en
Feedback
"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"

Open in Telegram

@Dan12bot ለአስተያየትዎ ይህን ይጠቀሙ እናመሠግናለን

Show more
1 134
Subscribers
No data24 hours
-27 days
-2330 days
Posts Archive
#ጥር_14 አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ጥር አሥራ አራት በዚህች ቀን #ጻድቁ_አቡነ_አረጋዊ (ዘሚካኤል) የተወለዱበት እና ወደ ደብረ ዳሞ የወጡበት ነው፣ የከበረችና የተመረጠች #ቅድስት_ምህራኤል በሰማእትነት አረፈች፣ በገድል የተጠመደ የከበረ #ቅዱስ_አባ_አርከሌድስ አረፈ፣ የከበረች #ቅድስት_እምራይስ በሰማእትነት አረፈች። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ጻድቁ_አቡነ_አረጋዊ (ዘሚካኤል) ጥር አሥራ አራት በዚህች ቀን ታላቁና የከበረው አባታችን አቡነ አረጋዊ (ዘሚካኤል) የተወለዱበት እና ወደ ደብረ ዳሞ የወጡበት ነው። እኚህ አባት ከ9 ቅዱሳን አባቶች አንዱ ሲሆኑ አባታቸው ይስሐቅ የሮም ንጉስ ነበሩ፡፡ እናታቸው ንግስት እደና ይባሉ ነበር፡፡ የመጀመሪያ ስማቸው ዘሚካኤል ነው፡፡ ጥበብ መንፈሳ ሲማሩ አድገው ወደ እስክንድርያ ገዳም ገቡ፡፡ አበምኔቱ አባ ጳኩሚስ በፈቃደ እግዚአብሔር የመጡ መሆናቸውን አውቀው መዓረገ ምንኩስና ሰጥተዋቸዋል፡፡ የንጉሳዊ የቅንጦት ኑሮ ንቀው ትተው ገዳም ገብተው በምንኩስና ተወስነዋል፡፡ አባታችን በተጋድሏቸውም ከአባ እንጦንስ፣ ከአባ ጳውሊ እና ከአባ መቃርስ ቀጥሎ በአራተኛ ማዕረግ አበ መነኮሳት ሆነው ተመርጠዋል። በገዳመ ዳውናስ 7 ዓመት ከቆዩ በኋላ ወደ ሮም ተመልሰው ሲያስተምሩ የሀገራችን ኢትዮጵያን ዜና ሰምተው ለመምጣት በ480 ዓ.ም ከአባ ፍሬምናጦስ በኋላ መንገድ ጀመሩ፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም በክንፉ ተሸክሞ አክሱም አድርሷቸዋል፡፡ ተመልሰውም ሄደው ስለ ቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ  መስክረዋል፡፡ ሐዋርያ ሳይላክላት በሃይማኖት በምግባር ጸንታ ትኖራለች ብለው ለሰባቱ ዘመዶቻቸው አበው መነኮሳት ነገሯቸው፡፡ ስምንቱም ጓዛቸውን ጠቅልለው በሮም ነግሶ የነበሩ ይስሐቅን (አባ ገሪማን) ጨምረው ንጉስ አልአሜዳ በነገሰ በአምስተኛ ዓመት ማለትም በ480 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ ዘጠኝ ሆነው መጥተዋል፡፡ አባ አረጋዊ እናታቸው ቅድስት እድናን ደቀ መዝሙራቸውን ማትያስን አስከትለው እግረ መንገዳቸውን እያስተማሩና ድውያንን እየፈወሱ ደብረ ዳሞ ደረሰዋል፡፡ ከእግረ ደብር ሆነው አሁን ይህን ተራራ በምን ልወጣው እችላለሁ እያሉ ሲያወጡ ሲያወርዱ በንግግሩ ሐሰት የሌለበት አምላካችን በነቢዩ ዳዊት ላይ አድሮ በመዝሙር 90/91፥11-16 ላይ “በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋልና፤ እግርህም በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸው ያነሡሃል። በተኵላና በእባብ ላይ ትጫማለህ፤ አንበሳውንና ዘንዶውን ትረግጣለህ። እንዳለው የታዘዘ ዘንዶ መጥቶ ስደሳ ክንድ በሚያህል ጅራቱ ጠምጥሞ ቅዱስ ሚካኤል ሰይፈ እሳት ይዞ እየጠበቃቸው ከተራራው አናት አድርሷቸዋል፡፡ ወዲያው ሃሌ ሉያ ለአብ ሃሌ ሉያ ለወልድ ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ ብለው አመስግነዋል፡፡ ቦታውም ደብረ ሃሌ ሉያ ተብሏል፡፡ በዚያ ዕለት ግማሽ ህብስት በልተው ጠገቡ፤ ከዚያ በኋላ ግን ምድራዊ ሕብስት አልተመገቡም፡፡ በሰንበተ ክርስታያን ከቅዳሴ በኋላ ሕብስተ ሰማያዊ እያመጡላቸው ይመገቡ ነበር እንጂ፡፡ ኋላም ዜና ጽድቃቸውን ሰምተው ከስድስት ሺህ ያላነሱ ደቀ መዛሙርት ተሰብስበውላቸዋል፡፡ ዘጠና ዘጠኝ አመት ሲሞላቸው ጌታ በመንፈቀ ሌሊት ተገልጾ ምድራዊ መንግስትህን ትተህ ስላገለገልከኝ ህልፈት ሽረት የሌለባት ሰማያዊ መንግስቴን አወርሰሃለሁ ብሎ ቃልኪዳን ሰጣቸው፡፡ በስምህ የተማጸነውን እስከ አስራ አምስት ትውልድ ድረስ እምርልሃለሁ አንተም ከሞት ገጽ ትሰወራለህ ብሎ ተስፋቸውን ነገራቸው፡፡ እሳቸው መነኮሳቱን ሰብስበው ከእንግዲህ በሥጋ አታዩኝም ብለው ነግረዋቸው አበምኔት ሾመውላቸው በደብረ ዳሞ ተራራ በስተምስራቅ አቅጣጫ ተሰውረዋል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅድስት_ምህራኤል በዚህች እለት ጠምዋህ ከሚባል ሀገር ሰዎች የከበረችና የተመረጠች ምህራኤል በሰማእትነት አረፈች። የዚችም ቅድስት ወላጆቿ እግዚአብሔርን የሚያመልኩ ክርስቲያኖች ናቸው አባቷም ስሙ ዮሐንስ የሚባል ቄስ ነው እናቷም ኢላርያ የምትባል ደግ ናት።ነገር ግን ልጅ ስለሌላቸው ስለዚህ እያዘኑ ወደ እግዚአብሔር ይለምኑ ነበር ከብዙ ዘመንም በኃላ ይህቺን የከበረች የተቀደሰች ልጅ ተሰጠቻቸው ስሟንም ምህራ ኤል ብለው ጠርዋት። ዐስራ ሁለት ዓመትም በሆናት ጊዜ በላይዋ በአደረ በመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ድንቆች ተአምራቶችን መስራት ጀመረች።ከዚህም በኃላ ከሀዲ ንጉስ ዲዮቅልጣኖስ በተነሳ ጊዜ ወደ ባህር ዳርቻ ወጣች መርከበም አግኝታ በላዩ ተሳፈረች ለሰማእትነት ከሚሄዱት ጋር በመሄድ ወደ እንፅና ከተማ በደረሰች ጊዜ ስሙ ፍልፍልያኖስ በሚባል መኮንን ፊት ቆመች በአያትም ጊዜ ስለታናሽነቷ ራርቶላት ሊተዋት ወደደ። ሊተዋትም እንደወደደ አውቃ እርሱንና የረከሱ አማልክቶቹን በድፍረት ረገመች።ስለዚህም መኮንኑ ተቆጥቶ ፅኑእ የሆነ ስቃይን አሰቃያት ከቀናች ሀይማኖቷ ሸንግሎ ይመልሳት ዘንድ በተሳነው ጊዜ ጊንጦችን እፉኝቶችንና እባቦችን ሰብስበው በዳውላ ውስጥ እንዲጨምሩአቸው እርሷንም ከእነርሱ ጋር በዳውላ ውስጥ እንዲጨምሩ አጥማጆችን አዘዛቸው እነርሱም እንዲሁ አደረጉ። ያን ጊዜ የእግዚአብሄር መልአክ ተገለፀላትና ከጌታችን ዘንድ የተሰጣትን ቃል ኪዳን አስረከባት ከዚህም በኃላ ነፍሷን አሳለፈች የምስክርነት አክሊልንም ተቀበለች ከዳውላውም ውስጥ አውጥተው በዚያች ቦታ ቀበሩዋት። ከዚህም በኃላ አባቷና እናቷ በሰሙ ጊዜ ስጋዋ ወዳለበት ከብዙ ህዝብ ጋር መጡ ከዚያም ስጋዋን አፈለሱና ወሰዱአት በታላቅ ክብርም ገንዘው በአማረች ሳጥን ውስጥ አኖሩዋት በስውር ቦታም ያማረች ቤተ ክርስቲያን ሰሩላት ከእርሷም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አባ_አርከሌድስ በዚህችም ቀን በገድል የተጠመደ የከበረ አባት አርከሌድሰ አረፈ። ይህም ቅዱስ ከሮሜ ሀገር ከታላለቆች ወገን ነው የአባቱ ስም ዮሀንስ የእናቱም ስም ሰንደሊቃ ነው ሁለቱም እውነተኞች የሆኑ በእግዚአብሄር ህግ ያለ ነቀፋ የፀኑ ናቸው። ቅዱስ አርከሌድስም እድሜው አስራ ሁለት አመት በሆነው ጊዜ አባቱ ሞተ እናቱም ሚስት ልታጋባው አሰበች እርሱ ግን ይህን አልወደደም። ከዚህም በኃላ ወደ ንጉስ ሄዶ የአባቱን ሹመት ይቀበል ዘንድ መከረችው ከእርሱም ጋር ሁለት አገልጋዮችን ላከች ልንጉስም እጅ መንሻ የሚሰጠውን ብዙ ገንዘብ ሰጠችው።በመርከብም ተጭኖ በባህር መካከል ሳለ ጥቅል ነፋስ በላዩ ተነሳ ማእበሉም እጅግ ከፍ ከፍ ብሎ መርከቡ ተሰበረ እርሱም በአንዲት የመርከብ ስባሪ ሰሌዳ ተንጠልጥሎ ወደ የብስ አደረሰችው። ከባህሩም ሲወጣ ማእበል የተፋው በድን አገኘ ተቀምጦም በላዩ አለቀሰ የአለምን ኃላፊነትም አሰበ ነፍሱንም የሚገስፃትና የዚህ የኃላፊው አለም ገንዘብ ምኔ ነው ላንቺስ ምንሽ ነው ከሞትኩ በኃላ ወደ አፈር እመለሳለሁና የሚላት ሆነ። በዚያንም ጊዜ የክብር ባለቤት ወደ ሆነ ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለመነ የቀና መንገድን ይመራው ዘንድ ከዚህም በኃላ ተጓዘ በቅዱስ ሮማኖስ ስም በሶርያ አገር ወደ ተሰራ ወደ አንድ ገዳም ደረሰ። ከገንዘብም ከእርሱ ጋር የቀረውን ሁለት መቶ የወርቅ ዲናር ለአበ መኔቱ ሰጠው የምንኩስና ልብስንም እንዲያለብሰው ለመነው ።

የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም" "በልቡ ለተከማቸ ፍቅሯ በሚሻል ነገር መለሰላት። እርሷ ስለ ምድራዊ ወይን ለመነችው፣ እርሱም ስለ ጎኑ   የደሙ ወይን በምሥጢር መለሰ" አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ፣ መጽሐፈ ምሥጢር መልካም የቃና ዘገሊላ በዓል!

✝ ዓርብ የከተራ በዓል አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ጥር ዐሥር በዚችም ዕለት ምንም ምን መብልን ሳይቀምሱ ምእመናን ሁሉ እስከ መሽት ይጾሙ ዘንድ ከእኛ አስቀድመው የነበሩ ታላላቅ ሊቃውንት የቤተ ክርስቲያን መምህራን ሥርዓት ሠሩ:: በምሽትም ቢሆን በታላቁ ጾም ከሚበላው በቀር ጥሉላትን እንዳይቀምሱ:: የሚያሰክር መጠጥም ፈጽመው እንዳይቀምሱ ጾም ነውና:: በዚህች ጥር ዐሥር የከተራ ዕለት ምእመናን እስከ ምሽት እንዲጾሙ ያዘዙበት ምክንያት ይህ ነው:: እኛ በዚህ በኃላፊው ዓለም ተድላ ደስታ ደስ የሚለን ለሌሎች እንዳይመስላቸው እንደ አይሁድና እንደ አረማውያን በዓል በመብልና በመጠጥ ብቻ አናድርግ:: ስለዚህ ከልደትና ከጥምቀት በዓል በዋዜማው ያሉትን ሁለቱን ዕለታት እንድንጾም አዘዙን:: በዚህም ሁለት ሥራ ይፈጸምልናል:: የጾም ሥራና የበዓል ማክበር ሥራ ነው:: በጥምቀት ዕለት ከእኵለ ሌሊት በፊት ተነሥተው በውኃ ላይ ይጸልዩና ይጠመቁ:: ሕፃናትም በሚጠመቁ ጊዜ በውኃ እንዳይገድፉ ካህናቱም ከመንጋቱ በፊት ቀድሰው ቍርባለኑን ያሳርጉ:: እጅግም ማልደው በጥዋት ከቤተ ክርስቲያን ይውጡ በከበረ ሥርዓታቸው ሐዋርያት እንዳዘዙ:: እኛንም ከበደላችን ያነጻን ዘንድ በዮርዳኖስ ወንዝ እንደ ገለጸ የጌትነቱን ክብር በልቡናችን ይገልጥልን ዘንድ የክብር ባለቤት የሆነ ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን እንለምነው:: ጌትነት ክብር ስግደት ለእርሱ ይገባልና ከቸር አባቱ ጋር ይቅር ባይ ከሆነ መንፈስ ቅዱስም ጋር ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን:: መልካም የከተራ በዓል!      👉  ዓርብ የከተራ በዓል ኢየሱስ ክርስቶስ አምላከ አማልክት የጌቶች ጌታ የነገሥታት ንጉሥ ሲሆን ወደ ዮርዳኖስ ወርዶ በዮሐንስ እጅ ተጠምቋል:: የሁሉ አስገኝ ፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዮሐንስ ሔዶ መጠመቁን ለማዘከር ማደሪያው የሆኑት ታቦታት ወደ ጥምቀተ ባህር ይሔዳሉ:: ጌታችን በዮርዳኖስ ወንዝ በመጠመቁ ዮርዳኖስን እንደ ቀደሰ ሁሉ ታቦታቱም ባህረ  ጥምቀቱን ሊቀድሱ ይወጣሉ:: በዚህ በከተራ ዕለት ምእመናን ሁሉ ታቦታትን አጅበው ነጭ ለብሰው እያሸበሸቡና እየዘመሩ ፍጹም መንፈሳዊ በሆነ ሥርዓት ያከብራሉ:: ታቦታቱ ከመንበራቸው ተነስተው ወደ ጥምቀተ ባህሩ ሲሔዱም ሆነ ሲመለሱ በሙሉ ኃይሉ ሕዝቡ ሁሉ እየተከተለ ይዘምራል:: ልክ እንደ ዳዊት "ዳዊት በሙሉ ኃይሉ በእግዚአብሔር ፊት ይዘምር ነበር::" እንዳለ:: መጽ. ሳሙኤል ካልዕ ም.5 -:-15:: በቃል ኪዳኑ ታቦት ፊት የምንፈጽማቸው ማንኛውም መልካምም ሆነ ክፉ ነገር በእግዚአብሔር ፊት እንደፈጸምነው ነውየሚቆጠረው መጽሐፍ እንደሚለን:: ዳዊትም ሆነ ሕዝቡ የእግዚአብሔር ታቦት ወደ ከተማቸው ስትገባ በቅኔ በበገና በከበሮ በመስንቆ በነጋሪት በጸናጽል ሆ እያሉ እየዘመሩ ይሔዱ ነበር ነው የሚለን:: ልብ እንበል በእግዚአብሔር ፊት ነው የሚለው መጽሐፍ:: በታቦታቱ ፊት የምንፈጽመው ዝማሬ በእግዚአብሔር ፊት ነው የምናደርገው:: መጽ. ሳሙኤል ም.5 በሙሉ እንመልከት:: ሁላችን የቤተ ክርስቲያን ልጆች በዚህ ቀን ደምቀን ነጭ ለብሰን የቃል ኪዳኑ ታቦት በሚያልፍበት አካባቢ ሙሉ ኃይላችን ተጠቅመን ልንዘምር ይገባል:: አካባቢውን ሙሉ ኃይላችን ተጠቅመን በዓሉን በሚመጥን ከፍ ባለ ክብር በጥቅስ በቅዱሳን ሥዕላት በምንጣፍ በቀጤማ በሽቶ ልናከብረው ይገባል:: የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት የሁሉ ቅዱሳን በረከትና ረድሄት ከሁላችን ላይ ይኑር ለዘላለሙ አሜን::

#ጥር_10 #ጾመ_ገሃድ ጥር አስር በዚህች ዕለት ምንም ምን መብልን ሰይቀምሱ ምእመናን ሁሉ እስከ ምሽት ይጾሙ ዘንድ ከእኛ አስቀድመው የነበሩ ታላላቅ ሊቃውንት የቤተ ክርስቲያን መምህራን ሥርዓትን ሠሩ በምሽትም ቢሆን በታላቁ ጾም ከሚበላው በቀር ጥሉላትን እንዳይቀምሱ። በዚች ዕለት ምእመናን እስከ ምሽት እንደመጾሙን ያዘዙበት ምክንያቱ ይህ ነው የልደትና የጥምቀት በዓል በዓል በረቡዕ ወይም በዓርብ ቀን ቢሆን በበዓለ ኃምሳ የሚበላውን የጥሉላት መብል በጥዋት በመብላት ምእመናን ሁሉ በዓሉን እንዲአከብሩ የከበሩ አባቶቻችን ሐዋርያት አዝዘዋል እሊህ ሁለቱ የእግዚአብሔር ታላላቅ በዓላቶቹ ናቸውና። እኛ በዚህ በኅላፊው ዓለም ተድላ ደስታ ደስ የሚለን ለሌሎች እንዳይመስላቸው እንደ አይሁድና እንደ አረማውያን በዓል በመብልና በመጠጥ ብቻ እንዳናደርግ ስለዚህ ከልደትና ከጥምቀት በዓል በዋዜማ ያሉትን ሁለቱን ዕለታት እንድንጾም አዘዙን የልደትና የጥምቀት በዓል በረቡዕና በዓርብ ላይ በሚሆን ጊዜ በረቡዕና በዓርብ ፈንታ እንድንጾማቸው ይገባልና በዚህም ሁለት ሥራ ይፈጸምልናል የጾም ሥራና የበዓል ማክበር ሥራ ነው። እንዲሁም በግብፃውያን አብያተ ክርስቲያን የተሠራ ነው። በይረሙን በእሑድ ወይም በአይሁድ ሰንበት ቀን ቢሆን ይህም ጌታ የተገለጸበት ጥር ዐሥራ ቀን ነው በዋዜማው ዐርብ እስከ ምሽት ይጹሙ አስቀድመን እንደተናገርን ጥሉላት አይብሉ የልደትና የጥምቀት በዓልም ሰኞ ቀን ቢሆን በሰንበት ቀን ይጾም ዘንድ አይቻልም ነገር ግን ጥሉላትን ከመብላት ይጠበቁ። በጥምቀትም ዕለት ከእኵለ ሌሊት በፊት ተነሥተው በውኃው ላይ ይጸልዩና ይጠመቁ ሕፃናትም በሚጠመቁ ጊዜ በውኃ እንዳይገድፉ ካህናቱም ከመንጋቱ በፊት ቀድሰው ቊርባኑን ያሳርጉ እጅግም ማልደው በጥዋት ከቤተ ክርስቲያን ይውጡ በከበረ ሥርዓታቸው ጌቶቻችን ሐዋርያት እንዳዘዙ። የመለካውያን ወገኖች ግን የልደትና የጥምቀት ዋዜማ በቅዳሜ ቀን ወይም በእሑድ ቀን ቢሆን በሦስት ሰዓት ይቀድሳሉ ከወደዱም የተባረከ ኅብስት ተመግበው ውኃ ይጠጣሉ ከዚህም በኋላ ካህናቱ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሁነው በየሰዓቱ በመጸለይ ለበዓሉ የሚገባውን የነቢያትን ትንቢቶች ያነባሉ በዚያች ቀን በምሽት ይኸውም ጥር ዐሥር ነው በውኃው ላይ ይጸልያሉ ይህም አባቶቻችን ሐዋርያት እንዳዘዙት አልሆነም። እርሳቸው የኤጲፋንያን በዓል እንዲአክብሩ አዘዋል ይኸውም መድኃኒታችን የተገለጠበት ካኑን በሚባል በሮም ሁለተኛ ወር በሰባት ይህም ጥር ዐሥራ አንድ ቀን ነው። መለካውያን ግን የከበሩ አባቶች የቤተ ክርስቲያን መምህራን ያዘዙትን ይተላለፋሉ በልደትና በጥምቀት በዓል ዓርብም ረቡዕም ቢሆን አስቀድመው በርሱ ፈንታ ሳይጾሙ በጥዋት ተነሥተው ይበላሉና። እኛንም ከበደላችን ያነጻን ዘንድ በዮርዳኖስም ወንዝ እንደ ተገለጸ የጌትነቱን ክብር በልቡናችን ይገልጥልን ዘንድ የክብር ባለቤት የሆነ ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን እንለምነው። ጌትነት ክብር ስግደት ለእርሱ ይገባልና ከቸር አባቱ ጋር ይቅር ባይ ከሆነ መንፈስ ቅዱስም ጋር ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን። (#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር)

#ጥር_7 #በዓለ_ሥሉስ_ቅዱስ ጥር ሰባት በዚች ቀን በዓለ ሥላሴ የሚከበረው ስለ ሁለት ምክንያቶች ነው:: ቀዳሚው ሕንጻ ሰናዖርን ማፍረሳቸው ሲሆን ሌላው ደግሞ ቅዳሴ ቤታቸው ነው:: #ሕንጻ_ሰናዖር ሰናዖር ከሺዎች ዓመታት በፊት በአሁኗ ኢራቅ አካባቢ እንደ ነበረ የሚነገርለት ግዛት ሲሆን ስሙ ለሃገሪቱም: ለንጉሡም በተመሳሳይ ያገለግል ነበር:: ከናምሩድ ክፋት በሁዋላ ሰናዖርና ወገኖቹ ከሰይጣን ተወዳጁ:: ከጥፋት ውሃ (ከኖኅ ዕረፍት) በሁዋላ በሥፍራው በአንድነት ይኖሩ ነበርና እርስ በርሳቸው "ኑ ሳንበተን ስማችን የሚጠራበትን ሕንጻ እንሥራ:: በዚያውም አባቶቻችን በውሃ ያጠፋ እግዚአብሔርን እንውጋው" ተባባሉ:: ቀጥለውም ሰማይ ጠቀስ ፎቅን ገነቡ:: ከሕንጻው መርዘም የተነሳ በጸሐይ አብስለው በልተዋል ይባላል:: ቀጥለውም ጦር እያነሱ ፈጣሪን ሊወጉ ወርውረዋል:: መቼም የእነዚህን ሰዎች ክፋትና ቂልነት ስንሰማ ይገርመን ይሆናል:: ግንኮ ዛሬ ሰለጠንኩ በሚለው ዓለም እየተሠራ ያለው ከዚህ የከፋ ነው:: ቸርነቱ ቢጠብቀን እንጂ እንደ ክፋታችንስ ጠፊ ነበርን:: ርሕሩሐን ሥላሴ ግን የሰናዖር ሰዎች የሠሩትን አይተው ማጥፋት ሲችሉ አላደረጉትም:: የባሪያቸውን የኖኅን ቃል ኪዳን አስበዋልና:: ይልቁኑ "ንዑ ንረድ ወንክአው ነገሮሙ ለከለዳውያን-ቁዋንቁዋቸው እንደባልቀው" አሉ እንጂ:: ከለዳውያን ልሳናቸው ተደበላልቆ 71 ቁዋንቁዎች ተፈጠሩ:: እነርሱም ስምምነት አጥተው ተበተኑ:: ሥላሴም ያን ሕንጻ በነፋስ ትቢያ እንዲሆን በተኑት:: ስለዚህም እስከ ዛሬ ሥፍራው "ባቢሎን (ዝሩት)" ሲባል ይኖራል:: #ቅዳሴ_ቤት ልክ የዛሬ 324 ዓመት አድያም ሰገድ ኢያሱ በኢትዮዽያ በነገሡ በ10ኛው ዓመት (በ1684 ዓ.ም) በጐንደር ከተማ ንግሥተ አድባራት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ተሰርታ ተጠናቃለች:: ጥር 7 ቀንም ሊቁ ክፍለ ዮሐንስን ጨምሮ በርካታ ምዕመናን: ሠራዊት: መሣፍንትና ሊቃውንት ባሉበት ቅዳሴ ቤታቸው ተከብሯል:: በዕለቱም ታላቅ ሐሴት ተደርጉዋል:: ኢያሱ አድያም ሰገድ ኃያል: ደግ: ጥበበኛ: አስተዋይ: መናኝ ንጉሥ ነውና:: ቤተ ሥላሴን አስጊጿታልና ከዚህ ቀን ጀምሮ ጥር ሥላሴ በድምቀት የሚከበር ሆኗል:: ነገር ግን በተሠራች በ16 ዓመቷ ደጉ ኢያሱ ከተገደለ በሁዋላ ቤተ ክርስቲያኑ በአደጋ ፈርሷል:: ዛሬ የምናየው በ1708 ዓ.ም በልጁ በአፄ ዳዊት ሣልሳዊ የታነጸውን ነው:: ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን። አሜን።

+• ምን ይዘህ ወጥተሃል? •+ በአንድ መንደር ዝናብ ጠፍቶ ተቸገሩ አሉ። ሰው ተሰብስቦ "ምን ይሻላል? ምን እናድርግ?" ብሎ ተማከረ። ትልቁ መፍትሔ የዝናቡ ጌታ የሆነውን እግዚአብሔርን መማጸን እንደሆነ ተገንዝበው ጸሎትና ምሕላ ለማድረስ ተስማሙ። ጸሎቱ በሚጸለይበት ዕለት አንዲት እናት ከቤት ለመውጣት እየተዘጋጀች እያለ፥ ልጇ "እማዬ የት ልንሄድ ነው?" ብላ ጠየቀቻት። እናትም "እግዚአብሔር ዝናብ እንዲሰጠን ልንጠይቅ ወደ ቤተክርስቲያን ልንሄድ ነው" ብላ መለሰች። ዝግጅታቸውን ጨርሰው ሲወጡ፥ ልጅቷ መለስ ብላ "እማዬ፥ ጥላ አንይዝም እንዴ?" ብላ ጠየቀች። እናት በመገረም "ለምንድር ነው ጥላ የምንይዘው ደግሞ?" አለች። ልጅም "እግዚአብሔርን ከጠየቅነው ስለሚሰጠን፥ ስንመለስ ዝናብ እንዳይመታን ነው።" ብላ መለሰች። እናት የልጇን ንጹሕ እምነት ልብ ማለት ቢያቅታትም፥ እግዚአብሔር ግን ይህንን ፍጹም መታመን አይቶት ነበር። ጸሎታቸውን ጨርሰው ሲመለሱ፥ ድንገተኛ ዝናብ መጥቶ በመንደሪቷ ላይ ዶፍ ዝናብ ጣለ። ጥላ ሳይይዙ የሄዱ እናትና ልጅም በዝናብ ርሰው ወደ ቤታቸው ገቡ። ማመን መታመን እንዲህ ነው! ሰው እምነትን ከሞኝነት ቢቆጥረው፥ እግዚአብሔር ግን ከተግባር ያደርሰዋል። ሰው ከቅርብ ማየት የማይችለውን እምነት፥ እግዚአብሔር ግን ከሩቅ ያየዋል። በሕይወትህ እግዚአብሔርን ብዙ ጠይቀኸው ሊሆን ይችላል፥ ግን ይሰጠኛል ብለህ ምን ይዘህ ወጥተሃል? 🖋 Fresenbet G.Y Adhanom

ብሠራት:- አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ታኅሣሥ ሃያ ሁለት በዚህ ቀን እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያምን የከበረ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ያበሠራት ቀን ነው:: ይህም መልአክ ስለ ወልደ እግዚአብሔር ሰው መሆን ምሥጢር የታመነ ሆኖ ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተላከው ነው። የደስታ መገኛ ደስ ይበልሽ ጸጋን የተመላሽ ሆይ እግዚአብሔር ካንቺ ጋር ነው አንቺም ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ አላት:: ስለ መጥምቁ ዮሐንስ መወለድም ካህኑን ዘካርያስን ያበሠረውም ቅዱስ ገብርኤል ነው:: ይህ መልአክ  የከበረ የተመረጠ ገናና የሆነ ነውና ስለ እኛ ወደ እግዚአብሔር ይማልድ ዘንድ ልባችንን አንጽተን ወደዚህ የከበረ መልአክ እየለመንን መታሰቢያውን ልናደርግ ይገባናል:: ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ በከበረ መልአክ አማላጅነት ይማረን በረከቱ ረድኤቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን::

አግዚአብሔር ዝም ሲል አቅቶት አይደለም፡፡ እርሱ ዝም ሲል የእኛ ነገር ሰልችቶት አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ዝም ሲል ረስቶንም አይደለም፡፡ ሰው ይረሳል እርሱ ግን በነገሩ ሁሉ ታማኝ ነውና አይረሳም፡፡ በዝምታ ውስጥ መሰራት አለ። በዝምታው ውስጥም መልስም አለ፡፡

+++ የአንድ ኃጢአተኛ ሰው ጸሎት ++         ( ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ ) አቤቱ “በጎውን ነገር ማን ያሳየናል?” የምንልበት ዘመን አይደለም፤ እንኳን በእኛ ዘንድ ይቅርና ወንጌል በአሕዛብ ዘንድ ሳይቀር የተሰበከበት ዘመን ነውና። ነገር ግን የተሰበከውን ቃል በልቤ አኑሬ ሕይወቴን ሳልለውጥበት ብዙ ዘመናትና ዓመታት አለፉ። ቃልህን ሰምቶ አለማድረግ በአንተ መዘባበት መሆኑን አውቃለሁ፤ ቃልህን የምሰማ እንጅ የምፈጽም ባለመሆኔም ምክንያት በድቡሽት ላይ እንደተሠራ ቤት ሆኛለሁ። ጥልቀት በሌለው አኗኗር ላይ የተገነባው መንፈሳዊነቴ ጎርፍ በጎረፈ፣ ነፋስ ባለፈ ጊዜ የሚናወጥ ደካማ ሆኖብኛል። ዓለምን ለማሳለፍ ዳግመኛ መምጣትህን ባሰብሁ ጊዜ እደነግጣለሁ። ጻድቃን “አሜን ጌታ ኢየሱስ ሆይ ቶሎ ና” እያሉ የምትመጣበትን ቀን ሙሽራዋን እንደምትጠብቅ ሴት በተስፋ ይጠባበቃሉ፤ እኔ ግን አሁንም ለንስሐ ዕድሜ እንድትጨምርልኝ እለምናለሁ። ለንስሐ ብየ የለመንሁትን ዕድሜ አሁንም ማለቂያ ለሌለው ፍላጎቴ ባውለውም አንተ ግን የለመንሁትን ዕድሜ ሰጥተህ አጠገብኸኝ። ሰው ምን ቢቸግረው ነው የሠርጉን ቀን የሚያራዝመው? የደስታ ቀኑ እንዳትደርስ የሚከላከል ሰው ማለት እኔ ነኝ። አንተ የምትመጣበት ቀን ከዓለም አስቀድሞ ያጨኻትን የጻድቃንን ነፍስ እንደ ሴት ሙሽራ በአፍህ መሳም ስመህ መኃ 1፥2 የምትቀበልበት ቀን ነው። ፀሐይና ጨረቃ በማያስፈልጓት ከተማ ለመኖር ጻድቃን ራሳቸው እንደ ፀሐይና ጨረቃ የሚያበሩበትን ያንን ቀን በቶሎ እንዲመጣ አለመለመን እንዴት ያለ ሞኝነት ነው? ያንጊዜ ታላቅ ደስታ ይደረጋል፤ ሙታንን የሚያነቃቸው ታላቁ ዝማሬ በሰማያውያን መላእክት ይጀመራል፤ መላእክት “ቅዱስ እግዚአብሔር” ሲሉ ምድራውያን ጻድቃንም “ቅዱስ ኃያል.......”  እያሉ ያንን ዝማሬ ሊቀበሉ ከመቃብራቸው ይወጣሉ። ሞት ያንን ምስጋና ሰምቶ ይደነግጣል። ዲያብሎስ ይገሠጻል። በእውነት የዚያን ቀን የሚደረገው ተድላ ደስታ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ እስካሁን አልተደረገም። እመቤታችን “ተፈሥሒ” የሚለውን የምስጋና ቃል በሰማች ጊዜ ያገኘችውን ደስታ ጻድቃን ያንጊዜ ያገኙታል። ያችን የደስታ ቀን ባለመዘጋጀቴ መድረሷን እየቸኮሉ ከሚጠባበቁት ውስጥ አይደለሁምና አዝናለሁ። ጌታዬና አምላኬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ያንን ቀን በደስታ እንድጠብቅ እንጅ ባሰብሁት ጊዜ ከመደንገጥ አውጣኝ። አውቃለሁ ጌታዬ ዛሬ ቃልህን ሰምተው ደስ የማይላቸው ሰዎች ያንጌዜ “ንዑ ኀቤዬ” የሚለውን ቃልህን ሰምተው ደስ አይላቸውም። ያንጊዜም ደስታን የሚሰጠን ዛሬ የምንሰማው ቃልህ ነው። ይህንንማ በመካከላችን ስብከትን በጀመርህባት ቀን “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ” ባልኸን ጊዜ ገልጠህልን ነበር። መንግሥተ ሰማያት ብለህ የጠራሃት ቃልህን መሆኑን መምህራኖቻችን፥ “መንግሥተ ሰማያት፡− ሕገ ወንጌል፣ ሕገ ወንጌል፡− ተስፋ፣ ተስፋ፡− እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው” ብለው ተርጉመው ነግረውን ተረድተን ነበር። መንግሥተ ሰማያትን በመካከላችን ያኖርህልን ሆይ! ቃልህን በሰሙ ጊዜ የማር ወለላ እንዳቀረቡላቸው ሕጻናት ሳስተው እንደሚሰሙህ ወዳጆችህ እንድሆን እርዳኝ። ደፍሬ ስምህን መጥራቴን ሳስብ አንዳንድ ጊዜ ፍርሃት ይይዘኛል፤ ደግሞ “ሰውን የምትወድ ሆይ” ብለው ካህኑ በቅዳሴ ጊዜ ሲጠሩህ ስሰማ ፍርሀቴን ያርቅልኛል። አንተ በምትከብርበት መቅደስ ውስጥ ገብቼ መቆሜንም ሳስብ በቅዱሳን ጉባኤ መካከል የአንድ ኃጢአተኛ የእኔ መገኘት ያስጨንቀኛል፤ ነገር ግን ካህኑ በቅዳሴው መካከል “ወንጌል” ብለው ወጥተው “ኃጥአንን ለንስሐ እንጅ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም” የሚለውን ቃልህን ሲያነቡ በሰማሁ ጊዜ በሰጠኸኝ ዕድል ድምጼን ከፍ አድርጌ አመሰገንሁህ። ሰዎች እስኪገርማቸው ድረስ በእኔ በቀራጩ ቤት መዋልህ ለምንድነው? በፊትህ በድለው ከማያውቁ መላእክት ይልቅ የእኔን ምስጋና ለመስማት መምጣትህ ለምንድነው? ሰውን መውደድህ ያስደንቃል! ከተግሣጽህ ይልቅ ፍቅርህ ማርኮኝ መጥቻለሁ። ደዌ ከጸናበት ሰው በቀር ሀኪሙን በብርቱ ፍለጋ ማን ይፈልገዋል? እኔም ደዌ ነፍስ ቢጸናብኝ ኃጢአት ቢያስጨንቀኝ መጥቻለሁና ፈውሰኝ። ላገለግልህ ብወድም እንደ ሐማተ ጴጥሮስ ሳልፈወስ ላገለግልህ አልፈቀድሁም። ለአንተ ምን ይሳንሃል? ከለምጼ ልታነጻኝ ብትወድ ይቻልሃል። ከአልጋዬ ልታነሣኝ ብትወድስ ማን ይከለክልሃል? ፈውሰኝና ዕድሜዬን በሙሉ አገልጋይህ አድርገኝ። ሳልፈወስ ባገለግል ደዌዬ ወደ ሌሎችም እየተዛመተ ብዙዎችን ይበክላል። ይሁዳ ባዛመተው ገንዘብ መውደድ፣ አፍኒንና ፊንሐስ በጀመሩት የመቅደስ ውስጥ ድፍረት፣ ዳታንና አቤሮን ባቀጣጠሉት ዘረኝነት፣ ሲሞናውያን ባሳዩት ጉቦኛነት ተይዘው ያልተፈወሱ ብዙ ናቸው፤ የእኔም ተጨምሮ የፈውስ ጊዜአችንን እንዳያርቅብን ስለምፈራ ፈውሰኝና አገልጋይህ ልሁን። እኔ ሥጋህንና ደምህን የምቀበለው ዝቅ ብለህ አጥበህ እንዳነጻሓቸው እንደ ሐዋርያት ንጹሕ ሆኜ አይደለም፤ እንዲያውም ስቆርብ ያዩኝ ሰዎች ገርሟቸው “ይሄ ኃጢአተኛ ሰው ቆራቢ ለመባል ብሎ ነው እንጅ አምኖበት ነው?” ብለው ተሳለቁብኝ። በሽታ የጸናበት ሰው መድኃኒቱን የሚወስደው ደዌው እንዲለቀው እንጅ ደዌው ከለቀቀው በኋላ ነውን? እኔስ ይህ ቍርባን ፈራጅ እንደሆነ ባውቅም ማኅየዊ እንደሆነም አምናለሁ። ሐዋርያት “የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻናል” 1ዮሐ 1፥7 ብለው ያስተማሩት ትዝ ይለኛል። የምትፈርድብኝ ፍርድ ሳይሆን “እንካችሁ ብሉ ሥጋዬን፣ እንካችሁ ጠጡ ደሜን” ብለህ ወደ እኔ የዘረጋሃት እጅህን አያታለሁ። ስለዚህም አፌን ከፍቼ እቀበልሃለሁ። ዛሬ “በምሕረትህ ብዛት ወደ ቤትህ እገባለሁ አንተን በመፍራትም ወደ ቅድስናህ መቅደስ እሰግዳለሁ” ዳግመኛ በምትመጣ ጊዜም በምሕረትህ ብዛት በሚያስፈራና በሚያስደነግጥ ዙፋንህ ፊት እቆማለሁ። ጭብጥ አፈር ወደ ባሕሩ ቢወረወር ባሕሩን ያደፈርሰዋልን? የእኔ የኃጢአተኛው ወደ መቅደስህ መግባትስ ያንተን ባሕርይ ያሳድፈዋልን? በእውነት በስምዖን ቤት መዋልህ ስምዖንን ያነጻዋል እንጅ አንተን አያረክስህም። ማርያም ኃጥዕት እግርህን ያጠበችበት እንባ እሷን አነጻት እንጅ አንተን አላረከሰህም። ደም የሚፈሳት ሴት ልብስህን በመንካቷ ካንተ የወጣው ኃይል እሷን ጎበኛት እንጅ አንተን አልለወጠኸም። እኔም ወደ ቤትህ የምገባው ይህንን እያሰብሁ ነው። በተራራው ስብከት ጊዜ ተገኝቼ ስታስተምር ባልሰማህም፤ በደብረ ታቦር በተገለጥህ ጊዜ ክብርህን ካዩት መካከል ባልሆንም፤ በደብረ ዘይት እጅህን ጭነህ ከሾምኻቸው ውስጥ ባልመደብም አንተ ግን ለእኔ ምሕረት ማድረግን አትሰለችም። ወደ አንተ ባልመጣ እንኳን በተኛሁበት መጥተህ “ልትድን ትወዳለህ?” ማለትህ አይቀርም። ከሰማይ የወረድህልኝ ሆይ! ኢያሱ ለእስራኤል ርስታቸውን እስኪያወርሳቸው ፀሐይን እንዳቆምህለት በምድር ላይ ያለን ኃጥአን ልጆችህ ሰማያዊት ርስትህን ሳንወርሳት ፀሐይ አትጥለቅብን፤ ዕድሜአችን አይለቅብን።  አሜን!   @ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ

#ታህሳስ_3                                                                            #በዓተ_ለእግዚእትነ_ውስተ_ቤተመቅደስ             በብስራተ መልአክ የተወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከወላጆቿ ጋር እስከ ሦስት ዓመቷ ድረስ ከኖረች በኋላ እናቷ ቅድስት ሐና እና አባቷ ቅዱስ ኢያቄም ብፅዓት(ስእለት) ገብተው ስለወለዷት "አንድ ነገር ብትሆንብን ከእግዚአብሔርም ከልጃችንም ሳንሆን እንቀራለንና ሆዷ ዘመድ ሳይለምድ ፤ አፏ እህል ሳይወድ ወስደን እንስጣት" ተባብለው ይዘዋት ወደ ቤተ መቅደስ ሄዱ። ሊቀ ካህናቱ ዘካርያስም ደወል ደውሎ ሕዝቡን ሰበሰበና ነገሩን አሳወቀ። የምግቧ ነገርም አሳስቦት ስለነበር "እርሱን እንዴት እናድርግ" ብሎ አዋያቸው። ወዲያው ግን ሊቀ መልአክ ቅዱስ ፋኑኤል ሰማያዊ ሕብስትና ጽዋዕ ይዞ ሲረብ ታየ። ካህኑ ዘካርያስም ለእርሱ የመጣ መስሎት " ዛሬስ ፈጣሪ ክብሬን በሰው ፊት ሊገልጠው ነው" ብሎ ሊቀበል ተነሳ። መልአኩ ግን ወደ ላይ ራቀበት። የእርሱ ረዳት ስምዖንም "እንኪያስ ለእኔ የመጣ ይሆናል" ብሎ ቀረበ ከእርሱም ራቀበት። ካህናቱም ሕዝቡም ሁሉም በየተራ መልአኩን ቢቀርቡ ወደ ላይ ከፍ እያለባቸው ሄደ። የዚህን ጊዜ ሊቀ ካህኑ ዘካርያስ "ምናልባት ጥበበ እግዚአብሔር አይመረመርምና ለዚህች ብላቴና የመጣ እንደሆነ እንይ ፤ ሐና ሆይ ትተሻት እልፍ በይ" አላት። ሐናም ትታት እልፍ ብትል እመቤታችን ድክ ድክ እያለች እርሷን ስትከተል መልአኩ ፈጥኖ ወረደና አንድ ክንፉን አንጥፎ አንድ ክንፉን ጋርዶ በሰው ቁመት ልክ ከመሬት ከፍ አድርጎ መግቧት ዐረገ። ይህን ጊዜ ካህናቱ "የምግቧ ነገር ሀሳቡ ከተቀረፈልንማ እንቀበላት እንጂ" ብለው በዚህች በተባረከች ዕለት #ታህሳስ_3 ቀን ወደ ቤተ መቅደሱ አስገቧት። በዚያም በንጽሕናና በቅድስና ተጠብቃ 15 ዓመት እስኪሞላት ድረስ ውኃ ቀድታ እያጠጣች ሐርና ወርቅ አስማምታ እየፈተለች ቅዱሳን መላእክትም እየጎበኟት ሰማያዊ ሕብስትና ጽዋዕ ም  እየተመገበች ኖረች። እንኳን አደረሰን አደረሳችሁ

ወዳጄ ሆይ መልካም ወዳጅ ትባል ዘንድ እግዚአብሔር አምላክህን ካላወቅክና ካልመሰልከው በቀር ባልንጀራህን፣ ወንድምህን፤ እኅትህን ከዛም አለፍ ሲል እናትህን አባትህን ከዚህም ሲከፋ የገዛ ሚስትህን ጤናማ በሆነ መውደድ ልትወዳቸው አትችልም፡፡ ስለዚህ ወዳጄ ይህን እርከን ተከትለህ ወደ እውነተኛው ወዳጅነት እለፍ፡፡ “በእምነት ላይ በጎነትን፤ በበጎነት ላይ እውቀትን፤ በእውቀት ላይ ራስን መግዛትን፤ ራስንም በመግዛት ላይ መጽናትን፤ በመጽናትም እግዚአብሔርን መምሰል፤ እግዚአብሔርንም በመምሰል የወንድማማች መዋደድ፤ በወንድማማች መዋደድ ላይ ፍቅርን ጨምሩ” (2ጴጥ.1÷7) እንዲህ አድርጎ ራሱን በቅድስና ያበቃ ሰው ራሱን ከራስ ወዳድነት በጠራ መልኩ ይወዳል፡፡ ስለዚህም ባልጀራውንም መውደድ ለባልንጀራው መልካም ወዳጅ መሆን ይቻለዋል፡፡

እጅህ ላይ ባለው ነገር ከታመንህ እግዚአብሔር አምላክ በእጁ ውስጥ ያለውን ነገር ይሰጥሃል። በውስጥህ ያለውን አቅም መጠቅም ከቻልህ እግዚአብሔር የአንተ ያልሆነ ተጨማሪ አቅም ይሰጥሃል። ከእግረኞች ጋር ሳትደክም እኩል መራመድና መቅደም ከቻልህ እግዚአብሔር ፈረስን ለውድድር ይሰጥሃል። ኤር. 12፥5 የሚታዩ ኃጢአቶችን ለመዋጋት ታምነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር የተሸሸጉና የማይታዩ ኃጢአቶችን ድል እንድትነሣ ይሾምሃል። በሕፃንነትህ በልጅነትህ ለእግዚአብሔር የታመንህ ሆነህ ከተገኘህ እርሱ በወጣትነትህ በምታደርገው ውጊያ ውስጥ ታማኝነትን ያድልሃል። ልያን ለመቀበል ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር ራሔልን ሚስት አድርገህ ታገባት ዘንድ ይሰጥሃል። ዘፍ. 29፥27 በሲና ምድረ በዳ ለመቀመጥ ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር አምላክ የተስፋይቱን ምድር ከንዓንን ያወርስሃል። በዚህ በተወሰነና አጭር ሕይወት ታማኝ ሆነህ ከተገኘህ እግዚአብሔር መጨረሻ የሌለውን ዘላለማዊ ሕይወት ያድልሃል። ትልቁ ቁም ነገር በእጅህ ውስጥ የገባው ነገር ትንሽም ይሁን ጥቂት በእርሱ መታመን መቻልህ ነው። ስለሆነም ባለህ አንድ መክሊት ታምነህ ስትገኝ እግዚአብሔር አምስት መክሊቶችን በአደራ ይሰጥሃል። አንተ በሚታዩት ነገሮች ላይ ታማኝ ሆነህ ስትገኝ እርሱ በማይታዩት ነገሮች ላይ ይሾምሃል።በመሆኑም ዓይን ያላየችውን ጆሮ ያልሰማውን በሰው ልብ ያልታሰበውን መንግሥቱን ያወርስሃል። 1ኛ ቆሮ 2፥9 (#አቡነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ - #መንፈሳዊው_መንገድ መጽሐፍ #አያሌው_ዘኢየሱስ እንደተረጎመው።) @Ewnetgen

"ኃጢአት ሲሠራ ባየኸው ወንድም ላይ አትፍረድ፥ አንተ ግልጽ የወጣ ኃጢአቱን እንጅ በስውር ለካህን የሚነግረውን ንስሐ አታውቅምና። ስለዚህ የራስህን ድካም ተመልከት።" @Ewnetgen #ታላቁ_ቅዱስ_ባስልዮስ

ጊዜ ለመቆጠብ የሚባክን ጊዜ! .................   ...................... ብዙ ጊዜ በአገልግሎት የምናውቃቸው፣ነግህ ለኪዳን ሠርክ ለጸሎት ከአውደ ምሕረቱ የማይጠፉ። በጎደለው በኩል ቆመው የሚሞሉ፣ ለአገልግሎት የማይታክቱ ብዙ እህትና ወንድሞች ከሆነ ጊዜ በሗላ ሥራ ጀምረው፣ትዳር መስርተው...ወዘተ በአጋጣሚ አግኝታችሁ "ምነው ጠፋችሁ ከቤተክርስቲያን ?" ብላችሁ ስትጠይቋቸው። መልሳቸው ጊዜ አጣሁ ነው። ብዙዎቻችን ለእግዚአብሔር ጊዜ የምንሰጠው በችግር ጊዜ፣ባጣን ጊዜ፣ተስፋ በቆረጥን ጊዜ፣ በጎደለብን ጊዜ እንጂ በበረታን፣ በተሳካልን፣ በሆነልን ጊዜ አይደለም። የሚገርመው ለጸሎት ጊዜ፣ለቤተክርስቲያን ጊዜ መስጠት በማቆማችን ባናውቅም ፣ባይገባንም ጊዜ ለመቆጠብ ብለን ከእግዚአብሔር ቤት በመራቃችን በሕይወታችን ብዙ ነገር ይባክናል። ጥቂት ጊዜ ከአምላክ ፊት በመቆም የምናገኘው መልስ በአቅም ስንደክም ዘመናትን እናስቆጥራለን። አንድ  ታሪክ አለ ማሳያ የሚሆን" በአንድ ወቅት ሰውየው በደነዘ መጥረቢያ የዛፉን ግንድ ለመቁረጥ ይታገላል። መጥረቢያው እየነጠረ ከመመለስ ውጪ የተፈጠረ ነገር የለም። ይህን ሁኔታ ያስተዋለ አንድ መንገደኛ ሰው ጠጋ ይልና  << ወንድሜ መጥረቢያዉ እኮ ደንዟል አንድ ጊዜ አረፍ ብለህ ሳል ሳል ብታደርገው ጥሩ ነው " አለው። በደነዘ መጥረቢያ  እየታገለ ያለው ምስኪን ሠው መንገደኛውን ዞር ብሎ አየውና "እርሱን የምስልበት ጊዜ  የለኝም" በማለት በደነዘው መጥረቢያ መደብደቡን ቀጠለ ይባላል፡፡ ይኼ ሰው እኛን ይመስላል። መጥረቢያ ለመሳል የቆጠበውን ጊዜ ግንዱን ለመቁረጥ የወሰደበትን ጊዜ ተመልከቱ። መጥረቢያውን ለመሳል የሚወስድበት ጊዜ 10 ደቂቃ ሊሆን ይችላል። ባልተሳለ መጥረቢያ ቢቆርጥ ግን ሰዓታትን ይፈጅበታል።ጊዜውንም ጉልበቱንም ያባክናል። ወደ ቤተክርስቲያን በመሄድ፣በመጸለይ፣ቅዱሳት መጻሕፍን በማንበብ፣ በማገልገል የምናባክነው ጊዜ የለንም።በቀናችን ውሎ ካለን ጊዜ በቤተክርስቲያን የሚኖረን ቆይታችንም ጥቂት ጊዜ ነው።ያውም በብዙ የምናተርፍበት። ለጸሎትና ለአገልግሎት የምናውለውን ጊዜ እንደባከነ ልንቆጥረው አይገባም። ምክንያቱም በዓለም ሀሳብ እንዳንባክን፤የተሰጠን ነገር እንዲባረክ፣ በስራና በትዳር ሕይወታችን እንዳንዝል፤እግዚአብሔር ካዘጋጀልን መልካም ስጦታ እንዳንዘገይ ይረዳናል ይረዳናልና። ጊዜ ለመቆጠብ ብለን ከሕይወት ምእራፍ እንዳናረፍድ እንጠንቀቅ። ጊዜ የእግዚአብሔር ነውና

የታላቁ ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ #ሐብተማርያም እረፍት በዓል:-ኅዳር 26 ቀን 2016 ዓ.ም አቡነ ሐብተማርያም በሽዋ (ቡልጋ) ከአባታቸው ፍሬ ቡሩክ ከእናታቸው ቅድስት ዮስቴና ነው የተወለዱት፣ ወላጆቹ በተለይም እናቱ ከማግባቷ በፊት መናኝ ነበረች፣ ጻድቁን እንደምትወልድ በበቃ ባሕታዊ ተነግሯት ጻድቁን ወልዳ በጽድቅ ኑሮ ከኖረች በኋላ  7 አክሊላትን ተቀብላ በክብር አርፋለች፣  ጻድቁ ከእናታቸው ጋር ቆመው ሲያስቀድሱ "እግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ" ሲባል ይሰማሉ፤ ይህንንም በሕፃን አንደበታቸው ይዘው ሌሊት ሌሊት እየተነሱ "ማረን እባክህን" እያሉ ይሰግዱ ነበር፣ ትንሽ ከፍ ብለው በእረኝነት ሳሉም ፍጹም ተሐራሚና ጸዋሚ ነበሩ፣ ጸጋው ስለ በዛላቸውም ልጅ ሆነው ብዙ ተአምራትን ሠርተዋል፤ የፈጣሪውን ስም ያቃለለውን አንድ እረኛም በዓየር ላይ ሰቅለው አውለውታል፣ ለአካለ መጠን ሲደርሱ ወደ ትምህርት ቤት ገብተው ትምህርትን ከቀሰሙ በኋላ መንነዋል፣ በታላቁ አባት በአባ መልከጼዴቅ እጅ ምንኩስናን ከተቀበሉ በኋላም ብዙ ትርፋትንና ተጋድሎን ሠርተዋል፡፡ ለአብነትም :- ባሕር ውስጥ ሰጥመው 500 ጊዜ ይሰግዳሉ፣ በየቀኑ 4ቱን ወንጌልንና 150 መዝሙረ ዳዊትን ይጸልያሉ፣ በ40 ቀናት፣ ቀጥሎ በ80 ቀን አንዴ ብቻ ይመገባሉ፣ ምግባቸውም  ሣርና ቅጠል ነው፣ በየዕለቱ ያለ ማስታጎል ማዕጠንት ያሳርጋሉ፣ ዘወትር በንጽሕና ቅዱስ ሥጋውን ይበላሉ፣  ክቡር ደሙን ይጠጣሉ፣ በልባቸው ውስጥ በፍጹም ቂምን፣ መከፋትን አላሳደሩም፣ "ረአዬ ኅቡዓት" በመባል ይታወቃሉ፣ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ትዕዛዝ ቦታውን ሲባርኩት ሦስት አጋንንት በጸሎቱ ሥልጣን የታሠሩላቸው ታላቅ ጻድቅ ናቸው፣ "ጽድቅና ትሩፋት እንደ አቡነ ሐብተ ማርያም " ጌታችን ለጻድቁ የእሳትና የብርሃን ሠረገላን ሰጥቷቸው በዚያ እየበረሩ ወደ ኢየሩሳሌምና ወደ ተለያዩ ቦታዎች ይሔዱ ነበር፣ ከብዙ የተጋድሎ ዘመናት በኋላም የክብር ባለቤት መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዕላፍ መላእክትን አስከትሎ መጥቶ እንዲህ አላቸው፤ "ስለ እኔ ረሃብና ጥምን ስለ ታገስክ፣ ስለ ምናኔህ፣ ስለ ተባረከ ምኩስናህ፣ ስለ ንጹሕ ድንግልናህ፣ ቂምና በቀልን ስላለመያዝህ፣ ስለ ንጹሕ ክህነትህና ማዕጠንትህ፣ ቅዱስ ወንጌልን በፍቅር ስለ ማንበብህ ሰባት አክሊላትን እሰጥሃለሁ" በሰማይም ከመጥምቁ ዮሐንስ ጎን 500 የዕንቁ ምሰሶዎች ያሉበትን አዳራሽ ሰጥቼሃለሁ፣በስምህ የሚለምኑ፣ በቃል ኪዳንህ የሚማጸኑትንም ሁሉ እንድምርልህ "አማንየ በርእስየ" ብዬሃለሁ አላቸው፡፡ ቅዱሳን መላእክትም ሐብተ ማርያም ወንድማችን ሲሉ አቀፏቸው፣ ጌታ ግን በዚያች ሰዓት አንድም ሦስትም ሆኖ ታያቸውና አቅፎ ሦስት ጊዜ ሳማቸው፣  ከፍቅሩ ጽናትም የተነሳ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለየች፣ በዝማሬም ወሰዷት፣ ለአባታችን ከተሰጣቸው ቃል ኪዳኖች ውስጥ አምስት መቅሰፍቶች የማስወገድ ሥልጣን ተሰጥቷቸዋል እነርሱም መብረቅ፣ ቸነፈር፣ ረሃብ፣ ወረርሽኝ፣ የእሳት ቃጠሎ ናቸው፣ በተሰጣቸው ቃል ኪዳንም እነዚህን    መቅሰፍቶች የሚያርቁ በመሆናቸው ከጥንት ጀምሮ እስከ አሁን በደብረ ሊባኖስ ገዳም እነዚህ አምስቱ መቅሰፍቶች እንዳይቀርቡ የሐብተ ማርያም ካህናት ከኅዳር 1ቀን እስከ ኅዳር 7 (አሥር) ማዕጠንት ያጥናሉ። ደብረ ሊባኖስ ገዳምም ለደብረ ይሰበይ አቡነ ሐብተማርያም ገዳም አንድ በሬ ስጦታን ያበረክታሉ፣ በዛሬው ዕለት በኅዳር 26 ባረፈ ጊዜ፤ ካህናት በመልካም ልብስ ገንዘው፤ በዝማሬ ፥ በማኅሌት ከቅዱስ አባታችን ከአቡነ ተክለሃይማኖት አጽም ጋር በጻድቁ መቃብር ቀበሩት፡፡ የጻድቁ አባታችን የጸሎታቸው በረከት አይለየን።

#መጽሐፍ_ቅዱስ በአንድ ተራራማ ስፍራ እርሻ በማረስ ከልጅ ልጁ ጋር የሚኖር አንድ ሽማግሌ ነበር፡፡ ይህ ሽማግሌ ዘወትር ፀሐይ ብርሃኗን ስትፈነጥቅ እየተነሳ መጽሐፍ ቅዱስን ያነባል፡፡ የልጅ ልጁ የአያቱን ተግባር ይከታተል ስለነበር እሱም ያያቱን ፈለግ በመከተል ጠዋት ጠዋት እየተነሳ መጽሐፍ ቅዱን ማንበብ ጀመረ፡፡ አንደ ቀን ታድያ አያቱን “አባባ መጽሐፍ ቅዱስን ለማንበብ እየሞከርኩ ነበር፡፡ ነገር ግን ልረዳው አልቻልኩም ደግሞም አንብቤ እንደጨረስኩ ወዲያውኑ እረሳዋለሁ እናም እንድረዳውና እንዳልረሳው ምን ማደረግ አለብኝ?” ሲል ጠየቀ፡፡ ሽማግሌው ምንም ድምጽ ሳያሰሙ “ከሰሉን ወደ ምድጃው ጨመሩና እንካ ይሄን የከሰል ቅርጫት ይዘህ ወንዝ ውረድና ውሃ ይዘህልኝ ተመለስ” አሉት፡፡ ልጁ ትዛዙን ለመፈጸም ወደወንዝ ወርዶ ውሃውን ይዞ ሊመለስ ቢመክርም ቅርጫቱ ውሃውን እያንጠባጠበ ቤት ከመድረሱ በፊት ፈሶ አለቀበት፡፡ ሽማግሌው የልጁን ሁኔታ እያስተዋሉ “አሁን ለሁለተኛ ጊዜ ይዘህ ስትመጣ ግን ፈጠን ፈጠን ብለህ ተመሰለስ ብለው” ድጋሜ ላኩት፡፡ አሁንም ልጁ እንደተነገረው በፍጥነት ውሃውን ቀድቶ ሊመለስ ቢሞክርም ቤቱ ሳይደርስ ውሃው ፈሶ አለቀበት፡፡ አያቱንም “በቅርጫት ውሃ ማምጣት ስለማይቻል ሌላ መያዥ ይስጡኝና ላምጣ” ሲል ጠየቀ፡፡ ሽማግሌ አያቱም “እኔ የምፈልገው የቅርጫት ውሃ ነው፡፡ ጠንክረህ ባለመሞከርህ ነው ፈሶ ያለቀብህ” በማለት እንደገና ላኩት፡፡ በዚህ ጊዜ ልጁ በቅርጫት ውሃን ማምጣት እንደማይቻል ቢያውቅም ለአያቱ ታዛዥነቱን ለማሳየት ከበፊቱ ፈጥኖ ለማምጣት ሲሞክር ውሃው ፈሶ ስላለቀበት ባዶውን ቅርጫት እያሳየ “ተመልከት አባባ! እዲሁ ነው የምደክመው እንጅ እኮ ጥቅም የለውም” አለ፡፡ ከዚህ ጊዜ ምልልስ በኋላ ሽማግሌው “እስኪ ቅርጫቱን ተመልከተው” አሉት፡፡ ልጁ ቅርጫቱን ሲመለከት ከዚህ በፊት የማያውቀው ቅርጫት ይመስል ቅርጫቱ የተለየ ሆነበት የከሰል መያዣ እያለ በጅጉ የቆሸሸ ነበር፡፡ አሁን ግን ሙልጭ ብሎ ጸድቷል፡፡ ውስጡን ሲመለከተው ከመንጻቱ የተነሳ የበፊቱ ቅርጫት አልመስለው አለ፡፡ ስለዚህ ልጄ መጽሐፍ ቅዱስን ስታነብ የሚሆነው እደሱ ነው፡፡ ላትረዳው ትችል ይሆናል ወይም ደግሞ ያነበብከውን ሁሉንም ነገር ላታስታውሰው ትችል ይሆናል ዳሩ ግን ባነበብክ ቁጥር ለውጨኛው የሚተርፍ ውስጣዊ ንጽህና እያመጣህ መሆኑን አትዘንጋ የመንፈስ ሥራ እንደዚህ ነው በማለት አስተማሩት፡፡ (ከምስጋናው ግሸን ወልደ አገሬ)

​​ኅዳር 24 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ኅዳር ሃያ አራት በዚች ቀን የሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ የበዓላቸው መታሰቢያ ነው፣ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር ያጠኑበት ነው፣ የአቡነ ዜና ማርቆስ ልደታቸው ነው። ሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ኅዳር ሃያ አራት በዚህች ቀን በእግዚአብሔር ዙፋን ዙሪያ የሚኖሩ የሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ የበዓላቸው መታሰቢያ ነው። እሊህም ሥጋ የሌላቸው ረቂቃን የእውነት ካህናት የሆኑ ከቅዱሳን ሁሉ በላይ የሆኑና ከሰማይ ሠራዊት ሁሉ ከፍ ከፍ ያሉ ናቸው እነርሱም ለእግዚአብሔር ቀራቢዎች በመሆን ለሰው ወገን የሚማልዱ ከእጃቸው ውስጥ ካለ ማዕጠንት ጋርነ እንደ ዕጣን የቅዱሳንን ጸሎት የሚያቀርቡ ናቸው ያለእነርሱም አቅራቢነት ጽድቅና ምጽዋት ወደ እግዙአብሔር አይቀርብም። ወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ እንዲህ ብሎ እንደተናገረ። በዙፋኑ ዙሪያ ሃያ አራት መንበሮች አሉ በእነዚያ መንበሮች ላይም ሃያ አራት አለቆች ተቀምጠዋል ነጭ ልብስ ለብሰዋል በራሳቸውም ላይ የወርቅ አክሊል አለ። ሁለተኛም እንዲህ አለ ሌላም መልአክ መጥቶ በመሠዊያው ፊት ቆሞ የወርቅ ጽንሐሕ ይዟል በመንበሩ ፊት ባለ በወርቁ መሠዊያ ላይም የቅዱሳንን ሁሉ ጸሎት ያሳርግ ዘንድ ብዙ ዕጣንን ሰጡት ። የዕጣኑም ጢስ ከቅዱሳኑ ጸሎት ጋር በዚያ መልአክ እጅ ወደ እግዚአብሔር ፊት ዐረገ። የነበረ የሚኖር የአማልክት አምላክ እግዚአብሔር ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ነው እያሉ በመዓልትና በሌሊት ዕረፍት የላቸውም ። እሊህም እንስሶቹ ለዘላለሙ ሕያው ለሚሆን በዙፋን ላይ ለተቀመጠ ለሱ እንዲህ እያሉ ክብር ምስጋና አቀረቡ። እሊህ ሃያ አራቱ አለቆች አክሊላቸውን በዙፋኑ ፊት አውርደው ለዘላለሙ ሕያው ለሚሆኑ በዙፋን ላይ ለተቀመጠ ለእሱ ሰገዱለት ። አክሊላቸውንም ወደ ዙፋኑ ፊት ወስደው አቤቱ ፈጣሪያችን ኃይልና ምስጋና ክብር ላንተ ይገባል ይሉታል አንተ ሁሉን ፈጥረሃል የተፈጠረውም ሁሉ በአንተ ፈቃድ ይኖራልና ። እነርሱ በእግዚአብሔር ዘንድ በባለሟልነት እጅግ የቀረቡ መሆናቸውንና ስለሁላችን የአዳም ልጆች ስለሚለምኑና ስለሚማልዱ ከብሉይና ከሐዲስ የከበሩ መጻሕፍት ምስክር ሁነዋል ስለዚህም የበዓላቸውን መታሰቢያ እናደርግ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አዘዙ። ቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር እንዳጠኑ፡- አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ መጥተው በሐይቁ ዳር ቆመው ሳለ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ተገልጦላቸው ነው በእግሩ በውኃው ላይ እየሄደ እያሳያቸው ተከትለውት እንዲሄዱ የነገራቸው። አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖትም መልአኩን ተከትለው ሐይቁን በእግራቸው ተራምደው ተሻግረው አቡነ ኢየሱስ ሞዐን አገኟቸው፡፡ እርሳቸውም አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ እርሳቸው እየመጡ እንደሆነ በመንፈስ ዐውቀው ነበርና ሲያገኟቸው በጣም ተደስተው ከተቀበሏቸው በኋላ አመነኩሰዋቸዋል፡፡ ከዚህም በኋላ አባታችን በዚያው በሐይቅ በታላቅ ተጋድሎ መኖር ጀመሩ፡፡ አክፍሎትንም በየሳምንቱ ያከፍላሉ፣ ከእሁድና ከቅዳሜ በቀር ምንም አይቀምሱም ነበር፡፡ በእነዚህም ዕለት የአጃ ቂጣ ወይም የዱር ቅጠል ይመጉ ነበር፡፡ ወዛቸው እንደ ውኃ ፈስሶ ምድሪቷን እስኪያርሳት ድረስ እስከ 70 ሺህ ስግደትንም በመስገድ ራሳቸውን እጅግ አደከሙ፡፡ በእነደዚህ ዓይነቱ ተጋድሎ ላይ ሳሉ ነው ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ድንገት ነጥቆ ወስዶ ከሥሉስ ቅዱስ ዙፋን ፊት ያቆማቸው፡፡ ከዚህ በኋላ ስለሆነው ነገር ራሳቸው አባታችን ተክለ ሃይማኖት ሲናገሩ ‹‹…ከዚህ በኋላ መልአኩ ወደ ሰማይ አውጥቶ ከመጋረጃው ውስጥ አስገብቶ ከሥላሴ ዙፋን ፊት አቆመኝና ሰገድኩለት፡፡ ከዚያ አስቀድሞ በማላውቀው በሌላ ምስጋና አመሰገንኩት፡፡ ‹ተክለ ሃይማኖት ክፍልህ ከ24ቱ ካህናቶቼ ጋር ይሁን› የሚል ቃል ከዙፋኑ ውስጥ ወጣ፡፡ የወርቅ ጽና አምጥተው ሰጡኝና ከእነርሱ ጋር አንድነት አጠንሁ፡፡ ምስጋናዬ ከምስጋናቸው ጋር ልብሴም እንደልብሳቸው ሆነ፡፡ ፈጣሪዬንም በሦስትነቱ ተገልጦ አየሁት፡፡ በጸሎትህ የሚታመን ሰው ሁሉ ስለአንተ ይድናል አለኝ…..›› (ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገጽ 216-223) ይህንን ታላቅ በዓል ነው ዛሬ የምናከብረው፡፡ አቡነ ተክለሃይማኖት እንኳን አንደበታቸው የለበሱትም ልብሳቸውም ጭምር እግዚአብሔርን በሰው አንደበት እንደሚያመሰግን በቅዱስ ገድላቸው ላይ ተጽፏል።

❤ህዳር 21 ታቦተ ጽዮን የምትከብርበት ዕለት ሰው ሁሉ እናታችን ጽዮን ይላል መዝ 86+5 ጽዮንን የሚጠሉ ሁሉ  ይፈሩ መዝ 128+5 እግዚአብሔር ጽዮንን መርጧታልና ይላል መዝሙረኛው እግዚአብሔር የመረጣትን መጥላት ከእግዚአብሔር ጋር መጣላት ነው ❤በተለየ መልኩ የምናከብርበት ምክንያት፦ 1 ታቦተ ጽዮን በምርኮ በሄደችበት በሀገረ ፍልስጤም ዳጎን የተባለ የአህዛብን ጣኦት አድቅቃ በድል የተመለሰችበትን ዕለት ነው 2 ታቦተ ጽዮን ንጉሥ ሰሎሞን ወደ ሠራላት ቤተመቅደስ በክብር የገባችበትን ዕለት ነው 3 አበው  ነቢያት ስለእመቤታችን በተለያየ አምሳል ያዩበት ለምሳሌ፦ ነቢዩ ዕዝራ በሃገር መንፈሳዊት፣ ነቢዩ ሕዝቅኤል በተዘጋች ቤተ መቅደስ፣ ነቢዩ ዘካርያስ በተቅዋመ ወርቅ ያዩበትን ዕለትነው 4 ቀዳማዊ ምኒሊክ ከዐሥራ ሁለቱ ነገደ እስራኤል የበኩር ልጅ ጋር ሊቀ ካህናቱን አዛሪያስንና ታቦተ ጽዮንን ይዞ አክሱም የደረሰበትን ዕለት ነው 5  በአብርሃ ወአፅብሃ ዘመነ መንግሥት ክርስትና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሃይማኖት ሆኖ አዋጅ የታወጀበትን ዕለት ነው 6 ለታቦተ ጽዮን ማደሪያ አብርሃ ወአጽብሃ በወርቅና በዕንቁ ያሠሩት ባለ አሥራ ሁለት ክፍል ቤተ መቅደስ ለመጀመሪያ ጊዜ ቅዳሴ ቤቱ የተከበረበት ዕለት በመሆኑ ነው 7 በዘጠነኛው መቶ ክፍለ ዘመን ዮዲት ጉዲት አብያተ ክርስቲያንን ስታቃጥል ታቦተ ጽዮንን ይዘው ወደ ዝዋይ ሀይቅ ከተሰደዱ በኋላ ዘመነ ሰላም ሲጀመር አክሱም በነበሩ ካህናት አስታዋሽነት ከዝዋይ ወደ አክሱም የገባችበት ዕለት በመሆኑ ነው መልካም በዓል

"ሰይጣን ክፉ ነው፡፡ ቢሆንም ደካማ ነው፡፡ እርሱ ጋር ካለው ኃይል እኛ ጋር ያለው ጸጋ እግዚአብሔር ይበልጣልና፡፡ እኛው ራሳችን በፍቃዳችን ከረድኤተ እግዚአብሔር እያራቅን በሄድን ቁጥር ግን እርሱ እየፈራ እየተንቀጠቀጠም ቢሆን እየቀረበ ይመጣል፡፡ ቤቱ ዘበኛ ከሌለው አልያም እንዲሁ ክፍት ከሆነ ሌባ እየፈራም ቢሆን እንደሚገባ፡፡ ለቀዳማይቱ ሔዋን ያደረገውም እንደዚህ በቀስታ ነበር፡፡ አስቀድሞ በኀልዮ (በሐሳብ) ይሞክራል፡፡ በጣም መንቻካ ከመሆኑ የተነሣም ይህን ደግሞ ደጋግሞ ይደርጓል፡፡ ሐሳቡን ለመቀበል ዝግጁዎች እንደሆንን ሲረዳም ሐሳቡን ፈጥነን ወደ ገቢር (ተግባር) እንድንለውጠው ሹክ ይለናል፡፡ ይህም እንደ ሐሳቡ ደጋግሞ ያደርጓል፡፡ በተለይ ምቹ ሁኔታዎችን ሲመለከት ይህን ደጋግሞ ይሞክራል፡፡ እንደ ተዘጋጀን ሲያውቅም ክፉ መርዙን እፍ ይልብናል፡፡ ከዚያም ሙሉ ለሙሉ ይቆጣጠረናል፡፡ በጣም የሚገርመው ደግሞ ከወደቅን በኋላ የመጀመርያው ከሳሻችን እርሱ መሆኑ ነው፡፡ “አሁን አንተ መንፈሳዊ ነኝ ትላለህ፤ ሆኖም ደግሞ እንዲህ በመሰለ ርካሽ ኀጢአት ትወድቃለህ” እያለ ሰላም ያሳጣናል፡፡ ለሁሉም ግን ወደ እግዚአብሔር መመለሱ ይሻላል፡፡ በረከታቸው ይደርብንና ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ እንዳሉት “የሰነፍ አእምሮ የሰይጣን ቤተ ሙከራ ነው” እንዳሉት ነፍሳችንን ቃለ እግዚአብሔርን አናስርባት፡፡ በየጊዜው ምክርን ከሐኪሞቻችን (ከንስሐ አባቶቻችን) እንሻ፡፡" (መቅረዝ ዘተዋሕዶ)

ልጆቼ፦ እግዚአብሔርን በእምነት በፀሎት እንሻው ከእኛ የጠፋ ገንዘባችንን ነቅተን ተግተን በብዙ ድካም እንድንሻው እንዲሁ ሃሳባችንን ወደ እግዚአብሔር ልናቀርብ ይገባናል፤ ልጃችን ቢጠፋብን ፈልገን በቅርብ ያላገኘነው እንደሆነ ሃይላችንን በድካም ድካማችንን በሃይል የምንለውጥ አይደለንምን? የጠፋውን ልጃችንን ስለመፈለግስ እናገኘው ዘንድ የብሱን በእግር ባህሩን በመርከብ የምንዞር አይደለንምን? ፈልገንም ያገኘነው እንደሆነ ዳግመኛ እንዳይጠፋብን ለመጠበቅ እንተጋ የለምን? እንዲህ ከሆነ መሓሪ እግዚአብሔርን በእምነትና በፀሎት እንሻው ዘንድ ምን ያህል ይገባን ይሆን? እግዚአብሔርን ፈልጉት ነጋዴ ወርቅ ቢጠፋበት ወርቁን ያገኘው እንደሆነ ሁሉን ቦታ እንደሚፈልግ እንዲሁ እግዚአብሔርን ፈልጉት እናት ልጇ ቢጠፋባት እስክታገኘው ድረስ አርፋ እንደማትቀመጥ እንዲሁ እግዚአብሔርን ፈልጉት እግዚአብሔርን እሹት ፈልጉት እስክታገኙት ድረስ በእምነት በፀሎት እሹት፡፡” ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ