977
Subscribers
No data24 hours
-27 days
-730 days
Posts Archive
ከጓደኛዬ ጋር ራት ለመብላት፣ በሻማ መብራት ስንንደፋደፍ፣ ውሀ መጣች፣ የመታጠቢያ ቤቱ ውሀ፣ በጨለማው ድንገት ፊሽሽሽሽሽ!!! ሲል፣ ሁለታችንም፣ አንድ ላይ፣ መጣ! መጣ! አልን። እናቲቱ እና ልጆቿምጋ፣ ውሀ መጥቶ ይሆን?!ለእሷ እና ለልጆቿ ብዬ፣ ተስፋ አደረግኩ።
ቢሄድም፣ ይመጣል!
ቢጠፋም ይበራል!!!
(አቃቂ በሰቃ)
#ሰላም_ግቢ___ኢትዮጵያ❗️
(አፈረሱት አሉ … 8)
ኢትዮጵያን አገኘኋት። ወንድና ሴት ህፃን ልጆቿን ይዛ በዝናብና በጨለማ ውስጥ ችላ ስትጓዝ ሀገሬን በአይኔ በብረቱ አየኋት። ችላ መጓዟን ባይ ከሎሬት ጸጋዬ ስንኝ ተዋስኩና...
«አዎን መቻል ባንቺ ያምራል፥» አልኳት።
«አዎን መቻል ባንቺ ያምራል
ያን የትዝታ ሰቀቀን
ያን የልጅነት ሰመመን
ምንም በውል ባንደርስበት፥ ጭላንጭሉ እየታወሰን
ውል ሲል እንዳልጠፋ ቀን
ከዓመት ዓመት ተሽጋግረን፥ አዳዲስ ዘመን ሲሰለፍ
ሰንበሌጡ ሲንተረከክ፥ የአዝመራ እሸት ሲትረፈረፍ
የማር እሸት እንቁረጥ ተይ፥ የጥቅምት አበባ እንቅጠፍ
ነይ ሸጎዬ አብረን እንግዘፍ »
ብዬ ከሎሬቱ «አቴቴ ዱብራ ኦሮሞ» ግጥም ተውሼ በጎ በጎውን ተመኘሁላት። ይሄ ሰው አበደ እንዴ? ከማለትሽ በፊት ላብራራልሽ ተከተይኝ።
“አፈረሱት አሉ” የሚሉ ወጎች በተከታታይ ሳወጋሽ አልነበር? መቼም ወጎቹ አትለቁ ተብለው ተመርቀዋል መሰል የሚቀጥሉበት ምክንያት አልጠፋ አለ። ለነገሩ የግንባታና የፈረሳ፣ የገንቢና የከሳሽ፣ የአፍራሽና አዳሽ ነገር.... ሳይቋጭ የኔ ወግ ለምን በአጭሩ ይቋጫል? ኢንሻአላህ እስካለን ይቀጥላል!
እናልሽ የቀድሞዎቹን ተከትሎ፡ በአንድ ወዳጄ ጋባዥነት ኢትዮጵያን ያየሁበት ግሩም ታሪክ ተወለደ። እሱን ነው ዛሬ በራሴ መንገድ ላጋራሽ የወደድኩት። ደግሞም የኔውም ያንቺም መንገድ በመሆኑ ከመንገዳችን ጋር ያገናኘናል። በእርግጥ አዲስና የማናውቀው ይመስለናል። ግን አዲስ ነገር አይደለም አልተባባልንም? እንደዛ ነው ይሄም። ነይ ወደ አዲሱ ሰፈር ሄደን፣ ኢትዮጵያን እንያት።
#ኢትዮጵያን_አየኋት❗
የጓደኛዬ ቤት ያላለቀም ቢሆን፣ ሶስት ፎቅ ያለው መኖሪያ ነው።
ሶስተኛው ፎቅ ላይ፣ ዙሪያውን በግንብ የታጠረ፣ የሰፈሩን ብዙ ክፍል የሚያሳይ፣ ሰገነት ነገር አለው። ቤቱ በመጣሁ ቁጥር፣ ከጓደኛዬ ጨዋታ እኩል የሚያዝናናኝ አንዱ ጉዳይ፣ ሰገነቱ ላይ ሆኖ፣ ሰፈሩን ከላይ ታች ማየት እና መመሰጥ ነው።
ነፋሱ ደስ ይላል፣ ከፍታው ያሳሳል፣ እይታው ይመስጣል፣ ብዙ ያሳስባል። ስለ ራስ፣ ስለ ሰፈር፣ ስለ ሀገር፣ ስለ አለም ሁሉ።
ሰፈሩ፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተገነባ፣ ከከተማ ወጣ ያለ፣ ሁሉም አይነት የቤት ግንባታ ደረጃ (የታጠረ ባዶ መሬት፣ መሰረቱ ብቻ የተገነባ ትንሽ መሬት፣ ስላቦቹ ያለቁለት ግንባታ፣ ብሎኬቱ ተገንብቶለት፣ ፊኒሺንግ ብቻ የቀረው ቤት፣ (እንደ ጓደኛዬ) ሁሉ ነገሩ (ከአጥር እስከ መናፈሻ፣ ከውሻ ቤት እስከ መኪና ማቆሚያ፣ ከአደገኛ አጥር እስከ መጠባበቂያ ሮቶ …) አልቆለት፣ ከሩቅ የሚያበራ ቤት፣ በየአቅጣጫው የተገጠገጠበት፣ እና በርካታ ሰው የሚኖርበት ሰፈር ነው።
መንገድ፣ ከአስፋልት ጀምሮ፣ እስከ ጥርጊያ፣ እስከ ኮብል ስቶን፣ እስከ አሸዋ፣ እስከ አፈር፣ በየመልኩ የተሰራለት፣ 24 ሰአት ግንባታ የማይቆምበት ሰፈር ማለት ይቻላል።
በነገርሽ ላይ እየተገነባ ያለ ቤት፣ ሰፈር እየፈረሰ እንደሚመስል ማሳያም ሆኖ እየታየኝ ነው። ይህ አዲስ ሰፈር ነው። ግንባታዎች እዚህና እዛ በመጀመራቸው ምስቅልቅል ያለ ገፅታ ጎልቶ ይታያል። ካላስተዋልሽው እየፈረሰ ያለ ሰፈርም ይመስላል። …
ከጓደኛዬ ጋር፣ ስለ ሰፈር፣ ስለ አገር፣ ስለ ኢኮኖሚ፣ ስለ ፖለቲካል ኢኮኖሚ፣ ታች ስንጫወት ቆይተን፣ እንደተለመደው፣ ብቻዬን ወደ ሰገነቱ ስወጣ፣ ምሽቱ እንደ መጀመር ብሏል፣ ዝናብ እያካፋ ነው፣ ሰሞኑን እንዲሁ እያካፋ ስለሆነ፣ የውስጥ ለውስጥ መንገዱ፣ እንደ መጨቅየት ብሏል፣ ጭርም ብሏል።
አልፎ አልፎ ካልሆነ፣ ሰፈርተኛ ወይም እንግዳ፣ በመንገዱ አይታይም። ውሾች፣ ካፍያው፣ ነፋሱ እና ብርዱ ምንም ሳይመስላቸው፣ እዚያ እዚህ፣ ያለ ድምጽ ይንቀሳቀሳሉ፣ ከካፍያው ይጠለላሉ፣ ወደ ካፍያው ይወጣሉ። የነፋሱ ሀይል በረታ፣ ካፍያው እየጨመረ መጣ፣ መንገዱ ይበልጥ ተራቆተ፣ ጭለማውም ከበድ እያለ ሄደ።
ወዲያ ማዶ፣ ወደ ላይ፣ ወደ ታች፣ የማይቆም ግንባታውን፣ የቤቶቹን፣ የመጠናቸውን፣ የቅርጻቸውን መለያየት፣ ከባዶ መሬት ተነስተው፣ ድንገት ሰፈር ሆነው መብቀላቸውን፣ በማንም ያልተነገረ ታሪካቸውን፣ ዝምታቸውን በተመስጦ እያማተርኩ ሳለ፣ አንድ እናት፣ ከላይ ከኮብል ስቶኑጋ ታጥፋ፣ ወዲህ ወደ ሰፈሩ ገባች።
ሁለት፣ ወንድ እና ሴት ህጻናት አስከትላለች (ልጆቿ መሆን አለባቸው መቸስ!) ወንዱ 10፣ ታናሹ፣ 6-7 ገደማ ቢሆናት ነው።
ሴትየዋ (እናታቸው) ዣንጥላ ብትይዝም፣ ወንዱ ልጅ ካፍያውን እንደ መዝናኛ ስለቆጠረው፣ እንደ መዝለል እንደ መደነስ እያለ፣ ከዣንጥላው ውጭ ነው የሚራመደው፣ እናቱ፣ ግራ ቀኝ እያየች፣ ልጆቿን ወደቤታቸው ከመምራትም በላይ፣ ከጨርቅ የተሰፋ ቦርሳ፣ በጀርባዋ አንግታለች።
ህጻኗ ልጅ፣ የእናቷን እጅ አጥብቃ መያዝ ብቻ ሳይሆን፣ እናቷ ላይ ጥብቅ ብላ፣ ከካፍያው ተጠልላ ነው የምትጓዘው። በዚህ ዝናብ፣ በዚህ ከፊል ጨለማ፣ በዚህ ጭር ያለ ሰፈር፣ ውሾቹ፣ ከግራ ከቀኝ እየጮሁባቸው፣ እናት ልጆቿን፣ ግራ ቀኝ አስከትላ፣ የጨርቅ ቦርሳውን በጀርባዋ አዝላ፣ ያለምንም መሸበር፣ ወደ ታች ሰፈር እየወረደች ነው።
ብቸኝነቷ አልከበዳትም፣ ጨለማው አላስፈራትም፣ በጀርባዋ የያዘችው ቦርሳ አልከበዳትም። ሴት ልጇን አጥብቃ እንደያዘች፣ ወንድ ልጇን፣ ና ዝናብ እንዳይመታህ! እያለች እየገሰጸች፣ ቦርሳዋን ተሸክማ፣ ዣንጥላዋን ይዛ፣ መንገዷን ትቀጥላለች።
እናቲቱ፣ ልክ እኔ ያለሁበትን የጓደኛዬን ቤት ሰገነት አልፋ ስትሄድ፣ እና የሰገነቱን መደገፊያ ይዜ፣ በከፍተኛ መመሰጥ ሳያት፣ ይህች እናት፣ ድንገት፣ ኢትዮጵያን መስላ ታየችኝ። ተገረምኩ፣ አዘንኩ፣ ሩ….ቅ አሰብኩ።
ሰፈሩንም ዞር ዞር ብዬ ሳየው፣ ቁርጥ፣ ኢትዮጵያን መስሎ ታየኝ፣ የቅርቡም ሆነ የሩቁ አንድ መልክ፣ አንድ ትርጉም ነው ያላቸው፣ አንድ ታሪክ ነው የሚናገሩት።
እናትየዋ፣ ልጆቿን ይዛ፣ ቦርሳዋን ተሸክማ፣ ቤት ለመድረስ፣ ጉዞዋን ቀጥላለች፣ ካፍያው ጭፍ ጭፍ እያለ ቢቀጥልም፣ ጨለማው እየበረታ ቢሄድም፣ ብርዱ ቢያይልም፣ የውሾቹ ጩኸት ባይቆምም፣ ከነ ልጆቿ፣ ከነ ሸክሟ፣ ቤቷ መድረሷ አይቀርም።
ካፍያው መቆሙ፣ ዝናቡ ማባራቱም አይቀርም፣ ጧት ሲነጋ፣ ጨለማው ብርሀን ይሆናል፣ ሙቀት ብርዱን ይተካል፣ የተኛው ሰፈር ዳግም ይነቃል።
እናትየዋ፣ አንድ ሶስት ቅያሶች ወርዳ፣ ወደ ቤቷ ስትታጠፍ፣ ምንም ሳይታወቀኝ፣ ሰላም ጊቢ ኢትዮጵያ! አልኩ፣ በአፌ፣ ይሁን በሆዴ።
ባሰብኩት ነገር ልቤ ተነካ፣ የእናትየዋ ሁኔታ፣ ሰፈሩ፣ ዝናቡ፣ ጨለማው፣ አስተከዘኝ።
ጓደኛዬ ደንገት ከወደታች እየተጣራ፣ መሸኮ፣ እራት አንበላም እንዴ! ሲለኝ፣ ከትካዜዬ ሳልወጣ፣ እንደ ቀልድ፣ ኢትዮጵያን አየኋት! አልኩት።አልሰማኝም፣ ወይም፣ ያልኩት ነገር አልገባውም፣ እኔ ግን ከልቤ ነው፣ ያች እናት፣ ኢትዮጵያ ናት፣ ሰፈራቸውም ኢትዮጵያ!
ራት አቅርቤአለሁ ና! አለኝ ጓደኛዬ ከታች። ኢትዮጵያን አየኋት ሰምተኸኛል! አልኩት ደግሜ (አልሰማኝም)
ውሀ የለም፣ ከጄሪካኑ ቀድተህ ታጠብ! ራት እንብላ! ዝናቡ ቆመ፣ ቀኑ ሙሉ በሙሉ ጨለመ፣ ሲነጋ፣ ማታው ጧት፣ ጨለማው ብርሀን ይሆናሉ።
ታች ስወርድ እና ከጓደኛዬ ጋር ራት ለመብላት ስንዘገጃጅ፣ ብቻህን ምን እየሰራህ ነበር! ያልኩህንኮ አልሰማኸኝም! … ስንባባል፣ መብራቱ፣ ድርግም ብሎ ጠፋ። መብራቱ ከመጥፋቱ በፊት፣ ያች እናት፣ ከእነ ልጆቿ፣ ከእነ ጨርቅ ብርሳዋ፣ ቤት ገብታ ይሆን ብዬ ራሴን ጠየቅኩ።
#ሰላም_ግቢ___ኢትዮጵያ❗️
(አፈረሱት አሉ … 8)
ኢትዮጵያን አገኘኋት። ወንድና ሴት ህፃን ልጆቿን ይዛ በዝናብና በጨለማ ውስጥ ችላ ስትጓዝ ሀገሬን በአይኔ በብረቱ አየኋት። ችላ መጓዟን ባይ ከሎሬት ጸጋዬ ስንኝ ተዋስኩና...
«አዎን መቻል ባንቺ ያምራል፥» አልኳት።
«አዎን መቻል ባንቺ ያምራል
ያን የትዝታ ሰቀቀን
ያን የልጅነት ሰመመን
ምንም በውል ባንደርስበት፥ ጭላንጭሉ እየታወሰን
ውል ሲል እንዳልጠፋ ቀን
ከዓመት ዓመት ተሽጋግረን፥ አዳዲስ ዘመን ሲሰለፍ
ሰንበሌጡ ሲንተረከክ፥ የአዝመራ እሸት ሲትረፈረፍ
የማር እሸት እንቁረጥ ተይ፥ የጥቅምት አበባ እንቅጠፍ
ነይ ሸጎዬ አብረን እንግዘፍ »
ብዬ ከሎሬቱ «አቴቴ ዱብራ ኦሮሞ» ግጥም ተውሼ በጎ በጎውን ተመኘሁላት። ይሄ ሰው አበደ እንዴ? ከማለትሽ በፊት ላብራራልሽ ተከተይኝ።
“አፈረሱት አሉ” የሚሉ ወጎች በተከታታይ ሳወጋሽ አልነበር? መቼም ወጎቹ አትለቁ ተብለው ተመርቀዋል መሰል የሚቀጥሉበት ምክንያት አልጠፋ አለ። ለነገሩ የግንባታና የፈረሳ፣ የገንቢና የከሳሽ፣ የአፍራሽና አዳሽ ነገር.... ሳይቋጭ የኔ ወግ ለምን በአጭሩ ይቋጫል? ኢንሻአላህ እስካለን ይቀጥላል!
እናልሽ የቀድሞዎቹን ተከትሎ፡ በአንድ ወዳጄ ጋባዥነት ኢትዮጵያን ያየሁበት ግሩም ታሪክ ተወለደ። እሱን ነው ዛሬ በራሴ መንገድ ላጋራሽ የወደድኩት። ደግሞም የኔውም ያንቺም መንገድ በመሆኑ ከመንገዳችን ጋር ያገናኘናል። በእርግጥ አዲስና የማናውቀው ይመስለናል። ግን አዲስ ነገር አይደለም አልተባባልንም? እንደዛ ነው ይሄም። ነይ ወደ አዲሱ ሰፈር ሄደን፣ ኢትዮጵያን እንያት።
#ተዳሳሽ_እውነት_ተዳሳሽ_ውበት❗️
አገሬ ውበት ነው፤
ለምለምና ነፋስ የሚጫወትበት፣
ፀሐይ የሞላበት፤ ቀለም የሞላበት፡፡
አገሬ ቆላ ነው፤ ደጋ ወይናደጋ
እዚያ ብርሃን አለ ሌሊቱ ሲነጋ፡፡
አገሬ ተራራ፣ ሸለቆ ረባዳ፣
አገሬ ጅረት ነው ገደልና ሜዳ፡፡
ውሸት ነው በበጋ ፀሐይ አትፋጅም፤
ክረምቱም አይበርድም፤
አይበርድም፤ አይበርድም፡፡
(ገብረክርቶስ ደስታ)
#ግንቦት20 ቀን 2016 ዓ.ም በስራ ላይ
“Traveling outside is, traveling inside”
በዱባይ መጓዝ በኢትዮጵያም መጓዝ ነው❗️
➖
ዱባይ ቆሜ ኢትዮጵያን … ብዬ ወጌን ጀምሬ ነበር። ይህንን የሚያጠናክርልኝን ሌላ ተጨማሪ ሀሳብ በመምዘዝ ልጀምር።
አንድ የጉዞ ወኪል ባልደረባ፤ “Traveling outside is, traveling inside” ይላል፡፡ “በውጭ መጓዝ፣ በውስጥ መጓዝ ነው፡፡ውጫዊ ጉዞህ፤ ለውስጣዊ ጉዞ ማብቃት አለበት፡፡ በውጭ ከቦታ ቦታ ስትጓዝ፤ ውስጥህ ተጉዘህ (የግል እምነትህን፣ ሀገርህን፣ ባህልህን፣ አስተሳሰብህን፣ አሰራርህን ወዘተ) ለመመዘን ካልገፋፋህ ከንቱ ድካም ነው›› ይላል፡፡ ለሥልጣኔ ምቹ አውድ የሚፈጠረው፤ የተለያየ ባህል ያላቸው ሰዎች መገናኛ በሆነ ሥፍራ ነው፡፡ ግሪኮች ይህ ዕድል ነበራቸው፡፡ ሐረር ለዚህ አብነት ነች፡፡
ይህም ዕድል የሚፈጠረው ንግድ ነው፡፡ አለቃ ታየ በአንዱ ደብዳቤአቸው፤ “የአውሮፓን ሥልጣኔ አይቼ ለሀገሬ መንግስት ቅንአት በላኝ” ይላሉ፡፡ አለቃ ታየ ነቁ፡፡ “በውጭ መጓዝ፣ በውስጥ መጓዝ ነው” ይሉሃል ይህ ነው፡፡
ዱባይ ከሜይ 21-24 የተካሄደውን የካብሳት ኤክስፖ አስተናግዳ ነበር፡፡ በውጭ ተጉዤ ዱባይ ስደርስ፣ መዳረሻው የራቀ ውስጣዊ የጉዞ በር ተከፈተ፡፡ ዱባይና ሀገሬ እንደ መርፌና ክር ተያይዘው ሀሳቤን ይሰፉት ጀመር፡፡
ዱባይ ባአፍም በመጣፍም የሚተረክ ታሪክ አላት፡፡ ዱባይን በጆግራፊ መጻህፍት ተጠቅሳ የምናገኘው፤ በ1095 ነው፡፡ ቢያንስ፣ በመጣፍ ለአንድ ሺህ 70 ፈሪ የሆነ ዕድሜ አላት፡፡ ግዛቷ እንጂ ታሪኳ ትልቅ ነው፡፡ ቀልብ ሳቢ ነው፡፡
ዱባይ የሲራራ ነጋዴ ጣቢያ ነበረች፡፡ ከኦማን ወደ ኢራቅ በተዘረጋው የንግድ መስመር ለሚመላለሱ ነጋዴዎች ፌርማታ ነበረች፡፡ ሲራራ ነጋዴዎቹ ዱባይ አረፍ ብለው ምግብ ቀምሰው ጎዙ ይቀጥላሉ፡፡ በኋላ እንግሊዝ ዓይኗን ጣለችባት፡፡ ይህ የእንግሊዝ ሞግዚትነት ያልተመቻቸው አልመክቱም ቢን ቡቲ፤ ትንሽ ራቅ ብለው አንዲት ነጻ መንደር መሠረቱ፡፡ በሂደት ዱባይ በ1971 ከእንግሊዝ የሞግዚት እጅ ተላቀቀች፡፡ በመጨረሻም፤ ዱባይን፣ አቡዳቢን፣ ሻርጃህን፣ አጅማንን፣ ኡምን፣ ፉጃይራህን፣ ራስ አልካይማህን (በ1972 ዓ.ም) ያካተተ ‹‹የተባበሩት አረብ ኤሚሬት›› ሀገር መስርታ ጉዞዋን ቀጠለች፡፡ የዱባይ ዘመናዊ የታሪክ ምዕራፍ ተከፈተ፡፡ አሁንም ዱባይን የሚገዛው በመስራቹ የተመሰረተው ስርወ መንግስት ነው፡፡
በአልመክቱም ቢን ቡቲ፤ ‹‹ጁምራህ›› ከተባለ ሥፍራ የተወለደችው ዱባይ፤ ዓሳ እያሰገረች፤ ከባህር የሉል እየለቀመች፣ ለነጋዴዎች ማረፊያ እያዘጋጀች፣ ጀልባ እየገነባች፤ በንግዱ ነቃ ነቃ አለች፡፡ በአል መክቱም አገዛዝ ዱባይ በፍጥነት ተነሳች፡፡ ያቺ የዓሳ አጥማጆች መንደር ፈጣን የዝመና ጉዞ ጀመረች፡፡ በ1894 የውጭ ዜጎችን ከግብር ነጻ የሚያደርግ አዋጅ አወጀች፡፡ አዋጁ የሳባቸው በርካታ የውጭ ሀገር ሰዎችን ሳበች፡፡ በርካታ ህንዶችና ፓኪስታኒዎች ወደ ዱባይ ፈለሱ፡፡
በ1950ዎቹ ጃፓን ሰው ሰራሽ ሉል ለገበያ ማቅረብ ስትጀምር፤ በጊዜው ዱባይ በጣም ደነገጠች፡፡ ይህ የጃፓን ፈጠራ የአካባቢውን ንግድ ተገዳደረው፡፡ ግን ዱባይ ገና ከድንጋጤ ሳትወጣ፤ በ1966 አንድ ታሪክ ቀያሪ ዕድል አገኘች፡፡ ዱባይ ነዳጅ ዘይት ባለቤት መሆኗን አወቀች፡፡ መልሳ አንሰራራች፡፡ ሸክ ራሺድ ቢን አል መክቱም ይህን ዱባይ የዕድል በር አሰፉት፡፡
ታዲያ ባለፈው እንደጠቀስኩት፣ ነዳጅ ብቻውን የሀገር እድገት ዋስትና አይደለም። ነዳጅ ያላቸው ሁሉ እንደማይለወጡ ጎረቤቶቻችንና ዛሬ የሚታመሱ ሀገራትን ማየት በቂ ነው።
ዱባይ ግን አወቀችበት። ብልሀቱን ፈጥና ቀየሰች። ከነዳጅ ጥገኝነትም ተላቀቀች። ዛሬ ከዱባይ ጠቅላላ ዓመታዊ ምርት የነዳጅ ዘይት ያለው ድርሻ 1 በመቶ ብቻ ነው፡፡
ዱባይ ከዓሳ አስጋሪዎች መንደር ወደ ዘመናዊ ከተማ ከፍ አለች፡፡ የንግድ ማዕከልና የወደብ አገልግሎት ሰጪ ሆነች፡፡ በርካታ ከወደብ አገልግሎት ጋር የተያያዙ ሥራዎችን ጀመረች፡፡ አሁንም በዚህ ዘርፍ ዝነኛ ነች፡፡ ኢኮኖሚዋን በፈጠራ ላይ መሰረተች፡፡ ባለ ራዕይ መሪ አግኝታለችና ዱባይ ተመነደገች፡፡ በ50 ዓመታት ብዙ ተለወጠች፡፡ በመላው ዓለም እንደ ትንግርት የሚታዩ ህንጻዎችን ገነባች፡፡ ነጋዴዎችን እና ቱሪስቶችን የሚያማልሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን መስራቷን ቀጠለች፡፡
#ካብሳት
በዱባይ ዓለም ገበያ ማዕከል በተዘጋጀው 30ኛው የ”ካብሳት” የንግድ ትርዒት ለመሳተፍ በሄድኩ ጊዜ፣ የሀገራችን ፖሊሲ አውጭዎች ለሚዲያው ዘርፍ፡ የበለጠ ትኩረት መስጠት እንዳለባቸው ማሰብ ብቻ ሳይሆን፤ ባለራዕይ መሪ ሀገርን በትውልድ ዕድሜ ከፍ ሊያደርግ እንደሚችል አሰላስል ነበር፡፡ አዎ ሀገሬ ዛሬም ተስፋ አላት፡፡
እንደኔ በብሮድካስት ዘርፍ ለተሰማራ ሰው፣ ዓይን ገላጭ ትርዒት ነበር፡፡ በሳተላይት አገልግሎት፣ በብሮድካስት ቴክኖሎጂ፣ በኬብል ኔትወርክ አሰራር፣ በቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፍ ዓለም ከምን ደረጃ እንደ ደረሰች ለመረዳት፤ በተጠቀሱት ዘርፎች ያለውን ችግር እና መፍትሔ ለማወቅ የሚያግዝ ትርዒት ነበር፡፡ አዳዲስ ምርቶች እና አገልግሎቶች ይተዋወቁበታል፡፡ ምርትን ከፈላጊ ያገናኛል፡፡ የየዘርፉ ኤክስፐርቶችም፣ ስለ አዳዲሶቹ ፈጠራዎች እና ቴክኖሎጂዎች ማብራሪያ ያገኛሉ፡፡
በኬብል ኔትወርክ፣ በሳተላይት፣ በብሮድካስቲንግ እና በቴሌኮሙኒኬሽን መስክ የተሰማሩ አምራቾች፣ ኤክስፐርቶችና ተገልጋዮች አንድ ቦታ ተገናኝተው፣ ስለ ኢንዱስትሪው ዕድገት ይመክራሉ፡፡ ትብብር ይፈጥሉ፡፡ የግንኙነት መስመር ለመዘርጋት (ኔትወርክ) ዕድል ይሰጣሉ፡፡
“#ሚዲያ__ሲቲ”
ዱባይ በሚዲያው ዘርፍም ቢሆን አስገራሚ ስራ ነው የሰራችው። ዱባይ “የሚዲያ ሲቲ”ፈጥራለች፡፡ ባለፉት 20 ዓመታት፡ በቀጣናው ተአማኒ የሆነ የሚዲያ ማህበረሰብ ለመፍጠር ችላለች፡፡ ፍሪላንስ ጋዜጠኞችን፣ ስታርታፖችን፣ አነስተኛ፣ መካከለኛ እና ትላልቅ ኢንተርፕራይዞችን የሚያቅፈው የዱባይ የሚዲያ ሲቲ ማህበረሰብ፣ እርስ በእርስ ለመደጋገፍና የማያቋርጥ እድገት ለመፍጠር የሚያስችል ምቹ አውድ አግኝቷል፡፡ ይህ የሚዲያ ሲቲ፣ ዱባይን “የዓረብ ሚዲያዎች መዲና” አሰኝቷታል፡፡ የቀጣናው የሚዲያ ኢንዱስትሪ መናኸሪያም አድርጓታል፡፡ ዛሬ ዱባይ የበርካታ ዓለም አቀፍ የሚዲያ ብራንዶች መዳረሻ ነች፡፡ ዱባይ ልበ ሰፊ ነች፡፡ ዱባይ “የውጭ ሰዎች መጥታችሁ ሥሩ” ማለቷን ልብ በሉ፡፡ ከ100 የዱባይ ሰዎች 90ው የውጭ ሰው መሆኑን እያሰባቸሁ፤ የሥልጣኔ ማህጸን የባህሎች ውህደት መሆኑን አክላችሁ፤ በኛ ሀገር የሚታዩ መጥፎ ዝንባሌዎችን መርምሩ፡፡ ጉዞዬ፤ ‹‹Traveling outside is, traveling inside›› ሆኖልኛል፡፡
#Ethiopia #Dubai #CABSAT2024
+1
የኛ ቅዳሜ⁉️
➖ #walk_and_Talk
እውነት ይህ ደግሞ ኢትዮጵያ ነው! …
ያው “የኔ ቅዳሜ” የሚለውን ዋልታ ቀድሞን ይዞታል ብዬ ነው የኛ ቅዳሜ ያልኩት።😁😁 በርግጥ ስያሜው ብቻ ሳይሆን፣ የኛ ቅዳሜ ግማሹ ቀንም ቢሆን የተቋሙ ነው።
ታዲያ ትርፍ ቀናችንን ብቻ ሳይሆን፣ ከስራ ሰአት በፊትና በሁላ ያሉ ሰአቶቻችንንም መጠቀማችንን ዛሬም ቀጥለናል። የራሳችንን ሰአት፣ የራሳችንን ስልክና ካሜራ ተጠቅመን ተጨማሪ ለመሮጥ ሞክረናል። በመደበኛው የሚዲያ ሃላፊነትና ሰአት ብቻ ተገድበን፡ እንዲህ የቆምንባትን አይነት ኢትዮጵያ ማፍጠን አንችልም።
እሱ ብቻም አይደለም። በተያያዝነው አይናፋርነትና የመደበኛው ሚዲያ አዝጋሚነት፡ ይህንን የቆምንበትንም አፅንቶ ለማቆየት እንቸገራለን። እናም መንቀሳቀሳችንን ቀጠልና።
ዛሬም ፍለጋችንን ቀጥለን walk N Talk ብለናል። ኢንሻአላህ በአንድና ሁለት ቀናት ውስጥ ወደናንተ እንደርሳለን።🙏
ሁላችንም ከያለንበት እንንቀሳቀስ። ለዚህም በቀደመው ርእስ ላይ walk the talkንም እናክልበትና ዳይ እንንቀሳቀስ!
ሰናይ ቅዳሜ ለሁላችን!🙏🙏
#ዱባይ_ቆሜ__ኢትዮጵያን⁉️
ለሥራ ጉዳይ ዱባይ ጎራ ብዬ ነበር፡፡ በዱባይ ሆኜ የምትታየኝ ሀገሬ ናት፡፡ በዱባይ መስታወት የማየው ኢትዮጵያን ብቻ ነው፡፡ ዱባይ ብዙ የተሰራ ሀገር ነው፡፡ ከተሰራው ነገር ይልቅ፤ ራሱ በሚሰራው ነገር የሚደሰት ሰው ሀገሩ ኢትዮጵያ ነች፡፡ ሀገሬ ዱባይን በተስፋዋ ትበልጣታለች፡፡ እንዲያም ሆኖ ዱባይ ተንቀሳቃሽ ምድር ናት፡፡ ዱባይ ውስጥ ትናንትን ብዙ አታዩትም፡፡ ዛሬም ዕረፍት የለውም፡፡ ዱባይ ሩጫዋ ነገን ለመያዝ ነው፡፡ ከትንሽ የዓሣ አጥማጆች መንደር ከመሆን ተነስታ፤ የቀጣዊና የዓለም አቀፋዊ ንግድ መናኸሪያ የሆነችው ነገን በመናፈቅ ነው፡፡ ከነዋሪዎቿ 90 በመቶው የውጭ ሀገር ሰዎች ናቸው፡፡ ከሰባቱ የተባበሩት አረብ ኤሚሬት ግዛቶች በህዝብ ቁጥር ቀዳሚ ናት፡፡ የዱባይ ስቴት ዋና ከተማ ዱባይ 3.6 ሚሊየን ህዝብ አላት፡፡
ያቺ ትንሽ የዓሣ አጥማጆች መንደር ዛሬ በቱሪዝም እና በቅንጡ የኑሮ ዘይቤ የምትታወቅ ሆናለች፡፡ በርካታ ባለ አምስት ኮከብ ሆቴሎችን በመያዝ በዓለም ሁለተኛዋ ከተማ ነች፡፡ ዱባይ በረጃጅም ህንፃዎቿ ትታወቃለች፡፡ ቡርጂ ከሊፋ አንዱ ነው፡፡ 828 ሜትር ከፍታ አለው፡፡ ብዙ መንገደኛ እና ጓዝ የምታስተናግድ የትራንስፖርት ማዕከል ናት፡፡ ቀደም ሲል የዕድገቷ ሞተር ነዳጅ ዘይት ነበር፡፡ ዛሬ ከዱባይ ጠቅላላ ዓመታዊ ምርት ነዳጅ ዘይት ያለው ድርሻ 1 በመቶ ብቻ ነው፡፡ አሁን የዱባይ ኢኮኖሚ የተመሠተው በፈጠራ ሃሳብ ነው፡፡
የታመነች የፋይናንስ ምስጢር ጣባቂ ነች፡፡ ከፍተኛ ግብር አትጠይቅም፡፡ ከፍተኛ ዋጋ ያላቸው ሪል ስቴት መገኛ ነች፡፡ በዚህም ብዙዎችን ትስባለች፡፡ ‹‹ገንዘብ ለመሸሸግ እና ለማጠብ የሚፈልጉ ወንጀለኞች መደበቂያ›› ይሏታል፡፡ ዱባይ የግዙፍ ዓለም አቀፍ የሚዲያ ብራንዶች ማዕከል ናት፡፡ ሰሞኑን፤ ከሜይ 21-23 ‹‹ካብሳት 2024›› (CABSAT - Cable, Satellite, Broadcast, and Telecommunications) በዱባይ ተካሄዶ ነበር፡፡ እኔም ታዳሚ ነበርኩ፡፡
ያየሁትን እቀጥላለሁ።🙏
“#እንደ_ዛፍ_እንሁን፡፡”❗️
የፋርሱ ገጣሚ ጀላሉዲን ሩሚ፡ “እንደ ዛፍ እንሁን፡፡ ዛፍ የደረቀ ቅጠሉን ይጥላል” እንዳለው፣ በዚህ በኛ ዘመንም፡ ጽንፈኝነት፣ ዘረኝነት፣ ጦርነት፣ ሌብነት … የደረቁ ቅጠሎች ናቸው፡፡ በህያውያኑ ላይ የተጣበቁ ሙቶች። የኛ ደግሞ ከደረቀው ቅጠልም የከፋ ይመስላል። ቅጠሉ ቢያንስ ኡደቱን ጠብቆና ጨርሶ ነው። የኛው ግን ድርቅና ነው። ከሰውነት የራቀ ድርቀት! እሱንም ሰፋ ያለ ጉዳይ ስለሆነ እንተወው። ሰፋና ዘለግ ያለ ፅሁፍ እራሱ በሽታችን አይደል?😁😁 አዎ እሱን እናቆየውና፣ ቢያንስ ግን ከዛፉ እንማር። ዛፍና ለወገን የቆመ ዛፍ፣ ልምላሜም ባየን ቁጥር ድርቅናችን የበለጠ አይገለጥብን። እናም የደረቁ ቅጠሎቻችንን እንጣል! እንደዛፍም እንደግ! እንለምልም! እንግዘፍ!
#ልጆቻችን_ይቅበሩን ወይስ #ልጆቻችንን_እንቅበር⁉️
“በሰላሙ ጊዜ፣ ልጆች አባቶቻቸውን ይቀብራሉ። በጦርነት ጊዜ፣ አባቶች ልጆቻቸውን ይቀብራሉ።”
‘In peace, sons bury their fathers. In war, fathers bury their sons’ ግሪካዊው ፈላስፋ ሄሮዶተስ።
በሰላም ኖረን፣ በክብር አርጅተን፣ ልጆቻችን ይቅበሩን። አለዚያ ልጆቻችንን እየቀበርን እንኖራለን!
#ሰላም🙏🙏
#ማንበብ_ማደግም_ነው❗️
“የሁለት ውሀዎች ዐቢይ ስትራቴጂ”ን ብቻ ሳይሆን፣ መጽሀፍትን በአጠቃላይ ለምን እናነባለን?
አሁን በህይወት የሌለው እና ከ200 በላይ መጻህፍት የደረሰው፣ ከ200 በላይ የመጽሄት መጣጥፎችን የከተበው፣ በርካታ አጫጭር ታሪኮችን፣ ተውኔቶችን፣ የጻፈው አሜሪካዊው ጌሪ ፖልሰን፣ ለዚህ ቁልፍ ጥያቄ፣ መልስ ይሰጠናል።
-መጽሀፍ የምናነበው፣ ለመሳቅ፣ ለመመሰጥ፣ ወዘተ ብቻ ሳይሆን፣ ለመማር እና ለማደግም ጭምር ነው።
-አይቼ የማላውቃቸውን ነገሮች ለማየት፣ አነባለሁ።
-የተሰበርኩ፣ ተስፋ የቆረጥኩ እና የደከምኩ ሲመስለኝ፣ ብርታት እንዳገኝ አነባለሁ።
-ፍርሀት ሲሰማኝ፣ በአለም ስበሳጭ፣ ረጋ ለማለት፣ አነባለሁ።
-ከስጋና አጥንት፣ ከቆዳና ከደም ብቻ ስላልተሰራሁ፣ አነባለሁ።
-ማንበብ ለእኔ፣ ከጓደኛዬ ጋር እንደመጫወት ነው።
“የሁለት ውሀዎች ዐቢይ ስትራቴጂ”ን ማንበብም፣ ስለ ኢትዮጵያ የበለጠ ማወቅና ማደግ ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በአደባባይ ደጋግመው እንደተናገሩት፣ “ቀይ ባህር እና ዓባይ፣ ኢትዮጵያን የሚበይኑ፣ ከኢትዮጵያዊነት ጋር የተቆራኙ፣ ለኢትዮጵያ እድገት እና ጥፋት መሠረት የሚሆኑ ናቸው።”
-የኢትዮጵያ ሕልውናዋ እና ልዕልናዋ፣ ከቀይ ባህር ጋር የተሳሰረ ነው።
-ኢትዮጵያ፣ በውሀ ተከባ፣ ውሀ የሚጠማት ሀገር ነች።
-በዓለም ላይ 44 ሀገራት የባህር በር የሌላቸው ሲሆን፣ 120 ሚሊዮን ሕዝብ ይዞ፣ የባህር በር የሌለው፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ብቻ ነው። የኢትዮጵያ ህዝብ ቁጥር በ2030፣ 150 ሚሊዮን ይደርሳል። 150 ሚሊዮን ህዝብን፣ የጂኦግራፊ እስረኛ ወይም ወደብ አልባ ማድረግ፣ በእሳት እንደመጫወት ያለ አደገኛ ነገር ነው።
አዎ! ሁለቱ ውሀዎች (ዓባይ እና ቀይ ባህር) የኢትዮጵያ ህልውና መሰረቶች ናቸው። “የሁለት ውሀዎች ዐቢይ ስትራቴጂ”ን በማንበብ፣ ይህን ሁሉ በቅጡ እናውቃለን።
ያላየነውን እናያለን፣ እናድጋለን፣ እንማራለን!
-በውሀ ተከበን አስከመቼ ውሀ ይጥማን?!
-120 ሚሊየን ህዝብ ሆነን፣ እስከመቼ በአለም ብቸኛዋ የባህር በር የሌላት አገር እንሁን?!
መጽሀፉ፣ ሁሉንም ያብራራል።
የሁለት ውሀዎች አቢይ ስትራቴጂን ያንብቡ!
ከአገር ጋር፣ ከወገን ጋር እንደመጫወት ማለትም ያለ ነው!
#የሁለትውሀዎችዐቢይስትራቴጂ
#ለናንተ … ይሁን⁉️
#ጦርነት ሰላም ነው!
ነጻነት ባርነት ነው!
ድንቁርና ጥንካሬ ነው!
የነገው መልክ፣ የሰው ፊት ላይ - ለዘላለሙ - የቆመ ቦት ጫማ ማለት ነው። (1984 ጆርጅ ኦርዌል።)
👉🏿በሀገሬ የተለያየ አቅጣጫ፡ ነውጥን ለመረጡ፤ እሱንም ተከትሎ ለተከሰተው ምስቅልቅል፣ ምስቅልቅሉንም እንደ ድል ለሚቆጥሩት ሁሉ መታሰቢያ ይሁንልኝ!!)
#አፈረሱት_አሉ❗️(ጾሙን እንዳይሆን ብቻ⁉️)
እንኳን አደረሳችሁ ወገኖቼ ! ፋሲካም አይደል? በጾም የጀመርናትን ጨዋታችንን በፍስኩ ከነመረቅና አጥንቷ ልንቀጥላት ነው።
አንዱ ልጅ የጀመረውን የሁዳዴ ፆም በጊዜ አፍርሶ ፍስክ ፍስኩን በመብላቱ፤ ቤተሰቦቹና የሰፈሩ ሰዎች እየወቀሱ ሲያማርሩት ከርሙ። አንድ ቀን በማለዳ...ጎረቤታቸው በሚኖሩ አንድ ቄስ ቤት ሲያልፍ፣ ቄሱ ስጋ እየቆረጡ፣ አጥንት እየጋጡ ሲበሉ አያቸው። ብቻውን ተዋርዶ ባለመቅረቱ ተደስቶ ወሬውን ሊነግራት እየሮጠ እናቱ ጋር ሄደ...
«እማዬ ቄሱም ፆማቸውን አፈረሱት!» ቢላት...
« ጅሎ... ዛሬኮ ፋሲካ ነው። ሁላችንም እንበላለን። ስለዚህ አፈረሱት ሳይሆን ተፈታ ነው የሚባለው!» ብላ ኩም አደረገችው።
የማወራው ስለ ሀይማኖታዊው ፆም ማፍረስና ፍቺ አይደለም። ስለ ሀገር ጥቅም ነው። ማፍረስ እና መፍታት ይለያያሉ። ሁሉ እየፆመ ብቻ ለመብላት ብሎ ማፍረስ እና ከሁሉም ጋር አብሮ የሚበላበት የፆም ፍቺ ትርጉማቸው ለየቅል ነው። ማን ነው አፍራሽ? ማንስ ነው ፈቺ? ይህንን ነው መጠየቅ ያለበት ዋናው ጥያቄ...
አሁን ለምሳሌ...
የባህር በር ስንፆም ኖርን። ከባህር ሀይሉም ሳንቀምስ ዘመናት አለፉ ። በመካከላችን ስለባህር በሩ ፍቺ መጽሐፍ እየፃፉ፣ ስለ ቀይ ባህር እየዘፈኑ፣ ስለባህር ሀይል ፊልም እየሰሩ፣ ስለ ወደብ በቁጭት እየተናገሩ፣ ፆማችንን ሊፈቱልን ምርጫ እየቀሰቀሱ ያበረቱን አንዳንዶች ነበሩ። በርግጥ የሀገሬውን ፆም አፍርሰው ሀገር ቀይረው... ዜግነት ለውጠው... የሰው ባህር ሲበሉና ሲጠጡ የከረሙ ብዙዎች ነበሩ።
እኛ ግን ታግሰን... ጊዜውም ደርሶ... በስንት ጥረት ከሶማሌላንድ ጋር ባደረግነው የባህር በር ስምምነት ፆማችንን ስንፈፅም፣ የባህር ሀይላችንን ስንፈታ... ለፍቺው የሚበቃንን ሁሉ በጋራ ልንቋደስ የጎረቤቶቻችንን በር ስናንኳኳ... ሊከሱን የሚሯሯጡት... ፆማቸውን ቀድመው ያፈረሱት ከሀዲዎች ናቸው። ምን እነሱ ብቻ? አብረውን ፆመዋል ብለን ያመንናቸው... ባህሩን በዘፈን፣ በድርሰት፣ በግጥም... ሲናፍቁ የኖሩት "የጥበብ ሰዎች" ለፍቺው ቀን አፋቸውን ለጉመው ዝም ቢሉ... አንዳንዶቹም በዓሉን ሲራገሙና ሲያጣጥሉ ብናያቸው... ጠረጠርናቸው። በድብቅ አፍርሰው ነበር ማለት ነው። በፆሙ ሲበሉ ነበር የከረሙት ማለት ነው...
አሁን ለምሳሌ...
በፆሙ... ኤርትራን ሲናፍቁ... አስመራ ...ከረን... ዳህላክ ሲሉ የከረሙት ሁሉ፣ ፍቺው መጥቶ በሮቻችን ሲከፈቱ... አፋቸውን ሲለጉሙ...ፊታቸውን ሲከሰክሱ... ሴራ ሲጠነስሱ ብናይ... አብረውን እንዳልፆሙ አወቅን። በፆሙ ኤርትራ በረሃ የማይጠፉት... አስመራ ቤተመንግስት የተመላለሱት... በጋራ እንፍታ ሲባል... ክስ የጀመሩት... አብረውን ስላልፆሙ ነው። አሁንም የተኳረፍን ሲመስላቸው ደጅ እየጠኑ... የታረቅን ሲመስላቸው ነጠላ የሚዘቀዝቁት ለብቻቸው መብላት ስለለመዱ ነው። በፆም አፍርሶ መብላት ለለመደ... ፍቺው በዓል ሳይሆን መርዶ ነው።
አሁን ለምሳሌ...
የአድዋ በዓልን በግድ ፁሙት ስንባል... ከጊዮርጊስ አደባባይ ሳይጠፉ... የአድዋ ድግስ... የአድዋ ጉዞ.. የአድዋ ዝክር... የአድዋ ቴዓትር እያዘጋጁ ሲያከብሩ የኖሩት ሁሉ፣ ለአድዋ ፆም ፍቺ ግዙፍ መታሰቢያ ሲሰራ... ታሪካችንን ሽጠን በጋራ እንብላ ሲባል... እንኳን የአድናቆት ቃል ሊወጣቸው... መታሰቢያው ላይ አቃቂር በማውጣት ቢጠመዱ... ጠረጠርናቸው...። በፆሙ ብቻቸውን መብላት ስለለመዱ... ሀገር በአንድነት ይብላ ሲባል መርዶ ይሆንባቸዋል።
አሁን ለምሳሌ...
እኩልነትን እየፆምነው ሳለ... የጋራውን ፆም አፍርሰው የበላይ ነን ሲሉ የነበሩት... እኩልነታችን ሲፈታ... እኩል እንሁን ሲባል... የበታች የሆኑ ይመስላቸዋል።
የወንዝ ልማቱም... የኮሪደር ስራውም፣ የሰፈር እና የከተማ እድሳቱም፣ ገበታ ለሀገር ፕሮጀክቱም፣ የበጋ ስንዴውም፣... ሁሉም ሀገራዊ ጾሞቻችን ነበሩ። ሲፈቱ የምንደሰተው ስለፆምን ነው። አብረውን ያልፆሙት፣ ፆማቸውን ያፈረሱት ሁሉ ፍቺው ቢያስከፋቸው እንረዳቸዋለን። ለብቻው መብላት የለመደ በጋራ እንብላ መብላት መርዶው ነው።
አንቺ ግን ስትፆሚ ስለከረምሽ እንኳን አደረሰሽ። በዓሉ ታምኖ ለፆመና ለፀለየ ነው። ኦርቶዶክሱና ካቶሊኩ ከፋሲካው በፊት ይፆማል ይፀልያል። ሙስሊሙ ከኢዱ በፊት ረመዳንን ይፆማል ይፀልያል። ፕሮቴስታንቱ ከበዓሉ በፊት ፆም ፀሎት ይይዛል።
ስለዚህ ሁሉም እንደየእምነቱ ስለጾመና ስለፀለየ በዓሉ የደስታ ይሆንለታል።
ነገር ግን ፍርፋሪ ባየ ቁጥር እምነቱን ለሚጥል... እህል በተሰፈረበት ሁሉ ለሚያጎነብስ... ከሰው ተሰውሮ ትርፍራፊ ለመልቀም ለሚያደባ ሁሉ ፍቺው ፍቺ በዓሉም በዓል አይሆንም። ለፆሙት ለፀለዩት ለታመኑትና ለፀኑት ብቻ የእውነት በዓል ይሆንላቸዋል። ያኔ የክብር መዓዱ ተዘርግቶላቸው ሲቋደሱ... ፆሙን ያፈረሰ ሁሉ እየመጣ «አፈረሱት!» እያለ ቢያማቸው መሳቂያ መሳለቂያው እሱ እንጂ እነሱ አይደሉም። ምክንያቱም በጋራ መብላት... ፆም መፍታት እንጂ ማፍረስ አይደለምና።
መልካም በዓል!
"አፈረሱት አሉ..." #ቅንነት_አዲስ_ልብስ⁉️
እያወጋነው ባለው ርእሰጉዳይ ላይ፣ እንደወዳጆቻችን እንዳትሳሳቺ አደራሽን! ለጉዳዩ ባዳ አይደለሁም። ደግሞም ከሚሰራው ስራም፡ ከሚሰሩት ሰዎችም: በግል ጭራሽ የጥቅም ተቋዳሽ አይደለሁም። የማወራሽ ስለኔው ህይወትና እውነት ጭምር ነው። ኢህአዴግ ፊትበርን ሲያፈርስና ነዋሪውን ሲበትን፣ ከተቃወሙትና ከተጠቁትም እንደ አንዱ ነኝ። የአራት ኪሎን ቤተመንግስት ተንተርሰው ከሚኖሩት ውስጥም ነበርኩኝ። (ይልቅ ከ4ኪሎ የተገፋነውና ለሰፈሩም ባዳ የሆንነው አሁን ነው😁😁 ለከንቲባ ፅህፈት ቤቱማ ጭራሽ ማን አድርሶን!😁 )
ኢህአዴግ “ድህነትን አጠፋለሁ” በሚል ሽፋን ደሀውን ከተወለደበት እያፈናቀለ ሲያጠፋ፣ በብዕር ከተፋለሙት ወገን ነኝ። (ፅሁፎቹን ብሎግ ላይ አለያም ወደ ወመዘክር ጎራ ብለሽ አንብቢ። በጋዜጦች ላይ ተሰንዶ ቁጭ ብሎልሻል።) ምክንያቱም ድርጊቱን ሳይሆን አድራጊውና የድርጊቱን ዓላማ ስለተረዳሁት። ፈረሳው ለልማት ሳይሆን ለገንዘብ ጥማት ፣ ማፈናቀሉም ለበቀል መሆኑ ስለሚገባኝ። ድሮ ምን ጠፋ? አሁንስ ምን ተገኘ ካልሽኝ ተቀየረ... ካልሽኝ መልሴ ቅንነት ነው። ቅንነት ሰልባጅ አይደለም። ለብሰነው አናውቅም። ቅንነት አዲስ ልብስ ነው። ያንን አዲስ ልብስ የለበሰ መሪ ማየቴ ነው አዲሱ ነገር። ዶ/ር አንማው አንተነህ አቶ መለስ ዜናዊን «ኳሷ በርሶ ቁጥጥር ስር ስለሆነች... እርስዎ ቅን እንዲሆኑ ብቻ ነው የምመኘው!» እንዳሉት። አሁን የተገኘው ቅንነት ነው።
ምስክር ጥራ ካልሽኝ የፒያሳንና የአራት ኪሎን አብሮ አደግ አቧሬን ጥሪና ጠይቂያት። አፈረሱት አሉ ብላ ያልዘፈነችውን አቧሬን። የፈረሰ ቤት ውስጥ የወደቁ አዛውንት አያቶችሽ ቤት በየክረምቱ እየፈረሰ የታደሰላቸው መራቂ እናቶችሽን ጠይቂ። ከጭቃ ውልቅ ከፎቅ ጥልቅ የሚለው ምርቃት የደረሰላቸውን ምስኪን አባቶችንና እናቶችን ጠይቂ። በርሃብ ይወድቁበት የነበረው ትምህርት ቤታቸው ውስጥ ምግብ እየተመገቡ የሚማሩትንና ዩኒፎርም በነፃ የለበሱትን ህፃናት ጠይቂያቸው። በፈገግታ ይመልሱልሻል። ለገዛ ልጆቻቸው በየትምህርት ቤቱ ምግብ እንዲያበስሉ ደሞዝ የሚከፈላቸውን እናቶቻቸውን ጠይቂ... አይሱዙ የሚያጎብጥ እንጨት አዝለው የእንጦጦን ጋራ ይወጡ የነበሩ እናቶችን አዲሱ ስራ ቦታቸው ጋር ሄደሽ ጠይቂ... በምርቃት ይነግሩሻል።
በየሰፈሩ በተገነቡትን የነፃ ምገባ ማዕከላት ራታቸውን በልተው የሚወጡትን ምስኪን አያቶችሽን ጠይቂ... እጆቻቸውን ወደሰማይ ዘርግተው ከምስጋና ጋር ይነግሩሻል። በሙሉ አይናቸው ለማየት በሚፈሩት ቤተመንግስት፣ ጠቅላይ ሚኒስትር እያስተናገዳቸው፣ ቀዳማዊት እመቤት እያጋፈረቻቸው፣ የገና እና የፋሲካ ምሳ በክብር ተጋብዘው የሚወጡትን ምስኪኖች ጠይቂያቸው። በቤተመንግስት ከሀገር መሪ ጋር አፍጥረው የሚወጡትን ፆመኛ ምንዱባን ጠይቂያቸው። ከእንባ ጋር ይነግሩሻል። ድሀና ድህነትን የሚለይ መሪ መኖሩን... ድህነት የሚጠላ ድሃ የሚወድ መሪ መኖሩን... ከሁሉም በላይ ቅንነት መኖሩን ያበስሩሻል።
ፒያሳም ከፈራች ትጠይቅ። መስቀል አደባባይን ትጠይቅ... እንጦጦን ትጠይቅ፡ ፊት በርን... ወዳጅነትን...ትጠይቅ... ቃሊቲን ቦሌን...ሸጎሌን...ትጠይቅ... ጫካን ትጠይቅ...። ነገዋን ይነግሯታል። ላይኛውንም ታችኛውንም ቤተመንግስት ትጠይቃቸው.... ሀብቷን ይነግሯታል። ብዙ መራቅ ካልፈለገች... እንብርቷ ላይ ያለውን አድዋ ሙዚየምን ምን እንደነበረ... አሁን የት እንደደረሰ... ትጠይቀው። ተስፋዋን ያሳያታል።
ያኔ የከተማ ዘፈን ትክክለኛ ትርጉም ይገባታል። አፍራሿ ማን እንደሆነ ይገባታል። ገንቢዋ ማን እንደሆነ ይገባታል። ያለ እናት እና አባት ያሳደገቻቸውን... ለልጆቻቸው ጥሩ እናትና አባት እንዲሆኑ ታስተምራለች። ያኔ
«ከእንግዲህ ደጃች ውቤ ምን ሀገር ሆነች
ያቺም ልጅ አገባች፡ ያቺም ልጅ ቀረች !»
መባሏ ቀርቶ፣ ያኔ..ማጀቧ ቀርቶ... ያኔ አግብቶ የራቃትን መቁጠሯ ቀርቶ... ለራሷ ይዘፈንላታል። ያውም የሰርግ ዘፈን...
«አይዞሽ ሙሽሪት አይበልሽ ከፋ... አይበልሽ ከፋ
ሁሉም ያገባል በየወረፋ በየወረፋ። »
ገና… #እቀጥላለው …
ደግሞም ሁላችንንም እንኳን አደረሰን። መልካም ቀን።🙏
👇👇
(በፅሁፎቼ ውስጥ ሁሉ ለሚስተዋሉ የስርአተ ነጥብና የቃላት ግድፈት አፉ በሉኝ። ዋናው ለከፋው የሀሳብ ዝንፈት አለመዳረግ ነው😁 ደግሞም የተጣመመውን እያቃናን: የጎደለውንም እየሞላን እናንብብ። ያለቀለትን ብቻ ካላጎረሳችሁኝ ባዩ ጩኸትም አይደል የበረከተው። ከተማና ሀገርም የሚሰራው እንደዛ ነው። እናም እየሰራንና እየተንቀሳቀስን።🙏)
