የቀሲስ ታምራት ውቤ ትምህርቶች
Open in Telegram
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን! ይህ ቻናል ቀሲስ ታምራት ውቤ በተለያዩ መንፈሳዊ ጉባያት ያስተማሯቸው ትምህርቶች እየተቀረጹ የሚቀርብበት ነው:: yeneta.info
Show more902
Subscribers
No data24 hours
+37 days
+1130 days
Posts Archive
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
አሐተ ወሊዳ ወተወሊዳ አሐተ
መልአት ምድረ ወሰማያተ
ዛሬ የምናከብረው የታላቁ ልደት ዋዜማ የሆነን ታላቅ ልደት ነው፡፡ የታላቋ ሙሽራ ልደት ከሊባኖስ ኮረብቶች መሰማት በቤተልሔም ለሚሆነው የዘላለም ሙሽራ ልደት መለከት ነበር። ዛሬ የተወለደች ለልጇ እናትም ሙሽራም የምትሆን፤ ንጉሠ ሰማያት ወምድር እንኳን ለምድራውያን ለሰማያውያንም ተገልጦ የሚታይባት ንጽሕት እልፍኝ ናት።
ክርስትናን ወይም የሰውን ታሪክ ስናጠና ሁለት ሴቶች ጎልተው መነሣታቸው የግድ ይሆናል። ቀዳሚት ሔዋንን እና ዳግሚት ሔዋንን። የቀዳሚት ሔዋንን ይቅር የተባለ በደል በልጇ በተካሰች (በትንሣኤ) ማግስት ማንሣት ከካሣው በደሉን ማግዘፍ መስሎ ሰውነቴን ስለታየኝ በትንሣኤው ደስታ አዳፈንሁት፤ ምን በወጣት እናቴ! አምስት ሺ አምስት መቶ ዓመት የተወቀሰችው መች አነሣት?! የእርሷን ያህልስ በጻድቁም በኃጥኡም አንደበት ማን ተብጠለጠለ?! ዛሬ ግን እላለሁ "አምሳያሽ ተወልዳ ወንድ ልጅ ወልዳ በደልሽ የተደመሰሰልሸ እናቴ ሔዋን ሆይ ደስ ይበልሽ! ደስተኛይቱ ልጅሽ የደስታ መፍሰሻ ሆና ደስታሽ የተመለሰልሸ እናቴ ሔዋን ሆይ ዳግም የማትነጠቂው ደስታ ተሰጥቶሻልና ደስ ይበልሽ! የአዳምን ፊት በሰቀቀን ከማየት አርፈሻል እርሱም እንደ ቀድሞው በፍቅር አይቶሻልና ደስ ይበልሽ!"
ይህን የቀዳሚት ሔዋን በዳግሚት ሔዋን መካስ የተመለከተ ኢትዮጵያዊ ሊቅ ከላይ በርዕስ የተቀመጠውን ሀሳብ ነው በቅኔው የገለጠው። ሔዋን ከድቀት በኋላ ከአዳም ዘር ተቀብላ በምጥ በጣር በገዓር ልጆች ብትወልድም ሁሉ በሞት ጠፉባት። ኀዘኗም ለወትሮው በሴቶች እንደሚሆን ምጡ ሲቀርብ አዝነው ከወለዱ በኋላ እንደሚፅናኑት አልነበረም። ወደ ጥፋት ሲሄዱ እያየች አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን አዘነች እንጂ። ዮሐ 16
እንዚራ መንፈስ ቅዱስ ማር ኤፍሬም "ኢቀደሞ ዘር ለልደቱ" እንዳለ ዳግሚት ሔዋን ለመፅነሷ ቅድሚያ ዘር መቀበል ሳያስፈልጋት የተዛባውን ሁሉ ድጋሚ ሊዛባ ወደማይችል አዲስ ሥርዓት ያስገባውን ወለደችው። ባለ ቅኔው እንዳመሰጠረው እንደ ሔዋን በሠላሳ ጊዜ ምጥ ስድሳ ሳይሆን:-
"አንድ ሆና ተወልዳ ያለ ምጥ አንድ ወልዳ፤
መላችው የምድርን የሰማይን ጓዳ" ተባለ ለዛሬይቱ ሕጻን ዳግሚት ሔዋን።
ቀዳሚት ሔዋንም በልጇ የልጅ ልጆች ብቻ ሳይሆን ያገኘችው ቀድሞ በሞት የተነጠቀቻቸው ልጆቿ ሁሉ ተመለሱላት። የልጅ ልጇም ልጇም፤ ፈጣሪዋም አምላኳም የሆነው እርሱ ከርስቷ የነቀላትን ከክብሯ ያዋረዳትን በጥልቁ ጥሎና እንዳይወጣ በማኅተም ዘግቶ ካሠረው በኋላ "ከደነ ሰማያተ ሥኑ፤ ወመልአ ምድረ ስብሐቲሁ" እንዲል በቤዛነት ሥራው በውበቱ (በምዕመናን) ሰማይና ምድርን መልቶ በግርማው ክብር ተቀመጠ፤ ምስጋናውም ምድርን መላ። ትን.ዕን. 3፥3፤ ሉቃ 24፥26
እንግዲህ የዛሬው የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ልደት ለንጉሠ ሰማያት ወምድር ኢየሱስ ክርስቶስ ልደትና በእርሱ ቤዛነት ለሆነው የፍጥረት ዳግም ልደት ሁሉ ዋዜማ ነው ያልነው። በእርሷ መወለድ አይቀሬው ልደት በደጅ ቀርቦ ያየንበት ቀን ነው። ዛሬ የተወለደችዋ ሕፃን ከአሥራ አምስት ዓመት በኋላ "እነሆ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፤ ሕዝቡን ከኋጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን ኢየሱስ ትይዋለሽ" የሚል ቃለ ብሥራትን ሰምታ እርሱን ብቻ ሳይሆን እኛንም በእምነት ትወልደናለች። ሉቃ 1፥26
በእርሷ የተደረገውን ስናስብ ልባችንን በሚያረካ መጠን ልናመስግናት ብንጓጓም ግን አይቻለንም። እንደ ቅዱስ ኤፍሬም ልባችንን ቀርባ "አመስግኑኝ" ብትለንም መልሳችን "እፎ ንክል ወድሶተኪ ዘኢይክሉ ሰማያውያን ወምድራውያን" ሰማያውያን መላእክት ምድራውያን ነቢያት ሐዋርያት ጻድቃን ሰማዕታት አንቺን ማመስገን የማይቻላቸው እንዴት ለእኛ ይቻለናል? ስንላት "በከመ አለበወክሙ መንፈስ ቅዱስ" መንፈስ ቅዱስ እንደ ገለጠላችሁ ተናገሩ ብላ በእኛ ለመመስገን መፍቀዷንና መባረካችንን ከንፈራችን "ተፈሥሒ፣ ሰላም ለኪ" ሲላት አወቅን።
አሁንም ግን የሰማይ የምድር ንግሥት ሆይ በአባትሽ በክቡር ዳዊት ቃል "ነኪር ነገሩ በእንቲአኪ ሀገረ እግዚአብሔር " የእግዚአብሔር ከተማ (ሀገር) ሆይ ባንቺ የተደረገ ነገር ድንቅ ነው፤ አንቺም የማይወሰነውን የወሰንሽ ሁሉን የሚሸከመውን የተሸከምሽ ድንቅ ነሽ! ከማለት በቀር ምን እንል ዘንድ ይቻለናል?
የእኔ የደካማው ልጅሽ ልመና አንድ ነው:-
". . . ዓመትየ በንዝህላል እመ ተሰልጠ ወኃልቀ፤ ወስክኒ ክራማተ እስከ እገብር ጽድቀ" ማለት፦ "እስከ ዛሬ ያለው ዘመኔ ልጅሽን ሳላውቀው በከንቱ አለቀ፤
እድሜን ጨምሪልኝ እስከ እገብር ጽድቀ"
ተጻፈ፦ በልደትሽና በልጅሽ ልደት ልደቱን ከሚያከብር፤ ልጅሽ ተብሎ መጠራቱ መጠን የሌለው ደስታን በልቡ ከሚያፈስለት ልጅሽ፤
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል!
በክርስቶስ አገልጋያችሁ!
ቀሲስ ታምራት ውቤ
ግንቦት ፩ ልደታ ለማርያም, 2016 ዓ.ም
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
በልብህ:- ማን ወደ ጥልቁ ይወርዳል?
አትበል!
ምዑዘ ቃል ጳውሎስ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ከዕለተ ዓርብ ጀምሮ ትንሣኤውን እስከ ገለጠበት ዕለተ እሁድ ድረስ ያደረገውን ሰውን የማዳን ጉዞ በደኅንነቱ ጊዜም ሆነ በወኅኒ ሲጣል፤ በባህርም ሆነ በየብስ ሲጓዝ፤ በወንድሞችም ሆነ በወንበዴዎች መካከል ያለ ዕረፍት ልቡናው እየተቃጠለ ሲከተለው ይታየኛል። ጌታችን ወደ ክብሩ ከመመለሱ በፊት ለሰው ፍቅር ከፍና ዝቅ ማለቱን ከእምነት በተራቆተ ኅሊና እንዳናስብ "በልብህ ወደ ሰማይ ማን ይወጣል? አትበል፤ ይህ ክርስቶስን ለማውረድ ነው:: ወይም በልብህ ማን ወደ ጥልቁ ይወርዳል? አትበል፤ ይህ ክርስቶስን ከሙታን ለማውጣት ነው" ይላል። እኛ ያወቅነው፣ የተከተልነው፣ የተገዛንለት ክርስቶስ በፈቃዱ በዚህ ከፍታና ዝቅታ ውስጥ ያለፈ ነው። ይህን የማያምን 'በከመ ይቤ ጳውሎስ ውጉዘ ለይኩን!' 1 ቆሮ 10
የከፍታውን ነገር እናቆየውና የዝቅታውን ነገር እንመርምር :-
ዝቅ ማለቱ (ተዋርዶው) ሰው ከመሆን ይጀምራል። ንዋይ ኅሩይ ጳውሎስ "እርሱ በእግዚአብሔር መልክ ሲኖር ሳለ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን መቀማት እንደሚገባ ነገር አልቆጠረውም፤ ነገር ግን የባሪያን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ባዶ አደረገ ፤ በምስሉም እንደ ሰው ተገኝቶ ራሱን አዋረደ፤ ለሞትም ይኸውም ለመስቀል ሞት እንኳ የታዘዘ ሆነ" በማለት በሚደንቅ ሁኔታ ገልጾታል። ፊልጵ. 2
ቀጣዩ የዝቅታ መንገድ ፍኖተ መስቀል ነው። የፍኖተ መስቀል (የዝቅታው ጉዞ) የመጨረሻ ምዕራፍ ሦስት ክንድ ከስንዝር በሆነ መቃብር ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት ለማደር ፈቃዱ መሆኑና በአካለ ነፍስ ወደ ሲዖል መውረዱ ነው።
ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ጲላጦስን ለምነው የጌታን በግርፋትና በእንግልት በችንካርም የተጎሳቆለ ሥጋውን ከመስቀል አወረዱ። ምን ይመስል ይሆን ያ ስሜት? ኡህ . . . ችንካሩን ከእጆቹና ከእግሮቹ ሲነቅሉ፣ የእሾህ አክሊሉን በደም ከተነከረ ራሱ ላይ ከጠጉሩ ጋር የተጋመደውን ሲያስለቅቁ፣ በግርፋት የተተለተለ ቁስሉን ሲነኩት፣ ጣቶቻቸው ሥጋውን አልፈው አጥንቶቹን ሲቆጥሩ፣ ከተወጋ የጎኑ ቁስል ደምና ውኃ የፈሰሰበትን ሲያዩ ምን ብለው ይሆን?
አሁን እነዚያ በፍቅር የሚያዩ አይኖች ተከድነዋል፤ ለኒቆዲሞስ የዳግም ልደትን ድንቅ ምሥጢር የነገረው ያ ጮኾ የማይናገር አንደበት በአርምሞ ተይዟል፤ የብዙ ሽባዎችን ሰውነት ያበረቱ እጆች ተዝለፍልፈዋል። ብዙዎችን ከደዌ የፈቱ እጆቹን፤ በትሕትና በኃጢአተኞች መካከል ለመመላለስ የፈቀዱ እግሮቹንስ በመግነዝ ስታሥሩ ምን ተሰማችሁ? ቅዱስ ሥጋውን ለማጠብ ጊዜ አገኛችሁ ይሆን ወይስ ለአይሁድ ሰንበት ስትሉ ተቻኩላችሁ በመቃብር አኖራችሁት? ለብዙዎች ጎስቋላ ሕይወት አዲስ ምዕራፍ የሆነ እርሱን በቀዝቃዛ ዓለት መቃብር አስቀምጣችሁ ድንጋይ ዘግታችሁበት ስትሄዱ ዓይኖቻችሁ ስንቴ ተመልሰው አማተሩ ይሆን? የደረሰበት መከራ ትንሣኤውን ተስፋ ማድረግን ከልባችሁ አጥፍቶት ስለነበር እርሱን ለመጨረሻ ጊዜ መሰናበት ልባችሁን እንዴት አደረገው? ጌታ ሆይ ትንሣኤህን ማመኔ ስለ እኔ የተቀበልከውን መከራ ያስረሳኝ ዘንድ፤ መከራህም ትንሣኤህን እጠራጠር ዘንድ አያሰናብተኝም።
ያልተፈጠረው ብርሃን የፍጥረታት ሁሉ ሕይወት በሥጋው በጨለማ መቃብር አደረ። ሞት አዳምን ለመቃብር አስረክቦ የአዳም አካል ለመበስበስ ተላልፎ ተሰጥቶ ነበርና "በመበስበስ የተዘራው ባለመበስበስ እንዲነሣ፤ በውርደት የተዘራው በክብር እንዲነሣ፤ በድካም የተዘራው በኃይል እንዲነሣ" የትንሣኤያችን በኵር ይሆን ዘንድ እርሱ መለኰቱ ለቅጽበተ ዓይን እንኳ ባልተለየው በሥጋው ወደ መቃብር ወረደ። 1 ቆሮ 15፥42
ሥጋ ያድርበት ዘንድ ከመቃብር የጠለቀ ምን አለ? ስለዚህ እኛን ከመቃብር ጥልቅ ሊያወጣን እርሱ ወደ ጥልቁ ወረደ። ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤውን ከገለጠ በኋላ በእርሱ ያመንን ወደ መቃብር በትካዜ አቀርቅረን ሳይሆን "ስለዚህ ልቤም ደስ አለው፤ ምላሴም ሐሴትን አደረገች፤ ሥጋዬም ደግሞ በተስፋ ታድራለች፤ ነፍሴን በሲዖል አትተዋትምና . . ." በሚል ዝማሬ የምንሄድ ሆንን። መዝ 15 (16)፥ 9 - 11
ቀጣዩ የዝቅታ ጉዞ ጌታ በአካለ ነፍስ ወደ ሲዖል ያደረገው ነው። ቅዱስ ጴጥሮስ ". . . እርሱ ጻድቅ ሆኖ ስለ ዓመፀኞች አንድ ጊዜ በኃጢአት ምክንያት ሞቶአልና፤ በሥጋ ሞተ በመንፈስ ግን ሕያው ሆነ፤ በእርሱም ደግሞ ሄዶ በወኅኒ ለነበሩት ነፍሳት ሰበከላቸው" በማለት ጉዞውንና ምክንያቱን ገልፆታል። ንጉሥ በጥፋቱ ይቅርና በስህተት ያሠረው ባለሟል ቢኖረው መልእክተኛ ልኮ ከወኅኒ ያወጣዋል እንጂ እራሱ ወኅኒ ድረስ ወርዶ ነፃ መሆኑን አይነግረውም። የነፍሳችን ንጉሥ ክርስቶስ ግን በበደላችን የተወረወርንበት ጥልቁ የጨለማ አዘቅት ድረስ "በጥልቁ የተጣላችሁ ውጡ፤ በጨለማ ያላችሁም ተገለጡ" የሚል የምሕረት ድምጹን ሊያሰማን መጣ። ከአዳም ጀምሮ በዚያ ድቅድቅ ጨለማ ቀን እየቆጠሩ የኖሩ ሁሉ በዚያች ቅጽበት ምን እንደ ተሰማቸው ለመግለጽ ከመካከላቸው ለአንዱ እንኳ አይቻለውም። የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የፍቅሩን ነገር ለመግለጥ በትንሹም ቢሆን አቅም ያለው "ዝምታ" ነው። የአንደበት፣ የኅሊና፣ የልቡና፣ የሕዋሳት፣ የፍጥረት፣ የሁሉ ዝምታ!!! 1 ጴጥ 3፥18
ልባችን ብቻ ከሚያውቀው እንደ መቃብር ከተዘጋንበት እንደ ሲዖል ከተወርወርንበት የውርደት ሕይወት ያለንበት ድረስ መጥቶ ሊያወጣን የሚችል ከእርሱ በቀር ሌላ አምላክ፣ ሌላ አባት፣ ሌላ ወዳጅ፣ ሌላ ጌታ፣ ሌላ እረኛ፣ እንዳለ አልሰማንም፤ አላየንም፤ አባቶቻችንም አልነገሩንምና 'በልባችን ማን ወደ ጥልቁ ይወርዳል? አንበል!' ያለንበት ድረስ ወርዶ አድኖናል። ነገ እንደሚያደርገው ማስረጃው ትናንት ማድረጉ ነው። ትናንት ካደረገው ዛሬም እያደረገው ነው ነገም ያደርገዋል። ምክንያቱም "ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትናና ዛሬ እስከ ዘላለምም ያው ነውና"። አንዴ ያደረገው እስከ ዓለም ፍፃሜ የተዋረዱትን ሲያከብር፤ የበሰበሱትን ሲያድስ፤ የወደቁትን ሲያነሣ፤ የራቁትን ሲያቀርብ ይኖራልና። ዕብ 13፥8
"ተንሥአ ወአንሥአ ሙታነ!"
ተነሣ ሙታንንም አነሣ!
ለትንሣኤው በዓል ሁሉ ለብርሃነ ትንሣኤው የሚደርሱ ግን ጥቂቶች ናቸውና፤ ለብርሃነ ትንሣኤው ከሚደርሱ ይደምረን!
በክርስቶስ አገልጋያችሁ !
ቀሲስ ታምራት ውቤ
በዓለ ትንሣኤ፤ ሚያዚያ 2016 ዓ.ም
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
"ዕለተ ዓርብ ዕለተ ድኀነት"
የነገረ መለኰት ሊቃውንት የዕለተ ዓርብን ስሜት በአጭሩ ሲገልጹት "sweet sadness or bright sadness" የሚረብባት ናት ይላሉ። እውነት ነው በዚህች ቀን ኀዘንና ደስታ፤ ዕንባና ፈገግታ፤ ሙሾና እልልታ እኩል ነግሠው ይውላሉ። ተቃራኒዎቹ ተሰማምተው ሳይገፋፉና አንዱ ከሌላው ጋር ምን ክፍል አለኝ? ሳይል በአንድነት የመድኃኔ ዓለም ዕፁብ ሥራውን ይሰብካሉ። መፍቀሬ ሰብእ ክርስቶስ ለሰው ሲል (ለእኔ ሲል) የደረሰበትን መከራና ውርደት ስናስብ ኀዘን፣ ዕንባና ሙሾ እንደ ማዕበል ልባችንን ይደፍቃታል። መጠኑ በማይመረመር ያልተፈጠረ ፍቅር ሰውን (እኔን) ስለ መውደዱ ከወደቅንበት ማንሣቱን፤ እርግማናችንን መሻሩን፤ ከቀደመ ክብራችን በሚልቅ ክብር እንዳስጌጠን፤ ደሙን ማጫ አድርጎ እኛን ሙሽሮቹ ያደረገበት የሠርጋችን ቀን፣ አመንዝሮቹ እንደ ድንግል በክብር የተዳርንበት ዕለት መሆኗን ስንረዳ ደግሞ ፊታችን በደስታ፣ በፈገግታና በእልልታ እንደ ንጋት ብርሃን ይፈካል።
በዚህች ቀን ሌላም ኀዘንና ደስታ አለኝ። ኀዘኔ የክፋቴንና የድንቁርናዬን ጥግ በአይሁድና በሮማ ወታደሮች ማየቴ ነው፡፡ ሰው የዲያብሎስን ክፋት የተዋረሰበትን መጠን ሲያስተውሉት ከሰው ጋር መኖር ያስፈራል። ጌታም "በእርጥቡ እንጨት ይህን ያደረጉ በደረቁማ . . . " ብሎናል። ምንም በደል ባልተገኘበት በክርስቶስ ላይ የሰው ክፋት በዚህ ልክ ከተገለጠ ምክንያት በሚገኝብን በእኛ ላይማ እንዴት ይሆን?
ደስታዬ ደግሞ መልክና ደምግባቱ እስኪጠፋ ድረስ ለግርፋትና ለችንካር አካሉን ሰጥቶ፤ ሰውነቱ ውስጥ ያለው ፈሳሽ ተንጠፍጥፎ እስኪያልቅ ላቡንና ደሙን አፍስሶ ለዘላለም በማይወድቅ ፍቅር ያፈቀረኝ ዋጋ ያለኝ ፍጥረቱ እንደሆንሁ ያሳወቀኝ አባት እንዳለኝ ማወቄ ነው:: ይህን ስጽፍ ሥጋዬን፣ አጥንቴንና ጅማቴን እስኪለይ የሚወጋ ፍርሃት ሰቅዞ ያዘኝ። ይህን ፍቅር የከዳ መጨረሻው ምን ይሆን? ለኃጢአትስ ይህን ፍቅር መክዳት እንጂ ሌላ ምን ትርጉም ይሰጠዋል?! ጌታ ሆይ እኔ ጎስቋላው ፍቅርህን ስለ መክዳቴ እንደ ቀራጩ አንቴን አቀርቅሬ ሳይሆን በፊቴ ምድር ላይ ተደፍቼ በጥርሴ ድንጋይ ነክሼ "ማረኝ ለማለት እንኳ ስለ ደፈርሁ ማረኝ" እልሃለሁ። ማረኝ ለማለት ድፍረት የሰጠኝን ፍቅርህንም አመሰግናለሁ!!!
ለድኅነታችን በተመረጠች በዚህች ዕለት ጌታችን በመስቀሉ በዚህ ዓለም ያሉ ክፉ ነገሮች ትክክለኛ ማርከሻቸው ምን እንደሆነም አሳየን። መከራ የሚሸነፍ በትዕግሥት፤ ጥላቻ የሚሸነፍ በፍቅር፤ የክስና የሁከት መቋጫው አርምሞ፤ የፍርድ መሻሪያው ምሕረት፤ ቂምን ማጥፊያው ይቅርታ፤ ዘላለማዊ ሞትን ድል መንሻውም ለሥጋ ፈቃድና ለዓለም ምውት መሆን አልያም የምሥክርነት ሞት (መናንያንን፣ ምዕመናንንና ሰማዕታትን ሕይወት ልብ ይዟል፤ ሞትን ድል የነሡት እንደ ጌታቸው በሞት ነው)፤ ወዘተ . . . መሆኑን አሳየን።
ጨምሮም በምድር በሚደረስብን መከራና ሥቃይ ብንታገሥ ቃላት የማይገልጸው መጽናናት ከብርሃናት አባት እንደሚሰጠን አስገነዘበን። መከራና ሥቃይ የዕድለ ቢስነት አንዳንዴም በእግዚአብሔር የመቀሰፍ ምልክት ተደርጎ ይወሰድ የነበረውን አስተሳሰብ ቀየረው። ስለ እርሱ እንኳ "እኛ ግን እንደ ተመታ በእግዚአብሔርም እንደ ተቀስፈ እንደ ተቸገረም ቆጠርነው" እንዳለ ነቢየ ልዑል ኢሳይያስ። ኢሳ . 53 እኛ ካሳደርነው አመለካከት ውጪ የእርሱ መከራና ሥቃይ ማኅየዊት (የምታድን፤ ሕይወትን የምትሰጥ) መሆኗን አሳየን። በመከራ የሚማረር ሳይሆን የሚያመሰግን አዲስ መንፈስ ተቀበልን።
የጌታ ሞቱ ደግሞ ሞትን ራሱን ሳይቀር ተናፋቂ፣ ተፈላጊ አደረገው። ቀድሞ በአንዳንዶች ዘንድ ይፈራ ወይም በሌሎች ዘንድ ትርጉምና ስሜት የማይሰጥ (meaningless and senseless) የነበረውን የሞትን መሠረታዊ ባሕርይ በሞቱ ቀይሮ በእርሱ ወደ አገኘነው ዘላለማዊ ሕይወት መሻገሪያ መንገድ ስላደረገው ክርስቶስን በሚወድ ልብ ሁሉ ሞት ተናፋቂ ሆነ። ቅዱስ ጳውሎስ ስለ ሞቱ ሲናገር "ልሄድ ከክርስቶስ ጋር ልኖር እናፍቃለሁ" በማለት 'ናፍቆት' ብሎ ሞትን ጠራው። ሞት እራሱ በዚህ ቸርነትና የማዳን ጥበብ እንዴት ይደነቅ? ፊልጵ. 1
ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ የማይሞተው መሞቱን ካደነቀ በኋላ ምክንያተ ሞቱን ሲያብራራ ". . . ሞተ ከመ ይሥዓሮ ለሞት፤ ሞተ ከመ ያኅይዎሙ ለሙታን" ይላል። የማይሞተው የሞተው ሞትን ይሽረው ዘንድ ማለት ለጊዜው የቀደመ ግብሩን ያስጥለው ዘንድ ኋላም በትንሣኤ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ሊሽረው ነው በማለት ያውጃል። የሞት የቀደመ ግብሩ ትርጓሜ ሞተ ነፍስ እንዳለብን ማመልከትና የነፍስ ከሥጋ ብቻ ሳይሆን የነፍስ ከእግዚአብሔር መለየት ጭምር ነበር። ከጌታ ሞትና ትንሣኤ በኋላ ግን በሥጋ ርስት የነፍስና የሥጋ መለየት ብቻ ሲሆን እኛን ከእግዚአብሔር የመለየት ግብሩንና መዳረሻ መሆኑን ትቶ ወደ አባታችን መንግሥት መሄጃ ጎዳና ሆነ።
ሁለተኛውን የጌታን ምክንያተ ሞት 'ሙታንን ሕያዋን ያደርጋቸው ዘንድ ሞተ' በማለት ገልጾታል:: በኅሊና ምውት የነበሩ በአሚን በንስሐ ሕያዋን ይሆናሉ። ይህም ፊተኛው ትንሣኤ ወይም ትንሣኤ ኀሊና ይባላል። ይህቺ ምዕመን ዘወትር የሚኖራት ዕለተ ዓርብ ናት። ዕለተ ዓርብ ዕለተ ድኅነት እንደ መሆኗ ካሣና የሰውም ድኅነት ሳይፈፀም አላደረም። ምዕመናንም የመዳን ቀን አሁን ናት በማለት ቅዱስ ጳውሎስ በምሥጢር የገለጣትን ዕለተ ዓርብን በየዕለቱ ሳይኖሯት፤ ለድኅነታቸውም አንብዓ ንስሐን ሳይክሱ ማደር አይገባቸውም፡፡ እያንዳንዷ ዕለት በተለየ ስያሜ ብትጠራም ክርስቲያን ግን የሚኖረው ሁለት ዕለታትን ነው፤ ዓርብንና እሁድን። በየዕለቱ ዓርብን የሚኖሩ ብፁዓን፤ በሥጋ ርስት ሳሉ ዕለተ እሁድን የሚኖሯት ደግሞ ፍፁማን ናቸው። በሥጋ ምውት የሆኑም በትንሣኤ ዘጉባኤ ተነሥተው ይገለጣሉ። ይህም ኋለኛው ትንሣኤ ነው። ለሁሉ ይደረጋል ግን አንዱ ለክብር አንዱ ለኀሣር ይነሣል።
ዕለተ ዓርብ በአንድ ቀን በአንድ ጸሐፊ ብዕር ወይም በአንድ ተናጋሪ ከንፈር የምትገለጥ አይደለችም፤ እስከ ምጽዓት በሰማይም ሆነ በምድር ባለ ፍጥረት ሁሉ ስትተረክ ስትዘከር የምትኖር እንጂ። ("እስከ" ው ፍጻሜ የሌለው እስከ ነው:: "እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ከእናንተ ጋር ነኝ" እንዳለው ያለ ነው) ዕለቲቱን በልቡናው ሕያው የሚያደርግ ሕያው ይሆንባታል፤ የሚያስባት ይታሰብባታል፤ የሚያከብራት ይከብርባታል!!!
የተለዩት መከራውንና ሞቱን በሚሞት ሥጋቸው ተሸክመው 'አቤቱ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበን ' ይሉታል። እርሱም የእኛን ድኅነት የተጠማበትን ልክ በሚያሳይ ደርቆ ምላሱ ከትናጋው በተጣበቀ አንደበት 'ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናላችሁ!' በማለት በአጽንዖት ፍጻሜያችንን ያበስረናል።
ጌታ ሆይ ነፍሳችን አንተን ብቻ ትሻለች፤ አንተ ባለህበት መኖርን ብቻ ትናፍቃለች። አንተ እንጂ ሌላ ምንም ምን ለነፍሳችን ዕረፍትን ሊሰጣት አይችልምና፤ ከአንተ ጋር እንኖር ዘንድ ምራቅንና ንቀትን በመታገስህ፣ በግርፋትህ፣ በችንካርህ፣ ደምህን በማፍሰስህ፣ በሞትህ ፈቅደሃልና አጽናልን!!!
"ተዘከረነ እግዚኦ በውስተ መንግሥትከ፤ ተዘከረነ እግዚኦ አመ ዳግም ምጽአትከ፤ አሜን!"
በክርስቶስ አገልጋያችሁ!
ቀሲስ ታምራት ውቤ
ሚያዚያ ዕለተ ስቅለት, 2016 ዓ.ም
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን !
ጌታቸው ይፈልጋቸዋል!
ማቴ 21፥3
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ ለመግባት በተቃረበበት ሰዓት ከደቀ መዛሙርቱ ሁለት ጠርቶ "በፊታችሁ ወዳለች መንደር ሂዱ፤ አህያ ከውርንጫዋ ጋር ታሥራ ታገኟታላችሁ፤ ፈትታችሁ አምጡልኝ፤ ማንም ቢጠይቃችሁ ጌታቸው ይፈልጋቸዋል በሉ" ሲል ላካቸው። እነርሱም ለጠያቂዎቻቸው የነገራቸውን መልስ ሰጥተው ማንም ሳይቃወማቸው አህያይቱን ከውርንጫዋ ጋር አመጡለት። ማቴ 21፥3 በአማርኛው "ለጌታ ያስፈልጉታል" ተብሎ የተተረጎመው ትንሽ የቀና አይደለም። በግዕዝ "በሉ እግዚኦሙ ይፈቅዶሙ" የሚለው ሲተረጎም ጌታቸው ይሻቸዋል፤ ጌታቸው ይፈልጋቸዋል የሚለው የቀና ይሆናል።
ይህ ጌታ ለደቀ መዛሙርቱ የሠጠው የተልዕኮ መመሪያና የተፈጸመበት ሁኔታ እስከ ምጽአት ለምንኖር ክርስቲያኖች ጥልቅ የሕይወት መመሪያ ነው፡፡ እንደ አበው ትርጓሜ አህያይቱና ውርንጫዋ ቀድሞም የተሰረቁ ስለ ነበሩ ወደ ቀደመ ቤታቸው እንዳይመለሱ ነበር ሰራቂዎቹ ያሰሯቸው። የጌታ ደቀ መዛሙርት ሲፈቷቸው ለጠየቋቸው "ጌታቸው ይፈልጋቸዋል" የሚል መልስ ሲሰጡ ተቃውሞ ያልገጠማቸው ለዚያ ነው::
ምሥጢሩ ግን የሰው ልጅን ታሪክ የሚገልጥ ነበር። አዳምና ሔዋን እንዲሁም ልጆቻቸው ወደ ጌታቸው እንዳይመለሱ የበደል እሥራት ጠፍንጎ ያዛቸው። እነርሱ የታሰሩበትን መበጠስ ስላልቻሉ ፈትቶ ነጻ ሊያወጣቸው እርሱ ወደዚህ ዓለም መጣ። ስለዚህ የአህያይቱና የውርንጫይቱ ታሪክ አዳምና ዘሩ በዲያብሎስ ተታለው በኋጢአትና በበደል እሥራት ተይዘው መቆየታቸውንና አሁን የሚፈቱበት ጊዜ መድረሱን ይጠይቃል። ለምን ይፈታሉ? የሚል ጠያቂ ቢኖር ምክንያቱም "ጌታቸው ይፈልጋቸዋል" ነው መልሱ፡፡
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያይቱና በውርንጫዋ ተቀምጦ በምስጋና ወደ አባቱ ቤት እንደ ገባ በልባችን ዙፋን እንዲቀመጥና በሕይወታችን በክብር እንዲገለጥ መጀመሪያ ከእስራት መፈታት ይኖርብናል። ብዙዎቻችን የምኞት፣ የፉክክር፣ የስስት፣ የትዕቢት፣ የምቾት፣ የቀጠሮ፣ የልማድ፣ የዓለም፣ ወዘተ . . . እሥረኞች ሆነን ሳንፈታ እንደ አህያይቱ እንዲቀመጥብን (እንዲያድርብንና እንዲገለጥብን) እንመኛለን። የታሰረ ወዴት መንቀሳቀስ ይችላል? የብዙዎቻችን መንፈሳዊ ሕይወት "ባለህበት እርገጥ" የሆነው ለዚህ ነው። የቦታ፣ የጊዜ ማሳለፊያ፣ የጓደኞችና የመሳሰሉት ለውጥ ብቻውን የሕይወት ለውጥ ለመባል አይበቃም። እውነተኛ ለውጥ የሀልዮ፣ የነቢብ፣ የገቢር ለውጥ የሚታይበት የውስጥ መታደስ ነው።
ይህ ለውጥ በሕይወታችን እንዲገለጥ ከእሥራት የሚፈታን ምንድር ነው? ካልን 'ጌታችን እንደሚፈልገን' አምኖ መቀበል ነው፡፡ ጌታችን ሊያድርብን እንደሚፈልግ ሲያመለክተን ከእሥራት የሚፈታንን ቃሉን ልኮልናል፡፡ በምኞት ለታሠርን "ዓለሙም ምኞቱም ያልፋሉ ፤ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ ግን ለዘላለም ይኖራል" 1ዮሐ 2፥16-17፤
በፉክክር ለታሠርን "ሰው ፊተኛ ሊሆን ቢወድ ከሁሉ በኋላ የሁሉም አገልጋይ ይሁን " ማር 9፥33-37፤
በስስት ለታሠርን "የሰው ሕይወት በገንዘቡ ብዛት አይደለምና ተጠንቀቁ፤ ከመጎምዥትም ሁሉ ተጠበቁ" ሉቃ 12፥13-21፤
በትዕቢት ለታሠርን " እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ይቃወማል ለትሑታን ግን ጸጋን ይሰጣል" ያዕ 4፥6፤ በምቾት ለታሠርን "ቀይ ልብስና ቀጭን የተልባ እግር የለበሰ አንድ ባለ ጠጋ ሰው ነበረ፤ ዕለት ዕለትም እየተመቸው በደስታ ይኖር ነበር " ብሎ ፍጻሜው ስላላማረው ሰው ሉቃ 16፥19-31፤ በጥዑመ ልሳን ጳውሎስም ቃል ". . . ቅምጥሊቱ ግን በሕይወቷ ሳለች የሞተች ናት" 1 ጢሞ 5፥6፤
በቀጠሮ ለታሠርን "ጌታችሁ በማታውቋት ሰዓት ይመጣል . . . ቀኒቱንና ሰዓቲቱን አታውቁምና እንግዲህ ንቁ " ማቴ 25፥1-13፤
በልማድ ለታሠርን "እግዚአብሔር መንፈስ ነው፤ የሚሰግዱለት በመንፈስና በእውነት ሊሰግዱለት ያስፈልጋቸዋል" ዮሐ 4፥21-24፤
በዓለም ለታሠርን "ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱን ቢያጎድል ምን ይጠቅመዋል? ወይስ ሰው ስለ ነፍሱ ቤዛ ምን ይሰጣል?" ማቴ 16፥26፤ የሚል ቃሉን ልኮ ሊፈታን ወደደ፤ እኛ ግን አመነታን! ፈቃዳችንን ለመሠዋት አንገራገርን። የሁል ጊዜ ጭቅጭቃችን ከነ እሥራታችን እንዲያድርብን ነው። እርሱ ደግሞ የሚቀመጥብን/ የሚያድርብን ወደ አባቱ ቤት ይዞን ሊገባ ነው:: የታሠረ ሕይወት ለጌታ ክብር ሊሆን አይችልም።
ኅሊናችን በሀሳብ ብዛት፤ ልባችን በምኞትና ጭንቀት፤ መንፈሳችን በድካም፣ በመዘንጋት፣ በቸልተኛነት፣ የሚበልጠውን ባለ ማስቀደም፤ ጊዜያችን በዋዛ ፈዛዛ፤ ፍቅራችን በግብዝነት ባልንጀርነታችን በጥቅም፤ ራዕያችን በምድራዊነት፤ ማንነታችን በማስመስል አምልኳችን በከንፈር ታሥሯል። ከዚህ እሥራት በቃሉ ካልተፈታን መቼም መች "ሆሣዕና" ብለን ልንዘምር አንችልም። ሆሣዕና ድኅነትን የምትጠማ ነፍስ የየሰከንዱ ዝማሬና ጸሎት ነውና። ሆሣዕና ማለት "አቤቱ እባክህ አሁን አድን" ማለት ስለሆነ።
የነፍሳችን መድኃኒት 'አቤቱ እባክህ አሁን አድን' ስንለው ሰምቶ እንዲቀርበን፤ ተሰርቀን ከታሰርንበት ሊፈታን ቃሉን በአገልጋዮቹ ሲልክ ለመፈታትና ወደ እርሱ ለመሄድ ቁርጥ የልብ ፈቃድ ያስፈልጋል። ከቁርጠኛ ልብ የሚወጣ ፈቃድን የመሠዋት ቃልም "ጌታ ሆይ ምን አደርግ ዘንድ ትወዳለህ?" ይላል። አፈ በረከት ጳውሎስ የእግዚአብሔር ጥሪ ሲደርሰው እንዳላመነታ ሲገልፅ " ነገር ግን በእናቴ ማኅፀን ሳለሁ የለየኝ በጸጋውም የጠራኝ እግዚአብሔር በአሕዛብ መካከል ስለ እርሱ ወንጌልን እሰብክ ዘንድ ልጁን በእኔ ሁኔታ ሊገልጥ በወደደ ጊዜ ወዲያው ከሥጋና ከደም ጋር አልተማከርሁም" ይላል። ከላይ የጠቀስናቸው ሁሉ ኅሊናችንን፣ ልባችንን፣ መንፈሳችንን፣ ጊዜያችንን፣ ማንነታችንን፣ ፍቅራችንን፣ ወዘተ . . . ብቻ ሳይሆን ለዘለዓለም ከእርሱ ከጌታችን ጋር የሚኖረንን ሕይወት ሰርቀውናል፡፡ ዛሬ መቁረጥ ካልቻልን ከሕይወት ግንድ ለዘላለም ተቆርጠን እንጣላለን። የሐዋ.ሥራ 9፥6፤ ገላ 1፥15 ፤ ዮሐ 15፥1
ልጆቼ ማስተዋል ካልተለየን በቀር ጌታችን እኛን ከመፈለግ የደከመበት ጊዜ የለም። ከእሥራታችን ሊፈታንም ቃሉን በአገልጋዮቹ ልኳል። እነርሱም ጌታችሁ ይፈልጋችኋል እያሉ ከመጮኽ አልሰለቹም። ጥሪውን ሰምተን ከመለስን "ነፍሳችን እንደ ወፍ ከአዳኞች ወጥመድ አመለጠች፤ ወጥመድ ተሰበረ እኛም አመለጥን፤ ረድኤታችን ሰማይንና ምድርን በሠራ በእግዚአብሔር ስም ነው" የሚለው ዝማሬ ከነፍሳችን ጥልቅ የሚወጣ ይሆናል። መዝ 123(124)፥7-8
በሰማይ የሃሉ ልብክሙ!!!
ሆሣዕና
አቤቱ እባክህ አሁን አድን፤
አቤቱ እባክህ አሁን አቅና!
መዝ 117(118)፥25
በክርስቶስ አገልጋያችሁ !
ቀሲስ ታምራት ውቤ
ሚያዚያ, 2016 ዓ.ም
💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ወዴት ነው?
ሰው በሕይወቱ 'ምን' እንደሚፈልግና 'ለምን' እንደሚፈልግ ብቻ ሳይሆን 'የትና እንዴት' መፈለግ እንዳለበት ማወቅ ይኖርበታል። የክርስቲያን ዋና ፍለጋው እግዚአብሔርን መሆን ይገባል። የፈለገው እግዚአብሔር ራሱን እንዲገልጥለት ግን ለምን እንደሚፈልገው ከእውነተኛ ልብ የፈለቀ ምክንያት ይሻል። ጌታ እግዚአብሔር ራሱን የሚገልጥልን በጥያቄያችን ልክ ነው። ለመብል ከፈለግነው ምግቡን ያቀርብልናል፤ ጤና ከጠየቅነው ፈውስ ይልክልናል፤ እውቀትና ሀብት ከሆነም ያንኑ ይሰጠናል፤ . . . እያለ ይቀጥላል እርሱ ግን አይኖርም። እርሱ አብሮን የሚኖር ዘላለማዊ ጥያቄ ስናቀርብ ብቻ ነው፤ ሕይወት! ሕይወት በመልእክተኛ የምትላክ ነገር አይደለችምና፤ ሕይወትም እርሱ ነውና ፤ ሕይወትን ስንጠይቀው ራሱን ይሰጠናል፤ አብሮንም ይኖራል።
ቀጥሎ የሚመጣው የት ነው የምናገኘው? የሚለው አድካሚ ጥያቄ ነው፡፡ ሰማይ መስሏቸው አሻቅበው ሲጠብቁ በአጠገባቸው አልፏቸው ሲሄድ ያላወቁት ብዙዎች ናቸው፤ "እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሟል" እንዲል። በርካቶችም "እንግዲህ እነሆ በበረሃ ነው ቢሏችሁ አትውጡ፤ በእልፍኝ ነው ቢሏችሁ አትመኑ" የሚለውን ዘንግተው ደጋ በመውጣትና ቆላ በመውረድ ይደክማሉ። ዮሐ 1፥26፤ ማቴ 24፥26፤ ዮሐ 10፥10
ሰብአ ሰገል "የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ የት ነው?" እያሉ ንጉሥ ፈልገው ቢመጡም ቤተ መንግሥት አላገኙትም። ሐዋርያት "መምህር ወዴት ትኖራለህ "? ብለው የት ሊያገኙት እንደሚችሉ ቢጠይቁት "መጥታችሁ እዩ" አላቸውና በሕመምና በኑሮ የተጠቁ ምንዱባን ያሉበት ሥፍራ፤ ኃጢአተኞችና ቀራጮችም መካከል አዋላቸው። የእውነተኛይቱ ድንኳን አገልጋይ የሆነው ሊቀ ካህናት በመቅደስ አልተገኘም በመስቀል ላይ እንጂ። ማቴ 2፤ ዮሐ1፤ ማቴ 27
ራሱን ለሞት አሳልፎ ከሰጠ በኋላ ሥጋውን ሽቱ ለመቀባት ወደ መቃብሩ የመጡ ሴቶችም በዚያ አላገኙትም። ይልቁን ነጫጭ የለበሱ ጎልማሶች "ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትሹታላችሁ? በዚህ የለም፤ እንደ ተናገረ ተነሥቶአል" በማለት ከማመን የዘገየ ልባቸውንና ከንቱ ድካማቸውን ወቀሱ። ዛሬም ልናገኘው ያልቻልን ሕያውን ከሙታን መካከል እየፈለግን ነው። ሉቃ 24፥5
በኃጢአት፣ በትዕቢትና በልማድ የሞተ ኅሊና፤ በፍቅር፣ በይቅር ባይነት፣ በትሕትና ሕያው ያልሆነ ልቡና ውስጥ አይገኝም። እዚያ ውስጥ ለመፈለግ ብንሞክር ". . . በዚህ የለም" የሚል ድምፅ ነው የምንሰማ። በሽንገላና ማስመሰል በሞተ ሕይወት ውስጥም አይኖርም።
መተሳሰብ፣ መከባበር፣ መደማመጥ፣ መሸናነፍ፣ ወዘተ. . . ተቀብረው፤ ራስ ወዳድነት፣ መናናቅ፣ እልህ፣ በነገሠበት የሞተ ትዳር ውስጥ ብንፈልገው አይገኝም። በአንድ ሀሳብና በአንድ ልብ ሆነው በማይተጉበት፤ ማንም ከእርሱ ይልቅ ወንድሙ እንደሚበልጥ በትሕትና በማይቆጥርበት፤ ሐሜትና ወረት በበዛበት፤ አድማና ነቀፌታ በሠለጠነበት፤ ፍቅር በኩራት መታዘዝ በልግም ትጋት በምክንያት በመከኑበት የሙታን ጉባኤም የሕያዋን አምላክ አይኖርም። የሐዋ. ሥራ 1 እና 2፤ ቈላ 3፥12-17
ወንድሙን በእውነተኛ ፍቅር መሳም ያቃተው ኢየሩሳሌም ሄዶ ለመሳለም የሰበሰበውን ይከስራል። የሞቱና የትንሣኤው ነገር ያልገባው የጌታን መቃብር አየሁ ተሳለምሁ እያለ ዕድለኛነቱን ይለፍፋል። በትንሣኤው ያመኑ 'ኮ ድጋሚ ወደ መቃብሩ እንደሄዱ አልተጻፈም!!! እርሱም ሞቶ በመቃብር ያደረ ሞትና መቃብርን ለማጥፋት እንጂ መቃብሩን የሚጎበኝ ተከታይ ለማፍራት አልነበረም። ያደላት ሀገር ባላመነችበት እውነት እየነገደች ሕዝቧን ትመግባለች። የሕይወት ኅብስት መሆኑን ባለመቀበሏ ሳይጨክን ለአባቶቿ ቃል እንደገባ ማርና ወተት ሆኗት ትኖራለች። ለገዳዮች መብልና መጠጥ መሆን እንዴት ያለ ኂሩት (ቸርነት) ነው?! ኋላ ግን አልሰማሁም በማለት ከፍርድ እንዳታመልጥ በቱሪዝም የበላችው ገንዘብ ምስክር ይሆንባታል።
ክቡር ዳዊት "የእግዚአብሔርን ቸርነት በሕያዋን ምድር አይ ዘንድ አምናለሁ" ይላል። ከቅን ኅሊናና በፍቅር ከተሞላ ልቡና በላይ የሕያዋን ምድር ምንድር ነው? ራሳችንን ክደን በመተሳሰብ ከምንኖርበት ትዳር፤ ሽንገላ ከሌለበትም ሕይወት በቀር የሕያዋን ምድር ምን ሊሆን ይችላል? በአንድ ልብ በትሕትና ከመሰብሰብ፤ በቅንነት ከመታዘዝ፤ ግብዝነት በሌለው ፍቅር ወንድምን ከመውደድ፤ በደልን ሳይቆጥሩ ይቅር ከማለትስ ያማረ የሕያዋን ምድር የት ይገኛል? መዝ 66፥12
የልጁን መልክ እንዳንመስል፤ መዓዛው መዓዛችን እንዳይሆን ከሚያደርጉን ትዕቢት፣ ክፋት፣ ምቀኝነት፣ ሐሜት፣ ግብዝነት፣ ሽንገላ፣ ሀሰት፣ ዝሙት፣ ምኞትና የመሳሰሉት ከሌሉበት በላይ የሕያዋን ምድር ወዴት ይገኛል? የት እንፈልገው? ለሚሉ የሕያዋን ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ያለ በዚያ ነው።
ጽሑፋችንን በአረጋዊው በአባ ሕርያቆስ ቡራኬ እንፈጽም "የእሳት ነበልባል ድንኳኖች ወደ ተተከሉበት የካህናት አለቃ ወዳለበት ያግባችሁ፤ የተሳለ የፊቱ መልክ ከዚያ አለ፤ ንጹሕ አክሊልና ብሩህ ልብስ ከዚያ አለ። እርሱም ከላይ የተገኘ ነው እንጂ የሰው እጅ ያልተጠበበበት ነው!" አሜን!!!
ምስጋናና ክብር ጥበብም ባለጠግነትም ውዳሴም ጌትነትም በዘፋኑ ላይ ለተቀመጠው ድል ለነሣው ለበጉም ከዘላለም እስከ ዘላለም ይሁን፤ አሜን!!!
በክርስቶስ አገልጋያችሁ!
ቀሲስ ታምራት ውቤ
መጋቢት, 2016 ዓ.ም
💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠💠
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
"ኢየሱስም ከመቅደስ ወጥቶ ሄደ"
ማቴ 24፥1
ለአካሉ መጠን ለግዛቱ ድንበር የሌለው አምላክ በመጠነ ብእሲ ተወስኖ፤ ለመላእክት ዓይነ ኅሊና እንኳ ረቂቅ የሆነው ተገልጦ በታየበት ወራት በ፵ ቀኑ እናቱና ቅዱስ ዮሴፍ ወደ መቅደስ ወሰዱት ተባለ። በዚያን ጊዜ በመቅደሱ የእግዚአብሔርን ማዳን ሳያይ እንዳይሞት በመንፈስ ቅዱስ ተረድቶ የሚኖረው ስምዖን አረጋዊ፤ ዕድሜዋን ሙሉ በጾምና በጸሎት እግዚአብሔርን እያገለገለች የምትኖረዋ ነቢይት ሀና ነበረች። እነርሱ በነበሩበት ወራት በንጽሕት ዙፋኑ (በእመቤታችን እቅፍ ) ሆኖ ወደ መቅደስ መጣ። ሉቃ 2
ጌታችንን ድጋሚ በመቅደስ ከአሥራ ሁለት ዓመት በኋላ ስናገኘው የመጻሕፍትን ነገር መመርመር በሚወዱ እውቀት ትሑት ባደረጋቸው መምህራን መካከል ነበር። ልጅ መሆኑን ሳይንቁ አብረውት መቀመጣቸውን ልብ ይሏል። ለነገሩ እርሱ "ልጅ" ያልነበረበት ጊዜ አልነበረም፤ አይኖርምም! ሉቃ 2 ፤ መዝ 2፥7
ጌታ አርባ ቀን ከጦመ በኋላ ፈታኝ ኢየሩሳሌም መቅደስ ጫፍ ላይ አቁሞ " ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝልሃል፤ እግርህንም በድንጋይ ከቶ እንዳትሰናከል በእጃቸው ያነሡሃል ተብሎ ተጽፎአልና የእግዚአብሔር ልጅስ ከሆንህ ከዚህ ወደ ታች ራስህን ወርውር" በማለት በትዕቢት ሲፈትነው እናያለን። ዲያብሎስ በመቅደስ ካህናትን በምን ዓይነት እንደሚፈትናቸው አሳይቶ ድል ነሣላቸው። ፈታኙን ድል የነሣልንን ራሱን ጌታችንን ካህናት ግን አሁንም በመቅደስ እንፈታተነዋለን። ሉቃ 4
በሌላ ጊዜ ወደ መቅደስ ሲመጣ መቅደሱ የገበያ ሥፍራ ሄኖ አገኘው። በዚህ አዝኖ በሬዎችንና በጎችን ርግብንም የሚሸጡትን፤ ገንዘብ ለዋጮችንም አስወጣ። "ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፤ እናንተ ግን የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁት" አላቸው። ተግሣጹን ተቀብለው ከመስተካከል ይልቅ አንተ ይህን ለማድረግ ምን ሥልጣን አለህ? እያሉ ሙግት ያነሡ ነበር። ሊቃውንት ጌታ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ተገልጦ ሲያስተምር ወደ መቅደስ የሄደ አራት ጊዜ እንደሆነና በመጨረሻው እንደ ሰቀሉት ያትታሉ። በእነዚህ ጊዜያት ግን የማይገባ ሥራ የሚሠሩትን እንደሚገሥፅ ሁሉ የታመሙትን ይፈውስ ሕዝቡንም ይመክር ነበር። ዮሐ 2
በመጨረሻ በአህያ ውርንጫ የሆሣዕና ዕለት ወደ ቤተ መቅደስ "ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ፤ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረከ ነው" እያሉ በሕዝብ ታጅቦ ገባ። አሁንም የገጠመው ግን ያው ንግድ ነበር። የገንዘብ ለዋጮችን ጠረጴዛ ገለበጠ፤ ርግብ ሻጮችን አስወጣ። አይሁድ ግን መልሰው ይህን በምን ሥልጣን ታደርጋለህ? እያሉ መሟገታቸውን ቀጠሉ። በመጀመሪያ ሲጠይቁት "ይህን መቅደስ አፍርሱት፤ በሦስት ቀን አነሣዋለሁ" በማለት ምልክት ሊሰጣቸው ሞክረ። በመጨረሻው ግን ጥያቄያቸውን ላለመመለስ በጥያቄ ዘጋው። ይህም ከእነርሱ ጋር ለመነጋገር ጊዜው መርፈዱን አመላካች ሆነ። ማቴ 21
ከሆሣዕና መልስ የምናየው ጌታችን ከመቅደስ ወጥቶ ሲሄድ ነው። ከዚያ በኋላ ዳግመኛ ወደ አይሁድ መቅደስ አልተመለሰም። ዶሮ ጫጩቶቿን ከክንፎቿ በታች እንድትሰበሰብ ልጆችሽን እሰበስብ ዘንድ ስንት ጊዜ ወደድሁ፤ አልወደዳችሁምም። እነሆ ቤታችሁ የተፈታ ሆኖ ይቀርላችኋል። እንደ ተናገረውም ሆነ! ማቴ 23፥37 ፤ ሉቃ 13፥35፤ ማቴ 24፥1
ከመጀመሪያ የነበረውን ሂደት አስተውሉ። ስምዖን አረጋዊን የመሰለ የእምነትና የተስፋ ሰው፤ እንደ ነቢይት ሀና በጾምና በጸሎት የሚጋደሉ በነበሩበት ሰዓት፤ የመጻሕፍትን ቃል የሚመረምሩ ትጉሃን መምሕራን በነበሩበት ጊዜ ሕፃኑ ኢየሱስ በእናቱ እቅፍ ወደ መቅደስ ሄደ፤ በአባቴ ቤት መሆን እንዲገባኝ አታውቁምን? አለ።
"ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፤ እናንተ የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁት" ሲል ያሰማው ተግሳፅ እንደ ስምዖን አረጋዊና ነቢይት ሀና ሆናችሁ በመቅደስ መገኘት ሲኖርባችሁ እናንተ ግን የአባቴን ቤት የገበያ ሥፍራ አደረጋችሁት ማለቱ ነው። ሊቀበሉት አልወደዱም፤ ይልቁን እንዴት እንዲያጠፉት መምከር ያዙ።
በቤቱ የሚሠሩትን ንግድ፤ ከዚያ አልፎ ክፋታቸውን፣ ተንኰላቸውን፣ ትዕቢታቸውን፣ አድማቸውን፣ ግብዝነታቸውን፣ ጥላቻቸውን ሲያይ "ኢየሱስ ከመቅደስ ወጥቶ ሄደ"። ጌታችን መቅደሱን ላይመለሰበት ጥሎት እንዲሄድ እንዲርቀው ያደረገ በውስጡ የነበሩ ካህናትና አይሁድ ክፋት ነው።
ጌታ እግዚአብሔር እኛ የምንሠራው የዕብነ በረድ መቅደስ የሚደንቀው አይደለም። "To a great mind nothing is great!" እንዲሉ። ወደ መቅደሱ የሚስበው የእኛ ሁኔታ ነው። በእምነት፣ በተስፋና በፍቅር ጸንተን፤ በጾም በጸሎት ተግተን፤ ከክፋት፣ ከተንኰል፣ ከምቀኝነት፣ ከትዕቢት፣ ከግብዝነት፣ ከአድማ፣ ከመለያየት፣ ከስግብግብነት፣ ወዘተ . . . ርቀን ካላየን ወደ መቅደሱ ላይመለስ ወጥቶ ይሄዳል።
ጌታ ከመቅደሱ ወጥቶ ከሄደ በኋላ በደብረ ዘይት ተራራ ሲቀመጥ ደቀ መዛሙርቱ ቀርበው ስለ ቤተ መቅደሱ ማማር ነገሩት። እርሱ ግን መልሶ "ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም" አላቸው። እርሱ የተለየው ነገር ፍጻሜው መፍረስ፣ ጥፋት፣ መበተን፣ መዋረድ፣ ጉስቁልና፣ ሞት፣ ኀዘን ነው፡፡ ጌታ ከመቅደሱ ወጥቶ ከሄደ ከጥቂት ቀናት በኋላ የመቅደሱ መጋረጃ ሲቀደድ ከ ፵ ዓመታት በኋላም ጨርሶ ሲፈርስ ይታያል።
እኛ እንደ ሕዝብ መከፋፋታችን፣ ጥላቻችን፣ መለያየታችን፣ ስግብግብነታችን፣ ትዕቢታችን፣ ወዘተ. . . እንደ መቅደሱ አገልጋዮች ደግሞ በቤቱ በምንፈጽምው የድፍረት ኃጢአት፤ መንጋውንም ስለ መርሳታችን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከኢትዮጵያና ከቤተክርስቲያን ለአንዴና ለመጨረሻ ወጥቶ የሄደ ጊዜ መጨረሻችን . . . (ጥፋቱ የማይቀር ከሆነ ጌታ ሆይ የሚፈሩህ "የሀገራቸውንና የቤተክርስቲያንን ጥፋት እንዳያዩ ባሮክንና አቤሜሌክን እንዳሰብሃቸው አስባቸው!)
የአዲስ ኪዳን መቅደስ የእኛ ሰውነት ነው:: ሰውነታችንን በተደጋጋሚ ሲጎበኘው በሚሞት ሥጋችን ኃጢአት ነግሦ በልቡናችን ሰሌዳ ርኵሰት ተነስንሶ አግኝቶት ሲገሥፀን አልሰማ ካልን በረድኤት ይለየናል። መጨረሻችን . . .
በሌላውም በእውቀታችን፣ በሥራችን፣ በትዳራችን፣ በባልንጀርነታችን፣ ወዘተ . . . ግብዝነት፣ ትዕቢት፣ አለመከባበር፣ ራስ ወዳድነት፣ ማስመሰል ከሆነ ተለይቶን ይሄዳል። ያን ጊዜ እውቀታችን ለጥፋት ሥራችንም ልፋት ይሆናል። ትዳራችን ሰላም ባልንጀርነታችን መተማመን አይኖረውም። መጨረሻችንም . . .
ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ከእነርሱ በራቅሁ ጊዜ ወዮላቸው! ትን. ሆሴዕ 9፥13
"ጌታ ሆይ እንደ ቸርነትህ እንጂ እንደ በደላችን አይሁን!"
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!
በክርስቶስ አገልጋያችሁ!
ቀሲስ ታምራት ውቤ
መጋቢት 29, 2016 ዓ.ም (የደብረ ዘይት
💠🎚️💠🎚️💠🎚️💠🎚️💠🎚️💠🎚️💠🎚️
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን !
በክርስቶስ ኢየሱስ እህት ወንድሞቻችን ሰላም!
ቀጥሎ ለተዘረዘሩት ጥያቄዎች አባታችን የሰጡትን መልስ ልናካፍላችሁ ወደድን!
🔴 ጥያቄዎቹም ፦
📣 1ኛ) ሰው የተፈጠረው በፈቃዱ አይደለምና ለምን ራሱን ማጥፋት ተከለከለ? (ራስ ማጥፋት ለምን ኃጢአት ሆነ?)
📣 2ኛ) ካለፈቃዳችን የተፈጠርንባት ሕይወት ለምን በፈተና የተሞላች ሆነች?
📣 3ኛ) ሰው ኑሮው ከሰለቸው (if he is burned out)፥ ህይወቱ ካስመረረችው ምን ያድርግ?
📣 4ኛ) ግራ የተጋባ ሰው መልስ ከአምላኩ እንዴት ያግንኝ? (ጸሎት እያረገም መልስ ያላገኘ)!?
🔴📖 መልስ:-
👉1. ራስን ማጥፋት ለምን ተከለከለ?
📌 ሀ. ከእምነት ማጣት መገለጫ የመጨረሻው ነው። ሰው ፈቅዶም ይሁን ሳይፈቅድ የፈጠረው እንዳለ ካመነ፤ ይህ ፈጣሪም ከራሱ ሕይወት ጀምሮ በዙሪያው ያለውን ሁሉ የፈጠረ መሆኑን ካመነ፤ አንድ ሊጠራጠረው የማይችለው ነገር ቢኖር ይህ ፈጣሪ የሚሠራውን አውቆ የሚሠራ መሆኑን ነው። ዙሪያችን ያለው በድንገተኛ አጋጣሚ የተገኘ ካልሆነ እኔም በአጋጣሚ ድንገት የተፈጠረሁ አይደለሁም ማለት ነው። ዙሪያዬን ያለውን የምገነዘበውንም ሆነ የማልገነዘበውን ሁሉ የፈጠረ እኔን እንደ ፈጠረኝ ካመንሁ፤ ፍጥረትም ዓላማና ጥቅም እንዳለው ከተረዳሁ፤ እንግዲያውስ እኔን ከሌላው ፍጥረት ተለይቼ የማልጠቅምና ዓላማ የሌለኝ ተደርጌ ልፈጠር እንዴት እችላለሁ? አይ እንዲህ የሚሠራ አምላክ መኖሩን ካላመንሁ ደግሞ ራስን ስለ ማጥፋት መጨነቅ የለብኝም! Just ማድረግ ነው። የሚገርመው ራስን ማጥፋት ዕረፍት የሚሰጣቸው የሚመሰላቸው ብዙ ሰዎች ከሞት በኋላ የሚብስ እንደማይጠብቃቸው ምን ማረጋገጫ አላቸው?
📌 ለ. ከእግዚአብሔር መሠረታዊ መርሕ ጋር የሚቃረን ስለሆነ ነው። እግዚአብሔር በባሕርዩ ሕይወት ነው:: ሁሉን የፈጠረውና ያንን ሕይወትነቱን በመፍጠር ያጋራን እርሱ ሕይወት በመሆኑ ነው:: በእርሱ ዘንድ ሞት የለም። ስለዚህ በራሳችን ላይ ሞትን መፍረድ የተሰጠንን ሕይወት ማቃለልና ከሕይወት በተቃራኒ መቆም ነው። ምክንያቱም እግዚአብሔር ማንም እንዲጠፋ (እንዲሞት) የማይፈቅድ ሕይወት ነውና።
📌ሐ. አንድ ሰው ሳይጠይቅ ተፈጠረ ማለት ሕይወቱ ዓላማ (ዋጋ) የለውም ማለት አይደለም። Nothing is precious than Life in the eyes of GOD! ስለዚህ ሰው ራሱን ሲያጠፋ ከዚህ ተቃራኒ ራሱን ዋጋ እንደሌለው ይቆጥራል። በሌላ አንጻር ስናየው ሠሪው (ፈጣሪው) ሳያስብ እንደፈጠረው ቆጥሮ የሚያሳየው ተግባራዊ ዘለፋ ነው።
🎚️🎚️🎚️🎚️🎚️🎚️🎚️
👉 2. ካለፈቃዳችን ተፈጥረን ለምን ሕይወት በፈተና የተሞላች ሆነች?
ጌታ እግዚአብሔር ሕይወታችን እንዲህ እንድትሆን አልፈጠረንም። ይህን ያመጣው የእኛ አልጠግብ ባይነት ነው። የአዳም ያላልኩት ይህ አልጠግብ ባይነት በእኛም ጎልቶ ስለሚታይ ነው። ሕይወታችን በፈተና የተሞላ እንዲሆን የሚያደርጉ ብዙ ምክንያቶች (በግልም በማኅበረሰብም ደረጃ ) መጥቀስ ይቻላል። በጥቅል ሲታይ ግን፦
📌ሀ. በሕይወታችን የምንወስናቸው ነገሮች ላይ ጥንቃቄ አለማድረግ** (በችኮላ፣ በይሉኝታ፣ በቂ መረጃ ሳይኖረን፣ የተለየ ጥቅም ፍለጋ፣ ራስን መግዛት አለመቻል፣ ፉክክር ፣ ወዘተ. . . )
📌ለ. ራስ ወዳድነት፦ ከራስ ጥቅምና ሀሳብ ወጥቶ ዛሬ ላሉ ብዙኃንና ነገ ለሚመጣው ትውልድ የማያሰብ ሥራ መሥራት
📌ሐ. ራስን አለመሆን፦ የምንፈልገውንና የምንሆነውን በራሳችን አቅምና ልኬት አለማድረግ፡፡ ሌሎችን በማየት ራሳችንን ጫና ውስጥ የሚከት አዙሪት ውስጥ ማስገባትና የመሳሰሉት ለእኛ ሕይወትን በፈተና የተሞላች እንድትሆን ያደርጋታው።
📌መ. ሌላው ብዙዎች ለመገንዘብ የሚከብደን እዚች ዓለም ላይ ለራሳችን ጥቅም ብቻ አለመምጣታችን ነው።ከእኛ የሚጠበቀው ያላትን በረከት የቻልነውን ያህል ተጠቅመን መሄድ ብቻ ይመስለናል። ግን ትናንት የኖሩ ሰዎች ያለፉበት መከራ ለእኛ የተሻለ ሕይወት አስተዋፅዖ እንዳለው ሁሉ ዛሬ እኛ የምናልፍበት ፈተናና መከራም ነገ ለሚመጡት የተሻለ ዓለም (ሕይወት) ፈጥረን እንድናልፍ ምክንያት ነው።
ለምሳሌ:- ትናንት ብዙ እናቶች በወሊድ መሞታቸው በባሎቻቸውና በቤተሰባቸው ላይ የፈጠረው ኀዘን ዛሬ ሴቶች በወሊድ እንዳይሞቱ የህክምና ጥበቡን አሳድጎታል። ትናንት ብዙዎች በወረርሽን መከራ ውስጥ ማለፋቸው ዛሬ ክትባት እንዲኖር አስችሏል። እኛም ዛሬ የምናልፍበት መከራ ለነገ የተሻለ ሕይወት ዘር (seed) ይሆናል።
🎚️🎚️🎚️🎚️🎚️🎚️🎚️
👉3. ሕይወት አትሰለችም ሕይወትን የምንኖርበት መንገድ ነው የሚሰለቸን።
ሕይወት የምትኖረው በአንድ ወይም በተወሰነ መንገድ ብቻ ስላልሆነ በቁርጥ ውሳኔ ለለውጥ መነሳት። ከቀን ተቀን እንቅስቃሴያችን ጀምሮ ትናንሽ ቢሆኑ እንኳ ለውጦች ማድረግ። አዲስ ነገር መማር፣ መሞከር፣ መተዋወቅ፣ ወዘተ . . . ሕይወትን የምንኖርበት መንገድ አሰልቺ እንዳይሆን ያደርገዋል።
ሌላው ባለን ነገር መደስትን መለማመድ ነው። ደስታ ከውስጥ የሚፈልቅ እንጂ ከውጪ የሚቀዳ አይደለም። ባለን ትንሽ ነገር ተጠቅመን ሕይወትን ውብ ለማድረግ ከሞከርን ብዙ ይጨመርልናል። ባለን የመደሰት ልምድ ከሌለን ግን በዓለም ያለው ሁሉ ቢሰጠን ደስታን ማምጣት አንችልም። ሁሉ ያለው ደግሞ እርካታውን ስለሚነጠቅ ደስታ አይኖረውም። ጌታ እግዚአብሔር ሁሉን የማይሰጠን ጉድለት በራሱ የደስታ ምንጭ መሆኑን ስለሚያውቅ ነው። ሁሉ ሲሞላ ደስታ ይጎድላል! ልብ ያለው ያስተውል !!!
📌📌📌 እና ከሁሉ መረሳት የሌለበት ተስፋ ላለመቁረጥና በሕይወት ላለመሰላቸት "ነገ ሌላ ቀን መሆኑን አስብ" ማንም ነገ ምን ይዞ እንደሚጠብቀው አያውቅም። Learn from the past, enjoy the present, plan with hope for the future. That's it !!!
🎚️🎚️🎚️🎚️🎚️🎚️🎚️
👉4. የጠየቅነውን ሁሉ መስጠት እግዚአብሔር ለእኛ ያለው የአባትነት ፍቅር አይፈቅድለትም፡፡ የተጠየቀውን መስጠት የትክክለኛ ወላጅ መገለጫም አይደለም። እኛ ለልጆቻችን የማናደርገውን እርሱ እንዲያደርግ መጠበቅ ምክንያታዊ አይደለም። ስለዚህ፦ የጠየቅነው ምንድር ነው? ያላገኘነው መልስ ነው ወይስ እኛ የምንፈልገው ዓይነት መልስ? ይህን ርቱዕ በሆነ ኅሊና መመርመር ይገባል።
በቀሲስ ታምራት ውቤ
መጋቢት 2016 ዓ.ም
💠🎚️💠🎚️💠🎚️💠🎚️💠🎚️💠🎚️💠
ጸሎት ከምጽዋትና ከፍቅር ከእምነትም ነገር ጋራ ያማረ የተወደደ ነው ሠርቆ ቀምቶ ካጠራቀሙት ከብዙ ገንዘብ በእውነት ያጠራቀሙት ጥቂት ገንዘብ ይሻላል።
ምጽዋት ከሞት ታድናለችና ከኃጢአትም ሁሉ ታነፃለችና ወርቅ ከማደለብ ምጽዋት መስጠት ይሻላል ምጽዋትና ጽድቅንም የሚያደርጉ ሰዎች ሁሉ ለራሳቸው ሕይወትን ያገኛሉ።
መጽሐፈ ጦቢት 12፥8-9
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን !
መንግሥተ ሰማያት
በክርስቶስ ልጆቼ ሰላም ለእናንተ ይሁን!
በቅርቡ አንድ ልጄ ከማንኛውም ምድራዊ ምኞት እንዴት ነጻ መሆንና ጣዕመ መንግሥተ ሰማያት መቅመስ እንደሚቻል ጥያቄ ላከልኝ። ጥያቄውን በራሱ መንገድ እንዲመልሰው ለመፍቀድ አስቤ መንግሥተ ሰማያት ምንድር ናት? የሚለውን ሀሳብ በማብራራት መንገድ ልጠርግለት አሰብሁ።
መንግሥተ ሰማያት ተቀዳሚ ተከታይ የሌላት ቅድምና መጨረሻ አልቦ ፍጻሜ ናት። ተነጻጻሪ የሌላት ምርጫ፤ አምሳያ የሌላት ዓይነተኛ ናት።
መንግሥተ ሰማያት ሀሰት የማይቀርባት እውነት፤ ጨለማ የሌለባት ብርሃን፤ ድካም የማያውቃት ብርታት፤ ድንቁርና የማይደፍራት እውቀት፤ ዝንጋዔ የሌለባት ንቃት፤ ሽንፈት ማታስተናግድ ጽንዓት፤ ቅሬታ ያልለከፋት ምስጋና ናት።
መንግሥተ ሰማያት ቍጣ የሌለባት ትዕግሥት፤ ትዕቢት የማታውቅ ትኅትና፤ መለያየት የማያሰጋት አንድነት፤ ንፍገት የማይደፍራት ልግስና፤ ርኵሰት የማታስተናግድ ንጽሕና፤ ልግም የሌለባት መታዘዝ፤ ቂም የማያሸንፋት ይቅርታ፤ ጥርጥር የሌለባት እምነት፤ መዛል የማታውቅ ተስፋ፤ ጥላቻ የማይከድናት ፍቅር፤ ኀዘን የማይጎበኛት ደስታ፤ ሁከት የማያደፈርሳት ሰላም ናት።
ሁሉን አጥቶ አለመጉደል፤ ተንቆ አለመዋረድ፤ ሆድ ባዶ ሆኖ አለመራብ፤ ጉሮሮ ደርቆ አለመጠማት፤ ለብቻ ሆኖ ኅብረት፤ በመከራ መደሰት፤ ሁሉን ትቶ ለአንድን ብቻ ራስን መስጠት ናት መንግሥተ ሰማያት።
ይህ የገባው በዓለም ባለው ይጠቀማል እንጂ ከዓለም ምንም አይፈልግም። መንግሥተ ሰማያትንም ለመኖር ሞቱን አይጠብቅም፤ መንግሥተ ሰማያት ትገለጥለታለችና።
ልጄ ሆይ . . . መንግሥተ ሰማያት ገና የምትወርሳት ዓለም አይደለችም ዕለት ተዕለት የምትኖራት ሕይወት እንጂ! በትክክል ያልታወቀ መንገድ ያደክማል፤ ቅኝት የሌለው ዜማም ያውካል፤ ትርጒሙ ያልታወቀ ሕይወትም ፍጻሜው . . .
ይቆየን !
ወስብሐት ለእግዚአብሔር !
በክርስቶስ አገልጋያችሁ፤
ቀሲስ ታምራት ውቤ
የዘወረደ፤ 2016 ዓ.ም
አስደሳች ዜና
** ሎጎስ በማኅበራዊ ጉዳዮች የማማከርና የሥልጠና ተቋም መሰረታዊ ዓላማው የሚያፈራ ትውልድ ማትረፍ ስለሆነ ከሚሰጣቸው ስልጠናዎች ላይ ለተወሰነ ጊዜ የሚቆይ የ2000ብር ቅናሽ ማድረጉን በደስታ እንገልፃለን።
Repost from Janderebaw Media
"የወርቅ ቀለበት በእሪያ አፍንጫ"
|ጃንደረባው ሚድያ | ኅዳር 2016 ዓ.ም.|
✍🏽 ቀሲስ ታምራት ውቤ እንደጻፉት
ገና በአፍላ ዕድሜው እግዚአብሔር በመረጠው ታላቅ ሕዝብ ላይ የነገሠው ጠቢቡ ሰሎሞን በልጅነት ጫንቃው ላይ የወደቀበትን ኃላፊነት እንዴት ሊወጣ እንደሚችል ቢጨንቀው የበጎ ሥጦታዎች ሁሉ ባለቤት የሆነውን የአባቱን የዳዊትን አምላክ ጥበብን እንዲሰጠው ለመነ። ልዑሉም ከእርሱ በፊት ከእርሱ በኋላ የሚነሡ እንዳይተካከሉት ባለ ጠግነትንና መፈራትን ዳረጎት ጥበብን ደግሞ ዋና አድርጎ ሰጠው። የሰሎሞን ትልቁ ተግዳሮት እግዚአብሔር በመረጠው ሕዝብ ላይ መንገሡ ብቻ አልነበረም ይህን ሕዝብ ቀድሞ በንግሥና ሲመራ የነበረው ዳዊትን ያህል የከበረ ሰው መሆኑ ጭምር እንጂ።
የዛሬ አሳቤ ይህ ጠቢብ ንጉሥ በንግሥና ዘመኑ ስለነበረው ብዙ አስደናቂ ነገር ለመተረክ አይደለም። በጊዜው ከምናየውና ከምንሰማው አንጻር በሕይወቱ መጨረሻ ዘመናት ከተወልን የምክርና የተግሳፅ መጻሕፍቱ በአንዱ ባገኘሁዋት ኃይለ ቃል ቆይታ እንድናደርግ ወደድሁ፤ "የወርቅ ቀለበት በእሪያ አፍንጫ" ምሳሌ 11 ፥ 22
ሙሉውን ያንብቡ
Repost from Janderebaw Media
ደም ላነሳት ደም ልገሳ
| ጃንደረባው ሚድያ | ኅዳር 2016 ዓ.ም.|
✍🏽 ቀሲስ ታምራት ውቤ እንደጻፉት
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የ 12 ዓመት ታዳጊ የነበረችዋን የኢያኢሮስን ልጅ ከሕመሟ ለመፈወስ ሲጓዝ በመንገድ ብዙ ሕዝብ ያጨናንቀው ነበር። ከሚተራመሰው ሕዝብ የተወሰነው ተአምራት ሊያይ፤ ገሚሱ ሕብስት ሲያበረክት ጠብቆ ሊበላ፤ ሌላው መልኩን ሊያይ፤ ደግሞ ለበላይ አለቆች ያየና የሰማውን መረጃ ለማቀበል፤ የተቀረው ትምህርቱን ሊሰማ ይጋፋ ይዟል። ጌታችንም የሚጓዝ ይህ ሁሉ ሕዝብ እያጋፋው ነበር።
ይህ ሕዝብ እስከ ምጽዓት ክርስቶስን የሚከተሉ ሰዎችን የሚወክል ማሳያ ነው። ዛሬም በቤተክርስቲያን ለሆዱ ሲል ወይም በዚያ ያለው ሥርዓት ማርኮት፤ ደግሞም ትምህርት ለመስማት ብቻ፤ ተአምራት ለማየት ወይም ለተቃዋሚዎች ወሬ ለማቀበል የሚጋፋ አለ።
ሙሉውን ያንብቡ
