየኖርክ አይደለም። ስለዚህ አንተነትህ በዚህ ምድራዊ ተስፋ የታጠረ ነው። መንፈስህም ከስጋ ፍላጎቶች መራቅን ትመኛለች ሥጋ በመንፈስ ላይ መንፈስ በሥጋ ላይ ይመኛልና። (ገላ.5፥17) እነዚህ ሥጋዊ ተስፋዎችና ፍላጎቶች ስኬታማ ስለማይሆኑ ግራ ትጋባለህ። ይህን በእርግጥ ቅሬታን ያመጣብሃል። እነዚህን ነገሮች ሁሉ ትናፍቃለህ ነገር ግን ናፍቆትህ አያስደስትህም። ስለዚህ ለምኞትህ ሁሉ ማስተካከያ ታበጅለት ይሆናል ምናልባትም ይጠቅሙኛል የምትላቸውን ሰዎች ማግኘት፣ በምኞትህ ዙሪያ የተጻፈ መዛግብት ማገላበጥ ትፈልግ ይሆናል በዚህም ላይ ታች ስትል ምኞትህን ለማሳካት ትታገላለህ እንዲሆን ሌላ ዘዴ ልትፈጥር ትችላለህ ይሁን እንጂ ሳይሳካልህ ቀርቶ በሃሳብና በጥረት ትታክታለህ ከዚያም ትበሳጫለህ። ከዚህ የከፋው ነገር በእነዚህ ምኞቶችና ተስፋዎች ስኬታማ አለመሆን ምክንያት ለከፋ ሕይወት መዳረግህ ነው። እንደምትሰለች አውቃለሁ አዘንኩልህ እስከመቼ ድርስ በምኞት ማዕበል ውስጥ ትኖራለህ? የምትመኘውን ባገኘህ ጊዜ ደስተኛ ትሆናለህ ይህ ደስታ ስለማያረካህ ሌላ አዲስ ደስታን እንድትመኝ ያደርግሃል። ልክ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ "ከዚህ ውሃ የሚጠጣ ሁሉ እንደገና ይጠማል" (ዮሐ.4፥13 ) እንዳለው እርካታ አይኖርህም። ስለዚህ ውድ ወንድሜ ነገሩን በእርጋታ ከአንተ ጋር ለመነጋገር እፈልጋለሁ። "አለሙም ምኞቱም ያልፋል" (1ኛ ዮሐ.2፥17) ታዲያ ይህን ቃል ካወክ ለምን አለማዊ ፍላጎቶችን ለማግኘት ትታክታለህ? አንተ ልክ እንደ እኔ ለመሬት እንግዳ ነህ። ዓለም የሚያልፍበት አንተም የምትጠፋበት ጊዜ ይመጣል ልክ ከእናትህ ማህጸን ራቁትህን እንደመጣህ እንደዚሁ ራቁትህን ትመለሳለህ።(ኢዮ. 1፥21) ዓለምን ከነክብሯ ከነሀብቷና ከነስሟ ለቀሃት እንድትሄድ በመገደድ እንደ ማንኛውም ሰው ወደ መሬት ትወርዳለህ። ከዚያም ከዓለም ያገኘኽውን ደስታ ታወቂነት ወይም ምንም ይሁን ምን ሥጋህን ከሞት ሊከላከልልህ አልያም ሥጋን ከሚበሉት ትል ሊከላከልልህ አይችልም። በፍርድ ቀን ከዓለም ሀብትና ንብረት ውጭ በእግዚአብሔር ፊት ትቆማለህ። መልካም ይሁን ክፉ የሰራኸው ሥራ እንጂ የዓለም ቁሳዊ ነገር አይከተልህም። ስለዚህ ውድ ወንድሜ ምኞትህንና ተስፋህን በዓለም ላይ በማድረግ መታወክህ ለአንተ ጥሩ አይደለም ይህችን ምድር እሾህንና አሜኬላን እንዳበቀለችልህ ትዘነጋለህን!!! ከእኛ በፊት የነበሩና ምድርን ሊረግጧት የማይገባት የቅዳሳን አባቶችና እናቶች አሠራርና ፈለግ ተከተል ቅድስናቸውን ያገኙት ይህችን ዓለም በመውደድ ሳይሆን በመናቅ ነበር ሁኔታዎች ሁሉ ተመቻችተውላቸው ሳለ በዓለም ስላሉ ነገሮች ለማንኛውም ጉጉት አልነበራቸውም ። ውድ ወንድሜ አሁንም ምኞት አሉህ መዝገብህ ባለበት ልብህ ደግሞ በዚያ ይሆናልና (ማቴ.6፥21) የሥጋን ምኞቶችን ስለተቆራኘ መንፈሳዊ ነገሮች በአንተ አመለካከት ዋጋቸውን ያጣሉ ይህ የክብር ጌታ እንደተፈተነው ዓይነት ፈተና ነው። (ማቴ.4፥8-9) አሁን አስተውል እነዚህን ነገሮችን ብትይዝ በጥሩ ምኞት ያላሰርካት ነፍስህን ብታጣ ጥቅሙ ምንድን ነው? ነፍስህ ነጻነትን ትሻለች። ከስጋ ምኞት ተላቀን የመንፈስ ፍሬ የሆኑትን " የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፣ ደስታ፣ ሰላም፣ ትዕግሥት፣ ቸርነት፣ በጎነት፣  እምነት፣ የውሃት፣ ራስን መግዛት ነው።"(ገላ.5፥22) እንዳለው ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ እነዚህን ገንዘብ አድርገን እንድንኖር እግዚአብሔር አምላክ ይርዳን!! (የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ሳልሳዊ "የመንፈስ ነጻነት "ከሚለውና በዲ/ን ደስታ ፍፁም ከተተረጎመው መጽሐፍ ላይ የተወሰደ።

"በጎ ነገር አግኝተህ እንደ ሆነ እግዚአብሔርን አመስግን፤ ያም በጎ ነገር ከአንተ ጋር ጸንቶ ይኖራል፡፡ በጎ ያልሆነ ነገር ደርሶብህ እንደሆነም እግዚአብሔርን አመስግን፤ ያም በጎ ያልሆነ ነገር ወደ በጎ ነገር ይቀየራል፡፡" ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

ጥቅምት 14 የጻድቁ አባታችን አቡነ አረጋዊ በዓለ ንግሥ አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ጥቅምት ዐሥራ አራት በዚች ቀን ከዘጠኙ ቅዱሳን አባቶች አንዱ የሆነው ጻድቁ አቡነ አረጋዊ የተሠወሩበት ቀን ነው አቡነ አረጋዊ በ 480 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ መጡ ሀገራቸው ሮም ነው አባታቸ ይስሐት ይባላል የሮም ንጉሥ ነበር እናታቸው እድና ትባላለች ቀዳሚ ስማቸው ዘሚካኤል ነው ፡፡ ጥበብ መንፈሳዊ ሲማሩ አድገው 14 ዓመት ሲሆናቸው ከአዝማደ ነገሥት  የሆነች ሚስት አጬላቸው ወደ ጽርዕ ኮብልለው ገዳመ ዳውናስ ገቡ አበ ምኔቱ አባ ኩሚስ ፈቃደ እግዚአብሔር መሆኑን አውቀው መዓረገ ምንኩስና ሰጥተዋቸዋል ። ከዘመዶቻቸውም ሰባቱ ዜናቸውን ሰምተው መንፈሳዊ ቅንዓት አነሣሥቷቸው እንደሳቸው ዓለምን ትተው ገዳም ገብተው በምንኩስና ተወስነዋል እነሱም አባ ሊቃኖስ ዘቁስጥንጥንያ ፣ አባ ይምአታ ዘቁስያ ፣ አባ ጽሕማ ዘኣንጾኪያ ፣ አባ ጉባ ዘቂልቅያ ፣ አባ ጰንጠሌዎን ዘሮምና አባ አሌፍ ዘቂሣርያ ናቸው ፡፡ እሳቸውንም መንጋውን እንደሚንከባክብ መልካም እረኛ ወደዚህች ሕኖተ ሕይወት ስለመራኸን ብፁዕ አረጋዊ መባል ይገባሀል ብለዋቸዋል አባ አረጋዊ የተባሉ ከዚህ በኋላ ነው ። ከዚህ በኋላ እናታቸው ንግሥት እድና ዜናቸውን ሰምታ ልትጠይቃቸው መጣች እናትህ ትፈልግሀለች አሏቸው አይሆንም አሉ ግድ አሏቸው ወጥተው እናቴ ስለምን መጣሽ አሏት ልጄ አንተ በሕፃንነትህ የናቅኽ ዓለም ለኔስ ምን ሊረባኝ ብዬ ነው እለቻቸው ዴስ አላቸው መዓረገ ምንኩስና አስጥተው በምኔተ.አንስት አስቀመጧቸው ። ከስባት ዓመት በኋላ ወደሮም ተመልሰው ሲያስተምሩ የሀገራችንን ዜና ሰምተው ለመምጣት መንገድ ጀመሩ ቅዱስ ሚካኤል በክንፉ ተሽክሞ አክሱም አድርሏቸዋል ። ተመልሰው ሄደው ሀገር ይሏቹሁዋል ምድረ አዜብ ሐዋርያ ሳይላክላት በሃይማኖት በምግባር ፀንታ ትኖራለች አሏቸው ስምንቱ ሁሉ ጓዛቸውን ጠቅልለው ወገኖቻቸውን አስከትለው አክሱም ገበ ይም የሆነ አልዓሜዳ በነገሠ በአምስተኛ ዓመት ነበር አባ ገሪማ / ይስሐቅ / እስከዚህ ጊዜ ድረስ በሮም ነግሠው ይኖሩ ነበር ልከውባቸው መንግሥታቸውን ትተው መጥተው ዘጠነኛ ሆነዋል ። ከ12 ዓመት ኋላ በአንድነት መኖሩ ለጽሙና ለብሕትውና የማይመቻቸው ቢሆን አባ አረጋዊ ከመዶቻችን መለየታችን ከሀገራችን መውጣታችን በጽሙና በብሕትውና ልንኖር አይደለምን ብለው ተለያይተን እንኑር አሉ ፡፡ ተለያይተው አባ ሊቃኖስ ደብረ ቆናጽል አባ ጰንጠሌዎን ሁለት ምዕራፍ ያህል ርቀው አባ ይስሐቅ መደራ አባ ጽሕማ ጼዴንያ አባ ይምዓታ ገርዓልታ አባ አፍጼ ይሓ አባ አሌፍ አሕስኣ ገብተው በዓት ሠርትው ተቀምጠዋል አባ አረጋዊም እናታቸው ቅድስት እድናን ደቀመዝ ሙራቸው ማትያስን አስከትለው እግረ መንገዳቸውን እያስተማሩ ሕመማንን እየፈወ ሊሄዱ ደብረ.ዳሞ ደረሱ ፡፡ አምነው ለተከተሏቸው ብዙ ሴቶች በእግረ.ደብር ገዳም ገድመውላቸው እናታቸውን እመ.ምኔት አድርገው ሾመውላቸዋል ከዚህ በኋላ ከእግረ ደብር ሆነው አሁን ይህን ተራራ በምን ልወጣው እችላለሁ እያሉ ሲያወጡ ሲያወርዱ የታዘዘ ዘንዶ መጥቶ ጅራቱን ከመንፈቀ . ደብር አድርጎ « ከዚህች ተራራ ምን አለህ የምትቀምሰው የምትልሰው አታገኝ ዋዕየ ፀሐዩ ቁረ.ሌሊቱም አያስቀምጥህም አላቸው የታዘዝከውን አትፈጽምምን ? ይልቅስ ጅራትህን አውርድና ጎትተህ አውጣኝ አሉት 60 ክንድ በሚያህል ጅራቱ ጠምጥሞ ቅዱስ ሚካኤል ሰይፈ . እሳት ይዞ እየጠበቃቸው ከተራራው ራስ አድርሷቸዋል ። ወዲያውም ሃሌ ሉያ ለአብ ሃሌሉያ ለወልድ ሃሌሉያ ለመንፈስ ቅዱስ ብለው አመስግነዋል ደብረ ሃሌ ሉያ መባሉ ቅሉ ስለዚህ ነው ፡፡ እስከዚህ ጊዜ ድረስ እህል የሚቀምሱት በሰንበተ ክርስቲያን ብቻ ነበር በዚህ ዕለት ግማሽ ኅብስት በልተው ጠገቡ ከዚህ በኋላ ግን ምድራዊ ኅብስት አልተመገበም መላእክት በሰንበተ ክርስቲያን ሰማያዊ ኅብስት ሰማያዊ ወይን እያመጡላቸው ያን ቀድሰው ይቀበሉት ነበር ኋላም ዜና ጽድቃቸውን ሰምተው ከስድስት ሺህ ያላነሱ ደቀመዛሙርት ተሰብስበዋቸዋል ፡፡ ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ሲመላቸው ጌታ በመንፈቀ ሌሊት ተገልጾ ❝ ድካምህን አይቻለሁ ጸሎትህን ሰምቻለሁ ምድራዊ መንግሥትህን ትተህ ስላገለገልከኝ ኅልፈት ሽረት የሌለባት ሰማያዊ መንግሥቴን አወርስሀለሁ ። መታሰቢያህንም ላደረገ በጸሎትህም ለታመነው ሁሉ በመላእክቴ ፊት ባለሟልነትን እሰጠዋለሁ በስምህም የተራበውን ያበላ የተጠማውን ያጠጣ ቤተ ክርስቲያን የሠራ ያሠራውን ዜና ገድልህን የጻፊ ያጻፈውን የሰማ ያሰማውን እስከ 15 ትውልድ ድረስ እምርልሀለሁ ። የእናትህን መቃብር እንደ ሙሴ መቃብር እሠውረዋለሁ አንተንም ሞት አያስደነግጥህም ። ❞ ብሉ ተስፋቸውን ነገራቸው መነኮሳቱን ሰብስበው ❝ ከእንግዲህ በሥጋ አታዩኝም ብለው ነግረዋቸው አበ ምኔት ሾመውላቸው በዚህች በተባረከች ዕለት በጥቅምት 14 ቀን ተሰውረዋል ። በረከታቸው ቃልኪዳናቸው አማልጅነታቸው በሁላችንም ላይ ይደር አሜን

+++ "ለዚህ መች ጸለይን?" +++ በግብጽ ቤተ ክርስቲያን ቤተሰባዊ የሆኑ ችግሮችን ለመቅረፍ እንዲረዳ የተቋቋመ የካህናት (የቀሳውስት) ጉባኤ ነበረ። የቀድሞው የቅብጥ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ ሺኖዳም ይህን ስብስብ እንዲቀላቀሉ ለአባ ሚካኤል ባቀረቡላቸው ጥሪ መሠረት የዚህ ጉባኤ አባል ሆኑ። ታዲያ አንድ ቀን አባ ሚካኤልን ጨምሮ የጉባኤው የበላይ ኃላፊ የሆኑት ጳጳስና ሌሎችም ካህናት የተጣሉ ባልና ሚስትን ሊያስታርቁ ተሰበሰቡ። ይሁን እንጂ የባልና የሚስትየው ጠብ እንዲህ በቀላሉ ሊበርድ የሚችል አልነበረምና ጳጳሱም ሆኑ ቀሳውስቱም ሁለቱን ለማስማማት ብዙ ቢጥሩም ግን አልተሳካላቸውም። በስተመጨረሻም ጳጳሱ ወደ አባ ሚካኤል እየጠቆሙ "አባ ሚካኤል ለምን ዝም ብለው ተቀመጡ? እስኪ እርሶ ይሻላል ብለው የሚያስቡትን ይንገሩን?" አሏቸው። አባ ሚካኤልም "ብፁዕነትዎ፣ እንጸልይበት!" አሉ። ጳጳሱም "ይህን ጉባኤ ከመጀመራችን በፊት እኮ ጸልየናል" ቢሏቸው አባ ሚካኤል "አዎን አባታችን፤ ለዚህ ችግር ግን አልጸለይንም" አሉ። ከዚያ ሁሉም ለጸሎት ተነሡ። በጳጳሱ ፈቃድ በአቡነ ሚካኤል መሪነት ጸሎት አደረጉ። ጸሎቱ እንዳለቀም እነዚያ የተጣሉት ባልና ሚስት ክርክራቸውን ሁሉ ትተው በጉባኤው ፊት በፍቅር ተቃቀፉ። ሰላም አወረዱ። ይህን ጊዜ ከቀሳውስቱ አንዱ "አባታችን ከመጀመሪያ እንዲህ ቢሉን ምን ነበር?! አሳረፉን እኮ" ብለው ጉባኤውን ፈገግ አሰኙት። እኛስ ያልጸለይንባቸው ስንት ችሮች አሉብን? ብዙ ቋጠሮ የሚፈታው ግን በብዙዎች የሚረሳው ትልቁ መፍትሔ፣ ጸሎት!!! (አባ ሚካኤል ኢብራሂም (1899-1975) የግብጽ ቤተ ክርስቲያንን ለበርካታ ዓመታት በትጋት ያገለገሉና እጅግ የሚያስቀና የጸሎት ሕይወት የነበራቸው አባት ናቸው።) ዲያቆን አቤል ካሳሁን

✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞✞✞ ❖ ጥቅምት ፭ (5) ❖ ✞✞✞ እንኩዋን ለጻድቁ "አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ" እና "ቅዱስ ኪራኮስ አረጋዊ" ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞✞✞ +"+ አቡነ ገብረ ሕይወት +"+ =>ጻድቁ የተወለዱት ግብፅ (ንሒሳ አካባቢ) ሲሆን አባታቸው ስምዖን እናታቸው አቅሌስያ ይባላሉ:: አባታችን ገብረ ሕይወት የጻድቃን አለቃ: የቅዱሳን የበላይ:ተጋድሎአቸውና ድንቅ ተአምራቸው እንደ ሰማይ ከዋክብት የበዛ ቅዱስ ሰው ናቸው:: +የጻድቁን ክብር መናገር የሚችል ምን አነደበት ይኖራል? እንደ ምንስ ባለ ብራና ይጻፋል? ዜናቸውንስ ለመስማት የታደለ እንደ ምን ዓይነት ሰው ይሆን? +አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስ ለ562 ዓመታት በዚህች ዓለም ሲኖሩ እህል ያልቀመሱ (ምግባቸው ምስጋና ነውና): ልብስ ያልለበሱ (ጠጉር አካላቸውን ይሸፍን ነበርና): ሐዋርያዊ ሆነው ከግብፅ እስከ ኢትዮዽያ ብዙ ነፍሳትን ያዳኑ አባት: ሃገራችንን አስምረው: አስራት እንድትሆናቸውም ተቀብለው ምድረ ከብድ አካባቢ አርፈዋል:: +ጻድቁ ገብረ መንፈስ ቅዱስም: ገብረ ሕይወትም ይባላሉ:: በ562 ዓመታት ሕይወታቸው እንደ ሐዋርያት ከምድረ ግብጸ እስከ ኢትዮዽያ ወንጌልን ሰብከዋል:: በዚህም በሚሊየን (አእላፍ) ለሚቆጠሩ ነፍሳት የድኅነት ምክንያት ሆነዋል:: +ጻድቁ እንደ ሰማዕታትም ከከሃዲ ሰዎች ብዙ መከራን ተቀብለዋል:: እንደ ባሕታውያን ለብዙ መቶ ዓመታት ሰው ሳያዩ ቆይተዋል:: ለየት የሚለው ግን የጽድቅ ሕይወታቸው ነው:: ከእልፍ አዕላፍ አጋንንት ጋር ተዋግተው ድል ማድረግ ችለዋልና:: +የንሒሳው ኮከብ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ለኢትዮዽያ ልዩ ፍቀር አላቸው:: ስለ ሃገሪቱና ሕዝቧ ፍቅር ሲሉ ለ100 ዓመታት በደብረ ዝቁዋላ መከራን ተቀብለዋል:: ምሕረትን ሲለምኑ ሥጋቸው አልቆ በአጥንታቸው ቁመው ነበርና ሃገራችን አሥራት ሆና ተሰጠቻቸው:: +ስለዚህም ነው በሃገሪቱ ውስጥ ከ2,000 በላይ የጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳማትና አድባራት ዛሬም ድረስ ያሉት:: በ8ኛው ክ/ዘመን አካባቢ የተወለዱት አባታችን ያረፉት በ14ኛው መቶ ክ/ዘመን አካባቢ ነው:: ፍጥረታትን ሁሉ አዘው መጋቢት 5 ቀን ሲያርፉ ግሩማን መላእክት ገንዘው አካላቸውን ሠውረዋል:: +ሥላሴን የተሸከመ አካላቸው በጐልጐታ ተቀብሯል የሚሉም አሉ:: "ሰላም ለመቃብሪከ ዘኢተከሥተ ለባዕድ: ከመ መቃብሩ ለሙሴ ወልደ ዮካብድ: ዜና መቃብሪከሰ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጸማድ: ቦ ዘይቤ በኢየሩሳሌም አጸድ: ወቦ ዘይቤ ኀለወ በከብድ::" እንዲል:: +የጻድቁ በዓል ጥቅምት 5 ቀን የሚከበረው ብዙ ጊዜ መጋቢት 5 ዐቢይ ጾም ውስጥ ስለሚውል ተውላጥ (ቅያሪ) ሆኖ ነው:: +"+ ቅዱስ ኪራኮስ አረጋዊ +"+ =>ይህ ቅዱስ አባት ስም አጠራሩ የከበረ: ሽምግልናውም ያማረ ነው:: ብዙዎቻችን የምናውቀው በበዓለ መስቀል ስሙ ተደጋግሞ ሲጠራ ነው:: ግን ይህ ታላቅ ሰው ለቅድስት እሌኒ.መካነ መስቀሉን አሳያት ከሚል አረፍተ ነገር የዘለለ ታሪኩ ሲነገርለት ብዙ ጊዜ አንሰማምና እስኪ በዕለተ ዕረፍቱ ስለ ቅዱሱ ጥቂት እንበል:: +ቅዱስ ኪራኮስ የተወለደው በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን ሲሆን እናቱ ቅድስት ሐና ትባላለች:: በእጅጉ የተባረከች ሴት ናት:: ምንም በነገዳቸው አይሁድ ቢሆኑም የዘመኑ የአይሁድ ክፋት አልገዛቸውም:: የተባረከች እናቱ ታሪክ እያስጠናች ከማሳደጉዋ ባለፈ አስቀድማ ኦሪቱን: ነቢያቱን እንዲያውቅ አደረገች:: +አስከትላም ሕገ ክርስትናን እንዲረዳ አደረገችው:: የታሪክና የመጻሕፍት ምሑሩ ቅዱስ ኪራኮስ ከእናቱ ጋር ሆኖ እግዚአብሔርን እያገለገለ: ክርስቶስን እያመለከ ቆየ:: በዚህ ጊዜ ግን እድሜው እየገፋ ነበር:: +ሠለስቱ ምዕት (318ቱ ሊቃውንት) ጉባኤያቸውን ከፈጸሙ በሁዋላ ቅድስት እሌኒም መስቀሉን ፍለጋ ስትወጣ ትልቁ ፈተናዋ የተቀበረበትን ቦታ ማወቅ አለመቻሏ ነበር:: እንዲያውም አማራጭ ስታጣ በአካባቢው የነበሩ አይሁድን ምሥጢር እንዲያወጡ ቀጥታቸው ነበር:: በሁዋላ ግን ኪራኮስ ስለሚባል ደግ ታሪክ አዋቂ ሰው ሰምታ ተገናኙ:: +ቅዱስ ኪራኮስም አባቶቹ አይሁድ ናቸውና አካባቢውን ያውቀው ነበር:: ችግሩ ቆሻሻው ተራራ በመሆኑ ከ3ቱ የትኛው እንደ ሆነ አለመታወቁ ነበር:: ቅዱሱ ግን ለዚህም መፍትሔ ነበረውና "ደመራ ደምረሽ: በእሳት አቃጥለሽ: እጣን ጨምሪበትና ይገለጥልሻል" አላት:: +ቅድስት እሌኒም የተባለችውን በትክክል ፈጽማ የመድኅን ክርስቶስን ቅዱስ ዕጸ መስቀል አገኘች:: ቅድስት እሌኒ ወደ ሃገሯ ከተመለሰች በሁዋላም ቅዱስ ኪራኮስ በኢየሩሳሌም አካባቢ ዻዻስ ሆኖ ተሾመ:: +አረጋዊው ቅዱስ የሚገርም እረኛ ነውና የባዘኑትን ሲፈልግ: በቤቱ ያሉትንም ሲያጸና ብዙ ደከመ:: በቅርቡ ያሉትን በአፉ: የራቁትን ደግሞ በጦማር (በመልእክት) አስተማረ:: በወቅቱ በአካባቢው ኤልያኖስ የሚሉት ከሃዲ ንጉሥ ነበርና በቅዱስ ኪራኮስ ላይ ተቆጣ:: +ወደ እርሱ አስጠርቶ በአደባባይ: ቅዱስ ቃሉን ይጽፍበት የነበረው ቀኝ እጁን አስቆረጠው:: ቅዱስ ኪራኮስ ግን እጁ መሬት ላይ ወድቃ: ደሙ እየተንጠፈጠፈ ተናገረ:- "አንተ ልብ የሌለህ ንጉሥ! እጄን ቆርጠህ ከክርስቶስ ፍቅር ልትለየኝ አትችልም" አለው:: +በዚህ የተበሳጨ ንጉሡ እሳት አስነድዶ: አልጋውን አግሎ ቅዱሱን ጠበሰው:: ኪራኮስ ግን በእሳቱ ላይ ሳለ ወደ እሥራኤል ፈጣሪ በእብራይስጥኛ ጸለየ:: በማግስቱ እናቱን ቅድስት ሐናን አምጥተው የነደደ እሳት ውስጥ ጣሏት:: +ለ3 ሰዓት ያህል በእሳት ውስጥ ስትጸልይ ቆይታ በጦር ወግተው ገደሏት:: ቅዱስ ኪራኮስንም ለአራዊት ሰጡት:: አራዊቱ ሰገዱለት:: ዓይነት ስቃዮችም ፈተኑት: ግን እንቢ አላቸው:: በመጨረሻው በዚህ ቀን ገድለውት የክብርን አክሊል ተቀዳጅቷል:: =>አምላከ ቅዱሳን በእነርሱ ላይ የበዛች ፍቅሩን ለእኛም ያድለን:: ፍሬ ትሩፋት: ፍሬ ክብር እንድናፈራም ይርዳን:: ክብራቸውንም አያጉድልብን:: =>ጥቅምት 5 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት= 1.አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጻድቅ 2.ቅዱስ ኪራኮስ አረጋዊ (ዻዻስ ወሰማዕት) 3.ቅድስት ሐና ሰማዕት (እናቱ) 4.ቅዱስ ያዕቆብ ወልደ እልፍዮስ (ከ12ቱ ሐዋርያት) 5.አባ ዻውሎስ ሰማዕት (አርዮሳውያን አንቀው የገደሉት አባት) =>ወርሐዊ በዓላት 1.ቅዱስ ዼጥሮስ ሊቀ ሐዋርያት 2.ቅዱስ ዻውሎስ ብርሃነ ዓለም 3.ቅዱስ ዮሐኒ ኢትዮዽያዊ 4.ቅዱስ አሞኒ ዘናሒሶ 5.ቅድስት አውጋንያ (ሰማዕትና ጻድቅ) =>+"+ ነገር ግን ዓለም ለእኔ የተሰቀለበት: እኔም ለዓለም የተሰቀልሁበት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ.መስቀል በቀር ሌላ ትምክህት ከእኔ ይራቅ:: በክርስቶስ ኢየሱስ አዲስ ፍጥረት መሆን ይጠቅማል እንጂ መገረዝ ቢሆን ወይም አለመገረዝ አይጠቅምምና:: +"+ (ገላ. 6:14) <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>

"በጎ ነገር አግኝተህ እንደ ሆነ እግዚአብሔርን አመስግን፤ ያም በጎ ነገር ከአንተ ጋር ጸንቶ ይኖራል፡፡ በጎ ያልሆነ ነገር ደርሶብህ እንደሆነም እግዚአብሔርን አመስግን፤ ያም በጎ ያልሆነ ነገር ወደ በጎ ነገር ይቀየራል፡፡" ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

የክርስቶስን አካል ልታክብሩት ትወዳላችሁ? መልሳችሁ አዎ ከሆነ ራቁቱን ሆኖ እያያችሁት አትልፉት፤ በየመንገዱ ራቁቱን ሆኖ በብርድ እየተሰቃየ አለና። ራቁቱን ሆኖ በብርድ እየተሰቃየ ልፋችሁት መጥታችሁ በዚህ በቤተ መቅደስ በብርና በወርቅ ላስጊጥህ አትበሉት። ወንድምህ በረሀብ እየተሰቃየና እየሞተ ቅዱስ ደሙ የሚቀዳበት ፅዋ በወርቅ ቢለበጥና ቢንቆጠቆጥ ጥቅሙ ምን ላይ ነው? አስቀድመህ የወንድምህን ረሀብ በማጥገብና ጥሙን በማርካት ጀምር፣ ከዚህ በኋላ በገንዘብ ቤተ መቅደሱንና ንዋያተ ቅድሳትን እንዲህ ማስጌጥ ትችላለህ።" (ከቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱና ትምህርቱ)

ባለትዳሮች ሆይ፦ ቤታችሁ (ትዳራችሁ) እንደ ማሠልጠኛ ማዕከል አድርጉት ምግባርን (ለምሳሌ ፍቅርን፣ አለመቈጣትን፣ አለመቅናትን፣ አለመማልን፣ ወዘተ) የምትሠለጥኑበት ማዕከል! እዚያ [ተመርቃችሁ ከማትወጡበት ማዕከል በየጊዜው] በደንብ ስትሠለጥኑም፥ በውጭ (ለምሳሌ በሥራ ቦታ) የሚያጋጥማችሁን ፈተና በጥበብ በብልሐት ማለፍ ይቻላችኋል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

ብዙኃን ማርያም ክፍል ሁለት ዐፄ ዳዊት ስናር (ሱዳን) ደርሰው ከመልእክተኞቹ ጋር ተገናኝተው መስቀሉን በክብር አጅበው ወደ መካከል ኢትዮጵያ ለማስገባት ሲነሡም ከበቅሏቸው ወድቀው ጥቅምት ፱ ቀን ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፤ በዚህም ሠራዊታቸው ተደናግጠው የጌታችንን መስቀል እዚያው ትተው የዐፄ ዳዊትን አስከሬን ይዘው ተመለሱ፡፡ መስቀሉ በስናር ከቆየ በኋላ የዐፄ ዳዊት ልጅ ዘርዐ ያዕቆብ ሲነግሡ ወደ መሃል ኢትዮጵያ አምጥተው ቤተ ክርስቲያን አሠርተው ለማስቀመጥ ቢያስቡም ምቹ ቦታ ግን ሊያገኙ አልቻሉም ነበር፡፡ ንጉሡና ሠራዊታቸው ምቹ ቦታ ሲፈልጉ መስቀሉን በኤረር ተራራ፣ በደብረ ብርሃን፣ በመናገሻ ማርያም ዓምባ፣ በእንጦጦ ጋራ ብዙ ጊዜ አስቀምጠውት ቆይተዋል፡፡ መስቀሉ በእንጦጦ ጋራ ሳለ እግዚአብሔር አምላክ ‹‹አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል፤ መስቀሌን በመስቀለኛ ተራራ ላይ አስቀምጥ›› የሚል ቃል ለንጉሡ በራእይ ነገራቸው፡፡ መስቀሉን ወደ ወሎ ሀገረ ስብከት እንዲወስዱትም አዘዛቸው፡፡ ንጉሡና ሠራዊታቸው በእግዚአብሔር መሪነት መስቀሉን ይዘው ወሎ ሲደርሱም ጌታችን ወደ አምባሰል እያመለከተ ‹‹አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል፤ መስቀሌን በመስቀለኛ ተራራ ላይ አስቀምጥ›› ይላቸው ነበር፤ ንጉሡ መስቀሉን ይዘው ወደ ቦታው ሲያመሩ መስቀለኛው የግሸን ተራራን አገኙ፤ በዚያም ቤተ ክርስቲያን አሠርተው በ፲፬፻፵፮ (1446) ዓ.ም የጌታችንን መስቀል በክብር አስቀምጠውታል፡፡ ከዚህ በኋላ ንጉሡ ‹‹መካከሏ ገነት፤ ዳሯ እሳት ይኹን! የበረረ ወፍ፣ የሠገረ ቆቅ አይታደንባት! በድንገት ሰው የገደለ፣ ቋንጃ የቈረጠ ወንጀለኛ አይያዝባት!›› ብለው ዐዋጅ ነግረዋል፡፡ የእመቤታችን ጽላትም አብሮ በግሸን ደብረ ከርቤ እንዲቀመጥ አድርገዋል፡፡ ስለዚህም መስከረም ፳፩ ቀን በየዓመቱ በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል፡፡ ኀጢአታቸውን ለካህን ተናዘው፣ ንስሐ ገብተው በዚህ ዕለት ወደ ግሸን ደብረ ከርቤ በመሔድ የሚጸልዩና የሚማጸኑ ምእመናን ኹሉ እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደሚያገኙም ጤፉት በተባለችው መጽሐፍ ተጠቅሷል፡፡

ብዙኃን ማርያም በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው ክፍል አንድ በቤተ ክርስቲያናችን ከሚዘከሩ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ክብረ በዓላት መካከል መስከረም ፳፩ ቀን የሚውለው በዓል ‹‹ብዙኃን ማርያም›› በመባል ይታወቃል፡፡ በዓሉ በሁለት ዐበይት ምክንያቶች ይከበራል፤ የመጀመሪያው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሃይማኖታዊ ውሳኔ ለማዘጋጀት ከሩቅም ከቅርብም የተሰባበሰቡት ቀን፤ ሁለተኛው ደግሞ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ዕፀ መስቀል በግሸን ደብረ ከርቤ የተቀመጠበት ዕለት መኾኑ ነው፡፡ ሁለቱንም ታሪኮች ከዚህ ቀጥለን እንመለከታቸዋለን፤ በ፫፻፳፭ ዓ.ም አርዮስ የሚባል መናፍቅ የእግዚአብሔር ወልድን የባሕርይ አምላክነት አልቀበልም በሚል ክህደት እርሱ ተሰናክሎ ለሌሎችም መሰናክል ኾነ፡፡ ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት አርዮስ ክህደቱን እንዲተው ቢመክሩትም ሊመለስ አልቻለም፡፡ ይህ የአርዮስ ክህደትም በሊቃውንቱ መካከል መለያየትን ፈጥሯል፡፡ ጊዜው ታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ‹‹አብያተ ጣዖታት ይትአጸዋ አብያተ ክርስቲያናት ይትረኀዋ፤ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ! አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ!›› የሚል ዐዋጅ የነገረበት ወቅት ነበርና ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ በአርዮስ ክህደት ምክንያት በኒቅያ የሃይማኖት ጉባኤ እንዲካሔድ በየአገሩ ላሉ ሊቃውንት መልእክት አስተላለፈ፡፡ በዚህም መሠረት ከሚያዝያ ፳፩ ቀን ጀምሮ እስከ መስከረም ፳፩ ቀን ድረስ ፳፫፻፵፰ (ሁለት ሺሕ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንት) ሊቃውንት በኒቅያ ተሰበሰቡ፡፡ ኒቅያ ለዚህ ጉባኤ የተመረጠችበት ምክንያትም ጳጳሱን ከማኅበረ ካህናቱ፤ ንጉሡን ከሠራዊቱ ጋር አጠቃላ ለመያዝ የምትችል ሰፊና ምቹ ቦታ ከመኾኗ ባሻገር ለኹሉም አማካይ ሥፍራ ስለ ነበረች ነው፡፡ በጉባኤው ከተሰበሰቡ ሊቃውንት መካከልም እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ሙታንን ያስነሡ፣ ለምጽ ያነጹ፣ አንካሳ ያረቱ፣ የዕውራንን ዓይን ያበሩ ድውያንን የፈወሱ፣ ሌላም ልዩ ልዩ ተአምር ያደረጉ፤ እንደዚሁም ስለ ርትዕት ሃይማኖታቸው በመጋደል ዓይናቸው የፈረጠ፣ እጃቸው የተቈረጠ ይገኙበታል፡፡ ሊቃውንቱ ሱባዔ ይዘው በጸሎት ከቆዩ በኋላ ኅዳር ፱ ቀን በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሊቀ መንበርነት፣ በእለእስክንድሮስ አፈ ጉባኤነት ጉባኤው ተጀመረ፡፡ ንጉሡ ሊቃውንቱን ‹‹ስማችሁን፣ አገራችሁንና ሃይማኖታችሁን ጽፋችሁ ስጡኝ›› ባላቸው ጊዜም ከ፳፫፻፵፰ቱ መካከል ፫፻፲፰ (ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ) ሊቃውንት ሃይማኖታቸውን ሲገልጹ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾነው ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ፤ ወልድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በመለኮት፣ በሥልጣን፣ በፈቃድ፣ በህልውና አንድ ነው›› ብለው ጽፈው ሰጡት፡፡ ንጉሡም ‹‹ሃይማኖት እንደ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት ይኹን›› ብሎ ዐዋጅ አስነግሯል፡፡ እነዚህ ሊቃውንት በኦሪት ዘፍጥረት የተጠቀሱት ፫፻፲፰ቱ የአብርሃም ብላቴኖች ምሳሌዎች ናቸው /ዘፍ.፲፬፥፲፬/፡፡ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት በጉባኤው አርዮስን አውግዘው በመለየት ‹‹ነአምን በአሐዱ አምላክ፤ በአንድ አምላክ እናምናለን›› የሚለውን የሃይማኖት ጸሎት (የሃይማኖት መሠረት) እና ሌሎችንም የሃይማኖት ውሳኔዎችን ደንግገዋል፡፡ ሊቃውንቱ ጉባኤውን ያካሔዱት ኅዳር ፱ ቀን ይኹን እንጂ በአንድነት የተሰባሰቡት መስከረም ፳፩ ቀን ስለ ነበረ ይህ ዕለት ‹‹ብዙኃን ማርያም›› እየተባለ ይጠራል፡፡ ብዙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ለሃይማኖታዊ ጉባኤ የተሳባሰቡበት ዕለት ነውና፡፡ በሌላ በኩል መስከረም ፳፩ ቀን የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በአምባሰል ተራራ በግሸን ደብረ ከርቤ የገባበትና በዓሉ የከበረበት ዕለት ነው፡፡ ታሪኩም በአጭሩ የሚከተለው ነው፤ ዐፄ ዳዊት መንፈሳዊና ደግ ንጉሥ ነበሩ፡፡ በዘመናቸው በኢትዮጵያ ቸነፈር ተከሥቶ ሕዝቡ ስለ ተሰቃየባቸው እጅግ አዘኑ፤ በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ቢያመለክቱም ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላኩ ባሕታዊ መጥተው ‹‹የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል አስመጥተህ በአገርህ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አሠርተህ ብታስቀምጥ ረሃቡ፣ ቸነፈሩ ኹሉ ይታገሥልሃል›› አሏቸው፡፡ ዐፄ ዳዊትም ከብዙ ገጸ በረከት (ስጦታ) ጋር ‹‹የጌታችንን መስቀል ላኩልኝ›› የሚል መልእክት አስይዘው መልእክተኞችን ወደ ኢየሩሳሌም ሰደዱ፡፡ መልእክተኞቹም በታዘዙት መሠረት መስቀሉን ይዘው መምጣታቸውን ዐፄ ዳዊት ሲሰሙ ‹‹ክተት ሠራዊት ምታ ነጋሪት›› ብለው መስቀሉን ለመቀበል ጉዞ ጀመሩ፡፡

በጸሎት ኃይል የሚያምን አንድ ጽኑዕ ክርስቲያን ነበር፡፡ ይህም ክርስቲያን ጥሪት የሌለው ደሃ፣ የሚበላ የሚቸግረው ረሃብተኛ፣ ልብሱ በላዩ ላይ አልቆ የታረዘ ምስኪን ነው፡፡ ከእለታት አንድ ቀን በጸሎት ሕይወቱ የነበረውን ትጋት በቅርበት ያውቅ የነበረው አንድ ወዳጁ እየተቆጣ 'ቢያንስ ለረሃብህ ማስታገሻ ቁራሽ ዳቦ እንኳን ማሰጠት ካልቻለ የአንተ ጸሎት ፋይዳው ምንድር ነው? ይቅርብህ በቃ! ፈጣሪህ አይሰማህም ማለት ነው' ሲል ተስፋ በሚያስቆርጥ ቃል ተናገረው፡፡ ያም ምስኪን ክርስቲያን እንዲህ ሲል መለሰለት፦ 'እግዚአብሔርማ አልረሳኝም። ለአንዱ ሰው ከዕለት እንጀራው የበለጠ አትርፎ በመስጠት ለእኔ እንዲያካፍለኝ መልእክተኛ አድርጎት ነበር፡፡ ነገር ግን ይህን አደራ የተቀበለው ሰው ዘነጋኝ፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ሳይሆን አድራሹ ሰው ረስቶኛል!' መጻሕፍት እንደሚያስተምሩን "የዕለት እንጀራችንን ስጠን" የሚለው ጸሎት ለመነኮሳት ሲሆን "ለዕለት"፣ በዓለም ለሚኖሩ ሰዎች ሲሆን ደግሞ "ለዓመት" የሚሆን እንጀራ ስጠን ማለት ነው። ታዲያ ለምን አንዳንዶች ከዓመት የሚተርፍ ብዙ እንጀራ ሲያገኙ፣ ሌሎች ደግሞ ለዕለት እንኳን የሚሆን ቁራሽ ያጣሉ ? መቼም 'ለሰው ፊት የማያዳላ' እግዚአብሔር "አድልዎ ቢኖርበት ነው" ብለን የድፍረት ቃል በእርሱ ላይ አንናገርም። (ሐዋ 10፥34) ይህ የሆነው እንደ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ትምህርት አትርፈው ያገኙ ሰዎች ምንም የሌላቸውን እንዲረዱ እና መግቦት የባሕርይው የሆነውን አምላካቸውን በጸጋ እንዲመስሉት ነው። በዚሁም ላይ በፈጠራቸው ሰዎች መካከል ያለውን የመተዛዘንና የፍቅር ትስስር የበለጠ ለማጠናከር ነው፡፡ 'የዕለት እንጀራችንን ስጠን ለዛሬ' ብለን የለመንነው አምላክ ከዓመት እንጀራችን በላይ አትርፎ የሚሰጠን፣ የሚበቃንን ያህል ተመግበን በቀረው ለሌሎች አድራሽ መልእክተኞች እንድንሆን ነው። ስለዚህ ይህን የተጣለብንን አምላካዊ አደራ ባለመወጣት ድሆችን አንበድል፤ ተማርረው ከፈጣሪያቸውም ጋር እንዲጣሉ አናድርጋቸው። (Deacon Abel Kassahun Mekuria)

ብዙ ሰው "ያሰብኹት ሁሉ ምንም ሊሳካልኝ አልቻለም" እያለ ያጉረመርማል፤ "እግዚአብሔርማ እኔን ሳይተወኝ አልቀረም!" እያለ ፈጣሪውን ያማርራል። "ይሰጠኛል" ሳይሆን "አገኘዋለሁ" ብሎ ይጀምርና ሳይሆን ሲቀር በእጁ የነበረውን የነጠቀው ያህል አምላኩ ላይ ያለቅሳል። ስታቅድ ያላስታወስከውን አምላክ ያቀድከው ሲፈርስ ስሙን እየጠራህ ስለምን ትወቅሰዋለህ? በሕይወትህ መቼ ቦታ ሰጠኸው? እንደ ፈቃዴ ካልሆነ አልህ እንጂ መቼ "እንደ ፈቃድህ ይሁን" ብለህ ጸለይህ? ባላማከርከው ለምን ተከሳሽ ታደርገዋለህ? ልሥራ ብለህ በተነሣህበትም ቀን እንዲሁ በግዴለሽነት ስሙን ጠርተህ እንደ ሆነም ራስህን መርምር? በትክክል ጸልየህና በመንገድህ ሁሉ ይመራህ ዘንድ ፈቅደህ ከጀመርህ ግን ግድ የለም እረኛህን እመነው። አንተ እንደ ሎጥ ከመረጥኸው እና ለጊዜው የገነት አምሳል ሆኖ ከሚታይህ ነገር ግን እግዚአብሔር ከማይከብርበት ከለምለሙ ሰዶምና ገሞራ ይልቅ፣ አሁን ብዙም ለአይን የማይስበው በኋላ ግን ወተትና ማር የሚያፈሰው ለልጅ ልጆችህም ርስት የሚሆነው እግዚአብሔር የሚሰጥህ ከነአን ይሻልሃል።  (Deacon Abel Kassahun Mekuria

+ ዘኬዎስ አጭር ባይሆን + ዘኬዎስ በማጠሩ ምክንያት በኢያሪኮ እያለፈ ያለውን ክርስቶስን ለማየት ተቸገረ:: ሕዝቡ ብዙ ነውና የቆሙት ሁሉ ጌታን ከማየት ከለሉት:: የሾላ ዛፍ ላይ ወጥቶ ጌታን ለማየት ሲሞክር ጌታ አሻቅቦ አየው:: እሱ ዛፍ ላይ ጌታን ሊያይ እንጂ ሊታይ አልወጣም:: ጌታ ሊታዩ ከሚሞክሩ ይልቅ ሊያዩት የሚሹትን ይወዳልና ዘኬዎስን ጠራው:: ከምድር ቆመን ዓይናችንን አንጋጥጠን ማረን የምንለው ጌታ ዘኬዎስን ከምድር ሆኖ ወደ ላይ እያየ ና ልማርህ አለው:: "ዛሬ በቤትህ እውል ዘንድ ይገባኛል" አለው:: ጌታ ወደ ቤቱ ገባ:: ለዘኬዎስ ቤት መዳን ሆነለት:: ዘኬዎስ አጭር ባይሆን ኖሮ ከሰዎች ጋር እየተጋፋ ጌታን ያይ ይሆናል እንጂ በጌታው ዓይን ለመታየት የሚያበቃ ትጋት አያሳይም ነበር:: ምናልባትም ሰዎችን ገለል በሉ እያለ በኩራት ሲጋፋ ከአንዱ ጋር ሲጣላ ሊቆይ ይችል ነበር:: ዘኬዎስ አጭር ባይሆን ከዛፍ ላይ አይወጣም ነበር::  ዘኬዎስ አጭር ባይሆን የሠራዊት አምላክ ወደ ቤቱ አይገባም ነበር:: በኪሩቤል ላይ የሚቀመጠው ንጉሥ በቤቱ ወንበሮች ላይ የተቀመጠው ዘኬዎስ በማጠሩ ምክንያት ነው:: የዘኬዎስ ነፍስ የዳነው በቁመቱ ማጠር ነበር:: እግዚአብሔር የመዳኑን ቀን የቆረጠለት ቁመቱን ሲያሳንሰው ነበር:: በምድር በመጽሐፍ ቅዱስ በሰማይ በሕይወት መዝገብ ስሙ የተጻፈው ዘኬዎስ አጭር በመሆኑ ነው:: ስለ ቁመት የማወራ እንዳይመስልህ:: እግዚአብሔር ለነፍሳችን መዳን የሚያሳጥርብን ብዙ ነገር አለ:: እንደ ዘኬዎስ ቁመትህ አጭር ባይሆን የሚያጥርህ ነገር ግን አይጠፋም:: ይሄ ጎደለኝ የምትለው ከሰዎች አነስኩበት የምትለው ነገር አንዳች ነገር የለም? እሱን ማለቴ ነው:: ይሄ ይጎድለኛል ከሰው አንሳለሁ እያልክ አትማረር:: እጥረትህ መክበሪያህ ነው:: ጉድለትህም መዳኛህ ነው:: እግዚአብሔር ያጎደለብህ የመሰለህ ነገር ወደ ዛፍ እንድትወጣ ምክንያትህ ይሁን:: በጉድለትህ እንደ ዘኬዎስ ከፍ በልበት:: ያኔ ሰዎች አንተን አንጋጠው ከማየት ውጪ አማራጭ አይኖራቸውም:: ፈጣሪ በፍቅሩ ይይህ እንጂ ሰዎች ወዳንተ ያዘነብላሉ::  በቤትህ መዳን ይሆንልሃል:: ከዚያም ስላጠረህ ስለጎደለህ ነገር ፈጣሪህን ስታመሰግነው ትኖራለህ:: እመነኝ አንዳንድ ጉድለቶች እድሎች ናቸው:: ዘኬዎስ አጭር ባይሆን ይሄኔ በሾላው ዛፍ ጥርሱን እየፋቀ ይቀር ነበር:: ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ ግንቦት 23 2014 ዓ.ም. አዲስ አበባ

እጅህ ላይ ባለው ነገር ከታመንህ እግዚአብሔር አምላክ በእጁ ውስጥ ያለውን ነገር ይሰጥሃል። በውስጥህ ያለውን አቅም መጠቅም ከቻልህ እግዚአብሔር የአንተ ያልሆነ ተጨማሪ አቅም ይሰጥሃል። ከእግረኞች ጋር ሳትደክም እኩል መራመድና መቅደም ከቻልህ እግዚአብሔር ፈረስን ለውድድር ይሰጥሃል። ኤር. 12፥5 የሚታዩ ኃጢአቶችን ለመዋጋት ታምነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር የተሸሸጉና የማይታዩ ኃጢአቶችን ድል እንድትነሣ ይሾምሃል። በሕፃንነትህ በልጅነትህ ለእግዚአብሔር የታመንህ ሆነህ ከተገኘህ እርሱ በወጣትነትህ በምታደርገው ውጊያ ውስጥ ታማኝነትን ያድልሃል። ልያን ለመቀበል ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር ራሔልን ሚስት አድርገህ ታገባት ዘንድ ይሰጥሃል። ዘፍ. 29፥27 በሲና ምድረ በዳ ለመቀመጥ ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር አምላክ የተስፋይቱን ምድር ከንዓንን ያወርስሃል። በዚህ በተወሰነና አጭር ሕይወት ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር መጨረሻ የሌለውን ዘላለማዊ ሕይወት ያድልሃል። ትልቁ ቁም ነገር በእጅህ ውስጥ የገባው ነገር ትንሽም ይሁን ጥቂት በእርሱ መታመን መቻልህ ነው። ስለሆነም ባለህ አንድ መክሊት ታምነህ ስትገኝ እግዚአብሔር አምስት መክሊቶችን በአደራ ይሰጥሃል። አንተ በሚታዩት ነገሮች ላይ ታማኝ ሆነህ ስትገኝ እርሱ በማይታዩት ነገሮች ላይ ይሾምሃል።በመሆኑም ዓይን ያላየችውን ጆሮ ያልሰማውን በሰው ልብ ያልታሰበውን መንግሥቱን ያወርስሃል። 1ኛ ቆሮ 2፥9 (#አቡነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ - #መንፈሳዊው_መንገድ መጽሐፍ #አያሌው_ዘኢየሱስ እንደተረጎመው።)

+ ከአንተ ባላውቅም ...+ በገነተ አበው (The Paradise of Fathers) መጽሐፍ ላይ ይህ ታሪክ ተጽፎአል:: አንድ መነኩሴ በበአቱ ቁጭ ብሎ መጽሐፍ ቅዱስን ሲያነብ አንድ ቃል ሊገባው አልቻለም:: ለመረዳት በጣም ሲያስቸግረው "ይኼን ቃልስ እንዲገልጽልኝ ወደ እግዚአብሔር መጸለይ አለብኝ" ብሎ ወሰነ:: ነቢያቱ ያደርጉት እንደነበረውም እግዚአብሔር የቃሉን ፍቺ እስኪገልጽለት ድረስ መጾምና መጸለይ ጀመረ:: ነገር ግን ለሰባ ሳምንታት ያህል እየጾመ ቢጠባበቅም ምንም ነገር ሊገለጽለት አልቻለም:: በየሳምንቱ መጨረሻ ቃሉን ደግሞ ሲያነበውም የበለጠ እየተወሳሰበበት ሔደ እንጂ ጨርሶ ሊገባው አልቻለም:: በመጨረሻም ተስፋ ቆረጠ:: ስለዚህ ሌላ መነኩሴ ጋር ሔዶ ስለዚህ ቃል ትርጉም ሊጠይቀው ወሰነ:: በአቱን ዘግቶ መንገድ ሊጀምር ሲዞር ግን የእግዚአብሔር መልአክ በፊቱ ቆሞ ታየው:: "አይዞህ አትፍራ የፈለግኸውን የቃሉን ትርጉም ልገልጽልህ ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኬያለሁ" አለው:: መነኩሴው ግራ ገባው "የጌታ መልአክ ሆይ ሰባ ሳምንት ሙሉ እየጾምሁ እንዲገልጥልኝ ስለምን ቆይቼ ምንም መልስ አላገኘሁም:: አሁን ተስፋ ስቆርጥ እግዚአብሔር ስለምን መለሰልኝ?" አለ በፍርሃት ውስጥ ሆኖ "እግዚአብሔር ሰባ ሳምንታት ከጾምኸው ጾም ይልቅ ወንድምህን ለመጠየቅ በመሔድ ያሳየኸውን ትሕትና ተቀብሎታል" አለው:: አላዋቂ መስሎ መታየትን ያህል የምንፈራው ነገር የለም:: "አላውቀውም አንተ ንገረኝ" ከማለት ይልቅ ብዙ ሰው ሞት ይመርጣል:: ትንሽ ተምሬያለሁ የሚል ሰውማ ጥያቄ መጠየቅ ዲግሪውን ማቃጠል ይሆንበታል:: የብዙዎቻችን ትሕትና የሚፈቅድልን ሰዓት ለመጠየቅ ብቻ ነው:: "ከአንተ አላውቅም ..." ብለው የሚጀምሩ ዐረፍተ ነገሮች ራሱ ልብ ብለን ከሰማናቸው ይዘታቸው "ከእኔ አታውቅም" ነው:: የእውቀታችንን ውስንነት ለማመን የሚከብደን በሥጋችን ውስጥ ያለችው ለባዊት ነፍሳችን በሥጋዊ እውቀት ራስዋን መገደብ ስለምትቸገርም ነው:: እንደ ቅዱስ ጳውሎስ "አሁን ከእውቀት ከፍዬ አውቃለሁ" ብሎ የእውቀትን ውስንነት ማመን ግን ዕረፍት ይሠጣል:: 1ቆሮ. 13:12 በመንፈሳዊው ዓለም እንዲህ ሲሆን ደግሞ ይበልጥ አሳዛኝ እውነታ ነው:: "የቀለም ቀንድ" ፣ "የእውቀት ምንጭ" ፣ "መልስ በጉንጩ"፣  "ተጠያቂው" የሚለውን የክብር ሥፍራ ስንፈልግ በማናውቀው ጉዳይ ሌሎችን ከመጠየቅ ይከለክለናል:: አላውቀውም አላነበብኩትም አልሰማሁትም ከማለት ይልቅ ሁሉን አዋቂ ሆኖ ለመገኘት ስንል የምንበላቸው ዕፀ በለሶች ብዙ ናቸው:: "ብዙ የማውቀው ነበረ ሰዓት ገደበኝ እንጂ" ብሎ ውስን እውቀቱን ባሕር ለማድረግ የሚደክምና ሰዎች ከተናገረው ከጻፈው በላይ አድርገው እንዲያስቡት የሚገፋፋ ሰው የሚወለደው ካላዋቂነት ፍርሃት ውስጥ ነው::  በጥቂት ንባብ ውስጥ ራስን በጥልቅ ምሁር ዓይን ማየትና "እኔ የማውቀው ማወቄን ነው" ማለት የአላዋቂነት ፍርሃት የሚወልዳቸው ኢሶቅራጥሶች መርሕ ነው:: ከሌላው በታች አላዋቂ መስሎ መታየትን እንፈራለን:: ስለዚህ ሌላውን ከመጠየቅና እንደ ጃንደረባው "የሚመራኝ ሳይኖር እንዴት ይቻለኛል?" "ነቢዩ ይኼን ስለማን ተናግሮታል?" ብሎ ከመማር ይልቅ በራሳችን ለመረዳት ብንሟሟት እንመርጣለን:: ብዙ "የእምነት" denominations የተፈጠሩትም ሌላውን ከመጠየቅ ሞት በሚመርጡ ትዕቢተኞችና "እንደገባኝና እንደተረዳሁት" በሚል አስተሳሰባቸው እንደነበር ታሪክ ያስረዳናል:: "ነገር ግን እያንዳንዱ ባልንጀራው ከራሱ ይልቅ እንዲሻል በትሕትና ይቍጠር" ፊልጵ. 2:3 ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ መስከረም 2016 ዓ.ም.

+  አምናለሁ  እና አላምንም + ልጁ የታመመበት አባት ነው:: ጌታን "ቢቻልህስ ልጄን ፈውስልኝ" አለው:: ኢየሱስም፦ ቢቻልህ ትላለህ፤ ለሚያምን ሁሉ ይቻላል፡ አለው። ይህን ጊዜ ሰውዬው  "ወዲያውም የብላቴናው አባት ጮኾ፦ አምናለሁ፤ አለማመኔን እርዳው፡ አለ" ማር. 9:24 የዚህ ሰውዬ ንግግር ፍቺ የሚፈልግ ቅኔ ይሆንብኛል "አምናለሁ አለማመኔን እርዳው" ይኼ ሰውዬ ያምናል ወይንስ አያምንም? ያምናል እንዳንል "አለማመኔን" ይላል ፤ አያምንም እንዳንል "አምናለሁ" ይላል:: የቸገረ ነገር ነው? ሁሉን አዋቂው መድኃኔዓለም  ምን ለማለት እንደፈለገ ገብቶት ልጁን ፈወሰለት:: እኔ አላዋቂው ግን "አምናለሁ አለማመኔን እርዳው" የሚለውን ቃል እየደጋገምኩት ቀረሁ:: እያመኑ አለማመን እንዴት ያለ ነው? ብዬ መላልሼ ሳጤነው ግን ሰውዬው የእኔኑ ድክመት እየተናገረ እንደሆነ ገባኝ:: አምናለሁ እላለሁ:: በእርግጥም በፈጣሪ መኖር አምናለሁ:: ሁሉን እንደሚችልም አምናለሁ:: ግን ደግሞ በእርሱ ታምኜ አላውቅምና በሥራዬ እክደዋለሁ:: ኑሮዬ  "በሥራቸው ይክዱታል" ከተባሉት የሚመደብ ነው:: (ቲቶ 1:16) አቅዋሜ የማመን ኑሮዬ ያለማመን ነውና አምናለሁ አለማመኔን እርዳው ብል ለእኔ የሚገባ ጸሎት ነው:: ወረደ ተወለደ ተጠመቀ ተሰቀለ ሞተ ተነሣ ዐረገ ብዬ አምናለሁ:: በትሕትና መውረድን ፣ በንስሓ መወለድን ፣ በታናሽ እጅ ዝቅ ብሎ ጽድቅን መፈጸምን ፣ መከራን በትዕግሥት መቀበልን ፣ ከመከራ ሞት ወዲያ ተነሥቶ በክብር ከፍ ማለትን ግን እኔ ሕይወት ላይ አላውቀውም:: የምተርከው ክርስቶስ እንጂ የሚተረክ ክርስትና የለኝም:: ስለዚህ አምናለሁ አለማመኔን እርዳው በልኬ የተሰፋ ጸሎት ነው:: መች በዚህ ያበቃል:: እጾማለሁ አለመጾሜን እርዳው:: ከምግብ እጾማለሁ ከኃጢአት ግን አልጾምም:: ሥጋ መብላት ትቼ የሰው ሥጋ በሐሜት የምበላ ነኝና እጾማለሁ አለመጾሜን እርዳሁ እላለሁ:: እጸልያለሁ አለመጸለዬን እርዳው:: ቆሜ የማደርሰው ጸሎትስ አለኝ:: ግን ልቤ ሠላሳ ቦታ ደርሶ ይመለሳል:: የምጸልየው ማናገር የማልፈልገውን ሰው በግድ የማናግር ያህል የግብር ይውጣ እንጂ ነፍሴ እርሱን ሽታ አይደለምና እጸልያለሁ አለመጸለዬን እርዳው እላለሁ:: እሰግዳለሁ አለመስገዴን እርዳውስ? ላቤ እስኪወርድ ሰግጄ አውቃለሁ:: ልቤ ግን አንዴ አልሰገደም:: ጌታ ሆይ እመጸውታለሁ አለመመጽወቴን እርዳው:: እዘምራለሁ አለመዘመሬን እርዳው:: አስቀድሳለሁ አለማስቀደሴን እርዳው:: እማራለሁ አለመማሬን እርዳው:: ሆኜ ያልሆንሁትን አድርጌ ያላደርግሁትን ሁሉ አንተ ታውቀዋለህና እርዳኝ:: ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ ጳጉሜን 3 2015 ዓ.ም.