እሸት ሐሳቦች - Fresh Ideas (እ.ብ.ይ.)
Open in Telegram
666
Subscribers
-124 hours
-17 days
+1630 days
Posts Archive
ችግርህን ወይ ተቋቋመው፤ ወይ ተሰቃይበት!
(Mope or Cope)
(እ.ብ.ይ.)
የብዙዎቻችን ቸግር የደረሰብንን ችግር የምናይበት መንገድ ነው፡፡ ችግሩን የምናይበት መንገድ ራሱ ችግር ነው! (The way we see the problem is the problem)፡፡ አንደኛ ከችግሩ ልንወጣበት ያሰብነው መንገድ ራሱ ሌላ ችግር ውስጥ የሚከትት ነው፡፡ መንገዱ ወደገደል ይዞን የሚገባው መውጫ መንገዱን ያየንበት መንገድ የተሳሳተ በመሆኑ ነው፡፡ ሁለተኛ ችግሩን ልንፈታበት ያሰብነው መላ ትናንት በወደቅንበት መላ ነው፡፡ በወደቅንበት በኩል መነሳት ከባድ ነው፡፡ ጊዜ ባለፈበት ዘዴ አዲስ በር መክፈት አይቻልም (Old ways do not open new doors)፡፡ አዲስ እይታ፣ አዲስ መንገድ ወሳኝ ነው፡፡
ሰውየው ዛፍ እየቆረጠ ነው፡፡ አንድ መንገደኛ ‹‹ምን እየሠራህ ነው?›› ብሎ ይጠይቀዋል፡፡ ዛፍ ቆራጩም ‹‹የምሠራው አይታይህም? ዛፍ እየቆረጥኩ ነው እኮ!›› አለው፡፡ መንገደኛውም ‹‹በጣም የደከመህ ትመስላለህ፡፡ ምን ያህል ጊዜ ሆነህ ዛፍ መቁረጡን ከጀመርክ?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ ዛፍ ቆራጩም ‹‹ከአምስት ሠዓታት በላይ ይሆናል፡፡ ከአቅሜ በላይ ሆኗል፡፡ ከባድ ስራ ነው›› በማለት ስልችት ባለ ድምፀት መለሰለት፡፡ መንገደኛውም ‹‹ታዲያ ለምን ትንሽ ደቂቃ አታርፍምና መጋዙን ሞርደህ አትቀርጥም? ቶሎ የምትጨርስ ይመስለኛል›› አለው፡፡ ዛፍ ቆራጩም ‹‹ለመሞረድ ጊዜ የለኝም›› በማለት መለሰለት ይባላል፡፡
ዛፍ ቆራጩ ጊዜ የሌለው ለሚያደክም ስራ ነው፡፡ ጊዜውን ባግባቡ ለመጠቀም አልሞከረም፡፡ ፈረንጆቹ Busy for nothing እንደሚሉት ዓይነት ነው፡፡ ድካማችንን የሚያረዝመው ለችግሩ ያለን አስተሳሰብ ነው፡፡ ጊዜን ባግባቡ መጠቀም ማለት እንደዚህ አይደለም፡፡ አምስት ደቂቃ አርፈህና መጋዝህን ሞርደህ ድካምህንና ጊዜህን መቀነስ በማሰብ የሚገኝ መላ ነው፡፡ አምስት ደቂቃ አስቦ አምስት ሰዓታትን ማትረፍ ጊዜን በአግባቡ ከመጠቀም አልፎ ከጊዜ ከራሱ ማትረፍ ነው፡፡
በዋናነት እኛን የሚጎዳን ወይም የሚሰብረን የደረሰብን ወይም እየሆነብን ያለው ነገር ሳይሆን እየሆነ ላለውና ለደረሰብን ነገር የምንሰጠው መፍትሄ ወይም ምላሽ ነው፡፡ (It is not what happens to us but our response to what happen to us that hurts us):: እንቅፋቶቻችንን ሙሉ በሙሉ ቀድመን አውቀናቸው ልናስወግዳቸው አንችልም፡፡ የምንችለው ከእንቅፋቱ በኋላ ያለውን ሁኔታ ነው፡፡ ሳንካ፣ ፈተና፣ ጋሬጣ በህይወት መንገድ ላይ ያጋጥማል፡፡ በሳንካው ወይም በጋሬጣው መሰቃየት ግን ምርጫ ነው፡፡ ከሁኔታው በኋላ ያለው ነው በእኛ አዕምሮ ፈቃድ የሚወሰነው፡፡ በደረሰብን የምንተክዝና የምንሰቃይ ከሆነ የሚተርፈን ወዮታ ብቻ ነው፡፡ የደረሰብንን ነገር ገልብጠን ወደመልካም የምንለውጥ ከሆነ ግን የምናገኘው ከችግር ነጻ መውጣትን፣ አዲስ ልምድና ደስታ ነው፡፡
የጋራ ችግሮቸቻችንም የማይፈቱት ስለማንደማመጥ ነው፡፡ ብንሰማማም አንደማመጥም፤ ብንደማመጥም አንግባባም፡፡ በቃላት የማንግባባው፣ በሃሳብ የምንለያየው፣ በጉንጭ አልፋ ክርክር ጊዜ የምናጠፋው እርስበርስ ለመግባባትና አንዱ አንዱን ለመረዳት ስለማንፈቅድ ነው፡፡ ብዙ ክርክሮቻችን ያን ያህል የሃሳብ ልዩነት የሉባቸውም፡፡ ስቴቨን ኮቪይ “Most arguments are not disagreements but are rather little ego battles and misunderstandings” እንዲል እርስበርስ አለመግባባትና ‹‹እኔ እበልጥ- እኔ እበልጥ›› የሚል በልጦ የመገኘት የግል ጦርነት ነው ልዩነታችንን እያሰፋ ያለው፡፡
ወዳጄ ሆይ..... ከችግርህ ጋር ስትሰቃይ ትኖራለህ? ወይስ ችግርህን ገንድሰህ ትጥለዋለህ? (Are you going to cope or mope?) ምርጫው ያንተ ነው፡፡ ከራስ ጋር የሚደረገው ጦርነት ቀላል አይምሰልህ፡፡ አጉል ልማድህን ድል ማድረግ፣ ለከት ከሌለው ፍላጎትህ ነጻ መውጣት፣ ስሜትህን መግራት ከቻልክ የትኛውም ችግር አያስደነግጥህም፡፡ ችግርህን ተራራ የሚያሳክለው የተሳሳተው አስተሳሰብህና ስሱ ስሜትህ ብቻ ነው፡፡ ስሜትህ ስስ ከሆነ በደረሰብህ ሁሉ ታላዝናለህ፡፡ አስተሳሰብህን ካዘመንክ፣ ስሜትህን ካጠነከርክ ግን ከችግር መውጫ መንገዱን ማግኘት አይከብድህም፡፡ መላው በእጅህ ይሆናል፡፡
በችግርህ ላይ በማላገጥ ከችግርህ መላቀቅ አትችልም፡፡ ችግርህን የሚፈታ አዲስ ሃሳብና ተግባር ግድ ይልሃል፡፡
ቸር ብልሃት!
ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
_______________
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ሠኞ ጥቅምት ፲፰ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም.
‹‹እጅና እግርን ከማጣት የአካልጉዳት በላይ ፍርሃት ትልቁ ጉዳት ነው፡፡››
(Fear is the bigger disability than having no arms and legs)››
(እ.ብ.ይ.)
ፍርሃት ተፈጥሯዊ ነው፡፡ የማይፈራ ማንም የለም፡፡ ሃብታም በለው ንጉስ፤ ደሃ ይሁን ተራ ፍርሃት ሁሉንም ያንቀጠቅጣል፡፡ ከሞት ጋር አብሮ የሚውለው፤ ነፍሱን ለሐገሩ አሲይዞ የሚዋጋው ወታደር እንኳን በፍርሃት ይናጣል፡፡ ፍርሃት ከእኛ ጋር ተፈጥሯል፡፡ ፍርሃት የወደፊቱን ያለማወቃችን ምልክት ነው፡፡ ሁሉን አለማወቅ ደግሞ ሃብት ንብረታችን ነው፡፡ ሁሉን አውቀን መጨረስ አንችልም፡፡ ከምናውቀው በላይ የማናውቀው እልፍ ነው፡፡ በርግጥ ብናውቅም ባናውቅም፤ ሊቅም ሆንን ደቂቅ፤ መረጃ ኖረን አልኖረ የሚያስፈራን ብዙ ነገር አለ፡፡ ነገር ግን ከሚያስፈራን አስፈሪው ነገር የበለጠ ራሳችን በአስተሳሰባችን የፈጠርነው ምክንያታዊ ያልሆነ ፍርሃት (Irrational In-house fear) ነው ከዓላማችን የሚያደናቅፈን፡፡ ብዙዎች በሰው ሰራሽ ፍርሃት ምክንያት ፀጋቸውን አልተጠቀሙበትም፤ ህልማቸውን እውን ሳያደርጉ ያለፉና የጋን ውስጥ መብራት የሆኑ ቤት ይቁጠራቸው፡፡ በአካል ጉዳታቸው ምክንያት በጓዳ የቀሩ ብዙ መክሊቶች አሉ፡፡
ፍርሃታቸው ቤት ካላስቀራቸው ለዓለም ሕዝብ ምሳሌ ከሆኑ ሰዎች መካከል የአንዱ ሰው ታሪክ ግን ለየት ያለ ነው፡፡ ወደዚች ዓለም ሲመጣ Tetra-ameliua syndrome ተጠቂ ሆኖ ነው የተወለደው፡፡ ይሄ በሽታ በዩኤስኤ እንኳን ከአንድ ሚሊየን ሰዎች መካከል ባንድ ሰው ብቻ የሚከሰት በተፈጥሮ የሚመጣ የእጅና እግር የማጣት የአካል ጉዳት ነው፡፡ ሰውየው የሚበላበት እጅና የሚንቀሳቀስበት እግር የለውም፤ ነገር ግን ተረከዝና ጣቱን በመጠቀም በደቂቃ እስከ 45 የሚደርሱ ቃላትን ኮምፕዩተር ላይ መተየብ ይችላል፡፡ ዋና መዋኘት፣ መኪና መንዳት፣ ከበሮ መምታት፣ ቴኒስ መጫወት፣ ሀይለኛ የባህር ሞገድ ላይ መንሳፈፍ (Surfing) አልተሳነውም፡፡ ተሰድቧል፣ ተንቋል፣ ብዙ መከራ አይቷል፤ ነገር ግን መከራውን ሁሉ ተሻግሮ ትልቅ ስኬት ላይ ደርሷል፡፡ ተስፋ ቆርጦ ራሱን እስከማጥፋት ቢደርስም ያንን ጨለማ አስተሳሰቡን አሸንፎና ራሱን ቀና አድርጎ እንደእሱ በእሱ መከራ መንገድ የሚመላለሱትን ሚሊዮኖች ምሳሌ በመሆን መንገድ አሳይቷል፤ የዓለምን ሕዝብ አነቃቅቷል፡፡ አካል ጉዳተኛ ነው፤ ነገር ግን አፍቅሮና ተፈቅሮ፣ አግብቶና ወልዶ ለመሳም አካል ጉዳቱ ምንም አላገደውም፡፡ የሁለት ወንድ እና የመንታ ሴቶች ልጆች አባት ሆኗል፡፡ እጅና እግር አልባ ሆኖ መወለዱ በቤት አስተኝቶ አላስቀረውም፤ እንደውም ዓለምን በአነቃቂ ንግግሩ አጥለቅልቋል፡፡ ራሱን አልደበቀም፤ ይልቁንስ እስከነጉዳቱ በአደባባይ ራሱን ገልጧል፡፡ ተሞክሮውን፣ ያሳለፈውን ውጣውረድ፣ በራሱና በአምላኩ ላይ ያለውን መተማመን፣ እምነትን በተግባር የመግለጥ አስፈላጊነትን፣ የፍቅር ግንኙነቱን፣ ራሱን በራሱ የጎዳበትን (Self destructive thoughts) ሃሳቡን፣ መቆጣጠር የማይችላቸው ከአቅሙ በላይ የሆኑ ክስተቶችን እንዴት ለአምላኩ አደራ እንደሰጠ፣ በአካሉ፣ በአዕምሮው፣ በልቡና በመንፈሱ መካከል ያለውን ሚዛን አጠባበቁንና ወዘተ ወደር የሌላቸው ሃሳቦቹን በተከታታይ ባሳተማቸው ሰባት መፅሐፎቹ ተሞክሮዎቹን በሙሉ ለአንባቢዎቹ አጋርቷል፡፡ መፅሐፎቹም ‹‹Life without limitation (2007)››፣ ‹‹Unstoppable: The Incredible Power of Faith in Action (2013)››፣ ‹‹Limitless: Devotions for a ridiculously good life (2013)›› ‹‹The power of Unstoppable faith (2014)››፣ ‹‹Stand strong (2015)››፣ ‹‹Love without Limits (2016)›› እና ‹‹Be the hands and feet (2018)›› ይባላሉ፡፡
ይሄ ሰው አውስትራሊያዊው አነቃቂና ወንጌላዊ የሆነው ኒክ ቩጂሊክ (Nick Vujicic) ነው፡፡ ‹‹ሰው እግዚአብሔር ካለው እጅና እግርን ማን ይፈልጋል (“Who needs limbs when you have God?”)›› ይላል፡፡ በእግዚአብሔር ላይ ያለው እምነቱ ጠንካራ ነው፡፡ በራሱ ይተማመናል፣ በአምላኩ ያምናል፡፡ እምነቱን በአፉ ብቻ ሳይሆን በተግባርም (Faith in action) ይኖርበታል፡፡ ልጆቹን አቅፎ የሚያጫውትበት፣ ባለቤቱን ዳስሶ የሚያሞቅበት እጅ የለውም፡፡ ነገር ግን ልቦቻቸውን በፍቅር የሚያቀልጥበት የሞቀ ልብ አለው፡፡
ኒክ ‹‹Unstoppable›› በተባለው ሁለተኛው መፅሐፉ በመጀመሪያው ምዕራፍ ‹‹Faith in Action›› ላይ በብዙ ምሳሌዎች እንደሚያብራራው እምነት ያለተግባር ከንቱ መሆኑን ነው፡፡ እምነትህን የሚያረጋግጠው መልካም ስራህ ነው፡፡ ሃይማኖተኝነት ወይም እምነት ትልቅ ነገር ነው፤ ነገር ግን ያንተን ሕይወት የሚለካው ሃይማኖትህ ብቻ ሳይሆን መልካም ስራህም ጭምር ነው ይላል፡፡ እግዚአብሔር እጅና እግር የሌለው አድርጎ የፈጠረኝ ሊቀጣኝ ሳይሆን ሌሎችን ማስተማሪያ እሆን ዘንድ ሊጠቀምብኝ ነው ብሎ ያስባል፡፡ ጉዳቱን ለበረከት ተጠቅሞበታል፡፡ ለዚህም ነው ‹‹በሕይወት ውስጥ አማራጮች አሉህ፡፡ መራራውን ወይስ ጣፋጩን ነው የምትመርጠው?›› ብሎ ይጠይቅና ‹‹መራራውን ትተህ ጣፋጩን ምረጥ›› በማለት ይመክራል፡፡ አዎ በሌለህ ነገር እያማረርክ ከኖርክ ሕይወትህን መራራ ይሆናል፡፡ ባለህ ፀጋ ተጠቅመህ ግን ራስህን ለመለወጥ ቆርጠህ ከተነሳህ ሕይወትህን ጣፋጭ ታደርጋለህ፡፡ ጨዋታው ያለው ጠቃሚውን መምረጥ ላይ ነው፡፡
ወዳጄ ሆይ..... ኒክ ‹‹እጅና እግርን ከማጣት የአካልጉዳት በላይ ፍርሃት ትልቁ ጉዳት ነው፡፡ (Fear is the bigger disability than having no arms and legs)›› የሚለው ራስህን ከሚጎዳህ ከአጉል ፍርሃት ራስህን ጠብቅ ለማለት ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ተሸናፊ የሆኑት ባላስፈላጊ ፍርሃት ነው፡፡ መፈራት የሚገባውን መፍራት ተገቢ ነው፡፡ የማያስፈራውን መፍራት ግን ስነልቦናዊ ህመም ነው፡፡ ፍርሃትህ ከአስተሳሰብህ፣ ከህልምህ፣ ከግብህ እንዳያቆምህ ተጠንቀቅ፡፡ ፍርሃትህን መዝነው፤ ሃሳብህን ፈትሸው፤ የምትችለውን ከማትችለው ለይ፡፡ እምነት የሚረጋገጠው በተግባር ነው፡፡ ሃይማኖት ኖሮህ መልካም ስራ ከሌለህ የምታምነውን የእውነት አታምነውም ማለት ነው፡፡ እምነትህን በተግባር ግለጥ፤ ሃይማኖትህን በመልካም ስራ አሳይ!
ቸር እምነት! ደግ ፍርሃት!
ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
_________________________
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ሠኞ ጥቅምት ፲፩ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም.
አውቆ አለመተግበር ያው አለማወቅ ነው!
(To know and not to do is not to know)
(እ.ብ.ይ.)
እውነተኛ እውቀት መምሰል ሳይሆን መሆን ነው (True knowledge is a state of being)፡፡ የሚያውቁ የሚመስሉ ነገር ግን መረጃ ብቻ ተሸክመው የሚዞሩ እልፍ ናቸው፡፡ መረጃ ሃሳባዊ፤ እውቀት ተግባራዊ ነው፡፡ መረጃን እውቀት የሚያደርገው ደግሞ ስራ ነው፡፡ እውቀት ኖሮት ተግባር የሌለው ፊደል ካልቆጠረው ቢያንስ እንጂ አይበልጥም፡፡ ፊደል ያልቆጠረው የሚፈራው ፈሪዓ እግዚአብሔር፣ የሚያስብበት ህገ ልቦና አለው፡፡ አንዳንድ አዋቂ ነኝ ባይ ግን እፍረትም ፍርሃትም የለውም፤ በሕሊና እውቀቱ ተጀቡኖ ስጋውን አወፍሮ፤ በትዕቢት ተወጥሮ፣ ሕሊናውን አደንድኖ ልቡን ደፍኖ ነፍሱን አክስቷል፤ መንፈሱን አመንምኗል፤ ሀገር አደህይቷል፡፡
ልብ ስር ነው፤ አዕምሮ ግንድ ነው፡፡ ስሩ መሬት ካልያዘ ግንዱ እድሜ አይኖረውም፡፡ ስሩን የሚንከባከብ ቅርንጫፉንም ተንከባከበ እንደማለት ነው፡፡ ልብህን ስትንከባከብ አዕምሮህ ብሩህ ይሆናል፡፡ ሕሊናህና ልብህ ሲናበብ መንፈስህ ይለመልማል፡፡ ለዚህ ነው ስቴቨን ኮቪይ ‹‹ስሩን ካልቀየርክ ፍሬውን ልትቀይር አትችልም (You can not change the fruit without changing the root)›› የሚለው፡፡ ስሩ ልብህ ውስጥ ያለው አንተነትህ ነው፡፡ አንተነትህን ስታሳድግ ነው አዕምሮህም የሚያድገው፡፡ አንተነትህ አዕምሮህ ውስጥ ያደገ፤ ነፍስህ ውስጥ የበቀለ፣ ልቦናህ ውስጥ የጎለበተ፣ ስሜትህ ውስጥ የበለፀገ ነው፡፡ እነዚህን ስታሳድግ የምትማረው ትምህርት የእውነት ይገባሃል፤ የምትመለከተውን ታስተውላለህ፤ የምትሰማውን አጥርተህ ታዳምጣለህ፤ የምታውቀውን በተግባር ትገልጣለህ፡፡ የእውነት ሲገባህ ትቀየራለህ፣ በትክክል ስትረዳ በህይወትህ ላይ ትርጉም ታመጣለህ፡፡
የልብ ጥበብ ያነሰው የአዕምሮ እውቀት ሰውን ጎዶሎ ያደርገዋል፡፡ እንደደሃ ቦርጭ ሆዱ ብቻ ወፍሮ ሌላው አካሉ ይከሳል፡፡ ማወቅ የህሊና ስራ ነው፤ መረዳት ግን የልብ ድርሻ ነው፡፡ መረዳት ማወቅ ብቻ ሳይሆን መፍቀድም ጭምር ነው፡፡ የልብ ፈቃድ የአዕምሮን በር ወለል አድርጎ ይከፍታል፡፡ አንድን ነገር በትክክለኛ መንገድ ያልተረዳ ሰው ነገርየውን በተሳሳተ መንገድ ይተረጉመዋል፡፡ አንዳንዱ ከእሱ የማይጠበቀውን አድርጎ የሚዋረደው እወቀቱ የሆድ ብቻ ስለሆነ ነው፡፡ መላ-ህይወቱን አላነፀም፣ ልቡን አልከፈተም፤ ስሜቱን አልገራም፡፡ የስሜት ወጀቡ እንደኳስ እያላጋ ወዲህ-ወዲያ ያነጥረዋል፤ የዘመን ጣጣ ይንጠዋል፤ ቀፈቱ ሕሊናውን ይዘጋዋል፤ ገደብ የሌለው አምሮቱ ልቡን ይቆልፈዋል፡፡ በሌሎች ሰዎች ፊትና ባህርዪ የተነሳ እሱነቱ ይዋዥቃል፡፡ ራሱን መጠበቂያ የራሱ አመለካከት የለውም፡፡ እንደፔንዱለም ከመጣ ከሄደው ጋር ይንዠዋዠዋል፡፡ ጤንነቱ የሚወሰነው በውጫዊ ሁኔታ ነው፡፡ ማንም እንደፈለገ ያሳምመዋል፡፡ የእሱ ባልሆነ ሃሳብ እላይ ታች ይላል፡፡
ደራሲ አለማየሁ ዋሴ በእመጓ መፅሐፉ ገፅ 38 ላይ፡-.. ‹‹ሰው እኮ ስጋው ብቻ አይደለም ጤነኛና በሽተኛ የሚባል፤ ነፍስም፣ አዕምሮም ወይም አስተሳሰቡም ጭምር እንጂ››... እንዲል ብዙ ሰው ልቡ ታምሟል፤ መንፈሱ አልጋ ላይ ውሏል፤ ነፍሱ እየተሰቃየ ነው፡፡ ይሄ ህመም እንደአካላዊው ህመም ሌላ ሰው በቀላሉ የሚረዳው አይደለም፡፡ ባለቤቱ በሽታውን አውቆ ራሱን ለማከም እስካልፈቀደ ድረስ የህመሙን ደረጃ ላያውቀው ይችላል፡፡ በሽታው በግለሰቡ የህይወት ጉዞው ላይ እንቅፋት እየሆነ የረጅም ዘመን ጠባሳ ያሳርፋል፡፡
ወዳጄ ሆይ.... ቻይናዊው ፈላስፋን ኮንፊሽየስን ተማሪዎቹ፡- ‹‹መልካም ተግባር ምንድነው?›› ሲሉት ‹‹ወንድምህን መውደድ ነው›› አላቸው፡፡ ‹‹እውቀትስ ምንድነው?›› ብለው ደግመው ሲጠይቁት ‹‹ዕውቀት ደግሞ ወንድምህን ማወቅ ነው›› አላቸው ይባላል፡፡ መልካም ተግባር በመውደድ፤ መውደድ ደግሞ በጎ በማድረግ ይገለፃል፡፡ ትክክለኛ እውቀትም ራስህን በማወቅ፣ አጠገብህ ያለውን ወንድምህን በመረዳት፣ ሐገርህን በመገንዘብ ለራስህም ሆነ ለወገንህ ችግር ማቅለያ መላ መፍጠር ነው፡፡ ዕውቀት አዋቂ በመምሰል፣ መፅሐፍት በመሸከም፣ በየመድረኩ በማነብነብ ብቻ አይገለፅም፡፡ እውቀት የችግር መፍቺያ ቁልፍ መሳሪያ እንጂ ንግግር ማሳመሪያና ድጋፍ ማሰባሰቢያ አይደለም፡፡ አመንክም አላመንክ እውቀት ኖሮህ መልካም ስራ ከሌለህ አንተ አላዋቂ ነህ፡፡
ቸር ጊዜ!
ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
________________________
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ሠኞ ጥቅምት ፬ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም.
ምህዋረ ሃሳብ፦
ሰዎች እንዲወዱህ ማድረግ የአንተ ድርሻ አይደለም”
ጸሐፊ፦እሸቱ ብሩ ይትባረክ
አቅራቢ፦ተስፋዬ ማሞ
ምህዋረ ሃሳብ፦
“በቂ ስንት ነው?” How much is enough?
ጸሐፊ፦እሸቱ ብሩ ይትባረክ
አቅራቢ፦ተስፋዬ ማሞ
ሰዎች እንዲወዱህ ማድረግ ያንተ ሃላፊነት አይደለም!
(እ.ብ.ይ.)
ለሰው ብለህ ምንም ነገር ብታደርግ ከሰዎች አቃቂር ነፃ መሆን አይቻልህም፡፡ የምታደርገውን ነገር አምነህበትና አንተኑ የሚያስደስት ካልሆነ ዋጋ የለውም፡፡ እመሰገንበታለሁ፣ ተቀባይነትን አተርፍበታለሁ ያልከውን ስራህን ጭራሽ አቃቂረኞቹ ስም ያወጡበታል፡፡ ዳኛቸው ወርቁ በአደፍርስ መፅሐፉ ገፅ 89 ላይ ‹‹ቀጣፊ፣ ለፍላፊ፣ እበላ ባይ፣ አጭበርባሪ የሚል ህዝብ ነው ዙሪያህን ያጠረህ፡፡›› እንዳለው ነው፡፡
ጂሊያን ዊልሰን የምትባል የሃፊንግተን ፖስት (Huffpost) ድረገፅ አምደኛ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ በፈረንጆቹ መስከረም 27 ቀን 2024 ዓ.ም. ‹‹አራት ነገሮች ካንተ ሃላፊነት ውጪ ናቸው (4 things that are not your responsibility – Even if your anxiety says they are)›› በሚል ርዕስ ዘርዘር ያለ ሃሳብ አንስታለች፡፡ በዚህ ጦማሯ የብዙዎቻችን ጭንቀት ምንጩ በእኛ ባልሆነ ሃላፊነትና በማይመለከተን ጉዳይ ስንባዝን የሚመጣ መሆኑን ታብራራለች፡፡
ከአራቱ ነጥቦቿ የመጀመሪያ ብላ ያስቀመጠችው የሌሎች ሰዎች ደስታ፣ ሀዘን እና ሌሎች ስሜቶቻቸው (Other people’s happiness, sadness and other emotions) ለእኛ ጭንቀት መንስኤ ሆነው ሲገኙ ነው ትላለች፡፡ ፀሐፊዋ ይሄን ስታስረዳ ሌሎች ሰዎች ደስተኛ ስሜት እንዲኖራቸው ማድረግ አይቻልም፡፡ ሰዎች ይደሰታሉ ወይም ያዝናሉ ተብሎ የሚደረግ ነገር ልክ አይደለም፡፡ ለሰዎች የምታደርገው ነገር መጀመሪያ አንተን ማስደሰት አለበት፡፡ አንተን የማያስደስትህን ነገር ለሰዎች የምታደርግ ከሆነ ያደረግከው ነገር ከልብህ የሆነ ሳይሆን ለይምሰል ያደረግከው ነው ማለት ነው፡፡ ሰዎች እንዲደሰቱ የማድረግ ስልጣን የለህም፡፡ ሰዎች የደስታ ወይም የሀዘን ስሜት እንዲሰማቸው ማድረግ የእኛ ሃላፊነት አይደለም፡፡ ማንም ሰው የደስታ ስሜት እንዲሰማው የሚያደርገው ራሱ ነው ትለናለች፡፡
በሁለተኛ ደረጃ ያስቀመጠችው የሌሎች ሰዎች ውሳኔ (Other people’s decision) ሲያስጨንቀን ነው፡፡ ሰዎች የሚወስኑት በራሳቸው የፍላጎት፣ የዕውቀትና የሰሜት ደረጃ ነው፡፡ ማንም በራሱ ህይወት የመወሰን መብት አለው፡፡ እኛም በነሱ ህይወት ውስጥ ገብተን መፈትፈት የለብንም፤ እነሱም እንደዛው፡፡ ለራሳችን እንጂ ለሌሎች የመወሰን ሃላፊነት አልተሰጠንም፡፡ ሰዎች በራሳቸው ውሳኔ ምክንያት ለሚመጣባቸው ማንኛውም ነገር ተጠያቂዎቹም ተመስጋኞቹም ራሳቸው ናቸው፡፡ ብዙ ሰዎች ከወዳጆቻቸው፣ ከዘመዶቻቸውና ከባልንጀራዎቻቸው ጋር ጠላት የሚሆኑት በማያገባቸው በሰዎች የግል ጉዳይ ጥልቅ ስለሚሉ ነው፡፡ በሳል ሰው በማይመለከተው ጉዳይ ዘው ብሎ አይገባም፤ ወሰኑንና ድንበሩን ያውቃል፡፡
ሶስተኛው የጥረታችን ውጤት (The outcome of our effort) ቀድሞ ሲያስጨንቀን ነው የሚል ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ብዙ ጥረት አድርገን የምንጠብቀው ነገርና በመጨረሻ የምናገኘው ውጤት አልተገናኝቶም ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን ቀድመን በመጨረሻ ለምናገኘው ውጤት መጨነቅ የእኛ ሃላፊነት መሆን አይገባውም፡፡ ውጤቱ በጊዜው ይመጣ ዘንድ በእቅዳችን መሰረት ጥረት ማድረግ ነው የእኛ ሃላፊነት፡፡ ምክንያቱም ነገ ከቁጥጥራችን ውጪ ነው፤ ምን ይዞ እንደሚመጣ አናውቅም፡፡
በመጨረሻም አምደኛዋ ያስቀመጠችው አራተኛው ነጥብ ሌሎች ሰዎች ወይም ማህበረሰቡ ከእኛ የሚጠብቀው ነገር (Other people’s or society;s expectation) የእኛ ሃላፊነት አይደለም የሚል ነው፡፡ የቤተሰቦችህን፣ የጓደኞችህን ወይም በጠቅላላው የማህበረሰቡን ፍላጎት ማሟላት የአንተ ሃላፊነት መሆኑን ካመንክ ለጭንቀት ትጋለጣለህ፡፡ የወዳጆቾህ፣ የዘመዶችህና የማህበረሰብህ ፍላጎት ተሟልቶ አያልቅም፡፡ ደሞም የማህበረሰቡ ፍላጎት ወይም expectation ያንተ ፍላጎት ላይሆን ይችላል፡፡
ወዳጄ ሆይ..... ለሰው መልካም ማድረግ ጥሩ ነገር ነው፡፡ ነገር ግን መልካም የምታደርገው በሰዎች ዘንድ ሞገስ ለማግኘት ሳይሆን መልካምነት ለራስ የሚሰጠው ደስታ ስላለው ነው፡፡ ያንተ ሃላፊነት ባልሆነ ነገር ላይ አትጨነቅ፡፡ በሰው ስታንዳርድ አትመራ፡፡ የራስህን ስታንዳርድ ፍጠር፡፡ ማሕበረሰቡን ለማስደሰት ብለህ የማትችለውን አታድርግ፡፡ አቅምህን እወቅ፡፡ ከሁሉ በፊት አንተን የሚያስጨንቅህን ሳይሆን የሚያስደስትህን ነገር አድርግ፡፡ በሌሎች ፍላጎትና expectation ጊዜህን አታባክን፡፡
ቸር ጊዜ!
ኢትጵያና ኢትጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
-----------------------------------
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ሠኞ መስከረም ፳ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም.
አዲስ ዓመት የህይወት አላርም ነው!
(New Year is an alarm for Life)
(እ.ብ.ይ.)
ሰው በጊዜ ሰንሰለት የተሸመቀቀ ፍጥረት ነው፡፡ ሰው በዘመናት መካከል የሚመላለስ ነገር ግን ዘመኑ ቶሎ የሚያልቅ ምስኪን ነው፡፡ ሰው ትንሽም ነው ትልቅም ነው፤ ብዙም ነው ጥቂትም ነው፤ ደግም ነው ክፉም ነው፤ አዋቂም ነው አላዋቂም ነው፤ ብልጥም ነው ሞኝም ነው፡፡ ሰው የህይወት ዘመኑ አጭር ነው፡፡ በዚች አጭር የህይወት ዘመኑ ውስጥ ግን ብዙ ማንነቶችን ያስተናግዳል፤ የተለያዩ ስሜቶች ይንጡታል፤ የማይሆነው የለም፡፡ በዚች አሳስቃ በምታልቅ እድሜ ውስጥ ስንቶቻችን እራሳችንን ትተን የእኛ ባልሆነ ህይወት ውስጥ እንደምንዳክር ሳስበው ይገርመኛል፡፡
የሰው ህይወቱ መገባደጂያ ጊዜ አለው፡፡ ነገር ግን ሕይወቱ የሚያበቃበትን ቀን፣ ወር እና ዓመተ ምህረት (Expired Date) አያውቅም፡፡ ግን የሆነ ጊዜ ላይ ያበቃል፡፡ አንድ ቀን የመጨረሻውን ራት ይበላል፡፡ የሆነ ጊዜ ላይ የሚናገራቸው ቃሎቹ የመጨረሻ ንግግሮቹ ይሆናሉ፡፡ በሆነ ክፉ ቀን የደም ዝውውሩ ይቆማል፡፡ በሆነ ደስ በማይል ቀን የልብ ምቱ ቀጥ ይላል፤ ትንፋሹ ይቋረጣል፡፡ ድካሙ፣ ልፋቱ መና ሆኖ ይቀራል፡፡ መፍጨርጨሩ፣ ዓላማው፣ ግቡ፣ ውጥኑ፣ ትልሙ፣ ፍላጎቱ፣ ምኞቱ ውሃ ይበላዋል፡፡ ትዕግስቱ፣ ብስለቱ፣ እውቀቱ፣ ወረቀቱ፣ ኩራቱ፣ ትዕቢቱ፣ መወጣጠሩ፣ ንቀቱ አፈር ከድሜ ይገባል፡፡ ሞቱ ልክ ህይወቱ እንደተሰጠው አብሮ ተሰጥቶታል፡፡ ከሞት የሚቀር ማንም ጀግና፣ ማንም ፈሪ የለም፡፡ ከሊቅ እስከ ደቂቅ፣ ከተራው እስካለባለስልጣኑ፣ ትንሹ ትልቁ፣ ሃብታሙ ድሃው በሞት መጠቅለያ ይጠቀለላል፤ መኖሩ ይደመደማል፤ ውጣ ውረዱ ያቆማል፤ አንደበቱ ይዘጋል፡፡ ማንም ከሞት ማምለጥ አይችልም፡፡ ዋናው ጉዳይ ሞትን አውቆ መኖር ነው፡፡ መኖር ብቻ ሳይሆን መሞትም ዕጣ ፋንታችን መሆኑን መረዳት አኗኗራችንን ያስተካክላል፡፡ ሞትን መፍራት ሳይሆን ሞት እንዳለ ማወቅ ሕይወታችንን የተሻለ ያደርጋል፡፡
በርግጥ ከሞት ይልቅ አሟሟት ያስፈራል፡፡ በምን ይሆን የምሞተው ብሎ ማሰቡ ራሱ ያስጨንቃል፡፡ ያም ሆነ ይህ ግን የተፈጠርነው ልንኖር ብቻ ሳይሆን ልንሞትም ነው፡፡ ይሄ ያገጠጠ ሃቅ ነው፡፡ የትኛውም ሕይወት ያለው ነገር ሁሉ ሟች ነው፡፡ ዋናው ጉዳይ ያለው ከሞት በፊት ያለው ሕይወታችን ወይም አኗኗራችን እንዴት ያማረ ይሁን የሚለው ጉዳይ ነው፡፡
ወዳጄ ሆይ.... የአዲስ ዓመት መጥፎ ዜናው ዕድሜህ አየበረረ መሆኑ ነው፤ ጥሩ ዜናው ግን የዕድሜህ አብራሪው አንተው ራስህ መሆንህ ነው፡፡ ጥሩ አብራሪ ካልሆንክ ይዘህ የምትከሰከሰው ውዱን የሕይወት ዘመንህን ነው፡፡ አዲስ ዓመት አዲስ የበራራ መስመር ነው፡፡ አዲስ በረራ አዲስ አስተሳሰብ ይፈልጋል፡፡ አዲስ ዓመት የህይወት አላርም የሞት ነጋሪት ነው፡፡ አዲስ ዓመት በመጣ ቁጥር ከምንኖርበት የዕድሜ ቁጥር እየተቀነሰ መሆኑን ማወቅ ግድ ይለናል፡፡ ዕድሜህን ማቆም አይቻልህም፡፡ ሞትን ከህይወትህ ማስቀረት አትችልም፡፡ አለመናደድን፣ አለመፍራን፣ አለመቆጣትን፣ አለመውደድን፣ አለማፍቀርን፣ አለመደሰትን፣ አለማዘንን፣ አለመበሳጨትን፣ አለመጠላትን፣ አለመካድን፣ አለመታለልን ወዘተ ጥሩም ሆኑ መጥፎ ስሜቶችን ከህይወትህ መደምሰስ አቅም የለህም፡፡ ስሜትህ ከአንተነትህ፣ ከነፍስያህ፣ ከህልውናህ፣ ከሩህህ ጋር ተሳስሯል፡፡ አንተ የምትችለው ከፍ ዝቅ የሚያደርጉህን ስሜቶች መቆጣጠር ብቻ ነው፡፡ ያንተ ችሎታ ዘመንህን በትክክለኛው መስመር ማብረር መቻሉ ላይ ነው፡፡ ስሜቶችህ ጎጂ እንዳይሆኑ በቁጥጥርህ ስር ልታውላቸው ካልቻልክ ዘመንህን የሚያበርረው አንተ ሳትሆን ውጫዊ ወጀቡ ነው ማለት ነው፡፡ ስሜትን መግራት መቻል የዕለት ተዕለት ልምምድን ይሻል፡፡ ት/ቤቶች፣ ዩንቨርስቲዎች፣ የትምህርት ተቋማት ባጠቃላይ ስሜትህን እንዴት ትቋቋመው ዘንድ እንደምትችል አያስተምሩህም፡፡ እነሱ የሚያስቆጥሩህ ቀለም ለእንጀራ ብቻ የሚሆነውን ነው፡፡ ሶሻል ሚዲያው፣ ቲቪው፣ ሬዲዮው ባዲስ ዓመት ሙዚቃ፣ በእንቁጣጣሽ ዘፈን፣ በአሸሼ ገዳሜ፣ በአስረሽ ምቺው፤ አቅልህን ያስቱሃል እንጂ ትኩረትህን ሰብስበህ የቀሩህን ዘመናት እንዴት በብልሃት እንደምትኖር አይነግሩህም፡፡ ሁሉም ትኩረትህን ነጣቂ፣ መረጋጋትህን ሰራቂ ነው፡፡ አንተ ቶሎ ካልነቃህ የሚያፈዝህ ዙሪያህን ከብቦሃል፡፡ ንቃ በአዲስ ዓመት!
ቸር የመንቃት ዘመን!!
መልካም አዲስ ዓመት!
ኢትጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
-----------------------------------
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ሠኞ ጳጉሜ ፬ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም.
ምህዋረ ሃሳብ፦
“ሕይወት እንደገና ሊጀምር ይችላል"
(Life can be restart)
ጸሐፊ፦እሸቱ ብሩ ይትባረክ
አቅራቢ፦ተስፋዬ ማሞ
ሰዎች የሚናገሩትን ብቻ ሳይሆን የማይናገሩትንም አስተውል!
(Understand to what people don’t say)
(እ.ብ.ይ.)
ብዙ ጊዜ ሰው በንግግሩ ብቻ አይታወቅም፡፡ የሚናገረው ሌላ ማንነቱ ሌላ የሆነ ሰው እልፍ ነው፡፡ ሰው ከሚናገራቸው ይልቅ ድርጊቶቹ ናቸው የሰውየውን ማንነቱን የሚናገሩት፡፡ ቃል አሳሳች ነው፡፡ አፍ ወላዋይ ነው፡፡ ስሜታዊ ንግግር አይጨበጥም፡፡ ስብከት ብቻ ሰውን አይለውጥም፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹አትስረቅ እያልክ የምትሰብክ ትሰርቃለህን?›› የሚለው ለዚህ ነው፡፡ ተራ ዲስኩር የሰዉን ልኩን አያሳውቅም፡፡ የሰው ልኩ ያለው ድርጊቱ ላይ ነው፡፡ ድርጊቱ ከሃሳቡ የተወለደ ነው፡፡ የሰውን ሃሳብ ማወቅ አዳጋች ቢሆንም አስተዋይ ከሆንክ ግን ከንግግሮቹ መሃል ያልተናገራቸውንና ያልገለጣቸውን ስሜቶቹን በማንበብ ልትረዳው ትችላለህ፡፡
ብዙ ሰው የእሱን እውነት አምነህ እንድትቀበለውና እንድትረዳው የማያደርገው ጥረት የለም፡፡ እሱ ግን አንተን አንድ ሰከንድ አድምጦህ ሊገነዘብህ አይፈቅድም፡፡ የማያዳምጥ ሰው ማሳመንም ማመንም አይችልም፡፡ ፕሌቶ “ሪፐብሊክ” በተባለ ስራው ‹‹የማያዳምጡ ሰዎችን ማሳመን አትችልም (You can not persuade people who won’t listen)›› የሚለው ለዚህ ነው፡፡ የማያዳምጥ ሰው ቢናገርም ንግግሩ ውሃ አይቋጥርም፤ ቢሰማምም ከልቡ አያዳምጥም፡፡ ዲስኩሩ ከማሳመን ይልቅ ደካማ አስተሳሰቡን ያሳብቃል፡፡
ሰዎች ብዙ ጊዜ ከሚናገሩት ይልቅ የማይናገሩትን ናቸው፡፡ ከተነፈሱት ይልቅ ያልተነፈሱት ነው የነሱን ትክክለኛ ማንነት የሚገልፀው፡፡ ከሚናገሩት መሀል ያልተናገሩትን የምታሰብ ከሆነ የሰዎችን ትክክለኛ ማንነት ልትደርስበት ትችላለህ፡፡ ብዙ ሰዎች ከሚናገሩት በታች አልያም ከሚናገሩት በላይ ናቸው፡፡ የተናገሩትን እሱኑ በትክክል የሆኑ ማግኘት ከባድ ነው፡፡ ወይ ይጨምራሉ፤ ወይ ይቀንሳሉ፤ አልያም ያልሆኑትን ለመምሰል ይሞክራሉ፡፡
ታዋቂዋ አሜሪካዊ የፊልም ተዋናይት እና የቴሊቭዥን አቅራቢ እንዲሁም ኮሜዲያን የሆነችው ኤለን ዴጄነሬስ (Ellen Degeneres) ‹‹ሰዎች የማያዩትን አያለሁ፤ ሰዎች ትኩረት ያላደረጉበትን፣ ያልተረዱትንና ዋጋ ያልሰጡትን ለመረዳት እጥራለሁ፡፡ ለዚህ ይመስለኛል ኮሜዲያን የሆንኩት፡፡ ሰዎች በሚያዩትና በማያዩት መካከል ትንሽ ቦታ አለች፡፡ ያቺን ቦታ ነው እኔ የተጠቀምኩባት›› ትላለች፡፡ እውነት ነው! ሰዎች የማያዩትን ማየት፣ የማያስተውሉትን ማስተዋል፣ ትኩረት ያልሰጡበትን ትኩረት መስጠት የተለየ አዲስ ሃሳብ እንድትፈጥር የደርግሃል፡፡
ወዳጄ ሆይ.... ሮማዊው ፈላስፋ ሴኔካ ‹‹እኔ ሰውን በአዕምሮ እንጂ በዓይን አልለይም፡፡ ትክክለኛ ዳኛው እሱ ነውና (I do not distinguish by the eye, but by the mind, which is the proper judge of the man)››› የሚለው ሰውን ልትረዳው የምትችለው በነፍሱ መሆኑን አፅንኦት ሲሰጥ ነው፡፡ ዓይንና ጆሮህ በሚሰጡህ መረጃ ብቻ ታምነህ የሰውን ልኩን ልታውቅ አትችልም፡፡ ከቃሉ ጀርባ ያለው ስሜቱን፣ ለንግግሩ መግፍኤ የሆነው መንፈሱን፤ ለድርጊቱ መነሻ የሆነውን ሃሳቡን ለመረዳት ካልሞከርክ የሰውን ማንነት በቀላሉ አታገኘውም፡፡ ለዚህ ደግሞ ዋናው ዘዴ ራስን ማወቅ ነው፡፡ ለእያንዳንዱ ድርጊትህ መነሻ ሃሳብህንና አመለካከትህን ስታውቅ የአንተነትህን ቦታ ታገኘዋለህ፡፡ ራስህን ማወቅ የምትጀምረውም ለሰዎች ከምታሳየው ፌኩ አንተነትህ ጀርባ እውነተኛው አንተነትህን መረዳት ስትችል ነው፡፡ ከዛ በኋላ ነው ሌሎች ሰዎችን ከንግግራቸውና ከፊታቸው ባሻገር ያለውን ትክክለኛ መልካቸውን አጥርተህ ማየት የምትችለው፡፡
ቸር መረዳት!
ኢትዮጵያና ኢትዮያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
------------------
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ሠኞ ነሐሴ ፳ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም.
ምህዋረ ሃሳብ
“የህይወትህ ጉዳይ ያለው ካለፈው ይልቅ የሚቀጥለው ላይ ነው”
Prescribe versus Subscribe
ጸሐፊ፦እሸቱ ብሩ ይትባረክ
አቅራቢ፦ተስፋዬ ማሞ
ብልሆች ትዕግስተኞች ናቸው፤ ሞኞች ጠባቂዎች ናቸው!
(Patience is not the ability to wait)
(እ.ብ.ይ.)
ብልሆች ትዕግስተኞች ናቸው፤ ሞኞች ጠባቂዎች ናቸው፡፡ ጠባቂነት ትዕግስተኝነት አይደለም፤ ትዕግስትም ጠባቂነት አይደለም፡፡ የምትታገሰው እየሰራህ ነው፤ ግብህን ቆመህ አይደለም የምትጠብቀው፤ እየሄድክ ነው የምትደርስበት፡፡ መጠበቅ በሽታ ነው፡፡ ከመጠበቅ በሽታ መዳን የሚቻለው በስራ ነው፡፡ ከሰው የምትጠብቅ ከሆነ መተማመኛህ ውጫዊ ነገር ነው፡፡ ከጊዜ የምትጠብቅም ከሆነ ጊዜ በራሱ ይዞት የሚመጣው ነገር የለም፡፡ በጊዜ ውስጥ ያለኸው አንተ ነህ አምጪውም አስቀሪውም፡፡ ዕድል የሚሰምርልህ፣ አጋጣሚ የሚሳካልህ እጅና እግርህን ታቅፈህ ቁጭ ብለህ በመጠበቅ ሳይሆን የልብህን በር ለመልካም አጋጣሚ ክፍት ስታደርግና ዕድልህን ፍለጋ አደባባይ ስትወጣ ነው፡፡ ሎተሪ ካልቆረጥክ እንደማይደርስህ ሁሉ ልታገኘውን የምትሻውን ዝም ብለህ ከጠበቅከው አይመጣም፤ ከሞከርከው ግን አንተው ራስህ በጊዜ ሂደት ታመጣዋለህ፡፡
በአንድ ሐገር ውስጥ ታማኝ ውሻ የነበረው አልቃድር የሚባል ሰው ነበር፡፡ ይህ ሰው ኑሮ አልሰምርለት ሲል የመከራ ጎጆውን ዘግቶ ላይመለስ ተሰደደ፡፡ ውሻው ለሣምንታት በቤቱ በራፍ ላይ ኩርምት ብሎ ጌታውን ሲጠብቅ ከሰነበተ በኋላ በተኛበት ሞቶ ተገኘ፡፡ የአልቃድርን ውሻ መጨረሻ የተመለከተና ሕይወት የከፋችበት የመንደሩ ነዋሪ፡-
‹‹እሄዳለሁ እንጂ፤ እሄዳለሁ የትም፣
እንደአልቃድር ውሻ ስጠብቅ አልሞትም፡፡››..... ሲል አንጎራጎረ ይባላል፡፡
አዎ ትዕግስት እጅን አጣጥፎ መጠበቅ አይደለም፡፡ ትዕግስተኞች እየሞከሩ፣ እየተፍጨረጨሩ ነው የሚሹትን የሚጠብቁት፡፡ ትዕግስት የመጠበቅ ችሎታ አይደለም፡፡ ይልቁንስ እቅድን በትናንሽ ጊዜ ከፋፍሎ በትንሹ እያሳኩ ትልቁን ግብ ለማሳካት ጠንክሮ የመስራት ችሎታ ነው፡፡
ብዙዎቻችን የምንወደውንና የምንፈልገውን ነገር ያላገኘነው ነገርየውን ስለምንጠብቀው ብቻ ነው፡፡ አብዛኛዎቻችን ከቤተሰብ እንጠብቃለን፤ ከወዳጆቻችን እንጠብቃለን፤ ከአለቃችን እንጠብቃለን፤ ከመንግስት እንጠብቃለን፤ ከጊዜ እንጠብቃለን፤ ከአምላክ እንጠብቃለን፡፡ ጠባቂነት ተጠናውቶናል፡፡ ፍቅርንም፣ ደግነትንም፣ ቅን አሳቢነትንም፣ ሰላምንም የምንጠብቀው ከሌላ ነው፡፡ ምንም ነገር እንዲሰጠን (ጠብቆ ይነበብ) እንጂ እኛ ለመስጠት ፍቃደኛ አይደለንም፡፡ እኛ የምንፈልገውን ሌላውም እንደሚያስፈልገውም አንረዳም፡፡ ማህተመ ጋንዲ ‹‹ትዕግስት ማጣት በጦርነቱ መሸነፍ ነው (To lose patience is to lose battle)›› የሚሉን ለዚህ ነው፡፡ አላማህን የሚያደነቃቅፍ ሳንካ ሲገጥምህ ትዕግስት የምታጣ ከሆነ የኑሮህን ጦርነት እየተሸነፍክ ነው ማለታቸው ነው፡፡ እየተንገዳገዱ መራመድ፣ እየወደቁ መነሳት የሚቻለው ትዕግስት ሲኖር ነው፡፡ ትዕግስተኞች ከልፋታቸው የሚጠብቁ፤ ዘርተው ለማጨድ ግባቸውን እየተንከባከቡ፣ እቅዳቸውን ውሃ እያጠጡ ፍሬውን በተስፋ የሚጠባበቁ ምርጥ ገበሬዎች ናቸው፤ ጠባቂዎች ግን እንዲሁ በነፃ ከሰማይ መና የሚጠብቁ አደገኛ ቦዘኔዎች ናቸው፡፡
ወዳጄ ሆይ... መጠበቅ በራስ የሕይወት ጊዜ ላይ መተኛት ነው፡፡ የተኛ ከሞተ የሚሻለው መንቃት ስለሚችል ነው፡፡ አሁን ካልነቃህ፣ ዛሬ ራስህን ካልቀሰቀስክ የመኝታ ዘመንህ ይረዝማል፡፡ የመንቂያ ጊዜ አሁን ነው፡፡ ትክክለኛውን የለውጥ ጊዜ የምትጠብቅበት ትክክለኛው ሰዓት ነገ ሳይሆን ዛሬ ነው፡፡ አሁን የነገ አልፎም ተርፎም የወደፊቱ የሕይወትህ ዕጣ ፋንታ መክፈቻ ቁልፍ ነው፡፡ ስለነገ እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ ስለወደፊቱ ለማወቅ አይቻልም፡፡ ነገ ጉልበት ሊከዳህ ይችላል፡፡ ከነገ ወዲያ በህይወትህ ላይ ምን እንደሚፈጠር የማወቅ ችሎታ የለህም፡፡ በእጅህ ያለው ውዱ ሀብትህ አሁን ነው፡፡ ነገን አትጠብቅ፡፡ ዛሬህን ተንከባክበህ ያዘውና ተጠቀምበት፡፡ ዛሬን በእጃቸው ያደረጉ ነገም፣ ወደፊትም የነሱ ነው፡፡ እየሰሩ መታገስ እንጂ ባዶ እጅ ሆኖ መጠበቅ የትም አያደርስህም፡፡ አርባአራት ነጥብ!
ቸር ትዕግስት! ደግ ጅማሬ!
ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
-----------------------------------
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ማግሠኞ ነሐሴ ፯ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም.
