የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)
前往频道在 Telegram
2 636
订阅者
+124 小时
+167 天
+5630 天
帖子存档
ከዚህ በኋላ ይህ አባት እለእስክንድሮስ ሊቀ ጵጵስና ተሹሞ በመንበረ ሢመቱ ላይ ተቀመጠ አርዮስንም ከወገኖቹ ጋራ አውግዞ አሳደደው። የሀገር ታላላቆችም ከሕዝቡ መጡ ከውግዙቱ እንዲፈረታውም ለመኑት። በውግዘት ላይ ውግዘትን እንዲጨምር እንጂ እንዳይፈታ አባ ጴጥሮስ እንዳዘዘው ነገራቸው።
ከዚህ በኋላ አርዮስ ወደ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሒዶ በግፍ አወገዘኝ ብሎ እለእስክንድሮስን ከሰሰው። ስለዚህም ንጉሡ ሦስት መቶ አሥራ ስምንት የከበሩ አባቶችን በኒቅያ ከተማ ሰበሰበ፡፡ ይህም አባት እለእስክንድሮስ ተመርጦ ለጉባኤው ሊቀ መንበር ሆነ አትናቴዎስም ጸሐፊ ነበር። አርዮስንም ተከራክረው ክህደቱን ግልጽ አደረጉ ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከአባቱ ከአብ ጋራ ከሕይወቱ መንፈስ ቅዱስም ጋራ በመለኮቱ ትክክል እንደሆነ አስረዱት።
ከክህደቱ ባልተመለሰ ጊዜ አውግዘው ለይተው ከቤተ ክርስቲያን አሳደዱት። በአንድ ቃልም ጸሎተ ሃይማኖትን ከአባቶች ጋራ ሠሩልን ደግሞ በእርሳቸው ቤተ ክርስቲያን ለዘላለም የምትመራባቸው ሃያ ቀኖናን ሠርተው ወሰኑ።
ከዚህ በኋላም ይህ አባት እለእስክንድሮስ ወደ መንበረ ሢመቱ ከድል ጋራ ተመለሰ። በበጎ አጠባበቅም መንጋውን ጠበቀ በወንጌላዊ ማርቆስ መንበርም አሥራ ሰባት ዓመት ኖሮ በሰላም አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ማርቆስ_ሐዲስ
በዚህችም ቀን የሐዲስ ማርቆስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ፡፡ እርሱም በእስክንድርያ ለተሾሙ አባቶች አርባ ዘጠነኛ ነው ። ይህም አባት ከእስክንድርያ አገር ነው እርሱም በሥራው ሁሉ ቅድስናውን ጠብቆ ኖረ የተማረም ዐዋቂ ሆነ ለወንጌላዊ ማርቆስም በስም ሁለተኛ ነው ።
አባ ዮሐንስም ዲቁና ሾመው እጅግ መልካም ካህን ሆነ መጻሕፍትን በሚያነብ ጊዜ በአንደበቱ ቅልጥፍና በነገሩ ጣዕም የሚሰሙት ሁሉ ደስ የሚላቸው ሆኑ ። ከዚያም አባ ዮሐንስ ከእርሱ ጋራ አኖረው በሊቀ ጵጵስናው ሥራ ሁሉ ሥልጣን ሰጠው ያለ እርሱም ምክር አባ ዮሐንስ ምንም ምን አይሠራም ።
ከዚህ በኋላ በአባ መቃርስ ገዳም የምንኲስና ልብስ አለበሰው በዚያች የምንኵስና ልብስ በለበሰባትም ቀን ከቅዱሳን አረጋውያን አንድ ጻድቅ ሰው መጥቶ በእርሱ ላይ እንዲህ ብሎ በሕዝብ ፊት ይህ ስሙ ማርቆስ የሚባል ዲያቆን በአባቱ በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበር ሊቀመጥ አለው ብሎ ትንቢት ተናገረለት ።
የአባ ዮሐንስም የሚሞትበት ጊዜ ሲቀርብ አባ ማርቆስን ሊቀ ጵጵስና እንዲሾሙት ኤጲስቆጶሳቱን አዘዛቸው በእርሱ መሾምም ደስ አላቸው ። ከአባ ዮሐንስ ዕረፍት በኋላም ያለ ፈቃዱ ሾሙት እርሱ ግን ከእርሳቸው ሸሽቶ ወደ አስቄጥስ ሔደ ሰዎችንም ልከው አሥረው ወደ መንበረ ሢመቱ አመጡት ።
ከዚህ በኋላም ጸጥ ብሎ ስለ አብያተ ክርስቲያን የሚያስብ ሆኖ የፈረሰውን አነፀ ጠገነ፡፡ በዘመኑም የመናፍቃንን ጠባይ ከሕዝቡ ውስጥ አስወገደ ይኸውም በግብጽ አገር የተገለጡ ለብቻቸውም ቤተ ክርስቲያን ሠርተው የሚኖሩ ናቸው እርሱም አስተምሮ መክሮ መልሶ ከመንጋዎቹ ጋራ አንድ አደረጋቸው። እግዚአብሔርም በዚህ አባት እጅ ድውያንን በመፈወስ አጋንንትን በማስወጣት ብዙ ድንቆች ምልክቶችን ገለጠላቸው።
ከእርሳቸውም አንዱን አስተውል አንተ ያለ ፍርሀት በድፍረት ሥጋውንና ደሙን የምትቀበል ባትሆን ይህ ባላገኘህም ነበር ከእንግዲህ ከክፉ ሥራና ከአንደበትህ ከሚወጣ ከከንቱ ነገርም ሰውነትህን ጠብቅ አለው።
በዘመኑም በምዕራብ ያሉ እስላሞች ይሸጡአቸው ዘንድ ብዙ ክርስቲያኖችን ከሮም ግዛት ውስጥ ማርከው ወደ እስክንድርያ አመጡአቸው ይህም አባት እጅግ አዘነ ከየገዳማቱና ከምእመናን ብዙ ገንዘብ ለምኖ ከእስላሞች እጅ በሠላሳ ሽህ የወርቅ ዲናር ዋጃቸው የነፃነትም ደብዳቤ ጽፎ ነፃ አወጣቸው ። እንዲህም አላቸው ወደ አገሩ መመለስ የሚሻ እኔ ስንቅ ሰጥቼ አሰናብተዋለሁ ከእኔ ጋራ መኖር የሚሻም ካለ እኔ እጠብቀዋለሁ አላቸው። የተመለሱ አሉ ስንቅ ሰጥቶም ያሰናበታቸው አሉ ከእርሱ ዘንድ የቀሩትንም ጠበቃቸው አጋባቸውም።
ከዚህ በኋላ ስለ መድኃኒታችን ቤተ ክርስቲያን አሰበ አደሳትም ሰይጣንም በሀገር ውስጥ ሁከት አስነሥቶ በእሳት አቃጠላት ይህም አባት መልሶ ዳግመኛ አደሳት። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ሊአሳርፈው በወደደ ጊዜ ጥቂት ታመመ በፋሲካ በዓል በእሑድ ቀንም ወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ ተገለጠለት ለሚወዱት እግዚአብሔር ስለ አዘጋጀው ተድላ ደስታ ነገረውና ሥጋውንና ደሙን ከተቀበልክ በኋላ ታርፋለህ አለው። በነቃ ጊዜም እንዴት እንዳየ ከእርሱ ዘንድ ላሉ ኤጲስቆጶሳት ነገራቸው።
ከዚያም የቅዳሴውን ሥርዓት ጀምሮ ቀድሶ ሥጋውን ደሙን ተቀበለ በዚያን ጊዜም አረፈ የሹመቱም ዘመን ሃያ ዓመት ሆነ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ሚካኤል_ዘእስክንድርያ
በዚህችም ቀን የከበረ አባት አባ ሚካኤል የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አረፈ፡፡ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃምሳ ሦስተኛ ነው ። ይህም ቅዱስ ጻድቅ መንኲሶ በአስቄጥስ በቅዱስ ዮሐንስ ገዳም አበ ምኔት ሁኖ ተሾመ ከዚያም ያለ ፈቃዱ ወስደው በግድ ሊቀ ጵጵስና በእስክንድርያ አገር ላይ ኅዳር ሃያ አራት ቀን ሾሙት ። በሊቀ ጵጵስናውም ሥራ ተጠምዶ የሚጋደል ሆነ እንደ ሐዋርያትም አጠባበቅ መንጋውን ጠበቀ ።
ታላቁ ጾምም በደረሰ ጊዜ ወደ አስቄጥስ በዚያ ሊጾም ወጣ ከመሾሙ በፊት በዚያ ገዳም ውስጥ በብሕትውና ሁኖ መጠመዱንና የቀድሞ መጋደሉን አሰበ ።
ወደ ጌታችንም እንዲህ ብሎ ለመነ አቤቱ እኔ በብቸኛነት መኖርን እንደምሻ አንተ ታውቃለህ ለዚች ለተሾምኩባትም ሹመት ችሎታ የለኝምና የምትገባኝም አይደለችምና በይቅርታህም ብዛት ነፍሴን ወስደህ ከዚህ ድካም ታሳርፈኝ ዘንድ እለምንሃለሁ ጌታም ልመናውን ተቀበለ ከፋሲካ በዓል በኋላም በፍቅር አንድነት አረፈ፡፡ የሹመቱም ዘመን ሁለት ዓመት ከአምስት ወር ነው።
ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_22
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሚያዝያ ሃያ ሁለት በዚህች ቀን ኢትዮዽያዊው ጻድቅና ሐዋርያ #ቅዱስ_ተክለ_ሃይማኖት በዚህች ቀን ከኢትዮጵያ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዘው ከቅዱሳት መካናት ተባርከዋል፣ የከበረ #አባት_ይስሐቅ አረፈ፣ የከበረ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ የሆነ #ቅዱስ_እለእስክንድሮስ አረፈ፣ #የሐዲስ_ማርቆስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ፣ የከበረ አባት #አባ_ሚካኤል የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት
ሚያዝያ ሃያ ሁለት በዚህች ቀን ኢትዮዽያዊው ጻድቅና ሐዋርያ ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት በዚህች ቀን ከኢትዮዽያ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዘው ከቅዱሳት መካናት ተባርከዋል::
ጻድቁ ምድረ እሥራኤል የገቡት በየመንገዱ መንፈሳዊ ዘርን እየዘሩ: እያስተማሩና እያሳመኑ ነበር:: የወቅቱ ሊቀ ዻዻሳት አባ ሚካኤል ጋርም ተገናኝተው ቡራኬን ተሰጣጥተዋል::
ዋናው ጉዳይ ግን ከዚህ በሁዋላ ነው:: ጻድቁ እመቤታችንና ጌታችን ከጽንሰታቸው እስከ ዕርገታቸው የረገጧቸውን ቦታዎች ሲመለከቱ በፍጹም ተደሞ እንባቸው ይፈስ ነበር:: ምክንያቱም እግዚአብሔር ስላበቃቸው ተክለ ሃይማኖት የሚያዩት ቦታውን አልነበረም::
በገሃድ በቤተ መቅደስ ብስራቱን፣ በቤተ ልሔም ልደቱን፣ በቤተ ዮሴፍ ግዝረቱን፣ በፈለገ ዮርዳኖስ ጥምቀቱን፣ በቤተ አልዓዛር ተአምራቱን ይመለከቱ ነበር::
የጉብኝታቸው የመጨረሻ ክፍል ወደ ሆነው ቀራንዮ ደርሰው ጌታቸውን እንደ ተሰቀለ ሆኖ ቢመለከቱት ከዓይናቸው ይፈስ የነበረው ቁጡ እንባ መልኩን ቀየረና ዓይናቸው ጠፋ:: በዚያች ቅጽበት ስም አጠራሯ የከበረ እመቤታችን ድንግል ማርያም ፈጥና ደርሳ ተክልየን ወደ ሰማይ አሳረገቻቸው::
በዚያም የብርሃን ዐይን ተቀብለው፣ 6 ክንፍ አብቅለው፣ የወርቅ ካባ ላንቃ ለብሰው፣ ማዕጠንተ ወርቁን ይዘው፣ ከ24ቱ ካህናተ ሰማይም ተደምረው፣ ሥላሴን በአንድነቱና ሦስትነቱ ተመልክተው "ስብሐት ወክብር ለሥሉስ ቅዱስ ይደሉ" ብለው መንበረ ጸባኦትን አጥነው ወደ መሬት ተመልሰዋል::
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አባት_ይስሐቅ
ዳግመኛም በዚህች ቀን ከግብጽ ደቡብ ከእብክ አውራጃ ከሆሪን ከተማ የከበረ አባት ይስሐቅ አረፈ። የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም አብርሃም የእናቱም ስም ሶስና ነው ታናሽም ሆኖ ሳለ እናቱ ሙታብቻውን ያለእናት አባቱ እያሳደገው ኖረ።
ጥቂት በአደገም ጊዜ የአባቱን በጎች የሚጠብቅ ሆነ አባቱም ሌላ ሚስት አገባ በዚያ ወራትም ታላቅ ረኃብ ሆነ የአባቱም ሚስት ትጠላው ነበረ ከጥቂትም በቀር እንጀራ አትሰጠውም ያንኑም ሁልጊዜ ለእረኞች ሰጥቶ እርሱ ግን እሰከምሽት ይፈጸማል።
ምሳውን ለእረኞች እንደሚሰጥና ሁልጊዜ እስከምሽት እንደሚጾም አባቱ ሰምቶ ዕውነት እንደሆነ ሊያይ ወደርሱ ሔደ ። ቅዱሱም ሕፃን የአባቱን መምጣት ዐውቆ በልብሱ ሦስት ጭቃ አድበልብሎ አሠረ እንደ ታሠረ በሚያየው ጊዜ ለአባቱ አምባሻ እንዲመሰለው ብሎ
አባቱም በመጣ ጊዜ የልጁን ልብስ ፈትቶ አየ አምባሻም ሁነው አገኛቸው። የነገረውንም ሰው ምግቡን ለእረኞች ከሰጠ በዛሬዪቱ ቀን ይህ አምባሻ ከወዴት ተገኘለት ብሎ ጠየቀው እርሱም በእውነት ሰጥቷል አለ ሌሎችም ብዙዎች መጥተው በዚህ ነገር ምስክሮች ሆኑ አባቱም አደነቀ እግዚአብሔርንም አመሰገነ።
ይህም በአደገ ጊዜ አባ ኤልያስ ወደሚባል ሰው ሔዶ መንኲሶ በዚያ እየተጋደለ ብዙ ዓመታት ኖረ። አባ ኤልያስም በአረፈ ጊዜ በርኑግ ወደሚባል ገዳም ሔደ ስሙ ዘካርያስ ከሚባል አረጋዊ ዘንድ በታላቅ ገድል ተጠምዶ ኖረ።
አባቱም ያገኘው ዘንድ በሀገሮች ሁሉ ይዞር ነበረ በዚህ በበርኑግ ገዳምም በአገኘው ጊዜ ከእርሱ ጋራ እንዲመለስ አባቱ ለመነው አይሆንም አለ አባ ዘካርያስም ከአባቱ ጋራ ይሔድ ዘንድ እስከ ሚዐርፍም ከእርሱ ዘንድ እንዲኖር አዘዘው ይህ ቅዱስም ከአባቱ ጋራ ሔዶ እስከሚዐርፍ ድረስ ከእርሱ ዘንድ ኖረ።
አባቱም በአረፈ ጊዜ አባቱ የተወውን ገንዘብ ሁሉንም ለድኆችና ለምስኪኖች ሰጠ ከከተማውም ጥቂት ራቅ ብሎ ለራሱ ታናሽ ማደሪያ ሠራ በሰላም እስከ ሚዐርፍባት ቀን ድረስ ያለ ማቋረጥ በበጎ ገድል በጾም በጸሎት በስግደት ኖረ በአረፈ ጊዜም በመልካም ቦታ አኖሩት ከዚያም ተሠወረ።
ከብዙ ዘመናትም በኋላ እግዚአብሔር ሊገልጠው ወዶ በመቃብሩ ላይ መብራት ሲበራ እህል ለሚዐጭዱ ሰዎች ሦስት ቀን ያህል ታየ ሊያዩትም ወደቦታው ሲደርሱ ያ መብራት ከእርሳቸው ይሠወራል በሁሉ ዘንድ እስቲሰማም እንዲህ ሁኖ ኖረ።
ከዚህም በኋላ በመቃብሩ ላይ እያበራ ያ መብራት ደግሞ ታያቸው ሥጋውም በዚያ እንዳለ ሁለተኛ በሕልም ነገራቸው ምእመናንም አክብረው በግመል ጭነው ወደ ሀገሩ መካከል ወደ ሆሪን ወሰዱት ነስሪን ከሚባል አገር መካከል ሲደርሱ ግመሉ በዚያ ተንበረከከ እንዲነሣም መቱት መነሣትንም እምቢ አለ መኖሪያው በዚያ ይሆን ዘንድ የእግዚአብሔር ፈቃድ እንደሆነ ዐወቁ።
በዚያም በስሙ ቤተ ክርስቲያን ሠርተው ሥጋውን በውስጥዋ አኖሩ ከእርሱም ብዙ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_እለእስክንድሮስ_ሊቅ
በዚህችም ቀን የከበረ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳትም ዐሥራ ዘጠነኛ የሆነ እለእስክንድሮስ አረፈ። ስለርሱም ሐዋርያዊ አባት አትናቴዎስ እንዲህ አለ አባቴ እለእስክንድሮስ ተቀምጦ ወንጌልን አያነብም ቁሞ ያነባል እንጂ ከርሱ ጋራም ብርሃን አለ።
ሁለተኛም ስለርሱ ሲናገር ወደርሱ እመምኔቶች መጥተው በእኛ ዘንድ ሰባት ሰባት ቀን የሚጾሙ ደናግል አሉ ። በእጅዎቻቸውም ምንም ምን ሥራ አይሠሩም ብለው ነገሩት ።
እርሱም እኅቶቼ ሆይ እኔ ሁለት ቀን እንኳ ከቶ አልጾምኩም ፀሐይ እስኪገባም ቆይቼ አልበላሁም በልክ እበላለሁ በልክም እጾናለሁ በልክ በመጠንም እሠራለሁ በልክ ይበሉ ዘንድ በልክም ይጾሙ ዘንድ በልክም ሥራ ይሠሩ ዘንድ ንጉሩአቸው በበጎ ሥራ ሁሉ ይሰለፉ አለ።
የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ ደጎች ምእመናን ናቸው እርሱም በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ውስጥ ሁኖ ከታናሽነቱ ጀምሮ በውስጥዋ አደገ ። አባ መክሲሞስ አናጉንስጢስነት አባ ቴዎናስ ዲቁና ተፍጻሜተ ሰማዕት ጴጥሮስም ቅስና ሹመውታልና እርሱም ከታናሽነቱ ጀምሮ ንጹሕ ድንግል ነው።
አባ ጴጥሮስ በሰማዕትነት የሚሞትበት ጊዜ ሲቀርብ በግዞት ቤት ሳለ ይህ እለእስክንድሮስና አኪላስ ከውግዘቱ ይፈታው ዘንድ ስለ አርዮስ ወደርሱ ገብተው ለመኑት ስለርሱ አባ ጴጥሮስን ይማልዱለት ዘንድ ሁለቱን ለምኖአቸዋልና።
አባት ጴጥሮስ ግን በውግዘት ላይ ውግዘትን ጨመረበት እንዲህም ብሎ ነገራቸው የክብር ባለቤት ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀደደ ልብስ ለብሶ ተገለጸልኝ ልብሴን አርዮስ ቀደዳት አለኝ። ይህም የባሕርይ አንድነቴን ለያት ማለት ነው ውግዘቱንም እንድጨምርበት እርሱ አዘዘኝ።
ደግሞ እንዲህ ገለጠላቸው አኪላስ ሊቀ ጵጵስና እንዲሾም ከርሱ በኋላም እለእስክንድሮስ እንደሚሾም አርዮስን እንዳይቀበሉት በምንም ሥራው እንዳይተባበሩት አዘዛቸው።
አባ ጴጥሮስም ምስክርነቱን በፈጸመ ጊዜ አኪላስ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ፡፡ የአባት ጴጥሮስንም ትእዛዝ ተላልፎ አርዮስን ከውግዘቱ ፈታው። ቅስናም ሾመው ስለዚህም አኪላስ በመንበረ ሢመቱ ያለ ስድስት ወር አልኖረም በድንገት ሞተ።
ተገለጠለትና
‹‹ወደ ደብርህ ሂድ›› አለውና ደብረ አንጎት አደረሰው፡፡ በዚያም አባ በትረ ማርያምን አገኛቸው፡፡ እርሳቸውም ወደ ደብሩ እንዲመለስ ስለመከሩት ወደ ደብረ ሊባኖስ ተጉዞ ከአባ ጴጥሮስ ጋር በድጋሚ ተገናኘ፡፡ እርሳቸውም ‹‹ከእንግዲህስ ወዲህ ወዲያ አትበል፣ የሞቴም ጊዜ ደርሷልና አንተ በመንበሬ ተተክተህ ትሾማለህ፡፡ እንደእኔም ለብዙዎች አባት ትሆናለህ ነገር ግን መነኮሳት በከንቱ ወንጅለውህ ንጉሡ ያሥርሃል፣ ትሰደዳለህም›› ብለው ትንቢት ነገሩት፡፡
አባ ጴጥሮስም ባረፈ በ40ኛው ቀን መነኮሳቱ ተሰብስበው ዕጣ ቢጥሉ ለአባ ዕንባቆም ስለወጣ በእጨጌነት ሾሙት፡፡ ወዲያውም ሴቶችና ወንዶች መነኮሳትን በመልክ እንኳን እንዳይተያዩ በማድረግ እያስተማረ አገልግሎቱን ሲያከናውን ፈቃደ ሥጋቸውን ማሸነፍ የተሣናቸው መነኮሳት ‹‹ክብርህን ያሳንሳል፣ ስለአንተም አይጸልይም፣ እንዲያውም ‹ንጉሡ በአሳርና በመከራ ይሞታል› እያሉ ይናገራሉ›› ብለው በሐሰት ለንጉሡ በመንገር አጣሏቸው፡፡ ክፉዎችም በወጠኑት ሴራ ጻድቁ በንጉሡ ፊት ለፍርድ ቀረቡና ብዙዎቹ ‹‹ይገደሉ›› ብለው ፈረዱባቸው፡፡ ነገር ግን የዐፄ ልብነ ድንግል እንደራሴ ‹‹ከምንገድላቸው አስረን በግዞት ጉንጭ ወደሚባለው ቦታ እንውሰዳቸውና በዚያ ከሞቱ ይሙቱ›› ብሎ ሌላ ሀሳብ አቀረበ፡፡ ንጉሡም በዚህ ተስማምተው አቡነ ዕንባቆምን እጅና እግራቸውን አስረው እየደበደቡ አጋዟቸው፡፡
አቡነ ዕንባቆምም በግዞት ሆነው ሳለ ውኃ ሳይቀምሱ አንድ ዓመት ተቀመጡ፡፡ ከዚህም በኋላ እስከጎጃም ድረስ እየተዘዋወሩ ወንጌልን ሰበኩ፡፡ በርካታ አብያተ ክርስቲያናትንም አነጹ፡፡ እስከ ምድረ ቢዘን ድረስም ወረዱ፡፡ በዚህም ጊዜ ግራኝ አህመድ ተነሥቶ ክርስቲያኖችን በግፍ መግደል አብያተ ክርስቲያናትን ማቃጠል ጀመረ፡፡ አቡነ ዕንባቆም ለግራኝ በዐረብኛ ቋንቋ ደብዳቤ ጻፉለት፡፡
‹‹ክርስቲያኖችን አትግደሉ ተብሎ በቁርአን ተጽፎ እያለ አንተ ግን ለምን ትገድላለህ? አብያተ ክርስቲያናትንስ ለምን ታቃጥላለህ?›› ብለው ጻፉለት፡፡ ግራኝ አህመድም ደብዳቤአቸውን ካነበበ በኋላ ‹‹ከእንግዲህ ወዲህ ክርስቲያኖችን እንዳልገድል ቤተ ክርስቲያኖችንም እዳላቃጥል ከሚወጉኝ በቀር በክርስቲያን ላይ ክፉ እንዳልሠራ በአላህና ከሚስቶቹ በሦስቱ ጠለቅ ማልሁ›› ብሎ ተናገረ፡፡ ለአቡነ ዕንባቆምም ‹‹የክርስቲያን ሃይማኖት ከቁርአን የሚለይበትን መንገድ ትገልጽልኛለህና መጥተህ እየኝ›› ብሎ ልኮባቸው ነበር ነገር ግን አቡነ ዕንባቆም መንፈስ ቅዱስ ሳይፈቅድላቸው ቀርቶ ሳያገኙት ቀሩ፡፡ ዐፄ ልብነ ድንግል ሞቶ ልጁ ገላውዴዎስ ሲተካ አቡነ ዕንባቆምን ወደ እርሱ ይመጡ ዘንድ መልእክተኛ ላከባቸውና ሲመጡ ‹‹ስለ አህመድ ግራኝ ምን ባደረግ ይሻላል?›› አላቸው፡፡ እርሳቸውም ‹‹የሥልጣንህ ሰይፍ ከአንገቱ ላይ ሆናለች፡፡ እኔም ወደ ጎጃም እሄዳለሁ፣ እከተልሃለሁ፣ በደንቢያ ላይም እንገናኛለን፡፡ ሐነፋውያን (የግራኝ ዘሮች) በእጅህ ይጠፋሉ፡፡ አንተም በመጨረሻ በእነርሱ እጅ በሰማዕትነት ታልፋለህ›› ብለው ይመጣ ዘንድ ያለውን ሁሉ በትንቢት ነገሩት፡፡
በትንቢታቸውም መሠረት ዐፄ ገላውዴዎስ ግራኝን ካጠፋው በኋላ በሌላ ጊዜ የግራኝ ተከታይ ኢማም ኑር ገላውዴዎስን ገደለው፡፡ የንጉሡ እኅት ወለተ ጊዮርጊስም ወደ አቡነ ዕንባቆም መጥታ ያመነኩሳት ዘንድ ስለለመነችው ሥርዓተ ምንኩናን ፈጸመላት፡፡ ከገላውዴዎስ ቀጥሎ ዐፄ ሚናስ ሲነግስ አቡነ ዕንባቆምን መጥተው እንዲባርኩት ለመናቸው፡፡ እርሳቸውም ከባረኩት በኋላ ወደ ደብረ ሊባኖስ እንዲመለሱ ለመናቸው፡፡ እርሳቸውም እምቢ ቢሉትም ከብዙ ልመና በኋላ እሺ ብለውት ወደ ደብረ ሊባኖስ ሲሄዱ ልጆቻቸው በደስታ ተቀበሏቸው፡፡ እርሳቸውም እያስተማሩና መልካም አገልግሎታቸውን እየፈጸሙ አንድ ዓመት ከቆዩ በኋላ በ137 ዓመታቸው ሚያዝያ 21 ቀን 1553 ዓ.ም በሰላም ዐረፉ፡፡ በአባቶቻቸውም መቃር ተቀበሩ፡፡ ዐፄ ሠርፀ ድንግልም በ1580 ዓ.ም የአቡነ ዕንባቆምን ገድል አጻፈላቸው፡፡ ይህ ታሪካቸውም ከዚሁ ገድላቸው ላይ የተቀዳ መሆኑን የ1990 ዓ.ም የካቲት/መጋቢት እትም ሐመር ትገልጻለች፡፡
ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_21
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሚያዝያ ሃያ አንድ በዚህች ቀን የከበረ #አባት_ብሩታዎስ አረፈ፣ ዕለት የሐዋርያት አምሳል ሃይማኖትን የሚሰብክ #ዕጨጌ_ዕንባቆም መታሰቢያው ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ቡሩታዎስ_ሐዋርያ
ሚያዝያ ሃያ አንድ በዚህች ቀን የከበረ አባት ብሩታዎስ አረፈ፡፡ ይህም አባት የአቴና አገር የሆነ ከምሁራን ጥበበኞች አንዱ ነው እርሱም ደግሞ ደራስያን ከሆኑ ከአረጋውያን መምህራን ጋራ የተቆጠረ ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስንም ተገኝቶት ስለ ቀናች ሃይማኖት ተከራከረው። የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት የቀናች እንደሆነች ተረድቶ አመነ በሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እጅ ተጠምቆ የቤተ ክርስቲያንን ሕግና ሥርዓት ተማረ።
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ጳውሎስ በአቴና አገር ቅስና ሾመው። በታላቂቱ አገር በአቴና የመምህራን አለቃ ከሆነ ዘመደ ላሕም አብሮባ ከተባለ ከከበረ ዲዮናስዮስ ጋራ ተገናኘ። እርሱም የክብር ባለቤት ስለሆነ ጌታ ኢየሱስ ሃይማኖት ብዙ ገለጠለት ከውስጡ ሥውር የሆነበትንም ተረጐመለት እጅግም ዐዋቂ ሆነ።
ይህም አባት አምላክን የወለደች እመቤታችን የከበረች ድንግል ማርያም በዐረፈችበት ቀን ደርሶ በሐዋርያት መካከልም ቆመ በደረሰው ማኅሌትና ዝማሬ ጣዕም ባለው በመሰንቆ በዜማ ድምጽም አጽናናቸው። ከአይሁድና ከአሕዛብም ብዙዎቹን መልሶ ወደ ክብር ባለቤት ወደ ጌታ ክርስቶስ እምነት አስገባቸው። በተሰጠችውም ጸጋ ነግዶ ታላቅ ትርፍ አስገኘ።
ሐዋርያትም ኤጲስቆጶስነት ሊሾሙት በፈለጉ ጊዜ ጌቶቼ ይቅርታ አድርጉልኝ እኔ ለዚች ለከበረች ሹመት አልበቃሁምና የቅስናንም አገልግሎት ልፈጽም አልቻልኩምና ተውኝ ብሎ ማለዳቸው። በዕውቀቱና በሥራው ሰማያዊ ሀብትን ተቀብሎ ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔር ሔደ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ዕንባቆም_ጻድቅ_ዘደብረ_ሊባኖስ
ዳግመኛም በዚኽች ዕለት የሐዋርያት አምሳል ሃይማኖትን የሚሰብክ ዕጨጌ ዕንባቆም መታሰቢያው ነው፡፡ እርሱም በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ወንበር ለመሾም እስከተገባው ድረስ እግዚአብሔር ከእስልምና እምነት መርጦ ያመጣውና በደብረ ሊባኖስ ገዳም በዕጨጌነት ተሹሞ ቤተ ክርስቲያንን ያገለገለ ብዙ ሰማዕትነትንም የተቀበለ ታላቅ አባት ነው፡፡
አባ ዕንባቆም ዕጨጌ ዘደብረ ሊባኖስ፡- የሐዋርያት አምሳያቸው የሆኑ ሃይማኖትን የሚሰብኩ ዕጨጌ ዕንባቆም ሚያዝያ 21 ዓመታዊ መታሰቢያ በዓላቸው መሆኑን ስንክሳሩ ይጠቅሳል፡፡ እርሳቸው በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ወንበር ለመሾም እስከተገባቸው ድረስ እግዚአብሔር ከእስልምና እምነት መርጦ ያመጣቸው ታላቅ ሐዋርያ ናቸው፡፡ የመናዊው እጨጌ ዕንባቆም በዐረብ ምድር በየመን የተወለዱ ሲሆን አስቀድመው እስላም ነበሩ በኋላ ግን መጻሕፍትን መርምረው ዕውነትን ፈልገው በማግኘት በጌታችን በክርስቶስ አምነው ተጠምቀው ከመነኮሱ በኋላ በደብረ ሊባኖስ በአቡተ ተክለ ሃይማኖት ወንበር ተሾመው እስከማገለግል የደረሱ ታላቅ አባት ናቸው፡፡
አባ ዕንባቆም በ1416 ዓ.ም አካባቢ የመን ውስጥ ነው የተወለዱ፡፡ አባታቸው እስላም ሲሆን እናታቸው ግን አይሁዳዊት ነበረች፡፡ አባታቸው በሕጋቸው መሠረት ሁለት ሚስት አግብቶ ከአንደኛዋ 7 ልጆችን ሲወልድ ከአንዷ ደግሞ 2 ልጆችን ወልዷል፡፡ ከሁለቱ አንዱ አባ ዕንባቆም ነበር፡፡ እርሱም ቁርአንን እና ልዩ ልዩ ቋንቋዎችን በሚገባ እየተማረ አደገ፡፡ ለእስልምና ሃይማኖቱ ቀናተኛ የነበረው ዕንባቆም የክርስትና ስም ሲነሳበት አይወድም ነበር፡፡ 114ቱንም የቁርአን ምዕራፎች (ሱራዎች) በቃሉ ይዞ ቀን ከሌሊት ይጸልይባቸው ነበር፡፡ አንድ ቀን በቁርአን ላይ ስለመሞትና መነሣት የተጻፈውን ሲያነብ ኅሊናው ታወከ፡፡ ወዲያውም ወደ ቁርአን ሊቅ ዘንድ ሄዶ ትርጉሙን ጠየቀ፡፡ ነገር ግን የተሰጠው ምላሽ ‹‹ለምን አነበብከው?›› የሚል ነበር፡፡ (በነገራችን ላይ ቁርአኑን ከዐረብኛ ቋንቋ ውጭ ወደ ሌሎች ቋንቋዎች መተርጎም እንደሌለበትና በእርሱ ላይ ስለተጻፉት ነገሮች ጥያቄ መጠየቅ ክልክል እንደሆነ ቁርአኑ ለራሱ ከለላ የሰጠ መሆኑ ይታወቃል፡፡)
ዕንባቆምም ለጥያቄው መልስ በማጣቱ ይልቁንም ስለጠየቀ በቁጣ ስለተገሠጸ በእስልምና ላይ የነበረው ፍጹም እምነት ወደ ጥርጣሬ ተቀየረ፡፡ በዚያም ዘመን የኢትዮጵያ ንጉሥና የአዳል ንጉሥ ጦርነት ገጥመው አዳሎች አሸነፉና ንጉሡ 51 የኢትዮጵያ ምርኮኞችን ለአባ ዕንባቆም አባት ላከለት፡፡ ምርኮኞቹም ዕንባቆም በሃይማኖት ምክንያት ከወገኖቹ ጋር አለመስማማቱን አይተው ወደ ኢትዮጵያ እንዲሄድ መከሩት፡፡ እርሱም አብሯቸው በመካ በኩል ዳህላክን አቋርጦ ከነጋዴዎች ጋር ወደ ኢትዮጵያ ወደብ ደረሰ፡፡
ዕንባቆምም መጀመሪያ ካገኘውና አብሮት ከመጣው ወሰንጌ ጋር በመርሐ ቤቴ ተቀመጠ፡፡ በዚያም ትምህርተ ሃይማኖትን መማር ጀመረ፡፡ በግእዝ ንባብ የጀመረውም ትምህርት ተአምረ ማርያም ላይ ሲደርስ የእመቤታችን ፍቅሯ ስላደረበት ወደ ክርስትናው ሃይማኖት ይበልጥ ተሳበ፡፡ የዕንባቆም የዘወትር ጸሎት ‹‹ወደ ዕውነተኛው ሃይማኖት ምራኝ›› የሚል ሆነ፡፡ አንድ ቀንም በክረምት ወደ ዠማ ወንዝ ወርዶ ሳለ በአንድ ጎልማሳ የተመሰለ ቅዱስ ተገለጠለትና የውኃውን ሙላት በተአምራት አሻግሮ ‹‹በዚህች መንገድ ሂድ›› ብሎ ካሳየው በኋላ ተሰወረው፡፡ ዕንባቆምም መንገዱን ይዞ ሲጓዝ ደገኛው አባ ጴጥሮስ ካለበት ገዳም ደረሰ፡፡ በገዳሙም ማረፊያ ሰጥተውት በዚያ ተቀመጠና ብዙ ቅዱሳት መጻሕፍትን ተማረ፡፡ ከዚህም በኋላ መጠመቅ እንደሚፈልግ ለአባ ጴጥሮስ ነገራቸውና አጥምቀው ስመ ጥቀቱን ዕንባቆም አሉት፡፡ ዳግመኛም በዚሁ ገዳም መነኮሰ፡፡ አባ ጴጥሮስም ከጳጳሱ ከአቡነ ማርቆስ በተገናኙ ጊዜ ስለ አባ ዕንባቆም ነገሯቸው፡፡ ጳጳሱም አባ ዕንባቆምን አስጠርተው በዐረብኛ ቋንቋ የተጻፈን ወንጌል እንዲያነብላቸው ሰጡት፡፡ እርሱም በድንብ አነበበላቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ዲቁና ሰጡትና በቤታቸው አስቀመጡት፡፡ በዚህም ጊዜ ለጳጳሱ የሶርያን፣ የቅብጥን፣ የዕብራይስጥንና የአርመንን ቋንቋዎች ከነጽሕፈታቸው አስተማራቸው፡፡ ጳጳሱም ቆይተው ቅስና ሾሙት፡፡ አባ ዕንባቆም አንዱን የካቶሊክ እምነት ተከታይ ተከራክሮ ሲያሳምነው ጳጳሱ ተመልክተው በዚህ ደስ ተሰኝተው ከአንግብጦን ወረዳዎች ጢቆ በምትባል አገር ላይ ሾመው ላኩት፡፡ እርሱም በዚያ በእመቤታችን ስም የተዋበች ቤተ ክርስቲያን ሠርቶ ስሟን ቤተልሔም አላት፡፡ ዜናውም በሁሉ ዘንድ መሰማት ጀመረ፡፡ የአባ ዕንባቆም የዘወትር ጸሎት መዝሙረ ዳዊት፣ መኅልየ ሰሎሞን፣ ወንጌለ ዮሐንስ፣ ውዳሴ ማርያምና አርጋኖን ነበሩ፡፡ የደብረ ሊባኖስ ገዳም መነኮሳት ራእይ ተገልጦላቸው አባ ዕንባቆምን ‹‹የደብረ ሊባኖስ አለቃ ትሆናለህ ነገር ግን መነኮሳቱ ከንጉሡ ጋር ያጣሉሃል›› ብለው ነገሩት፡፡ እርሱም ከዚህ ሹመትና የሰይጣን ፈተና ሸሽቶ ወደ ምድረ ግብጦን ሄዶ የሐብላሽ በምትባል ገዳም ተቀመጠ፡፡ ‹‹አቤቱ የገዳም አስተዳዳሪ ከመሆን ጠብቀኝ›› እያለ በመጸለይ በዚህች ገዳም 3 ዓመት ተቀመጠ፡፡ ነገር ግን የትሩፋቱ ዜና በእንደግብጦንና በዳሞት ተሰማ፡፡ ወደ ላሊበላም ተጉዞ ከዋልድባ መነኮሳት ጋር በመገናኘት ወደ ኢየሩሳሌም ለመሄድ ቁርጥ አሳብ አድርጎ ሳለ መነኮሳቱ ‹‹ይህ አይሰምርልህምና ወደ ደብርህ ተመለስ›› ብለው መከሩት፡፡ እርሱ ግን ሳይመለስ ቅጻ ወደምትባል ሥፍራ ሄዶ በአንድ ገዳም ተቀምጦ የተለያዩ ተአምራትን እያደረገ ተቀምጦ ሳለ በደዌ ተያዘ፡፡ በቤተ ክርስቲያንም ሳለ የታዘዘ መልአክ
#ሚያዝያ_20
🔴#ስንክሳር ቅዱስ_በብኑዳ_ሰማዕት
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሚያዝያ ሃያ በዚህች ቀን ደንደራ ከሚባል አገር ደግሞ እልበደራ ከሚባል አገር ቅዱስ በብኑዳ በሰማዕትነት አረፈ። ይህ ቅዱስ ለብቻው የሚኖር ዕውነተኛ ተጋዳይ ነው የእግዚአብሔር መልአክም ተገልጦለት የመቀደሻ ልብስ ለብሰህ ወርደህ ለመኰንኑ ተገለጥለት አለው።
በዚያን ጊዜ መኰንኑ አርያኖስ ከመርከብ ወርዶ ወደዚያች አገር ወደብ መድረሻው ጊዜ ነበር። ይህንንም ባሕታዊ ፈልጎት አላገኘውም ነበር ። እነሆ ቅዱስ በብኑዳም በፈቃዱ መጥቶ ወደ መኰንኑ ሔዶ በክብር ባለቤት በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ የማምን በግልጥ እኔ ክርስቲያን ነኝ ብሎ በታላቅ ቃል ጮኸ።
መኰንኑም ፈልጎ ያጣው የታወቀ ባሕታዊ መሆኑን በአወቀ ጊዜ እንዲአሠቃዩት በእግር ብረትም አሥረው ከጨለማ ቤት እንዲጥሉት አዘዘ። በዚያን ጊዜም ብርሃን ወጣ የእግዚአብሔር መልአክም ከሕማሙ ፈወሰው አበረታው አጽናናውም።
በዚያችም አገር ስሙ ቄርሎስ የሚባል ምእመን ሰው ነበረ ከእርሱ ጋራም ሚስቱና ዐሥራ ሁለት ጐልማሶች ልጆቹ አሉ። እነዚህን ሁሉንም የከበረ በብኑዳ አስተማራቸው አጽናንቷቸውም ራሶቻቸውን ቆርጠዋቸው በሰማዕትነት ሙተው አክሊልን ተቀበሉ።
አርያኖስም ተቆጥቶ በቅዱሱ አንገት ከባድ ደንጊያ ሰቅለው ወደ ባሕር ይጥሉት ዘንድ አዘዘ፡፡ በእግዚአብሔር ኃይልም ከድንጋዩ ጋራ ዋኘ። ደግሞ ከሰሌን ዛፍ ላይ ይሰቅሉት ዘንድ አዘዘ፡፡ ያቺም ሰሌን ዐሥራ ሁለት ዘለላን አፍርታ ለመጪው ትውልድም መታሰቢያ ሆነች።
ከዚህም በኋላ የከበረች ራሱን ቆረጡት የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበለ በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_19
#ቅዱስ_ስምዖን_ሰማዕት_ዘአርማንያ
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሚያዝያ ዐሥራ ዘጠኝ በዚች ቀን የአርማንያ ሰው የፋርስ ኤጲስቆጶስ የከበረ ስምዖን በሰማዕትነት አረፈ ከእርሱም ጋር መቶ ሃምሳ ሰማዕታት።
ይህም ቅዱስ ትከሻ ነቃይ የተባለ የሐርመዝ ልጅ በሳቦር ግዛት ውስጥ ይኖራል። ይህም ሳቦር ሌላውን ንጉሥ ድል በሚያደርግ ጊዜ አሥሮ ትክሻውን ይመዝዘዋልና ትከሻ ነቃይ ተባለ። ይህም ከሀዲ ለጣዖት እንዲሰግዱ እያስገደደ ምእመናንን በጽኑዕ ሥቃይ አሠቃያቸው።
ይህም የከበረ አባ ስምዖን ለንጉሥ ሳቦር መልእክት ጽፎ ላከለት። እንዲህ የሚል የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከበረ ደሙ የዋጃቸው ከሰው ተገዢነት ድነዋል የክብር ባለቤት የክርስቶስ ተገዢ ናቸውና። ስለዚህ ተገዢ መሆን ከተሠራው ሕግ አብዝቶ መገበርም አይገባቸውም። የሕያው እግዚአብሔርን ሕግ ለለወጡ ከሀድያን አይገዙም። ስለ እርሳቸው ደሙን በአፈሰሰ በክብር ባለቤት በክርስቶስ ስም እንዲሞቱ እነርሱ ይመርጣሉ።
ንጉሥ ሳቦርም ይህን መልእክት በአነበበ ጊዜ በዚህ አባት ላይ እጅግ ተቆጣ በሁለት ሰንሰለትም አሥሮ በእሥር ቤት ጣለው በዚያም ሃይማኖታቸውን ክደው ሰማይን ያመለኩ እነርሱም በሌላ የታሠሩ ብዙ እሥረኞችን አገኘ።
ይህ ቅዱስም ገሠጻቸው አስተማራቸው እነርሱም ተጸጽተው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምነው መሰከሩ ራሶቻቸውንም ቆረጡአቸውና የሕይወት አክሊልን ተቀበሉ።
ከዚህም በኋላ ይህን አባት ወደ ምስክርነት ሸንጎ አቀረቡት ከእርሱም ጋራ መቶ ሃምሳ ሰዎች አሉ እነርሱም አንገታቸውን እስከ ቆረጡአቸውና አክሊል እስከ ተቀበሉ ድረስ ያጽናናቸው ነበር።
ከእርሳቸውም አንዱ ሰይፍን ከመፍራት የተነሣ ደንግጦ ሃይማኖቱን ሊክድ ወደደ በዚያ ከቆሙት አንዱ አትደንግጥ የሰይፍ በትር ዓይንህን ከሸፈንክ ምንም አይደለም ጽና። ከሰማዕታት ጋራ ተቆጥረህ ከክብር ባለቤት ክርስቶስ ጋራ ለዘላለም ነግሠህ ትኖራለህ ብሎ አጽናናው። እንዲሁም አደረገ የሕይወት አክሊልንም ተቀበለ።
ስሙ ባሴቅ የተባለ ያንን ያጥናናውን ሰው ከሰሱት ንጉሡም አስቀርቦ ምላሱን አስቆረጠው። ቆዳውንም አስገፈፈውና ነፍሱን አሳለፈ የድል አክሊልንም ተቀበለ። ከዚህ በኋላም የከበረ ስምዖንን ወደ እርሱ አቅርቦ ለአማልክት ስገድ ያለዚያ በጽኑ ሥቃይ አሠቃይሃለሁ አለው። ቅዱሱም ትእዛዙን አልሰማም ሥቃዩንም አልፈራም ያን ጊዜም ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዝዞ ቆረጡት በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነትን አክሊል ተቀበለ።
ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን ።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_18
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሚያዝያ ዐሥራ ስምንት በዚህች ቀን የቅዱስ ሱስንዮስ አገልጋይ #ቅዱስ_አውሳብዮስ በሰማዕትነት አረፈ፣ የአባ ብሶይ ወንድም #አባ_ጴጥሮስ በሰማዕትነት አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አውሳብዮስ_ሰማዕት
ሚያዝያ ዐሥራ ስምንት በዚህች ቀን የቅዱስ ሱስንዮስ አገልጋይ ቅዱስ አውሳብዮስ በሰማዕትነት አረፈ፡፡
ዲዮቅልጥያኖስም ቅዱስ ሱስንዮስን በሚያሠቃየው ጊዜ ንጉሥ ሆይ አውሳብዮስ የሚባል አገልጋይ አለው፣ እርሱም በፍጹም ልቡ እንደ ጌታው ክርስቶስን ያመልከዋል፡፡ የአንተን አማልክ አያመልክም አሉት፡፡ አምጡት አለ፡፡ ወደ እርሱ በቀረበ ጊዜ ስለ ሃይማኖቱ ጠየቀው፡፡ እርሱም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ፡፡ ንጉሱም ብዙ አባበለው አማልክቶቹን ማምለክ በመተው ገሰጸው፡፡ ቅዱሱም የዕውነተኛ አምላክ የአግዚአብሔርን አምልኮ በመተው ንጉሡን መልሶ ገሰጸው፡፡
ስለዚህም ንጉሡ ቁጣን ጨመረ ሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ፡፡ ይህም ቅዱስ ከጌታ ከሱስንዮስ ቀድሞ የሰማዕትነትን አክሊል በመንግስተ ሰማያት ተቀበለ፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ጴጥሮስ_ሰማዕት
በዚችም ዕለት የአባ ብሶይ ወንድም አባ ጴጥሮስ በሰማዕትነት አረፈ። የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም ሲድራቅ የእናቱ ስም ማርያም ነው። ይህንንም ቅዱስ በወለዱት ጊዜ ከርሳ የምትባል የእናቱ እኅት ወስዳ ከልጅዋ ጋራ አሳደገችው። ሰባት ዓመትም በሆናችው ጊዜ ወደ መምህር ወሰደቻቸውና የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሕጉንም ተማሩ በጾም በጸሎትም ሲጋደሉ ኖሩ።
የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤልም ተገለጠላቸው ስለ ክብር ባለቤት ክርስቶስ ስም ምስክር እንደሚሆኑ ነገራቸው።
ከጥቂት ወራትም በኋላ ሰይጣን ዲዮቅልጥያኖስን አስቶት ለጣዖት በሰገደ ጊዜ እሊህን ቅዱሳን ክርስቲያኖች እንደሆኑ ነገር ሠሩባቸው። የእንዴናው ገዥ አርያኖስም ወደርሱ አስቀርቦ ለጣዖት እንዲሰግዱ ግድ አላቸው እምቢ በአሉትም ጊዜ ደማቸው እስኪፈስ ከባላ ላይ ሰቅለው እንዲገርፉአቸው አዘዘ።
ከጾምና ከስግደት የተነሣ ሥጋው ስለደከመ የሥቃዩ ሕማም ለጴጥሮስ ታወቀው ያን ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ከሕማሙ ፈወሰው። አርያኖስም አይቶ ጴጥሮስን ወደ ምሥራቅ ሀገር ወስደው በዚያ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡት አዘዘ።
አባ ብሶይም በእሥር ቤት እያለ መልአክ ነጥቆ ወደ ወንድሙ ወደ ጴጥሮስ አደረሰው፡፡ እርስ በርሳቸውም ተቃቅፈው ተሳሳሙ በሰማያዊት ኢየሩሳሌምም እንዲሰበስባቸው ወደ ጌታችን ጸለዩ እነሆ ወደ እርሳቸውም ከሰማይ ቃል መጣ። እንዲህ የሚል ተጋዳዮች ሆይ በሰማያት በብዙ ጉባኤ መካከል ትኖራላችሁና ሰላም ይሁንላችሁ ሥጋችሁም በምድር አይለያይም። ከዚህም በኋላ መልአክ አባ ብሶይን ወደ እሥር ቤት መለሰው።
ጭፍሮችም ኃያል ድል አድራጊ አባ ጴጥሮስን ራሱን ቆረጡ ሥጋውንም በዕንጨት ላይ ሰቀሉ። አባ ብሶይም በጭልታ ይሰደው ዘንድ የእሥር ቤት ጠባቂውን ለመነው ሒዶም የአባ ጴጥሮስን ሥጋ ዋጀው በሽቱ አድርጎ ገንዞም በሥውር ቦታ ቀበረ።
ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_17
#ሐዋርያው_ቅዱስ_ያዕቆብ_ወልደ_ዘብዴዎስ
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሚያዝያ ዐሥራ ሰባት በዚህች ቀን የዘብዴዎስ ልጅ የወንጌላዊ ዮሐንስ ወንድም ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም በእስያ ውስጥ ከአስተማረ በኋላ ዕርቅ በተገኘባት በእውነተኛ አምላክ በጌታችን ወንጌል ሊያስተምራቸው ወደ ተበተኑ ወደ ዐሥራ ሁለቱ ነገድ ወጣ። እነርሱም አንድ አምላክን የሚአመልኩ አልነበሩም እየራሳቸው የመረጡትን የሚአስቷቸው ጣዖታትን ያመልኩ ነበረ እንጂ። ከቄሣር ሥልጣን በታች የተሾመ ኄሮድስም ሹመቱ በሚዳብር መንግሥቱ በሚያጽና ገንዘብ ብዙ ግብር እንዲገብሩ እጅ መንሻም እንዲአስገቡ አዘዘ።
ያዕቆብ ግን ወደእርሳቸው በደረሰ ጊዜ በአገራቸው ቋንቋ ሰበከላቸው የፍጥረትን ሁሉ ቋንቋ ማወቅን እግዚአብሔር ሰጥቶት ነበርና የሚያውቀው የሰው ቋንቋ ብቻ አልነበረም የእንስሳና የአራዊት የሰማይ ወፎችንም ቋንቋ ነበረ እንጂ። በውስጣቸው በሰበከም ጊዜ የከፋ ሥራቸውን ትተው በሕያው እግዚአብሔር በአንድ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወት በሆነ መንፈስ ቅዱስ ነፍሶቻቸው በእጁ ውስጥ በተያዙ በአንድ አምላክ እንዲያምኑ አዘዛቸው። እርሱም በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ የሚመጣ ነው። ዳግመኛም በማይጠፋና በማይበላሽ በሰማያት ድልብ ይሆናቸው ዘንድ ከገንዘባቸው ለችግረኞችና ለድኆች እንዲመጸውቱ አዘዛቸው።
ትምህርቱንም በሰሙ ጊዜ ከክፋ ሥራቸው ተመልሰው በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። ሐዋርያ ቅዱስ ያዕቆብም ትምህርቱን ፈጥነው ስለተቀበሉት እጅግ ወደዳቸው በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው በየአገራቸው ቤተ ክርስቲያን ሠራላቸው። ዳግመኛም ከእንስሶቻቸው ከሚዘሩአቸው እህሎችና ወይን አትክልቶች ፍሬዎች ለካህናትና ለድኆች ምግብ ሊሆን ለቤተ ክርሰቲያን የመጀመርያውን መባ እንዲሰጡ አዘዛቸው። ሕዝቡም በአንድ ቃል ያዘዝከንን ሁሉ እኛ እናደርጋለን አሉት። ከዚህ በኋላ ከእንስሳት መጀመሪያ የተወለደውን ከእህሉም ቀዳምያቱንና ዓሥራትን ለቤተ ክርስቲያን አመጡ።
ኄሮድስም ቅዱስ ያዕቆብ ለቤተ ክርስቲያን መባ ይሰጡ ዘንድ እንዲሚያዝ በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ ጭፍራ ልኮ ወደርሱ አስመጣውና "ሕዝቡ ገንዘባቸውን ሁሉ ለድኆች ምጽዋትና ለቤተ ክርስቲያን መባ እንዲሰጡ የምታዝ አንተ ነህን" አለው። "አዎን እኔ ነኝ" አለው ያን ጊዜ ኄሮድስ ተቆጥቶ ራሱ በሰይፍ አንገቱን መትቶ ቆረጠው። በኢየሩሳሌምም ሁከትና ሽብር ሆነ ደግሞ ከፋሲካ በዓል በኋላ ሊገድለው አስቦ የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ ወስዶ አሠረው የእግዚአብሔር መልአክም ኄሮድስን ቀሠፈው ተልቶ ተበላሽቶ ሞተ ልዑል አምላክን አላከበረውምና። የቅዱስ ያዕቆብን ሥጋ ግን ምዕመናን ወሰዱት ገንዘው በቤተ መቅደስ ውስጥ ቀበሩት።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የሐዋርያው የቅዱስ ያዕቆብ በረከት ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_16
#ቅዱስ_አንቲቦስ
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሚያዝያ ዐሥራ ስድስት በዚህች ቀን የበአርማ አገር ኤጲስቆጶስ ቅዱስ አንቲቦስ በሰማዕትነት አረፈ። እርሱም የመለኮትን ነገር ለሚናገር ለወንጌላዊው ዮሐንስ ረድኡ ነው። እርሱም ከአይሁድ ወገን በግዛቱ ውስጥ አንድ ሰው የሚታይ እስከ አልሆነ ድረስ አይሁድን ያጠፋቸውና ኢየሩሳሌምንም በአፈረሳት በአስባስያኖስ ልጅ በግማትያኖስ ዘመን ነበረ። ከእስራኤል መንግሥት ትውልድ ያላቸውንም ብዙዎችን ገደላቸው ለመንግሥቱና ለራሱ ስለ ፈራ ነው።
የክብር ባለቤት ክርስቶስ አምላካቸውና ንጉሣቸው ድል አድራጊና እነርሱም ወገኖቹ እንደሆኑ ክርስቲያኖች ይናገራሉና ስለዚህ ከአማንያን ብዙዎችን ገደለ። ወንጌላዊ ዮሐንስም ከእርሱ ሸሸ የዮሴፍ ልጅ በሮሜ ከተማ ታሥሮ ሳለ ወደ ኢየሩሳሌም ጭፍራ ልኮ የይሁዳን ተወላጆች ወደርሱ አስመጣቸው የክብር ባለቤት ስለሆነ ክርስቶስ መንግሥት በጠየቃቸው ጊዜ ክርስቶስ ሰማያዊ ንጉሥና በሰማያት የሚኖር እንደሆነ በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ ለሁሉም እንደየሥራው ሊከፍለው ዳግመኛ ይመጣ ዘንድ እንዳለው አስረዱት።
ይህንንም ሰምቶ እጅግ ፈራ ክርስቲያኖችንም ማሠቃየቱን ተዋቸው። ቅዱስ አንቲቦስን ግን የክብር ባለቤት ክርስቶስን ሊአስክደው ሽቶ ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃየው እርሱም በሥቃዩ ውስጥ በመታመን ጸና ፣ ከዚህም በኋላ ከናስ በተሠራ በላመ ፈጅ ጋን ውስጥ አድርገው ከበታቹ እሳትን አነደዱ እርሱም በውስጧ ሁኖ ስለከበረ ስሙ ምስክር ሊሆን ያደለው እግዚአብሔርን ፈጽሞ ያከብርና ያመሰግን ነበር።
ከዚህም በኋላ ስሙን ለሚጠሩና መታሰቢያውን ለሚያደርጉ ከነፍስ ከሥጋ ደዌ ሁሉንም ይፈውሳቸው ዘንድ ከእግዚአብሔር ፈለገ። ከዚህም በኋላ ከነሐስ በተሠራው በላመ ፈጅ ውስጥ የምስክርነቱን ተጋድሎ ፈጽሞ ነፍሱን ሰጠ። በድኑንም ሲጥሉት ምእመናን አንሥተው በታላቅ ክብር ፈጽሞ እያመሰገኑ ወስደው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩት።
እርሱም አስቀድሞ በግዞት ቤት ሳለ ከወንጌላዊ ዮሐንስ ዘንድ የሚያጽናናውና የሚአረጋጋው ቸር ጠባቂ እረኛና ታማኝ አገልጋይ ካህን የሚለው መልእክት ወደርሱ መጣ። እንዲህም ብሎ ሁለተኛ ነገረው በሰማዕትነት እንደሚሞት አንተ ከከበሩ ሐዋርያትና ከሰማዕታት ጋራ ተቆጥረሃል። ደግሞ ከሥጋው ጣፋጭ የሽቱ ቅባት እንደሚፈስ ስለርሱ ተነገረ እርሱም መዓዛው እጅግ ጣፋጭ የሆነ በእምነት ለሚሻው ሁሉ እስከ ዛሬ ጠቃሚ የሆነ ነው በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።
ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_14
#አባ_መክሲሞስ_ሊቀ_ጳጳሳት
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሚያዝያ አሥራ አራት በዚች ቀን በእስክንድርያ ለተሾሙ ሊቃነ ጳጳሳት ዐሥራ አምስተኛ የሆነ የከበረ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ መክሲሞስ አረፈ። ይህም አባት መንፈሳዊና በሥራው ሁሉ እግዚአብሔርን የሚፈራ ነው።
እርሱም ከእስክንድርያ ሰዎች ወገን ነው ወላጆቹም ሃይማኖታቸው የቀና ነበረ የዮናናውያንንም ጽሕፈትና መጽሐፋቸውን ጥበባቸውንም ሁሉ ተምሮ ፍጹም አዋቂና አስተዋይ ሆነ በዮናኒ ቋንቋ።
ከዚህም በኋላ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ልዑል እግዚአብሔር የሠራውን ሕግና ሥርዓት ተማረ። አባት ያሮክላም ዲቁና በእስክንድርያ ሾመው ከዚያም በኋላ ዲዮናስዮስ ቅስና ሾመው በተሾመባት ሁሉ ላይ ተጠምዶ የሚአገለግልና የሚጋደል ሆነ ።
አባ ዲዮናስዮስም በአረፈ ጊዜ አዋቂዎች ኤጲስቆጶሳትና ካህናት ማኅበሩም ሁሉ መረጡት በእግዚአብሔርም ፈቃድ በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበር ላይ ሊቀ ጳጳሳት አድርገው ሾሙት ።
ዲዮናስዮስም ስለ ጳውሎስ ሳምሳጢ በአንጾኪያ ከተማ የተጀመረው የኤጲስቆጶሳት ማኅበር ጉባኤ ተጀመሮ ሳይፈጸም አረፈ። ይህም አባት መክሲሞስ በተሾመበት ወንበር በተቀመጠ ጊዜ በማኅበሩ ጉባኤ ስለ ተወሰነውና ከሀዲው ጳውሎስ ሳምሳጢን እንደአወገዙት ከጉባኤው ሹማምንት መልእክቶች ወደርሱ ደረሱ። በትምርቱ ያመኑትንም መልእክቶቹንም ካህናቱ በአንድነት በተሰበሰቡበት አነበበው።
ከዚያም በኋላ ዳግመኛ ከራሱ መልአክቶችን ጽፎ የጳውሎስ ሳምሳጢን ስሕተት ያርቅ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እንዲጸልዩና እንዲማልዱ እያዘዘ ወደ ግብጽ አገሮች ሁሉ ወደ ኢትዮጵያና ወደ ኖባ አገር ላካቸው ።
የክብር ባለቤት ጌታችን ልመናቸውን ተቀበለ ይህም ከሀዲ ከጥቂት ቀኖች በቀር አልኖረም በፍጥነት አጠፋው እንጂ የረከሰች ሃይማኖትንም ከዓለም አስወገደ አራቀ።
በዚህም አባት ዘመን ከምሥራቅ አገር ማኒ የሚባል ራሱን የዕውነት መንፈስ ጰራቅሊጦስን ያደረገና ክፉ ስሕተትን የሳተ ሰው ተገለጠ። ወደ ሶርያ ምድርም ደረሰ አርኬላዎስ የሚባል ኤጲስቆጶስም ከእርሱ ጋራ ተከራከረ ስሕተቱንም ገላልጦበት አሳፍሮ ከአገሩ አሳደደው ። ከዚያም ተመልሶ ወደ ፋርስ ሔደ ራሱንም ነቢይ አደረገ የፋርስ ንጉሥ ብህራምም ይዞ ከሁለት ሠነጠቀው። ተከታዮቹ የሆኑ ሁለት መቶ ሰዎችን ዘቅዝቆ እስከ ወገባቸው በምድር ውስጥ ተከላቸው እነሆ ከሰው አትክልትን ተከልሁ አለ።
ይህም አባት መንጋውን በመጠበቅ ሲጋደልና በቀናች ሃይማኖትም ሲያጸናቸው ኖረ ከመናፍቃንና ከከሀድያን ችግር እስከ አረፈባት ቀን ድረስ በድርሳናትና በተግሣጻት ጠብቆ አዳናቸው። በማርቆስም ወንበር ዐሥራ ስድስት ዓመት ኑሮ በሰላም አረፈ።
በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለም አሜን ትኑር ።https://t.me/finotebirhan12
የተከበራችሁ የሰ/ት/ቤታችን አባላት የሰ/ት/ቤታችንን የዩቲዩብ ቻናል ሰብስክራይብ ያድርጉ።
https://youtube.com/@finotebirhan7530
የተከበራችሁ የሰ/ት/ቤታችን አባላት የሰ/ት/ቤታችንን የዩቲዩብ ቻናል ሰብስክራይብ ያድርጉ።
#ስንክሳር የቅዱስ_አባ_ሜልዮስ_አርድእት_አባ_ኢያሱና_አባ_ዮሴፍ
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሚያዝያ ዐሥራ ሦስት በዚች ቀን ሁለት የከበሩ መነኰሳት የአባ ሜልዮስ አርድእት አባ ኢያሱና አባ ዮሴፍ በሰማዕትነት አረፉ እርሱም አባ ሜልዮስ በኮራሳን ተራራ በሰማዕትነት የአረፈ ነው።
እነሆ መላው ምስክርነታቸው ከመንፈሳዊ አባታቸው አባ ሜልዮስ ጋራ በዚሁ ወር በሃያ ስምንት ቀን እንዲህ ተጽፎ ይገኛል።
ቅዱስ ሜልዮስ ሰማዕት ኮራሳት በምትባል አገር በተራራ ባሉ ዋሻዎች ከሁለት አርድእት ጋር ይኖር ነበር፡፡ እርሱም በተጋድሎ ሕይወቱ እጅግ የተመሰገነ ነው፡፡ እግዚአብሔርም በአባ ሜልዮስ እጅ ብዙ አስገራሚ ተአምራትን አደረገ፡፡ ከዕለታትም በአንደኛው ቀን በመንገድ ሲሄድ የሞተ ሰው አገኘ፡፡ የአገሪቱ ሰዎችም አንዱን መነኮስ ‹‹የገደልከው አንተ ነህ›› ብለው ይዘው አስጨነቁት፡፡ የከበረ አባ ሜልዮስም ወደ ጌታችን ከጸለየ በኋላ ሬሳውን ‹‹በውኑ የገደለህ ይኽ መነኩሴ ነውንመንፈስ?›› አለው፡፡ የሞተውም ሰው አፈፍ ብሎ ተነሥቶ ‹‹እርሱስ አልገደለኝም ነገር ግን ብዙ ገንዘቤን ከአንድ ቄስ ዘንድ አደራ አስጠበቅሁ፣ ስለዚህም ገደለኝ፣ ከዚህም ጣለኝ›› ብሎ መሰከረ፡፡ ዳግመኛም አባ ሜልዮስን ‹‹ወደዚያ ቄስ ዘንድ ሄደህ ገንዘቤን ተቀብለህ ለልጆቼ ስጥልኝ›› ብሎ ለመነው፡፡ አባ ሜልዮስም ‹‹እስከትንሣኤ ቀን በሰላም አርፈህ ተኛ›› ብሎት ተመልሶ ዐረፈ፡፡
የኮራት አገር ንጉሥ ሁለቱ ልጆች ሠራዊቶቻቸውን ይዘው ለአደን ወደ ተራራው ቢወጡ የከበረ ቅዱስ አባ ሜልዮስን ማቅ ለብሶ ጠጉሩም የረዘመ ሆኖ አገኙት፡፡ የንጉሡ ልጆችም አባ ሜልዮስን ባዩት ጊዜ ፈርተውት ‹‹ሰው ነህን ወይስ መንፈስ?›› ብለው ጠየቁት፡፡ እርሱም ‹‹በዚህ ተራራ ውስጥ የምኖር ለጌታዬ ለኢየሱስ ክርስቶስ የምሰግድ ሰው ነኝ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ይህን ሲናገር ሰምተው ‹‹ከእሳትና ከፀሐይ በቀር አምላክ የለም፣ እንዳንገድልህ ሠዋላቸው›› አሉት፡፡ አባ ሜልዮስም የሰው ፍጥረት ሁሉ እሳትንና ፀሐይን ለፈጠረ አምላክ ብቻ መገዛት እንዳለት ነገራቸው፡፡ የንጉሡ ልጆችም አባ ሜልዮስን ከሁለቱ አርድእቱ ከአባ ኢያሱና ከአባ ዮሴፍ ጋር ይዘው ጽኑ ሥቃይ አሠቃዩአቸው፡፡ ከብዙ አሠቃቂ ሥቃይም በኃላ በዚህ ወር በ13ኛው ቀን የሁለቱን አርድእት አንገታቸውን በሰይፍ ቆረጧቸውና የሰማዕትነታቸው ፍጻሜ ሆነ፡፡
አረጋዊ ቅዱስ አባ ሜልዮስን ግን ለ15 ቀናት ሲያሠቃዩት ኖሩ፡፡ ከዚህም በኋላ ከመካከላቸው አቁመው አንዱ በፊት አንዱ በኋላ ሆነው በፍላጻ እየነደፉ በእጅጉ ያሠቃዩት ጀመር፡፡ አረጋዊ አባ ሜልዮስም ‹‹እኔን በፍላጻዎቻችሁ ለመግደል እንዳሠቃያችሁኝ እናንተም ደግሞ በገዛ ፍላጻዎቻችሁ ትሞቱ ዘንድ አላችሁ›› በማለት ትንቢት ተናገረባቸው፡፡ እነርሱም ቃሉን በመናቅ ነፍሱን እስከሚያሳልፍና ምስክር ሆኖ የሰማዕትነት አክሊልን እስከሚቀበል ድረስ በፍላጻዎች ነደፉት፡፡ እርሱም ሰማዕትትነቱን በዚህ ፈጽሞ የክብር አክሊልን ተቀዳጀ፡፡
አባ ሜልዮስን በግፍ የገደሉት ጭፍሮቹም በማግሥቱ እንደልማዳቸው ለአደን በወጡ ጊዜ የዱር አህያ አገኙ፡፡ ተከታትለውም ቀስታቸውን አስፈነጠሩ፡፡ እግዚአብሔርም ፍላጻቸውን ወደራሳቸው መልሶ ቅዱስ አባ ሜልዮስ እንደተናገረ በራሳቸው ፍላጻ ሞቱ፡፡
የሰማዕታቱ የአረጋዊ አባ ሜልዮስ፣ የአባ ኢያሱና የአባ ዮሴፍ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን
ሚያዝያ 13 የመልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል ወርሃዊ መታሰቢያ በዓሉ ነው።https://t.me/finotebirhan12
የተወደዳችሁ የሰ/ት/ቤታችን የወጣትና የባለትዳር ክፍል አባላት ዛሬ የአባታችን የቅዱስ ሚካኤል ወርሐዊ መታሰቢያ በዓል በመሆኑ ማታ ቀድመን በመገኘት የአውደ ምሕረት ጉባኤ ላይ የአገልግሎት ልብስ በመልበስ በዝማሬ እና በመስተንግዶ አገልግሎት በመሳተፍ የበረከቱ ተካፋይ እንሁን።
🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_12
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሚያዝያ ዐሥራ ሁለት በዚህችም ዕለት የመላእክት አለቃ #ቅዱስ_ሚካኤልን እግዚአብሔር ወደ #ነብዩ_ኤርምያስ ላከው፣ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ #አባ_እለእስክንድሮስ አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ኤርምያስ_ነቢይ
ሚያዝያ ዐሥራ ሁለት በዚህችም ዕለት የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን እግዚአብሔር ወደ ነብዩ ኤርምያስ ላከው፡፡ ጠባቡና ረግረግ ከሆነ እሥር ቤት ሴዴቅያስ ንጉሥ በአሠረው ጊዜ የንጉሡ ባለሟልና የጭፍራ አለቃ የሆነው አቤሜሌክ አወጣው።
ያንጊዜም የኢየሩሳሌምን ጥፋት እንዲያይ መራራ ምርኮንም እንዳይቀምስ ኤርምያስ ነብይ መረቀው እንዲሁም ሆነ። ስሳ ስድስት ዓመትም ተኝቶ ኖረ ከእርሱ ጋራ ወይንና በለስ ነበረ አልተለወጠም የእስራኤል ልጆች ከምርኮ እስቲመለሱ በለሱንም ከደብዳቤ ጋራ ወደ ኤርምያስ ባቢሎን አገር ላከው።
ስለዚህም የዚህን የከበረ መልአክ ሚካኤልን በየወሩ በዐሥራ ሁለት ቀን መታሰቢያውን እንድናደርግ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አዘዙን።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_እለእስክንድሮስ_ዘኢየሩሳሌም
በዚህች ቀን የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ አባ እለእስክንድሮስ አረፈ። ይህ ቅዱስም አስቀድሞ በቀጰዶቅያ አገር ኤጲስቆጶስነት ተሹሞ ነበር። እርሱም የከበሩ ቦታዎችን ተሳልሞ በረከት ተቀብሎ ወደ አገሩ ሊመለስ አስቦ ኢየሩሳሌም መጣ።
በኢየሩሳሌምም ስሙ በርኪሶስ የሚባል መቶ ዐሥር ዓመት የሆነው ጻድቅ ሰው ነበረ ሹመቱንም ሊተው ይወድ ነበረ ወገኖቹ ግን አልለቀቁትም።
ቅዱስ እለእስክንድሮስም ሥራውን ፈጽሞ ወደ አገሩ ቀጰዶቅያ ሊመለስ በፈለገ ጊዜ እግዚአብሔር እንዲህ የሚል ቃል እነሆ ከሰማይ አሰማ። ወደ እገሌ በርውጡ አስቀድሞ የሚገባውንም ይዛችሁ በላያችሁ ኤጲስቆጶስነት ሹሙት። ያን ጊዜም ሲወጡ አባ እለእስክንድሮስን አገኙትና ያዙት። እርሱም እኔ የቀጰዶቅያ ኤጲስቆጶስ ነኝ የክብር ባለቤት ክርስቶስ በእነርሱ ላይ የሾመኝን መንጋዎቼን ልተው አይቻለኝም አላቸው።
እነርሱም ከሰማይ ስለሰሙት ስለዚያ ቃል ስለርሱም እንደአመለከታቸው ነገሩት። ይህ ነገር ከእግዚአብሔር እንደሆነ በተረዳ ጊዜ ለበዓሉም የተሰበሰቡ አባቶች መከሩት ቃላቸውንም ተቀበለ ወደ ሀገሩ ቀጰዶቅያም እንዲህ ብሎ መልእክት ጽፎ ላካት። ይቅርታ አድርጉልኝ በእኔ ላይ አትዘኑ በእናንተ ላይም ኤጲስቆጶስ በእኔ ፈንታ ሹሙ እናንተም የተፈታችሁ ናችሁ ያቺን መልእክትም ከእርሱ ጋራ አብረው ከመጡ ከቀጰዶቅያ ሰዎች ጋራ ላከ።
ከዚህም በኃላ እየተራዳው አምስት ዓመት ያህል ከአባ በርኪሶስ ጋራ ኖረ። ከዚህም በኃላ ሽማግሌው አባ በርኪሶስ አረፈ። አባ እለእስክንድሮስም መንጋውን ተረክቦ እንደ ሐዋርያት በመልካም አጠባበቅ ጠበቃቸው። ከሀዲ መክስምያኖስም በነገሠ ጊዜ ይህን አባት ይዞ በየአይነቱ በሆነ ሥቃይ አሠቃየው። ከዚያም በላዩ የሚያደርግበትን እስከሚያስብ ድረስ አሠረው፡፡ ጌታችንም ይህን ከሀዲ ፈጥኖ አጠፋው፣ ወገኖቹም ይህን አባት እለእስክንድሮስን ከእሥር ቤት አወጡት።
ገርድያኖስም በነገሠ ጊዜ ጸጥታና ሰላም ሆነ ከክርስቲያን ወገኖች ላይም ጥቂት ወራት መከራው ጸጥ አለ። ገርድያኖስም በሞተ ጊዜ በርሱ ፈንታ አማኒ የሆነ ፊልጶስ ነገሠ። እርሱም በክብር ባለቤት በጌታችን ስለሚአምን በክብር ባለቤት በጌታ ክርስቶስ ሰም የታሠሩትን ምእመናንን ፈታቸው እጅግም አከበራቸው ይህም አባት በጸጥታ ኖረ።
ከዚህም በኃላ ከሀዲ ዳኬዎስ ተነሣ ፊልጶስንም ገድሎ መንግሥቱን ወሰደ ክርስቲያኖችንም እጅግ አሠቃያቸው ይህንንም አባት ያዘው ብዙዎችንም የቤተ ክርስተያን ሊቃውንት ጽኑ ሥቃይም አሠቃያቸው። ይልቁንም ይህን አባት አብዝቶ አሠቃየው ጽኑ ግርፋትንም ገርፎ ስለት በአላቸው በትሮች የጐኑ ዐጥንቶች ተሰብረው ወደሆዱ እስቲገቡ አስመታው።
ከዚህም በኃላ እስከ እሥር ቤት ጐትተው በዚያ እንዲጥሉት አዘዘ እንዲሁም አደረጉበት።እግዚአብሔር ለመረጣቸው ያዘጋጀውን መንግሥተ ሰማይ እስከ ወረሰ ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ እስከ ሰጠ ድረስ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እየታመነ በዚያ ወድቆ ኖረ በጸሎቱ የምትገኝ በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።
ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።https://t.me/finotebirhan12
አሳዛኝ ዜና
በጥንታዊው የሶደሬ ፈለገ ሰላም መድኃኔዓለም ገዳም ላይ የታጠቁ ኃይሎች የቦንብ ጥቃት እና እገታ ፈፀሙ!
በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ከአዳማ 25 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የሚገኘውና በቀዳማዊ አጼ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ፖትርያሪክ የተመሠረተው የሶደሬ ፈለገ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ትናንት ከምሽቱ 3:30- 4:00 ሰዓት ከ50 በላይ የሚሆኑ የታጠቁ ኃይሎች ቤተክርስቲያኑን ሰብረው በመግባት ከፍተኛ ጉዳት አድርሰዋል ፡፡
የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት የደረሰውን ጉዳት ለማጣራት ልዑካንን የላከ ሲሆን ወደ ቦታው ያቀኑ ልዑካንም ክቡር መልአከ ሳሕል ቀሲስ ነጋሽ ሀብተወልድ የሀገረ ስብከቱ ም/ሥራ አስኪያጅ ፡ ክቡር መጋቤ ጥበባት ቀሲስ ጌቱ ሞቲ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ልዩ ፀሐፊ : ሊቀ ስዮማን ዋሲሁን የሀገረ ስብከቱ የካህናት አስተዳደር ክፍል ኃላፊ ሊቀ ትጉሓን ቀሲስ ፀጋ ተገኝ የሀገረ ስብከቱ ሕዝግ ግንኙነት ሊቀ ካህናት ቀሲስ ዋካ የአዳማ ዙሪያ ወረዳ ቤተክህነት ሥራ አስኪያጅ ሲሆኑ የደረሰው ጉዳት ተመልክተዋል ከልብ ማዘናቸውን በመግለጽ የአካባቢውን ምዕመናን በቃሉ አጽናንተው ተመልሰዋል፡፡
በምልከታቸውም በሩ ጠንካራ በመሆኑ የታጠቁ ኃይሎች ቦንብ በማፈንዳት ሰብረው ለመግባት የቻሉ ሲሆን በቤተክርስቲያኑ ንዋየ ቅድሳት ላይ ከፍተኛ የቃጠሎ ጉዳት ደርሷል ፡፡ የቤተክርስቲያኑን አስተዳዳሪ ቤት ሰብሮ በመግባት በወቅቱ አስተዳዳሪው ባይኖሩም በቤት እቃዎች ላይ ጉዳት አድርሰዋል ፡፡ በካህናት ላይ ከፍተኛ ማዋከብ የተፈጸመ ሲሆን ይኸው የታጠቀ ኃይል የደብሩን ገንዘብ ያዥ የሆኑትን አቶ ተስፋዬን አፍነው መውሰዳቸውንና እስካሁን ሰዓትም የታገተው አቶ ተስፋ እንዳልተለቀቁ ተገልጿል ፡፡
ምንጭ:-የአ/አ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት
现已上线!2025 年 Telegram 研究 — 年度关键洞察 
