Finote Hiwot የቀጨኔ ደብረ ሰላም መድኀኔ ዓለምና ደብረ ትጉሃን ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ፍኖተ ሕይወት ሰንበት ትምህርት ቤት
前往频道在 Telegram
📈 Telegram 频道 Finote Hiwot የቀጨኔ ደብረ ሰላም መድኀኔ ዓለምና ደብረ ትጉሃን ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ፍኖተ ሕይወት ሰንበት ትምህርት ቤት 的分析概览
频道 Finote Hiwot የቀጨኔ ደብረ ሰላም መድኀኔ ዓለምና ደብረ ትጉሃን ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ፍኖተ ሕይወት ሰንበት ትምህርት ቤት (@finotehiwott) 阿姆哈拉语 语言赛道中的 是活跃参与者。目前社区聚集了 15 336 名订阅者,在 宗教与灵性 类别中位列第 5 643,并在 埃塞俄比亚 地区排名第 2 190 位。
📊 受众指标与增长动态
自 невідомо 创建以来,项目保持高速增长,吸引了 15 336 名订阅者。
根据 13 六月, 2026 的最新数据,频道保持稳定运转。过去 30 天订阅人数变化为 -75,过去 24 小时变化为 2,整体触达仍然可观。
- 认证状态: 未认证
- 互动率 (ER): 平均受众互动率为 22.35%。内容发布后 24 小时内通常能获得 10.54% 的反应,占订阅者总量。
- 帖子覆盖: 每篇帖子平均可获得 3 428 次浏览,首日通常累积 1 616 次浏览。
- 互动与反馈: 受众积极参与,单帖平均反应数为 25。
📝 描述与内容策略
作者将该频道定位为表达主观观点的平台:
“የቀጨኔ መድኃኔዓለም ፍኖተ ሕይወት ሰንበት ትምህርት ቤት ነሐሴ 26/ 1958 ዓ.ም ተመሠረተ።”
凭借高频更新(最新数据采集于 14 六月, 2026),频道始终保持新鲜度与高覆盖。分析显示受众积极互动,使其成为 宗教与灵性 类别中的关键影响点。
15 336
订阅者
+224 小时
-47 天
-7530 天
帖子存档
#ማኅበረ_ዴጎ (ዶጌ) /#ማኅበረ_ጻድቃናት)፤ #ጥር_29_ቃል_ኪዳን_የተቀበሉበት፤ #ጥር_30_ምስዋሮን_በተባለ_ቦታ_የተሰወሩበት_ዕለት_ነው፡፡
ማኅበረ ዴጎ ማለት የደጋጎች ሀገር ማለት ሲሆን የተባለበት ምክንያትም ቅዱሳን ስላሉበት ነው፡፡ በ365 ዓ.ም በአስፍሕ ወልደ አብርሃም ንጉሰ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ዘመነ መንግስት ‹‹ ሮምያ›› ከምትባል መንደር የቅዱስ መጽሐፍ ቃል የሆነውን መሠረት አድርገው፤ 1ኛ ‹‹ ስለ ጽድቅ ብለው የሚሰደዱ ብፁዓን ናቸው መንግሥተ ሰማያት የነርሱ ናትና›› ያለውን 2ኛ ‹‹ አባቱንና እናቱን ሚስቱንና ልጆቹን ያልተወ ሊያገለግለኝ አይችልም›› ብሎ ጌታችን እየሱስ ክርስቶስ የተናገረውን አንብበው የዚህን ዓለም ጣዕም ጥቅም ንቀው ሃገራቸውን ትተው መንነው ወደ ኢትዮጵያ የመጡ በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ነበሩ፡፡
እነዚህም በአኵሱም ከተማ በስተሰሜን በሐውልቱ ጀርባ ቤተ ቀጢን በሚባል ስፍራ አንድ ዓመት ከስድስት ወር ያህል እንደ ተቀመጡ በዚያም ምቾትና ድሎት ስለተሰማባቸው ለዚሁ ለዚሁማ ከሀገራችን ለምን ትተን መጣን? ስለዚህ ሱባዔ ገብተን በጾም በጸሎት ተወስነን የምንሄድበትን ቦታ በረከተ ነፍስ የምናገኝበትን ስፍራ እግዚአብሔር እንዲያሳየን እናመልክት ብለው ሱባዔ ገቡ ጾም ያዙ፡፡
ከሱባዔው በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተገልፃ ግማሾቹን እያንዳንዳቸው የሚኖሩበትን በዓት አመልክታቸው በዚያም በጾምና በጸሎት ፀንተው እንዲኖሩ ነገረቻቸው፡፡
ሦስት ሺህ/3000/ ያህሉ ደግሞ ከላይ ወደጠቀስነው ሄዱ፡፡ ከነርሱ የተቀሩት ደግሞ ወደ ቆየፃ ሓባር፣ ተድባ፣ አኮርየን፣ ተንስሓ፣ ደብረ አንሳ ወደ ተባሉ ቦታዎች ሄደዋል፡፡
ተጨማሪ ሦስት ሺ ደግሞ እዚያ ከነበሩት ጋርም ተደመሩ፡፡ ከዚያም የቅዱስ ጳውሎስና የቅዱስ ዮሐንስ መመሪያ ተከትለው ማለት ‹‹ከሁሉ ፍቅር ይበልጣል›› የሚለውን ጠብቀው በእምነት በፍቅር በአንድነት ፀንተው በየሳምንቱ እሑድ እሑድ ተዝካረ ሰንበትን ጠብቀው ማኅበር መጠጣት ጀመሩ፡፡ የማኅበረ ዴጎ ታሪክም ተቀየረ ፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን እየሱስ ክርስቶስ በአምሳለ ነዳይ ድሀ መስሎ በመካከላቸው ተገኘ፡፡ ከእነርሱ ጋርም አንድ ማኅበርተኛ ሁኖ እንዲታወቅ ጠየቃችው፣ እነርሱም ፈቀዱለት እና አንዱ የማኅበሩ አባል ሆነ፤ አንድ ዓመት ከስድስት ወር ያህልም ከነርሱ ጋር ሳይለይ ቆየ፡፡ በዚሁ ጊዜ ‹‹እስቲ ለኔም ተራ ስጡኝ እንደአቅሜ ዝክር ላውጣ፡፡›› አላቸው፡፡ በዚህ ግዜ ግን ድህነቱን አይተው ‹‹አይሆንም አንተ ድሀ ነህ ከኛ ጋር ሁነህ በዓሉን አክብር እንጂ ምን አለህና ነው የምትደግሰው ይቅርብህ›› አሉት፡፡ እርሱም ‹‹አይሆንም ስጡኝ እንጂ›› አላቸው እነርሱም ካልክማ ብለው ቀን ወስነው ሰጡት፡፡ ቀኑም ጥር 29 ነበር፡፡
ከማኅበርተኞቹ መካከል አሳላፊ ወይም ሙሴ ‹‹ሣይዳ ›› የሚባል ሰው ነበር፡፡ ይህም ሰው እንግዳና ድሀ ሰው ፈጽሞ አይወድም ነበርና ጌታችንም ከማኅበርተኞቹ መካከል ሲገኝ ደሀ መስሎ ስለነበር በጣም ይጠላው ነበር፡፡ አንድ ዓመት ከስድስት ወር ከነርሱ ጋር ሲቀመጥም አንድ ቀን ስንኳ አንድ ዋንጫ የወይን ጠጅ ሰጥቶት አያውቅም ነበር፡፡ የሆኖ ሆኖ የጌታችን ማኅበር መድረሱ አልቀረም ደረሰ፡፡ እንደማኅበሩ ሥርዐት የወይን ጠጅ የሚጠመቅባቸውን ጋኖች የሚያጥበው ሙሴው /አሳላፊው/ ነው፡፡ ስለሆነም በሥርዐቱ መሠረት ጌታችን ሙሴውን ጠርቶ ጋኖችን እጠብልኝ አለው፡፡ አሳላፊውም በቁጣ ‹‹አንተ ቤትህ የማይታወቅ፤ ከየት አምጥተህ ማኅበር ልታደርግ ነው አንተ ብሎ›› በማለት አናንቆ አልታዘዝህም ብሎ ሄደ፡፡ ይህን የተመለከተው ጌታም አንድ እረኛ ጠርቶ ‹‹አንተ ልጅ ከብቶችህን እኔ እጠብቅልሃለሁና በዚህ ውሀ አምጣልኝ›› አለው፡፡ ትንሹ እረኛ ልጅ ገምቦውን ይዞ ትንሽ ወጣ እንዳለ ጌታ ዘወትር በሚቀመጥበት ድንጋይ ላይ ሆኖ ዘንጉን ወደ ልጁ አቅጣጫ ወረወረው፣ ዘንጉንም ከልጁ ፊት ሂዶ ተተከለ፡፡ ልጁንም ጠርቶ ዘንጉንም እንዲነቅለው አዘዘው፡፡ ልጁም እንደታዘዘው ዘንጉንም ቢነቅለው ውሀ ፈለቀ፡፡ ከርሱ ቀድተህ አምጣልኝ አለው፡፡ ልጁም ከዚህ ውሀ ቀድቶ አመጣለት ጋኖቹን አጠባቸው፡፡
በበዓሉ ቀን ማህበርተኞቹ ምን ሊያበላን ነው፣ ምን ሊያጠጣን ነው ሳይሉ ኹሉም ተሰበሰቡ፡፡ ጌታችንም በፊታቸው ጋኖቹን ቢባርካቸው የወይን ጠጅ ሞልተው ተገኙ፡፡
ቀድቶ ቢሰጣቸውና ቢቀምሱትም በጣም ግሩም ጣፋጭ ስለነበር እጅግ አደነቁ፡፡ እነርሱም ጌታን ከጻድቃን አንዱ ስለመሰላቸው ከእግሩ ላይ ወድቀው እስካሁን ድረስ ሳንበድልህ አልቀረንምና ይቅር በለን ብለው ለመኑት፡፡ ተነሱ ብሎ ካስነሳቸው በኋላ እናንተ ምንም አልበደላችሁም የጠየኳችን እድርጋችኋል የበደለኝ ግን አሳላፊው ነው በማለትና አንድም ቀን ስንኳ አንድ ዋንጫ የወይን ጠጅ አልሰጠኝምና አፈራርዱኝ አላቸው፡፡ ነገር ግን ሙሴው/አሳላፊው/ የማያፍር ደፋርና ርጉም ስለነበር ‹‹ይህ ሰው ጌታችን በልቶ አልበላሁም ፣ ጠጥቶ አልጠጣሁም የሚል ስለሆነና ስለማይጠግብ ነው እንጂ እንዲያውም ለናንተ አንድ አንድ ዋንጫ ሲሰጣችሁ ለእርሱ ሁለት ሁለት ነበር የሚሰጠው ብሎ የሐሰት ቃል መለሰ፡፡
ጌታችንም እንግድያስ እኔ የጠጣሁበት ዋንጫ ትቅረብና ትመስክርብኝ አለው፡፡ በዚሁ ተስማምተው አሳላፊው/ሙሴው/ ሄዶ አንድ ሸራፋ ዋንጫ አምጥቶ በዚህ ነበር የሚሰጠውና የሚጠጣው ብሎ አቀረበ፡፡ ዋንጫዋም ከተቀመጠችበት አንድ ክንድ ከስንዝር ተነስታ ጽዋይቱን ስትመሰክር ‹‹ዓለማትን የፈጠረ አምላክ ምስክሬ ነው እኔ የያዝኩትን የወይን ጠጅ ዕቃ ሙሴም በእጆቹ አልያዝኩትም በከንፈሩ አልነካኝም በሌሎቹ ሰዎች እጅ ግን ተይዤ ያየን ነበር›› አለች ያን ጊዜ እንደ ዳታን እና አቤሮን ምድር ተከፈተችና ሙሴውን ከነልጁ ዋጠቻቸው፡፡
ማኅበረ ፃድቃንም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑ ተረድተው እንደገና ከእግሩ ወድቀው ይቅርታ እንዲያደርግላቸው ለመኑት፡፡ ቀኑም ጥር 29 ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይቅርታ ካደረገላቸው በኋላ ስማችሁ የጠራ በስማችሁ ተዝካር ያወጣ በስማችሁ ድሆችን የረዳ፣ ያለበሰ፣ ያጎረሰ፣ የሰጠ፣ የመጸወተ፣ ቤተ ክርስትያናችሁን የሠራ፥ ያሠራ፣ እሰከ 14 ትውልድ ደረስ ምሬላችኋለሁ ብሎ ቃል ኪዳን ሰጣቸው፡፡ ይህችን ቦታችሁ መጥቶ የሳመ እየሩሳሌም እንደሳመ አድርጌላችኋሁ አላቸው፡፡
በኦሪት ሔኖክ፣ ዕዝራ፣ ኤልያስ፤ በሐዲስ ኪዳንም እነ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድና በየጊዜውም እንደሚሰወሩ ቅዱሳን እንደዚሁም ጌታችን እነዚህን የማኀበረ ዴጎ ጻድቃንንም ከሞት ተሰወሩ ብሎ በበነጋታው ጥር 30 ቀን ሠውሯቸዋል፡፡ በዚህም መሠረት ይህ ታላቅ በዓል ሆኖ ዛሬም በየዓመቱ ጥር 30 ቀን በደማቅ ሁኔታ ሲከበር ይኖራል፣ ይከበራልም፡፡
በገዳመ ዴጎ በዓይን የሚታዩ፥ በእጅ የሚዳሰሱ ተአምራት የታየባቸውና የተደረገባቸው ንዋያት እስካሁንም አሉ፡፡ ወደ አኵሱም ስትሄዱ ታዩት ዘንድ እንጠቁማችሁ፡፡
1. ጌታችን የተቀመጠበትንና የቆመበትን ድንጋይ ከነምልክቱ
2. ምስዋሮም የሚባል ጻድቃኑ የተሰወሩበትን ስፍራ
#አቡነ_ገብረ_ናዝራዊ_ዘደብረ_ኀረይክዋ_ዘጥሙጋ)፤ #ጥር_29
ጻድቅሰ በአሚን የሐዩ (ጻድቅ ግን በሃይማኖቱ በሕይወት ይኖራል) /ዕን. 2፥4፤ ሮሜ 1፥17/ ጻድቃን ምንም እንኳን በሥጋ ቢሞቱም የነፍስ ሞት የለባቸውምና ነው፡፡
*አቡነ ገብረ ናዝራዊ ዘደብረ ኀረይክዋ(ዘጥሙጋ)፤ አባታቸው ስቡሐ አምላክ እናታቸው ክርስቶስ ክብራ የሚባሉና ከነገሥታት ወገን የነበሩ ናቸው፤ በ14ኛው ክፍለ ዘመን ሰሜን ሸዋ ይፋትና ጥሙጋ ደብረ ሲና ተወለዱ፡፡ ስማቸውን ያወጡላቸው ወላጆቻቸው ናቸው ገብረ ናዝራዊ ማለት በስዕለት ለእግዚአብሔር የተሰጠ ልዩና የተቀደሰ ማለት ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሲማሩ አድገው በ15 ዓመታቸው ከአቡነ ዮሐንስ ዘንድ ዲቁናና ተቀበሉ፡፡
*ኋላ ሥርዐተ ምንኵስናን ደግሞ ከአቡነ ጎርጎሬዎስ (የደብረ ጽጋጋው የታላቁ አኖሬዎስ ልጅ) ከተቀበሉ በኋላ የተወለዱበትን ደብር ሲያገለግሉና በምደረ ሸዋና አካባቢዋ ሲያስተምሩ ቆዩ፤ ንጉሡ ዐምደ ጽዮን የአባታቸውን ሚስት በማግባታቸው ጻድቁ አቡነ ገብረ ናዝራዊ፣ ጳጳሱ አቡነ ያዕቆብና ሌሎች ካህናት ይህንን ተግባር በመቃወማቸው ለጥቂት ሳምንታት በእስር ቤት ቆዩ፤ ጻድቁ ከእስር እንደተፈቱም በላስታ ላሊበላ ለ12 ዓመታት፣ በሐይቅ እስጢፋኖስ ደግሞ ለጥቂት ወራት ሰንብተው፤ ወደ ትግራይ ተጕዘው ከአባ የዕቆብ ዘንድ የመጻሕፍት ትርጓሜን ሲማሩ ቆዩ፤ ዛሬ በስማቸው ወደ ሚጠራው ታላቁ ገዳም እምባ ላም ደብረ ኀረይክዋ ለምናኔ ከመግባታቸው በፊትም በትግራይ ሃገር እየተዘዋወሩ ሦስት ገዳማትን መሥርተዋል፤ እነርሱም፤
#አጋዝና_ተራራ /#መበቊል_ቋጥኝ/ (ምዕራብ አዲግራት)
#ከቋጥኝ_ድንጋይ_ፈልፍለው_ያነጿት_ቂዓት_ማርያም፤ /ጻድቁ ለ8ዓመት ቆይተውባታል/
#ባለ_2ት_ዐምድና_ባለ_1_በር_አድርገው_ያነጹት_ማይ_ኢየሱስ_/#ቀበሌ_አዘባ_ቤት_ሓባ_ተራራ/
እነዚህን ገዳማት ከሠሩ በኋላ በዘንዶ እንደ አቡነ አገረጋዊ ወደ ደብረ ኀረይክዋ ተራራ ለምናኔ ወጥተዋል፤ ቦታውን ‹‹ደብረ ኀረይክዋ›› ብለው ራሳቸው ሲሆን የሰየሙት፤ ምክንያቱም ቦታው በተራራማና በተፈጥሮ የተዋበ ቦታ በመሆኑ፤ በተፈጥሮ ቅርጽነቱ ባለ ሦስት ማዕዝን ክብና በገመድ የሚወጣ ገዳም ነው፡፡
#ጻድቁ_ከሚታወቁባቸው_ነገሮች_ዋነኞቹም፤
**በተሰጠቻው ሀብተ ፈውስ ብዙ ሕሙማንን ይፈውሱ ነበር፤
**ፍጹም ተሐራሚ በመሆናቸው(የበሰለ ነገር ወደ አፋቸው ሳያስገቡ ሃያ አራት ሰዓት በዳዊት መዝሙር ይደሰቱና ላባቸው እስኪንጠፈጠፍም ይሰግዱ ነበር) ደቀ መዛሙርቶቻቸውም ከአንድ ማዕድ ውጪ አይቀምሱም ነበር፤
**ይስሐቅ የተባለው ደቀ መዝሙራቸው ሩቅ ሃገር ሄዶ ሲያርፍ ተገልጾላቸው ጸሎት እንዲደረግ ለደቀ መዛሙርቶቻቸው ተናገረዋል፡፡
*ከ44ት በላይ የውኃ ጕድጓዶችን ፈልፍለዋል /ለአብነትም ማይ መስቀል፥ ማይ ዮርዳኖስ፥ ማይ መቅደስ፥ ማይ ጠላዕ፥ ማይ ፀላእ ሰዋ የሚሉት ይገኙበታል/
**ሰንብታት እንዲከበሩ /በተለይ አብዛኛው ትቷት የነበረችውን ቀዳሚት ሰንበት እንድትከበር ታግለዋል/ በዚህም ከታላቁ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ቀጥሎም ሰንበትን አክብሮ በማስከበር ጻድቁ ትልቁን ቦታ ይይዛሉ፡፡
**በየሃገራቱ እየተዘዋወሩ ወንጌልን የሚሰብኩና ወንጌል የሚያዘውን ያለቻቸውን ነገር ይመጸውቱ ነበር
**ለደቀ መዛሙርቶቻቸውም ቅዱሳት መጻሕፍትን እንዲያስተምሩ፤ ሃይማኖታቸው በጸና ዓለት ላይ የተመሠረተ እንዲሆንና ሃይማኖትን ከሚያስቱ ሐሰተኞች እንዲጠበቁና ዓለምና ክብሩ እንዳያታልሏቸው ይመክሯቸው ነበር፡፡
**በርካታ ደቀ መዛሙርትን አፍርተዋል፡፡
#ላህም_አምባ_ደብረ_ኀረይክዋ
#እንደነ #ደብረ_ዳሞ፥ #ደብር_ማርያም #አቤር #አቡነ_ሰላማ ገዳም በገመድ የሚወጣበት ገዳም ነው፤
#በተራራማና በተፈጥሮ የተዋበና በተፈጥሮ ቅርጽነቱ ባለ ሦስት ማዕዝን ክብ ተራራ ነው፤
#የተራራው ርዝመትም 28ሜትር ነው፡፡
#ገዳሙ ከአዲግራት ደቡብ ምዕራብ በ27ኪ.ሜ. ርቀት ላይ ይገኛል፡፡
#በወቅቱ ከገዳመ ዋሊ (ዋልድባ) ቀጥሎ ጥብቅ ሥርዓት የነበረበት ታላቅ ገዳምም ሆኖ ነበር፡፡
#ጻድቁ በአንዶ አማካይነት ተራራውን ሲወጡ የረገጡበት የእግር ጣታቸው ምልክት ያለበት ዐለት ይገኛል፤
#እናቶች ምጥ ሲይዛቸው፥ ሰዎች ሲታመሙ የሚፈውስ፥ ድርቅና ችግር ሲፈጠር ምሕረት የሚያወርድ፥ የተጣሉ ሰዎች የሚታረቁበት #ነባኢ_መስቀል (አልቃሽ መስቀል) የሚገኝበት ነው፤
#ክረምት ከበጋ የማይደርቁና ፈውስን የሚሰጥ ጠበል ያለበት ቦታ ነው፡፡
ጻድቁ #ጥር_29_ዕረፍታቸው_ሲሆን፤ የከበረ አጽማቸው በገዳመ ደብረ ኀረይክዋ ከአንድ ቋጥኝ በተጠረበ ሦስት መዓዝን ባለው ድንጋይ ታትሞ ይገኛል፡፡
**ሰላም ለዝክረ ስምከ ዘተሰብሐ ወተወደሰ፤
በአፈ አምላክ አሚነ ወዕበየ ስብሐት ዘለብሰ፡፡
ገብረ ናዝራዊ እትናበብ ማኅሌተከ ሐዲሰ፤
አፉየ ምላእ እግዚኦ ማኅሌታዌ መንፈሰ፤
ወተናብቦትየ ረሲ ንባበ ቅዱሰ፡፡
/#ዋልድባ_ዋሊ/
#ጥር_29_ጻድቁና_ሰማዕቱ_አቡነ_ታዴዎስ_ዘጽላልሽና_አቡነ_ማትያስ_በውቢት_ገደል_/ጽላልሽ፥ ከሰም ወንዝ ቆላ ውስጥ የሚገኝ/ #ተወርውረው_ሰማዕትነት_የተቀበሉበት_ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ ለብዙ ዓመታት ጠፍ ኹኖ ቆይቶ በ2005ዓ.ም. የመቃኞ ቤተ ክርስቲያን ተሠርቶለታል፡፡
#አቡነ ታዴዎስ ዘጽላልሽ፤ አባታቸው ካህኑ ሮማንዮስ /የአቡነ ተክለ ሃይማኖት አጎት/ እናታቸው ማርታ ይባላሉ፡፡ የትልድ ቦታቸው ጽላልሽ ዞረሬ ነው፡፡ ሲወለዱ ዓምደ ብርሃን ተተክሎ የታየ ሲሆን እርሳቸውም በብርሃን ልብስ ተጠቅልለው ታይተዋል፡፡ ትምህርታቸውን ከሊቀ ካህናቱ ለሕይወት ብነ በጽዮን በሚገባ ተምረዋል፡፡
አቡነ ተክለ ሃይማኖት ዳሞት ተሻግረው ሞተሎሚን አስተምረው ካሳመኑት በኋላ አቡነ ታዴዮስን ወደ እርሳቸው እንዲመጡ ልከውባቸው ሄደው አቡነ ተክለ ሃይማኖትን እያገለገሉ ዘጠኝ ዓመት ተቀመጡ፡፡ ከዘጠኝ ዓመት በኋላ ግን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ አባ በጸሎተ ሚካኤል ሲሄዱ አቡነ ታዴዎስም ወደ ጽላልሽ ተመልሰዋል፡፡ ሁለቱም ከ32 ዓመት በኋላ ተመልሰው በጽላልሽ ተገናኘተው አቡነ ተክለ ሃይማኖት ለአቡነ ታዴዎስ ማዕረገ ምንኵስናን ሰጥተዋቸዋል፡፡ ከዚያም አቡነ ታዴዎስም በሥጋ ዕድሜ ታላቅ ቢሆኑም እንደታናሽ ብላቴና አቡነ ተክለ ሃይማኖትን እያገለገሉ በደብረ ሊባኖስ ተቀምጠዋል፡፡ ከዚህ በኋላ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አቡነ ታዴዎስን ወደ ጽጋጋ እንዲሄዱ ነገሯቸው ምክንያቱም አቡነ አኖሬዎስ በዚያ ሲያስተምሩ ከሃዲያን ደብድበው አስረዋቸው ነበርና አቡነ ታዴዎስን ሕዝቡን ከኃጢአት ግዞት፥ አኖሬዎስን ከእስራት እንዲያስፈቱ ላኳቸው፡፡
አቡነ ታዴዎስም በነፋስ ሠረገላ ተጭነው መዩጥ ከተባለውና አኖርዮስን ካሰራቸው ንጉሥ ፊት ቢደርሱ ንጉሡ በግንጋጤ መልአክ የመጣበት መስሎት ሲፈራ ከሰው ወገን መሆናቸውን ነግረው ክርስትናን አስተማሩት፡፡ ጋኔን ከእሳት ጥሎት ሲሠቃይ የሚኖርና ሊሞት የደረሰ ልጁን ቢፈውሱለት በትምህርታቸውና በተአምራታቸው አምኖ ሕዝቡ ክርስትናን እንዲቀበል በአዋጅ አስነገረ፡፡ አፍጃል የሚባለው ባለጸጋ ወደ አቡነ ታዴዎስ ቀርቦ ሲማር ‹‹ባለጸጋ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ከሚገባ ይልቅ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢሾልክ ይቀላል›› (ማቴ 19፡24፣ ማር 10፡25፣ ሉቃ 18፡25) የሚለውን የወንጌል ቃል ሲሰማ ለአእምሮው ረቆበት ‹‹እስቲ አድርገህ አሳየኝ?›› አላቸው፡፡ አቡነ ታዴዎስም እናቲቱን ግመል ከነጇ ቀጥሎም 28 ግመሎችን በየተራ በመርፌ ቀዳዳ እያሾለኩ አሳይተውታል፡፡ ሕዝቡ ሁሉ በእጅጉ ሲገረምና ‹‹በአምላከ ታዴዎስ ስም አምናለሁ›› ሲል የባለጸጋው ልጅ ሙሳ ግን ‹‹በምትሃት አሳይቶን ነው እንጂ የእውነት አይደለም›› በማለት አባቱንም እንዳያምን ይናገር ጀመር፡፡ ይህንንም ሲናገር በመጀመሪያ ያለፈችው እናቲቱ ግመል ረግጣ ገደለችው፡፡
አቡነ ታዴዎስም ንጉሡን፣ አባቱን አፍጃልንና ሕዝቡን የሞተ እንደሚነሣ ሲያስተምራቸው ‹‹የሞተ ይነሣልን? እስኪ ይህ የሞተው ልጅ ይነሳና ሁሉም አይቶ ይመን›› አሏቸው፡፡ እሳቸውም ‹‹ዛሬ ተቀብሮ ይዋልና ነገ በሦስተኛው ይነሣል›› ብለዋቸው ተቀብሮ ዋለ፡፡ በማግሥቱም አፍጃልን ጠርተው ‹‹‹አልዓዛርን ከሞት ባስነሣው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ልጄ ሆይ ና ውጣ› ብለህ ከልጅህ መቃብር ላይ አኑረው› ብለው ዘንጋቸውን ሰጡት፡፡ ሄዶም እንዳሉት ቢያደርግ ልጁ አፈፍ ብሎ ተነሥቷል፡፡ ይህንን ያዩ የሀገሩ ሰዎች ሁሉም አምነው ተጠምቀዋል፡፡ እሳቸውም 12 አብያተ ክርስቲያናትን አሳንጸው ሞቶ የተነሳውን ሙሳን ሙሴ ብለው ሰይመው አስተምረው ሊቀ ካህናት አድርገው ሾመውት አቡነ አኖሬዮስን ይዘው ወደ ጽላልሽ ዞረሬ ተመልሰዋል፡፡
አቡነ ተክለ ሃይማኖት ካረፉ በኋላ አባ ያዕቆብ የተባሉ ጳጳስ ከግብፅ መጡ፡፡ የአቡነ ታዴዎስን ዜና ሲሰሙ ተደስተው ከአቡነ ፊልጶስ ጋር ሆነው አስጠርተዋቸው ‹‹የአባታችሁን ዜና ገድል ንገሩኝ›› አላቸው፡፡ አቡነ ታዴዎስም ‹‹ጨዋታ በአስተርጓሚ አይሰምርም›› ብለው ወደ ጌታችን ቢጸልዩ የጳጳሱ ቋንቋ ለታዴዎስ፣ የታዴዎስም ቋንቋ ለጳጳሱ ተገልጦላቸው የመሸ የነጋ ሳይመስላቸው 40 ጾምን ሲጨዋወቱ ቆይተዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ጳጳሱ ከንጉሡ ተማክረው ‹‹ሊቀ ካህናት ዘጽላልሽ›› ብለው ሾመዋቸዋል፡፡
በነግህና በሰርክ ቤተ ክርስቲያንን እያገለገሉ፣ ቀን ወንጌልን እየሰበኩ፣ ሌሊት ከባሕር ገብተው ሲጸልዩ እያደሩ በታላቅ ተጋድሎ እየኖሩ ሳለ ከ10 ዓመት በኋላ ሰይጣን በንጉሡ በዓምደ ጽዮን ፍቅረ ዝሙት አሳድሮበት በክፉዎችም ምክር አታሎት የአባቱን ቅምጥ አገባ፡፡ አቡነ ታዴዎስም ይህን ሲሰሙ እንደ ነቢዩ ኤልያስና እንደ መጥምቁ ዮሐንስ በቀጥታ ሄደው ንጉሡን ገሥጸው አወገዙት፡፡ ገሥጸውና አውግዘው አቡነ ማትያስን አስከትለው ሲመለሱ ቅምጧ የንጉሡ ሚስት በፈረስ ተከትላ ደርሳ የኋሊት አሳስራ ዛሬ ‹‹ማርያም ገዳም›› ከሚባለው ቦታ ፊት ለፊት ካለውና ‹‹ውቢት ገደል›› ከሚባለው ትልቅ ገደል ውስጥ ሁለቱንም ጣለቻቸውና ጥር 29 ቀን በሰማዕትነት ዐረፉ፡፡
በሰማዕትነት ዐርፈው ደማቸው ከፈሰሰበት ከገደሉ ስር በፈለቀው ጸበላቸው ‹‹ታዴዎስ ወማትያስ›› እያለ ሦስት ጊዜ ብቅ ጥልቅ እያለ የተጠመቀ ሰው እንደ 40 ቀን ሕፃን እንደሚሆን ጌታችን ቃልኪዳን ገብቶላቷቸዋል፡፡ ይህ ሰማዕትነት በተቀበሉበት አካባቢ የተሠራው ቤተ ክርስቲያናቸው በጠላት ወረራ ጊዜ ፈርሶ ቦታው ጠፍ ሆኖ የኖረ ቢሆንም የአካባቢው ሕዝብ ቦታውን ከልሎ በክብር ሲጠብቀው ስለኖረ ፈቃደ እግዚአብሔር ሆኖ የአቡነ ታዴዎስ ታቦታቸው በ2005 ዓ.ም ከኢቲሣ ተክለ ሃይማኖት ገዳም ወጥቶ ጻድቁ ሰማዕትነት በተቀበሉበት አካባቢ በተሠራው መቃኞ ቤተ ክርስቲያናቸው በታላቅ ክብር ገብቷል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑም ከኢቲሣ በእግር የአንድ ሰዓት ተኩል ርቀት ላይ ይገኛል፡፡ በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን፡፡
(ዋቢ፤ ገድለ ታዴዎስ፣ በ2009ዓ.ም. የዋሊ ተጓዦች የቦታው አባቶች በቃል የነገሩን፣ በቦታው የተዘጋጀች በራሪ ጽሑፍ፣ ከገድላት አንደበት)
/በፍኖተ ሕይወት ሰ.ት.ቤት ሚድያና ሕዝብ ግንኙነት ዋና ማስተባበሪያ ክፍል የተዘጋጀ።/
• Facebook 👉 m.facebook.com/FinoteHiwotSundaySchool
• Telegram 👉 t.me/finotehiwott
• Tiktok 👉 tiktok.com/@finotehiwot
• YouTube 👉 m.youtube.com/@finotehiwot1958
🛑 ትብል ማርያም | ዝማሜ | ወረብ | ቀጨኔ ደብረሰላም መድኀኔዓለም || Finote Hiwot Sunday School
https://youtube.com/watch?v=qCa_iZdurAM&si=f6qa8PM4381865VY
"ሰማዕታት የዚህችን ዓለም ጣዕም በእውነት ናቁ ፤ ደማቸውን ስለ እግዚአብሔር አፈሰሱ ፤ ስለ መንግስተ ሰማያት መራራ ሞትን ታገሱ" ውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ
ዛሬ ጥር ፳፯ ቀን በሻሸመኔ ከተማ ስለሃይማኖታቸው ሰማዕታት የሆኑ ኦርቶዶክሳውያን መታሰቢያቸው ነው።
የሰማዕታቱ በረከት አይለየን !
መድኃኔዓለም ሆይ አስቀድሞ ፈያታዊ ዘየማንን እንዳስብከው አቤቱ አዳኝ ቤዛ በሚሆን መስቀልህ አስበኝ፤ ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ አቤቱ ቸር ጠባቂ ነህና እንደ ዓይን ብሌን ጠብቀኝ፤ አቤቱ እኔን መከረኛውን ሃዘንተኛውን በምስጋናህ የወይን ጠጅ አስደስተኝ አረጋጋኝ። "መልክአ መድኃኔዓለም"
የጥምቀት በዓል ዝግጅት ማጠቃለያ እና ልዩ የምስጋና መርሐ ግብር ተካሔደ::
የ2018 ዓ ም የጥምቀት በዓል በጃንሜዳ ተረኛ አዘጋጅ የነበረው ደብራችን ቀጨኔ ደብረሰላም መድኀኔዓለም እና ደብረ ትጉሃን ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን በዓሉን አስመልክቶ ከመጀመሪያው ቀን አንስቶ በዝግጅቱ ሒደት ላይ ተሳትፎ የነበራቸውን አካላት የማመስገን እና እውቅና የመስጠት ስነስርዓት ጥር 23 ቀን 2018 ዓ.ም አካሔደ ::
በመርሐ ግብሩ ስነ ስርዓቱ ላይም መጋቤ ካህናት እንቁ ባህሪ ተከስተ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የካህናት መምሪያ የበላይ ኀላፊ
መልአክ ሰላም ዓምደወርቅ ደሴ የደብሩ አስተዳዳሪን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው የደብራት አስተዳዳሪዎች የጠቅላይ ቤተ ክህነት የየመምሪያው ሀላፊዎች የደብሩ ካህናት እና ሊቃውንት እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል ።
በዚህም ደብራችን አዘጋጅ መሆኑ ከታወቀበት እለት አንስቶ በሀሳብ በገንዘብ በጉልበት በእቃ አቅርቦት የሚዲያ ሽፋን በመስጠት እና በሌሎችም የአገልግሎት ዘርፎች ሲያግዙ ለነበሩ ተቋማት ግለሰቦች የጥምቀት ኮሚቴው አባላት የእውቅና እና የምስጋና ሠርትፊኬት የመስጠት ስነ ስርዓት ተካሒዷል ::
ለአልባሳትና የተለያዩ ነዋየ ቅድሳት መግዣ እንዲሆን የገቢ ማሰባሰብ ኮሚቴ አዘጋጅቶት የነበረዉ የባለ መቶ ብር ትኬት እጣ ማዉጣት ፕሮግራም የተደረገ ሲሆን ከ1ኛ አስከ 3ኛ አሸናፊ የሆኑ የቲኬት ቁጥሮች ታዉቀዋል በዚሁ መሰረት 1ኛ እጣ ቁጥር 3045 ፣ 2ኛ እጣ ቁጥር 24313፣ 3ኛዉ እና የመጨረሻው እጣ ቁጥር 22988 ሆኖ ወጥቷል። እድለኞችም ወደ ደብሩ አስተዳደር በመምጣት ሽልማታቸውን መውሠድ እንደሚችሉ ተገልጿል።
በመጨረሻም መጋቤ ካህናት እንቁ ባህሪ ተከስተ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የካህናት መምሪያ ሀላፊ የዘንድሮው በዓል ላይ እጅግ አስደናቂ ስራ ለሠሩት የደብሩ የአስተዳደር አካላት የደብሩ ሰበካ ጉባኤ
ሊቃውንት እና የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ምስጋናቸውን በማቅረብ የደብሩን ጥንታዊነት ከእዚህም በበለጠ አጉልቶ ማሳየት የሚችል የልማት ስራ መሰራት እንዳለበት አፅንኦት ሰጥተው ተናግረዋል ::
በደብሩ ሊቃውንትም በዓሉን የሚያወሳ ወረብ እና መዝሙር ከቀረበ በኋላም ዝግጅቱ በጸሎት ተጠናቋል።
#የበረከት_ጥሪ_ለዓቢይ_ጾም
የነነዌ ሰዎችም ኃጢአታቸውን አምነው (ከኃጢአቱ የሌሉበትም ቢሆን መከራው ስለማይቀርላቸው) ከመሪ እስከ ተመሪ፤ እንደ አንድ ልብ መካሪ፥ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሁነው፤ ንጉሡም በከተማዋ የጾም አዋጅ አስነግሮ፥ ከዙፋኑ ወርዶ፤ ሕዝቡም ማቅ ለብሰው፥ አመድ ነስንሰው፥ በፍጹም ልባቸው አዝነው አልቅሰው፥ ሕፃናት ከጡት፥ ከብቶችም ከሣር መሠማራት ተከልክለው፥ ያለምግብ በበረት ተዘግተው፤ ጾሙንም በልባዊ ጸጸት፥ ራስን ዝቅ በማድረግና በማዋረድ ንስሓ ገቡ /“የነነዌ ሰዎችም እግዚአብሔርን አመኑ” ዮናስ 3፡5 ‹‹... ለጾም ዐዋጅ ነገሩ፤ ከታላቁም ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ፡፡ ወሬውም ወደ ነነዌ ንጉሥ ደረሰ፡፡ እርሱም ከዙፋኑ ተነሥቶ መጎናጸፊያውን አወለቀ፤ ማቅም ለበሰ፤ በአመድም ላይ ተቀመጠ...” ዮናስ 3፥5-9፡፡/ እንዳለ ከአምላካችን ምሕረትን አገኙ፡፡
ነቢዩ ዮናስም ይህን አይቶ በየዋሕነቱ ‹‹እንግዲህማ ሊምራቸው ነው፣ እኔም ሐሰተኛ ነቢይ ልባል ነው›› ብሎ እያዘነና ከሕይወት ሞት ይሻላል ነፍሴን ከእኔ ውሰድ እያለ ከከተማ ወጥቶ ዳስ ሠርቶ ተቀመጠ፡፡ እግዚአብሔርም በውኑ ትቆጣ ዘንድ ይገባሃልን አለው፡፡ /ዮናስ. 4፥3-11/ አምላካችን መሐሪ በመሆኑ /አባት ለልጆቹ እንደሚራራ እንዲሁ እግዚአብሔር ለሚፈሩት ይራራል ፍጥረታቸውን እሱ ያውቃልና መዝ. 102፥8-14፡፡ ጥበብ 3፡፡/ ብለዋል፤ አምላካችንም /እናንተ ክፉዎች ስትሆኑ ለልጆቻችሁ መልካም ስጦታ መስጠትን ካወቃችሁ በሰማይ ያለው አባታችሁ ለሚለምኑት እንዴት አብልጦ መልካም ነገርን አይሰጣቸው ብሏል ማቴ. 7፥12/ ቀጥሎም ነቢዩ ዮናስ እንቅልፍ እንቅልፍ ብሎት ተኝቶ ቢነቃ ከራስጌው ቅል በቅላ ፀሐይ ስትከለክልለት አየና እጅግ ደስ አለው፡፡ ሁለተኛም ተኝቶ ቢነሣ ቅሏ ጠውልጋ፥ ደርቃ አገኘና አዘነ፡፡ እግዚአብሔርም ‹‹አንተ ላልተከልካትና ውኃ ላላጠጣሃት ቅል እንዲህ ስታዝን እኔስ በዝናም አብቅዬ፥ በፀሐይ አብስዬ ለምመግባቸው ሕዝቤ አላዝንምን?›› አለው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የዮናስን ፈቃዱን ይፈጽምለት (ሐሳዊ ነቢይ እንዳይሉት) ለምልክት እንዲሆን በሦስተኛው ቀን እሳት ከሰማይ ወርዶ ከፍ ከፍ ያሉትን ዕፅዋት ጫፍ ጫፋቸውን በልቶ ተመልሷል፡፡
ነቢዩ ቅዱስ ዮናስ በቀሪ ዘመኑ ፈጣሪውን እያገለገለ ኑሮ፤ በመልካም ሽምግልና በ170 ዓመት እድሜም መስከረም 25 አርፏል፡፡ ዮናስ በሕይወት ሥጋ ሣለ ሰማርያንና ነነዌን ብቻ ነበር ያስተማረው፤ ከሞተ በኋላ ግን ዛሬ ዓለምን የሚያስተምር ነቢይ ነው፡፡
ከጾሙ ረድኤት በረከት ይክፈለን፤
/በፍኖተ ሕይወት ሰ.ት.ቤት ሚድያና ሕዝብ ግንኙነት ዋና ማስተባበሪያ ክፍል የተዘጋጀ።/
• Facebook 👉 m.facebook.com/FinoteHiwotSundaySchool
• Telegram 👉 t.me/finotehiwott
• Tiktok 👉 tiktok.com/@finotehiwot
• YouTube 👉 m.youtube.com/@finotehiwot1958
ጾመ ነነዌ፤ ከጥር 25-27 (ከሰኞ-ረቡዕ)
#ነነዌ
በጤግሮስ ወንዝ ምሥራቃዊ ቆሬ፥ ከዛሬዋ የሞሱል ከተማ በተቃራኒ ከባግዳድ በሰሜን ምዕራብ አቅጣጫ 350 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የነበረች ታላቅ ከተማ ነች፡፡
ነነዌን በመጀመሪያ የቆረቆራት ናምሩድ ነው፡፡ /ዘፍ. 10፥11/
በጣም ሰፊ ነበረች “የቅጥሯም ዙሪያ በእግር የሦስት ቀን መንገድ ያህል ነበረ” /ዮና. 3፥3/
እግዚአብሔር አምላካችን ነነዌን “ታላቂቱ ከተማ” በሚል ቅጽል ጠርቷል፤ /ዮናስ 3፥2፤ 4፥11/
ስለ መጥፋቷ ነቢዩ ሶፎንያስ “...ነነዌንም ባድማ እንደ በረሃም ደረቅ ያደርጋታል” በማለት ትንቢት ተናግሮባታል፡፡ /ትን. ሶፎ 2፥13/፡፡ እንደ ነቢያቱ ትንቢት ታላቋ ነነዌ ከ300 ዓመታት በኋላ ጠፍታለች፡፡
የነነዌ ሰዎች በስብከተ ዮናስ አምነው፥ ንስሐ ገብተው ድነዋል፤ በዚህም ጌታችን በወንጌል ላይ ስለ ንስሓቸውና ስለ እምነታቸው /‹‹...የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነሥተው ይፈርዱበታል፤ በዮናስ ስብከት ንስሐ ገብተዋልና፡፡›› በማለት አመስግኗቸዋል፡፡ ማቴ 12፥41/
#ዮናስ_ነቢየ_አሕዛብ_ወሕዝብ
ዮናስ ማለት ርግብ፥ የዋኅ ማለት ነው፡፡
በዳግማዊ ኢዮርብአም ዘመነ መንግሥት /825-784 ቅ.ል.ክ./ በሰማርያ የነበረ ነው፡፡ /2ነገሥ. 14፥25/፡፡
ቊጥሩ ከ12ቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ ነው፡፡
ነገዱ ከነገደ ይሳኮር ወገን ሲሆን፤ #አባቱ_አማቴ_እናቱም_ሶና(የሰራፕታዋ ደግ ሴት የሆነችውና ቅዱስ ኤልያስን በዚያ በረሃብ ዘመን የመገበችው ናት)፡፡
ኤልያስ በረሃቡ ዘመን ወደ ሰራፕታዋ መበለት ቤት በመሄድ "ውኃ አጠጪኝ ጥቂት ቁራሽም አምጪልኝ" አላት፡፡ ‹‹ሕያው እግዚአብሔርን እፍኝ ዱቄት አለችኝ ጋግሬያት አንተም እኔም ልጄም (ዮናስ) በልተናት እንሞታለን›› አለችው፡፡ ኤልያስም "የረሀቡ ዘመን እስኪያልፍ ይበርክት" አላት፤ ከቤቷ ብትገባ ዱቄቱ በማድጋው፣ ዘይቱ በማሰሮው መልቶ አገኘች፡፡ ከጥቂት ጊዜም በኋላ ልጇ ዮናስ ታሞ ሞተ፡፡ እናቱም ሄዳ ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስን "ሳይገባኝ ከቤቴ ገብተህ ኀጢአቴን ተመራምረህ ልጄን ትገድልብኝ?" አለችው፡፡ ነቢዩ ኤልያስም ወደ አምላኩ ሰባት ጊዜ ጸሎት አድርሶ ዮናስን ከሞተ በኋላ አስነሥቶታል፡፡
ዮናስ ትንሽ ከፍ ባለ ጊዜም ከነቢያት ጓደኞቹ አብድዩና ኤልሳዕ ጋር ሆነው የታላቁ ነቢይ የኤልያስ ደቀ መዛሙርት ሆኑ፡፡ /1ነገ.17፥1-24፤ 18፥10-24/ ነቢዩ ኤልያስ ካረገ በኋላ ደግሞ ሁሉም በተሰጣቸው አገልግሎት ተሠማርተው እግዚአቤሔርን አገለገሉ፡፡ ነቢዩ ዮናስ አርባ ዓመት ሲሞላው ሀብተ ትንቢት ተሰጥቶት ማስተማር ጀመረ፡፡
የሰማርያውን ንጉሥ ኢዮርብአምን ጠቃሚ ምክር በመለገስ የእሥራኤልን ድንበር ከሔማት እስከ ዐረብ ባሕር ድረስ እንዲይዝ አድርጎታል፡፡ /2ነገሥ. 14፥25/፡፡
ነቢዩ ዮናስ ምንም እንኳን የእስራኤል ነቢይ ቢኾንም ከምድረ እስራኤል ውጪ በነነዌ ስላስተማረ #ነቢየ አሕዛብ ወሕዝብ ይባላል፡፡ የትንቢት መጽሐፉም ዋና መልእክት እግዚአብሔር የእስራኤል ብቻ ሳይሆን የአሕዛብም አምላክ እንደሆነና በንስሐ ወደ እርሱ የተመለሱትን ሁሉ በምሕረት እንደሚጐበኝ ማሳየት ነው፡፡
#ዮናስና_ነነዌ_
የነነዌ ሰዎች ኀጢአት ከመሥፈርቱ በማለፉ፤ የእግዚአብሔር ቃል ወደ አማቴ ልጅ ወደ ዮናስ መጣ “ተነሥተህ ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ የክፋታቸውም ጩኸት ወደ ፊቴ ወጥቷልና ለእነርሱ ስበክ” አለው፤ ዮናስ ግን የፈጣሪው መሐሪነት፥ ቸርነት መስፈርት እንደሌለው ያውቃልና፤ እርሱ ቢምራቸው ማን ለቃሉና ለትንቢቱ ይገዛል፤ እኔም ሐሰተኛ ነቢይ ልባል አይደለምን? ብሎ አልሔድም አለ፤ እግዚአብሔር እየደጋገመ ሲናገረው ግን ዮናስ የዋሕ ነበረና እንዲህ የሚዘበዝበኝ ከፊቱ ብቀመጥ አይደል ብሎ ከፊቱ ለመሰወር ወደ ተርሴስ በመርከብ ኮበለለ፡፡
ዮናስ ወደ መርከብ ገብቶ ጕዞ ከተጀመረ በኋላ በእርሱ ምክንያት ታላቅ ማዕበል ተነሳ፤ በመርከቡ ውስጥ የተሣፈሩትም ሊያልቁ ሆነ፤ ሌሎች እንዲያ እየተናወጡ እርሱ ግን የእምነት ሰው፥ የዋሕና ቅን ስለሆነ ተረጋግቶ በመርከቡ ውስጥ ተኝቶ ነበር፡፡ መርከበኞቹም እጅግ ሲጨንቃቸው እያንዳንዳቸው ወደ አምላካቸው ጮሁ፤ መርከቢቱም እንድትቀልላቸው በውስጧ የነበረውን ዕቃ ሁሉ እያወጡ ወደ ባሕር ጣሉ፡፡ ባሕሩ ጸጥ ሊል ስላልቻለ ዮናስንም ቀስቅሰው “ይህ ክፉ ነገር በማን ምክንያት እንዳገኘን እናውቅ ዘንድ፤ ኑ ዕጣ እንጣጣል ተባባሉ፡፡” /ዮናስ 1፥7/፡፡ እጣ ቢጥሉ በዮናስ ላይ ወጣ፤ ዮናስም በራሱ ተጠያቂነት፤ ‹‹የእኔ ጥፋት ስለ ሆነ ወደ ማዕበሉ ጣሉኝ›› አላቸው፡፡ መርከበኞች ግን ዮናስን ለመታደግ የሚችሉትን ሁሉ አደረጉ፡፡ መርከቢቱ ወደ ምድር ትጠጋላቸው ዘንድ አብዝተው ቀዘፉ፤ የእርሱ ወደ ባሕር መጣል ፈቃደ እግዚአብሔር ስለሆነ ልፋታቸው ሁሉ ከንቱ ሆነ፡፡ ሁሉም አንድ ሆነው ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፡፡ “አቤቱ! አንተ እንደ ወደድህ አድርገሃልና ስለዚህ ሰው ነፍስ አታጥፋን፤ ንጹሕ ደምንም አታድርግብን፡፡” በማለት እያዘኑ በሐምሌ 15 ቀን ወደ ባሕሩ ጣሉት፤ ባሕሩም ከመናወጥ ጸጥ አለ፡፡
ነቢዩ ወደ ባሕር ቢጣልም የእግዚአብሔር ጥበቃ አልተለየውምና ዮናስን ይውጠው ዘንድ ታላቅ ዓሣ አንበሪን አዘዘለት፡፡ ነቢዩ ዳዊት ‹‹እግዚአብሔር የቀባውን እንዳዳነው ዛሬ ዐወቅሁ›› እንዳለ /መዝ. 19፥6/ የመረጠውን ነቢይ ለማዳን ዓሣ አንበሪን አዘጋጀለት፡፡
*ዮናስም በአሣ አንበሪ ሆድና በማዕበል ውስጥ ሆኖ ለ3 ቀናት ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፤ በመጽሐፍ ቅዱስም በዓሣ ሆድ ተጕዞ ያስተማረ፥ ትንቢትም የተናገረ የመጀመሪያ ነቢይ ሆነ፡፡ ዓሣ አንበሪው ዮናስን በሆዱ ቋጥሮ የሦስት ቀን ጎዳና በባሕር ውስጥ ገስግሶ በ3ኛው ቀን ነነዌ ዳር ደረቅ መሬት ላይ አራግፎ ተፋው፡፡ /ዮናስ 1፥4-16፤ 2፥1-11፣ መዝ. 138፥7-10/፡፡
ዮናስ በግዙፉ አሣ አነበሪ ውስጥም ያለ እንቅልፍ በጾም፥ በጸሎትና በምስጋና ለ3 ቀናት መቆየቱ ለክርስቶስ ትንሣኤ ምሳሌ ነው፤ ዮናስ በአሣ አንበሪ ሆድ 3 ቀን 3 ሌሊት ኑሮ፥ ሙስና (ጥፋት) ሳያገኘው መውጣቱ አዳምና ልጆቹን ለማዳን የመጣው ጌታችንም 3 መዓልትና 3 ሌሊት በከርሠ መቃብር አድሮ ከሙታን ተለይቶ የመምነሣቱ ምሳሌ ነው፡፡ ለዚህም ራሱ ጌታችን በወንጌል ‹‹ክፉና አመንዝራ ትውልድ ምልክት ይሻል፡፡ ከነቢዩም ከዮናስ ምልክት በቀር ምልክት አይሰጠውም፡፡ ዮናስ በአሣ አንበሪ ሆድ 3 ቀንና 3 ሌሊት እንደ ነበረ፤ እንዲሁ የሰው ልጅ በምድር ልብ 3 ቀንና 3 ሌሊት ይኖራል፡፡ የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነሥተው ይፈርዱበታል፡፡ በዮናስ ስብከት ንስሐ ገብተዋልና፡፡ እነሆም ከዮናስ የሚበልጥ ከዚህ አለ፡፡›› /ማቴ. 12፥39/
**እግዚአብሔር አምላክም ለሁለተኛ ጊዜ ዮናስን ወደ ነነዌ እንዲሄድ አዘዘው፤ “ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ የነገርሁህንም የመጀመሪያውን ስብከት ስበክላት” አለው፡፡ ዮናስም እንቀድሞው ሳያንገራግር ወደዚህች ከተማ ገብቶ እንዲህ እያለ ‹‹እስከ ሠሉስ ዕለት ትትገፈታእ ነነዌ ዐባይ ሃገር›› (እስከ ሦስት ቀን ድረስ ነነዌ ትገለበጣለች) ንስሐን ሰበከ፥ አስተማረ፡፡
#ስብስትያኖስ_ሰባስትያኖስ_ሰማዕት_ጥር_25
፠ በሕመም፥ በጭንቅ፥ በመከራ፥ በስቃይ፥ #በደዌ_ዳኛ፥ #በአልጋ_ቁራኛ_ላይ_ያላችሁ_ሁሉ በእምነት የሰማዕቱ የቅዱስ ስብስትያኖስን ስሙን ጥሩት፥ ገድሉን አድምጡ ተሻሹ፥ እምነቱን ተቀቡ፥ ቤተ ክርስቲያኑን ተሳለሙ #ፈዋሽ_ሰማዕት_ነው፡፡ #ፈትለ_ሥላሴ በመባል በሚጠራው ቤ.ክ. (ከአዲስ አበባ በሞጣ/በደብረ ድማኅ/ በኩል ወደ ባሕር ዳር ሲሄዱ አዴት ከተማ ከመድረስዎ በፊት ዠማ ወንዝ ለመድረስ ሲቃረቡ ያገኙታል)፡፡ ጥር 25 ዓመታዊ ክብረ በዓሉ ይከበራል፡፡ እንዲሁም በጥንታውያን ታላላቅ ገዳማትና አድባራት የብራና ገድሉ ስላለ አስነብቡ፥ ተሻሹ፤ ፍጹም ፈውስን ታገኛላችሁ፡፡
፠ ሰባ(ስብ)ስትያኖስ ሰማዕት፤ በስዕሉ ላይ እንደምንመለከተው በጽኑ ሕማምና ስቃይ ሰማዕትነትን የተቀበለ ነው፡፡ በተለይም በሕመም፤ በጭንቅ መከራ፤ በስቃይ ውስጥ ኾኖ ያለ ሰው አምላከ ሰብስትያኖስ ብሎ ለጠራኝ እደርስለታለሁ ብሎ በማይታበል ቃሉ እግዚአብሔር አምላካችን ቃል ኪዳን የሰጠው ሰማዕት ሲኾን ለጠሩትም ፈጥኖ የሚደርስ ሰማዕት ነው፡፡
፠ የስብስትያኖስ አባቱ የሮሙ ንጉሥ ሲሆን ሃይማኖቱ የቀናና እግዚአብሔርንም የሚወድ ስለነበር ልጁን የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያስተማረ ፈሪሃ እግዚአብሔርን እያስተማረ አሳደገው፡፡ አባቱም ከሞተ በኋላ ከሃዲያኑ ዲዮቅልጥያኖስና መክስምያኖስ ነገሡ፡፡ ቅዱስ ስብስትያኖስንም አገረ ገዥ አድርገው ሾሙትና እንደ አባቱ እጅግ አድርገው አከበሩት፡፡
፠ ቅዱስ ስብስትያኖስ በጥበብና በማስተዋል የሚጓዝ ነው፡፡ በተጋድሎ ሕይወቱ የተመሰገነ ሆነ፡፡ እግዚአብሔርም በእጆቹ የተለያዩ ተአምራትን ገለጠ፡፡ ድውያንን ይፈውሳል፤ በጸሎቱም የዕውራንን ዐይኖች ያበራል፡፡ በእንዲህም ዓይነት በተጋደሎ ሲኖር ዲዮቅልጥያኖስ እግዚአብሔርን ክዶ በዓለም ላይ ያሉ ክርስቲያኖችን እያሳረደ አብያተ ክርስቲያናትንም ማቃጠል ጀመረ፡፡ ይኸውም ከሃዲ አገረ ገዥ አድርጎ ሾሞትና በእጅጉ አክብሮት የነበረውን ቅዱስ ስብስትያኖስን አሁን ለጣዖት እንዲሰግድ ግድ አለው፡፡
፠ ቅዱስ ስብስትያኖስ ግን የከሃዲውን ንጉሥ ትእዛዝ ቸል በማለት በፊቱ ቆሞ የጌታችንን የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት መሰከረ፤ ጣዖታቶቹንም ረገመበት፡፡ ንጉሡም በዚህ ጊዜ በታላቅ ቁጣ ሆኖ ቅዱስ ስብስትያኖስን ብዙ አሠቃየው፡፡ ከግንድ ጋር አሥሮ በብዙ ፍላጻዎች(ቀስቶች) ሰውነቱን አስነደፈው፤ በዚህም ጊዜ እንደሞተ አስበው ትተውት ሄዱ፡፡ ምእመናንም ሥጋውን ለመውሰድ በሌሊት ቢመጡ በሕይወት አገኙትና ወስደው በደሴት መካከል አስቀመጡት፡፡
፠ ዲዮቅልጥያኖስም የቅዱስ ስብስትያኖስን በሕይወት መኖር ሲሰማ ድጋሚ አስመጣውና በብረት ዘንጎች ሲያስደበድበው ዋለ፡፡ ለብዙ ቀናትም እንዲሁ በብረት ዘንግ ሲያስደበድበው ቆየ፡፡ ቅዱስ ስብስትያኖስም በጥር 25 ቀን ነፍሱ ከሥጋው ተለየችና የሰማዕትነት ፍጻሜው ሆነ፡፡ ጌታችንም መታሰቢያውን ለሚያደርግና ስሙን ለሚጠራ የቸነፈር ሕመም፥ የሕመም ስቃይና መከራ እንዳይቀርበው ቃልኪዳን ሰጥቶታል፡፡ ቅዱስ ስብስትያኖስም ካረፈ በኋላ ውሉዱስና ለምትባል ለአንዲት ቅድስት ሴት ተገለጠላትና ቅዱስ ሥጋው ያለበትን ነገራት፡፡ እርሷም ወደ ከበሩ ቅዱሳን ጴጥሮስና ጳውሎስ መቃብር ወስዳ ቀበረችው፡፡
#ሰላም_ለዝክረ_ስምከ_ዘይትበደር እምብሩር፤
ወይጥዕም እም ሶከር፡፡
ሰባስትያኖስ ንጹሕ ትሩፈ ምግባር፤
በዝክረ ስምከ ተማኅጸንኩ ኢትኅድገኒ ለገብር፤
አመ ትወፅዕ ነፍስየ እምሥጋ በግብር፡፡
#ሰላም_ዕብል_ለፍጽምከ_መአድም፤
በስመ ሥላሴ ኅቱም፡፡
ሰባስትያኖስ አቡየ ሰላም ሰላም፡፡
በፍጽምከ ተማኅጸንኩ ኢይቅርበኒ ሕማም፤
ማዕተበ ፍጽምከ በፍጽምየ ሢም፡፡
#ሰላም_ለመልክዕከ_ዝብጠታተ ኀጺን ዘተወክፋ፤
ወትዕግስታተ አዝለፋ፡፡
ሰባስትያኖስ ጻማዊ ሱታፌ ሕማሙ ለዘልፋ፤
መልክዐ ገጽከ ኀበ ተጽሕፋ፥ ለመለክዕየ ጸሐፋ፤
ውስተ ምዕራፍከ ረሲ ምዕራፋ፡፡
**ዳግመኛም በዚህ ዕለት፤
#ሰማዕቱ_ቅዱስ_መርቆሬዎስ_በሥዕሉ_ላይ_አድሮ_ቅዱሳን_የሆኑ_ባስልዮስንና_ጎርጎርዮስን_በመርዳት_ከሃዲውን_ንጉሥ_ዑልያኖስን_የገደለበት_ዕለት_ነው፡፡
#ራሱን_የሸጠው_ቅዱስ_ጴጥሮስ_ዕረፍቱ_ነው፡፡
#ከበሬ_ጋር_ተጠምደው_በማረስ_ሰማዕትነትን_የተቀበሉት_አቡነ_ሕፃን_ሞዐ_ልደታቸው_ነው፡፡
(የስብስትያኖስ ቤተ ክርስቲያን ከአዴት በተጨማሪ ያለበትን ጠቁሙን ቢቻል በፎቶ ጭምር፤ አዴት አካባቢ የምትገኙ የፈትለ ሥላሴን ገዳም ፎቶ ላኩልን)
/በፍኖተ ሕይወት ሰ.ት.ቤት ሚድያና ሕዝብ ግንኙነት ዋና ማስተባበሪያ ክፍል የተዘጋጀ።/
• Facebook 👉 m.facebook.com/FinoteHiwotSundaySchool
• Telegram 👉 t.me/finotehiwott
• Tiktok 👉 tiktok.com/@finotehiwot
• YouTube 👉 m.youtube.com/@finotehiwot1958
+6
ዛሬ ጥር 22 ቀን፤ #የብርሃን_መልአክ_ከሣቴ_ምሥጢር_የሆነው_ቅዱስ_ዑራኤል_በዓለ_ሢመቱ ነው፤ እንኳን አደረሰን፡፡
በፎቶ ላይ የምትመለከቷቸው አብያተ ክርስቲያናት፤
1ኛ) በአዲስ አበባ የሚገኘውና ጥንታዊው ደብር #ደብረ_ጽጌ_ቅዱስ_ዑርኤል
2ኛ) #ግሸን_ቅዱስ_ዑርኤል
3ኛ) #ጎንደር_ደብረ_ኀይል_ቅዱስ_ዑርኤል_ወበዓታ፤ /ዛሬ ታቦተ ሕጉ ወደ ጠበል በመውረድ ይከብራል/
4ኛ) አዲስ አበባ አዲስ ሰፈር አንፎ መንበረ ብርሃን ቅዱስ ዑራኤልና መጥምቁ ዮሐንስና ቅድስት ልደታ ለማርያም ቤ.ክ. (ኮልፌ_ቀራንዮ_ክፍለ_ከተማ
5ኛ) ፉሪ ደብረ ገነት ቅዱስ ዑርኤል (የቤተ ክርስቲያኑ ፎቶ ካላችሁ ላኩልን)
6ኛ) ኤ(የ)ረር ምሥራቀ ፀሐይ ቅዱስ ዑርኤል (የቤተ ክርስቲያኑ ፎቶ ካላችሁ ላኩልን)
/በፍኖተ ሕይወት ሰ.ት.ቤት ሚድያና ሕዝብ ግንኙነት ዋና ማስተባበሪያ ክፍል የተዘጋጀ።/
• Facebook 👉 m.facebook.com/FinoteHiwotSundaySchool
• Telegram 👉 t.me/finotehiwott
• Tiktok 👉 tiktok.com/@finotehiwot
• YouTube 👉 m.youtube.com/@finotehiwot1958
现已上线!2025 年 Telegram 研究 — 年度关键洞察 
