en
Feedback
የማርያም ልጆች ®

የማርያም ልጆች ®

Open in Telegram

በቦሌ ኆኅተ ብርሃን ቅድስት ድንግል ማርያም ሰ/ት/ቤት ስር የተካተተ የአከባቢው ወጣቶች የዓርብ ጉባኤ ተማሪዎች መማማሪያ ትክክለኛ ገጽ ። ትምህርቶች ፣ መዝሙር እና የተለያዩ ሃይማኖት ቀመስ ጽሑፎችን ከዚህ ያገኛሉ ለጥያቄ እና አስተያየት @kimi_king

Show more
447
Subscribers
No data24 hours
-27 days
-1230 days
Posts Archive
††† እንኳን ለርኅወተ ሰማይ: ለቅዱስ ሩፋኤል: መልከ ጼዴቅ: ዘርዓ ያዕቆብና ሰራጵዮን ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ርኅወተ ሰማይ ††† ††† ይህች ዕለት የሰዎች ሁሉ ጸሎት የሚያርግባት: አራተኛው መጋቢ ኮከብ የሚያልፍባት: ለሰው ልጆች ከፈጣሪያቸው ጸጋ በረከት የሚሰጥባት ዕለት ስለሆነች "ርኅወተ ሰማይ-ሰማይ የሚከፈትባት ቀን::" ትባላለች:: አሁን በሰማይ መዘጋት መከፈት ኑሮበት አይደለም:: የሰው ልጆችን ልመና ቅዱሳን መላእክት ያለ ከልካይ የሚያሳርጉበት: አንድም ቅዱስ ሩፋኤል የዓመቱን የጸሎት መዝገብ የሚከፍትበት ቀን ስለሆነ እንዲህ ተባለ እንጂ:: እመቤታችን ድንግል ማርያም ለአጼ ናዖድ እንደ ነገረቻቸው በዚህች ዕለት ሁሉም ቅዱሳን ስለሚታሰቡ: የእግዚአብሔር የምሕረት መዝገቡ ስለሚከፈት: ዕለቷን ክብርት ያሰኛታል:: በቅዱስ ሩፋኤል አበጋዝነት (መሪነት) በዚህች ዕለት ለዓመት የሚበቃ ምሕረት ይገኛል:: ስለዚህም አባቶቻችን በዚህች ሌሊት ሦስት መቶ ስልሳ አምስት አቡነ ዘበሰማያትን ሲጸልዩ ያድራሉ:: በሌላ ወገን ደግሞ የጌታ ዳግም ምጽዓቱ መታሰቢያ እንደ መሆኗ ትልቅ ትኩረትም ይሰጣታል:: ቸሩ ጌታችን ከተከፈተች ገነት ከተነጠፈች ዕረፍት ሁላችንንም ያድርሰን:: ††† ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላእክት ††† ††† ቅዱስ ሩፋኤል በቤተ ክርስቲያን አስተምሕሮ ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት በደረጃው ሦስተኛ ነው:: በመጀመሪያዋ ዕለተ ፍጥረት እግዚአብሔር መቶ ነገደ መላእክትን ፈጥሮ በአሥር ከተማ ሲያኖራቸው የቅዱስ ሩፋኤል ዕድል ፈንታው ራማ ሆነች:: በዚያም "መናብርት" ተብለው ለሚጠሩ አሥሩ ነገድ አለቃ (መሪ) ሆኖ በፈጣሪው ተሹሟል:: በኋላም "መጋብያን" በሚባሉ በሃያ ሦስቱ ነገድ ላይ ሹሞታል:: ይህች ዕለትም በዓለ ሲመቱ ናት:: አንድ ቀን ጌታችን ክርስቶስ በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ ሐዋርያቱ ቅዱስ ሩፋኤልን እንዲያስተዋውቃቸው ለመኑት:: ጌታም ሦስቱን ሊቃናት (ሚካኤል: ገብርኤል እና ሩፋኤል) ይመጡ ዘንድ አዘዛቸው:: ቀጥሎም ቅዱስ ሩፋኤልን "ክብርህን ንገራቸው::" አለው:: እርሱም ለጌታ ሰግዶ ለሐዋርያት ብዙ ምሥጢር ነገራቸው:: በተለይ ስሙን ለሚጠሩ: መታሰቢያውን ለሚያከብሩ የሚደረገውን ጸጋ አብራርቶላቸው ዐረገ:: በመጽሐፈ ጦቢት ላይ ተጽፎ እንደምናገኘው ቅዱሱ መልአክ ሰው (አዛርያን) መስሎ: ጦብያን ለትዳር አብቅቶ: ሣራን አስማንድዮስ ከሚባል ሰይጣን አድኖ: የጦቢትን ዓይን አብርቷል:: በገድላተ ቅዱሳን እንደምናየውም ለብዙ ቅዱሳን ረዳታቸው ሆኖ ገድላቸውን አስፈጽሟል:: ታሪክ እንደሚለው ይህች ቀን ለቅዱስ ሩፋኤል ቅዳሴ ቤቱም ናት:: በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን በቅዱስ ቴዎፍሎስ ዘእስክንድርያ አማካኝነት ቤቱ ታንጿል:: የሚገርመው ደግሞ የታነጸው በዓሣ አንበሪ ጀርባ: ደሴት ላይ ነው:: በመልአኩ አጋዥነትም ለሦስት መቶ ዓመታት አገልግሏል:: ††† ቅዱስ ሩፋኤል ¤መስተፍስሒ (ልቡናን ደስ የሚያሰኝ) ¤አቃቤ ሥራይ (ባለ መድኃኒት ፈዋሽ) ¤መዝገበ ጸሎት (የጸሎት መዝገብ መክፈቻ የተሰጠው) ¤ሊቀ መናብርት (በዙፋን ላይ በክብር የሚቀመጡ መላእክት መሪ) ¤ፈታሔ ማኅጸን (የሰውንም ሆነ የእንስሳትን ማኅጸን የሚፈታ) ¤መወልድ (አዋላጅ: ምጥን የሚያቀል) ይባላል:: "ለሰብእ ወለእንስሳ ፈታሔ ማኅጸኖሙ አንተ" እንዲል:: ††† ቅዱስ መልከ ጼዴቅ ††† ††† ካህኑ መልከ ጼዴቅን ቅዱስ ጳውሎስ "የትውልድ ቁጥር የለውም: ለዘመኑም ጥንትና ፍጻሜ የለውም::" ይለዋል:: (ዕብ.7:3) ሐዋርያው ይህንን ያለው ለወልደ እግዚአብሔር ምሳሌ ሲያደርገው እንጂ ትውልዱ ከነገደ ካም ነው:: ወላጆቹም "ሚልኪ እና ሰሊማ" ይባላሉ:: ገና ከእናቱ ማኅጸን የተመረጠው ቅዱሱ "ካህነ ዓለም: ንጉሠ ሳሌም" ይባላል:: የዛሬ አምስት ሺ አምስት መቶ ዓመት አካባቢ ሴም ባኖረበት ቦታ (በደብረ ቀራንዮ) ለዘላለም ይኖራል:: ካህኑ መልከ ጼዴቅ ከሰው ወገን እጅግ ክቡርም ነው:: ††† አፄ ዘርዓ ያዕቆብ ††† ††† ሃይማኖቱ የቀና ኢትዮጵያዊው ንጉሥ አፄ ዘርዓ ያዕቆብ በኢትዮጵያ በነገሠባቸው ሠላሳ አራት ዓመታት (ከ1426 እስከ 1460 ዓ/ም) ብዙ በጐ ነገሮችን ሠርቷል:: ላለፉት ሰባ ዓመታት ግን አንዳንድ ጥቃቅን ሰብአዊ ስህተቶችን እየነቀሱ ተሐድሶዎቹ ስሙን ሲያጠፉት ኑረዋል:: ዛሬ ዛሬ ደግሞ የእኛ ቤት ሰዎችም ተቀላቅለዋቸዋል:: እነርሱ ያሉትን ይበሉ እንጂ ለእኛ ግን ዘርዓ ያዕቆብ ማለት:- 1.ጣዖት አምልኮን ከሃገራችን ለማጥፋት ብዙ ሺህ ካህናትን አሰልጥኖ አሰማርቷል:: 2.የኑፋቄ ችግሮችን ለመቅረፍ ጉባኤያትን አዘጋጅቷል:: 3.ከአሥራ አንድ ያላነሱ መጻሕፍትን በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ደርሶ ለአገልግሎት አብቅቷል:: 4.ብዙ መጻሕፍትን ከውጪ አስመጥቶ አስተርጉሟል (በተለይ ተአምረ ማርያምን) 5.ሰው ሁሉ ለእመ ብርሃንና ለመስቀሉ ፍቅር እንዲገዛ ጥረት አድርጓል 6.እመቤታችንን በፍጹም ልቡ ከመውደዱ የተነሳ ዛሬ ድረስ በሃገራችን ድንግል ማርያም "የዘርዓ ያዕቆብ እመቤት" እየተባለች ትጠራለች:: 7.ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን አንጾ: ብዙ ሥርዓቶችም በሊቃውንት እንዲሠሩ አድርጐ: ሌሎች ብዙ በጐ ተግባራትንም ፈጽሞ በዚህች ቀን ዐርፏል:: ቤተ ክርስቲያን ስለውለታቸው ዘርዓ ያዕቆብን: እናታቸው ጽዮን ሞገሳን እና አባታቸው ዳዊትን በክብር ታስባለች:: ††† ቅዱስ ሰራጵዮን ዘሰንዱን ††† ††† ይህ ቅዱስ እጅግ የበዛ ሃብቱን ለነዳያን አካፍሎ: ወደ ሌላ ሃገር ሔዶ ለባርነት ተሽጧል:: በተሸጠበት ሃገርም በጸሎት ተግቶ ከክህደት ወደ ሃይማኖት መልሷቸዋል:: ክብሩን ሲያውቁበትም በተመሳሳይ ወደ ሌላ ሃገር ሒዶ አሕዛብን አድኗል:: በፍጻሜው ወደ በርሃ ገብቶ በተጋድሎ ኑሮ በዚህች ቀን ዐርፏል:: ††† አምላከ ቅዱሳን የወዳጆቹን ሁሉ በረከትና ጸጋ ያብዛልን:: ለዓለምም ሰላሙን ይዘዝልን:: ††† ጳጉሜን 3 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ርኅወተ ሰማይ (የሰማይ መከፈት) 2.ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላእክት 3.ቅዱስ መልከ ጼዴቅ ካህን 4.አፄ ዘርዓ ያዕቆብ ንጉሥ (የእመቤታችን ወዳጅ) 5.ቅዱስ ሰራጵዮን ዘሰንዱን 6.ቅዱስ አኖሬዎስ 7.ቅዱስ ቴዎፍሎስ 8.አባ ዮሐንስ 9.ቅዱስ ጦቢት 10.ቅዱሳን ጦብያና ሣራ ††† ወርኀዊ በዓላት (የለም) ††† "እውነት እውነት እላችኋለሁ:: ሰማይ ሲከፈት: የእግዚአብሔርም መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ::" ††† (ዮሐ. ፩፥፶፪) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር ††† https://t.me/zikirekdusn

††† እንኳን ለቅዱስ ቲቶ ሐዋርያ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ቅዱስ ቲቶ ሐዋርያ ††† ††† የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዝሙር ቅዱስ ቲቶ ከሰባ ሁለቱ አርድእት አንዱ ሲሆን በተወሰነ መንገድም ቢሆን የተዘነጋ ሐዋርያ አይደለም:: በተለይ ደግሞ ቅዱስ ጳውሎስ ከጻፋቸው አሥራ አራት መልእክታት መካከል አንዷ የተላከችው ለዚህ ቅዱስ በመሆኗ ታሪኩ እንኳ ባይነገር ስሙ አይረሳም:: ቅዱስ ጳውሎስም በመልዕክታቱ በጐ ስሙን እየደጋገመ ያነሳዋል:: ለመሆኑ ሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ ማን ነው? ቅዱስ ቲቶ የተወለደው በ1ኛው መቶ ክ/ዘመን እስያ ውስጥ: ቀርጤስ በምትባል ከተማ ነው:: የዘር ሐረጉ ከእሥራኤልም: ከጽርእም (ግሪክ ለማለት ነው::) ይወለዳል:: አካባቢው አምልኮተ እግዚአብሔር የጠፋበት ስለሆነ እሱም: ቤተሰቦቹም የሚያመልኩት ከዋክብትን ነበር:: መዳን በእውቀት ይመስላቸው ስለ ነበር የአካባቢው ሰዎች የግሪክን ፍልስፍና ጠንክረው ይማሩ ነበር:: ቅዱስ ቲቶም በወጣትነቱ ወደ ት/ቤት ገብቶ የግሪክን ፍልሥፍናና የዮናናውያንን ጥበበ ሥጋ ተማረ:: በጥቂት ጊዜም የሁሉ የበላይ ሆነ:: ቅዱሱ በወቅቱ ምንም እውነተኛውን ፈጣሪ አያምልክ እንጂ በጠባዩ እጅግ ቅንና ደግ ነበር:: ምክንያቱን ሳያውቀው ለእኔ ቢጤዎች ያበላ: ያጠጣ: ይንከባከባቸውም ነበር:: እግዚአብሔር ግን የዚህ ቅን ሰው በጐነቱ እንዲሁ እንዲቀር አልወደደምና አንድ ቀን በራዕይ ተገለጠለት:: በራዕይም አንድ ምንነቱን ያልተረዳው ነገር "ቲቶ ሆይ! ስለ ነፍስህ ድኅነት ተጋደል:: ይህ ዓለም ኃላፊ ነው::" ሲለው ሰማ:: ከእንቅልፉ ነቅቶ በእጅጉ ደነገጠ:: የሚያደርገውንም አጣ:: ያናገራቸው ሁሉ ምንም ሊገባቸው አልቻለም:: ለተወሰነ ጊዜም ለጉዳዩ ምላሽ ሳያገኝለት በልቡ እየተመላለሰ ኖረ:: ድንገት ግን በዚያ ሰሞን ከወደ ኢየሩሳሌም አዲስ ዜና ተሰማ:: "ክርስቶስ የሚሉት ኢየሱስ: እርሱም የባሕርይ አምላክ የሆነ ወደ ምድር ወርዶ: ስለ እግዚአብሔር መንግስትም እየሰበከ ነው::" ሲሉ ለቲቶ ነገሩት:: "ሌላስ ምን አያችሁ?" አላቸው:: "በእጆቹ ድውያን ይፈወሳሉ:: ሙታን ይነሳሉ:: እውራን ያያሉ:: ለምጻሞች ይነጻሉ:: ሌሎች ብዙ ተአምራትም እየተደረጉ ነው::" አሉት:: የወቅቱ የሃገረ አክራጥስ መኮንን ፈላስፋ ነበርና ስለ ክርስቶስ ሲሰማ ሊመራመር ወደደ:: እርሱ መሔድ ስላልተቻለው "ብልህ ጥበበኛ ሰው ፈልጉልኝ::" ብሎ ተከታዮችን ቢልካቸው ከቲቶ የተሻለ በአካባቢው አልነበረምና እርሱኑ አመጡት:: መኮንኑ ቲቶን "ነገሩ ትክክል ወይም ስሕተት መሆኑን በጥልቅ መርምረህ ምላሽ አምጣልኝ::" ብሎ ላከው:: ቅዱስ ቲቶም ፈጥኖ ተነስቶ ወደ ኢየሩሳሌም ገሰገሰ:: ወደ ከተማዋ እንደገባም ጌታችንን አፈላልጐ አገኘው:: 1.ጌታችን ክርስቶስ በሥልጣነ ቃሉ ደዌያትን ሲያርቅ: አጋንንትን ሲያሳድዳቸው ተመልክቶ ይህ ሥራ የፍጡር እንዳልሆነ ተረዳ:: 2.ጌታችን የሚያስተምረው ትምሕርት ከግሪክ ፍልሥፍና እጅግ ርቆና መጥቆ አገኘው:: የግሪክ ፍልሥፍና መነሻውም ሆነ መድረሻው ሥጋዊ ነው:: ጌታ ግን በጣዕመ ቃሉ የሚያስተምረው ሰማያዊ: በዚያ ላይ ዘላለማዊ የሆነ ትምሕርት ነው:: በራዕይ "ስለ ነፍስህ ተጋደል::" ያለው ምሥጢር አሁን ተተረጐመለት:: በዚህ ምክንያትም ጊዜ አላጠፋም:: ወዲያውኑ አምኖ ተከታዩ ሆነ:: ጌታም ከሰባ ሁለቱ አርድእት ደመረው:: የአክራጥስ መኮንን "ምነው ዘገየህ?" ቢለው ያየውን ሁሉ ጽፎ: እንደማይመለስም አክሎ ደብዳቤ ላከለት:: ከዚህ በኋላ ቅዱስ ቲቶ ከጌታችን እግር ለሦስት ዓመታት ተምሮ: በበዓለ ሃምሳ መንፈስ ቅዱስን ተቀብሎ: በመላው እስያ ለስምንት ዓመታት ወንጌልን ሰብኳል:: ቅዱስ ጳውሎስ ባመነ ጊዜ ደግሞ የእርሱ ደቀ መዝሙር ሆኖ ለሃያ አምስት ዓመታት አስተምሯል:: ቅዱስ ጳውሎስ ሰማዕት ከሆነ በኋላ ደግሞ ወደ አክራጥስ ተመልሶ: ሕዝቡን አሳምኖና አጥምቆ: ቤተ ክርስቲያንን አንጿል:: ዕድሜው በደረሰ ጊዜም መምሕራንን: ካህናትን ሹሞላቸው: ባርኳቸውም በዚህች ቀን ዐርፏል:: ††† አምላከ ቅዱስ ቲቶ መልካሙን የሕይወት ምሥጢር ይግለጽልን:: ከሐዋርያውም በረከቱን ያድለን:: ††† ጳጉሜን 2 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ ቲቶ ሐዋርያ (ከሰባ ሁለቱ አርድእት) ††† ወርኀዊ በዓላት (የለም) ††† "የእግዚአብሔር ባሪያና የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የሆነ ጳውሎስ. . . መድኃኒታችን እግዚአብሔር እንዳዘዘ: ለእኔ አደራ በተሰጠኝ ስብከት ቃሉን ገለጠ: በሃይማኖት ኅብረት እውነተኛ ለሚሆን ልጄ ቲቶ:: ከእግዚአብሔርም አብ: ከመድኃኒታችንም ከጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ምሕረት: ሰላምም ይሁን::" ††† (ቲቶ. ፩፥፩) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር ††† https://t.me/zikirekdusn https://www.youtube.com/@ZikereKedusan

††† እንኳን ለተባረከ ወር ጳጉሜን እና ለቅዱሳኑ ዮሐንስ መጥምቅ : ዑቲኮስ ሐዋርያና ቀሲስ አባ ብሶይ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ወርኀ ጳጉሜን ††† ††† እግዚአብሔር አዝማናትን የፈጠራቸው ለሰው ልጆች ጥቅም መሆኑ ይታወቃል:: እርሱ ባወቀ: በረቂቅ ሥልጣኑ ዓለምን ፈጥሮ: ጊዜያትን እንዲከፍሉ ብርሃናትን (ፀሐይ: ጨረቃ: ከዋክብትን) ፈጥሮልናል:: ጊዜያትንም በደቂቃ: በሰዓት: በቀን: በሳምንት: በወር: በዓመታት: በኢዮቤልዩ: በክፍላተ ዘመናት እንድንቆጥር ያስማረንም እርሱ ነው:: የሰከንድ 540,000 ክፋይ ከሆነችው 'ሳድሲት' እስከ ትልቁ ቀመር (532 ዓመት) ድረስ እርሱ ለወደዳቸው እንዲያስተውሉት ገልጧል:: በየዘመኑም በቅዱስ ድሜጥሮስ: በቅዱስ ዮሐንስ ዘደማስቆ : በቅዱስ አቡሻኽር እና በሌሎቹም አድሮ መልካሙን አቆጣጠር አስተምሯል:: ሃገራችን ኢትዮጵያ ደግሞ የአሥራ ሦስት ወራት የፀሐይ ጸጋ (thirteen months sun shine) ያላት: አራቱ ወቅቶች የተስማሙላት ናት:: ††† ሌላው ዓለም ወሮችን 31,30,29 (28) እያደረገ ሲጠቀም እኛ ግን እንደ ኖኅ (ዘፍ. 8:1-15) አቆጣጠር ወሮችን በሠላሳ ቀናት ወስነን: ጳጉሜንን ለብቻዋ እናስቀምጣለን:: ጳጉሜን 'ኤጳጉሚኖስ' ከሚል የግሪክ (ጽርዕ) ቃል የተወሰደ ሲሆን ትርጉሙም 'ትርፍ: ጭማሪ' እንደ ማለት ነው:: የወርኀ ዻጉሜን አምስቱ (ስድስቱ) ቀናትም ወደ አዲስ ዓመት መሸጋገሪያ እንደ መሆናቸው ብዙ ምሳሌያት (ምሥጢራት) አሏቸው:: ዋናው ግን በዚህ ጊዜ ዳግም ምጽዓት ይታሠባል:: ጊዜውንም በጾምና በጸሎት ሊያሳልፉት ይገባል:: ግን በፈቃድ ነው እንጂ የግዴታ አይደለም:: ††† ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ††† ¤የቅዱሳኑ ዘካርያስና ኤልሳቤጥ ልጅ ¤በማኅጸን ሳለ መንፈስ ቅዱስ የሞላበት ¤በበርኀ ያደገና በገዳማዊ ቅድስና ያጌጠ ¤እሥራኤልን ለንስሐ ያጠመቀ ¤የጌታችንን መንገድ የጠረገ ¤ጌታውን ያጠመቀና ¤ስለ እውነት አንገቱን የተቆረጠ ታላቅ ሰው ነው:: ††† ስለዚህም ቤተ ክርስቲያን:- ነቢይ: ሐዋርያ: ሰማዕት: ጻድቅ: ገዳማዊ: መጥምቀ መለኮት: ጸያሔ ፍኖት: ቃለ ዐዋዲ ብላ ታከብረዋለች:: ††† ቅዱሱ በዚህች ዕለት ወደ እሥር ቤት ገብቷል:: ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ:- ንጉሡ ሔሮድስ የወንድሙን የፊልጶስን ሚስት ሔሮድያዳን በማግባቱና በመሰል ክፋቶቹ ቅዱስ ዮሐንስ ይገስጸው ነበር:: ቅዱስ ዮሐንስ "መምሕር ወመገስጽ: ዘኢያደሉ ለገጽ - ፊት አይቶ የማያዳላ" ነውና ገሰጸው:: ሔሮድስ ቅዱሱን ይፈራው: ያከብረውም ነበር:: በኋላ ግን ፈቃደ ሥጋው ስላየለበት: በተለይ ደግሞ ከሰባት ቀናት በኋላ ልደቱን ሲያከብር እንዳይረብሸው በመስጋት በዚህች ቀን በወታደሮቹ አስይዞ እሥር ቤት ውስጥ ጥሎታል:: ለሰባት ቀናት በጨለማ ውስጥ አሥሮ መስከረም 2 ቀን አንገቱን እንዴት እንዳስቆረጠው ዕለቱን ጠብቀን እንመለከታለንና የዚያ ሰው ይበለን:: ††† ቅዱስ ዑቲኮስ ሐዋርያ ††† ††† ቅዱሱ ሐዋርያ ጭራሽ ከነስማቸው እንኳ እየተዘነጉ ከሔዱ ሐዋርያት አንዱ ሲሆን ቁጥሩም ከሰባ ሁለቱ አርድእት ነው:: በወጣትነት ዘመኑ የጌታችን ደቀ መዝሙር መሆንን መርጦ ለሦስት ዓመት ከሦስት ወር ምሥጢረ ወንጌልን ጠንቅቆ ተምሯል:: መንፈስ ቅዱስ በወረደ ጊዜም እንደ መጠኑ ተቀብሎ ለአገልግሎት ወጥቷል:: በመጀመሪያ የወንጌላዊው ዮሐንስ ተከታይ ሁኖ ብዙ ምሥጢራትን ተካፍሏል:: ቀጥሎም ቅዱስ ጳውሎስን ተከትሎ ብዙ አሕጉራትን በስብከተ ወንጌል አዳርሷል:: በመጨረሻም በእስያ አካባቢ ለብቻው ተጉዞ: ብዙ ነፍሳትን ማርኮ: ጣዖታትን አጥፍቷል:: ስለዚህ ፈንታም በእሳት: በስለትና በግርፋት ብዙ መከራዎችን አሳልፏል:: በዚህች ቀንም በበጐው እርግና (ሽምግልና) ዐርፏል:: ††† ቅዱስ ብሶይ ቀሲስ ††† ††† ከ3ኛው መቶ ክ/ዘመን ካህናት አንዱ የነበረው አባ ብሶይ ለአገልግሎት ወጥቶ ሲመለስ የቤተሰቦቹ ቤት ሰው አልነበረበትም:: "የት ሔዱ?" ብሎ ቢጠይቅ "ወንድምህ አባ ሖር እና እናትህ ቅድስት ይድራ ወደ እስክንድርያ ሔደዋል:: በዚያም ስለ ክርስቶስ ፍቅር ተሰውተዋል::" አሉት:: በማግስቱ የኔ ብጤዎችን ጠርቶ ሃብቱን: ንብረቱን: ቤቱን አካፈላቸው:: ለራሱ ግን አንዲት በትር እና ሦስት የዳቦ ቁራሾች ይዞ ጉዞ ተነሳ:: ወደ እስክንድርያ እንደ ደረሰ አፈላልጐ የቤተሰቦቹን መቃብር አገኘ:: ከፊታቸው ወድቆም የናፍቆት ለቅሶን አለቀሰ:: ወዲያውም እንዲህ አላቸው:- "ፈጥኜ ወደ እናንተ ስለምመጣ ጠብቁኝ:: ደግሞም ጸልዩልኝ::" ከዚያ ተነስቶ በመኮንኑ ፊት ስለ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት መሰከረ:: በዚህ ምክንያት ብዙ ተሰቃይቶ በዚህች ቀን ሰማዕት ሆኗል:: ከወገኖቹም ጋር ተቀብሯል:: ††† አምላከ ቅዱሳን ተረፈ ዘመኑን ባርኮ ለአዲሱ ዘመን በቸር ያድርሰን:: ከወዳጆቹም ጸጋ በረከትን ይክፈለን:: ††† ጳጉሜን 1 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ (የታሠረበት) 2.ቅዱስ ዑቲኮስ ሐዋርያ (ከሰባ ሁለቱ አርድእት) 3.ቅዱስ ብሶይ ቀሲስ (ሰማዕት) 4.አባ ጳኩሚስ /ባኹም (የሦስት ሺ ቅዱሳን አባት) 5.አባ ሰራብዮን /ሰራፕዮን (የአሥር ሺ ቅዱሳን አባት) ††† ወርኀዊ በዓላት (የለም) ††† "ጌታ ኢየሱስ ለሕዝቡ ስለ ዮሐንስ ሊናገር ጀመረ . . . ምን ልታዩ ወጣችሁ? ነቢይን? አዎን እላችኋለሁ ከነቢይም የሚበልጠውን . . . እውነት እላችኋለሁ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሳም . . . ነቢያት ሁሉና ሕጉ እስከ ዮሐንስ ድረስ ትንቢት ተናገሩ:: ልትቀበሉትስ ብትወዱ ይመጣ ዘንድ ያለው ኤልያስ ይሕ ነው:: የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ::" ††† (ማቴ. ፲፩፥፯-፲፭) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር ††† https://t.me/zikirekdusn

††† እንኳን ለሐዋርያው ቅዱስ እንድርያስ እና ለቅዱስ ሚልክያስ ነቢይ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† መሐሪ እግዚአብሔር ኃጢአታችሁ በዛ: ሰውነታችሁ ከፋ ሳይል በአባታዊ ርሕራሔው ጠብቆ ይሔው ወርኀ ነሐሴን በሰላም አስፈጸመን:: አይመስለንም እንጂ በእነዚህ ሰላሳ ቀናት ሚሊየኖች አንቀላፍተዋል: ሚሊየኖች በደዌ ዳኝነት ተይዘዋል: በርካቶቹም ከሃይማኖታቸው ወጥተዋል:: እኛ ይህ ሁሉ ያልደረሰብን በጐ ስለሆንን አይደለም:: ይልቁኑ ቸርነቱ በእኛ ላይ ስለበዛ ብቻ ነው እንጂ:: አሁንም በሰላም ከአዲሱ ዘመን እንዲያደርሰን ልንማጸነው ይገባል:: በዚህች ዕለት ደግሞ እነዚህን ቅዱሳን እናከብራለን:: ††† ቅዱስ እንድርያስ ሐዋርያ ††† ††† ቅዱሱ ሐዋርያ ተወልዶ ያደገው በቤተ ሳይዳ አካባቢ ሲሆን የሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ትንሽ ወንድም ነው:: አባቱም ዮና ይባላል:: ገና ከልጅነቱ ጀምሮ ዓሣ ማጥመድን ከትልቅ ወንድሙ ተምሯል:: እድሜው ከፍ ባለ ጊዜ ኦሪትን ተምሮ የመጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ ደቀ መዝሙር ሆኗል:: ከእርሱም እያገለገለ ለስድስት ወራት ተምሯል:: በወቅቱ ከወንጌላዊው (ወልደ ዘብዴዎስ) ዮሐንስ ጋር ቅርብ ባልንጀራም ነበር:: ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተጠመቀ ጊዜ ያን ድንቅ ምሥጢረ ሥላሴ ከተመለከቱትም አንዱ ነው:: ጌታ ከጾም (ከገዳመ ቆረንቶስ) በተመለሰ ጊዜ እንድርያስ መንፈስ ቅዱስ አነሳስቶት ተከትሎታል:: መጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ "ነዋ በግዑ ለእግዚአብሔር ዘያዐትት ኃጢአተ ዓለም - የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ እነሆ::" ማለቱን ሰምቶ ቅዱስ እንድርያስ ጌታን ተከተለ:: በዚህም የመጀመሪያው የክርስቶስ ደቀ መዝሙር ለመባል በቃ:: (ዮሐ. 1:47) ሊቁ ማር ገላውዴዎስም እመቤታችንን ሲያመሰግናት "ለሐዋርያ እንድርያስ ቀዳማዊ ማርያም ሃይማኖቱ ( ለመጀመሪያው ሐዋርያ ለእንድርያስ ሃይማኖቱ ማርያም አንቺ ነሽ::)" ብሏል:: (መልክዐ ስዕል) ቅዱሱ ሐዋርያ ስሉጥ (ፈጣን) አገልጋይ እንደ ነበርም ወንጌል ይነግረናል:: (ዮሐ. 6:9, 12:22) ለሦስት ዓመታት ከሦስት ወር ከጌታ እግር ሥር ተምሮ: በበዓለ ሃምሳ መንፈስ ቅዱስን ተቀበሎ: ምን ሃገረ ስብከቱ ልዳ ብትሆን ብዙ አሕጉረ ዓለምን ሰብኳል:: ይህች ቀን ሐዋርያው ከጌታ ጋር በመርከብ ውስጥ የተነጋገረባትና ቅዱስ ማትያስን ሰውን ከሚበሉ ሰዎች እጅ ያዳነባት ናት:: ቅዱስ እንድርያስ ሰላሳ ቀናት የሚፈጅ የባሕር ላይ ጉዞ ለማድረግ ከአርድእቱ ጋር ወደ ወደብ ቢሔድም መርከበኞች ሁሉ አናሳፍርም በማለታቸው የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወጣት መርከበኛ መስሎ ሐዋርያውንና አርድእቱን የሰላሳውን ቀን መንገድ በሰዓታት ልዩነት እንዲጨርሱ አድርጓል:: ቅዱስ እንድርያስም ፍጡር (እንዲሁ ሰው) መስሎት ለጌታችን ስለ ጌታችን ሰብኮለታል: መርቆታልም:: መርከበኛው ጌታችን መሆኑን ሲያውቅም ደንግጦ አልቅሷል:: "ሶበ አእመረ ኪያሁ ወጠየቀ አምሳሎ: ዘተናገርኩ በድፍረት ምስሌከ ኩሎ: ሥረይ ሊተ ጌጋይየ ወኅድግ ይቤሎ::" እንዲል "ማረኝ?" ብሎታል:: ጌታችንም "አይዞህ እኔ ከአንተ ጋር ነኝ::" ብሎታል:: ቅዱሱ ሐዋርያ ለወንጌል አገልግሎት ተግቶ ያረፈው ታኅሣሥ 4 ቀን ነው:: ††† ቅዱስ ሚልክያስ ነቢይ ††† ††† ሚልክያስ ከአሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ ሲሆን "የመጨረሻው ነቢይ" እየተባለ ይጠራል:: ለዚህ ምክንያቶቹ ሁለት ናቸው:: 1ኛ. ከእርሱ በኋላ የተጻፈ ጥሬ የትንቢት መጽሐፍ የለም:: 2ኛ.እርሱ ካረፈ በኋላ ያለው ዘመን "ዘመነ ካህናት" በመሆኑ ምንም ነቢያት በየጊዜው ባይጠፉ ጐልተው የተነገረላቸው ጥቂቶቹ ናቸው:: ቅዱሱ የተወለደው ቅ/ል/ክርስቶስ ስድስት መቶ ዓመት አካባቢ ሲሆን ከሚጠት (ከባቢሎን ምርኮ መልስ) ሕዝቡን ገስጿል:: ሕዝቡ ከሰባ ዓመት መከራ እንኳን ተመልሶ ኃጢአትን መሥራትን ቸል አላለም ነበር:: በተለይ የልጅነት ሚስታቸውን የሚያታልሉትን ገስጿል:: (ሚል. 2:14) ስለ አሥራትና በኩራትም ተናግሯል:: (ሚል. 3:8) እመቤታችን ድንግል ማርያምንም በንጽሕት አዳራሽ መስሎ ተናግሯል:: "ጽርሕ ንጽሕት ዘሚልክያስ" እንዳሉ አባ ሕርያቆስ:: (ቅዳሴ ማርያም) ነቢዩ ቅዱስ ሚልክያስ ፈጣሪውን አገልግሎ: ሕዝቡን መክሮ ዐርፏል:: ሚልክያስ ማለት "መልአክ: አንድም የተላከ" ማለት ነው:: ነገዱ ከነገደ ይሳኮር ነው:: ††† አምላከ ቅዱሳን አሥራ ሁለቱን ወራት እንደ ባረከልን አሥራ ሦስተኛዋንም ለንስሐ ቀድሶ ይስጠን:: ከቅዱሳኑም በረከትን ያካፍለን:: ††† ነሐሴ 30 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ እንድርያስ ሐዋርያ 2.ቅዱስ ሚልክያስ ነቢይ 3.አባ ሙሴ ዘሃገረ ፈርማ ††† ወርኀዊ በዓላት 1.ቅዱስ ማርቆስ ዘአንበሳ (ሐዋርያ) 2.አባ ሣሉሲ ክቡር 3.ቅዱስ ጐርጐርዮስ ነባቤ መለኮት 4.ቅድስት ሶፍያ ሰማዕት 5.ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት ††† "ስለዚህ መንፈሳችሁን ጠብቁ:: ማንም የልጅነት ሚስቱን አያታልል:: 'መፋታትን እጠላለሁ' ይላል የእሥራኤል አምላክ: የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር::" ††† (ሚል. ፪፥፲፭) ††† "ሰው እግዚአብሔርን ይሰርቃልን? እናንተ ግን እኔን ሰርቃቹሃል:: እናንተም 'የሰረቅንህ በምንድን ነው?' ብላቹሃል:: በአሥራትና በበኩራት ነው:: እናንተ: ይህ ሕዝብ ሁሉ እኔን ሰርቃቹሃልና በእርግማን ርጉሞች ናችሁ::" ††† (ሚል. ፫፥፰) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

✝️✝️✝️††† እንኳን ለታላቁ ቅዱስ አባ ዮሐንስ ሐጺር ዓመታዊ የፍልሠት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† †††✝️✝️ ቅዱስ አባ ዮሐንስ ሐጺር †††✝️✝️ ††† በቤተ ክርስቲያን ያሉ አበው ሊቃውንት እንደሚሉት ከቅዱሳን በቁመቱ የአባ #አርሳኒን ያክል ረዥም አልነበረም:: እርሱ እንደ ዝግባ ቀጥ ያለ ነበር:: በዚያው ልክ ደግሞ የቅዱስ ዮሐንስን (ዛሬ የምናከብረውን) ያህል አጭር አልነበረም:: በዚህ ምክንያት ይሔው ለዘለዓለም " #ዮሐንስ_ሐጺር- አጭሩ አባ ዮሐንስ" ሲባል ይኖራል:: ሊቃውንትም ቁመቱንና ቅድስናውን በንጽጽር ሲገልጡ:- "ሰላም ሰላም ዕብሎ በሕቁ: ለዮሐንስ ሐጺር ዘነዊኅ ሒሩተ ጽድቁ" ይላሉ:: "ቁመቱ እጅግ ያጠረ: ጽድቁ ግን ከሰማይ የደረሰ ቅዱስ ዮሐንስን ሰላም ሰላም እንለዋለን" እንደ ማለት ነው:: ቅዱሱ የተወለደው በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን በምድረ ግብጽ ነው:: ወላጆቹ ምንም ከሥጋዊ ሃብት ድሆች ቢሆኑም ባለ መልካም ክርስትና ነበሩና በጐውን ሕይወት አስተምረውታል:: ወደ ምናኔ የገባው ገና በ18 ዓመቱ ሲሆን የታላቁ አባ ባይሞይ ደቀ መዝሙር ሆኖ ተጋድሎንና ትሕርምትን ተምሯል:: ቅዱስ ዮሐንስ ሐጺር በወቅቱ ከነበሩ ቅዱሳን ከቁመቱ ባሻገር በትሕትናው: በትእግስቱና በመታዘዙ ይታወቅ ነበር:: አባ ባይሞይ ይጠራውና ያለ ምንም ምክንያት ደብድቦ ያባርረው ነበር:: እርሱ ግን "ምን አጠፋሁ?" ብሎ እንኩዋ ሳይጠይቅ "አባቴ ሆይ! ማረኝ?" እያለ ከእግሩ ሥር ይወድቅ ነበር:: ለብዙ ጊዜ በተመሳሳይ ሲደበድበው: እርሱም እርሱው ተደብድቦ: እርሱው ይቅርታን ሲጠይቅ ኖረ:: አንድ ቀን ግን እንደ ልማዱ ሊገርፈው ሲሔድ 7ቱ ሊቃነ መላእክት ከበውት አይቶ ደንግጦ ተመልሷል:: #አባ_ባይሞይ ይሕንን ሁሉ የሚያደርገው ጠልቶት ወይ ክፉ ሆኖ አይደለም:: አንድ ሰው የሌላኛውን ግፍ መቀበል ካልቻለ ሰይጣንን ድል አይነሳም የሚል ትምሕርት ስለ ነበረ ነው እንጂ:: አንድ ቀን ቅዱስ ዮሐንስ ወደ መምሕሩ ቀርቦ "አባቴ ጅብ ካገኘሁ ምን ላድርግ?" ሲል ጠየቀው:: (የአካባቢው ጅብ መናጢ ነበር) አባ ባይሞይ ግን "ይዘህልኝ አምጣው" አለው:: ትዕዛዝ ነውና ቅዱሱ ወደ በርሃ ወርዶ: ጅብ አልምዶ ይዞለት መጥቷል:: ሌላ ቀን ደግሞ አባ ባይሞይ ቅዱስ ዮሐንስን ጠራውና ተፈልጦ የወደቀ ደረቅ እንጨት ሠጠው:: "ምን ላድርገው አባ?" አለው:: "ትከለውና እንዲያፈራ አድርገው:: ከዚያ አምጥተህ አብላኝ" ሲል መለሰለት:: ይህ ነገር ከተፈጥሮ ሥርዓት ውጪ መሆኑን እያወቀ ቅዱስ ዮሐንስ "እሺ" ብሎ ወስዶ ተከለው:: ከዚያም ለ2 ዓመታት ሳይታክት ውሃ አጠጣው:: ውሃውን የሚያመጣበት ቦታ ደግሞ 10 ኪሎ ሜትር ያህል ከገዳሙ ይርቅ ነበር:: ቅዱሱ ላቡን እያፈሰሰ አሁንም ማጠጣቱን ቀጠለ:: በ3ኛው ዓመት ግን ለምልሞ አበበ: ደግሞም አፈራ:: ካፈራው በኩረ ሎሚም ወስዶ ለመምሕሩ "አባቴ! እንካ ብላ" ብሎ ሰጠው:: አባ ባይሞይ ግን ማመን አልቻለም:: እጅግ አደነቀ: አለቀሰም:: ወዲያው ያን ፍሬ ታቅፎ ወስዶ ለገዳሙ መነኮሳት አላቸው:- "ንሱ ብሉ: በረከትንም አግኙ:: ይህ የዛፍ ሳይሆን የመታዘዝ ፍሬ ነው::" ቅዱስ ዮሐንስ አባ ባይሞይ ቢታመም ለ12 ዓመት አስታሞታል:: መምሕሩ ከማረፉ በፊትም መነኮሳቱን ሰብስቦ የቅዱስ ዮሐንስን እጅ አስጨበጣቸው:: "ይህ የያዛችሁት እጅ የሰው ሳይሆን የመልአክ እጅ ነው" ብሏቸው ዐርፏል:: ቅዱስ ዮሐንስም ከዓመታት ቆይታ በሁዋላ የገዳሙ አበ ምኔት ሆኖ አገልግሏል:: ብዙ ነፍሳትንም ለቅድስና ማርኩዋል:: #መላእክት ንጽሕናው ደስ ስለሚያሰኛቸው አብረውት ይውሉ ነበር:: ሲተኛም በተራ በተራ ክንፋቸውን ያለብሱት ነበር:: ምጽዋትን በጣም ስለሚወድ ሰፌድ እየሰፋ ይሸጥና ገንዘቡን ለነዳያን ያን ያካፍል ነበር:: አንድ ቀን እንደ ልማዱ ወደ ገበያ ወጥቶ ሳለ ተደሞ (ተመስጦ) መጣበት:: ሰማያት ተከፍተው: ቅዱሳን #ሊቃነ_መላእክት #ሚካኤል እና #ገብርኤል በግርማ በጌታ ፊት ቆመው ተመለከተ:: "እጹብ: እጹብ" እያለ ሲያደንቅ አንድ ገዢ መጥቶ "ባለ እንቅብ ዋጋው ስንት ነው?" ቢለው "እኁየ ሚካኤልኑ የዓቢ ወሚመ ገብርኤል - ከሚካኤልና ከገብርኤል ማን ይበልጣል?" ብሎታል:: ገዢውም ደንግጦ "እብድ መነኩሴ" ብሎት ሔዷል:: ቅዱስ ዮሐንስ ሐጺር ወደ #ባቢሎን (የአሁኗ ኢራቅ) ሒዶ ከተመለሰ በሁዋላ በበርበሮች ምክንያት ከአስቄጥስ ወደ #ቁልዝም ተሰዷል:: በዚያም በአባ እንጦንስ በዓት ውስጥ ዐርፏል:: ለ400 ዓመታት በዚያው ቆይቷል:: በ825 ዓ/ም ግን በአባ #ዮሐንስ_ፓትርያርክ ዘመን ክቡር ሥጋው ወደ #ገዳመ_አስቄጥስ ተመልሷል:: ቅዱሱ ያረፈው ጥቅምት 20 ቀን ሲሆን ዛሬ ሥጋው የፈለሠበት ነው:: በዚህ ዕለትም የቅዱስ ዮሐንስ ሐጺርና የታላቁ #ቅዱስ_መቃርስ ሥጋ በተገናኙ ጊዜ ግሩም ተአምር ተደርጉዋል:: ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ሲገባም ታላቅ የብርሃን ጐርፍ ሲፈስ ታይቷል:: ሰማያዊ መዓዛም አካባቢውን ሞልቶታል:: ከዻዻሳቱ አንዱ እባረካለሁ ብሎ የቅዱስ ዮሐንስን ሥጋ ቢገልጠው አካባቢው ተናወጠ:: መባርቅትም (መብረቆች) ተብለጨለጩ:: ደንግጠው ቶሎ ቢያለብሱት ጸጥታ ሆኗል:: በዚህ ሁሉ ደስ ያላቸው አበው ቅዱሱን በዝማሬ ሲያወድሱት ውለዋል:: ††† አምላከ ቅዱሳን የሐጺር ቅዱስ ዮሐንስን መታዘዙን: ትሕትናውን: ትእግስቱንና ቅንነቱን ያድለን:: በበረከቱም ይባርከን:: ††† ነሐሴ 29 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ አባ ዮሐንስ ሐጺር (ፍልሠቱ) 2.ቅዱስ አትናቴዎስ ሰማዕት 3.ቅዱሳን ገርሲሞስና ቴዎዶጦስ (ሰማዕታት) 4.አባ ባስልዮስ ጻድቅ (ዘትግራይ) ††† ወርኀዊ በዓላት 1.የፈጣሪያችንና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት 2.ቅድስት አርሴማ ድንግል 3.ቅዱስ ዼጥሮስ ተፍጻሜተ ሰማዕት 4.ቅዱስ ማርቆስ ዘቶርማቅ 5.ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ኢትዮዽያዊት 6.ቅዱስ ዘርዐ ክርስቶስ (ጻድቅና ሰማዕት) ††† "እናንተ ደግሞ የታዘዛችሁትን ሁሉ ባደረጋችሁ ጊዜ 'የማንጠቅም ባሪያዎች ነን: ልናደርገው የሚገባንን አድርገናል' በሉ::" ††† (ሉቃ. 17:10) †††✝️✝️ ወስብሐት ለእግዚአብሔር✝️✝️ †††

ህች የሰማይ ደጅ ናት: ቤተ እግዚአብሔርም ይታነጽባታል::" ብሎ ትንቢት ተናግሯል:: ይህ ቅዱስ አባት ለድንግል ማርያም ቅድመ አያት ከመሆኑ ባሻገር ነቢያትን: ካህናትን: ነገሥታትንና መሣፍንትን ወልዷል:: ከሁለቱ ሚስቶቹ (ልያና ራሔል) : ከሁለቱ ደንገጥሮች አሥራ ሁለት ልጆችን ወልዷል:: ከአጐቱ ከላባ ዘንድ ለሃያ አንድ ዓመታት አገልግሎ: ሃብት ንብረቱን ጠቅልሎ ወደ ርስቱ ከነዓን ሲመለስ ለብቻው ራቅ ብሎ ይጸልይ ገባ:: በዚያም እግዚአብሔር ሲታገለው አደረ:: (ይኸውም የፍቅርና የምሥጢር ነው::) ለጊዜው ጌታ ያዕቆብን "ልቀቀኝ?" ቢለው "ካልባረከኝ አለቅህም?" አለው:: ጌታም ስሙን "እሥራኤል" ብሎ ባርኮታል:: ቅዱስ ያዕቆብ በስተእርጅና ብዙ መከራ አግኝቶታል:: ልጁን ዮሴፍን ወንድሞቹ ሽጠው "አውሬ በላው" ብለውታልና በለቅሶ ዓይኑ ጠፋ:: በረሃብ ምክንያትም በመቶ ሰላሳ ዓመቱ ከሰባ አምስት ያህል ቤተሰቦቹ ጋር ወደ ግብጽ ወረደ:: በዚያም ለሰባት ዓመታት ኑሮ በመቶ ሰላሳ ሰባት ዓመቱ ዐርፏል:: ልጆቹም ቀብረውታል:: ††† በሰማይና በምድር ከሞላው ከአባቶቻችን በረከት ፈጣሪያቸው አብዝቶ: አትርፎ: አትረፍርፎም ያድለን:: ††† ነሐሴ 28 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ አብርሃም (የአባቶች አለቃ) 2.ቅዱስ ይስሐቅ (የአባቶች አለቃ) 3.ቅዱስ ያዕቆብ (የአባቶች አለቃ) ††† ወርኀዊ በዓላት 1.አማኑኤል ቸር አምላካችን 2.ቅድስት ዓመተ ክርስቶስ 3.ቅዱስ ቴዎድሮስ ሮማዊ 4.ቅዱሳን እንድራኒቆስና አትናስያ ††† "አብርሃምንና ይስሐቅን: ያዕቆብንም: ነቢያትንም ሁሉ በእግዚአብሔር መንግስት ባያችሁ ጊዜ: እናንተ ግን ወደ ውጭ ተጥላችሁ ስትቀሩ በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል::" ††† (ሉቃ. ፲፫፥፳፰) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

††† እንኳን ለአበው ቅዱሳን አብርሃም: ይስሐቅ እና ያዕቆብ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† †††በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† እኒህ ቅዱሳን ከሰው ወገን እጅግ ክቡራን ከመሆናቸው የተነሳ መንግስተ ሰማያት በእነርሱ ስም ተጠርታለች:: ጽድቃቸውና ክብራቸው እንደ ሰማይ ከዋክብት የበዛ ነውና ጽፈንም: ተናግረንም አንፈጽመውም:: እንዲሁ "ዕጹብ! ዕጹብ!" እያልን ፈጣሪያቸውን ከማመስገን በቀር:: ††† ቅዱስ አብርሃም ርዕሰ አበው ††† ††† የሃይማኖት: የደግነት: የምጽዋት: የፍቅር አባት የሆነው አብርሃም በቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት አባቱ ታራ ጣዖትን ይጠርብና ይሸጥ ነበር:: ሽጦ ገንዘብ የሚያመጣለት ደግሞ ልጁ አብርሃም ነበር:: በዚያ ወራት አብርሃም እውነተኛውን አምላክ ፍለጋ ገብቶ ነበር:: አንድ ቀን ጣዖቱን ሊሸጥ ወደ ገበያ እየሔደ የተሸከመውን እንጨት ይመራመረው ገባ:: "አሁን ይሔ ምኑ ነው አምላክ!" እያለም ያደንቅ ገባ:: መንገድ ላይም ደክሞት ካረፈበት "ለምን አልጠይቀውም?" በሚል አናገረው:: "እርቦኛል አብላኝ?" አለው:: መልስ የለም:: "እሺ አጠጣኝ?" አለው:: አሁንም ያው ነው:: "ባይሆን እሺ አጫውተኝ?" አለው:: ጣዖቱ ተራ እንጨት ነውና መልሱ ዝምታ ነበር:: ከዚያ ተነስቶ ወደ ገበያው ሲደርስ "ዓይን እያለው የማያይ: ጆሮ እያለው የማይሰማ አምላክ የሚገዛ?" እያለ ይጮህ ጀመር:: ይህን ሲሰሙ አንዳንዶቹ "የታራ ልጅ አብዶ" ሲሉ ሌሎቹ ደግሞ "እሱ ያቀለለውን ማን ይገዛዋል::" ብለውት ሔደዋል:: ሲመለስም ጣዖቱን ተመልክቶ አብርሃም እንዲህ አለ:: "አንተ ቀድሞውን በዕለተ ሠሉስ የተፈጠርክ ዕፅ ነህ::" ብሎ ሰባበረው:: ወደ ቤቱ ሲመለስም ሁሉንም ጣዖታት ሠባበራቸው:: የመንግስተ ሰማያት አበጋዝ: የእግዚአብሔር ወዳጅ አባታችን አብርሃም የሕዝብና የአሕዛብ አባት የሆነው አብርሃም እግዚአብሔርን አምልኮ: ጣዖታትን ሰብሮ ወደ ከነዓን ከወጣ በኋላ ብዙ ችግርን አሳልፏል:: በረሃብ ምክንያት ከአንድም ሁለት ጊዜ ወደ ግብጽና ፍልስጥኤም ተሰዷል:: በዚያ ግን ፈጣሪው አክብሮታል:: ሁለቱ ነገሥታት (ፈርኦንና አቤሜሌክ) ሣራን እንነካለን ቢሉ ተግሣጽ ደርሶባቸዋል:: ነቢይ ነውና በአብርሃም ጸሎት ተፈውሰዋል:: ቅዱስ አብርሃም ከደግነቱ የተነሳ በኬብሮን (በተመሳቀለ መንገድ) ላይ ድንኳን ሠርቶ እንግዳ ይቀበል ነበር:: ምሥክር ሳይዝም እህል አይቀምስም ነበር:: ሰይጣን ከፍቶ እንግዳ ቢያስቀርበት ያለ ምግብ ለሦስት ቀናት ቆይቷል:: በፍጻሜውም ሥላሴ በእንግድነት መጥተውለት በክብር ላይ ክብር: በጸጋ ላይ ጸጋ: በጣዕም ላይ ጣዕም ተጨምሮለታል:: እርሱ የሥላሴን እግር ያጥብ ዘንድ: በጀርባውም ይሸከማቸው ዘንድ አድሎታልና:: ሥላሴም በቤቱ ተስተናግደው: ልደተ ይስሐቅን አብሥረውታል:: ጻድቁ ሰውም በፈጣሪው ፊት ስለ ሰዶምና ገሞራ ለምኗል:: አብርሃም በአምልኮው ፍጹም ነውና የሚወደውን ልጁን ይስሐቅን ለመስዋዕት አቅርቧል:: በዚህም የነቢያት: የሐዋርያት: የነገሥታት: የካህናት አባት: ሥርወ ሃይማኖት (የሃይማኖት ሥር) ተብሏል:: ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ አያቱም ተብሏል:: አንድ ቀን እግዚአብሔር መላእክቱን "ብየ አርክ አብርሃም በዲበ ምድር - በምድር ላይ ወዳጄ አብርሃም አለ::" አላቸው:: ያን ጊዜ ዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት ፈጣሪያቸውን አመሰገኑ:- *"አብርሃም አርከ እግዚአብሔር (አብርሃም የእግዚአብሔር ወዳጅ)" *"አብርሃም ብእሴ እግዚአብሔር (አብርሃም የእግዚአብሔር ሰው)" *"አብርሃም ገብረ እግዚአብሔር (አብርሃም የእግዚአብሔር አገልጋይ)" *"አብርሃም ምዕመነ እግዚአብሔር (አብርሃም የእግዚአብሔር ታማኝ) *"አብርሃም ፍቁረ እግዚአብሔር (አብርሃም የእግዚአብሔር ተወዳጁ ነው::) እያሉ አሰምተው ተናግረዋል:: አባታችን አብርሃም በክብር: በቅድስናና በሞገስ ከዘፍጥረት እስከ ዮሐንስ ራእይ ድረስ ተጠቅሷል:: ፈጣሪ በስሙ ለቅዱሳን ተለምኗል:: ስለ ክብሩም በሲዖል ውስጥ እንኳ ማረፊያን ሠርቶለታል:: አጋንንትም ሊቀርቡት አልተቻላቸውም:: ያረፈውም ከክርስቶስ ልደት አንድ ሺ ዘጠኝ መቶ ዓመታት በፊት ነው:: እድሜውም መቶ ሰባ አምስት ዓመት ነበር:: *ፍቅሩን የተረዱ ሊቃውንት ድንግል ማርያምን "ሐይመቱ (ድንኳኑ): ተናግዶቱ (እንግድነቱ) ለአብርሃም" ሲሉ አመስግነዋታል:: ሊቁም:- ††† "አብርሃም ፍጹም በሒሩት ወበአምልኮ: እግዚአብሔር አዕበየከ ወባረከከ ባርኮ: እስከ ሰመየከ ዲበ ምድር አርኮ::" ብሎ በምሥጢር ገልጾታል:: ††† ቅዱስ ይስሐቅ ርዕሰ አበው ††† ††† የደግ ዛፍ ፍሬ: የአብርሃም ልጅ ደጉ ይስሐቅ እጅግ ንጹሕ በመሆኑ የወልድ ክርስቶስ ምሳሌ ተብሏል:: የይስሐቅ ልደት እጅግ የተጠበቀ ከመሆኑ ባሻገር የተፈጸመውም በብሥራተ አምላክ ነው:: ስሙንም ያወጡለት ሥላሴ ናቸው:: ቡሩክ ይስሐቅ በብዙ ነገሩ ድንቅ ነው:: ለእርሱ ሃያ ዓመት ለአባቱ መቶ ሃያ ዓመት በሆናቸው ጊዜ ጭንቅ ትዕዛዝ ከፈጣሪ ዘንድ ተሰማ:: አብርሃም ይሰዋው ዘንድ ወደ ደብረ ምሥጢር ይዞት ከወጣ በኋላ መስዋዕቱ እርሱ እንደ ሆነ አወቀ:: ለፈጣሪውና ለአባቱ ይታዘዝ ዘንድ "እሺ" አለ:: በዚያውም ላይ አባቱን "አባ ስንፈራገጥ እንዳልጐዳህ እሠረኝ:: ዓይኔን አይተህ እንዳትራራ በሆዴ አስተኛኝ::" አለው:: አቤት ትሕትና! አቤት መታዘዝ! ወዮ አባታችን ይስሐቅ! ቅንነትህ ምን ይደንቅ! ለዚህ አነጋገርህ አንክሮ ይገባል! ††† "ሰላም ለይስሐቅ ዘኢያግዘፈ ክሳዶ: ለደኒን ወለተሐርዶ" እንዲል:: ቸር ፈጣሪ ግን የአብርሃምን አምልኮ: የይስሐቅን ንጹሕ መታዘዝ ለዓለም ገለጠ እንጂ እንዲሞት አላደረገም:: ቅዱስ ይስሐቅ በዚህች ዓለም ለመቶ ሰማንያ ዓመታት: በትዳር ደግሞ ለመቶ ሃያ ዓመታት ቆይቷል:: ከቅድስናው የተነሳ በእነዚህ ጊዜያት ከአንድ ቀን በቀር ከሚስቱ ርብቃ ጋር አልተኛም:: በዚህቺው ዕለትም ያዕቆብና ኤሳው ተጸንሰዋል:: እግዚአብሔር በመቶ ሰማንያ ዓመቱ ወደ ሰማይ ይዞት ወጣ:: በዚያም ግሩም ምሥጢርን ተመለከተ:: በእሳት መጋረጃ መካከል አብርሃምን አየው:: ከአምላክ ዙፋንም እንዲህ የሚል ቃል ወጣ:: *"ወዳጄን ይስሐቅን የሚያከብረውን አከብረዋለሁ:: *ልጁን አምኖ "ይስሐቅ" ብሎ የሚጠራውን *በስሙ ለነዳያን የሚራራውን *ለቤቱ እጣን ያመጣውን *በዚህች ሌሊት በጸሎት የተጋውን *'አምላከ ይስሐቅ' እያለ መቶ (100) ጊዜ የሰገደውን *ዜና ይስሐቅን የጻፈውን: ያነበበውን ሁሉ በመንግስተ ሰማያት ዋጋውን እከፍለዋለሁ:: ይህንንም ልጁ (አባታችን ያዕቆብ) ተመልክቶ ከትቦታል:: ቅዱስ ይስሐቅም ከንጽሕናው ሳይጐድል በበረከት እንዳጌጠ ዐርፏል:: ††† ወገኖቼ! ከላይ ካነበባችሁት መርጣችሁ አንዷን በእምነት እንድትፈጽሙ አደራ እላለሁ! ††† ቅዱስ ያዕቆብ ርዕሰ አበው ††† ††† የአባቶች አለቃ የተሰኘ ቅዱስ ያዕቆብ ለሁለቱ ታላላቅ አባቶቹ እርሱ ሦስተኛቸው ነው:: እነርሱን መስሎ: እነርሱንም አህሎ በጐዳናቸው ተጉዟል:: በፈቃደ እግዚአብሔር ብኩርናን ከኤሳው ተቀብሎ ወደ ሶርያ ሲሸሽ ቤቴል (ፍኖተ ሎዛ) ላይ ድንጋይ ተንተርሶ በተኛበት ግሩም ራዕይን አይቷል::ይህችውም የወርቅ መሰላል የድንግል ማርያም ምሳሌ ናት:: "አንቲ ውዕቱ ሰዋስው ዘርእየ ያዕቆብ" እንዳለ ቅዱስ ኤፍሬም (ውዳሴ ማርያም ዘሠሉስ) ተነስቶም "ዛቲ ይእቲ ኈኅታ ለሰማይ: ዝየ ይትሐነጽ ቤተ እግዚአብሔር - ይ

✝✞✝ በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን:: ✝✞✝ """ ነሐሴ 27ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት """ +" 12ቱ አበው ደቂቀ እሥራኤል "+ =>እነዚህ አበው የአብርሃምና የይስሐቅ የልጅ ልጆች የያዕቆብ ደግሞ ልጆች ናቸው:: ትውልድ ከአዳም እስከ ቅዱስ ያዕቆብ አንድ ሐረግ ይዞ መጥቶ እዚህ ላይ ሲደርስ ይበተናል:: አባታችን ያዕቆብን እግዚአብሔር ሲባርከው እሥራኤል አለው:: ትርጉሙም "ሕዝበ እግዚአብሔር: ወልድ ዘበኩር (የበኩር ልጅ): ከሃሊ: ነጻሪ (አስተዋይ) እንደ ማለት ነው:: +ይህ ቅዱስ አባት ለድንግል ማርያም ቅድመ አያት ከመሆኑ ባሻገር ነቢያትን: ካህናትን: ነገሥታትንና መሣፍንትን ወልዷል:: ከወንድሙ ኤሳው ጋር ተጣልቶ ወደ ሶርያ በሔደ ጊዜ ከ2ቱ ሚስቶቹ (ልያና ራሔል) 8 ልጆችን: ከ2ቱ የሚስቶቹ ደንገ ጥሮች (ዘለፋና ባላ) 4 ልጆችን: በድምሩ 12 ልጆችን ወልዷል:: #‎ልያ  የወለደቻቸው:- 1.ሮቤል 2.ስምዖን 3.ሌዊ 4.ይሁዳ 5.ይሳኮር እና 6.ዛብሎን ይባላሉ:: #‎ራሔል  የወለደቻቸው:- 7.ዮሴፍና 8.ብንያም ይባላሉ:: #‎ባላ :- 9.ዳን እና 10.ንፍታሌምን ስትወልድ #‎ዘለፋ :- ደግሞ 11.ጋድና 12.አሴርን ወልዳለች:: #‎12ቱ  ደቂቀ እሥራኤል (ያዕቆብ) ማለት እኒህ ናቸው:: +ከ12ቱ በቅድስና ዮሴፍ ከፍ ቢልም እግዚአብሔር ለክህነት ሌዊን: ለመንግስት ደግሞ ይሁዳን መርጧል:: ከእነሱ ዘርም ዓለምን ለማዳን ተወልዷል:: 10ሩ አበው በተለይ በዮሴፍ ላይ ግፍ ሠርተው የነበረ ቢሆንም በኋላተጸጽተዋል:: እነሆ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ታስባቸዋለች:: (ዘፍ. ከ28-31) +" ነቢዩ ቅዱስ ሳሙኤል "+ +እሥራኤል ከግብፅ ባርነት ወጥተው ከነዓንን ከወረሱበት ዘመን ጀምረው መሳፍንትና ካህናት ያስተዳድሯቸው ነበር:: በወቅቱ ታዲያ ክህነት ከምስፍና ተስማምቶለት ኤሊ የተባለ ሊቀ ካህናትና ልጆቹ (አፍኒና ፊንሐስ) ያስተዳድሩ ጀመር:: +በዘመኑ ደግሞ ማሕጸኗ ተዘግቶባት ዘወትር የምታለቅስ ሐና የሚሏት ደግ ሴት ነበረች:: እግዚአብሔር የእርሷን ጸሎትና የሊቀ ካህናቱን ምርቃት ሰምቷልና ቅዱስ ልጅን ሰጣት:: "ሳሙኤል" አለችው:: "ልመናየን አምላክ ሰማኝ" ማለት ነውና:: +ሐና ስዕለቷን ትፈጽም ዘንድ ሳሙኤልን በ3 ዓመቱ ለቤተ እግዚአብሔር ሰጠችው:: በዚያም ስብሐተ እግዚአብሔርን እየሰማ: ማዕጠንቱን እያሸተተ: ከደብተራ ኦሪቱ ሳይለይ በሞገስ አደገ:: የኤሊ ልጆች (አፍኒና ፊንሐስ) በበደል ላይ በደልን አበዙ:: +ወቅቱ የአሁኑን ዘመን ይመስል ነበር:: ሁሉም ሰው ክፋተኛ የሆነበት በመሆኑ እግዚአብሔር ርቆ ስለ ነበር ትንቢትና ራዕይ ብርቅ ነበር:: አምላክ ተቆጥቷልና ሳሙኤልን በሌሊት 3 ጊዜ ጠራው:: ነቢዩም ታጥቆ የፈጣሪውን ቃል ሰማ:: በዚሕም የተነሳ ታቦተ ጽዮን ለመጀመሪያ ጊዜ በአሕዛብ ተማረከች:: ከ34ሺ በላይ ሕዝብ በኢሎፍላውያን አለቀ:: አፍኒና ፊንሐስም ተገደሉ:: ኤሊም ወድቆ ሞተ:: +ከዚህች ቀን በኋላ ቅዱስ ሳሙኤል በእሥራኤል ላይ ነቢይና መስፍን ሆኖ ተሾመ:: በዘመኑ ሁሉ እንደሚገባው እየኖረ: የእግዚአብሔርን ለእሥራኤል: የእሥራኤልን ለእግዚአብሔር ሲያደርስ ኑሯል:: ሕዝቡ ንጉሥ በፈለጉ ጊዜ ሳዖልን ቀብቶ አነገሠላቸው:: እርሱ (ሳዖል) እንደ ሕጉ አልሔደምና ፈጣሪ ናቀው:: +ሳሙኤል ግን ደግ አባት ነውና ክፋተኛውን (ሳዖልን) ከጌታው ጋር ያስታርቅ ዘንድ ብዙ ደከመ: አለቀሰም:: እግዚአብሔር ግን ሳሙኤልን:- "አትዘን! እንደ ልቤ የሆነ: ፈቃዴን የሚፈጽም ዳዊትን አግኝቸዋለሁና እርሱን በእሥራኤል ላይ አንግሠው" አለው:: ቅዱስ ሳሙኤልም ወደ ቤተ ልሔም ሔዶ: ከእሴይ ልጆችም መርጦ ልበ አምላክ ዳዊትን ቀባው: አነገሠውም:: +ቅዱስ ሳሙኤል በተረፈው ዘመኑ ለፈጣሪው እየተገዛ ኑሯል:: ነቢዩ ዘወትር ከእጁ የሽቱ ሙዳይና የቅብዐት እቃ (ቀንድ) አይለይም ነበረ:: እነዚህም የድንግል ማርያም ምሳሌዎች ናቸውና አባ ሕርያቆስ:- "ሙዳየ ዕፍረት ወቀርነ ቅብዕ ዘሳሙኤል" ብሎ አመስግኗታል:: +ነቢዩም በወገኖቹ መካከል በዚሕች ቀን አርፏል:: እሥራኤልም አልቅሰውለታል:: ዛሬ ቅዱሱ ነቢይ ለአገልግሎት የተጠራበት ቀን ነው:: +" ቅዱስ ሱርያል ሊቀ መላዕክት "+ +ከታላላቅ ሊቃናት አንዱ የሆነው ቅዱስ ሱርያል ክብሩ ብዙ ቢሆንም ብዙ ምዕመናን አያውቁትም:: የመላእክት መዓርግ ሲነገር ሚካኤል: ገብርኤል: ሩፋኤል ብሎ ቀጥሎ የሚመጣው ሱርያል ነው:: +በ3ቱ ሰማያት ካሉት 9ኙ ዓለመ መላእክት የአንዱ (የሥልጣናት) መሪ (አለቃ) ነው:: መልአኩ እጅግ ርሕሩሕ እና ተራዳኢ ነውና አንዘንጋው:: ለኖኅ መርከብርን ያሳራው: ከጥፋት ውሃም ያዳነው ይህ ቅዱስ መልአክ ነው:: +በገድለ ሰማዕታትም ላይ እንደተጠቀሰው የሰማዕታት ረዳትና አዳኝም ነው:: ቅዱስ ሱርያል በሌላ ስሙ "እሥራልዩ" ይባላል:: "የእሥራኤል ረዳት" እንደ ማለት:: =>ቸሩ አምላከ ቅዱሳን ስለ አባቶቻችን ብሎ ይማረን:: ከበረከታቸውም ያድለን:: =>ነሐሴ 27 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት= 1."12ቱ" ደቂቀ ያዕቆብ (እሥራኤል) 2.ቅዱስ ሳሙኤል ነቢይ (የተጠራበት) 3.ቅዱስ ሱርያል ሊቀ መላእክት 4.ቅዱስ ብንያሚንና እህቱ አውዶከስያ (ሰማዕታት) 5.ቅዱስ ፊቅጦርና እናቱ ሣራ 6.አባ ባስልዮስ ፓትርያርክ ዘኢትዮዽያ (የተሾሙበት) በ 27 የሚከበሩ ወርኀዊ የቅዱሳን በዓላት 1.የጌታችንና አምላካችን መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ በዓለ ስቅለት 2.አቡነ መብዐ ፅዮን ጻድቅ 3.ቅዱስ መቃርስ (የመነኮሳት ሁሉ አለቃ) 4.ቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ 5.ቅዱስ ገላውዴዎስ ሰማዕት (ንጉሠ ኢትዮዽያ) 6.ቅዱስ ቢፋሞን ጻድቅና ሰማዕት 7.ማር ቅዱስ ፊቅጦር ሰማዕት =>+"+ እነዚህም ሁሉ አሥራ ሁለቱ የእሥራኤል ነገዶች ናቸው:: አባታቸው የነገራቸው ይህ ነው:: ባረካቸውም:: እያንዳንዳቸውን እንደ በረከታቸው ባረካቸው:: +"+ (ዘፍ. 49:28) =>+"+ በመንፈስም ወደ ታላቅና ወደ ረዥም ተራራ ወሰደኝ:: የእግዚአብሔርም ክብር ያለባትን ቅድስቲቱን ከተማ ኢየሩሳሌምን ከሰማይ: ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አሳየኝ . . . አሥራ ሁለት ደጆችም ነበሯት:: በደጆቹም አሥራ ሁለት መላእክት ቆሙ:: የአሥራ ሁለቱም የእሥራኤል ልጆች ነገዶች ስሞች ተጽፈውባቸው ነበር:: +"+ (ራዕይ. 21:11) <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>

††† እንኳን ለእናታችን ብጽዕት ሣራ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ቅድስት ሣራ ብጽዕት ††† ††† አበው እናታችን ሣራን " #ቡርክተ_ማሕጸን" ይሏታል:: (የቅዱሱ ዘር የይስሐቅ እናት ናትና) በዚያውም ላይ የደጉ ሰው የአብርሃም ሚስት ናት:: ልክ በዓለም ታሪክ "ከጠንካራና ስኬታማ ወንዶች ጀርባ ጠንካራ ሴቶች አሉ" እንደሚባለው ከአብርሃም አባታችን ስኬታማ የቅድስና ሕይወት ጀርባ ብጽዕት ሣራ አለች:: ለአብርሃም አባታችን መጽሐፍ የተናገረው ክብር ሁሉ ለቅድስት ሣራ ይገባታል:: አንድም ገንዘቧ ነው:: ቅድስቷ እናት ደጉ አብርሃምን ያገባችው ገና በከላውዴዎን (በ2ቱ ወንዞች መካከል) ሳለ ነው:: ገና ከልጅነቷ ጀምራ አብርሃምን "ጌታየ" እያለች ታገለግለው እንደ ነበር ቅዱስ መጽሐፍ ይናገራል:: (1ዼጥ. 3:5) በዚህም ከብራበታለች: ገናበታለች እንጂ አልተጐዳችበትም:: አብርሃም ወደ ካራን ሲወጣ "ለምን?" አላላችም:: እንዲሁ ለፈቃደ እግዚአብሔር ታዘዘች እንጂ:: በካራን ታራን ቀብረው: በፈጣሪ ትዕዛዝ ወደ #ከነዓን ሲፈልሱም ቅድስት ሣራ አልተቃወመችም:: ለፈጣሪዋ ትዕዛዝና ለባሏ ስትል ርስቷን: ሃገሯን: ዘመዶቿን ሁሉ ትታ ሔዳለች:: ይሔውም በጐ ምናኔ ነው:: እናታችን ሳራ በከነዓን የተመቸ ነገር አልገጠማትም:: ከአንዴም ሁለቴ በረሃብና በድርቅ ምክንያት ወደ ግብጽ እና #ጌራራ ተሰደዋል:: በዚያም ፈርዖን "እነካለሁ" ቢል እግዚአብሔር ተቆጥቶ: ፈርኦንንና ግብጽን በደዌ መታ:: በዚህም ክብረ ሣራን ተመለከትን:: ከስደት መልስም በኬብሮን (በተመሳቀለ መንገድ ላይ) ድንኩዋን ሠርተው የወጣ የወረደውን ሲያበሉ: እንግዳ ሲቀበሉ ኑረዋል:: (ልብ በሉልኝ ይህን ትጋትና ደግነት ያሳየችውን ቅድስት ሣራን ልናከብራት ይገባል) እድሜ ዘመኗን ያሳለፈችው እንግዳ በመቀበል: እግዚአብሔርን በማምለክ ነው:: ምንም እንኩዋ ማሕጸኗ ለጊዜው ቢዘጋ ተስፋ አልቆረጠችም:: ለአብርሃምም ከአጋር እንዲወልድ ፈቃድ ሰጥታለች:: ዕድሜዋ 89 ዓመት በሆነ ጊዜ ሰይጣን እንግዳ እንዳይመጣ ለ3 ቀናት ቢያስቀርባቸው እንደ ባሏ እርሷም 3 ቀናትን ያለ ምግብ አሣልፋለች:: በ3ኛው ቀን ሥላሴን በቤቷ አስተናግዳለች:: ስለ ክብሯም ከ3 መሥፈሪያ ዱቄት ለውሳ ያዘጋጀችውን እንጐቻ ሥላሴ በልተውላታል:: (ምንም ሥላሴ ምግብን ባይመገቡም) የሥላሴ በዚያች ድንኩዋን ውስጥ መስተናገድ ታላቅ ምሥጢር አለው:: ከግብዣው በሁዋላም እግዚአብሔር አለ:- "አመ ከመ ዮም እገብእ ኀቤከ . . . እንዲሁ ከርሞ እመለሳለሁ: ሣራ ወንድ ልጅን ትወልድልሃለች" አለው:: ያን ጊዜ ሣራ በውሳጤ ሐይመት (በድኩዋኑ ውስጥ) ሆና ሰምታ ሣቀች:: ለምን ሳቀች ቢሉ:- እጅግ ደስ ቢላት! አንድም ቢገርማት:: ይሕስ በምን ይታወቃል ቢሉ:- ልጇ " #ይስሐቅ" የተባለው "ለእናቱ ሣቅን: ደስታን ያመጣ" ለማለት ነውና:: ሥላሴም:- "ምንት አስሐቃ ለሣራ በባሕቲታ: እንዘ ትብል ዓዲየኑ እስከ ይእዜ: ወእግዚእየኑ ልሕቀ: ቦኑ ነገር ዘይሰዓኖ ለእግዚአብሔር - ሣራን ምን አሳቃት? ለእግዚአብሔርስ የሚሳነው ነገር አለን" ብለዋል:: ቅድስት ሣራ በ90 ዓመቷ ይስሐቅን ወልዳ በቀሪ ዘመኖቿ በደስታ ኑራለች:: በዚህች ቀንም በመልካም ሽምግልና ዐርፋ: አባታችን #አብርሃም ከታላቅ ሐዘን ጋር ቀብሯታል:: ሐዋርያው #ቅዱስ_ዻውሎስ ብጽዕት ሣራን በበጐ ምሳሌ መስሏታል:: (ዕብ. 11:11) ††† ቅዱሳን ሞይስስና ሣራ ††† ††† እነዚህ ቅዱሳን ግብጻውያን የአንድ እናት: የአንድ አባት ልጆች ሲሆኑ የነበሩትም በዘመነ ሰማዕታት ነው:: ከወላጆቻቸው ጋር በሥርዓተ ክርስትና አድገው ዕድሜአቸው ለአካለ መጠን ሲደርስ ወላጆቻቸው ሞቱባቸው:: ያን ጊዜ #ቅዱስ_ሞይስስ እህቱን ቅድስት ሣራን ጠርቶ "እህቴ! እኔ ወደ ገዳም መሔዴ ስለሆነ አንቺ ባል አግብተሽ: ሃብት ንብረቱን ወርሰሽ ኑሪ" አላት:: #ቅድስት_ሣራ ግን መልሳ "እንዴት እኔን በዚህ ዓለም ወጥመድ ውስጥ ትተወኛለህ? ሁለታችንም ከአንድ ማሕጸን ነን:: ስለዚህ ላንተ የምትፈልገው ሁሉ ለእኔም ያስፈልገኛልና እኔም መናኝ ነኝ" አለችው:: ቅዱስ ሞይስስ የልቡናዋን መጨከን ሲያይ ነዳያንን ሰበሰበ:: ገንዘቡን: ቤቱን: ሃብቱንና ንብረቱን ሁሉ በየስልቱ ለነዳያን አካፈለ:: ሳይዘገይም እህቱን ይዞ ወደ በርሃ ተጉዋዘ:: እርሷን ከደናግል ገዳም አስገብቶ እርሱ ከወንዶች ገዳም ውስጥ መነኮሰ:: ለ10 ዓመታት ሁለቱም ለፈጣሪያቸው በጾምና በጸሎት: ከስግደት ጋር ሲገዙ: ለአባቶችና እናቶች ደግሞ በትሕትና ሲታዘዙ ኖሩ:: በእነዚህ ሁሉ ዓመታት አንድም ቀን ተገናኝተው አያውቁም ነበር:: አንዱ ለሌላኛው ተግቶ መጸለይን ግን ቸል አላሉም:: ዘመኑ ዘመነ ዐጸባ (የመከራ) ነውና መከራው እየገፋ ሲመጣ ቅዱስ ሞይስስ አንድ ነገር አሰበ:: በክርስቶስ ስም ደሙን ለማፍሰስም ወሰነ:: ወደ ከተማ ከመውጣቱ በፊት ግን ለቅድስት ሣራ መልዕክት ላከባት:: "እኔ ወደ ምስክርነት እየሔድኩ ስለሆነ ቸር ሁኚ" የሚል ነበር መልእክቱ:: እርሱ ይህንን ብሎ ወደ ከተማ ሲሔድ ግን መንገድ ላይ እህቱን አገኛት:: ገርሞት የፍቅር ሰላምታን ከተለዋወጡ በሁዋላ "እንዴት መጣሽ?" ቢላት "ወንድሜ! ቀድሞም ነግሬሃለሁ:: ላንተ የምትፈልገው የድኅነት መንገድ ሁሉ ለእኔም ያስፈልገኛል" አለችው:: ሁለቱም ተያይዘው ወደ መከራ አደባባይ ደረሱ:: በዚያም ስመ ክርስቶስን ሰብከው: ብዙ መከራንም ተቀብለው በዚህች ቀን ሰማዕት ሆነዋል:: ††† አምላከ ቅድስት ሣራ ደግነቷን: መታዘዟን ያሳድርብን:: ከበረከቷ: ከሌሎችም ቅዱሳን በረከትን ይክፈለን:: ††† ነሐሴ 26 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ብጽዕት ሣራ (የአብርሃም ሚስት) 2.ቅዱሳን አባ ሞይስስና እህቱ ሣራ (ሰማዕታት) 3.ቅዱሳን አጋቦስና ቴክላ (ሰማዕታት) ††† ወርሐዊ በዓላት 1.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ 2.አቡነ ሐብተ ማርያም ጻድቅ 3.አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ 4.ቅዱሳን ሰማዕታተ ናግራን 5.ቅዱስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ††† "እንዲህ በቀድሞ ዘመን በእግዚአብሔር ተስፋ ያደረጉት ቅዱሳት ሴቶች ደግሞ ለባሎቻቸው ሲገዙ ተሸልመው ነበርና:: እንዲሁም #ሣራ_ለአብርሃም:- #ጌታ ብላ እየጠራችው ታዘዘችለት:: እናንተም ከሚያስደግጥ ነገር አንዳች እንኩዋ ሳትፈሩ መልካም ብታደርጉ ልጆቿ ናችሁ::" ††† (1ዼጥ. 3:5) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

††† እንኳን ለቅዱስ እንድርያኖስ ሰማዕት እና ለታላቁ አባ ቢጻርዮን ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† †††በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ቅዱስ እንድርያኖስ ሰማዕት ††† ††† ቅዱሱ በ3ኛው መቶ ክ/ዘ የነበረ አረማዊ ሰው ሲሆን ከከሃዲው መክስምያኖስ ወታደሮችም አንዱ ነበር:: "ሊቀ መሓዛት" ይሉታል: የጐበዛዝቱ አለቃም ነበር:: ይህ ሰው ምንም ክርስቲያን አይሁን እንጂ በልቡ ቅንነት ተገኝቶበታል:: እንደ አሕዛብ ልበ ድንጋይ አልነበረም:: በወጣትነቱም አንዲት ደመ ግቡ ሴት አግብቷል:: ይህች ሴት ' #ኤልያና' ስትባል የተባረከች ክርስቲያን ናት:: እርሱ ግን አያውቅም:: ከተጋቡ ከዓመታት በሁዋላ ጌታ እግዚአብሔር ስለ ሚስቱ ጸሎት በጐ ጐዳና ሊመራው ፈለገ:: እንድርያኖስ ሁሌም በየቀኑ ክርስቲያኖች ደማቸውን ሲያፈሱ ይመለከታል:: የትእግስታቸው መጠንም ይገርመው ነበር:: በተለይ አብዛኞቹ በመከራው ደስተኞች ነበሩ:: ነገሩ ግራ ቢያጋባው 24 ባለንጀሮች ሊገደሉ ወደ ታሠሩበት ቦታ ሒዶ ጠየቃቸው:: "ምን ልታገኙ ነው ግን ይሕንን ሁሉ ስቃይ በአኮቴት (በምስጋና) የምትቀበሉት?" ቢላቸው "በሰማይ በክርስቶስ ዘንድ የሚጠብቀንን የክብር ሕይወት ሥጋዊ አንደበት አከናውኖ መናገር አይቻለውም:: ዝም ብሎ 'ዕጹብ: ዕጹብ' እያሉ የሚያደንቁት ነው እንጂ" አሉት:: እርሱም ተደላድሎ ተቀምጦ "እስኪ በደንብ አስረዱኝ" አላቸው:: ከዓለም መፈጠር እስከ ጌታችን የማዳን ሥራ: አልፎም ስለ ፍርድ ቀን በጥዑም አንደበታቸው አስተማሩት:: ቅዱስ እንድርያኖስ በቅጽበት ልቡ ወደ ክርስቶስ ፍቅር ሸፈተ:: በፍጥነት ተነስቶ የራሱን ስም ከሰማዕታቱ 25ኛ አድርጐ አጻፈ:: ንጉሡ ይሕንን ሲሰማ "አብደሃል" ቢለው ቅዱሱ መልሶ "የለም! ዛሬ ገና ከእብደቴ ተመለስኩ" በማለቱ ከ25ቱ ቅዱሳን ጋር ታሠረ:: ቅድስት ኤልያና (ሚስቱ) ነገሩን ስትሰማ ፈጽሞ ደስ አላት:: ወደ እስር ቤት ሒዳ "አይዞህ በርታ! ስለ ክርስቶስ የሞትክ ቀን ብቻ እኮራብሃለሁ" ብላ: እግራቸውን አጥባቸው ተመለሰች:: በሚገደሉበት ቀንም ልሰናበታት ብሎ ቅዱስ እንድርያኖስ ቢመጣ ቅድስት ኤልያና ቤቷን ዘግታ ገሠጸችው:: እርሷ ክዶ የመጣ መስሏት ነበር:: እርሱ ግን የሚስቱን የእምነት ጥንካሬ ተረዳ:: ቅዱሱና 24ቱ ቅዱሳን ለቀናት ብዙ መከራን እየተቀበሉ ሰነበቱ:: አካላቸውን እየቆራረጡ: ደማቸውን እያፈሰሱ ሆዳቸውንም እየቀደዱ መከራን አጸኑባቸው:: በመጨረሻው በዚህች ቀን ሲገደሉ ቅድስት ኤልያና "የእኔን ባል አስቀድሙት" አለች:: (የሌሎቹን አይቶ እንዳይደነግጥ ነው) እንዳለችውም የእርሱንና የባልንጀሮቹን ጭን ጭናቸውን እየሰበሩ ገድለዋቸዋል:: ቅድስት ኤልያናንም መሣፍንቱ "ካላገባንሽ" እያሉ ሲያስቸግሯት ተሰዳ ሒዳ ከሰማዕታቱ መቃብር ላይ አለቀሰች:: ጌታም ጠርቷት እዚያው ዐረፈች:: ††† ታላቁ አባ ቢጻርዮን ††† ታላቁ ገዳማዊ ሰው የመጀመሪያ መነኮሳት ከሚባሉ አባቶች አንዱ ሲሆን ዓለምን ንቆ ከመነነ በሁዋላ ከአባ #እንጦንስ ዘንድ መንኩሷል:: ከእርሳቸው ዘንድ በረድእነት ለብዙ ዓመታት አገልግሏል:: አገልግሎቱን በፈጸመ ጊዜም አስኬማን ተቀብሎ ወደ በርሃ ወጥቷል:: ምንም የራሱን ገዳም ባይመሠርትም በ4ኛው መቶ ክ/ዘ የምናኔ ሕይወት እንዲስፋፋ ካደረጉ አበው እርሱ ዋነኛው ነው:: በተጋድሎ ዘመኑም የሚታወቅባቸው ነገሮች አሉ:: ከእነሱም ጥቂት እንጠቅሳለን:: አባ ቢጻርዮን:- 1.ጾሙም ሆነ ጸሎቱ በ40 ቀናት የተወሰነ ነበር:: ጾምን ከጀመረ ያለ 40 ቀን እህል አይቀምስም:: ለጸሎት ከቆመም የሚቀመጠው ከ40 ቀናት በሁዋላ ነው:: 2.ሁሌም በየበርሃው እየዞረ ያለቅሳል:: "ምነው" ሲሉት "ወገኖቼ አለቁብኝ: ደሃም ሆንኩ" ይላቸው ነበር:: እንዲህ የሚለው አጋንንት ብዙ ነፍሳትን እየነጠቁ ሲወስዱ ስለሚመለከት ነው:: 3.በየገዳማቱ እየለመነ ለነዳያን ያከፋፍል ነበር:: 4.ሐፍረቱን ከሚሸፍን ጨርቅ በቀር ምንም ልብስ አይለብስም ነበር:: 5.ውዳሴ ከንቱን አምርሮ ይጠላ ነበር:: 6.በባሕር ላይ ተራምዶ ሲሔድና እግሮቹ ሳይርሱ ሲቀሩ አበው ተመልክተዋል:: 7.መርዝነት ያለውን ውሃም ጣፋጭ አድርጐታል:: ††† ቅዱሱ ድውያንን ፈውሶ: አጋንንትን ከአካባቢው አሳዶ: ብዙ ፍሬ አፍርቶ: ገዳም ውስጥ በገባ በ57 ዓመቱ በመልካም ሽምግልና ዐርፏል:: ††† ቸር አምላክ በክብረ ቅዱሳን ይከልለን:: ከበረከታቸውም ያብዛልን:: ††† ነሐሴ 25 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ እንድርያኖስ ሰማዕት 2."24ቱ" ሰማዕታት (ማሕበሩ) 3.ቅድስት ኤልያና (ሚስቱ) 4.ታላቁ አባ ቢጻርዮን ገዳማዊ 5.ቅዱስ ኤልያኖስና እህቱ አውዶክስያ (ሰማዕታት) ††† ወርሐዊ በዓላት 1.ቅዱስ መርቆሬዎስ ሰማዕት 2.ቅድስት ቴክላ ሐዋርያዊት 3.ቅዱስ አበከረዙን ሰማዕት 4.ቅዱስ ዱማድዮስ ሶርያዊ 5.አቡነ አቢብ (አባ ቡላ) 6.ቅዱስ አባ አቡፋና ጻድቅ ††† "ነገር ግን የሆነው ሁሉ በክርስቶስ ከራሱ ጋር ካስታረቀን: የማስታረቅም አገልግሎት ከሰጠን ከእግዚአብሔር ነው:: #እግዚአብሔር በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከእርሱ ጋር ያስታርቅ ነበርና: በደላቸውን አይቆጥርባቸውም ነበር:: በእኛም የማስታረቅ ቃል አኖረ:: እንግዲህ እግዚአብሔር በእኛ እንደሚማለድ ስለ ክርስቶስ መልእክተኞች ነን:: ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ብለን ስለ ክርስቶስ እንለምናለን::" ††† (2ቆሮ. 5:18) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

+" ቅዱስ ቶማስ "*ከልጅነቱ ቅዱሳት መጻሕፍትን የተማረ *ገና በወጣትነቱ መንኖ ገዳም የኖረ *መ ርዓስ በምትባል ሃገር ዽዽስና ተሹሞ በእረኝነት ያገለገለ *በሐዋርያዊ አገልግሎት ብዙ አሕዛብን ወደ ክርስትና የመለሰ *በዘመነ ሰማዕታት ብዙ መከራን የተቀበለ አባት ነው:: +ጨካኞቹ ቅዱሱን ለ22 ዓመታት አካሉን እየቆራረጡ ለጣዖታቸው ያጥኑ ስለ ነበር 2 እግሮቹ: 2 እጆቹ: 2 ጀሮዎቹ: 2 አፍንጫዎቹ: 2 ዐይኖቹ: ሁሉ አልነበሩም:: ነገር ግን እንዲህም ሆኖ አልሞተም ነበር:: +በመጨረሻም በዘመነ መናፍቃን አርዮስን ካወገዙት 318ቱ ሊቃውንት እንዳንዱ ተቆጥሯል:: ቅዱስ ቶማስ ዽዽስና በተሾመ በ40 ዓመቱ በዚህች ቀን ዐርፏል:: የጻድቃንን: የሰማዕታትን: የሐዋርያትንና ሊቃውንትን አክሊልም ተቀብሏል:: ††† የጻድቁ አባታችን ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት የቅድስናና የክብር ስሞች ††† 1.ተክለ አብ: ተክለ ወልድ: ተክለ መንፈስ ቅዱስ 2.ፍስሐ ፅዮን 3.ሐዲስ ሐዋርያ 4.መምሕረ ትሩፋት 5.ካህነ ሠማይ 6.ምድራዊ መልዐክ 7.እለ ስድስቱ ክነፊሁ (ባለ ስድስት ክንፍ) 8.ጻድቅ ገዳማዊ 9.ትሩፈ ምግባር 10.ሰማዕት 11.የኢትዮዽያ መነኮሳት አለቃ 12.ፀሐይ ዘበፀጋ 13.የኢትዮዽያ ብርሃኑዋ 14.ብእሴ እግዚአብሔር (የእግዚአብሔር ሰው) 15.መናኒ 16.ኤዺስ ቆዾስ (እጨጌ) ††† እነዚህ የአባታችን ስሞች እንደዘመኑ ሰው ለመሞጋገስ የወጡ ሳይሆኑ ሁሉም በትክክል ሥራዎቹንና ለቤተ ክርስቲያን የሆነላትን የሚያዘክሩ ናቸው:: ††† =>አምላከ ቅዱሳን በወዳጆቹ ምልጃ ክብራቸውን ያድለን:: በረከታቸውም በዝቶ ይደርብን:: =>ነሐሴ 24 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት= 1.ቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት (መምሕረ ትሩፋት) 2.ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ (ጻድቅት) 3.ቅዱስ ቶማስ ዘመርዐስ 4.አበው አብርሃም: ይስሐቅና ያዕቆብ =>ወርኀዊ በዓላት 1.አቡነ ዘዮሐንስ ጻድቅ ዘክብራን 2.ቅዱስ አጋቢጦስ (ጻድቅ ኤዺስቆዾስ) 3.ቅዱስ አብላርዮስ ታላቁ 4."24ቱ" ካኅናተ ሰማይ (ሱራፌል) 5.ቅዱስ አባ ሙሴ ጸሊም =>††† ነቢይን በነቢይ ስም የሚቀበል የነቢይን ዋጋ ይወስዳል:: ጻድቅን በጻድቅ ስም የሚቀበል የጻድቁን ዋጋ ይወስዳል:: ††† (ማቴ.10:40) <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>

: ✝️††† እንኩዋን ለታላላቁ ቅዱሳን አቡነ ተክለ ሃይማኖት: ቅድስት ክርስቶስ ሠምራና ቅዱስ ቶማስ ዘመርዓስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✝††† ††† ✝ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ሐዋርያዊ ††† *ልደት* =>መልካም ዛፍ መልካም ፍሬን ያፈራልና ተክለ ሃይማኖትን የወለዱት ደጋጉ: ጸጋ ዘአብ ካህኑና እግዚእ ኃረያ ናቸው:: እርሱ በክህነቱ: እርሷ በደግነቷ: በምጽዋቷ ጸንተው ቢኖሩ እግዚአብሔር ጣፋጭ ፍሬን ሰጥቷቸዋል:: +በዳሞቱ ገዢ በሞተለሚ አደጋ ቢደርስባቸው ቅዱስ ሚካኤል: ጸጋ ዘአብን ከሞት: እግዚእ ኃረያን ከትድምርተ አረሚ (ከአረማዊ ጋብቻ) አድኗቸዋል:: በሁዋላም የቅዱሱን መወለድ አብስሯቸዋል:: +ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የጸነሱት መጋቢት 24 ቀን በ1206 ዓ/ም ሲሆን የተወለዱት ደግሞ ታሕሳስ24 ቀን በ1207 ዓ/ም ነው:: በተወለዱበት ቀንም ብዙ ተአምራት ተገልጸዋል:: ቤታቸውም በበረከት ሞልቷል:: *ዕድገት* =>የጻድቁ የመጀመሪያ ስማቸው "ፍሥሃ ጽዮን" ይሰኛል:: ይሕንን ስም ይዘው: አባታቸው ጸጋ ዘአብን ተከትለው አድገዋል:: በተለይ ቅዱሳት መጻሕፍትን (ብሉያት: ሐዲሳትን) ተምረዋል:: በሥጋዊው ጐዳናም ብርቱ አዳኝ እንደ ነበሩ ይነገራል:: ዲቁናም ከወቅቱ ዻዻስ አባ ጌርሎስ ተቀብለዋል:: *መጠራት* =>አንድ ቀን ፍሥሃ ጽዮስ ለአደን ወጥቶ ሲያነጣጥር ድንገት ከሰማይ አስደንጋጭ ድምጽ ተሰማ:: የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አእላፍ መላእክት እያመሰገኑ በሚካኤል ክንፍ ተቀምጦ ወረደ:: +የወጣቱን አዳኝ ፍርሃቱን አርቆ ጌታችን ተናገረ:: "ከዛሬ ጀምሮ ስምህ ተክለ ሃይማኖት (ተክለ ሥላሴ) ይሁን:: ከዚህ በሁዋላ አራዊትን ሳይሆን ነፍሳትን ታድናለህ:: ዘወትር ካንተ ጋር ነኝ" ብሎ በግርማ ዐረገ:: ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ከዚህ ጊዜ በሁዋላ ሰዓትን አላጠፉም:: ንብረታቸውን ለነዳያን በትነው በትር ብቻ ይዘው ቤታቸው እንደ ተከፈተ ወደ ምናኔ ወጡ:: *አገልግሎት* =>ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ከዻዻሱ ቅስና ተቀብለው የወንጌል አገልግሎትን ጀመሩ:: በመጀመሪያ ስብከታቸው እዚያው ሽዋ (ጽላልሽ) አካባቢ ብቻ በ10ሺ የሚቆጠሩ ሰዎችን አሳምነው አጠመቁ:: ያን ጊዜ ኢትዮዽያ 2 መልክ ነበራት:: +1ኛ ዮዲት (ጉዲት) በፈጠረችው ጣጣና በእስላሞች ተጽዕኖ ወደ ደቡብ አካባቢ ያለው ነዋሪ አንድም ሃይማኖቱን ክዷል: ወይም በባዕድ አምልኮ ተጠምዷል:: +2ኛው ደግሞ በዛግዌ ነገሥታት ጥረት ክርስትናና ምናኔ ተነቃቅቶ ነበር:: +ግማሹ ሃገር በጨለመበት ወቅት የደረሱት ሐዲስ ሐዋርያ አባ ተክለ ሃይማኖት በወጣት ጉልበታቸውና በኃይለ መንፈስ ቅዱስ ብዙ ቦታዎችን አደረሱ:: ሕዝቡን: መሣፍንቱን ወደ ሃይማኖት መልሰው: ማርያኖችን (ጠንቁዋዮችን) አጥፍተዋል:: *ገዳማዊ ሕይወት* =>ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት በወንጌል ብርሃን ኢትዮዽያን ከማብራታቸው ባለፈ ገዳማዊ ሕይወትንም አስፋፍተዋል:: እርሳቸው ከሁሉ የተሻሉ ሳሉም በ3 ገዳማት በረድዕነት አገልግለዋል:: +እነዚህም በአቡነ በጸሎተ ሚካኤል ገዳም ለ12 ዓመታት: በአቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ ገዳም ለ7 ዓመታት: በደብረ ዳሞ ከአቡነ ዮሐኒ ጋር ለ7 ዓመታት: በአጠቃላይ ለ26 ዓመታት አገልግለዋል:: +በአቡነ ኢየሱስ ሞዐ ከመነኮሱ በሁዋላም ወደ ምድረ ሽዋ (ዞረሬ) ተመልሰው በአንዲት በዓት ውስጥ ለ22 ዓመታት ቆመው ጸልየዋል:: በተሰበረ እግራቸውም 6 ጦሮችን በግራና በቀኝ ተክለው ለ7 ዓመታት ጸልየዋል:: *ስድስት ክንፍ* =>ኢትዮዽያዊው ጻድቅና ሐዋርያ ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ከኢትዮዽያ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዘው ከቅዱሳት መካናት ተባርከዋል:: ጻድቁ ምድረ እሥራኤል የገቡት በየመንገዱ መንፈሳዊ ዘርን እየዘሩ: እያስተማሩና እያሳመኑ ነበር:: +የወቅቱ ሊቀ ዻዻሳት አባ ሚካኤል ጋርም ተገናኝተው ቡራኬን ተሰጣጥተዋል:: ዋናው ጉዳይ ግን ከዚህ በሁዋላ ነው:: ጻድቁ እመቤታችንና ጌታችን ከጽንሰታቸው እስከ ዕርገታቸው የረገጧቸውን ቦታዎች ሲመለከቱ በፍጹም ተደሞ እንባቸው ይፈስ ነበር:: +ምክንያቱም እግዚአብሔር ስላበቃቸው ተክለ ሃይማኖት የሚያዩት ቦታውን አልነበረም:: በገሃድ:- -በቤተ መቅደስ ብስራቱን -በቤተ ልሔም ልደቱን -በቤተ ዮሴፍ ግዝረቱን -በፈለገ ዮርዳኖስ ጥምቀቱን -በቤተ አልዓዛር ተአምራቱን ይመለከቱ ነበር:: +የጉብኝታቸው የመጨረሻ ክፍል ወደ ሆነው ቀራንዮ ደርሰው ጌታቸውን እንደ ተሰቀለ ሆኖ ቢመለከቱት ከዓይናቸው ይፈስ የነበረው ቁጡ እንባ መልኩን ቀየረና ዓይናቸው ጠፋ:: በዚያች ቅጽበት ስም አጠራሯ የከበረ እመቤታችን ድንግል ማርያም ፈጥና ደርሳ ተክልየን ወደ ሰማይ አሳረገቻቸው:: +በዚያም:- -የብርሃን ዐይን ተቀብለው -6 ክንፍ አብቅለው -የወርቅ ካባ ላንቃ ለብሰው -ማዕጠንተ ወርቁን ይዘው -ከ24ቱ ካህናተ ሰማይም ተደምረው -ሥላሴን በአንድነቱና ሦስትነቱ ተመልክተው -"ስብሐት ወክብር ለሥሉስ ቅዱስ ይደሉ" ብለው መንበረ ጸባኦትን አጥነው ወደ መሬት ተመልሰዋል:: *ተአምራት* =>የተክልየ ተአምራት እንደ ሰማይ ከዋክብት የበዛ ነው:: *ሙት አንስተዋል *ድውያንን ፈውሰዋል *አጋንንትን አሳደዋል *እሳትን ጨብጠዋል *በክንፍ በረዋል *ደመናን ዙፋን አድርገዋል:: +ብዙ ደቀ መዛሙርትን አፍርተው ደብረ ሊባኖስን መሥርተዋል:: በዚያም ሴትና ወንድ መነኮሳት እንደ ሕጻናት አብረው ኑረዋል:: በዘመናቸው ሰይጣን ታሥሯልና:: *ዕረፍት* =>ጻድቅ: ሰማዕትና ሐዋርያ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ብርሃን ሆነው መከራን በብዙ ተቀብለው: እልፍ አእላፍ ፍሬን አፍርተው: በተወለዱ በ99 ዓመት: ከ8 ወር: ከ1 ቀናቸው ነሐሴ 24 ቀን በ1306 ዓ/ም ዐርፈዋል:: ጌታ: ድንግል ማርያምና ቅዱሳን ከሰማይ ወርደው ተቀብለዋቸዋል:: 10 ትውልድ የሚያስምር ቃል ኪዳንም ተቀብለዋል:: ††† ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ††† =>እጅግ የከበረችና የተመሰገነች እናታችን ቅድስት ክርስቶስ ሠምራን እናመሰግናታለን:: እርሷ በሁሉ ጐዳና ፍጹምነትን ያሳየች ኢትዮዽያዊት እናት ናት:: ገና ከልጅነት የነበራት የትሕትናና የመታዘዝ ሕይወት እጅግ ልዩ ነበር:: እናታችን ቅድስናን ያገኘችው ገና በትዳር ውስጥ እያለች ነው:: +ከተባረከ ትዳሯ 12 ልጆችን አፍርታ: ምጽዋትን የዕለት ተግባሯ አድርጋ ኑራለች:: በዚህ ደግነቷም ሙት እስከ ማንሳት ደርሳለች:: አብያተ ክርስቲያናትን አንጻ አንድ ልጇን (ዳግማዊ ቂርቆስን) አዝላ ምናኔ ወጥታልች:: +በደብረ ሊባኖስ ውስጥ የቆየችው ቅድስት እናት ተጋድሎዋን የፈጸመችው ግን ጣና ሐይቅ ውስጥ ነው:: በተለይ ለ22 ዓመታት ሐይቁ ውስጥ አካሏ አልቆ: አሣ በሰውነቷ ውስጥ እስከሚያልፍ ድረስ ተጋድላለች:: በቀኝና በግራ 12 ጦሮችን ተክላም ጸልያለች:: +ብዙ ኃጥአንን አማልዳ: 12 ክንፎችን አብቅላ: ከፍ ከፍ ብላለች:: ከርሕራሔዋ ብዛት የተነሳ ሰይጣንን እንኩዋ ለማስታረቅ ሞክራለች:: ጌታም ከሲዖል ነፍሳትን እንድታወጣ ፈቅዶላታል:: ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ያረፈችው በዚህ ዕለት ሲሆን አጽሟ ዛሬ በራሷ ገዳም (ጣና ዳር) ይገኛል:: +" ቅዱስ ቶማስ ዘመርዓስ "+ =>ቅዱስ ቶማስ "መርዓስ" በምትባል ሃገር የፈለቀ የንጋት ኮከብ: ጻድቅ: ገዳማዊ: ዻዻስ: ሐዋርያ: ሰማዕትና ሊቅ ነው:: የዚህን ቅዱስ ተጋድሎ እንደ እኔ ያለው ሰው አይቻለውም:: የእርሱ ሕይወት ክርስትና ምን እንደ ሆነ ያሳያል::

††† እንኳን ለሰላሳ ሺ ግብጻውያን ሰማዕታት ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ሠለስቱ እልፍ ሰማዕታት ††† ††† ዘመነ ሰማዕታት አርባ ሰባት ሚሊየን ክርስቲያኖችን በአርባ ዓመታት ከበላ በኋላ በ305 (312) ዓ/ም ቢጠናቀቅም ስለ ሃይማኖት መሞት ግን እስከ ምጽዓት ድረስ ይቀጥላል:: ለእያንዳንዱ ክርስቲያን ከሚቀርቡ ፈተናዎች ሁሉ እጅግ ከባዱ ይሔው ሰማዕትነት ነውና ሊቀበለው ያለው (ያደለው) ይቀበለዋል:: ቤተ ክርስቲያን በባሕር ላይ ያለች መርከብ ናትና ዘወትር በፈተና ውስጥ መኖሯ የሚጠበቅ ነው:: ዘመነ ሰማዕታትን ተከትሎ የመጣው የመናፍቃን ዘመን ሲሆን ለመቶ ሃምሳ ዓመታት ያህል መናፍቃን እንደ አሸን ፈልተዋል:: በዚያው ልክ ከዋክብት ቅዱሳን ሊቃውንት ነበሩና በየጊዜው ጉባኤያትን እየሠሩ: መናፍቃንን አሳፍረዋል:: ምዕመናንንም አጽንተዋል:: በ451 ዓ/ም የተፈጸመው ድርጊት ግን ዛሬም ድረስ ጠባሳው የሚለቅ አልሃነም:: ንጉሡ መርቅያንና ጳጳሱ ልዮን የንስጥሮስን ትምሕርት አለባብሰው ሊያስተምሩ ሲሞክሩ ግጭት በመፈጠሩ ቤተ ክርስቲያን ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሁለት ተከፈለች:: በጉባኤው የነበሩ ስድስት መቶ ሰላሳ ስድስት ጳጳሳት ስቃይና ሞትን ፈርተው በኑፋቄ መጽሐፍ ላይ በመፈረማቸው "መለካውያን" (ከእግዚአብሔር ይልቅ ለንጉሥ የሚታዘዙ) ተባሉ:: ጉባኤውም "ጉባኤ ከለባት" (የውሾች ስብሰባ): "ጉባኤ አብዳን" (የሰነፎች ጉባኤ) ተብሏል:: የወቅቱ የእስክንድርያ ፓትርያርክ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ግን "በኑፋቄው ላይ አልፈርምም::" ከማለቱ አልፎ መናፍቃኑን አወገዛቸው:: በዚህ ምክንያት ጽሕሙን ነጭተው: ጥርሱንም አርግፈው: ወደ ጋግራ ደሴት ከሰባት ደቀ መዛሙርቱ ጋር አሳደዱት:: በዚያም ለሦስት ዓመታት ቆይቶ በ454 ዓ/ም ዐረፈ:: እግዚአብሔር ፈርዶባቸው ንጉሡ መርቅያን እና ንግሥቲቱ ብርክልያ (ክፉ ሴት ናት) ድንገት ሞቱ:: ፈተናው ግን በዚህ አላበቃም:: በዙፋኑ የተተካው ሌላኛው ጨካኝ ልዮን ነበር:: መንፈሳዊውን አርበኛ አባ ዲዮስቆሮስን በሞት ያጡት የግብጽ ክርስቲያኖች ደቀ መዝሙሩን "አባ ጢሞቴዎስን እንሾማለን::" ቢሉ ንጉሡ ከለከለ:: የሚሾመው መለካዊ ነው ብሎ አብሩታርዮስ የሚባል መናፍቅ ጳጳስ በላያቸው ላይ ሾመባቸው:: ይህንን መታገስ ለሕዝቡና ለካህናቱ ከባድ ነበር:: ተኩላ እንኳን በበጐች ላይ በይፋ ተሹሞ: ተደብቆም ቢሆን እየነጠቀ መብላት ልማዱ ነው:: መናፍቁ ጳጳስ በተለያየ መንገድ ሕዝቡን ለመሳብ ሞክሮ ነበር:: ለምሳሌ አውጣኪን (የክርስቶስን ሰው መሆን ምትሐት የሚል 'የቱሳሔ' አስተማሪ መናፍቅ ነው::) አወገዘው:: እነሱ ግን ተረድተውታልና ቦታ አልሰጡትም:: ምክንያቱም አውጣኪ ከቀድሞም የተወገዘ መናፍቅ ነውና:: የሚገርመው ከሕዝቡ አንድስ እንኳ ከመናፍቁ ጳጳስ የሚባረክ አልነበረም:: ሥጋውን ደሙንም ከእውነተኛ ካህናት በድብቅ ይቀበሉ ነበር:: አንድ ቀን ግን መናፍቁ ጳጳስ አብሩታርዮስ ተገድሎ ተገኘ:: (መልአክ ቀሥፎት ነው የሚሉ አሉ:: እስካሁን ድረስ የገዳዩ ማንነት አልታወቀም::) ግብጻውያን ክርስቲያኖች ግን የእርሱን ሞት ሲሰሙ ደጉን እረኛ አባ ጢሞቴዎስን ሾሙ:: ችግሩ የመጣው ከዚህ በኋላ ነው:: የመናፍቁ ተከታዮች ለንጉሡ ልዮን "አንተን ንቀው: የሾምከውን ገደሉ:: ሌላ ጳጳስም ሾሙ::" ብለው መልዕክት ላኩለት:: በዚህ የተበሳጨው ልዮን ኦርቶዶክሳውያንን ባገኛችሁበት ሁሉ ግደሉ የሚል አዋጅ አወጣ:: ይህን አዋጅ ተከትሎ ሰላሳ ሺ ሰዎች በእስክንድርያ ከተማ ተጨፈጨፉ:: ገዳዮቹ ወንድ: ሴት: ሕፃን: ሽማግሌ ሳይመርጡ የክርስቲያኖችን ደም አፈሰሱ:: ለሦስት ቀናትም ግድያው ቀጥሎ እንደ ነበር ይነገራል:: ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት "ወኀጥኡ ዘይቀብሮሙ" እንዳለ ቀባሪም አጡ:: ገዳዮቹ ቀጥለውም አባ ጢሞቴዎስን አስረው አጋዙት:: ለአሥር ዓመታትም አሰቃዩት:: ከእነዚህ ዓመታት በኋላ ግን ንጉሡ ተጸጽቶ አባ ጢሞቴዎስን ወደ መንበሩ መልሶታል:: ወገኖቻችን የግብጽ ክርስቲያኖች እንኳን ያኔ ዛሬም በጽናታቸው አብነት ልናርጋቸው የሚገቡ ናቸው:: ††† አምላከ ሰማዕታት በቸርነቱ ይጠብቀን:: ከበረከታቸውም ያድለን:: ††† ነሐሴ 23 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ሰላሳ ሺ የእስክንድርያ (ግብጽ) ሰማዕታት 2.ቅዱስ ድምያኖስ ሰማዕት ††† ወርኀዊ በዓላት 1.ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት 2.ቅዱስ ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት 3.ነቢየ ጽድቅ ቅዱስ ሰሎሞን (ንጉሠ እሥራኤል) 4.አባ ጢሞቴዎስ ገዳማዊ 5.ቅዱስ ዳንኤል ነቢይ 6.አባ ሳሙኤል 7.አባ ስምዖን 8.አባ ገብርኤል ††† "በጐንም ለማድረግ ብትቀኑ የሚያስጨንቃችሁ ማን ነው? ነገር ግን ስለ ጽድቅ እንኳ መከራን ብትቀበሉ ብጹዓን ናችሁ:: ማስፈራራታቸውንም አትፍሩ: አትናወጡም:: ዳሩ ግን ጌታን እርሱም ክርስቶስን በልባችሁ ቀድሱት:: በእናንተ ስላለ ተስፋ ምክንያትን ለሚጠይቋችሁ ሁሉ መልስ ለመስጠት ዘወትር የተዘጋጃችሁ ሁኑ:: ነገር ግን በየውሃነትና በፍርሃት ይሁን::" ††† (፩ጴጥ. ፫፥፲፫-፲፮) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

††† እንኳን ለታላቁ ነቢይ ቅዱስ ሚክያስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† †††በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ቅዱስ ሚክያስ ነቢይ ††† ††† ነቢይ ማለት በቁሙ ኃላፍያትን (አልፎ የተሠወረውን ምሥጢር): መጻዕያትን (ገና ለወደ ፊት የሚሆነውን) የሚያውቅ ሰው ማለት ነው:: ሃብተ ትንቢት የእግዚአብሔር የባሕርይ ገንዘቡ ሲሆን እርሱ ለወደደው ደግሞ በጸጋ ይሰጠዋል:: እነዚህም ከጌታ ሃብተ ትንቢት የተሰጣቸው አባቶችና እናቶች "ቅዱሳን ነቢያት" በመባል ይታወቃሉ:: ዘመነ ነቢያት ተብሎ የሚታወቀው ብሉይ ኪዳን ቢሆንም እስከ ምጽዓት ድረስ ጸጋውን እግዚአብሔር ለፈቀደላቸው አይነሳቸውም:: በሐዋርያት መካከልም ቅዱስ አጋቦስን የመሰሉ ነቢያት ነበሩ:: (ሐዋ. 11:27) ቅዱሳን ነቢያት ከእግዚአብሔር እየተላኩ ሰውን ከፈጣሪው እንዲታረቅ ይመክራሉ: ይገስጻሉ:: ከበጐ ሃይማኖታቸውና ንጽሕናቸው የተነሳም እግዚአብሔርን በተለያየ አርአያና አምሳል አይተውታል:: "እስመ በአንጽሖ መንፈስ ርዕይዎ ነቢያት ለእግዚአብሔር: ወተናጸሩ ገጸ በገጽ" እንዳለ አባ ሕርያቆስ:: (ቅዳሴ ማርያም) የብዙ ነቢያት ፍጻሜአቸው መከራን መቀበል ነው:: እውነትን ስለ ተናገሩ: አንዳንዶቹም በእሳት: አንዳንዶቹም በሰይፍ: አንዳንዶቹም በመጋዝ ተፈትነዋል:: ሌሎቹ ለአናብስት ሲጣሉ ቀሪዎቹ ደግሞ በድንጋይ ተወግረዋል:: ስለዚህም መከራቸው ለቤተ ክርስቲያን መሠረት ተብለዋል:: ጌታም ለደቀ መዛሙርቱ "ሌሎች ደከሙ: እናንተ በድካማቸው ገባችሁ::" ብሎ የነቢያቱን መከራ ተናግሯል:: (ዮሐ. 4:36) ነቢያት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እና ድንግል እናቱን ለማየት ብዙ ጥረዋል: ሽተዋልም:: "ብዙ ነቢያትና ጻድቃን እናንተ የምታዩትን ሊያዩ ሹ::" እንዳለ ጌታ በወንጌል:: (ማቴ. 13:16, 1ጴጥ. 1:10) ዛሬ ግን በሰማያት ጸጋ በዝቶላቸው: ክብር ተሰጥቷቸው ሐሴትን ያደርጋሉ:: ††† ቅዱሳን ነቢያት በዋነኝነት ¤አሥራ አምስቱ አበው ነቢያት: ¤አራቱ ዐበይት ነቢያት: ¤አሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያትና ¤ካልአን ነቢያት ተብለው በአራት ይከፈላሉ:: ††† አሥራ አምስቱ አበው ነቢያት ማለት:- *ቅዱስ አዳም አባታችን *ሴት *ሔኖስ *ቃይናን *መላልኤል *ያሬድ *ኄኖክ *ማቱሳላ *ላሜሕ *ኖኅ *አብርሃም *ይስሐቅ *ያዕቆብ *ሙሴና *ሳሙኤል ናቸው:: ††† አራቱ ዐበይት ነቢያት *ቅዱስ ኢሳይያስ ልዑለ ቃል *ቅዱስ ኤርምያስ *ቅዱስ ሕዝቅኤልና *ቅዱስ ዳንኤል ናቸው:: ††† አሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት *ቅዱስ ሆሴዕ *አሞጽ *ሚክያስ *ዮናስ *ናሆም *አብድዩ *ሶፎንያስ *ሐጌ *ኢዩኤል *ዕንባቆም *ዘካርያስና *ሚልክያስ ናቸው:: ††† ካልአን ነቢያት ደግሞ:- *እነ ኢያሱ *ሶምሶን *ዮፍታሔ *ጌዴዎን *ዳዊት *ሰሎሞን *ኤልያስና *ኤልሳዕ . . . ሌሎችም ናቸው:: ††† ነቢያት በከተማም ይከፈላሉ:: *የይሁዳ (ኢየሩሳሌም): *የሰማርያ (እሥራኤል)ና *የባቢሎን (በምርኮ ጊዜ) ተብለው ይጠራሉ:: ††† በዘመን አከፋፈል ደግሞ:- *ከአዳም እስከ ዮሴፍ (የዘመነ አበው ነቢያት): *ከሊቀ ነቢያት ሙሴ እስከ ነቢዩ ሳሙኤል (የዘመነ መሳፍንት ነቢያት) *ከቅዱስ ዳዊት እስከ ዘሩባቤል ያሉት (የዘመነ ነገሥት ነቢያት) *ከዘሩባቤል ዕረፍት እስከ መጥምቁ ዮሐንስ ያሉት ደግሞ (የዘመነ ካህናት ነቢያት) ይባላሉ:: ††† ስለ ቅዱሳን ነቢያት በጥቂቱ ይህንን ካልን ወደ ዕለቱ በዓል እንመለስ:: ቅዱስ ሚክያስ ቁጥሩ ከአሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት ሲሆን ዘመነ ትንቢቱም ቅ.ል. ክርስቶስ በ800 ዓ/ዓ አካባቢ ነው:: "ደቂቀ ነቢያት" ማለት በጥሬው "የነቢያት ልጆች" ማለት ነው:: አንድም የጻፏቸው ትንቢቶች ሲበዙ አሥራ አራት ምዕራፍ: ሲያንስ አንድ ምዕራፍ ያላቸው ናቸውና ደቂቅ ይላቸዋል:: ሚክያስ አባቱ ሞራት (ሞሬት) ይባላል:: ሚክያስ ማለት "መኑ ከመ አምላክ - እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው!" ማለት ነው:: አንድም "መልአከ እግዚአብሔር" ማለት ነው:: የአባቶቻችን ሁሉ ስማቸው እግዚአብሔርን የሚሰብክ ነው:: ቅዱሱ ነቢይ ገና ልጅ እያለ መላእክት ያነጋግሩት ነበር:: በዚህ ምክንያት ከሰው አይቀርብም:: ትክ ብለው ሲያዩት በፊቱ ላይ ብርሃን ቦግ ቦግ እያለ ይታይ ነበር:: በወጣትነት ዘመኑ እግዚአብሔር ለትንቢት ሲጠራው በእሺታ ታዘዘ:: በሦስቱ ነገሥታት (በኢዮአታም: አካዝና ሕዝቅያስ) ዘመንም ትንቢቶችን ተናግሯል:: ሕዝቡን: መሣፍንቱን: ነገሥታቱን አስተምሮ ገስጿል:: አንድ ቀን በቤተ ልሔም ሲያልፍ የዳዊት ከተማ ፈት ሁና: ዳዋ በቅሎባት ቢመለከት አዘነ:: ወዲያውም ትንቢት ተናገረላት:: "ወአንቲኒ ቤተ ልሔም ምድረ ኤፍራታ: ኢትቴሐቲ እምነገሥተ ይሁዳ: እስመ እምኔኪ ይወጽዕ ንጉሥ: ዘይርዕዮሙ ለሕዝብየ እሥራኤል::" "አንቺም የኤፍራታ ምድር ቤተ ልሔም: የይሁዳ ነገሥታት ከነገሡባቸው ከተሞች ከቶ አታንሺም:: ወገኖቼን እሥራኤልን የሚጠብቃቸው ንጉሥ (መስፍን) ካንቺ ዘንድ ይወጣልና::" አለ:: ይኸውም አልቀረ ለጊዜው ከሚጠት በኋላ ደጉ ዘሩባቤል ነግሦባታል:: በፍጻሜው ግን የባሕርይ ንጉሠ ነግሥት ኢየሱስክርስቶስ ከንጽሕት ድንግል ማርያም ተወልዶባታል:: ቅዱስ ሚክያስ ወገኖቹን ሲያስተምርና ሲመራ ኑሮ: ሰባት ምዕራፎች ያሉትን ሐረገ ትንቢት ተናግሮ: በመልካም ሽምግልና: በንጉሡ ሕዝቅያስ ዘመን ዐርፏል:: ወገኖቹ ቀብረውታል:: ጌታም በክብረ ነቢያት ከልሎታል:: ††† ቸር አምላከ ነቢያት የነቢያቱን መከራ አስቦ ከመከራ: በእንባቸውም ከእንባ ይሰውረን:: ከተረፈ በረከታቸውም አያጉድለን:: ††† ነሐሴ 22 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ ሚክያስ ነቢይ ††† ወርኀዊ በዓላት 1.ቅዱስ ዑራኤል ሊቀ መላእክት 2.ቅዱስ ሉቃስ ወንጌላዊ 3.ቅዱስ ደቅስዮስ (የእመቤታችን ወዳጅ) 4.አባ እንጦንስ አበ መነኮሳት 5.አባ ጳውሊ የዋህ ††† "ምን ይዤ ወደ እግዚአብሔር ፊት ልምጣና በልዑል አምላክ ፊት ልስገድ? የሚቃጠለውን መስዋዕትና የአንዱን ዓመት ጥጃ ይዤ በፊቱ ልምጣን? እግዚአብሔርስ በሺህ አውራ በጐች: ወይስ በእልፍ የዘይት ፈሳሾች ደስ ይለዋልን? . . . ሰው ሆይ! መልካሙን ነግሮሃል:: እግዚአብሔርም ከአንተ ዘንድ የሚሻው ምንድር ነው? ፍርድን ታደርግ ዘንድ: ምሕረትንም ትወድ ዘንድ: ከአምላክህም ጋር በትሕትና ትሔድ ዘንድ አይደለምን?" ††† (ሚክ. ፮፥፮) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

†††✝️🌻 እንኳን ለቅዱሳት አንስት ኄራኒ ሰማዕት: ንግሥተ ሳባ እና ንግሥት ዕሌኒ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††✝️🌻 †††✝️🌻 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††✝️🌻 ††† ✝️🌻ቅድስት ኄራኒ ሐዋርያዊት ሰማዕት †††✝️🌻 ††† ይህቺ ቅድስት ወጣት መልክ ከደም ግባት: ምግባር ከሃይማኖት: ስም ከመልካምነት የተባበረላት ሰማዕት ናት:: #ኄራኒ ማለት "ሰላማዊት: የተወደደች" ማለት ነው:: አንድም በጥሬው "ሰላምና ፍቅር" ማለት ነው:: ቅድስት ኄራኒ በመጀመሪያው መቶ ክ/ዘመን በታናሽ እስያ የንጉሥ #ሉክያኖስ ልጅ ናት:: ከተወለደች ጀምሮ ስለ ክርስትና ሰምታ አታውቅም:: ምክንያቱም አባቷ ጣዖት አምላኪ ከመሆኑ ባለፈ ክርስቲያኖችን ይቀጣ ስለ ነበር ነው:: ልጁን ማንም እንዳያገኛት ሲል ንጉሡ ለቅድስት ኄራኒ ቤተ መንግስት ሠራላት:: ማንም እንዳይገባ በዙሪያው 12 አጥር አጠረበት:: ጣዖቶቹን እንድታጥን አገልጋዮችንም ሾመላት:: ምናልባት አጥር ሰውን ሊከለክለው ይችላል:: #እግዚአብሔር ግን እግዚአብሔር ነውና ምንም አይከለክለውም:: ጌታ ደግሞ ይህቺን ወጣት ለወንጌል አገልግሎት ይፈልጋታል:: አንድ ቀን አባቷ: ልጁ ምሑር እንድትሆንለት አለ የተባለ ሽማግሌ ፈላስፋ ቀጠረላት:: ጥበበ እግዚአብሔር ማለት ይሔ ነው:: አባቷ ይሕ ሽማግሌ ማንን እንደሚያመልክ አልተረዳም:: አረጋዊው እጅግ የተዋጣለት ክርስቲያን ነው:: ግን ማንም አያውቅበትም:: አረጋዊው ቅድስት ኄራኒን ዝም ብሎ ሊሰብካት አልወደደም:: መጀመሪያ በስነ ምግባር አነጻት:: ቀጥሎ ግን "ጌታ ሆይ! ጐዳናህን ምራት" እያለ ይጸልይላት ገባ:: ጌታችን ልመናውን ሰምቶታልና ቅድስቷ አንድ ቀን ግሩም ራዕይን አየች:: እርሷ ለማዕድ ተቀምጣ ሳለ: የምሥራቅና የምዕራብ መስኮቶቿም ተከፍተው ሳሉ: በምሥራቁ መስኮት ነጭ ርግብ በአፏ የወይራ ዝንጣፊ (ቆጽለ ዘይት) ይዛ ገባችና ማዕዷ ላይ አኑራው ሔደች:: እርሷን ተከትሎ ደግሞ ንስር በአፉ አክሊል ይዞ ገብቶ ማዕዷ ላይ ጥሎት ሔደ:: በ3ኛው ግን ቁራ: እባብ በአፉ ይዞ በምዕራቡ መስኮት ገብቶ ማዕዷ ላይ ጥሎት ወጣ:: ቅድስት ኄራኒ ያየችው ራዕይ ቢጨንቃት ሽማግሌ መምሕሯን "ተርጉምልኝ" አለችው:: እርሱም "ልጄ ሆይ! ለዘመናት ስጠብቀው የነበረ ምኞቴን ነው ጌታ ያሳየሽ:: የሕልምሽ ትርጉም እንዲህ ነው:- ነጭ ርግብ የመንፈስ ቅዱስ (የሃይማኖት) ምሳሌ ናት:: የወይራ ዝንጣፊው ደግሞ #ማሕተመ_ጥምቀት( #ሜሮን) ነው:: ቁራ የክፉ ነገሥታት ምሳሌ ሲሆን እባብ የመከራ ምሳሌ ነው:: ንስር ድል የመንሳት ምልክት ሲሆን አክሊል ደግሞ የመንግስተ ሰማያት ምሳሌ ነው:: ልጄ! ክርስቲያን ሆነሽ የሚደርስብሽን ሁሉ ጌታ አሳይቶሻል" ብሎ ተርጉሞላት ተሰናበታት:: እርሷም ወደ ምሥራቅ ዙራ ጸለየች:- "የማላውቅህ አምላክ ሆይ! ወደ እውነትህ ምራኝ" ስትል ለመነች:: በዚያች ሰዓት የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ አጽናናት:: የሚያጠምቃትም እንደሚልክላት ነገራት:: በዚያን ጊዜ አባቷ ገብቶ "ልጄ! ከመሣፍንቱ ላንዱ ልድርሽ ስለሆነ ምን ትያለሽ?" አላት:: "3 ቀን ስጠኝ" አለችውና ሰጣት:: ወደ ጣዖቶቹ ዕለቱኑ ወርዳ "ላግባ ወይስ ይቅርብኝ?" አለቻቸው:: ከቀድሞም በወርቅ የተለበጡ ድንጋዮች ናቸውና ዝም አሉ:: በሙሉ ቀጥቅጣ ሰባብራቸው ተመለሰች:: በዘመኑ #ቅዱሳን_ሐዋርያት(በተለይ እነ #ቅዱስ_ዻውሎስ) በሕይወተ ሥጋ ነበሩና ከቅዱስ ዻውሎስ ደቀ መዛሙርት አንዱ ቤቷ እንደ ተዘጋ ገባ:: ክርስትናን ከጥንቱ እስከ ተፍጻሜቱ አስተምሮ አጠመቃት:: በ3ኛው ቀን አባቷ "ምን መከርሽ?" ቢላት "የእኔ ምክር #መርዓተ_ክርስቶስ(ሰማያዊ ሙሽራ) መሆን ነው" አለችው:: አባቷ ደነገጠ:: እጅግ ስለ ተናደደ ወደ አደባባይ አውጥቶ: አስሮ መሬት ላይ ጣላትና በመቶ የሚቆጠሩ ፈረሶች እንዲረግጧት አደረገ:: በወቅቱ ሰው የሚጠብቀው የአካሏን ቁርጥራጭ ነበር:: ነገር ግን ጌታ ከእርሷ ጋር ነበርና ልብሷ እንኩዋ ጭቃ አልነካም:: አባቷ ንጉሥ ሉክያኖስና ሠራዊቱ ያዩትን ማመን አልቻሉም:: ሁሉም ድምጻቸውን ከፍ አድርገው "ከክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ የለም" አሉ:: ቅድስት ኄራኒ ምንም ሳትናገር ይህንን ሁሉ ሰው ማረከች:: ወዲያውም ንጉሡ መልእክተኛ ልኮ: የቅዱስ ዻውሎስ ደቀ መዝሙርን አስጠርቶ: ከነ ቤተሰቦቹ ተጠመቀ:: የዚህን ዓለም ክብር ንቆም ንግሥናውን ተወ:: የጸሎት ሰውም ሆነ:: የቅድስት ኄራኒ ተጋድሎ ግን ቀጠለ:: በአካባቢው የነበረ ንጉሥ መጥቶ የአባቷን መንግስት ቀማ:: እርሷንም እጅግ አሰቃያት:: እርሱ አልፎ አርማንዮስ የሚባል ንጉሥ እንዲሁ አሰቃያት:: እርሱም አለፈ:: ከእርሱ ቀጥሎ የመጣው ንጉሥ ብዙ መከራዎችን በእርሷ ላይ አደረሰ:: በጦርም ጐኗን ወግቶ ገደላት:: ከጥቂት ሰዓታት በሁዋላ ግን ልክ ከእንቅልፉ እንደሚነቃ ሰው ተነስታ ጠራችው:: በጣም ደንግጦ "አምላክሽ አምላኬ ነው" ሲል አመነ:: ከ30,000 በላይ ሠራዊቱን ይዞም ተጠመቀ:: ቅድስት ኄራኒ በቀረ ሕይወቷ በስብከተ ወንጌል እስያን አድርሳለች:: ጌታ አብርቶላት: እርሷም አብርታ: እልፍ ፍሬን አፍርታ: በዚህች ቀን ዐርፋለች:: የሐዋርያትንም: የሰማዕታትንም አክሊል ተቀዳጅታለች:: †††✝️🌻 ንግሥተ ሳባ †††✝️🌻 ††† ይሕቺ ኢትዮዽያዊት ከ3 ሺ ዘመናት በፊት የነበረች ደግ እናት ናት:: በሥጋዊ ደረጃ ከታንዛንያ እስከ #የመን ያስተዳደረች ስመ ጥር ንግሥት ስትሆን በመንፈሳዊው ደረጃ ደግሞ እግዚአብሔር የቀባውን ሰው ፍለጋ ወደ #ኢየሩሳሌም ተጉዛለች:: ከዚያውም አምልኮተ እግዚአብሔርን ከሥርዓተ ኦሪት ጋር አምጥታለች:: ድንግልናዋን ለታላቁ #ንጉሥ_ሰሎሞን ሰጥታ #ምኒልክን ወልዳለች:: ይህቺ ንግሥት በጌታችን (በፈጣሪ) አንደበትም ተመስግናለች:: (ማቴ. 12:42) በስምም " #ሳባ: #አዜብና #ማክዳ ተብላ ትታወቃለች:: ዛሬ ዕለተ ልደቷ ነው:: ††† ቅድስት ዕሌኒ ንግሥት ††† ††† ይሕቺ ቅድስት የቅዱስ #ቆስጠንጢኖስ እናቱ: የመስቀሉ ወዳጅ: የቤተ ክርስቲያን ባለውለታ የሆነች ክብርት እናት ናት:: ይህቺም ቅድስት የተወለደቺው በዚሁ ዕለት ነው:: ††† የቅዱሳት እናቶቻችን አምላክ እህት እናቶቻችንን ከክፋትም: ከጥፋትም: ይሠውርልን:: ለሃገርም: ለሃይማኖትም የሚጠቅሙ ሴቶችንም ጌታ አይንሳን:: በረከታቸውም ይደርብን:: ††† ነሐሴ 21 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ተዝካረ ፍልሠታ ለማርያም ድንግል (6ኛ ቀን) 2.ቅድስት ኄራኒ ሐዋርያዊት (ሰማዕት) 3.ቡርክት ንግሥተ ሳባ (ልደቷ) 4.ቅድስት ዕሌኒ ንግሥት (ልደቷ) ††† ወርኀዊ በዓላት 1.ቅድስት ድንግል እግዝእትነ ማርያም ወላዲተ አምላክ 2.አበው ጎርጎርዮሳት 3.አቡነ ምዕመነ ድንግል 4.አቡነ አምደ ሥላሴ 5.አባ አሮን ሶርያዊ 6.አባ መርትያኖስ ጻድቅ ††† " #ንግሥተ_አዜብ በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነስታ ትፈርድበታለች:: የሰሎሞንን ጥበብ ለመስማት ከምድር ዳር መጥታለችና:: እነሆም ከሰሎሞን የሚበልጥ ከዚህ አለ::" ††† (ማቴ. 12:42) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

††† እንኳን ለቅዱሳን 7ቱ ደቂቅ እና ለአቡነ ሰላማ ካልዕ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ቅዱሳን 7ቱ ደቂቅ ††† ††† እነዚህ 7 ቅዱሳን ከዘመነ ሰማዕታት እስከ ዘመነ ጻድቃን የተዘረጋ ታሪክ አላቸው:: 7ቱም ባልንጀሮች ሲሆኑ በ2ኛው መቶ ክ/ዘመን በኤፌሶን ተወልደው አድገዋል:: ክርስትናን ተምረውም በወጣትነታቸው የንጉሥ ጭፍሮች ሁነዋል:: የተቀጠሩትም የቤተ መንግስቱን ግምጃ ቤት ለመጠበቅ ነው:: በሥራቸውም ሆነ በጠባያቸው ደጐች ነበሩና ንጉሡ ዳኬዎስም: ሕዝቡም ይወዷቸው ነበር:: እነርሱ ግን በጉብዝና ወራት ፈጣሪን ማሰብን መርጠው በፍቅር: በጸሎትና በምጽዋት ይተጉ ነበር:: ከጥቂት ዓመታት በሁዋላ ግን ጭንቅ መከራ መጣ:: ንጉሡ ዳኬዎስ ክርስትናውን ትቶ ጣዖት አምላኪ ሆነ:: አዋጅም አስነገረ:: አዋጁም "ክርስቶስን ያልካደ: ለጣዖትም ያልሰገደ: ሃብት ንብረቱ ለዘረፋ: እጅ እግሩ ለእስር: ደረቱ ለጦር: አንገቱ ለሰይፍ: ቤቱም ለእሳት ይሰጣል" የሚል ነበር:: በዚህ ምክንያት ብዙ ክርስቲያኖች ተሰደዱ:: የበርካቶቹም ደማቸው ፈሰሰ:: #ኤፌሶን የግፍና የአመጻ ከተማ ሆነች:: የመከራ ጽዋው ጊዜውን ጠብቆ ወደ 7ቱ ወጣቶች ዘንድ ደረሰ:: ንጉሡ እነሱንም አስጠርቶ "ለጣዖት ስገዱ" አላቸው:: እነርሱ ግን የአምላካቸውን ፍቅር በዋዛ የሚቀይሩ አልነበሩምና "እንቢ" አሉት:: ንጉሡ ምንም ክፉና አውሬ ቢሆንም ይወዳቸዋል:: ሊገድላቸው አልፈለገምና አሳሰራቸው:: ከቀናት በሁዋላ አስጠርቶ ሊያታልላቸው ሞከረ:: ግን አልተሳካለትም:: በዚያ ወራት ጦርነት ይበዛ ነበርና ግዛት ለማስፋትም ቢሉ ለማስገበር ወጣ:: ከመውጣቱ በፊት ግን 7ቱን አስጠርቶ "አሁን ከእስር ፈትቻቹሃለሁ:: ከጦርነት እስክመለስ ከልባችሁ ጋር ምከሩ:: ካልሆነ ሞት ይጠብቃቹሃል" ብሏቸው ነበር የወጣው:: ቅዱሳኑ ንጉሡ እንደ ወጣ ተቀምጠው መከሩ:: ውሳኔንም አስተላለፉ:: ዓለምን ንቀው: ሃብት ንብረታቸውን መጽውተው: ትንሽ ሳንቲም ብቻም ይዘው በድብቅ ወጡ:: አንድ ወታደር (በጐች አሉት) ይከተላቸው ነበርና የት እንደ ገቡ ተመለከተ:: ቅዱሳኑ ዘወትር በመዓልትና በሌሊት በበዓታቸው ውስጥ ይተጉ ነበር:: ከእነሱም አንዱ በተራ እየወጣ ቂጣ ይገዛ ነበር:: አንድ ቀን ግን ከእነሱ አንዱ ራት ሊገዛ ሲወጣ ንጉሡ መመለሱን ሰማ:: ወደ በዓቱ ተመልሶ ለወንድሞቹ ነገራቸው:: ከዚያች ቀን በሁዋላ 7ቱም አልወጡም:: በዓታቸውን ዘግተው ሲጸልዩ ደክሟቸው ተኙ:: ከዚያች ቀን በሁዋላ ግን አልነቁም:: ያ የበጐች ባለቤት (ወታደር) ለብዙ ቀናት አለመውጣታቸውን ሲመለከት "ሙተዋል" ብሎ አዘነ:: በድብቅ ክርስቶስን ያመልከው ነበርና:: እርሱ የቅዱሳኑን ተጋድሎ በድንጋይ ሰሌዳ ላይ ጽፎ ወደ በዓታቸው ውስጥ ጣለው:: ትልቅ ድንጋይም አምጥቶ ገጠመው:: እነዚህ ቅዱሳን ተኝተዋልና አልነቁም:: ቀናት: ወራት: ዓመታት ተዋልደው ለ372 ዓመት ተኙ:: አንድ ቀን አንድ እረኛ ለሥራ ፈልጐት ድንጋዩን ፈነቀለው:: በዚህ ጊዜ ቅዱሳኑ ነቁ:: በወቅቱ መልካቸው የወጣት ነው:: እድሜአቸው ግን 400 ሊሞላ ትንሽ ቀርቶት ነበር:: ልክ እንደ #አቤሜሌክ ብዙ መተኛታቸው አልታወቃቸውምና ከመካከላቸው አንዱ የራት ዳቦ ሊገዛ ቢወጣ ግራ ተጋባ:: ኤፌሶን የማያውቃት ሌላ ሃገር ሆነችበት:: ከተማዋ ዘምናለች:: በየቦታው አብያተ ክርስቲያናት: ቅዱስ መስቀልም በየአደባባዩ ተተክለዋል:: ነገሩ ግር ቢለው አንዱን ከመንገድ ጠርቶ "ወንድሜ! ይህቺ ከተማ ኤፌሶን አይደለችምን?" አለው:: እርሱም "አዎ ናት" ብሎት አለፈ:: ችግሩ ግን "ራት ልግዛ" ብሎ ወደ ገበያ ሲሔድ: እርሱ የያዘው ገንዘብ የዳኬዎስ ስም የተጻፈበት መሆኑ የፈጠረው ነበር:: በነጋዴዎቹ "የተደበቀ የጥንት ገንዘብ አግኝተሃል" በሚል ተከሶም ወደ ንጉሡ #ቴዎዶስዮስ ዘንድ ቀረበ:: (ትንሹ ቴዎዶስዮስ ነው:: የነገሠውም በ5ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው) በክርክሩ መካከል ቅዱሱ የእሱንና የወንድሞቹን ነገር ሲናገር ንጉሡም: ሊቀ ዻዻሱም ( #አባ_ቴዎድሮስ ይባላል) ተገረሙ:: አብረው ከከተማ ወጥተው ሔደው: 7ቱንም ሲጸልዩ አገኟቸው:: ፊታቸውም እንደ እግረ ፀሐይ ያበራ ነበር:: 7ቱም ለ7 ቀናት በኤፌሶን ድውያንን እየፈወሱ: ሰውን ሁሉ እየባረኩ ቆዩ:: ይህ ሁሉ የተደረገው በወቅቱ "ትንሳኤ ሙታን የለም" የሚሉ መናፍቃን ተነስተው ብዙ ሰው ክዶ ነበርና ለእነሱ ምሥክር ሊሆንባቸው ነው:: በርካቶችም በዚህ ድንቅ ተስበው ወደ ሃየማኖት ተመልሰዋል:: 7ቱ ቅዱሳን ግን በ7ኛው ቀን በክብር ዐርፈዋል:: ንጉሡ በ7 የወርቅ ሣጥኖች ቀብሯቸዋል:: ††† አቡነ ሰላማ ካልዕ ††† ††† እኒህ ታላቅ ደግ ሰው የነበሩት በሃገራችን ኢትዮዽያ ከ1340 እስከ 1380 ዓ/ም ነው:: በትውልድ ግብጻዊ ቢሆኑም ለኢትዮዽያ ቤተ ክርስቲያን ብዙ ውለታን ውለዋል:: በዘመኑ ዻዻስ ሁነው ቢመጡም እንደ ሌሎቹ ዻዻሳት በቤተ መንግስት አካባቢ ሥራ ፈትተው መቀመጥን አልፈለጉም:: ወዲያው እንደ መጡ የግዕዝ ልሳንን ልቅም አድርገው ተማሩ:: ቀጥለው ኢትዮዽያውያን ሊቃውንትን ሰብስበው ቅዱሳት መጻሕፍትን ይተረጉሙ ገቡ:: አሥራው መጻሕፍትን (81ዱን) ጨምሮ ብዙ መሠረታዊ መጻሕፍትን መተርጐም ችለዋል:: ††† ይህም ሥራ አድካሚ በመሆኑ ከ30 ዓመታት በላይ ጊዜን ወስዷል:: ከተረጐሟቸው መጻሕፍትም:- * #ስንክሳር * #ግብረ_ሕማማት * #ላሃ_ማርያም * #ፊልክስዩስ(መጽሐፈ መነኮሳት) * #መጽሐፈ_ግንዘት *ድርሳን ዘቅዱስ #ያዕቆብ_ዘሥሩግ. . . ይጠቀሳሉ:: #አቡነ_ሰላማ በስብከተ ወንጌል አገልግሎታቸውና በገዳማዊ ሕይወታቸው ይታወቁ ነበር:: በተጨማሪም በየቦታው እየዞሩ ይናዝዙ: ያጠምቁም ነበር:: በወቅቱ ልክ እንደ ስማቸው ሰላም እንዲሰፍን ይተጉ ነበር:: መሣፍንቱን: ነገሥታቱን እያስታረቁ ለቤተ ክርስቲያን በአንድነት እንዲቆሙ አድርገዋል:: ጻድቁ አቡነ ፊልዾስን ጨምሮ ቅዱሳንን ገንዘውም ቀብረዋል:: በቀደመ ስማቸው #አባ_ፊቅጦር የሚባሉት ካልዕ (2ኛው) ሰላማ በ1380 ዓ/ም ከ40 ዓመታት ትጋት በሁዋላ ዐርፈዋል:: ሲጠሩም:- * #መተርጉም (መጻሕፍትን የተረጐሙ) * #ብርሃነ_አዜብ(የኢትዮዽያ ብርሃን) * #መጋቤ_ሃይማኖት ተብለው ነው:: ††† አምላከ ቅዱሳን ወዳጆቹን እንዳጸናቸው ያጽናን:: ከበረከታቸውም ያድለን:: ††† ነሐሴ 20 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ተዝካረ ፍልሠታ ለማርያም ድንግል (5ኛ ቀን) 2.ቅዱሳን 7ቱ ደቂቅ 3.አቡነ ሰላማ ካልዕ (መተርጉም) 4.ቅድስት ሔዛዊ ††† ወርኀዊ በዓላት 1.ቅዱስ ዮሐንስ ሐፂር 2.ቅዱስ አክሎግ ቀሲስ 3.ቅዱስ አፄ ካሌብ ጻድቅ (ንጉሠ ኢትዮዽያ) 4.አባ አሞንዮስ ዘሃገረ ቶና 5.ቅድስት ሳድዥ የዋሒት 6.ቅዱስ ወክቡር ማር ቴዎድሮስ ሰማዕት ††† "በተቀደሰ አሳሳም እርስ በርሳችሁ ሰላምታ ተሰጣጡ:: ቅዱሳን ሁሉ ሰላምታ ያቀርቡላቹሃል:: የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ: የእግዚአብሔርም ፍቅር: የመንፈስ ቅዱስም ኅብረት ከሁላችሁ ጋር ይሁን:: አሜን::" ††† (2ቆሮ. 13:12) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

††† እንኳን ለቅዱሳን አበው አባ መቃርስ: ቅዱስ አብርሃም እና ቅዱስ ፊንሐስ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ታላቁ ቅዱስ መቃርስ ††† ††† ታላቁ ቅዱስ መቃርስ ( #መቃሬ) "ጽድቅ እንደ መቃርስ" የተባለለት: የመነኮሳት ሁሉ አለቃ: ከ80 ዓመታት በላይ በበርሃ የኖረ: በግብፅ ትልቁን ገዳም (አስቄጥስን) የመሠረተ: ከ50,000 በላይ መነኮሳትን ይመራና ይመግብ የነበረ ፍፁም ጻድቅ ነው:: በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን አርዮሳውያን ደጉን ታላቅ አባት በሰንሰለት አስረው ከግብፅ ወደ እስያ በርሃ ከጉዋደኛው #ቅዱስ_መቃርዮስ እስክንድርያዊ ጋር አሰድደውታል:: በዚያ ለ2 ዓመታት ስቃይን ከተቀበሉ በሁዋላ በአረማውያን ፊት ድንቅ ተአምር አድርገው አረማውያንን ከነንጉሳቸው አጥምቀዋል:: በተሰደዱባት ሃገርም #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ (ስም አጠራሩ ይክበርና) #እመቤታችንን: #ቅዱሳን_ሐዋርያትን: #አዕላፍ_መላእክትን: በተለይ ደግሞ ቅዱሳኑን #ዳዊትን: #ዮሐንስ መጥምቁንና ወንጌላዊውን: #ማርቆስን: #ዼጥሮስን: #ዻውሎስን አስከትሎ ወርዶ ተገልጦላቸዋል:: በቅዱስ አንደበቱም የምሕረት ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል:: ታላቁ ቅዱስ መቃርስና መቃርዮስ ከ2 ዓመታት ስደትና መከራ በሁዋላ ስደት በወጡባት በዚችው ዕለት መልዐኩ ኪሩብ በክንፉ ተሽክሞ ወደ ግብፅ መልሷቸዋል:: በወቅቱም ጻድቁን ለመቀበል ከ50,000 በላይ የሚሆኑ ልጆቻቸው መነኮሳት በዝማሬ ወጥተዋል:: ይህች ዕለት ለአባታችን መቃሬ በዓለ ፍልሠቱ ናት:: ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ:- ታላቁ ቅዱስ መቃርስ ካረፈ በሁዋላ ከክቡር ሥጋው ብዙ ተአምራት ይታዩ ነበርና የሃገሩ (የሳስዊር) ሰዎች ሊወስዱት ፈለጉ:: #ሳስዊር ማለት ቅዱሱ ተወልዶ ያደገባት ወላጆቹ (አብርሃምና ሣራ) የኖሩባት ቦታ ናት:: የምትገኘውም ግብጽ ውስጥ ነው:: በምድረ ግብጽ: በተለይም በገዳመ #አስቄጥስ የአባ መቃርስን ያህል ክቡርና ተወዳጅ የለምና የሃገሩ ሰዎች የነበራቸው አማራጭ መስረቅ ነበር:: መሥረቅ ኃጢአት ቢሆንም እነሱ ግን ስለ ፍቅር: አንድም ለበረከት (በረከትን ሲሹ) አደረጉት:: ወደ ሳስዊርም ወስደው: ቤተ ክርስቲያን በቅዱሱ ስም አንጸው በክብር አኖሩት:: በዚያም ለመቶዎች ዓመታት ተቀመጠ:: በ7ኛው መቶ ክ/ዘመን ግን ተንባላት (እስላሞች) መጥተው ቤተ ክርስቲያኑን አጠቁ:: በዚህ ጊዜም ሕዝቡ የጻድቁን አጽም ይዘው ሸሹ:: በሌላ ቦታም እንደ ገና በስሙ #ቤተ_ክርስቲያን አንጸው በዚያ አኖሩት:: በእነዚህ ሁሉ ዓመታት የመንፈሳዊ አባታቸውን ሥጋ ያጡት የገዳመ አስቄጥስ ቅዱሳን ያዝኑ ይጸልዩ ነበርና ልመናቸውን ፈጣሪ ሰማ:: #አባ_ሚካኤል ሊቀ ዻዻሳት በነበረበት ዘመን: ከገዳሙ ለሌላ ተግባር ወደ ሳስዊር የተላኩ አበው ከታላቁ አባት ቤተ ክርስቲያን ሲደርሱ ሰውነታቸው ታወከ:: ይዘው ለመውሰድ ሙከራ ቢያደርጉ ሊሳካላቸው አልቻለም:: ምክንያቱም የቤተ ክርስቲያኑ ጠባቂ ደወል ደውሎ ሕዝቡን ሁሉ ጠርቶ ነበርና:: ሕዝቡና ሃገረ ገዢው የሆነውን ሲሰሙ "የቅዱሱን ሥጋ ብትነኩ እንገላቹሃለን" ብለው ሰይፍ: ዱላ: ጐመድና ጦር ይዘው መጡባቸው:: መነኮሳቱ ግን ባዷቸውን ሊመለሱ አልፈቀዱምና ሌሊቱን ሲያለቅሱና ሲጸልዩ አደሩ:: መንፈቀ ሌሊት በሆነ ጊዜም #ታላቁ_መቃርስ በግርማ ወርዶ መኮንኑን "ለምን ወደ ልጆቼ እንዳልሔድ ትከለክለኛለህ?" ሲል በራዕይ ተቆጣው:: በዚህ ምክንያትም መነኮሳቱ የቅዱሱን ሥጋ ተቀበሉ:: ሕዝቡም በዝማሬና በማሕኅሌት: ከብዙ እንባ ጋር ሸኟቸው:: ታላቁ መቃሬ ወደ ገዳሙ ሲደርስም ታላቅ ደስታ ተደረገ:: #ቅዱሳን ልጆቹ ከመንፈሳዊ አባታቸው ተባርከው በክብር አኑረውታል:: ይህ የተደረገው በዚህች ዕለት ነው:: ††† አባታችን ቅዱስ አብርሃም ††† ††† የሃይማኖት-የደግነት-የምጽዋት-የፍቅር አባት የሆነው #አብርሃም ደጉ በዚህች ቀን ይታሠባል:: በቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት የአብርሃም አባቱ ታራ ጣዖትን ይጠርብና ይሸጥ ነበር:: ሽጦ ገንዘብ የሚያመጣለት ደግሞ ልጁ አብርሃም ነበር:: በዚያ ወራት አብርሃም እውነተኛውን አምላክ ፍለጋ ገብቶ ነበር:: አንድ ቀን ጣዖቱን ሊሸጥ ወደ ገበያ እየሔደ የተሸከመውን እንጨት ይመራመረው ገባ:: "አሁን ይሔ ምኑ ነው አምላክ!" እያለም ያደንቅ ገባ:: መንገድ ላይም ደክሞት ካረፈበት "ለምን አልጠይቀውም" በሚል አናገረው:: "እርቦኛል አብላኝ" አለው:: መልስ የለም:: "እሺ አጠጣኝ" አለው:: አሁንም ያው ነው:: "ባይሆን እሺ አጫውተኝ" አለው:: ጣዖቱ ተራ እንጨት ነውና መልሱ ዝምታ ነበር:: ከዚያ ተነስቶ ወደ ገበያው ሲደርስ "ዐይን እያለው የማያይ: ጀሮ እያለው የማይሰማ አምላክ የሚገዛ" እያለ ይጮህ ጀመር:: ይህን ሲሰሙ አንዳንዶቹ "የታራ ልጅ አብዶ" ሲሉ ሌሎቹ ደግሞ "እሱ ያቀለለውን ማን ይገዛዋል" ብለውት ሔደዋል:: ከገበያ ሲመለስም ጣዖቱን ተመልክቶ አብርሃም እንዲህ አለ:: "አንተ ቀድሞውን በዕለተ ሠሉስ የተፈጠርክ ዕፅ ነህ" ብሎ ሰባበረው:: ወደ ቤቱ ሲመለስም ሁሉንም ጣዖታት ሠባበራቸው:: ይህ የተደረገው ከ2,000 ዓመታት በፊት በዚህች ቀን ነው:: የመንግስተ ሰማያት አበጋዝ: የእግዚአብሔር ወዳጅ አባታችን አብርሃም በመጨረሻው በውሃ: በነፋስ: በእሳትና በፀሐይ ተመራምሮ ፈጣሪውን አግኝቷል:: ††† ቅዱስ ፊንሐስ ካህን ††† ††† ካህኑ ፊንሐስ የብሉይ ኪዳን ዘመን አገልጋይ: ከነገደ #ሌዊ: የሊቀ ካህናቱ የአሮን የልጅ ልጅ ነው:: አባቱም ሊቀ ካህናቱ #አልዓዛር ነው:: ፊንሐስ #እሥራኤል ከግብጽ ሲወጡ ሕጻን የነበረ ሲሆን አድጐ በመጀመሪያ ካህን: አባቱ አልዓዛርና አያቱ #አሮን ሲያርፉ ደግሞ ሊቀ ካህንነትን ተሹሟል:: አንድ ቀን በጠንቅ-ዋዩ በበለዓም ክፉ ምክር እሥራኤላውያን ከሞዐብ ሴቶች ጋር በኃጢአት በመሳተፋቸው #እግዚአብሔር ተቆጥቶ ነበር:: ያጠፋቸው ዘንድም መቅሰፍት ተጀምሮ ሳለ ፊንሐስ ወንድና ሴት: በደብተራ ኦሪቱ አንጻር የማይገባውን ሲሠሩ አያቸው:: ለፈጣሪው ቀንቶ በአንድ ጦር ሁለቱንም በአንድ ላይ ጥሏቸዋል:: ያን ጊዜ ጌታ "አስተንፈስካ ለነፍስየ" ብሎታል:: መቅሰፍቱም ተከልክሏል:: በዚህም ምክንያት ካህኑ ፊንሐስ የ300 ዓመት ዕድሜ ተጨምሮለት: እግዚአብሔርን ሲያገለግል ኑሮ በዚህች ቀን ዐርፏል:: (ዘኁ. 25:7, መዝ. 105:30) ††† ለአበው ቅዱሳን የተለመነ አምላክ ለእኛም ይለመነን:: ክብራቸውንም በእኛ ላይ ይሳልብን:: ††† ነሐሴ 19 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ተዝካረ ፍልሠታ ለማርያም ድንግል (4ኛ ቀን) 2.ታላቁ ቅዱስ መቃርስ (ፍልሠቱ) 3.አባታችን ቅዱስ አብርሃም (ጣዖቱን የሰበረበት) 4.ቅዱስ ፊንሐስ ካህን (ወልደ አልዓዛር) ††† ወርሐዊ በዓላት 1.ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት 2.ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት 3.አቡነ ዓቢየ እግዚእ ጻድቅ 4.አቡነ ስነ ኢየሱስ 5.አቡነ ዮሴፍ ብርሃነ ዓለም ††† "እግዚአብሔርም ለአብርሃም ተስፋ በሰጠው ጊዜ:- 'በእውነት እየባረክሁ እባርክሃለሁ:: እያበዛሁም አበዛሃለሁ' ብሎ ከእርሱ በሚበልጥ በማንም ሊምል ስላልቻለ በራሱ ማለ:: እንዲሁም እርሱ ከታገሠ በሁዋላ ተስፋውን አገኘ::" ††† (ዕብ. 6:13) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞✞✞ ❖ ነሐሴ ፲፰ ❖ ✞✞✞ እንኩዋን ለሊቁ #ቅዱስ_እለእስክንድሮስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞✞✞ +"+ #ቅዱስ_እለእስክንድሮስ_ሊቅ +"+ =>ቅዱሱ ታላቅ የሃይማኖት ጠበቃ ሲሆን ሃገረ ሙላዱ (የተወለደባት) #ግብጽ ናት:: የተወለደው በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን ሲሆን በምግባሩ: በትምሕርቱ ለምዕመናን ጥቅም ሆኗቸዋል:: ቅዱስ እለእስክንድሮስ ገና ልጅ ሳለ ምሥጢረ ክርስትናን ይማር ዘንድ ወደ #ቅዱስ_ዼጥሮስ #ተፍጻሜተ_ሰማዕት ሔዷል:: +ቅዱስ ዼጥሮስ የግብጽ 17ኛ ፓትርያርክና ሊቅ ሲሆን በታሪክ የዘመነ ሰማዕታት መጨረሻ ተብሎ ይታወቃል:: ከዚህ ሰማዕት ሥር የሚማሩ ብዙ አርድእት ቢኖሩም 3ቱ ግን ተጠቃሽ ነበሩ:: 1.ቅዱስ እለእስክንድሮስ (ደጉ) 2.አኪላስ (ውዳሴ ከንቱ ወዳጅ) 3.አርዮስ (የቤተ ክርስቲያን ጠላት) +ከእነዚህም አርዮስ ቤተ ክርስቲያንን ለማጥፋት ሲታትር ነበር:: አኪላስ ደግሞ ሆዱ ዘመዱ: ስለ ምንም የማይጨንቀው ሰው ነበር:: ቅዱስ እለእስክንድሮስ ግን በጾምና በጸሎት እየተጋ መምሕሩን ቅዱስ ዼጥሮስን ለመተካት (ለመምሰል) ይጥር ነበር:: +ወቅቱ ዘመነ ሰማዕታት እንደ መሆኑ ቅዱሱ ከመምሕሩ ጋር ብዙ ነገሮችን አሳልፏል:: አርዮስ ክዶ: ቅዱስ ዼጥሮስ ካወገዘው በሁዋላ እንደ ባልንጀራ ገስጾ ሊመልሰውም ሞክሮ ነበር:: ነገር ግን የአርዮስን ክፋት ከጌታ ዘንድ የተረዳው ቅዱስ ዼጥሮስ ደቀ መዝሙሩን እለእስክንድሮስን ጠርቶ መከረው:: +"እኔ ከሞትኩ በሁዋላ አኪላስ ይተካል:: ከአርዮስ ጋር ስለሚወዳጅ በ6 ወሩ ይቀሠፋል:: አንተ ግን ከአርዮስ መርዝ ተጠበቅ" አለው:: ይህንን ካለው በሁዋላ ወታደሮች የቅዱስ ዼጥሮስን አንገት ቆረጡ:: ይህ የተደረገውም እ.ኤ.አ በ311 ዓ/ም ነው:: +ወዲያውም አኪላስ ተሾመ:: እንደ ተባለውም ከአርዮስ ጋር ስለተወዳጀ በ6 ወሩ ተቀሰፈ:: በዚያው ዓመትም ቅዱስ እለእስክንድሮስ የእስክንድርያ (ግብጽ) 19ኛ ፓትርያርክ (ሊቀ ዻዻሳት) ሆኖ ተሾመ:: +ሊቁ ሲሾም መልካም አጋጣሚ የነበረው ያ የመከራ ዘመን ማለፉ ሲሆን በጣም ከባዱ ግን የአርዮስ ተከታዮች ከተገመተው በላይ መበብዛታቸው ነው:: ቅዱሱ ሊቅ በዽዽስና መንበሩ ለ17 ዓመታት ሲቆይ ዕንቅልፍም ሆነ ዕረፍት አልነበረውም:: +በዚህ እየጾመ: እየጸለየ: ሥጋውን እየጐሰመ ለፈጣሪው ይገዛል:: በዚያ ደግሞ ሕዝቡን ነጋ መሸ ሳይል ያስተምራል:: ምዕመናንን ከአርዮስ የኑፋቄ መርዝ ለመታደግ ባፍም: በመጣፍም (በደብዳቤ) አስተማረ:: +ብርሃን የሆነ ደቀ መዝሙሩ #ቅዱስ_አትናቴዎስ እያገዘው: አርዮስን ከነአበጋዞቹ አሳፈሩት:: ለእያንዳንዷ የኑፋቄ ጥያቄ ተገቢውን መንፈሳዊ ምላሽ ከመስጠቱ ባለፈ አርዮስን ከአንዴም 2: 3ቴ በጉባኤ አውግዞታል:: +ነገሩ ግን በዚህ መቁዋጨት ባለመቻሉ ንጉሡ ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ ጉባኤ ኒቅያ እንዲደረግ አዋጅ ነገረ:: እ.ኤ.አ በ325 ዓ/ም (በእኛ በ318 ዓ/ም) ከመላው ዓለም ለጉዳዩ 2,348 የሚያህሉ ሰዎች ተሰበሰቡ:: ከእነዚህ መካከል 318ቱ ሊቅነትን ከቅድስና የደረቡ: ስለ ቀናች ሃይማኖት ብዙ መከራ ያሳለፉ ነበሩ:: +ይህንን የተቀደሰ ጉባኤ እንዲመራ ደግሞ መንፈስ ቅዱስ ቅዱስ እለአእስክንድሮስን መረጠ:: ሊቁም አበው ቅዱሳንን አስተባብሮ በሺህ የሚቆጠሩ ተከታዮች ያሉትን አርዮስን ተከራክሮ ረታው:: +በጉባኤው መጨረሻ አርዮስ "አልመለስም" በማለቱ እርሱን አውግዘው: ጸሎተ ሃይማኖትን ሠርተው: 20 ቀኖናወችን አውጥተው: መጽሐፈ ቅዳሴ ደርሰው: አሥራው መጻሕፍትን ወስነው: ቤተ ክርስቲያንን በዓለት ላይ አጽንተው ተለያይተዋል:: የዚህ ሁሉ ፍሬ አበጋዙ ደግሞ ቅዱስ እለእስክንድሮስ ነው:: +እርሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን "#ወልድ_ዋሕድ: #አምላክ: #ወልደ_አምላክ: #የባሕርይ_አምላክ" መሆኑን መስክሮ ክብርን አግኝቷል:: የእምነታችንም መሠረቱ ይሔው ነው:: ክርስቶስን "ፈጣሬ ሰማያት ወምድር: የባሕርይ አምላክ: ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ (ከአባቱ ጋር በመለኮቱ የሚተካከል)" ብለው ካላመኑ እንኩዋን ድኅነት ክርስትናም አይኖርም:: +ከጉባኤ #ኒቅያ በሁዋላ ቅዱስ እለእስክንድሮስ በመልካሙ ጐዳና ሲጋደል: ምዕመናንንም ሲያጸና ኑሯል:: ዘወትር ወንጌልን በፍቅር ያነብ ነበርና ሲጸልይ የብርሃን ምሰሶ ይወርድለት ነበር:: +ስለ ውለታውም #ቤተ_ክርስቲያን በግብጽ ካበሩ 5ቱ #ከዋክብት_ሊቃውንት እንደ አንዱ ታከብረዋለች:: ቅዱሱ ሊቅ በ328 ዓ/ም (በእኛ በ320 ዓ/ም) በዚህች ቀን ዐርፎ በክብር ተቀብሯል:: =>ቸር አምላከ ቅዱሳን ቤተ ክርስቲያንን ከነጣቂ ተኩላ ይጠብቅልን:: ከቅዱሱ ሊቅም በረከትን ይክፈለን:: =>ነሐሴ 18 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት= 1.ተዝካረ ፍልሠታ ለማርያም ድንግል (3ኛ ቀን) 2.ቅዱስ እለእስክንድሮስ ሊቅ 3.ቅዱስ እንድራኒቆስ ዲያቆን 4.አባ ዘክርስቶስ ዘወሎ (ኢትዮዽያዊ ጻድቅ) =>ወርሐዊ በዓላት 1.ቅዱስ ፊልዾስ ሐዋርያ 2.አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ሰባኬ ሃይማኖት (ረባን) 3.አቡነ አኖሬዎስ ዘደብረ ጽጋጋ 4.ማር ያዕቆብ ግብፃዊ 5.ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ (ከ72ቱ አርድእት) =>+"+ . . . ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለ ተሰጠ ሃይማኖት እንድትጋደሉ እየመከርኩአችሁ እጽፍላችሁ ዘንድ ግድ ሆነብኝ:: +"+ (ይሁዳ. 1:3) <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>> https://t.me/zikirekdusn።

††† እንኳን ለሰማዕታት ቅዱስ እንጣዎስ እና ቅዱስ ያዕቆብ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ቅዱስ እንጣዎስ አሞራዊ ††† ††† ይሕ ቅዱስ በቀደመ ሕይወቱ ክርስቲያኖችን የሚጠላ አስቸጋሪ አረማዊ ነበር:: ሃገሩ #ሶርያ( #ደማስቆ) ሲሆን ግብሩ ጣዖት ማምለክና መስረቅ ነበር:: በቅድስት ቤተ ክርስቲያንና በምዕመናን ላይም ግፍን ፈጽሟል:: በሥጋዊ ጉልበቱ ኃይለኛ ስለ ነበር የተፈራ ነው:: ሁልጊዜ በጠዋት ወደ #ቤተ_ክርስቲያን ይሔዳል:: የሚሔደው ግን ንዋያተ ቅድሳትን ለመዝረፍ: አንድም ካህናትን ለመደብደብ ነበር:: የሚገርመው ግን የወቅቱ ምዕመናንና ካህናት ይህን ሁሉ እያደረገባቸው አይጠሉትም:: ይልቁኑ ይጸልዩለት ነበር እንጂ:: ምክንያቱም ክርስትና ማለት ጠላትን መውደድ ነውና:: (ማቴ. 7) የእግዚአብሔር ትዕግስትና የምዕመናን ጸሎት ተደምሮው አንድ ቀን ፍሬ አፈራ:: እንጣዎስ እንደ ለመደው ለክፉ ሥራ ወደ #ቅዱስ_ቴዎድሮስ ቤተ ክርስቲያን ይሔዳል:: ከዚያም እንደ ደረሰ ወደ ውስጥ ገብቶ: የሚማታውን ተማቶ: የሚዘርፈውንም ዘርፎ: የተረፉትን ንዋያተ ቅድሳት በእሳት አቃጠላቸው:: #እግዚአብሔር ከዚህም በላይ ታጋሽ ነውና አላጠፋውም:: "ዘኢይፈቅድ ለኃጥእ ሞቶ" እንዲል የኃጢአተኛውን መመለስ እንጂ መሞቱን አይፈልግም:: ለዚያም ነው ዛሬ ይሔ ሁሉ ግፍ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እየተሠራ እግዚአብሔር እንደማያይ ዝም የሚለው:: ለሁሉም ቀን አለውና በፈረደ ቀን ግን በፊቱ የሚቆም አይኖርም:: እንጣዎስ ግን የሠራውን ሠርቶ እወጣለሁ ሲል አልተሳካለትም:: ከበሩ አካባቢ ሲደርስ: ከወደ ሰማይ አካባቢ ድምጽ ሰምቶ ቀና ሲል መላእክት እንደሱ ዓይነት ኃጢአተኞችን አሰልፈው በጦርና በቀስት ሲወጉአቸው ተመለከተ:: ድንገት ግን ከመላእክቱ አንዱ ዘወር ብሎ አንድ ቀስት ወደ እንጣዎስ ወረወረ (ተኮሰ):: ቀስቷ አካሉ ውስጥ ገብታለችና እንጣዎስ መሬት ላይ ወድቆ ለሞት ደረሰ:: ላበቱ በግንባሩ ላይ በጭንቅ እየፈሰሰ ጮኸ:: "ጌታየ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ማረኝ? ራራልኝ? ይቅር በለኝ? በድፍረት ባለ ማወቅም በድየሃለሁ:: ይቅር በለኝና ላምልክህ: ስምህንም ልሸከም" ሲል በጭንቀት ውስጥ ሆኖ አሰምቶ ጸለየ:: በዚያ የነበሩ ምዕመናን ማን: በምን እንደ ወጋው ባያውቁም ባዩት ነገር ግን እጅግ ደስ አላቸው:: እነርሱም የፈለጉትና የጸለዩለት ነገር ይሔው ነበርና:: ወዲያው ግን እንጣዎስ ከሞት ጫፍ ተመልሶ ተነሳ:: መጀመሪያ በቦታው የነበሩ ካህናትና ምዕመናንን "ይቅር በሉኝ?" አለ:: ቀጥሎም ወደ ዻዻስ ዘንድ ሔዶ "አጥምቀኝ" ሲል ጠየቀ:: እርሱ በሚጠመቅበት ቀን ብዙ አሕዛብና ክርስቲያኖች ተሰብስበው ነበር:: እርሱ በከተማዋ ዝነኛ ነበር:: ሥርዓቱ ሁሉ ተደርሶ ቅዱሱ ወደ ውሃ ገንዳው ሲገባ ሁሉ እያዩ የብርሃን ምሰሶ ከሰማይ ወረደ:: ይህንን በገሃድ የተመለከቱ ከ10,000 በላይ አሕዛብ ወዲያውኑ በክርስቶስ አምነው አብረውት ተጠምቀዋል:: ቅዱስ እንጣዎስ ከዚህ በሁዋላ ምስጉን ክርስቲያን ሆነ:: ስለ ቀደመ ሕይወቱ ፈንታ ጾምን: ጸሎትን: ፍቅርን: ምጽዋትን ገንዘብ አደረገ:: ሕይወቱም ለብዙ ሰዎች መስታውት ሆነ:: #እመቤታችን ድንግል ማርያምንም ይወዳት ነበርና ወደ ቅዱሳን ማሕበር ( #ኢየሩሳሌም) ወስዳው በሥጋዊ አንደበት ተከናውኖ ሊነገር የማይቻል ምሥጢርን ገልጣለታለች:: እነዚህን የቅድስና ጊዜያት በስኬት ያሳለፈው ቅዱስ እንጣዎስ መጨረሻው ሰማዕትነት ሆነ:: አረማውያን ወገኖቹና ቀድሞ የሚያውቁት ወደ ቀደመ ክፋትና ክህደት እንዲመለስ ጠየቁት:: "አይሆንም" አላቸው:: በአደባባይ ለፍርድ አቅርበው ደሙ እስኪፈስ ገረፉት:: ጥርሶቹን በሙሉ በድንጋይ አረገፏቸው:: ደሙና ጥርሶቹ መሬት ላይ ተዘሩ:: ነገር ግን ይሕ ስቃይ ቅዱሱን ከፍቅረ ክርስቶስ ሊለየው አልቻለም:: አሕዛብም ተስፋ ቆርጠው በዚህች ቀን ገድለውታል:: ቅዱስ እንጣዎስም ከሁዋለኛው ዘመን #ሰማዕታት እንደ አንዱ ተቆጥሯል:: ††† ቅዱስ ያዕቆብ ግብጻዊ ††† ††† ቅዱስ ያዕቆብ ተወልዶ ያደገው #መኑፍ (ግብጽ) ውስጥ ሲሆን ዘመኑም 3ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው:: ወላጆቹ የተባረኩ ናቸውና እርሱ ሳይወለድ የነበሯቸውን 3 ሴቶች ልጆች "ተማሩ" ብለው ወደ ገዳም ቢያስገቧቸው በዚያው መንነው ቀሩባቸው:: በዚህ ሲያዝኑ #ቅዱስ_ያዕቆብ ተወልዶላቸዋል:: እነርሱም በቃለ እግዚአብሔርና በጥበብ አሳድገውታል:: ትንሽ ከፍ ሲል በአካባቢው ከነበረ አንድ ቅዱስ ሽማግሌ ጋር ተደብቀው ገድልን ይሠሩ ነበር:: ሁሌም መልካም ምግባራትን ከመፈጸም ባለፈ ሙሉውን ሌሊት ባሕር ውስጥ ሰጥመው ይጸልዩ ነበር:: ዘመነ ሰማዕታት በመጣ ጊዜም 2ቱ ተመካክረው ስመ ክርስቶስን በገሃድ ሰብከዋል:: በዚህ ምክንያት ቅዱሱን ሽማግሌ ወዲያው ሲገድሉት ቅዱስ ያዕቆብን ግን ብዙ አሰቃይተውታል:: በመጨረሻም በዚህች ቀን ተሰይፎ የክብርን አክሊል ተቀብሏል:: ††† አምላከ ሰማዕታት ቤተ ክርስቲያንን ከመከራ ይጠብቅልን:: ከበረከታቸውም ያሳትፈን:: ††† ነሐሴ 17 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ተዝካረ ፍልሠታ ለማርያም ድንግል 2.ቅዱስ እንጣዎስ አሞራዊ (ሰማዕት) 3.ቅዱስ ያዕቆብ ግብጻዊ (ሰማዕት) 4.ቅዱስ አክራጥስ ሰማዕት 5.አባ እለእስክንድሮስ ዘቁስጥንጥንያ ††† ወርኀዊ በዓላት 1.ቅዱስ እስጢፋኖስ ሊቀ ዲያቆናት (ቀዳሜ ሰማዕት) 2.ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ (ወልደ ዘብዴዎስ) 3.ቅዱሳን አበው መክሲሞስና ዱማቴዎስ 4.አባ ገሪማ ዘመደራ 5.አባ ዸላሞን ፈላሢ 6.አባ ለትጹን የዋህ 7.ቅዱስ ኤዺፋንዮስ ሊቅ (ዘደሴተ ቆዽሮስ) ††† "ኃጢአተኞችን ሊያድን #ክርስቶስ_ኢየሱስ ወደ ዓለም መጣ የሚለው ቃል የታመነና ሁሉ እንዲቀበሉት የተገባ ነው:: ከኃጢአተኞችም ዋና እኔ ነኝ:: ስለዚህ ግን የዘላለምን ሕይወት ለማግኘት በእርሱ ያምኑ ዘንድ ላላቸው ሰዎች ምሳሌ እንድሆን ኢየሱስ ክርስቶስ ዋና በምሆን በእኔ ላይ ትዕግስቱን ሁሉ ያሳይ ዘንድ ምሕረትን አገኘሁ::" ††† (1ጢሞ. 1:15) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

ድንግል ማርያምን ወደ #ግብጽ ሸሽጐ አሸሻት:: ሔሮድስንም ፊት ለፊት ተገናኘው:: ከአቅሙ በላይ ስለነበረም በወታደሮች ተማርኮ ወደ ሔሮድስ ቀረበ::+እመቤታችንንና ልጇን "አምጣ" ቢለው "አልናገርም" አለው:: በዚህ ምክንያት አካሉን ከብዙ ቆራርጦ ገድሎታል:: በቤተ ክርስቲያን ታሪክም #ስለ_እመ_አምላክ_ፍቅር የተሰዋ የመጀመሪያው ሰው ተብሎ ይታወቃል:: ጌታም ስለ ሃይማኖቱ: ፍቅሩና ሰማዕትነቱ 3 አክሊላትን ሰጥቶታል::=>አምላከ ቅዱሳን ከድንግል እመ ብርሃን ፍቅር: ከጣዕሟ: ከረድኤቷ ያድለን:: የወዳጆቿን (ጊጋርና ጊዮርጊስን) በረከትም ያብዛልን:: =>ነሐሴ 16 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት= 1.ቅድስት ድንግል እግዝእትነ ማርያም (ፍልሠቷ: ትንሳኤዋና ዕርገቷ) 2.ቅዱሳን ሐዋርያት 3.ቅዱስ ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት (ፍልሠቱ) 4.ቅዱስ ጊጋር ሶርያዊ (ሰማዕት) =>ወርኀዊ በዓላት 1.ኪዳነ ምሕረት (የሰባቱ ኪዳናት ማሕተም) 2.ቅድስት ኤልሳቤጥ (የመጥምቁ ዮሐንስ እናት) 3.ቅዱስ ገብረ ማርያም ጻድቅ ንጉሠ ኢትዮዽያ (የቅ/ ላሊበላ ወንድም) 4.ቅዱስ አኖሬዎስ ንጉሥ ጻድቅ 5.አባ አቡናፍር ገዳማዊ 6.አባ ዳንኤል ጻድቅ 7.ቅዱስ አባ ዮሐንስ ጻድቅ (ወንጌሉ ዘወርቅ) =>+"+ ወደ ማደሪያዎቹ እንገባለን:: እግሮቹ በሚቆሙበት ሥፍራ እንሰግዳለን:: አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነስ:: አንተና #የመቅደስህ_ታቦት:: ካህናቶችህ ጽድቅን ይልበሱ:: ቅዱሳንህም ደስ ይበላቸው:: ስለ ባሪያህ ስለ #ዳዊት . . ." (መዝ. 131:7) =>+"+ ወዳጄ ሆይ! ተነሺ:: ውበቴ ሆይ! ነዪ:: በዓለት: በንቃቃትና በገደል መሸሸጊያ ያለሽ ርግብ ሆይ! ቃልሽ መልካም: ውበትሽም ያማረ ነውና: መልክሽን አሳዪኝ:: ድምጽሽንም አሰሚኝ:: +"+ (መኃ. 2:13) <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>