የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)
前往频道在 Telegram
2 639
订阅者
-224 小时
+87 天
+5630 天
帖子存档
🔴#ስንክሳር የካቲት_20
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ሃያ በዚህች እለት #አቡነ_ክፍለ_ማርያም_ዘዲባጋ የተሰወሩበት ነው፣ የእስክንድርያ 21ኛ ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_ጴጥሮስ አረፈ፣ አዝማሪው #ቅዱስ_ፊልሞን በሰማዕትነት ሞተ፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_ክፍለ_ማርያም_ዘዲጋባ
የካቲት ሃያ በዚህች እለት አቡነ ክፍለ ማርያም ዘዲባጋ የተሰወረበት ነው፡፡ እኚኽም ቅዱስ ትውልዳቸው እንደርታ ሲሆን በ14 ዓመታቸው መንኩሰው መንነው በቅተው ሲኖሩ በአንድ ወቅት ወደ አክሱም ሄዱና ወላጆቻቸው ካሉበት ደረሱ፡፡ ከቅዳሴ በኋላ መበለት ቆርሰው ሲያድሉ ወላጅ እናታቸው ከስተውና ጠቁረው ስላዩአቸው ለእናታቸው አዳልተው በብዙ ሰጧቸው፡፡ እናትየው ግን ጻድቁ የሠሩትን አያውቁም ነበር፡፡
ጻድቁ ከብቃታቸው የተነሳ መና ከሰማይ እየወረደላቸው ከዓለትም ላይ ውኃ እያፈለቁ ይጠጡ ነበር፡፡ አድሎ ስላደረጉ ግን በዚህ ድርጊታቸው እግዚአብሔር ተቆጥቷቸው የሰጣቸውን ይህን ጸጋቸውን ነሳቸው፡፡ አቡነ ክፍለ ማርያምም ይህን ባወቁ ጊዜ ‹‹ወዮልኝ ወዮታ አለብኝ›› ብለው ከሰው ሳይገናኙ ዋሻ ገብተው ድፍን 11 ዓመት በለቅሶና በዋይታ እግዚአብሔርን ለመኑት፡፡ በኋላም እግዚአብሔር ይቅር እንዳላቸው ነገራቸውና የቀደመ ጸጋቸውና ክብራቸው መለሰላቸው፡፡ ስለ ዘረኝነት አስከፊነትም በብዛት አስተማሩ፡፡
ከዛ በኋላ ውኃ ከደረቅ ጭንጫ ላይ እያፈለቁ አሕዛብን ሁሉ እያስተማሩ ያጠምቁ ጀመር፡፡ ኅብስትም ከሰማይ እየወረደላቸው ሕዝቡን ያቆርቡ ጀመር፡፡ ጻድቁ በመጨረሻ በዚህች ቀን እንደነ ሄኖክና ኤልያስ ዐርገዋል እንጂ በምድር ሞትን አልቀመሱም፡፡ ትልቅና አስደናቂ ገዳማቸው አክሱም ይገኛል፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ሊቀ_ጳጳሳት_ጴጥሮስ
በዚህችም ዕለት የከበረ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ጴጥሮስ አረፈ፡፡ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃያ አንደኛ ነው። ይህንንም ቅዱስ ከሐዋርያዊ አትናቴዎስ በኋላ በሹመቱ ወንበር በተቀመጠ ጊዜ ከንጉሥ ዳርዮስና ከከሀዲ አርዮስ ወገኖች ብዙ መከራ ደርሶበታል።
ሊገድሉትም በፈለጉ ጊዜ ሸሽቶ ሁለት ዓመት ያህል ተሠወረ አርዮሳውያንም ሉቅዮስ የተባለ ከሀዲውን ሰው በእርሱ ፈንታ በወንበሩ ላይ አስቀምጠው ሁለት ዓመት ኖረ።
ከዚህም በኋላ ሃይማኖታቸው የቀና ምእመናን ሁሉም ተነሥተው አርዮሳዊ ሉቅዮስን አሳደዱትና ይህን አባት ጴጥሮስን ወደ መንበረ ሢመቱ መለሱት አርዮሳውያንንም በመጣላት እያወገዛቸውና እያሳደዳቸው ሰባት ዓመት ኖረ። ከዚህም በኋላ ከዚህ ዓለም ድካም አርፎ ወደ ዘላለም ዕረፍት ሔደ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ፊልሞን_መዐንዝር
በዚህችም ዕለት መኰንን አርያኖስን የሚያጫውተው አዝማሪው ፊልሞን በሰማዕትነት ሞተ። በአንዲትም ዕለት አርያኖስ አናጉንስጢስ አስቃሎንን ጠርቶ ለአጵሎን ሠዋ አለው አስቃሎንም ወደ ፊልሞን ሒዶ በእኔ ፈንታ ብትሠዋ አራት የወርቅ ዲናር እሰጥሃለሁ አለው ፊልሞንም ልብስህን ስጠኝና ተሸፋፍኜ በአንተ ፈንታ እሠዋለሁ አለው።
በገባም ጊዜ አውቀውት ምን ሆንክ አሉት ፊልሞንም በክርስቶስ የማምን ክርስቲያን ነኝ አላቸው አርያኖስም በሕይወት እንድትኖር ለአማልክት ሰዋ አለው ፊልሞንም በክርስቶስ ስም ከመሞት በቀር ሕይወት የለም አለው።
አርያኖስም ጥምቀትን ሳታገኝ ፈጥኜ እገድልሃለሁ ተስፋህን ታጣለህ አለው ፊልሞንም ሰምቶ የክርስትና ጥምቀትን ያድለው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ በዚያንም ጊዜ ከሰማይ ብሩህ ደመና መጥቶ አጠመቀው።
አርያኖስም አፍሮ ቢመለስ ብሎ ሦስት ወታደሮች እንዲጸፉት አዘዘ ፊልሞንም የእግዚአብሔር መላእክት ስለ እኔ ደስ ሲላቸው አያለሁና ከዚህ የከፋ ቢጸፉኝም እኔ አላፍርም አለ። አርያኖስም ባላ ባለው ግንድ ላይ ሰቅለው በፍላፃዎች ይነድፉት ዘንድ አዘዘ ግን ምንም የነካው የለም ፍላፃውም እንዳልነካው ለአርያኖስ ነገሩት ዳግመኛም እርሱ እንደ ቆመ ይነድፉት ዘንድ አዘዘ አንዲቱም ፍላፃ ተመልሳ የአርያኖስን ዐይን ነድፋ ዐሳወረችው በዚያንም ጊዜ ከተሰቀለበት አውርደው ከአናጉንስጢስ አስቃሎን ጋር ራሱን እንዲቆርጡ አዘዘ ገድላቸውንም ፈጽመው የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ።
መኰንኑም በፍላፃው ሕመም በተሠቃየ ጊዜ ከቅዱሳን ደም ወስዶ ከዐይኑ ውስጥ እንዲጨምር ሰዎች መከሩት ይህንንም ሲያደርግ ዳነ በክብር ባለቤት በጌታችን ክርስቶስም አመነ እስረኞችንም ሁሉ ፈታቸው እርሱም መጋቢት ስምንት ቀን በዲዮቅልጥያኖስ እጅ በሰማዕትነት ሞተ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ለዘለዓለሙ ከእኛ ጋር ትሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12
ከዚኽም በኋላ ወላጆቻቸው ቅዱስ አቃርዮስ እና ቅድስት ታውክልያ በመልአኩ ትእዛዝ መሠረት ወደ አክሱሙ ሊቀ ጳጳስ ወደ አባ ሉቃስ ዘንድ ወሰዷቸው፡፡ ሊቀ ጳጳሱም ሊያጠምቋቸው ሲቀርቡ ህቡዓን የምስጢር ስሞቹ የመለኮት ቃል ስለሆኑ ወዲያውኑ ደንግጠው ወደቁ፡፡ በዚህም ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ በፍጥነት አነሣቸውና ‹‹…በዚህ በምታየው ተኣምር ይህንን ሕፃን አጥምቀው፣ ስሙንም በህቡዓን ስሞች ትርጉም መሠረት አባለ ክርስቶስ ብለህ ጥራው›› በማለት ነገራቸው፡፡ ዳግመኛም መልአኩ ስለ አቡነ አባለ ክርስቶስ ‹‹..እንደ ፋኑኤል መልአክና እንደ አምላኩ መድኀኒዓለም ክርስቶስ የሕሙማን መድኀኒት ይሆናል›› ብሎ ከነገራቸው በኋላ ተሰወረ፡፡
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር የካቲት_19
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ዐስራ ዘጠኝ በዚች እለት #የአባ_መርትያኖስ ስጋው የፈለሰበት ሆነ፣ ታላቁ ጻድቅ #አቡነ_አባለ_ክርስቶስም ልደታቸው ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ታላቁ_አባ_መርትያኖስ
የካቲት ዐስራ ዘጠኝ በዚች እለት የተጋዳይ መነኰስ የአባ መርትያኖስ ስጋው ከአቴና አገር ወደ አንፆኪያ የፈለሰበት ሆነ። እርሱም ሽንግላ በኃጢአት ልትጥለው በወደደች ጊዜ ከአመንዝራ ሴት ከተፈተነ በኃላ እርሱ ግን መንኲሳ በገድል እስከ ተፀመደች ድረስ ስቦ ወደ ንስሀ የመለሰ ነው።
ይህም አባት በልጅነቱ ከአንድ ቅዱስ የሆነ አረጋዊ አባት ዘንድ መንኵሶ ታላቅ ገድልን ተጋደለ። ከዚህም በኋላ ሐመረ ኖኅ ወደምትባል በቂሣርያ ወደአለች ገዳም ሔደ በዚያም እጅግ በጣም የበዛ ገድልን ተጋደለ።
በጸሎት በጾም በስግደትም በሌሊትና በመዓልት በመትጋት እየተጋደለ ስድሳ ሰባት ዓመት በኖረ ጊዜ የገድሉና የትሩፋቱ ወሬ በቦታው ሁሉ ተሰማ። እነሆ አንዲት በክፉ ሥራዋና በዝሙቷ የታወቀች ኃጢአተኛ አመንዝራ ሴት ሰማች። ጽድቁንና ቅድስናውን በመናገር የሚያመሰግኑትን እንዲህ አለቻቸው። እናንተ ታመሰግኑታላችሁ እርሱ የሚኖረው በዱር ነው የሴት ገጽ ከቶ አያይም እኔን ቢያይ ድንግልናውን አጥፍቼ ቅዱስናውን በአረከስኩት ትኀርምቱንም ባፈረስኩት ነበር። እነርሱ ግን ጥንክርናውን ስለ ሚያውቁ ተከራከሩዋት። ስለዚህም በመካከላቸው ክርክር ሆነ ሔጄ ከእኔ ጋራ በኃጢአት ብጥለው ምን ትሰጡኛላችሁ አለቻቸውና ገንዘብ ሊሰጡአት ተስማሙ።
ያን ጊዜም ተነሥታ ጌጦቿን ልብሶቿንና ሽቱዎቿን ያዘች መልኳም እጅግ ውብ ነበረች ፊቷንም ተከናንባ ጨርቅ ለብሳ ወደ በዓቱ ሔደች። ልብሷንና ጌጦቿንም ለብቻቸው በከረጢት አሥራ ያዘች። ከበዓቱም ቅርብ በሆነ ቦታ ተሠውራ እስከ ሚመሽ ቆይታ የበዓቱን ደጃፍ አንኳኳች። አራዊት እንዲበሉኝ በውጭ አትተወኝ እኔ መጻተኛ ነኝና መንገድንም ተሳስቼ ወደዚህ ደረስኩ አለችው። እርሱም በልቡ አሰበ በውጭ ብተዋት አራዊት ይበሏታል ባስገባትም ስለርስዋ ጦር በኔ ላይ ይነሣብኛል አለ።
ከዚህም በኋላ ከፈተላት በዚያችም በዓት ውስጥ ትቷት ወደ ሌላ ቦታ ፈቀቅ አለ። እርሷ ግን ልብሶቿን ለብሳ ጌጦቿንም ተሸልማ ሽቱዎቿን ተቀብታ ወደርሱ ገባች ከርሷ ጋርም እንዲተኛ ፈልጋ ከዚህ ማንም የሚያየን የለም አለችው።
ቅዱሱም የሰይጣን ማጥመጃው እንደሆነች አውቆ ጥቂት ታገሺኝ መንገድን እስታይ እግዚአብሔርን የማንፈራው ከሆነ እንደእኛ ያሉ ሰዎችን ላንፈራቸው ይገባናል አላት። ይህንንም ብሎ ከእርሷ ዘንድ ወጣ ታላቅ እሳትም እንድዶ እግሩን ከውስጡ ጨመረ ነፍሱንም የሲኦልን እሳት የምትችዪ ከሆንሽ ኃጢአትን ሥሪያ አላት።
በዘገየ ጊዜ ወደርሱ ሔደች በእሳት ውስጥም እግሩን ሲያቃጥል አይታው እጅግ ደነገጠች። ከእሳትም ውስጥ ጐትታ አወጣችው ልቧም ወደ ንስሓ ተመለሰ። ልብሷንና ጌጦቿን ከላይዋ አውጥታ ጣለች ከእግሩ በታች ሰገደች ስለነፍሷ ድኅነትም እንዲረዳት ለመነችው። እርሱም ይህ ዓለም ፍላጎቱ ሁሉ ኀላፊ እንደ ሆነ ያስተምራትና ይመክራት ልብ ያስደርጋትም ጀመር እርሷም በጨከነ ልብ ንስሓ ገባች። ከዚህም በኋላ በአንድነት መኖር አግባብ አይደለም ብሎ ወደ ደናግል ገዳም ወሰዳት ትጠብቃትም ዘንድ እመ ምኔቷን አደራ አላት። በቀረው ዕድሜዋም በገድል ተጠምዳ እግዚአብሔርን አገለገለችው ወደ በጎ ሽምግልናም ደረሰች የመፈወስ ሀብትም አድሮባት ብዙዎች በሽተኞችን አዳነች።
የከበረ አባ መርትያኖስ ግን ሌላ ሴት እንዳያመጣበት ፈርቶ በባሕር መካከል ወዳለች ደሴት ገብቶ በዚያ የሚኖር ሆነ። አንድ ባለ ታንኳም የእጅ ሥራውን እየሸጠ ምግቡን ያመጣለት ነበር። ከብዙ ዘመናትም በኋላ መርከብ ተሰብራ ሰጠመች አንዲት ሴትም በመርከብ ስባሪ ተጣብቃ አባ መርትያኖስ ወደ አለበት ደሴት የባሕሩ ማዕበል አደረሳት በአያትም ጊዜ ደነገጠ አደነቀም። ከእርሷ ጋር በአንድነት ስለ መኖሩም አዘነ የእግዚአብሔርንም ቃል አስተምሮ የምንኲስና ልብስ አለበሳት ምግቧንም አዘጋጀላትና ለእኛ በአንድነት መኖር አግባብ አይደለም አላት። ያንንም ደሴት ትቶላት ወደ ባሕሩ ተወርውሮ ገባ አንበሪም ተሸክሞ ወደ የብስ አወጣው።
መቶ ስምንት አገሮችንም እስቲአዳርስ በአገሮች በአሉ ገዳማት ሁሉ ከዚያች ቀን ጀምሮ የሚዞር ሆነ በአንድ ቦታ እንዳይቀመጥ አስቦ ነው። ከዚህ በኋላም የዕረፍቱ ጊዜ እንደ ቀረበ አውቆ በበዓት ውስጥ ራሱን እሥረኛ አደረገ። ኤጲስቆጶሱንም ጠርቶ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ገድሉን ሁሉ ነገረው ኤጲስቆጶሱም ከጸጋው ገናናነት የተነሣ አደነቀ።
ከዚህም አስቀድሞ የእግዚአብሔር መልአክ ለኤጲስቆጶሱ ስለአባ መርትያኖስ ሥጋ እንዲአስብ ነግሮት ነበር። ከዚህም በኋላ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ ኤጲስቆጶሱም በታላቅ ክብር ገንዞ ቀበረው።
ያቺን ሴት ግን እስከ ዕረፍቷ ቀን ባለ መርከብ የሚጎበኛት ሆነ በአረፈችም ጊዜ ሥጋዋ እንደ በረዶ ነጥቶ አገኛት ሥጋዋንም ወደ ሀገሩ ተሸክሞ ወስዶ ቀበራት።
የከበረ ቴዎድሮስም ለአንፆኪያ ሀገር በከሀዲው የፋርስ ንጉስ ዘመን ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜ ይህ አባት የካህናት አለቆችንና ምእመናንን ልኮ ስጋውን ከአቴና አፍልሰው ወደ አንፆኪያ ከተማ አመጡት በምስጋናም እየዘመሩ አክብረው ተቀበሉት ሊቀ ጳጳሳቱም ተሳለመው በሳጥን አድርጎ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖረው። በዚችም እለት በአልን አደረጉለት።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_አባለ_ክርስቶስ
ዳግመኛም በዚህች ቀን ታላቁ ጻድቅ አቡነ አባለ ክርስቶስም ልደታቸው ነው። እርሳቸውም ገና ሲወለዱ ከሰውነታቸው ህቡዕ የሆኑ የእግዚአብሔር የምሥጢር ስሞች በሰውነታቸው ላይ ይዘው (ተጽፎባቸው) የተወለዱ ናቸው፡፡
አባታቸው ቅዱስ አቃርዮስ እናታቸው ቅድስት ታውክልያ የተባሉ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ደጋግ ቅዱሳን ናቸው፡፡ እነዚህ ቅዱሳን የኢትዮጵያ ነገሥታት መዲና በሆነችው በአክሱም ከተማ በንጉሥ አንበሳ ውድም በ910 ዓ.ም በቤተ ክርስቲያን ሥርዓትና ሕግ በቅዱስ ጋብቻ ተጋቡ፡፡ ንጉሥ አንበሳ ውድም በነገሠ በመጀመሪያ ዓመት እነርሱም በጾም በጸሎት ተወስነው ሲኖሩ እግዚአብሔር የተባረከ ልጅ ቅዱስ አባለ ክርስቶስን ሰጣቸው፡፡ በዚኽም መሠረት አቡነ አባለ ክርስቶስ የካቲት 19 ቀን በአክሱም ከተማ ተወለዱ፡፡ እንደ ነቢዩ ቅዱስ ኤርምያስ በእናታቸው ማሕፀን ሳሉ የተመረጡ ብፁዓት ናቸውና ብፁዕ አባታችን አባለ ክርስቶስ ከሰውነታቸው ህቡዕ የሆኑ የእግዚአብሔር የምሥጢር ስሞች በእብራይስጥ ቋንቋ ‹‹ዲካባ፣ ማርትያስ፣ ክስብኤል›› የተባሉ ህቡዓን የምሥጢር ስሞችን በሰውነታቸው ላይ ይዘው (ተጽፎውባቸው) ተወለዱ፡፡
እናታቸውና አባታቸው ይኽንን ተኣምር በማየት እየተደነቁና እየተገረሙ ትርጉሙ ምን ይሆናል እያሉ ሲደነቁ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል በድንገት መጥቶ ‹‹የእግዚአብሔር አገልጋዮች ጻድቃን ሆይ! ሰላም ለእናንተ ይሁን›› አላቸው፡፡ ዳግመኛም ‹‹እኔ የመጣሁት በእግዚአብሔር ትእዛዝ ነውና እነዚህን የእግዚአብሔር ህቡዓን ስሞች ልተረጉምላችሁ መጥቻለሁ፤ ይህ ታላቅ ስም አባለ ክርስቶስ ተብሎ ይጠራል አላቸው፤ ትርጉሙም አጋንንትን የሚያሥር፣ ጠላትን የሚያርቅ ማለት ነው ›› ብሎ ትርጒሙን ከነገራቸው በኋላ እንዲያጠምቁት አዘዛቸውና ከእነርሱ ተሰወረ፡፡
🔴#ስንክሳር የካቲት_18
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ዐሥራ ስምንት በዚች ቀን ታማኝ የከበረ አባት የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_መላልዮስ አረፈ፣ ከ72ቱ አርድእት አንዱ የሆነ የጌታችን ወንድም የተባለ የአረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍ ልጅ የሐዋርያ #ቅዱስ_ያዕቆብ መታሰቢያው ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አባ_መላልዮስ_ጻድቅ
የካቲት ዐሥራ ስምንት በዚች ቀን ታማኝ የከበረ አባት የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት አባ መላልዮስ አረፈ። ይህም ቅዱስ አዋቂና አስተዋይ ነበረ በታናሹ ቈስጠንጢኖስም ዘመነ መንግሥት በአንጾኪያ ሀገር ሊቀ ጵጵስና ተሾመ።
ከተሾመም እስከ ሠላሳ ቀን ኖረ ከዚህም በኋላ አርዮሳውያንን አወገዛቸው በአንጾኪያም ካለች ቤተ ክርስቲያን ሁሉንም አሳደዳቸው። ንጉሡም በሰማ ጊዜ ከመንበረ ሢመቱ ሊቀ ጳጳሳቱን አሳደደው እርሱ ንጉሡ አርዮሳዊ ነውና።
የአንጾኪያ አገርም ታላላቆችና ኤጲስቆጶሳት ካህናቱም ተሰበሰቡ ስለ ሊቀ ጳጳሳቱ ይመልስላቸው ዘንድ የልመና ደብዳቤ ጽፈው ላኩ ንጉሡም ልመናቸውን ተቀብሎ መለሰላቸው። ይህም አባት በተመለሰ ጊዜ አርዮሳውያንን ወደ ማውገዙ ተመለሰ በቃላቸው የሚያምኑትንም ስሕተታቸውንና ስድባቸውን ግልጽ እያደረገ ወልድ ከአብ ባሕርይ እንደ ተወለደ በመለኮቱም ትክክል እንደሆነ ለሁሉ የሚሰብክ የሚያስተምር ሆነ።
ዳግመኛም አርዮሳውያን ተነሡ የንጉሡን ልብ ወደእሳቸው እስከ መለሱት ድረስ ይህን አባት እየወነጀሉ ወደ ንጉሥ ጻፉ ዳግመኛም ልኮ ከፊተኛው ወደሚርቅ አገር አሳደደው። ወደ ተሰደደበትም አገር በደረሰ ጊዜ መልእክቶቹን ጽፎ በመላክ ከወገኖቹ ጋር እንዳለ ሆነ ከእርሳቸውም ሥውር የሆነውን የመጻሕፍትን ቃል ይተረጉምላቸው ነበር በአንጾኪያ ላሉ መንጋዎቹም ይደርሳቸዋል አዋቂዎች የሆኑ ኤጲስቆጶሳትንና ቀሳውስትን ልዩ በሆነች ሦስትነት ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ አባቶቻችን ያስተማሩዋት የቀናች ሃይማኖትን እንዲአስተምሩ ያዛቸዋል እንዲህም እያደረገ እስከ ዐረፈባት ቀን ድረስ በተሰደደበት ብዙ ዘመናት ኖረ።
ዮሐንስ አፈወርቅም አመስግኖታል የምስጋና ድርሰቶችንም ደረሰለት ስለ ቀናች ሃይማኖትም ብዙ መከራ ስለ ደረሰበት ክብሩና ግርማው ከከበሩ ሐዋርያት ክብር እንደማይጎድል ተናገረ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ሐዋርያው_ቅዱስ_ያዕቆብ
በዚችም ዕለት ከ72ቱ አርድእት አንዱ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ የጌታችን ወንድም የተባለ የአረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍ ልጅ የሐዋርያ ቅዱስ ያዕቆብ መታሰቢያው ነው።
ይህም ቅዱስ የጠራቢው የዮሴፍ ልጅ ነው። እርሱም ከልጆቹ ሁሉ የሚያንስ ነበር። እርሱም ንጹሕ ድንግል ነበር ከጌታችንም ጋራ አደገ ስለዚህም ክብር ይግባውና የጌታችን ወንድም ተባለ። ከጌታችን ዕርገትም በኋላ ሐዋርያት በኢየሩሳሌም ላይ ኤጲስቆጶስ አድርገው ሾሙት። ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አስተምሮ ብዙዎችን ወደ ቀናች ሃይማኖት መለሳቸው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው።
እግዚአብሔርም በእጆቹ ታላላቅ ድንቆችንና ተአምራቶችን አደረገ። በአንዲት ዕለትም በጐዳና ሲጓዝ አንድ ሽማግሌ አገኘ። ቅዱስ ያዕቆብም ሽማግሌ ሆይ በቤትህ ታሳድረኛለህን አለው። አረጋዊውም እሺ እንዳልክ ይሁን አለ በአንድነትም ሲጓዙ ጋኔን ያደረበት ሰው አገኘው በአየውም ጊዜ የክርስቶስ ሐዋርያ ሆይ እኔ ካንተ ጋር ምን አለኝ ልታጠፋኝ መጣህን ብሎ ጮኸ ሐዋርያውም በናዝሬቱ ኢየሱስ ስም ተጠጋ ከሰውዬውም ውጣ አለው። ወዲያውም ያ ጋኔን ከሰውዬው ላይ ወጣ።
ያ ሽማግሌም ይህን ድንቅ ተአምር አይቶ ደነገጠ ከሐዋርያው እግር በታችም ወድቆ እንዲህ አለው። ወደ ቤቴ ልትገባ አይገባኝም ነገር ግን እድን ዘንድ ቤተሰቦቼም ሁሉ ይድኑ ዘንድ ምን ላድርግ አለ ያን ጊዜም ሐዋርያው አቤቱ ጌታዬ ሆይ መንገዴን አሳምረህልኛልና አመሰግንሃለሁ ብሎ ጌታችንን አመሰገነው። ወደ ሽማግሌውም ተመልሶ የድኅነትን ነገር ነገረው ክብር ይግባውና ስለ ጌታችን ሰው መሆን ስለ መከራው ስለ ሞቱና ስለ መነሣቱ አስተማረው።
ከዚህም በኋላ ያ ሽማግሌ ሐዋርያውን ወደ ቤቱ አስገባው ቤተሰቦቹም ሁሉ ወደርሱ ተሰበሰቡ ቅዱስ ያዕቆብም አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው። ሥጋውንና ደሙንም አቀበላቸው።
የከተማው ሰዎችም በሰሙ ጊዜ በሽተኞችን ሁሉ ወደርሱ አመጡ ሁሉንም አዳናቸው ለእነርሱም ሃይማኖትን አስተምሮ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው፡፡ ቀሳውስትንና ዲያቆናትንም ሾመላቸው ያንን ሽማግሌም ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾመው ክብር ይግባውና የጌታችንንም ወንጌል ሰጣቸው ከዚህም በኋላ ያስተምር ዘንድ ወደ ሌሎች አገሮች ወጥቶ ሔደ።
አንዲት መካን ሴት ነበረች እግዚአብሔር ልጅን ይሰጣት ዘንድ ስለርሷ እንዲጸልይላት ቅዱስ ያዕቆብን ለመነችው። እርሱም ጸለየላትና ወንድ ልጅን ወለደች ስሙንም ያዕቆብ ብላ ጠራችው ልጅዋንም ተሸክማ ወደ ሐዋርያው መጥታ ሰላምታ አቀረበችለት ከልጅዋም ጋር ከእርሱ ተባረከች።
ከዚህም በኋላ በአንዲት ቀን ብዙዎች አይሁድ ወደርሱ ተሰበሰቡ ስለ ጌታ ስለ ኢየሱስም የማን ልጅ እንደሆነ ይነግራቸው ዘንድ ጠየቁት እነርሱ እርሱ ጌታን የዮሴፍ ልጅ እንደሆነ እርሱም ወንድሙ እንደሆነ እንደሚነግራቸው አስበው ነበርና።
ቅዱስ ያዕቆብም በሦስተኛ ደርብ ላይ ወጥቶ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነም ከአብ ጋራም ትክክል እንደሆነ ይገልጽላቸው ጀመረ። ይህንንም በሰሙ ጊዜ እጅግ ተቄጡ ከደርቡ ላይ አውርደው የጸና ግርፋትን ገረፉት ከእነርሱም ውስጥ የልብስ ማጠቢያ የዕንጨት ገበታ የያዘ አንድ ሰው መጣ በዚያ ዕንጨትም ቅዱስ ያዕቆብን ራሱ ላይ መታው ያን ጊዜም ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ።
ስለ እርሱም ወይን እንዳልጠጣ፣ ደም ካለው ወገን እንዳልበላ፣ በራሱም ላይ ምላጭ እንዳልወጣ፣ በውሽባ ቤት እንዳልታጠበ፣ ሁለት ልብስንም እንዳልለበሰ፣ ሁልጊዜም እንደሚቆምና እንደሚሰግድ ተጽፎአል። ከመቆም ብዛት የተነሣም እግሮቹ አብጠው ነበር፤ ከዚህም በኋላ አረፈና በቤተ መቅደሱ ጐን ቀበሩት።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
የየካቲት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ዓመታዊ ክብረ በዓል ላይ የተነሱ የፎቶ ማስታወሻ 2015 ዓ.ም
🔴#ስንክሳር የካቲት_17
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ዐስራ ሰባት በዚችም ቀን የእግዚአብሔር ሰው የሆነ የዋህ ቅን ጻድቅ #የሊቀ_ነቢያት_ሙሴ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፣ በዚህች ቀን ከላይኛው ግብጽ ከአክሚም መንደር #መነኰስ_ቅዱስ_ሚናስ በሰማዕትነት ሞተ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ሙሴ_ሊቀ_ነቢያት
የካቲት ዐስራ ሰባት በዚችም ቀን የእግዚአብሔር ሰው የሆነ የዋህ ቅን ጻድቅ የሊቀ ነቢያት ሙሴ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው። ይህ ነቢይ ነፍሱን ስለእሳቸው አሳልፎ እስከ መስጠት ከእግዚአብሔር ወገኖች ጋር የደከመ ነው እርሱም በግብጽ አገር በኤርትራ ባሕርም ድንቆች ተአምራትን ያደረገ ነው።
ይህም ስለ ፈርዖን ትእዛዝ ወላጆቹ በግብጽ ወንዝ ውስጥ በጣሉት ጊዜ አውጥታ ላሳደገችው ለፈርዖን ልጅ ለተርሙት ልጅዋ መባልን አልወደደም። እርሱ ፈርዖን የዕብራውያንን ወንዶች ልጆች ይገድሏቸው ዘንድ አዝዞ ነበርና። በአገኘችውም ጊዜ ለርሷ ልጅ ሊሆናት ወስዳ በመልካም አስተዳደግ አሳደገችው።
አርባ ዓመትም በሆነው ጊዜ አንዱን ዕብራዊ የግብጽ ሰው የሆነ ሲያጠቃው አየ ለዕብራዊውም ተበቅሎ ግብጻዊውን ገደለው። በማግሥቱ ደግሞ ሁለት ዕብራውያን እርስ በርሳቸው ሲጣሉ አያቸው ሊአስታርቃቸውና በመካከላቸው ሰላምን ሊአደርግ ወደደ። አንዱ ዐመፀኛም ትላንት ግብጻዊውን እንደገደልከው ልትገድለኝ ትሻለህን አለው።
ስለዚህም ነገር ሙሴ ፈርቶ ወደ ምድያም አገር ሸሸ በዚያም ሚስት አግብቶ ሁለት ልጆችን ወለደ በዚያም አርባ ዓመት ኖረ በጳጦስ ቍጥቋጦ ውስጥም እሳት እየነደደ ራእይን አየ። አይቶ ሊረዳ በቀረብ ጊዜ ጳጦስ በተባለ ቊጥቋጦ ውስጥ እግዚአብሔር ተናገረው። ወደ ግብጽ አገርም ሒዶ የእስራኤልን ልጆች ከዚያ እንዲአወጣቸው አዘዘው።
ከዚህን በኋላ እግዚአብሔር በሙሴ እጅ በግብጻውያን ላይ ዐሥር መቅሠፍቶችን አመጣ። መጀመሪያው የወንዙን ውኃ ደም ማድረግ የመጨረሻው የግብጻውያንን የበኵር ልጅ መግደል ነው።
ከዚህም በኋላ ሕዝቡን ከግብጽ አገር አወጣቸው የኤርትራንም ባሕር ከፍሎ በውስጡ አሳለፋቸው የባሕሩንም ውኃ በጠላቶቻቸው በፈርዖንና በሠራዊት ላይ ገልብጦ አሠጠማቸው።
ከዚህም በኋላ በምድረ በዳ ውስጥ አርባ ዓመት ሙሉ መና አወረደላቸው ውኃንም ከአለት አፈለቀላቸው ይህን ሁሉ በጎ ሥራ በዚህ በደግ ነቢይ ሙሴ እጅ እግዚአብሔር አደረገላቸው እነርሱ ግን ይዘልፉት ነበር ብዙ ጊዜም በድንጊያ ሊወግሩት ሽተው ነበር።
እርሱ ግን በእነርሱ ላይ ልቡን አስፍቶ በመታገሥ ስለርሳቸው ወደ እግዚአብሔር ይማልዳል። እነርሱንም አብዝቶ ከመውደዱ የተነሣ እግዚአብሔርን አቤቱ የዚህን ሕዝብ በደሉን ይቅር ካላልክ ከሕይወት መጽሐፍህ ሰርዘኝ አለው።
ሰው ከወዳጁ ጋር እንደሚነጋገር አምስት መቶ ሰብዓ ቃላትን ከእግዚአብሔር ጋር እንደተነጋገረ መጽሐፍ ምስክር ሆነ። የእስራኤል ልጆችም በሚያዩት ጊዜ እንዳይሞቱ ፊቱን እስከ ሸፈነ ድረስ በእግዚአብሔር በጌትነቱ ብርሀን ፊቱ በራ።
መቶ ሃያ ዓመት የሆነ ዕድሜውም በተፈጸመለት ጊዜ ለአገልጋዩ ለነዌ ልጅ ለኢያሱ ሕዝቡን እርሱ እንደጠበቃቸው እንዲጠብቃቸው በእጁ ውስጥ እንዲአስረክበው እግዚአብሔር ሙሴን ለኢያሱ አስረክብ ብሎ አዘዘው።
ሙሴም ኢያሱን ጠርቶ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ አዘዘው ሕጉንም እንዲጠብቅ ሕዝቡንም ለኢያሱ በእጁ አስረከባቸው ወደ ምድረ ርስትም እርሱ እንደ ሚአስገባቸው አረጋገጠለት፡፡ ሙሴም እግዚአብሔር እንዳዘዘው በምስክሩ ድንኳን ውስጥ የሚሠራውን ሁሉ ሠርቶ ከአዘጋጀ በኋላ በተራራ ውስጥ አረፈ በዚያም በመላእክት እጅ በሥውር ተቀበረ። የእስራኤል ልጆች ወስደው እንዳያመልኩት እግዚአብሔር የሙሴን ሥጋ ሠወረ።
በእስራኤል ልጆች ውስጥ እንደ ሙሴ ያለ ደግ የዋህ ቅን የሆነ ነቢይ እንደማይነሣ መጽሐፍ ምስክር ሆነ። ሰይጣንም የሙሴን ሥጋ ለእስራኤል ሊገልጥላችው በወደደ ጊዜ ሐዋርያው ይሁዳ በጻፈው መጽሐፉ እንደመሰከረ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ገሠጸው ከዚህም ሥራ ከለከለው የእስራኤል ልጆችም አርባ ቀን አለቀሱለት።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ሚናስ_ግብጻዊ (ሁለተኛው)
በዚህች ቀን ከላይኛው ግብጽ ከአክሚም መንደር መነኰስ ሚናስ በሰማዕትነት ሞተ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ ምድርን የሚያርሱ ክርስቲያን ገበሬዎች ናቸው እርሱም ይህን ዓለም ንቆ ትቶ በሀገረ አክሚም በሚገኝ በአንድ ገዳም መነኰሰ ለመብልና ለመጠጥ ሳይገዛ በየሁለት ቀን እየጾመ ብዙ ቀኖችን ኖረ ከዚያም ወጥቶ ወደ እስሙናይን ሀገር ሒዶ በአንድ ገዳም ውስጥ እያገለገለና እየተጋደለ ከገዳሙ ደጃፍ ሳይወጣ ዐሥራ ሰባት ዓመት ኖረ።
እስላሞችም በግብጽ አገር በነገሡ ጊዜ ለእግዚአብሔር ከርሱ ጋር ለዘላለሙ ህልው የሆነ ከባሕርዩ የተወለደ ልጅ የሚሠርፅ መንፈስ ቅዱስም የለውም እንደሚሉ ሰማ ስለዚህም ነገር እጅግ አዘነ።
ከአበ ምኔቱም ቡራኬ ተቀበለ ወደ እስሙናይን ከተማ ወጥቶ ሔደ የእስላሞች ሠራዊት አለቃ በሆነ በመኰንኑ ፊት ቁሞ እንዲህ አለው። እናንተ ለእግዚአብሔር ከባሕርዩ የተወለደ ልጅ እንደሌለው አድርጋችሁ የምትናገሩ እውነት ነውን መኰንኑም አዎን ልጅ አለው ማለትን ከእግዚአብሔር እናርቃለን አለ።
አባ ሚናስም ያለ ልጅ ልታምኑ አይገባም እርሱም ያለ ዘር ያለ ሩካቤ የሆነ ነው ከባሕርዩ ተወለደ እንጂ አለው። መኰንኑም ልጅ አለው ማለት በሕጋችን ክህደት ነው አለ አባ ሚናስም እንዲህ አለው መኰንን ሆይ እወቅ የከበረ ወንጌል በወልድ ያመነ የዘላለም ሕይወት አለው በእግዚአብሔር ልጅ በወልድ ያላመነ ሕይወትን አያይም የእግዚአብሔር ቁጣ በላዩ ይወርዳል እንጂ ብሏልና።
ስለዚህም መኰንኑ እጅግ ተቆጣ ራሱንም በሰይፍ እንዲቆርጡ ሥጋውንም በየቊርጥራጭ ቆራርጠው በባሕር እንዲጥሉት አዘዘ ምእመናንም ሥጋውን ወስደው በበጎ አገናነዝ ገንዘው ቀበሩት መታሰቢያውንም አደረጉ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
ድግስ አድርጎ ስለጠበቃቸው ‹‹የንጉሡ ልጅ ሞተ የተባለው ውሸት ነው›› ብለዋል። ቅዱስ ነአኵቶለአብ ክህነትን ከንግስና ይዘው ኢትዮጵያን ከመሩ ከአራቱ የዛጉዌ ነገሥታት አንዱ ሲሆን በነገሠበት 40 ዓመት ሙሉ ዓርብ ዓርብ ቀን የክርስቶስን ሕማም እያሰበ በዕንቁና በወርቅ በተሸቆጠቆጠው ዘውዱ ፈንታ የእሾህ አክሊልን ደፍቶና በአምስቱ ቅንዋተ መስቀሎች ምሳሌ አምስት ጦር ዙሪያውን ተክሎ እያለቀሰ ይጸልይና ይሰግድ ነበር። ለፍርድም በተቀመጠ ጊዜ ከንግሥና ልብሱ ውስጥ በስውር ማቅ ለብሶና ሰውነቱን በሰንሰለት አስሮ ከላይ ግን በክብር ልብሱ ተሸፍኖና በወርቅ ወንበር ተቀምጦ ይፈርድ ነበር። ፍርድ ሲሰጥም ሁሉንም ነገር በመንፈስ ቅዱስ እያውቅ ነበር።
ይህ ጻድቅና ቅዱስ ንጉሥ በዘመኑ ግብፆች ግብር አንሰጥም ብለው ስላመፁበት የዓባይን ወንዞች በጸሎቱ ወደ ሌላ ቦታ እንዲፈሱ ስላደረገባቸው ግብፆች ከበፊቱ ጨምረው ግብራቸውን አምጥተው ሰጥተውት ግዝቱን አንስቶላቸዋል።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ጻድቁ_አቡነ_መልከ_ጼዴቅ
ዳግመኛም በዚህች ዕለት ጻድቁ አቡነ መልከጼዴቅ ዘሚዳ ልደታቸው ነው። ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ መልከጼዴቅ። አቡነ መልከጼዴቅ በ13ኘው መ/ክ/ዘ መጨረሻ በንጉሥ ዐፄ በእደ ማርያም ዘመነ መንግሥት የነበሩ እደጃቸው የተቀበረውን ሰው አፈር የማያስበሉ እጅግ ድንቅ ቃልኪዳን ያላቸው ታላቅ አባት ናቸው። የአምላካቸውን የክርስቶስን መከራ ለማሰብ ገዳመ ቆሮንቶስን የመሰለ ዋሻ ቆፍረውና በዚያ ገብተው ቀንና ሌሊት ዘግተው በረደኝ ፀሐይ ልሙቅ፣ ጨለመኝ ብርሃን ልይ ሳይሉ በጸሎት ብቻ ዘግተው በመኖር ራሳቸውን በችንካር እያቆሰሉና ጭንቅላታቸውን እያተሉ ትሉን ለሰማይ አእዋፍ ይመግቡ ነበር። እግዚአብሔር ወልድ የተገረፈውን ግርፋት እያሰቡ በየቀኑ እስከ 3ሺህ ድረስ ይሰግዱ ሰውነታቸውንም እንዲሁ ይገርፉ እንደነበር መጽሐፈ ገድላቸው ይናገራል። የክርስቶስን መቸንከር እያሰቡ እጅና እግራቸውን፣ ወገብና ደረታቸውን በብረት ቸንክረው መከራውን ያስቡ ነበር። ጎኑ በጦር መወጋቱን አስበው አጥንታቸው እስኪሰበር ድረስ ጎናቸውን ወጉ። ሐሞትና ከርቤ መጠጣቱን አስበው እርሳቸውም መራራ ይጠጡና አንክርዳድን ይመገቡ ነበር። ሞቱን አስበው ደም እንባን ያነቡ ነበር። በእንደዚህ ዓይነቱ ተጋድሎ የክርስቶስን መከራ እያሰቡ ነቢያን፣ ሐዋርያትን፣ ሰማዕታትን፣ ደናግል መነኮሳትን መስለው ሁሉን እያከናወኑ እያለ የወዳጆቹን መከራ የማይዘነጋ፣ የሰውን የድካሙን ዋጋ ፈጽሞ የማያስቀር አምላክ ሠራዊተ መላእክትን አስከትሎ መጥቶ ‹‹መገረፍህ፣ ስለ እኔ መገረፍ ይሁንልህ፣ የደምህ መፍሰስ ስለ እኔ ደም መፍሰስ ይሁንልህ፣ መቸንከርህም ስለ እኔ መቸንከር ይሁንልህ፣ ሞትህም ስለ እኔ ሞት ይሁንልህ›› ብሎ የሚከተለውን ቃልኪዳን ሰጥቷቸዋል። ‹‹ከዚህ ቦታ መጥቶ የተሳለመውን እምርልሃለሁ፤ ነፍሱ በአንተ ቃልኪዳን የማይማር በአንተ ቦታ ለመሳለምም፣ ንስሓ ለመግባትም ሆነ ለመቀበር አላቀርብብህም፤ መጥቶም የተቀበረውን ሥጋውን አፈር አይበላውም›› የሚል እጅግ ድንቅ ቃልኪዳን ነው መድኃኔዓለም የሰጣቸው። ቃል ኪዳኑንም የሰጣቸው ቅዱሳን መልእክትን፣ ነቢያትን፣ ሐዋርያትን፣ ጻድቃንን፣ ሰማዕታትን፣ ቀሳውስትን፣ ዲያቆናትን፣ ደናግል መነኮሳትን ሁሉ ምስክር አቁሞ እንደሆነ ቅዱስ ገድላቸው ይናገራል።
ይህም ድንቅ ቃልኪዳን ዛሬም በገሀድ እየታየ ነው። እስከ ዕለተ ምጽዓትም ሲታይ ይኖራል። በደጃቸው የተቀበረ ሰው አይበሰብስም። ይህም የሥጋው አለመበስበስ ለሞተው ሰው ለሥጋው አንዳች ረብ ጥቅም ኖሮት ሳይሆን የጻዲቁ ቃልኪዳናቸው እስከ ዕለተ ምፅዓት ድረስ ተፈጻሚ መሆኑንና ምልክትን ለሚሻ ለዚህ ክፉ ዘመን ትውልድ ምልክት ይሆን ዘንድ ነው።
ከአ.አ 225 ኪ.ሜ ርቀት ለመራኛ ከተማ አቅራቢያ በሚገኘው የሚዳ አቡነ መልከጼዴቅ ገዳም ተፈጥሮአዊ አቀማመጡ እጅግ አስገራሚ በሆነው ዋሻ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሁሉም ነገር በግልጽ ይታያል። ይህም እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ሁሉ በተለይም እኛ ኢትዮጵያውን በኃጢአት ሳንጠፋበት የመዳኛ መንገድ አድርጎ የሰጠን ድንቅ የቃል ኪዳን አባታችን መሆናቸውን ተረድቶና አውቆ በቃል ኪዳናቸው መጠቀም መቻል በራሱ ዕድለኛነት ነው። አቡነ መልከጼዴቅ ጌታችን ዕድሜአቸው ረጅም መሆኑን በምሳሌ እያሳየ ሲነግራቸው ‹‹በዚህ ዓለም መኖር ጥቅሙ ምንድር ነው? ወደ እረፍትህ ውሰደኝ እንጂ›› ብለው ሞታቸውን የለመኑ ቅዱስና ጻዲቅ አባት ናቸው።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
ሕፃኑም በማሕፀኗ እያለ እመቤታችን ድንግል ማርያም ሰላምታ በሰጠቻት ጊዜ እንዲህ ብላ ጮኸች "ከሴቶች ተለይተሽ አንቺ የተባረክሽ ነሽ የማኅፀንሽም ፍሬ ቡሩክ ነው። የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጪ ዘንድ እኔ ምንድን ነኝ እነሆ እንዴት ነሽ ስትይኝ የሰላምታሽን ድምፅ በሰማሁ ጊዜ ልጁ በማሕፀኔ ውስጥ በደስታ ዘለለ።
ከዚህም በኋላ ጌታችንን አየችው በአምላክነቱም አመነች የሚያምኑበትም በመዳናቸው ደስ አላት ዕድሜዋንም በፈጸመች ጊዜ በበረሀ ውስጥ ሳለች አረፈች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ገብረ_ማርያም_ጻድቅ_ንጉሠ_ኢትዮዽያ
በዚህች እለት ጻድቁ ንጉሥ አፄ ገብረ ማርያም የእረፍት ቀናቸው ነው፡፡ የላስታ ገሥታት የዘር ሐረጋቸው ከንጉሥ ሰሎሞን ዘር ሲያያዝ የመጣ ነው፡፡ ከ10ኛው እስከ 13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን (920-1253 ዓ.ም ገደማ) በላስታ ቡግና ምድር የነገሡ የላስታ ቡግና ተወላጅ የሆኑ የኢትዮጵያ ቅዱሳን ነገሥታት የንግሥናቸው መጠሪያ "የዛጉዌ ሥርወ መንግሥት "ወይም" የላስታ መንግሥት" በመባል ይታወቃል፡፡ ከላስታ (ከዛጉዌ) ነገሥታት መካከል ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ፣ ቅዱስ ገብረ ማርያም፣ ቅዱስ ላሊበላና ቅዱስ ነአኵቶ ለአብ እነዚህ አራቱ ነገሥታት እንደ መልከጼዴቅ (ዘፍ14፥18) ክህነትን ከንግሥና፣ ቅድስናን ከንጽሕና ጋር አንድ አድርገው በመያዝ እግዚአብሔርንም ሰውንም በቅድስናና፡ በንጽሕና አገልግለው አልፈዋል፡፡
ጻድቁ ንጉሥ ቅዱስ ገብረማርያም በሌላኛው ስማቸው ሐርቤይ እየተባሉ የሚጠሩ ሲሆን የቅዱስ ላሊበላ ታላቅ ወንድም ናቸው፡፡ ታላቁ ጻድቅ ንጉሥ ቅዱስ ነዓኵቶ ለአብን ወልደዋል፡፡ አባታቸው ዣን ስዩም 40ዓመት ከነገሡ በኋላ በ76ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ሲለዩ ልጃቸው ገብረ ማርያም ንግሥናውን ተቀብለዋል፡፡ ከእርሳቸው ቀጥሎ ታናሽ ወንድማቸው ቅዱስ ላሊበላ ተወልዶ እንደሚነግስ በትንቢት ተነግሮ ነበር፡፡ ይህን ጊዜ ከላሊበላ ጋር በአባት እንጂ በእናት ይለያዩ ነበርና የበጎ ነገር ጠላት የሆነ ክፉ ሰይጣን የእኅታቸው ክፉ ምክር ተጠቅሞ በወንድማቸው በላሊበላ ላይ በቅናት ክፉ እንዲያስቡ አድርጓቸዋል፡፡ስለ ንግሥናቸው ሲሉ ምንም እንኳን በወንድማቸው ላይ ክፉ አስበው የነበረና በእኅታቸውም ክፉ ምክር መርዝ የሰጡት ቢሆንም በኋላ በክፉ ሀሳባቸው እጅግ ተፀፅተው "አምላኬንም ወንድሜንም አሳዘንኩ" በማለት ወንድማቸውን ይቅርታ በመጠየቅ ላሊበላን አንግሠውት እርሳቸው መንኵሰው ገዳም ገብተዋል፡፡
ቅዱስ ላሊበላ ካለበት አክሱም ድረስ ሄደው በዕንባና በልቅሶ ይቅርታ ጠይቀው ወደ አገራቸው ሮሐ ከተማ ይዘውት በመምጣት መንግሥታቸውን አስረክበውት ነው የመነኑት፡፡ በምንኵስናም ሆነው በታላቅ ተጋድሎ በጾም በጸሎት በመትጋት እግዚአብሔርን እያገለገሉ እያለ ጌታችን ተገልጦላቸው "ክብሩ እንደ መላእክት የሆነ ታላቅ ልጅ ትወልዳለህና ወደቤትህ ተመለስ" ብሎ ከነገራቸው በኋላ ወደቤታቸው ተመልሰው ቅዱስ ነአኵቶ ለአብን ወልደዋል፡፡
ንጉሥ ቅዱስ ገብረ ማርያም በዘመናቸው ከነበሩት ከእስክንድሪያ ሊቀ ጳጳሳት ከአባ ዳንኤል ጋር መልእክት በመላላክ "ከሀገሬ ሊቃውንት መነኰሳት የሕዝቡን ቋንቋ የሚሰሙና የሚያስተምሩ ጳጳስ ይሹሙልን" በማለት ለእስክንድሪያ ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ ምንም እንኳን የእስክንድሪያ ሲኖዶስ በወቅቱ ኢትዮጵያ የራሷንልጆች እንድትሾም ስላልፈለጉና በወቅቱ ፈቃደ እግዚአብሔር ስላልነበረ የቅዱስ ገብረ ማርያምን ጥያቄ ንግሥት ዘውዲቱና ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ድጋሚ በመጠየቅ ፍጻሜውን እንዲያገኝ ቢያደርጉትም መሠረቱን ግን የጣሉት ዐፄ ገብረ ማርያም ናቸው በዘመናቸው ብዙ አብያተ ክርስቲያናትንም ያሠሩ ሲሆን ጊዜ ዕረፍታቸው ሲደርስ ጌታችን ተገልጦላቸው "የእኔን መከራ እያሰብክ ከዓይንህ ዕንባ ሳያቋርጥ በጾም በጸሎት ተወስነህ ስላገለገልኸኝ በአንተ ስም ለተራበ ያበላውን፣ ለተጠማ ያጠጣውን፣ ለታረዘ ያለበሰውን ምሬልሃለሁ" በማለት ትልቅ ቃልኪዳን ሰጥቷቸው በካቲት16 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል፡፡ ጻድቁን ንጉሥ ዐፄ ገብረ ማርያምን ሚያዝያ10 ቀን የሚነበበው ስንክሳር በሰፊው ይጠቅሳቸዋል፡፡ ከጻድቁ ከአቡነ ገብረ ማርያም ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ጻድቁ_ንጉሥ_ቅዱስ_ነዓኩቶ_ለአብ
የስሙ ትርጓሜ ‹‹እግዚብሔር አብን እናመስግነው›› ማለት ነው። የቅዱስ ላሊበላ የወንድም ልጅ ሲሆን ከ11ዱ የዛጉዌ ነገሥታት ውስጥ 10ኛው ነው። አባቱ ቅዱስ ገብረ ማርያም ሥልጣኑን ለወንድሙ ለቅዱስ ላሊበላ ትቶ በመመንኮስ በበዓት ተወስኖ በጾም በጸሎት ሲጋደል ጌታችን ተገልጾለት ‹‹ክብሩ እንደ መላእክት የሆነ ልጅ ትወልዳለህና ወደቤትህ ተመለስ›› ብሎ አዘዘው። ንጉሡ ገብረማርያምም ‹‹40 ዓመት ስነግሥ ያልወለድኩትን አሁን ዓለም በቃኝ ስል ትወልዳለህ የተባልኩት ልጅ ምን ዓይነት ልጅ ይሆን!›› እያለ ወደ ቤቱ ተመለሰ። ሚስቱን መርኬዛንም መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ካበሰራት በኋላ ነአኵቶለአብ ጌታችን በተወለደበት ዕለት ታኅሳስ 29 ቀን ተወለደ። ቅዱስ ላሊበላም ቀደም ብሎ የተወለደው እንዲሁ በጌታችን የልደት ቀን ታኅሳስ 29 ቀን 1101 ዓ.ም ነው። መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም ነአኵቶለአብ እንደሚወለድ ቀድሞ ለንጉሥ ላሊበላ ነግሮት ነበርና አሁን ሲወለድ ‹‹ያ የነገርኩህ ሕፃን ተወልዷልና ወስደህ በሃይማኖት አንጸህ አሳድገው›› ብሎታል። እንዳለውም ሃይማኖቱን ጠንቅቆ እያስተማረ በእንክብካቤ አሳደገው። ግብፅ ሄዶ ከአቡነ ቄርሎስ ዲቁናን ተቀበለ። በኋላም ቅስናን ተቀበለ። ቅዱስ ላሊበላ ቤተ መቅደሶቹን ሠርቶ ከጨረሰ በኋላ በሕይወት ሳለ መንግሥቱን ስላወረሰው ከላሊበላ በኋላ ነግሦ ኢትዮጵያን መርቷል። ዕድሜው ሲደርስ መልአኩ ሚስት እንዲያጭለት ለቅዱስ ላሊበላ ነግሮት ሲያጭለት እግዚአብሔርን በድንግልና ማገልገል ይፈልግ ነበርና በዚህም እጅግ ሲያዝን እመቤታችን ተገልጻለት ጋብቻው ከእግዚአብሔር መሆኑን ነግራ አጽናንታዋለች፡፡ ‹‹የጌታህ ፈቃድ ነውና አትዘን ይልቁንም አግባ፣ ክብርህም ከደናግላን አያንስም›› ብላ ስለነገረችው ሚስት ቢያገባም ልክ እንደ ቅዱስ ዲሜጥሮስና ልዕልተወይን ንጽሕናቸውንና ድንግልናቸውን ለመጠበቅ በመማከር በግብር ሳይተዋወቁ ለ25 ዓመታት በድንግልና ሆነው በትዳር ኖረዋል። ምንኛ ድንቅ ነው የአባቶቻችን ጽናትና ተጋድሎ!!! እግዚአብሔርን በንጽሕና ለማገልገል ያላቸው ቁርጠኝነትስ በምን ቃላት ይገለጻል!!! ከዚህ በኋላ መልአክ መጥቶ ቅዱስ ነአኵቶለአብንና ባለቤቱን ‹‹በንጽሕና የተጋባችሁት ልትወልዱ ነው እንጂ ዝም ብላችሁ ልትኖሩ አይደለም›› አላቸው። እነርሱም በዚህ ጊዜ በጋብቻ 25 ዓመታት በድንግልና አብረው ከኖሩ በኋላ አንድ ቀን ብቻ በግብር ቢተዋወቁ እጅግ የሚያምርና የሚያሳሳ ወንድ ልጅ ወለዱ። ጻድቁን ንጉሥ ቅዱስ ነአኵቶለአብን ይበልጥ የምናደንቅበት ነገር የተፈጠረው ከዚህ በኋላ ነው። በመልአክ ትእዛዝ የወለደው ልጁ እጅግ የሚያምርና የሚያሳሳ ቢሆንም ንጉሡ ቅዱስ ነአኵቶለአብ ግን በእግዚአብሔር መንፈስ የወደፊቱን ያውቅ ነበርና ሱባኤ ገብቶ ‹‹በእኔ እግር ተተክቶ ሲነግሥ ፍርድ አጣሞ አንተንም ሰውንም ከሚበድል ይህን ልጄን ቅሰፍልኝና ሄሮድስ ካስፈጃቸው ሕፃናት ጋር ደምርልኝ›› በማለት ወደ እግዚአብሔር ጸለየ። እንደጸሎቱም ጌታችን በዛሬዋ ዕለት የካቲት 16 ቀን ልጁን በሰላም አሳርፎለት ሄሮድስ ካስፈጃቸው ሕፃናት ጋር ደምሮለታል። በዚህም ጊዜ መኳንንቶቹ፣ መሳፍንቶቹና ሕዝቡ ሁሉ ለልቅሶ ቢመጡ እርሱ ግን በቤተ መንግስቱ በልቅሶ ፈንታ ታላቅ የደስታ
🔴#ስንክሳር የካቲት 16
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ዐሥራ ስድስት በዚችም ዕለት የክርስቲያን ወገኖች ሁሉም አማላክን ለወለደች #ለእመቤታችን_ቅድስት_ድንግል_ማርያም በዓልን ያደርጋሉ፣ የመጥምቁ ዮሐንስ እናት የከበረች #ቅድስት_ኤልሳቤጥ አረፈች፣ ጻድቁ ንጉሥ #አፄ_ገብረ_ማርያም የእረፍት ቀናቸው ነው ፣ የጻድቅና #ቅዱስ_ንጉሥ_ነዓኩቶ_ለአብ መታሰቢያው ነው፣ #አቡነ_መልከ_ጼዴቅ ዘሚዳ ልደታቸው ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ኪዳነ_ምሕረት (#የሰባቱ_ኪዳናት_ማሕተም)
የካቲት ዐሥራ ስድስት በዚችም ዕለት የክርስቲያን ወገኖች ሁሉም አማላክን ለወለደች ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዓልን ያደርጋሉ። በዚች ዕለት መታሰቢያዋን ለሚያደርግ ስሟን ለሚጠራ ለድኆችና ለችግረኞች እስከ ቀዝቃዛ ውኃ ለሚሰጥ የክብር ባለቤት ከሆነ ከተወደደ ልጅዋ ከጌታችንና ከመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምሕረት ቃል ኪዳንን ተቀብላለችና።
ይህችም የከበረች እመቤታችን ልጅዋ ንጹሕ ሥጋዋን ተዋሕዶ ከብቻዋ ኃጢአት በቀር የሰውነትን ሥራ ፈጽሞ ስለእኛ መዳን ወዶ ያደረገውን መከራ ተቀብሎ ሙቶ ተነሥቶ ከዐረገና በአባቱ ዕሪና ከተቀመጠ በኋላ እርሷን እናቱን ማርያምን በደቀ መዝሙሩ ዮሐንስ ዘንድ ትቷት ነበር እነሆ ልጅሽ እርሱንም እነሆዋት እናትህ ብሎ አደራ እንዳስጠበቀው።
ከዚያንም ጊዜ ጀምራ እመቤታችን ማርያም ትጸልይ ዘንድ ያለ ማቋረጥ ወደ ልጅዋ መቃብር ሁል ጊዜ ስትሔድ ኖረች ይኸውም ጎልጎታ ነው።
አይሁድም በአዩዋት ጊዜ ቍጣንና ቅናትን ተመልተው በድንጊያ ሊወግሩዋት ወደዱ እግዚአብሔርም ከዓይናቸው ሠወራት ከዚህም በኋላ ዳግመኛ መጥታ በዚያ እንዳትጸልይ ተማክረው ከመቃብሩ ዘንድ ጠባቂዎችን አኖሩ እርሷ ግን በየዕለቱ መሔድን አላቋረጠችም ጠባቆችም አያይዋትም የልጅዋ የጌትነቱ መጋረጃ ሠውርዋታልና መላእክትም መጥተው ያገለግሏታል ጌታችንም ዘወትር ይጐበኛታል የምትሻውንም ይፈጽምላት ነበር።
ከዚህም በኋላ መላእክት ወደ ሰማይ አሳረጓትና የጻድቃንን ማደሪያዎች አሳዩዋት አብርሃም ይስሐቅ ያዕቆብም ወዳሉበት አደረሱዋት ከአዳም ጀምሮ እስከዚያ ዕለት በአካለ ነፍስ ያሉ አባቶች ሁሉ አንቺን ከሥጋችን ሥጋን ከዐፅማችን ዐፅምን ለፈጠረልን ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የአምላክ ልጅ ከአንቺ ሰው በመሆኑ በአንቺ ድህነት አግኝተናል ከጥፋትም የሕይወት ወደብ ሆነሽልናልና እያሉ ሰገዱላት።
ከዚያም ወደ ተወደደ ልጅዋ የእሳት መጋረጃ ወደተተከለበት ወደ ጌትነቱ ዙፉን አደረሷት ጌታችንም እጇን ይዞ ወደ ውስጠኛው መጋረጃ አስገብቶ ከጌትነቱ ዙፋን ላይ አውጥቶ ከእርሱ ጋር አስቀመጣት ያዘጋጀላትንም ዐይን ያላየው ጆሮ ያልሰማው በሰው ልቡና ያልታሰበ ተድላ ደስታን ሁሉ ነገራት።
ከጌትነቱ ዙፋንም በታች የእስራኤል ንጉሥ አባቷ ዳዊትን የነቢያትና የመላእክት ማኀበር እንደ ግድግዳ ከበውት በመሰንቆ ሲያመሰግን አየችው እንዲህም ይላል ልጄ ስሚ በጆሮሽም አድምጪ ወገንሽን የአባትሽንም ወገን ርሺ ንጉሥ ደም ግባትሽን ወዷልና እርሱም ጌታሽ ነውና።
ዳግመኛም የሥቃይን ቦታ ያሳዩዋት ዘንድ መላእክት ከዚያ ውሰዷት ለሰይጣንና ለሠራዊቱ በእርሱ ጐዳና ለሚጓዙ ሁሉ ወደተዘጋጀ ወደጨለማው ዳርቻ አደረሷት እመቤታችን ማርያምም ወዮልኝ ወደዚያ እንዳይመጡ ለሰው ልጆች ማን በነገራቸው አለች መልአኩም አመቤቴ ቡርክት ማርያም ሆይ እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ይኖራልና ለአንቺም ከአንቺ በኋላም በቃል ኪዳንሽ ለሚታመኑ አትፍሪ አላት ከዚህም በኋላ ወደ ቦታዋ መለሷት።
ከዚያንም ጊዜ ጀምራ እመቤታችን ድንግል ማርያም ስለ ኋጥአን እጅግ እያዘነች ኖረች እንደ ዛሬይቱም የካቲት ዐሥራ ስድስ ቀን በጎልጎታ ቦታ ቁማ ወደ ልጇ እንዲህ ብላ ለመነች ልጄ ሆይ በእግዚአብሔር አባትህ በክርስቶስ ስምህ ከአንተ ጋርም ህልው በሆነ አጽናኝ መንፈስ ቅዱስ አማፅንሃለሁ ዓለም ሁሉ ሊሸከምህ የማይችል ሲሆን ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በተሸከመችህ ማሕፀኔ አማፅንሃለሁ ልጄ ሆይ ያለ ሕማም ያለ ድካም ከእኔ በመውጣትህ በመወለድህ በአሳደጉህ ጡቶቼ በሳሙህ ከንፈሮቼ በአቀፋህ እጆቼ ከአንተ ጋር በተመላለሱ እግሮቼ አማፅንሃለሁ ። በውስጡ በተኛህበት በረት በተጠቀለልክበት ጨርቅ አማፅንሃለሁ የምወድህ ልጄ ሆይ በልቡናዬ ያለውን ሁሉ ትፈጽም ዘንድ የልመናዬን ቃል ሰምተህ ወደእኔ ትመጣ ዘንድ ወዳንተ ፈጽሜ እማልድሃለሁ።
የብርሃን እናቱ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንዲህ ብላ በጸለየች ጊዜ እነሆ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወረደ ከእርሱም ጋር አእላፍት መላእክት አሉ በዙሪያውም ሁነው ያመሰግኑታል እርሱም እናቴ ማርያም ሆይ ምን ላድርግልሽ አላት እመቤታችንም ለተወዳጅ ልጅዋ እንዲህ ብላ መለሰችለት ልጄ ወዳጄ ሆይጌታዬና ፈጣሪዬ አለኝታዬና መጠጊያዬ በእናቴ ማሕፀንም ሳለሁ ባንተ ጸናሁ አንተም ጠበቅኸኝ ሁልጊዜም ስም አጠራሬ አንተ ነህ።
አሁንም ጸሎቴንና ልመናዬን ስማኝ ቃሌንም አድምጥ እኔ እናትህ እኔም አገልጋይህ የምለምንህ ይህ ነው መታሰቢያዬን ለሚያደርጉ በስሜ አቢያተ ክርስቲያን ለሚሠሩ ወይም የተራቆተውን ለሚያለብሱ የተራበውን ለሚያጠግቡ የተጠማውንም ለሚያጠጡ የታመመውን ለሚጐበኙ ያዘነውን ለሚያረጋጉ የተከዘውንም ደስ ለሚያሰኙ ወይም ምስጋናዬን ለሚጽፉ ልጆቹንም በስሜ ለሚሰይም በበዓሌም ቀን በማኅሌት ለሚያመሰግን አቤቱ ዐይን ያላየውን ጆሮ ያልሰማውን በሰውም ልቡና ያልታሰበውን በጎ ዋጋ ስጣቸው በአማላጅነቴም የሚታመነውን ሁሉ ከሲኦል ነጻ አድርገው ከአንተ ጋር የደረሰብኝን ረኃቡንና ጥማቱን መከራውን ሁሉ አስብ አለችው።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንዳልሽው ይሁንልሽ የሰጠሁሽም ቃል ኪዳን እንዳይታበል በራሴ ማልኩልሽ አላት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በእመቤታችን ድንግል ማርያም በጸሎቷ ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_ኤልሳቤጥ
በዚህች ቀን የመጥምቁ ዮሐንስ እናት የከበረች ኤልሳቤጥ አረፈች። ይህች ቅድስት ከኢየሩሳሌም የሆነች የእናቱዋ ስም ሶፍያ ነው እርሷም ከሌዊ ነገድ ከአሮን ወገን ለሆነ ለማጣት ልጁ ናት በዝምድና አምላክን ለወለደች ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም የእናቷ እኅት ልጅ ናት።
ማጣት ሦስት ልጆችን ወለዷልና የታላቂቱም ስም ማርያም ነው እርሷም ወደ ግብጽ በተሰደደች ጊዜ እመቤታችንን ያገለገለች ሰሎሜን ወለደቻት ሁለተኛዋም ሶፍያ ናት እርሷም የዚች የቅድስት ኤልሳቤጥ እናቷ ናት የታናሺቱም ስም ሐና ነው። እርሷም የከበረች ድንግል እመቤታችንን ማርያምን ወለደቻት። ሰሎሜ ኤልሳቤጥ እመቤታችን ማርያም የእኅትማማች ልጆች ናቸው።
ይችንም ቅድስት ኤልሳቤጥ ካህኑ ዘካርያስ አገባት የከበረ ወንጌልም ስለርሳቸው ተናግሯልና እነርሱ ሁለቱም ያለ ነውር ያለ ነቀፋ በእግዚአብሔር ሕግ ጸንተው የሚኖሩ ዕውነተኞች ደጎች ሆኑ።
ኤልሳቤጥም መካን ስለሆነች ወደ እግዚአብሔር የሚለምኑና የሚማልዱ ሆኑ አርጅተውም የመውለጃቸው ዘመን በአለፈ ጊዜ እግዚአብሔር መልአኩን ገብርኤልን ወደ ዘካርያስ ልኮ ጸሎታቸው ልመናቸው እንደ ተሰማ ስለ ዮሐንስ መወለድና ከእርሱ ስለሚሆነው አስረዳው።
ከዚህም በኋላ ይቺ ቅድስት ኤልሳቤጥ መጥምቁን ዮሐንስን ፀንሳ ወለደችው ከሰዎችም የሚደርስባት ሽሙጥ ተወግዶ እጅግ ደስ አላት።
🔴#ስንክሳር የካቲት_15
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ዐሥራ አምስት በዚህች ቀን ከዐሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ ነቢይ #ቅዱስ_ዘካርያስ አረፈ፣ ሰብስጥያ በምትባል አገር የሰማዕታት #ቅዱሳን_አርባ_ሐራ_ሰማይ ቤተ ክርስቲያናቸው ተከበረች፣ በገድል ተጠምዶ የኖረ #ቅዱስ_አባ_በፍኑትዮስ አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ዘካርያስ_ነቢይ
የካቲት ዐሥራ አምስት በዚህች ቀን ከዐሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ ታላቅ ዕውነተኛ ነቢይ ዘካርያስ አረፈ። እርሱም ከሌዊ ነገድ ነው የአባቱም ስም በራክዩ ነው በገለዓድም ወለደው በባቢሎንም ምርኮ ጊዜ ተማረከ ከዚያ ሳለም በላዩ የወረደለትን መለኮታዊ ትንቢትን ተናገረ መንፈስ ቅዱስም በእርሱ አንደበት ጠቃሚዎች የሆኑ ብዙ ቃሎችን ተናገረ።
ለኢዮሴዴቅም እንዲህ ብሎ ትንቢትን ተናገረ በኢየሩሳሌም እግዚአብሔርን ካህን ሆኖ የሚያገለግል ልጅን ትወልዳለህ ከሚጠትም በኋላ እንደቃሉ ሆነ። ለሰላትያልም ትንቢት ተናገረለት ባረከውም ወንድ ልጅ ትወልዳለህ ስሙንም ዘሩባቤል ትለዋለህ እርሱም በኢየሩሳሌም መቅደስን ይሠራል አለው ዳግመኛም ለፋርስ ንጉሥ ተናገረ የድል ምልክትንም ገለጠለት። ጌታችን በውርንጫዪቱና በታላቂቱ አህያ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ስለ መምጣቱ ተናገረ።
ይሁዳም መድኃኒታችንን ክርስቶስን አሳልፎ በመስጠቱ ስለ ተቀበለው ሠላሳ ብር ትንቢት ተናገረ። መድኃኒታችንም በሚሰቀልበት ዐርብ ሌሊት ስለ ሐዋርያት መበተን ተናገረ። በቀትር ጊዜም ስለ ፀሐይ መጨለም ተናገረ። ስለ እስራኤል ልጆች ኀዘንም እንዲህ አለ ያን ጊዜ የወጉትን ያዩት ዘንድ አላቸው ወደ ኀዘንም ይመለሳሉ እንደ ሚወዱትም ያለቅሱለታል ሰው ለበኵር ልጁ እንደሚያዝን ጽኑ ኀዘንን ያዝናሉ። የትንቢቱም ወራት በተፈጸመ ጊዜ በሰላም አረፈ በነቢያት መቃብርም ተቀበረ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱሳን_አርብዐ_ሐራ_ሰማይ
በዚህችም ዕለት ሰብስጥያ በምትባል አገር የሰማዕታት አርባ ሐራ ሰማይ ቤተ ክርስቲያናቸው ተከበረች።
በስማቸው የተሠራች ቤተ ክርስቲያናቸውን ታላቁ አባት ቅዱስ ባስልዮስ በዚህች ዕለት አከበራት። ስለ እነርሱም ድርሳናትን ደረሰ። በዚህችም ዕለት በዓላቸውን አከበረላቸው። እነዚህም ቅዱሳን በአልፊያኖስ ዘመን ተጋደሉ እርሱም ከንጉሠ ነገሥት ቈስጠንጢኖስ ከመኳንንቶቹ አንዱ ነው። ከአይሁድ አገሮችም በአንዱ ላይ አነገሠው ክርስቲያኖችንም እንዲጠብቃቸውና እንዲያከብራቸው አዝዞት ነበር።
እርሱ ግን ወደዚያ አገር በደረሰ ጊዜ ጣዖትን አመለከ ሰዎችንም ሁሉ ጣዖት እንዲአመልኩ አስገደዳቸው ብዙዎች ምእመናንም ተነሥተው እርሱንና የረከሱ ጣዖቶቹን ረገሙ። በዚያችም ሌሊት እሊህ አርባ ጭፍሮች ወደ መኰንኑ ደርሰው በክብር ባለቤት ክርስቶስ ስም ምስክር ይሆኑ ዘንድ እርስ በርሳቸው ተስማሙ።
በእንቅልፋቸውም ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦ ለሰውነታቸው ብርታትን ሰጣቸው በጥዋትም ተነሥተው የጭፍራ አለቃ በሆነ በአግሪጎላዎስ ፊት ቁመው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ታመኑ። በላያቸውም ተቆጥቶ አስፈራራቸው እነርሱ ግን አልፈሩም በደንጊያም እንዲወግሩአቸው አዘዘ። በአቅራቢያቸውም የውሽባ ቤት በአጠገቧ ያለ የውኃ ጒድጓድ ነበረች ከውርጭ ጽናትም የተነሣ ትረጋለች በውስጥዋም ይጥሏቸው ዘንድ መኰንኑ አዘዘ።
በውስጥዋም በጣሉአቸው ጊዜ ከውርጭ ጽናት የተነሣ ሕዋሳታቸው ተቆራረጠ ከእርሳቸውም አንዱ ፈራ ከዐዘቅቱም አውጡኝ ብሎ ወጣ ወደ ወሽባው ቤትም ገባ ፈጥኖም ሞተ ዋጋውንም አጠፋ የፈለገውንም አላገኘም። አርባ አክሊላትም ከሰማይ ሲወርዱ በሠላሳ ዘጠኙ ሰማዕታት ላይም ሲቀመጡ አንዱ አክሊልም በመልአኩ እጅ ተንጠልጥሎ ሲቀር ከወታደሮች ይህን ያየ ከዚያ ተነሥቶ በጌታ አምኖ ልብሶቹንም አውልቆ ቅዱሳን ወደአሉበት ወደ ዐዘቅቱ ወረደ በመልአኩ እጅ ተንጠልጥሎ የቀረውንም አክሊል ወሰደ። እሊህም ጐልማሶች ሰማዕታት በዚያች
ዐዘቅት በነበሩበት ጊዜ እናቶቻቸው ያጽናኗቸውና ያስታግሡአቸው ነበር። እነርሱም ብዙ ጊዜ ቆዩ እንጂ ቶሎ አልሞቱም። ከሀድያንም ጭኖቻቸውን ሊሰብሩ ፈለጉ ፈጥነው እንዲሞቱ እግዚአብሔርም ወዲያውኑ ነፍሳቸውን ወሰደ ጭኖቻቸውን መስበር አልተቻላቸውም። ከዚህ በኋላም በእሳት ሥጋቸውን እንዲአቃጥሉ በተሽከረካሪም ጭነው ወስደው ወደ ባሕር እንዲጥሏቸው መኰንኑ ወታደሮችን አዘዘ። ሲጭኑአቸውም ያልሞተ ሕፃን አገኙና ተውት እናቱም ከሠረገላው ውስጥ ልትጥለው ተሸክማው ሮጠች ወታደሮችም ስለአልሞተ ከለከሉአት ወዲያውኑ በጫንቃዋ ላይ ሙቶ ከቅዱሳን ጋር እንዲሆን ወደ ተሽከርካሪው ጣለችው። ወደ ስብስጥያ ከተማ ጭነው ወስደው በእሳት አቃጠሉአቸው ወደ ባሕርም ጣሉአቸው።
ከዚህም በኃላ በሦስተኛ ቀን ለስብስጥያ አገር ኤጲስቆጶስ ተገለጡለተ። እንዲህም አሉት ወደዕገሌ ወንዝ ሐድ ሥጋችንንም ታገኛለህና አሸክመህ አምጣው ኤጴስቆጶሱም ከካህናት ጋራ በሌሊት ተነሥቶ ወደ ወንዙ ሔዱ የቅዱሳንንም ሥጋቸውን በአንድ ቦታ ተሰብስቦ እንደ ከዋክብት እያበራ አገኙት ከእርሳቸውም አንድ እንኳን አልጐደለም በክብር ተሸክመው ወስደው በመልካም ቦታ በክብር አኖሩአቸው። ዜናቸውም በአራት ማእዘን ተሰማ መታሰቢያቸውንም አደረጉ በዓለም ሁሉ ቤተ ክርስቲያን ታነፀላቸው ከሥጋቸውም ታላላቅ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_በፍኑትዮስ
በዚች ዕለት በገድል ተጠምዶ የኖረ አባ በፍኑትዮስ አረፈ። ይህም አባት ከታናሽነቱ መንኵሶ በጾም በጸሎት በስግደትም እየተጋ ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለ። ያማረ የምንኵስናውን ሥራ በፈጸመ ጊዜ መነኰሳት ከሚኖሩበት ገዳማት ርቆ ወደሚገኝ በረሀ ውስጥ ይገባ ዘንድ የከበሩ ገዳማውያንንም ይጐበኛቸው ዘንድ ለሚያነቧት ጥቅም ትሆን ዘንድ ገድላቸውንም እንዲጽፍ ልዑል እግዚአብሔር አዘዘው።
በዚያንም ጊዜ ለእግዚአብሔር ትእዛዝ ራሱን ዘንበል አድርጎ ወደ ውስጠኛው በረሀ ገባ በመንደር ውስጥ እንደ ሚዞር ሰው በዱር መካከል ዞረ። ከገዳማውያንም ብዙዎችን አገኛቸውና ዜናቸውን ተረድቶ ገድላቸውን ጻፈ ከውስጣቸውም የከበሩ ገዳማውያን ጢሞቴዎስና አቡናፍር አሉ። ይህንንም አባት በፍኑትዮስ ወደ ውስጠኛው በረሀ በመግባቱ ከረኃብ የተነሣ ሥቃይ ደርሶበታል ያለምግብ ሦስት ቀን አድሮአልና።
ከዚህም በኋላ ተርቦ ለሞት ተቃረበ ከእግዚአብሔርም የታዘዘ መልአክ ተገለጸለትና ሰውነቱን ሁሉ አፉንም ዳሠሠው ያለ ምግብም ዐሥራ ሰባት ቀን ኖረ። ዳግመኛም ከቶ ሰው ሳያዩ ስድሳና ሰባ ዓመት ከዚያም የሚበዛ የሚያስደንቅ የገዳማውያንን ኑሮአቸውን ተናገረ ወደ ውስጠኛው በረሀ በሚገቡ ጊዜ እነርሱን ስለሚዋጓቸው ከርኵሳን መናፍስትና ከሚያስፈሩ አራዊት ስለሚደርስባቸውም ፈተና ተናገረ። ከዚህም በኋላ በትዕግሥታቸው የሚዘጉላቸው ይሆናሉ አራዊትም እንደ ባሮች ያገለግሏቸዋል ቅዱስ ቍርባንንም እንዴት እንደሚቀበሉ ደግሞ ተናገረ በዕለተ ሰንበት የመድኃኒታችንን ክርስቶስን ሥጋና ደም መላእክት አምጥተው ያቀብሏቸዋልና ከገነትም ፍራፍሬዎችን ይሰጧቸዋል።
ለዚህም አባት ስለ እሊህ ድንቆች ሥራዎች አይቶ ምስክር ሊሆን የተገባው ሆነ ከዚህም በኋላ በሰላም አረፈ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
የተከበራችሁ የሰንበት ት /ቤታችን አባላት ለየካቲት ኪዳነ ምሕረት በዓል አገልግሎት እንድታገለግሉ የተመረጣችሁ አባላት የአገልግሎት ልብስ (ዩኒፎርም) የሚሰጥበት ቀን ዛሬ በ14/06/2015ማክሰኞ እና ነገ በ15/06/2015 ዓ.ም እንድትወስዱ ሰላመ እግዚአብሔር ከሁላችንም ጋር ይሁን።
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ደብራችን የጽ/ጽ/ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አባላትን በሕገ ቤተክርስቲያን መሠረት በየሦስት ዓመት ምርጫ ያካሂዳል፤ በመሆኑም ለቀጣይ ሦስት ዓመት ደብራችንን በሰበካ ጉባኤ አባልነት የሚያገለግሉትን ለመምረጥ የፊታችን የካቲት ፲፱/፳፻፲፭ ዓ.ም ጠዋት ከቅዳሴ በኋላ ቀጠሮ ስለተያዘ፤ አባላት ተገኝተን ለቤተክርስቲያናችን ይጠቅማሉ የምንላቸውን ለመምረጥና በንቃት እንድንሳተፍ ለማሳሰብ እንወዳለን፤ ስለምርጫው ዝርዝር መረጃዎች በጉባኤ ሰዓት ስለሚገለጥ እንድትከታተሉ በቅዱስ ሚካኤል ስም እናሳስባለን፡፡
现已上线!2025 年 Telegram 研究 — 年度关键洞察 
