የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)
前往频道在 Telegram
2 640
订阅者
+124 小时
+47 天
+6130 天
帖子存档
🔴 ስንክሳር #የካቲት_2
የካቲት ሁለት በዚህች ዕለት የትጉሃን መላእክት ወገን የሆነ የገዳማውያን ሁሉ አለቃ የከበረ #ታላቁ_ቅዱስ_ጳውሊ አረፈ፣ የደብረ ዝጋግ ገዳም አበ ምኔት የከበረ አባት #ቅዱስ_ለንጊኖስ አረፈ፣ የከበረ #ሐዋርያ_ቅዱስ_ቶማስ ተአምራትን አደረገ፡፡
▶️▶️▶️▶️▶️▶️▶️▶️▶️▶️
#ቅዱስ_ቶማስ_ሐዋርያ
በዚህችም ዕለት የከበረ ሐዋርያ ቶማስ ተአምራትን አደረገ፡፡ ጌታችን ወደ አዘዘው ሊአስተምር በወጣ ጊዜ ከመንገድ ጥቂት ፈቀቅ አለ ድንገትም የሞተ ጐልማሳ አየ መልኩ እጅግ የሚያምር ነበር ሐዋርያውም አቤቱ ይህን ጥፋት አይ ዘንድ ወደዚህ አመጣህኝን ነገር ግን ፈቃድህ ይሁን አለ።
ከዚህም በኋላ ስለሞተው ሰው ጸለየ ያን ጊዜ ታላቅ ከይሲ ከደንጊያዎች ውስጥ ወጥቶ በጅራቱ ምድሩን እየደበደበ መጣ የክርስቶስ ሐዋርያ ሆይ እኔ ካንተ ጋር ምን አለኝ ሥራዬን ልትዘልፍ መጣህን ብሎ በታላቅ ድምጽ ጮኸ ሐዋርያውም አዎን ሥራህን ተናገር አለው።
ከሲውም እንዲህ አለ በዚህ ቦታ አንጻር መልከ መልካም ሴት ነበረች እኔ የምወዳት ናት ይህም ጐልማሳ ሲስማት አየሁት በሰንበት ቀንም ከርሷ ጋር አደረ ስለዚህም ነክሼ በመርዝ ገደልኩት ሐዋርያውም መርዝህን ከሱ ትወስድ ዘንድ በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም አዝዤሃለሁ አለው።
ሔዶም ከዚያ ከሞተው መርዙን መጠጠና ወሰደ ወዲያውኑ ተነፍቶ አበጠ ተሠንጥቆም ሞተ የሞተውም ሰው ድኖ ተነሣ። ስለዚች ምልክትም ብዙዎች በክብር ባለቤት ጌታችን አመኑ እርሱም ሃይማኖትን አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት)
https://t.me/finotebirhan12
🔴 ስንክሳር #የካቲት_1
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት አንድ በዚህችም እለት የከበሩ መቶ ሃምሳ ኤጲስቆጶሳት የአንድነት ስብሰባ #በቍስጥንጥንያ_ጉባኤ አደረጉ፣ #አቡነ_እንድርያስ ዘደብረ ጽጌ ሰፍኣ አረፉ፣ የሰማዕታትም ፍጻሜ የሆነ የሊቀ ጳጳሳት #የቅዱስ_ጴጥሮስ ቤተ ክርስቲያን የከበረችበት ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#የቍስጥንጥንያ_ጉባኤ
የካቲት አንድ በዚህችም እለት የከበሩ የመቶ ሃምሳ ኤጲስቆጶሳት የአንድነት ስብሰባ በቍስጥንጥንያ ከተማ በታላቁ ቴዎዶስዮስ ዘመነ መንግሥት ተደረገ።
ስብሰባቸውም የሆነው በቍስጥንጥንያ አገር ላይ ሊቀ ጳጳሳት ስለ ሆነው የክብር ባለቤት የሆነ መንፈስ ቅዱስን በከፋች ኀሳቡ ፍጡር ነው ብሎ ስለ ካደው ስለ መቅዶንዮስ ሁለተኛም አንድ ገጽ ስለሚሉ ስለ ሰባልዮሳውያን ሦስተኛ ወልድ ከብቻው ሥጋ በቀር ነባቢት ለባዊት ነፍስን አልነሣም መለኮቱ በነፍስና በልቡና ፈንታ ሆነው ስለሚሉ ስለ አቡሊናርዮሳውያን ነው።
የእሊህ ከሀድያንም ስሕተት ግልጽ በሆነ ጊዜ አሰባስቦ የአንድነት ጉባኤ ያደርግላቸው ዘንድ ንጉሥ ቴዎዶስዮስን ለመኑት እርሱም ቃላቸውን ተቀብሎ ወደ ሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ወደ አንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ወደ ኢየሩሳሌምም ኤጲስቆጶስ ወደ እስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳትም መልእክትን ላከ ምሁራን የሆኑ ኤጲስቆጶሶቻቸውንም ይዘው እንዲመጡ አዘዛቸው።
እሊህም አባቶች በቍሰጥንጥንያ ከተማ ተሰበሰቡ የሮሜው ሊቀ ጳጳሳት ግን አልመጣም ምሁራን የሆኑ ሰዎችን ላከ እንጂ ከእሳቸውም ጋር በእጁ የጻፉትን ደብዳቤ ላከ።
የጉባኤውም ሊቀ መንበር የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ጢሞቴዎስ ነው መቅዶንዮስንም ጠርቶ የረከሰች ሃይማኖቱን ይናገር ዘንድ አዘዘው ያ ከሀዲም እንደ ፍጥረቶች ሁሉ መንፈስ ቅዱስ የተፈጠረ ነው አለ። ጢሞቴዎስም መልሶ መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ሕይወቱ እንደሆነ አታውቅምን የእግዚአብሔርን ሕይወት እንዴት ፍጡር ታደርገዋለህ አሁንም ከዚች ከረከሰች ሃይማኖትህ ተመለስ ወደ ዘላለማዊ እሳተ ገሃነም ከመግባትህ በፊት ንስሓ ግባ አለው። እርሱ ግን ሰምቶ አልተመለሰም እነርሱም አወገዙት ከሹመቱም ሻሩት ከቤተ ክርስቲያንም አሳደዱት።
ከዚህም በኋላ ሰባልዮሳውያንን ጠርቶ እናንተስ ስለ ሃይማኖታችሁ ምን ትላላችሁ ተናገሩ አላቸው እነርሱም አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ አንድ ገጽ አንድ ህላዌ ነው በምንም በምን ሦስት አይሆንም አሉ።
አባት ጢሞቴዎስም መልሶ እንዲህ አላቸው በዮርዳኖስ ውስጥ ወልድ ቁሞ ሳለ በፀዓዳ ርግብ አምሳል መንፈስ ቅዱስ ወርዶ በራሱ ላይ ተቀመጠ አብም ከደመና ውስጥ ሁኖ በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት ብሎ አሰምቶ ተናገረ ያለው የወንጌል ቃል ተሻረን። እናንተ እንደምትሉት ከሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የተጠመቃችሁት የክርስትናችሁ ጥምቀት ተሽሮአል አሁንም ክህደታችሁን ተዉ ብትመለሱም ይሻላችኋል። አርዮስም አስቀድሞ ወልድን ካደው ይህ መቅዶንዮስም መንፈስ ቅዱስን ካደው እናንተም የእነርሱ ተሳታፊዎች ሆናችሁ። እነርሱም ሰምተው አልተመለሱም የአንድነት ጉባኤም አውግዞ ከምእመናን አንድነት ለያቸው።
ከዚህም በኋላ ደግሞ ወልድ ነባቢት ለባዊት የሆነች ነፍስን አልነሣም ሥጋን ብቻ እንጂ የሚለውን የአቡሊናርዮስን ትምህርት አወገዙ።
እሊህ መቶ ኃምሳ የሆኑ ኤጲስ ቆጶሳት አባቶቻችንም በጸሎተ ሃይማኖት ላይ ጌታ አዳኝ በሚሆን ከአብ በሠረፀ በመንፈስ ቅዱስም እናምናለን እንሰግድለት እናመሰግነውም ዘንድ ከአብና ከወልድ ጋራ በነቢያት አድሮ የተናገረ የሚለውን ጨመሩ።
ከሁሉ በላይ በምትሆን ሐዋርያት በሰበሰቧት በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም እናምናለን። ኃጢአትን ለማስተሰረይ በአንዲት ጥምቀት እናምናለን። የሙታንንም መነሣት የሚመጣውንም ሕይወት ለዘላለሙ ተስፋ እናደርጋለን።
ሃይማኖታቸው የቀና ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ አባቶቻችን የተናገሩት ለመንግሥቱ ፍጻሜ የለውም እስከሚል ነው። እሊህ መቶ ኃምሳው አባቶች የተሰበሰቡት ስለ መንፈስ ቅዱስ ስለሆነ ስለርሱ የእርሱን ነገር አብራሩ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ጴጥሮስ_ተፍጻሜተ_ሰማዕት
በዚችም ዕለት በከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ መንግሥት ፍጻሜ በሰማዕትነት የሞተ ከሀዲ አርዮስንም ያወገዘ የሰማዕታትም ፍጻሜ የሆነ የሊቀ ጳጳሳት የቅዱስ ጴጥሮስ ቤተ ክርስቲያን የከበረችበት ነው።
ጻድቁ ቈስጠንጢኖስም በነገሠ ጊዜ የጣዖታትን ቤቶች ሁሉ አፈረሰ ይችንም ቤተ ክርስቲያን ከእስክንድርያ ከተማ በምዕራብ በኩል በቅዱስ ጴጥሮስ ስም አነፃት በዛሬዋም ዕለት ከበረች በውስጧም ብዙ የሆኑ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ። ያቺም ቤተ ክርስቲያን እስላሞች በግብጽ እስከ ነገሡበት ዘመን ኖረች ከዚያም በኋላ ቢሆን የታወቀች ሁና ትኖር ነበር ከዚህም በኋላ ፈረሰችና ምድረ በዳ ሆነች። የቅዱስ ጴጥሮስ ቤተ ክርስቲያን ግን በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እጅ የተያዘችና የተጠበቀች ናት።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት እና #ገድለ_ቅዱሳን)
https://t.me/finotebirhan12
🔴#ጥር_30
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር 30 በዚህች ቀን #ቅድስት_ሶፍያ ከሦስት ድናግል ልጆቿ ጋር በሰማእትነት ሞቱ፣የከበሩ #አምስቱ_ደናግል_ሰማዕታት (ጤቅላ፣ ማርያ፣ ማርታ፣ ዓበያ፣ ዓመታ) በሰማዕትነት አረፉ፣ የሮም ንጉስ ልጅ የከበረች #ቅድስት_ኦርኒ በሰማዕትነት አረፈች፣ የመለኮትን ነገር የሚናገር #የቅዱስ_ጎርጎርዮስ መታሰቢያ ነው፣ ተጋዳይ የሆነ መነኰስ የከበረ #ቅዱስ_አክርስጥሮስ አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_ሶፍያና_ሦስቱ_ሰማዕታት_ልጆቿ
ጥር ሰላሳ በዚች ቀን የከበሩ ድናግል ጲስጢስ አላጲስና አጋጲስ በሰማእትነት ሞቱ የተባረከች አናታቸው ሶፍያም ከአንፆኪያ ከከበረ ወገኖች ውስጥ ናት።
እነዚህንም ሶስት ልጆች በወለደቻቸው ጊዜ በእሊህ ስሞች ጠራቻቸው ትርጓሜያቸውም ሀይማኖት ተስፋ ፍቅር ነው የራሷም ስም ትርጓሜው ጥበብ ማለት ነው።
ጥቂትም በአደጉ ጊዜ ወደ ሮሜ ከተማ ወስዳ በጎ አምልኮን እግዚአብሄርን መፍራትን የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርት አስተማራቸው በከሀዲውም የሮሜ ንጉስ በአርያኖስ ዘንድ ወሬያቸው ተሰማ ወደርሱም የያመጡአቸው በማስተማር ትመክራቸውና ታፀናቸው ነበር። እንዲህም ትላቸዋለች ልጆቼ ተጠበቁ የዚህን የኃላፊውን አለም ክብር በማየት ልባችሁ እንዳይደክምና ከዘላለማዊ ክብር እንዳትርቁ ከሙሽራው ከክርስቶስ ጋር ሁናችሁ ወደ ሰማያዊ ሰርግ እንድትገቡ ጠንክሩ።እድሜያቸውም የታላቂቱ አስራ ሁለት የሁለተኛይቱ አስር የሶስተኛይቱ ዘጠኝ ነው።
እናታቸውም ወደ ንጉስ በአቀረበቻቸው ጊዜ ታላቂቱን ጲስጢስን እኔን ስሚ ከቤተ መንግስቴ ታላላቆች ለአንዱ አጋባሻለሁ ብዙ ስጦታም እሰጥሻለሁ ለአጵሎን ስገጂ አላት። እርሷም እርሱንና የረከሁ አማልክቶቹን ሰደበች እርሱም ተቆጥቶ በብረት ዘንጎች እንዲደበድቧት ጡቶቿንም እንዲቆርጡ እሳትንም ከብረት ምጣድ በታች በማንደድ ባሩድ ሙጫ ሰሊጥን በውስጡ አድርገው እጅግ አፍልተው ወደዚያ ይጨምሩዋት ዘንድ አዘዘ።
በጨመሩዋትም ጊዜ እየፀለየች በብረት ምጣዱ ውስጥ ቆመች ከቶ እሳት አልነካትም ።የምጣዱም ግለት ፀጥ ብሎ እንደ ጥዋት ጊዜ ጤዛ ቀዝቃዛ ሆነ ከዚያ ያሉ ሰዎችም አድነቀው እግዚአብሄርን አመሰገኑት ብዙዎችም በክብር ባለቤት እግዚአብሄር ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ራሶቻቸውንም ቆረጡዋቸውና በሰማእትነት ሞቱ።
ከዚህም በኃላ የቅድስት ጲስጢስን ራስ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ ምስክርነቷንም ፈፅማ የምስክርነት አክሊልን ተቀበለች እናቷም ስጋዋን አንስታ ወሰደች።ዳግመኛም ሁለተኛዋን አላጲስን አቀረቧትና ደበደቧት ፅኑእ ግርፋትንም ገረፏት ከጋለ ብረት ምጣድ ውስጥ ጨመርዋት በዚያንም ጊዜ ቀዝቅዞ እንደጥዋት ጤዛ ሆነ ንጉሱም ከዚያም እንዲአወጧትና ራሷን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ ምስክርነቷንም አድርሳ በመንግስተ ሰማያት የህይወት አክሊልን ተቀበለች እናቷም ስጋዋን ወሰደች።
ቅድስት ሶፊያም ከስቃይ የተነሳ እንዳትደነግጥ ስለ ልጅዋ ስለ አጋጲስ ትፈራ ነበር ታፅናናትና እንድትታገስ ታደርጋት ነበር በዚያንም ጊዜ ወስደው ከመንኮራኩር ውስጥ ጨመርዋት እግዚአብሄርም መልአኩን ልኮ ያንን መንኮራኩር ሰበረው እርሷም ፊቷን በመስቀል ምልክት አማትባ ወደሚነደው እሳት ተወርውራ ገባች በዚያንም ጊዜ እሳቱ እንደ ጥዋት ውርጭ የቀዘቀዘ ሆነ ከዚያ ያሉትም ሰዎች ብርሀን የለበሱ ሁለት ሰዎች ከነጫጭ ልብሶች ጋር ሲጋራድዋት አይተው እጅግ አደነቁ ብዙዎችም በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ራሶቻቸውንም ቆርጠዋቸው በሰማእትነት ሞቱ ያቺንም የዘጠኝ አመት ልጅ የከበረች አጋጲስን ራሷን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ።ምክስርነቷንም ፈፀመች ሁሉም የማያልፍ የማይጠፋ ሰማያዊ መንግስትን ወረሱ።
የከበረች ሲፊያም የሶስት ልጆቿን ስጋቸውን ወስዳ ገነዘቻቸው ወደ ከተማውም ውጭ አድርሶ በዚያ ቀበረቻቸው በሶስተኛውም ቀን ወደ መቃብራቸው ሄዳ አለቀሰች ነፍሷንም ይወስድ ዘንድ ወደ እግዚአብሄር ለመነች ልምናዋንም ተቀብሎ ነፍሷን ወሰደ ምእመናን ሰዎችም መጥተው ገንዘው ከልጆቿ ጋር ቀበርዋት።
በከሀዲው ንጉስ ላይ ግን እግዚአብሄር ጭንቅ የሆነ ደዌ ላከ አይኖቹም ፈረጡ አጥንቶቹም እስከሚታዩ ስጋው ሁሉ ተሰነጣጠቀ እጆቹም ተቆራረጡ ከእርሱም ደምና መግል ፈሰሰ ትልም ይወድቅ ነበር ሁለመናውም ተበላሽቶ በክፉ ሞት ሞተ።ስለ እነዚያ ደናግል ጌታ ተበቅሎታልና።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር እና #ከገድላት_አንደበት)
https://t.me/finotebirhan12
ወርሃዊ የሰንበት ት/ቤታችን ጉባኤ ደረሰ የፊታችን እሁድ ጥር 29, 2014 ዓ.ም
🔴 ስንክሳር#ጥር_28
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር 28 በዚህች ቀን #ጌታችን_ተአምራትን በማድረግ ሰባት እንጀራና ጥቂት ዓሣ አበርክቶ ብዙ ሰዎችን ያጠገበበት መታሰቢያ ነው፣ የከበረ #ቅዱስ_ቀሌምንጦስ በሰማዕትነት ሞተ፣ #መነኰስ_ቅዱስ_አካውህ በሰማዕትነት ሞተ፣ የከበረ አይሁዳዊ የማኀው ልጅ የእመቤታችን ወዳጅ #ቅዱስ_ዮሴፍ አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#የጌታ_ተአምር
(ጌታችን 5 እንጀራ 2 ዓሣ አበርክቶ 5 የገበያ ሕዝብ እንደመገበ)
ጥር ሃያ ስምንት በዚህች ቀን ጌታችን ተአምራትን በማድረግ ሰባት እንጀራና ጥቂት ዓሣ ቆራርሶ አበርክቶ ብዙ ሰዎችን ያጠገበበት መታሰቢያ ነው።
በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመዘገበው ይህ የጌታችን ተአምር በውስጡ ብዙ ምሥጢራትን የያዘ ነው እንጂ ስለ ሥጋዊ ምግብ ብቻ የተነገረ አይደለም፡፡ ማቴ 14፡13-23፡፡ የተመገቡትና የተቆጠሩት አምስት ሺህ ወንዶች ብቻ ናቸው እንጂ ሴቶችና ሕጻናት አልተቆጠሩም፡፡ ይህስ ለምን ነው ቢሉ ሴቶች በአደባባይ ሲበሉ በሃፍረት ዳር ዳር ስለሚሉ ነው፡፡ ሕጻናት ደግሞ ከሚበሉት የሚፈረፍሩት ይበዛልና ነው፡፡
ጌታችን ያንን ሁሉ ሕዝብ በመንደር አጠገብ ሊመግባቸው ሲችል ለምን አርቆ ወደ ምድረ በዳ ወሰዳቸው ከተባለ ስለ ሁለት ምክንያት ነው፡፡
አንድም ‹‹ጥንት አባቶቻችሁን ከመንደር (ከግብጽ) አውጥቼ አርባ ዘመን ሙሉ መና የመገብኳቸው እኔ ነኝ፤ አሁንም በሥልጣኔ በተአምራቴ መገብኳችሁ›› ሲላቸው ነው፡፡
አንድም ጌታችን ተአምራቱን ከመንደር አጠገብ አድርጎት ቢሆን ኖሮ ሁልጊዜ ክፋትንና ጠማማ ነገርን ማሰብ ለአይሁድ ልማዳቸው ነውና ‹‹ፈጣን ፈጣን ደቀ መዛሙርቱን በጎን ወደ መንደር እየላከ ያስመጣው ነው›› ይሉት ነበር፡፡ ስለሆነም ጌታችን ለጥርጥር ምክንያት እንዳይኖራቸው አድርጎ ነው ተአምራቱን የገለጠላቸው፡፡ ጊዜውም አመሻሽ ላይ ነበርና ምሽት ላይ ያደረገበትም ምክንያት ጠዋት ላይ ቢሆን ኖሮ ‹‹የበላነው ሳይጎድል ነው ያበላን›› ብለው ከማመን ይርቁ ነበር፡፡
በተጨማሪም በበረሃ ያውም በምሽት ሕዝቡን በውኃ አጠገብ በሣር ላይ አስቀምጧቸው መመገቡ ‹‹በፍጻሜው ዘመን በምቹ ስፍራ በመንግሥተ ሰማያት መንፈሳዊ ምግብ እመግባችኋለሁ፤ በውኃ (በጥምቀት) በሚገኝ ክብርም አከብራችኋለሁ›› ሲላቸው ነው፡፡ ተአምራቱን ከውኃ ዳር ማድረጉ ‹‹መታጠቢያ ብናጣ በደንብ ሳንበላ ቀረን›› እንዳይሉ ነው፡፡ ሳር የበዛበት ቦታ ላይ ማድረጉም ‹‹መቀመጫ ብናጣ በደንብ ሳንበላ ቀረን›› እንዳይሉ ነው፡፡
አምስቱ እንጀራ የአምስቱ አዕማደ ምሥጢር ማለትም የምሥጢረ ሥላሴ፣ የምሥጢረ ሥጋዌ፣ የምሥጢረ ጥምቀት፣ የምሥጢረ ቁርባንና የምሥጢረ ትንሣኤ ሙታን ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ሁለቱ ዓሣ ደግሞ የፍቅረ እግዚአብሔርና የፍቅረ ቢጽ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ፍቅረ እግዚአብሔር ማለት እግዚአብሔር አምላክን በፍጹም ነፍስና በፍጹም ሐሳብ መውደድ ነው፡፡ ፍቅረ ቢጽ ደግሞ ባልንጀራን እንደራስ አድርጎ መውደድ ነው፡፡ አንድም ደግሞ እንጀራውና ዓሣው የቅዱስ ሥጋውና የክቡር ደሙ ምሳሌ ነው፡፡
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር እና #ከገድላት_አንደበት)
https://t.me/finotebirhan12
🔴 ስንክሳር#ጥር_27
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር ሃያ ሰባት በዚህች ቀን #የቅዱስ_ሱርያል ሊቀ መልአክ በዓል ነው፡፡ የያሬድ ልጅ #ቅደስ_ኄኖክ_ነቢይ የተሰወረበት ነው፣ የከበረ #ቅዱስ_ሰራብዮን በሰማዕትነት ሞተ፣ የከበረ ሐዋርያ #ቅዱስ_ጢሞቴዎስ የሥጋው ፍልሰት ሆነ፣ የከበረ #ቅዱስ_ቢፋሞን በሰማዕትነት ሞተ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ሱርያል_ሊቀ_መላእክት
ጥር ሃያ ሰባት በዚህች ቀን የሊቀ መልአክ ሱርያል በዓል ነው፡፡ እርሱም ከሊቃናት አንዱ ነው፡፡ ቅዱስ ሱርያል ክብሩ ብዙ ቢሆንም ብዙ ምዕመናን አያውቁትም:: የመላእክት መዓርግ ሲነገር ሚካኤል፣ ገብርኤል፣ ሩፋኤል ብሎ ቀጥሎ የሚመጣው ሱርያል ነው::
በሦስቱ ሰማያት ካሉት ዘጠኙ ዓለመ መላእክት የአንዱ (የሥልጣናት) መሪ (አለቃ) ነው:: መልአኩ እጅግ ርሕሩሕ እና ተራዳኢ ነውና አንዘንጋው:: ለኖኅ መርከብን ያሳራው: ከጥፋት ውኃም ያዳነው፣ ከነቢይ እዝራ ጋር የኖረ የተሠወረ ምሥጢርንም የገለጠለት ነው እና ስለ ሰው ልጆች ወደ እግዚአብሔር የሚለምን ነው ይህ ቅዱስ መልአክ ነው::
በገድለ ሰማዕታትም ላይ እንደተጠቀሰው የሰማዕታት ረዳትና አዳኝም ነው:: ቅዱስ ሱርያል በሌላ ስሙ "እሥራልዩ" ይባላል:: "የእሥራኤል ረዳት" እንደ ማለት፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ኄኖክ_ነቢይ
በዚህችም ዕለት የያሬድ ልጅ ኄኖክን የመላልኤል ልጅ የቃይናን ልጅ የኄኖስ ልጅ የሴት ልጅ የአዳም ልጅ ኄኖክን መላእክት ይዘው አሳረጉት ይኸውም በመባርቅትና በነፋሳት ላይ ተጭኖ በመብረር ወደ ሰማይ ወስደው ከረቂቃን መላእክት ጋር አኖሩት የእግዚአብሔርም ትእዛዝ ጸሐፊ ተባለ።
እንዲህም አለ ከማደሪያው ከሚወጣው ከቅዱሱና ከገናናው በጸናች ኃይሉ ከሠራዊቱ ጋር በሲና ተራራ ከሚገለጠው ጋር በመነጋገር ተመላለስኩ። ሁሉም ይፈሩ ነበር በውኃ ዳርም ሳለሁ የልመናቸውን መታሰቢያ ጻፍኩ እስከ አንጎላቸሁና ሕልም እንደሚያይ እስከምሆን ይችም በአርሞን ግራና ቀኝ ያለች አገር ናት።
በደብር ቅዱስ ለነበሩ ለኃጢአት ለሚተጉ ለሴት ልጆች ይዘልፋቸው ዘንድ ቃል እንደጠራውና እንዳሳየው ተናገረ። እንዲህ አለ በበረድ ደንጊያ ወደ ተሠራ ታላቅ ቤት ቀረብኩ በበረድ ደንጊያ የተሠራ የዚያ ቤት ግድግዳ እንደ ሳንቃ ልዝብ ነው ከዚህ ቤት የሚበልጥም ሌላ ቤት አየሁ ደጃፉም የተከፈተ ነው በእሳት ቅጽርም የተሠራ በክብር ከሁሉ የሚበልጥ ነው።
በውስጡም ከፍ ያለ የእግዚአብሔርን ዙፋን አየሁ መልኩም እንደ ውርጭ ነው አጎበሩም እንደሚያበራ ፀሐይ ነው ከዙፋኑም በታች የኪሩቤል ድምፅ ይሰማል። ዳግመኛም ወደ ሰባት ተራራዎች ደረስኩ ሦስቱ በምሥራቅ በኵል ሦስቱ በአዜብ በኵል ናቸው የመካከለኛው ግን ሰማይ ጠቀስ ነው የመላእክትም ጌታ በላዩ አለ።
ሌሎች አራት ገጾች ኪሩቤልን አየ ስለ ክርስቶስም እንዲህ ብሎ ትንቢት ተናገረ የዘመናት አለቃ ወደ ሆነው የሰው ልጅ ተጠራ ዓለም ከመፈጠሩ አስቀድሞ የነበረ ሆነ ሁለተኛም ለጻድቃን የጽድቅ በትር ለአሕዛብም ብርሃን ተስፋ ለሌላቸውም አለኝታ ይሆናል አለ።
በሰማይ ገጽ ስለሚመላለሱ ብርሃናት እንዲህ አለ አንዱም አንዱ በየወገናቸው በሠለጠኑበትና በተሠየሙበት ጸንተው ይኖራሉ ስለ ነፋሳትም መውጫዎች እንዲህ ብሎ ተናገረ ሦስቱ በሰማይ ገጽ ሦስቱ በምድር ገጽ ሦስቱ በቀኝ ሦስቱ በግራ ናቸው። ስለ አዳምም እንዲህ አለ እነሆ በሬ ከምድር ወጣ ፀዓዳም ሆነ ስለ ሔዋንም ደግሞ ሴት እምቦሳ ከርሱ ወጣች አለ።
ስለ ምኵራብም ያንን አሮጌ ቤት እስከሚአሳንሰው ድረስ አየሁ አለ ምሰሶዎቹንም ከውስጡ አወጣ። ሰለ ቤተክርስቲያንም ጌታ አዲስ የበጎች ቤት አምጥቶ እስቲሠራ ድረስ አየሁ ከቀድሞውም ቤት የበለጠ ነው በጎችም ሁሉ በውስጧ ይሠማራሉ አለ። ስለ ምእመናንም የእሊህም በጎች ፀጕራቸው ንጹሕ ነጭ ነው የተበተኑትም ከአራዊት ጋራ ይሠማራሉ ሁሉም በአንድነት ተሰብስበው ገራሞች ሆነዋልና።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ሰራብዮን_ሰማዕት
በዚህች ዕለት ከግብጽ ደቡብ ከታችኛዪቱ ምስር አውራጃ በብኑዲ ከምትባል መንደር የከበረ ሰራብዮን በሰማዕትነት ሞተ። ለዚህም ቅዱስ ብዙ የገንዘብ ጥሪት እንስሳትም አሉት አብዝቶ መመጽወትንም የሚወድ ነው ስደትም በሆነ ጊዜ የክርስቲያን ወገኖችን ፈልጎ ያሠቃይ ዘንድ መኰንኑ ኄሬኔዎስ በየሀገሩ እንደሚዞር ሰማ ለርሱም ስማቸው ቴዎድሮስና ሁለተኛውም በግ አርቢ ሰርማ የሚባሉ ወዳጆች ነበሩት እነርሱም ተከተሉት ይህም ቅዱስ መኰንኑን ሊገናኘው ከሀገሩ ወጣ መኰንኑንም በአገኘው ጊዜ በፊቱ ቁሞ ከወገኖቹ ጋር በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ መኰንኑም ሁሉንም አሠራቸው።
የሀገር ሰዎችም በሰሙ ጊዜ ሁሉም ተሰብሰቡ መኰንኑን ገድለው ቅዱስ ሰራብዮንን ከእጁ ሊወስዱ ሽተው የጦር መሣሪያ በመያዝ ለጦርነት የተሰለፉ ሠራዊት ሁነው ደረሱ ቅዱሱ ግን ከለከላቸው እንዲህም አላቸው እኔ በጌታዬ ክርስቶስ ስም ደሜን አፈስ ዘንድ በፈቃዴ የመጣሁ አይደለምን መኰንኑም በመርከብ ተሳፍሮ ከዚያ ሔደ ቅዱሳኑም አብረውት ሔዱ።
ወደ እስክንድርያ አገርም በደረሰ ጊዜ የከበረ ሰራብዮንን በመንኰራኵር ውስጥ ጽኑዕ ሥቃይን እንዲአሠቃዩት ወደ እሳት ማንደጃም ይጨምሩት ዘንድ አዘዘ። ከዚህም በኋላ ከነዳጅ ድፍድፍና ቅመማቅመም ጋር በወጭት ውስጥ ቀቀሉት የሥጋውንም ሥሮች ቆረጡ በብረት ዐልጋ ላይም አስተኝተው በችንካር ቸነከሩት ይህን ሁሉ ሥቃይም የሚታገሥ ሆነ የእግዚአብሔርም መልአክ ሥቃዩን ከላዩ ይቀበልለት ነበር።
ከዚህም በኋላ ከእንጨት ላይ ሰቅለው በፍላፃዎች ነደፉት የእግዚአብሔርም መልአክ እርሱን ከተሰቀለበት አውርዶ በእርሱ ፈንታ መኰንኑን አሥሮ ሰቀለው። የከበረ ሰራብዮንም እንዲህ አለው ሕያው እግዚአብሔርን በክርስቶስ ስም የታሠሩትን ሁሉንም እስከምታወጣቸውና የሞታቸውን ፍጻሜ እስከምታዝዝ አንተ ከእዚህ ከተሰቀልክበት ዕንጨት እንደማትወርድ ዕወቅ። በዚያንም ጊዜ ሁሉንም አውጥተው ራሶቻቸውን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘና ቆረጧቸው የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ የእነዚህም ሰዎች ቊጥራቸው አምስት መቶ አርባ ነፍስ ሆነ።
ከዚህም በኋላ የከበረ ሰራብዮንን ወደ ሀገሩ ከእርሱ ጋር ወስዶ ያሠቃየው ዘንድ ከኀሳቡም ካልተመለሰ እራሱን በሰይፍ ይቆርጥ ዘንድ ኄሬኔዎስ አንዱን መኰንን አዘዘው። መኰንኑም ከርሱ ጋር በመርከብ ወሰደው ሌሊትም በሆነ ጊዜ ወደ አንድ ወደብ ደርሰው በዚያ ተኙ በእግዚአብሔርም ፈቃድ ያቺ መርከብ ወደ ቅዱስ ሰራብዮን አገር ደረሰች በጥዋትም በነቁ ጊዜ የመሔጃቸው አቅጣጫ ተለውጦ አገኙ እጅግም አደነቁ ወደ ሰራብዮንም እነሆ ይቺ ሀገርህ ናት የሚል ቃል ከሰማይ መጣ ከመርከብም አውርደው ታላቅ ሥቃይን አሠቃይተው ራሱን በሰይፍ ቆረጡት በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለ። መኰንኑም ልብሶቹን አውጥቶ ገንዞ ለዘመዶቹ ሰጠው።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
https://t.me/finotebirhan12
ወርሃዊ የሰንበት ት/ቤታችን ጉባኤ ደረሰ የፊታችን እሁድ ጥር 29, 2014 ዓ.ም
🔴 ስንክሳር #ጥር_26
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር ሃያ ስድስት በዚህች ቀን #ቅድስት_አንስጣስያ አረፈች፣ የከበሩ #አረጋውያን_መነኰሳት ከንጉሥ መልእክተኛ ከልጁም ጋር በሰማዕትነት አረፉ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_አንስጣስያ
ጥር ሃያ ስድስት በዚህች ቀን ከቍስጥንጥንያ ቤተ መንግሥት ታላላቆች የአንዱ ልጅ የሆነች ቅድስት አንስጣስያ አረፈች። እርሷም በላሕይዋ በደም ግባቷ እጅግ ያማረች ናት ንጉሥ ብስጥያኖስም ሊአገባት ፈለገ እርሷ ግን ይህን በልቧ አልወደደችም የንጉሡም ሚስቱ በሕይወት ነበረች ንጉሡ እንደሚሻትም ለንግሥት ሚስቱ አስረዳቻት በዚያንም ጊዜ ንግሥቲቱ ወደ ግብጽ በመርከብ አሳፍራ በሥውር ሸኘቻት ከእስክንድርያም ከተማ ውጭ ገዳም አሠራችላት በዚያም ኖረች ያም ገዳም በስሟ ተጠራ።
የከበረች እንስጣስያም በግብጽ አገር እንዳለች ንጉሥ በአወቀ ጊዜ ፈልገው ወደርሱ ያመጧት ዘንድ መልእክተኞችን ላከ ይህንንም ነገር ተረድታ ተነሣች የወንዶችንም ልብስ ለብሳ መስፍንን መሰለች ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔዳ ወደ አበ ምኔቱ ወደ አባ ዳንኤል ገባች ምሥጢሯን ሁሉ ገለጠችለት ።
እርሱም ወስዶ በዋሻ ውስጥ ለብቻዋ አኖራት እርሷም ሴት እንደሆነች ማንም አላወቀም በየሳምንቱም በእንስራ ውኃ ቀድቶ ከዚያ ዋሻ ደጃፍ እንዲያኖር አንዱን ደግ አረጋዊ አባ ዳንኤል አዘዘው ያም ሽማግሌ አያውቅም ይችም ቅድስት አንስጣስያ በጸሎት በጾምና በመስገድ በመትጋትም እየተጋደለች ሃያ ስምንት ዓመት ኖረች ።
ውኃ ሲቀዳላት የነበረ ያ ሽማግሌ በአረፈ ጊዜ አባ ዳንኤልም ያ ሽማግሌ ሲሠራ እንደ ነበረ ይሠራ ዘንድ ረዳቱን አዘዘው ቅድስት አንስጣስያም ሀሳቧን በገል ላይ እየጻፈች በበዓቷ ደጃፍ ታኖረው ነበር ረድኡም ወደ መምህሩ ወደ አባ ዳንኤል ይወስደዋል። የምትጽፈውንም ምን እንደሆነ አያውቅም ።
በአንዲት ዕለትም የጻፈችበትን ገል አመጣ አባ ዳንኤልም በአነበባት ጊዜ አለቀሰ ረድኡንም ልጄ ሆይ ተነሥ የዚያን ቅዱስ ሰው ሥጋ ሒደን እንቅበር እርሱ ከዚህ ዓለም ይለያልና አለው ። በሔዱም ጊዜ ወደ በዓቷ ገብተው ከእርሷ ተባረኩ እርሷም አባ ዳንኤልን አባቴ ሆይ ስለ እግዚአብሔር ብለህ በላዬ ካለው በቀር በምንም ልብስ እንዳትገንዘኝ አለችው ከዚህም በኋላ የከበረች አንስጣስያ ተነሥታ ጸለየች እኔ በእግዚአብሔር ዘንድ አደራ አስጠበቅኋችሁ አለችና በምድር ላይ ተቀምጣ አረፈች በላይዋም አለቀሱ ሊቀብሩዋትም አስበው ረድኡ ይገንዛት ዘንድ ሲቀርብ እንደ በለስ ቅጠሎች ደርቀው ጡቶቿን ተመለከተ። ከተጋድሎ ብዛትም የተነሣ እንዲህ ሁኗልና አባ ዳንኤልም አይቶ በማድነቅ ዝም አለ ።
ከቀበርዋትም በኋላ ወደ በዓታቸው ተመለሱ ረድኡም ወደ አባ ዳንኤል ቀርቦ ሰገደለትና እንዲህ ሲል ለመነው ስለ እግዚአብሔር ብለህ የዚችን ቅድስት ዜናዋን ንገረኝ ሴት እንደሆነች አይቻለሁና።
አባ ዳንኤልም የገድሏን ዜና ሊነግረው ጀመረ እንዲህም አለው እርሷ ከቍስጥንጥንያ አገር ከመንግሥት ታላላቅ ወገኖች ውስጥ የሆነች ስትሆን ሰውነቷን ለክርስቶስ ሰጥታ የዚህን የኃላፊውን ዓለም ክብር ሁሉ ተወች። ሰይጣንን ከተዋጋችበት ከዚህ ከታላቅ ተጋድሎዋ ለእኛ ለወንዶች መመከሪያ ሊሆነን ይገባል ከእርሷም የሴቶችን ደካማነት አርቃ የኃይለኞች ወንዶችን ብርታት ገንዘብ እስከማድረግ ደርሳ እግዚአብሔርን አገለገለችው።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር)
https://t.me/finotebirhan12
🔴 ስንክሳር #ጥር_25
ጥር 25 በዚህች ዕለት ሰማዕቱ #ቅዱስ_መርቆሬዎስ በሥዕሉ ላይ አድሮ ቅዱሳን ባስልዮስንና ጎርጎርዮስን የረዳበት ዕለት ነው፡፡ በገድል የተጸመደ የከበረ #ቅዱስ_ጴጥሮስ አረፈ፣ የከበረ #ቅዱስ_ስብስትያኖስ ምስክር ሁኖ ሞተ፡፡
#ቅዱስ_መርቆሬዎስ
ሰማዕቱ ቅዱስ መርቆሬዎስ በሥዕሉ ላይ አድሮ ቅዱሳን የሆኑ ባስልዮስንና ጎርጎርዮስን በመርዳት ከሃዲውን ንጉሥ ዑልያኖስን የገደለው በዚሁ ዕለት ነው፡፡
መርቆሬዎስ ማለት የአብ ወዳጅ ማለት ነው፡፡ ዳግመኛም የኢየሱስ ክርስቶስ አገልጋይ ማለት ነው፡፡ ወላጆቹ አስሊጥ ከምትባል ሀገር ቢሆኑም እርሱ ግን ተወልዶ ያደገው በሮሜ ከተማ ነው፡፡ አያቱና አባቱ ሥራቸው አውሬ ማደን ስለነበር አንድ ቀን እንደልማዳቸው አውሬ ሲያድኑ ከገጸ ከለባት ወገን የሆኑ ሁለት ወንዶች አግኝተዋቸው የመርቆሬዎስን አያት በሉት፡፡ አባቱንም ሊበሉት ሲሉ የታዘዘ መልአክ ከለከላቸው፡፡ ዙሪያቸውንም በእሳት አጥሮ ከበባቸው፡፡ እነርሱም በተቸገሩ ጊዜ ለመርቆሬዎስ አባት ሰገዱለት፡፡ በዚያን ጊዜም እግዚአብሔር ፍጥረታቸውን ወደገራምነት ለወጠውና እንደበጎች የዋሆች ሆነው አብረውት ወደ መንደር ገቡ፡፡
ከዚህም በኋላ ቅዱስ መርቆሬዎስ ተወለደና ስሙ ፒሉፓዴር ተባለ፡፡ የውሻ መልክ ያላቸውም በእርሱ ዘንድ ብዙ ዘመናት ኖሩ፡፡ ከዚህም በኋላ ክርስቲያኖች ሆኑ፡፡ የቅዱስ መርቆሬዎስም ወላጆች አስቀድመው አረማውያን ነበሩና የክርስትና ጥምቀትን በጸጋ ተቀበሉ፡፡ አባቱን ኖህ እናቱንም ታቦት ብለው ሰየሟቸው፡፡ ቀድሞ ፒሉፓዴር የነበረውም ስሙ ተለውጦ መርቆሬዎስ ተባለ፡፡ የውሻ መልክ ያላቸው ግን መልአኩ በተገለጠላቸው ጊዜ እንደነገራቸው ለቅዱስ መርቆሬዎስ አባት የሚታዘዙና የሚያገለግሉ ሆኑ፡፡ ንጉሡም የመርቆሬዎስን አባትና የውሻ መልክ ያላቸውን ዜናቸውን ሲሰማ ወታደሮቹን ልኮ በፊቱ አቆማቸው፡፡ እግዚአብሔርም የቀድሞ ፍጥረታቸውን መልሶላቸው አራዊት አደረጋቸውና ንጉሡን እጅግ አስፈሩት፡፡ ንጉሡም የቅዱስ መርቆሬዎስን አባት የአራዊት ተፈጥሮአቸውን ያርቅለት ዘንድ ለመነው፡፡ የቅዱስ መርቆሬዎስም አባት በለመነ ጊዜ ተፈጥሮአቸውን መልሶላቸው ገራሞች ሆኑ፡፡
ንጉሡም የመርቆሬዎስን አባት ገዥና የሠራዊቱ አለቃ አድርጎ ሾመው፡፡ የውሻ ፊት ያላቸውም አብረው ያገለግሉት ስለነበር ሁሉም ይፈራው ነበር፡፡ ንጉሡም የመርቆሬዎስን አባት ወደ ጦርነት ከላከው በኋላ ሳይመለስ ስለቀረ ሚስቱን ሊያገባት አሰበ፡፡ የመርቆሬዎስ አባትም የመርዶሳውያን አገሮች ሁሉ ገዢ በነበረው ንጉሥ ተይዞ ቢማረክም ገዥው ክርስቲያን መሆኑን አይቶ አከበረው፡፡ ቆይቶም በሀገሩ ላይ ሾመው፡፡ ሚስቱም ጠፍታ ከሀገሯ ወጥታ ሄዳ ስለነበር ከባሏ ተገናኝተው በዚያው መኖር ጀመሩ፡፡ መርቆሬዎስም አባቱና እናቱ ከሞቱ በኋላ ንጉሡ በአባቱ ፈንታ በመርዶሳውያን አገር ላይ ሾመው፡፡
መርቆሬዎስ መኰንንነት በተሾመም ጊዜ ገጸ ከለባቱ አብሮት ነበር፡፡ ለመዋጋትም በወጣ ጊዜ የቀድሞው የአራዊት የሆነ ተፈጥሮውን እግዚአብሔር ይመልስለት ስለነበር ማንም አይቋቋመውም ነበር፡፡ ለቅዱስ መርቆሬዎስ ታላቅ የድል አድራጊነት ኃይል ተሰጠውና ዜናው በሁሉም ሀገሮች ተሰማ፡፡ በሮሜ ሀገር ጣዖትን የሚያመልከው ዳኬዎስ የተባለውም ንጉሥ የበርበር ሰዎች ጋር ጦርነት ሊገጥም በወጣ ጊዜ እጅግ ሲበዙበት ፈራ፡፡ ቅዱስ መርቆሬዎስም በጦሩ መሀል የተሳለ ሰይፍ የያዘ የእግዚአብሔርን መልአክ ስላየ ንጉሡን እግዚአብሔር ያጠፋቸዋልና አትፍራ›› አለው፡፡ መልአኩም ሰይፉን ለቅዱስ መርቆሬዎስ ሰጠውና ‹‹ጦርነቱን ድል ባደረግህ ጊዜ እግዚአብሔርን አስበው›› አለው፡፡
ጦርነቱን ድል አድርጎ ሲጨርስም መልአኩ ድጋሚ ተገልጦለት ‹‹ለምን የፈጣሪህን ስም መጥራት እረሳህ?›› አለው፡፡ ከጦርነቱም በኋላ ንጉሥ ዳኬዎስ ለጣዖታቱ ዕጣን በማሳረግ በዓልን አደረገ፡፡ ቅዱስ መርቆሬዎስም በዚያ ስላልተገኘ ለጣዖታቱ ዕጣን በማሳረጉ እንዳልተባበረ ንጉሡ ሲያውቅ መልእክተኞችን ልኮ አስመጣው፡፡ ንጉሡም ‹‹ከእኔ ጋር ለምን አታጥንም?›› ባለው ጊዜ ቅዱስ መርቆሬዎስ ትጥቁንና ልብሱን አውልቆ ከወረወረለት በኋላ ‹‹ክብር ይግባውና አምላኬ ኢየሱስ ክርስቶስን ፈጽሞ አልክደውም፣ ለረከሱ ጣዖቶችህም አልሰግድም›› አለው፡፡ ንጉሡም ተናዶ ልዩ ልዩ በሆኑ ሥቃዮችም እጅግ አሠቃየው፡፡
ንጉሡም ስለ መርቆሬዎስ ብለው የአገሩ ሰዎች እንዳይነሱበት ፈርቶ በብረት ችንካር ቸንክሮ የቀጵዶቅያና የእስያ ክፍል ወደሆነች ወደ ቂሳርያ ከደብዳቤ ጋር ላከው፡፡ በዚያም እጅግ ካሠቃዩት በኋላ ንጉሡ ዳኬዎስ እንዳዘዘ ኅዳር 25 ቀን አንገቱን በሰይፍ ቆረጡትና የሰማዕትነት ተጋድሎውን ፈጸመ፡፡ የሕይወትንም አክሊል ተቀዳጀ፡፡ በዓለሙ ሁሉ አብያተ ክርስቲያናት ታነጹለት፡፡ እግዚአብሔርም ድንቅ ድንቅ የሆኑ ተአምራትን በቅዱስ መርቆሬዎስ ስም አደረገ፡፡
ከብዙ ተአምራቱም አንዱ የቂሳርያውን ሊቀ ጳጳስ ባስልዮስን እረድቶ ከሃዲውን ዑልያኖስን የገደለበት ነው፡፡ ዑልያኖስ ነግሦ የክብር ባለቤት ጌታችንን ክዶ ጣዖታትን ማምለክና ክርስቲያኖችን ማሠቃየት ጀመረ፡፡ የቂሳርያው ሊቀ ጳጳስ ባስልዮስም አስተምሮ ሊመልሰው ወደ ንጉሡ ቢመጣ ክብር ይግባውና ዑልያኖስ ጌታችንን ሰድቦ ባስልዮስንም አሰረው፡፡ ባስልዮስም በእሥር ቤት ሳለ በቅዱስ መርቆሬዎስ ሥዕል ፊት ጸለየ፡፡ ሥዕሉም ወዲያው ተሰወረው፡፡ ያንጊዜም ወደ ከሃዲው ንጉሥ ዑልያኖስ ዘንድ ሄዶ በጦር ወግቶ ገደለውና ወዲያው ወደ ቦታው ተመለሰ፡፡ ከጦሩም አንገት ደም ይንጠፋጠፍ ነበር፡፡ ቅዱስ ባስልዮስም ከሃዲውን ንጉሥ እንደገደለው ዐውቆ ‹‹የክርስቶስ ምስክር ጌታዬ ሆይ የእውነት ፀር የሆነ ዑልያኖስን ገደልከውን?›› አለው፡፡ ሥዕሉም ያን ጊዜ አዎን እንደሚል ራሱን ዘንበል አደረገ፡፡ ቅዱስ ባስልዮስም ደስ ብሎት እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎቱ ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር እና #ከገድላት_አንደበት)
https://t.me/finotebirhan12
ገብቶ ብዙ ከተጋደለ በኋላ እንደገና ወደ አገሩ ተመልሶ ብዙዎችን ወደ ክርስትና አምጥቷል፡፡ በቅዱስ መርቆሬዎስ ስም ቤተ ክርስቲያን አሠርቶ አበ ምኔትም ሆኖ ብዙ መነኮሳትን አፍርቷል።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎቱ ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር እና #ከገድላት_አንደበት)
🔴 ስንክሳር #ጥር_25
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር 25 በዚህች ዕለት ሰማዕቱ #ቅዱስ_መርቆሬዎስ በሥዕሉ ላይ አድሮ ቅዱሳን ባስልዮስንና ጎርጎርዮስን የረዳበት ዕለት ነው፡፡ በገድል የተጸመደ የከበረ #ቅዱስ_ጴጥሮስ አረፈ፣ የከበረ #ቅዱስ_ስብስትያኖስ ምስክር ሁኖ ሞተ፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_መርቆሬዎስ
ጥር ሃያ አምስት በዚህች ዕለት ሰማዕቱ ቅዱስ መርቆሬዎስ በሥዕሉ ላይ አድሮ ቅዱሳን የሆኑ ባስልዮስንና ጎርጎርዮስን በመርዳት ከሃዲውን ንጉሥ ዑልያኖስን የገደለው በዚሁ ዕለት ነው፡፡
መርቆሬዎስ ማለት የአብ ወዳጅ ማለት ነው፡፡ ዳግመኛም የኢየሱስ ክርስቶስ አገልጋይ ማለት ነው፡፡ ወላጆቹ አስሊጥ ከምትባል ሀገር ቢሆኑም እርሱ ግን ተወልዶ ያደገው በሮሜ ከተማ ነው፡፡ አያቱና አባቱ ሥራቸው አውሬ ማደን ስለነበር አንድ ቀን እንደልማዳቸው አውሬ ሲያድኑ ከገጸ ከለባት ወገን የሆኑ ሁለት ወንዶች አግኝተዋቸው የመርቆሬዎስን አያት በሉት፡፡ አባቱንም ሊበሉት ሲሉ የታዘዘ መልአክ ከለከላቸው፡፡ ዙሪያቸውንም በእሳት አጥሮ ከበባቸው፡፡ እነርሱም በተቸገሩ ጊዜ ለመርቆሬዎስ አባት ሰገዱለት፡፡ በዚያን ጊዜም እግዚአብሔር ፍጥረታቸውን ወደገራምነት ለወጠውና እንደበጎች የዋሆች ሆነው አብረውት ወደ መንደር ገቡ፡፡
ከዚህም በኋላ ቅዱስ መርቆሬዎስ ተወለደና ስሙ ፒሉፓዴር ተባለ፡፡ የውሻ መልክ ያላቸውም በእርሱ ዘንድ ብዙ ዘመናት ኖሩ፡፡ ከዚህም በኋላ ክርስቲያኖች ሆኑ፡፡ የቅዱስ መርቆሬዎስም ወላጆች አስቀድመው አረማውያን ነበሩና የክርስትና ጥምቀትን በጸጋ ተቀበሉ፡፡ አባቱን ኖህ እናቱንም ታቦት ብለው ሰየሟቸው፡፡ ቀድሞ ፒሉፓዴር የነበረውም ስሙ ተለውጦ መርቆሬዎስ ተባለ፡፡ የውሻ መልክ ያላቸው ግን መልአኩ በተገለጠላቸው ጊዜ እንደነገራቸው ለቅዱስ መርቆሬዎስ አባት የሚታዘዙና የሚያገለግሉ ሆኑ፡፡ ንጉሡም የመርቆሬዎስን አባትና የውሻ መልክ ያላቸውን ዜናቸውን ሲሰማ ወታደሮቹን ልኮ በፊቱ አቆማቸው፡፡ እግዚአብሔርም የቀድሞ ፍጥረታቸውን መልሶላቸው አራዊት አደረጋቸውና ንጉሡን እጅግ አስፈሩት፡፡ ንጉሡም የቅዱስ መርቆሬዎስን አባት የአራዊት ተፈጥሮአቸውን ያርቅለት ዘንድ ለመነው፡፡ የቅዱስ መርቆሬዎስም አባት በለመነ ጊዜ ተፈጥሮአቸውን መልሶላቸው ገራሞች ሆኑ፡፡
ንጉሡም የመርቆሬዎስን አባት ገዥና የሠራዊቱ አለቃ አድርጎ ሾመው፡፡ የውሻ ፊት ያላቸውም አብረው ያገለግሉት ስለነበር ሁሉም ይፈራው ነበር፡፡ ንጉሡም የመርቆሬዎስን አባት ወደ ጦርነት ከላከው በኋላ ሳይመለስ ስለቀረ ሚስቱን ሊያገባት አሰበ፡፡ የመርቆሬዎስ አባትም የመርዶሳውያን አገሮች ሁሉ ገዢ በነበረው ንጉሥ ተይዞ ቢማረክም ገዥው ክርስቲያን መሆኑን አይቶ አከበረው፡፡ ቆይቶም በሀገሩ ላይ ሾመው፡፡ ሚስቱም ጠፍታ ከሀገሯ ወጥታ ሄዳ ስለነበር ከባሏ ተገናኝተው በዚያው መኖር ጀመሩ፡፡ መርቆሬዎስም አባቱና እናቱ ከሞቱ በኋላ ንጉሡ በአባቱ ፈንታ በመርዶሳውያን አገር ላይ ሾመው፡፡
መርቆሬዎስ መኰንንነት በተሾመም ጊዜ ገጸ ከለባቱ አብሮት ነበር፡፡ ለመዋጋትም በወጣ ጊዜ የቀድሞው የአራዊት የሆነ ተፈጥሮውን እግዚአብሔር ይመልስለት ስለነበር ማንም አይቋቋመውም ነበር፡፡ ለቅዱስ መርቆሬዎስ ታላቅ የድል አድራጊነት ኃይል ተሰጠውና ዜናው በሁሉም ሀገሮች ተሰማ፡፡ በሮሜ ሀገር ጣዖትን የሚያመልከው ዳኬዎስ የተባለውም ንጉሥ የበርበር ሰዎች ጋር ጦርነት ሊገጥም በወጣ ጊዜ እጅግ ሲበዙበት ፈራ፡፡ ቅዱስ መርቆሬዎስም በጦሩ መሀል የተሳለ ሰይፍ የያዘ የእግዚአብሔርን መልአክ ስላየ ንጉሡን እግዚአብሔር ያጠፋቸዋልና አትፍራ›› አለው፡፡ መልአኩም ሰይፉን ለቅዱስ መርቆሬዎስ ሰጠውና ‹‹ጦርነቱን ድል ባደረግህ ጊዜ እግዚአብሔርን አስበው›› አለው፡፡
ጦርነቱን ድል አድርጎ ሲጨርስም መልአኩ ድጋሚ ተገልጦለት ‹‹ለምን የፈጣሪህን ስም መጥራት እረሳህ?›› አለው፡፡ ከጦርነቱም በኋላ ንጉሥ ዳኬዎስ ለጣዖታቱ ዕጣን በማሳረግ በዓልን አደረገ፡፡ ቅዱስ መርቆሬዎስም በዚያ ስላልተገኘ ለጣዖታቱ ዕጣን በማሳረጉ እንዳልተባበረ ንጉሡ ሲያውቅ መልእክተኞችን ልኮ አስመጣው፡፡ ንጉሡም ‹‹ከእኔ ጋር ለምን አታጥንም?›› ባለው ጊዜ ቅዱስ መርቆሬዎስ ትጥቁንና ልብሱን አውልቆ ከወረወረለት በኋላ ‹‹ክብር ይግባውና አምላኬ ኢየሱስ ክርስቶስን ፈጽሞ አልክደውም፣ ለረከሱ ጣዖቶችህም አልሰግድም›› አለው፡፡ ንጉሡም ተናዶ ልዩ ልዩ በሆኑ ሥቃዮችም እጅግ አሠቃየው፡፡
ንጉሡም ስለ መርቆሬዎስ ብለው የአገሩ ሰዎች እንዳይነሱበት ፈርቶ በብረት ችንካር ቸንክሮ የቀጵዶቅያና የእስያ ክፍል ወደሆነች ወደ ቂሳርያ ከደብዳቤ ጋር ላከው፡፡ በዚያም እጅግ ካሠቃዩት በኋላ ንጉሡ ዳኬዎስ እንዳዘዘ ኅዳር 25 ቀን አንገቱን በሰይፍ ቆረጡትና የሰማዕትነት ተጋድሎውን ፈጸመ፡፡ የሕይወትንም አክሊል ተቀዳጀ፡፡ በዓለሙ ሁሉ አብያተ ክርስቲያናት ታነጹለት፡፡ እግዚአብሔርም ድንቅ ድንቅ የሆኑ ተአምራትን በቅዱስ መርቆሬዎስ ስም አደረገ፡፡
ከብዙ ተአምራቱም አንዱ የቂሳርያውን ሊቀ ጳጳስ ባስልዮስን እረድቶ ከሃዲውን ዑልያኖስን የገደለበት ነው፡፡ ዑልያኖስ ነግሦ የክብር ባለቤት ጌታችንን ክዶ ጣዖታትን ማምለክና ክርስቲያኖችን ማሠቃየት ጀመረ፡፡ የቂሳርያው ሊቀ ጳጳስ ባስልዮስም አስተምሮ ሊመልሰው ወደ ንጉሡ ቢመጣ ክብር ይግባውና ዑልያኖስ ጌታችንን ሰድቦ ባስልዮስንም አሰረው፡፡ ባስልዮስም በእሥር ቤት ሳለ በቅዱስ መርቆሬዎስ ሥዕል ፊት ጸለየ፡፡ ሥዕሉም ወዲያው ተሰወረው፡፡ ያንጊዜም ወደ ከሃዲው ንጉሥ ዑልያኖስ ዘንድ ሄዶ በጦር ወግቶ ገደለውና ወዲያው ወደ ቦታው ተመለሰ፡፡ ከጦሩም አንገት ደም ይንጠፋጠፍ ነበር፡፡ ቅዱስ ባስልዮስም ከሃዲውን ንጉሥ እንደገደለው ዐውቆ ‹‹የክርስቶስ ምስክር ጌታዬ ሆይ የእውነት ፀር የሆነ ዑልያኖስን ገደልከውን?›› አለው፡፡ ሥዕሉም ያን ጊዜ አዎን እንደሚል ራሱን ዘንበል አደረገ፡፡ ቅዱስ ባስልዮስም ደስ ብሎት እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡
ሌላው ሰማዕት ቅዱስ መርቆሬዎስ በተአምሩ ከእስልምና እምነት መልሶ ክርስቲያን ያደረገው አንድ እስላም ሰው አለ፡፡ ይኸውም የቅዱስ መርቆሬዎስ ቤተ ክርስቲያኑ በተሠራችበት በምስር አገር የሚኖር ከመሳፍንት ወገን የሆነ ወጣት ነበረ፡፡ ከብዙ ሰዎችም ጋር ሆኖ ወደ መሐመድ መቃብር ለመሄድ እንዳሰበ ለአባቱ ሲነግረው ስንቅ ሰንቀው በሰላም ወደ መካ መዲና ሸኙት፡፡
መካ ደርሰውም ሥራቸውም ፈጽመው ወደቤታቸው እየተመለሱ ሰባት ቀን ተጓዙ፡፡ በሌሊትም ሲጓዙ ስለ ሥጋዊ ግዳጁ ያ እስላም ወጣት ከግመል ላይ ወርዶ ለመጸዳዳት ዘወር አለ፡፡ እነርሱም አብሯቸው የሚጓ መስላቸው ስለነበር ባልንጀሮቹም በበረሃው ውስጥ ትተውት ሄዱ፡፡ እርሱም ወዴት እንደሚሄድ ስላላወቀ አራዊትም እንዳይበሉት ፈርቶ እጅግ ደነገጠ፡፡
በዚያም ጊዜ በምስር አገር በአባቱ ቤት አቅራቢያ ያለች የሰማዕቱ የቅዱስ መርቆሬዎስን ቤተ ክርስቲያን አስታውሶ በልቡ ቅዱስ መርቆሬዎስን እንዲያድነው በመለመን ተሳለ፡፡ ወዲያውም ቅዱስ መርቆሬዎስ በፈረሱ ተቀምጦ ወደ እርሱ መጣና ‹‹ከወዴት ነህ? ከዚህ በረሃ ውስጥስ እንዴት ጠፋህ?›› አለው፡፡ ወጣቱ እስላምም የሆነውን ነገረው፡፡ ቅዱስ መርቆሬዎስም ‹‹ና በኋላዬ በፈረሱ ላይ ተፈናጠጥ›› አለውና በአየር ላይ እየበረረ በምስር አገር ወዳለች የቅዱስ መርቆሬዎስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንደ ዐይን ጥቅሻ አደረሰውና እንደተዘጋች በውስጧ አስገባውና ከእርሱ ተሰወረ፡፡ ይህም ወጣት በኋላ አምኖ ተጠምቆ ብዙ ሰማዕትነት ተቀብሏል፡፡ ገዳምም
ቅዱስ›› ብሎ የሹመትን ሀብት አሳደረባቸው፡፡ ዳግመኛም ‹‹በምድር ያሰርከው በሰማይ የታሰረ ይሁን፤ በምድርም የፈታኸው በሰማይ የተፈታ ይሁን፤ አንተን የሰማ እኔን መስማቱ ነው፤ የላከኝ አባቴንም መስማቱ ነው፡፡ አንተን እንቢ ያለ እኔን እንቢ ማለቱ ነው፡፡ የላከኝ አባቴንም እንቢ ማለቱ ነው፡፡ ይህን ሥልጣን ቀድሞ ለሐዋርያት ሰጥቻቸው ነበር፡፡ ከሐዋርያትም ሹመትን የተቀበለ ጳጳሱ ትሾምና ትሽር፣ ትተክልና ትነቅል ዘንድ ሥልጣንን ሰጠህ፡፡ ይህንንም ያደረኩልህ የጳጳሱን ቃል በመናቅ አይደለም፡፡ የፍቅሬን ጽናት ባንተ እገልጽ ዘንድ ነው እንጂ፡፡ ሐዋርያት ወዳልደረሱበት ሕዝብ በመምህርነት እልክህ ዘንድ በሚካኤል ቃል አዲስ ስም አወጣሁልህ፡፡ አንተም በማናቸውም ሥራ ከእነርሱ አታንስም፣ ሐዲስ ሐዋርያ አድርጌሃለሁና፡፡ ሰውን ሁሉ በእኔ ስም እያስተማርክ ታሳምን ዘንድ፣ ሚካኤልም ባሰብከው ሥራ ሁሉ ረዳት ይሁንህ፣ ሁል ጊዜ ካንተ አይለይም፤ በምትሄድበትም ጎዳና ሁሉ እርሱ መሪ ይሁንህ፤ እኔም ባለ ዘመንህ ሁሉ አልለይህም›› ካላቸው በኋላ ሰላምታ ሰጥቷቸው ዐረገ፡፡
ብፁዕ አባታችንም እጅ ነሥተው ‹‹ለእኔ ለኀጥኡ የማይገባኝ ሲሆን ይህን ሁሉ ጸጋ የጠኸኝ ስምህ በሰማይ በምድር የተመሰገነ ይሁን›› አሉ፡፡ ከዚያች ቀን ጀምሮ ሀብተ ኃይልን የተመሉ ሆኑ፡፡ ወደቤታቸው ተመልሰው ያላቸውን ሀብት ንብረት ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን፣ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ሰጥተው ጨረሱ፡፡ ከዚያም ‹‹አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደተከፈተ ተውኩልህ›› ብለው ቤታቸውን እንደተከፈተ ትተው ወንጌልን ለማስተማር ወጡ፡፡ ጻድቁ አባታችን በሀገራችን ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ ሕዝቡን ከኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ፣ ከክህደት ወደ ኃይማኖት ስለመለሱት በዚህም የተነሣ ለኢትዮጵያውያን ብርሃን ተብለዋል፡፡
አባ ተክለሃይማኖት ከበዓታቸው ሳይወጡ በጸሎት ተጠምደው ሌሊትና ቀን ይቆሙ ነበር። ከተጋድሎ የተነሳ ቁመትንም ካበዙ ወዲህ አንዲቱ የእግራቸው አገዳ ተሰበረች ደቀ መዛሙርቱ አንሥተው አክብረው በሰበን ጠቅልለው ከመንበሩ እግር በታች ቀበሯት። ከዚህም ባንዲት እግራቸው ሰባት ዓመትን ቆሙ። በዚህ ቀንም ቤተክርስቲያን በጸሎት ብዛት አንዲቱ የእግራቸው አገዳ የተሰበረበትን (ለስብረተ አፅማቸው) መታሰቢያ ታከብራለች።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር #ገድለ_ተክለ_ሃይማኖት #ከገድላት_አንደበት)
https://t.me/finotebirhan12
#ጥር_24
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር ሃያ አራት በዚህች ዕለት #አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት በጸሎት ብዛት አንዲቱ የእግራቸው አገዳ የተሰበረበት (ስብረተ አፅማቸው) መታሰቢያ ነው፣ የከበረች ተጋዳይ #ግብጻዊት_ቅድስት_ማርያ አረፈች፣ የሸዋው #እጨጌ_መርሐ_ክርስቶስ ዕረፍታቸው ነው፡።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት
ጥር ሃያ አራት በዚህች ዕለት ''ሐዲስ ሐዋርያ'' ብሎ የሾማቸው የኢትዮጵያ ብርሃኗ የሆኑ የደብረ ሊባኖሱ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በጸሎት ብዛት አንዲቱ የእግራቸው አገዳ የተሰበረበትን (ስብረተ አፅማቸው) መታሰቢያ ታከብራለች።
እግዚአብሔር አምላካችን ለኢትዮጵያ ሐዲስ ሐዋርያ አድርጎ የመረጣቸው ጻድቁ አባታችን ተክለ ሃይማኖት በሊቀ መላእክት በቅዱስ ሚካኤል አብሳሪነት ከአባታቸው ከካህኑ ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው ከቅድስት እግዚእ ኀረያ መጋቢት 24 ቀን ተፀንሰው ታኅሣሥ 24 ቀን 1197 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ ጻድቁ በተወለዱ በሦስተኛው ቀን ከእናታቸው ዕቅፍ ወርደው ‹‹አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ›› ማለትም ‹‹አንዱ አብ ቅዱስ ነው አንዱ ወልድ ቅዱስ ነው አንዱ መንፈስ ቅዱስ ቅዱስ ነው›› በማለት የፈጠራቸውን አምላክ አመስግነውታል፡፡ ወላጆቻቸውም ስማቸውን ፍሥሐ ጽዮን አሏቸው፡፡ ይኸውም የጽዮን ተድላዋ ደስታዋ ማለት ነው፡፡ የወላጆቻቸው የቀድሞ ስማቸው ዘርዐ ዮሐንስና ሣራ ይባል ነበር፡፡
ቅዱሳን አባቶቻችን እነ አቡነ ተክለ ሃይማኖትና እነ አቡነ ዜና ማርቆስ ሌሎቹም እነ አቡነ ሳሙኤል ዘወገግ፣ አቡነ ሕፃን ሞዐ፣ አቡነ አኖሪዮስ(ትልቁ)፣ አቡነ ገላውዲዮስ፣ አቡነ ማትያስ ዘፈጠጋርና አቡነ ቀውስጦስ ዘመሐግል የትውልዳቸው መሠረት ኢያሱ ለሌዋውያን ክፍል ትሆን ዘንድ ከለያት ከኢየሩሳሌም ነው፡፡ ስማቸውን የጠቀስኳቸው እነዚህ ቅዱሳን አባቶቻችን የወንድማማቾች ልጆች ሲሆኑ ከአዳም ጀምሮ 61ኛ ትውልድ ናቸው፡፡ ይኸውም እንዴት ነው ቢሉ ትውልዱ ከአዳም ጀምሮ በካህኑ አሮን በኩል የሆነውና የሌዋዊያን ሊቀ ካህን የነበረው የሳዶቅ ልጅ አዛርያስ በንጉሥ ሰሎሞን ዘመን ከታቦተ ጽዮንና ከብዙ ሌዋዊያን ካህናት ጋር ሊቀ ካህን ሆኖ ከኢየሩሳሌም ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ አክሱም ተቀምጦ ኖረ፡፡ የኦሪትንም ሕግ እየዞረ ለኢትዮጵያ ሰዎች አስተማረ፡፡ ትውልዱም በአብርሃ ወአጽብሓና በአባ ሰላማ ዘመን እስከነበረው እንበረም የሚባለው ጻድቅ ድረስ ደረሰ፡፡ የእንበረምም ትውልድ ደገኛው ሕይወት ብነ በጽዮን ድረስ ደረሰ፡፡ ሕይወት ብነ በጽዮንም የደማስቆ ምድር ከሚሏት ከወለቃ ሀገር የመኮንን ልጅ የሆነችውን ወለተ ሳውልን አግብቶ አበይድላን ወለደ፡፡ አበ ይድላም በንጉሡ ድልዓዥን ዘመነ መንግሥት ለ150 ካህናት አለቃ ሆኖ በወለቃ ሀገር የክርስቶስን የወንጌል ሕግ እያስተማረ ብዙዎችን አጠመቀ፡፡ እስከ ሸዋ ምድር ድረስ እያስተማረ መጥቶ በሸዋ ምድር ተቀመጠ፡፡ ብዙ አብያተ ክርስቲያናትንም አሳነጸ፡፡ እጅግ አስደናቂ ተአምራትንም ያደርግ ነበር፡፡ ‹‹በሸዋ ጽላልሽ ተቀምጦ ሲያስተምርም በአንዲት ቀን እስከ ሁለት መቶ ሺህ ሕዝብ ያጠምቅ ነበር›› በማለት ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ይመሰክርለታል፡፡
አበይድላ በመጨረሻ በፈቃደ እግዚአብሔር ከሸዋ ጽላልሽ ምድረ ዞረሬ ሚስት አግቶ ሀበነ እግዚእን ወለደ፤ ሀበነ እግዚእም በኩረ ጽዮንን ወለደ፤ በኩረ ጽዮንም ሕዝበ ቀድስን ወለደ፤ እርሱም ነገደ እግዚእ የተባለ ነው፡፡ ሕዝበ ቀድስም ብርሃነ መስቀልን ወለደ፤ እርሱም ዐቃቢነ እግዚእ የተባለ ነው፡፡ ብርሃነ መስቀልም ሕይወት ብነን ወለደ፤ እርሱም ሴትን ወለደ፡፡ ሴትም ወረደ ምሕረትን ወለደ፡፡ ወረደ ምሕረትም ዘካርያስን ወለደ፡፡ ዘካርያስም የእነ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አባት የሆኑ 6 ወንድማማች ልጆችን ወለደ፡፡ እነርሱም እንድርያስ፣ አርከሌድስ፣ ዘርዐ አብርሃም፣ ዘርዐ ዮሐንስ ወይም ጸጋ ዘአብ፣ ቀሲስ ዮሐንስና ቀሲስ ዮናስ ናቸው፡፡ እንድርያስም ሳሙኤል ዘወገግን ወለደ፤ አርከሌድስም ሕፃን ሞዐን ወለደ፤ ዘርዐ አብርሃምም ታላቁን አኖርዮስን ወለደ፤ ዘርዐ ዮሐንስ ወይም ጸጋ ዘአብም ተክለ ሃይማኖትን ወለደ፤ ቀሲስ ዮሐንስም ዜና ማርቆስን ወለደ፣ ቀሲስ ዮናስ ደግሞ የፈጠጋሩን ማትያስንና ገላውዲዮስን ወለዳቸው፡፡ ገላውዲዮስም የመሐግሉ ቀውስጦስን ወለደ፡፡ እነዚህ ደጋግ ቅዱሳን በእናታቸውም በኩል እንዲሁ በዝምድና የተሳሰሩ ናቸው:: ማቴዎስ የተባለው ደገኛ ክርስቲያን የሸዋ ገዥ የነበረ ሲሆን አንድ ወንድ ልጅ መድኃኒነ እግዚእንና ሦስት ሴቶች ልጆችን ወለደ፡፡ ሶስቱ ሴቶች ልጆችም እምነ ጽዮን፣ ትቤ ጽዮንና ክርስቶስ ዘመዳ ይባላሉ፡፡ ሦስቱ እኅትማማቾችም ደጋጎቹን አባቶቻችንን ወለዱልን፡፡ እምነ ጽዮን የእነ ዜና ማርቆስን እናት ማርያም ዘመዳንና ወለደች፡፡ ትቤ ጽዮንም ሕፃን ሞዐን ወለደች፡፡ ክርስቶስ ዘመዳ ደግሞ ታላቁን አኖሬዎስን ወለደች፡፡ የፈጠጋሩ ገዥ መድኃኒነ እግዚእ ደግሞ የተክለ ሃይማኖትን እናት እግዚእ ኀረያን ወይም በሌላ ስሟ ሣራን ወለደ፡፡
አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከልጅነታቸው ጀምሮ በወላጅ አባታቸው በካህኑ ቅዱስ ጸጋ ዘአብ ግብረ ዲቁናን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያጠኑ ቆይተው በ15 እና በ22 ዓመታቸው ከእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ከአቡነ ቄርሎስ (ጌርሎስ) ዲቁናንና ቅስናን ተቀብለዋል፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን ቅድስት ቤተክርስቲያንን በወጣትነት ዕድሜያቸው ያገለግሉ እንደነበር በዚህ ይታወቀል፡፡
ከዕለታት በአንዱ ቀን አባታችን ከጓደኞቻቸው ጋር ለአደን ወደ ዱር ሄደው ሳለ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ተገልጦ ታያቸው፡፡ ቅዱስ አባታችንም ‹‹እንደዚህ ባለ ገናንነት የማይህ ጌታዬ ማነህ?›› ባሉት ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል ‹‹ዘወትር የምጠብቅህ ካንተ የማልለይ እናትህንና አባትህንም ስላንተ ከውኃ ስጥመትና ከምርኮ ያዳንኳቸው እኔ ሚካኤል ነኝ፡፡ ከእንግዲህ አውሬ አዳኝ አትሁን፤ ሰውን ወደ እግዚአብሔር ለመመለስ ሰውን በትምህርት የምታድን ሁን እንጂ፡፡ እነሆ እግዚአብሔር ጽኑዕ ሥልጣን ሰጥቶሃልና፤ ሙት ታስነሣለህ፤ ድውያንን ትፈውሳለህ፤ አጋንንትም አንተን በመፍራት ይሸሻሉ፡፡ ስምህ ፍሥሐ ጽዮን አይሁን፤ ተክለ ሃይማኖት ይሁን እንጂ፡፡ ትርጓሜውም ተክለ አብ፥ ተክለ ወልድ፥ ተክለ መንፈስ ቅዱስ ማለት ነው›› አላቸው፡፡
ቅዱስ ሚካኤል ይህን ሲነግራቸው ጌታችን በሥጋ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር እንደነበር ሆኖ መልከ መልካም ጎልማሳ መስሎ ታያቸው፡፡ ጌታችንም ‹‹ወዳጄ እንዴት ሰነበትክ? ቸር አለህን?›› አላቸው፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ‹‹ጌታዬ ሆይ አንተ ማነህ?›› ብለው ሲጠይቁት ጌታችንም ‹‹እኔ የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ነኝ፤ በናትህ ማኅፀን ፈጥሬህ ያከበርኩህ እኔ ነኝ፡፡ በተወለድክ በሦስተኛው ቀን አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ ብለህ ታመሰግነኝ ዘንድ የምስጋና ሀብት ያሳደርኩብህ እኔ ነኝ፡፡ በርሃብ ዘመን በቤት የሚያሻው ምግብ ሁሉ ቅቤው፣ የስንዴው ዱቄት በእናት በአባትህ ቤት ይመላ ዘንድ በእጅህ ሀብተ በረከት ያሳደርኩብህ እኔ ነኝ፡፡ ያንን ሰው አንተን በተጣላ ጊዜ በነፋስ አውታር የሰቀለኩት በመዓት ጨንገር የገረፍኩት እኔ ነኝ፡፡ ውኃ ጠምቶህ በለመንከኝ ጊዜ ከደረቅ መሬት የጣፈጠ ውኃ ያመነጨሁልህ እኔ ነኝ፡፡ ከልጅነትህ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ብዙ ተአምራት እያደረግሁ በአንተ እጅ የታመሙትን ያዳንኳቸው እኔ ነኝ፡፡ ወደፊትም አደርግልሃለሁ›› አላቸው፡፡ ይህንን ብሎ በእጆቹ ባረካቸውና ‹‹ንሣእ መንፈስ
现已上线!2025 年 Telegram 研究 — 年度关键洞察 
