የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)
前往频道在 Telegram
2 639
订阅者
-224 小时
+37 天
+5630 天
帖子存档
#የካቲት_24
#ቅዱስ_አጋቢጦስ
የካቲት ሃያ አራት በዚች ቀን የከበረ አባት ኤጲስቆጶስ አጋቢጦስ አረፈ። ይህም አባት በከሀድያን ነገሥታት በዲዮቅልጥያኖስና በመክስምያኖስ ዘመን ነበር። ወላጆቹም ደጎች ምእመናን ነበሩ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት አስተምረውት ዲቁና ተሾመ።
ከዚህም በኋላ እናትና አባቱን ትቶ ወደ አንድ ገዳም ሔዶ የሸመገሉ መነኰሳትን አገለገለ። ከእርሳቸውም በጎ አምልኮትን ተማረ አረጋውያኑንም እያገለገለ በገድል ተጠመደ ያለማቋረጥም በጾም በጸሎትና በስግደት ይተጋል ከጥዋትም እስከ ምሽት በመጾም የሽንብራ አሠር የሚመገብ ሆነ።
ከእንቅልፍም ጋር ሊታገል በወደደ ጊዜ ከሽምብራ አሠር ጋር አመድ እየተመገበ ሰማንያ ቀን ኖረ በዚህም ተጋድሎ ውስጥ እያለ ኃይሉ ግን ይጨመርለት ነበር። ለአረጋውያንም አገልግሎቱን አላስታጐለም ሲጠራቸውም ጌቶቼ ይላቸዋል የጽድቅንና የትሩፋትን ሥራ ሁሉ ፈጸመ።
እግዚአብሔርም የሚያስደንቁ ብዙዎች የሆኑ ታላላቅ ተአምራቶችን በእጆቹ ገለጠ። ከእርሳቸውም አንዲቷን ብላቴና አዳናት እርሷም እንደ ዕንጨት የደረቀች እስከምትሆን ብዙ ዘመን ጭንቅ በሆነ ደዌ ታማ የኖረች ናት። ዳግመኛም ብዙ ሰዎችን ያጠፋውን ታላቅ ከይሲ በጸሎቱ ገደለው። ከሰውና ከእንስሳም አስጨናቂ የሆኑ በሽታዎችን አሰወገደ።
የተጋድሎውና የኃይሉ ጽናት ወሬው በተሰማ ጊዜ ስሙ ሉክያኖስ የሚባል መኰንን ወደርሱ ልኮ አስመጥቶ ያለ ውዴታው በግድ የጭፍራ አለቃ አድርጎ ሾመው እርሱ ግን ተጋድሎውን አልተወም ጾምንም ጸሎትንም የትሩፋትን ሥራ የሚጨመር ሆነ እንጂ የቀደመ ሥራውን አልተወም በጥቂት ቀኖችም ዲዮቅልጥያኖስንና መክስምያኖስን እግዚአብሔር አጠፋቸው አምላክን የሚወድ ጻድቅ ሰው ቈስጠንጢኖስ ነገሠ ይህም ቅዱስ ከጭፍራ ውስጥ ይወጣ ዘንድ ምክንያት የሚሻ ሆነ።
ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ እጅግ የሚወደው መልከ መልካም የሆነ ወጣት ብላቴና ነበር ክፉ ጋኔንም ተጫነበት በቀንም በሌሊትም ታላቅ ሥቃይን የሚያሠቃየው ሆነ ቅዱስ አጋቢጦስንም ከሚያውቁት ውስጥ አንድ ሰው በአየው ጊዜ የወታደር አለቃ አጋቢጦስ ቢመጣ በአዳነህ ነበር አለው የታመመውም እርሱ በንጉሥ ጭፍራ ሥርዓት ውስጥ ያለ በውኑ ይህን ሥራ መሥራት ይችላልን አለ ሰውዬውም ገድሉንና ሥራውን ሁሉ አስረዳው። ጋኔን ያደረበትም በእውነት ሊያድነኝ ይችላልና ከዚህ ከአስጨናቂ ደዌ ያድነኝ ዘንድ የወታደር አለቃ አጋቢጦስን ፈጥናችሁ አምጡልኝ አለ።
ንጉሥም ይህን በአወቀ ጊዜ ቅዱስ አጋቢጦስን እንዲአመጡለት አዘዘ በመጣ ጊዜም በወጣቱ ላይ ጸለየ በከበረ መስቀልም አማተበው በዚያንም ጊዜ በእግዚአብሔር ኃይል ዳነ ንጉሡም በዚህ ደስ ብሎት ቅዱስ አጋቢጦስን አከበረው ምን እንዳደርግልህ ትሻለህ አለው እርሱም ንጉሡን ከወታደርነት ውስጥ አሰናብተኝ አለውና አሰናበተው አስቀድሞ ወደ ነበረባትም ቦታው ተመለሰ ብዙ ዘመናትም እጅግ እየተጋደለ ኖረ።
ከዚህም በኋላ የዚያች አገር ኤጲስቆጶስ ይዞ ቅስና ሾመው ይህም ኤጲስቆጶስ በሞተ ጊዜ ቅዱስ አጋቢጦስን ይሾምላቸው ዘንድ ሕዝቡ ሊቀ ጳጳሳቱን ለመኑት እርሱም ሾመላቸው መልካም ተናጋሪዎች የሆኑትን የክርስቶስን መንጋዎች በበጎ አጠባበቅ ጠበቃቸው።
እግዚአብሔርም የትንቢትን ጸጋ የተሠወረውንም የማወቅ ድንቆች ተአምራቶችንም የማድረግ ሀብትን ሰጠው። በሥውር ኃጢአትን የሚሠሩትን ኃጢአተኞች የሚገሥጻቸው ሆነ በንስሐም እስኪመለሱ ከመቅደስ ያርቃቸዋል።
ዳግመኛም በገድሉ መጽሐፍ ተጽፎ የተገኘ የታላቅ ወንዝ ወራጅ ውኃን በመስቀሉ አቁሞ ወደ ሌላ መንገድ መለሰው የዕውር ዐይኖችንም ገለጠ ለምጻሞችንም አነጻ ብዙዎች በሽተኞችንም አዳነ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘለዓለም አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት)
🔴 ስንክሳር #የካቲት_23
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ሀያ ስሶት በዚህች ቀን #ቅዱስ_ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት አባቶቻችንን አድዋ ላይ የረዳበት ነው፣ የክቡር ፋሲለደስ ልጅ የከበረ #ቅዱስ_አውሳብዮስ በሰማዕትነት አረፈ፣ የሰርምኔሱ ሊቀ ጳጳስ ሐዋርያዊው ሰማዕት #ቅዱስ_ፖሊካርፐስ መታሰቢያው ነው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ጊዮርጊስ_ሊቀ_ሰማዕታት
የካቲት ሀያ ስሶት በዚህች ቀን ቅዱስ ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት አባቶቻችንን አድዋ ላይ የረዳበት ነው፡፡ በዚያን ወራት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ከአንድ ሺህ ስምንት መቶ ሃምሳ አራት ዓመት በኋላ የኢትዮጵያው ንጉሠ ነገሥት ዳግማዊ አጤ ምኒልክ በነገሡ በሃያ ስድስት ዓመት የምኒልክ የጦር አለቃ ገበየሁ ድል ከአደረጋቸው በኋላ እንደገና ምኒልክም ወግተው ኢትዮጵያን በቅኝ አገዛዝ ሊገዙ የሮም ሰዎች መጡ።
ከዚህም በኋላ የኢትዮጵያው ንጉሠ ነገሥት፡ ዳግማዊ አጤ (ዓፄ) ምኒልክ መስከረም ፯ ቀን ፲፰፻፹፰ (1888፡ዓ.ም ) ላይ "እግዚአብሔር በቸርነቱ፡ እስከ አሁን ጠላት አጥፍቶ አገር አስፍቶ አኖረኝ፡፡ እኔም እስከ አሁን በእግዚአብሔር ቸርነት ገዛሁ፡፡ እንግዲህ ብሞትም ሞት የሁሉ ነውና ስለ እኔ ሞት አላዝንም፡፡ ደግሞ እግዚአብሔር አሳፍሮኝ አያውቅም፡፡ እንግዲህም ያሳፍረኛል ብዬ አልጠራጠርም፡፡ አሁንም አገር የሚያጠፋ፤ ሃይማኖት የሚለውጥ ጠላት፤ እግዚአብሔር የወሰነልንን የባህር በር አልፎ መጥቷልና እኔም የአገሬን ከብት ማለቅ፤ የሰውን መድከም አይቼ እስከ አሁን ዝም ብለው ደግሞ እያለፈ እንደ ፍልፈል መሬት ይቆፍር ጀመር፡፡ አሁን ግን በእግዚአብሔር ረዳትነት አገሬን አሳልፌ አልሰጠውም፡፡ የአገሬ ሰው፤ ከአሁን ቀደም የበደልሁህ አይመስለኝም አንተም እስከ አሁን አላስቀየምኸኝም፡፡ ስለዚህ ስንቅህን በአህያ አመልህን በጉያህ ይዘህ ጉልበት ያለህ በጉልበትህ እርዳኝ፡፡ ጉልበት የሌለህ ለልጅህ፤ለሚስትህ፤ ለሃይማኖትህ ስትል በኀዘን እርዳኝ፡፡ ወስልተህ የቀረህ ግን በኋላ ትጣላኛለህ አልተውህም፡፡ ማርያምን! በዚህ አማላጅ የለኝም"፡፡ ዘመቻዬም በጥቅምት ነውና የሸዋ ሰው እስከ ጥቅምት እኩሌታ ድረስ ወረይሉ ከተህ ላግኝህ" ብለው አዋጅ አስነገሩ፡፡ ዳግኛም በፈረሶታቸው መጣብር ላይ በጦራቸው አንደበት ላይ የመስቀል ምልክት እንዲያደርጉ ጭፍሮችን አዘዛቸው መስቀል ጠላትን ድል አድራጊ እንደሆነ አስቀድሞ ያውቅ ነበርና።
አዋጁን ካስነገሩ በኋላ ከዚያም ተነሥቶ ወደ ትግራይ ክፍለ አገር ዘመቱና ከትግራይ አውራጃ አንዷ የምትሆን አድዋ የምትባል አገር ደረሱ፡፡ የሣህለ ማርያም (ዳግማዊ ምኒልክ) ሚስት ወለተ ሚካኤል (እቴጌ ጣይቱም) በንጉሡ ትዕዛዝ ታቦተ ጊዮርጊስን አስይዘው ከሊቀ ጳጳሱ ከአባ ማቴዎስ እንዲሁም ከቀሳውስቱና ከመነኰሳቱ ጭምር ከንጉሡ ጋር ወደ ጦርነቱ ተጓዘች፡፡በዚያም ጊዜ የአክሱም ጽዮን መነኰሳትና ካህናት የእመቤታችንን ሥዕል ይዘው ወደ ንጉሡ ወደ ምኒልክ መጥተው ከሊቀ ጳጳሱ ከነአቡነ ማቴዎስ ጋር ተቀላቀሉ ከዚያም ሌሊቱን ሙሉ ጸሎት ምሕላ ሲያደርሱ አደሩ።
ቅዳሜ ማታ ለእሑድ አጥቢያ የካቲት ሃያ ሁለት ቀን ነው ንጉሡ ሣህለ ማርያም (ምኒልክ) የጦር ልብሱን ለብሰው ከሠራዊቱ ጋር ወደ ጦር ግንባር ሄደ፡፡ ከዚያም ከሮማውያን የጠላት ጦር ጋር ተገናኝቶ ከሌሊቱ ዐሥራ አንድ ሰዓት ጦርነቱን ጀመረ፡፡ የንጉሡ የሣህለ ማርያም (የምኒልክ) ሚስት ወለተ ሚካኤል (እቴጌ ጣይቱም) ሌሊት በታቦተ ቅዱስ ጊዮርጊስና በእመቤታችን ሥዕል ፊት በጸሎትና በስግደት እያደረች ሲነጋ ወደጦርነቱ ቦታ በመሄድ እጅግ ለሚያስደንቅ የአነጋገሯ ኃይል ቃል በጦርነቱ መካከል እየተገኘች ለንጉሡ ወታደሮች የሞራልና የብርታት ድጋፍ ትሰጣቸው ነበር። በእውነትም ለተመለከታት ሁሉ እንደ ኃይለኛ ተጋዳይ አርበኛ ትመስል ነበር እንጂ የሴቶች የተፈጥሮ ባሕርይ በእርሷ ላይ አይታይባትም ነበር። የንጉሡም ወታደሮች የንግሥቲቱን የጀግንነት አነጋገር በሰሙ ጊዜ በእሳት ላይ እንደተጣደ የብረት ምጣድ ልባቸው ጋለ ይልቁንም ላም እንዳየ አንበሳና የፍየል መንጋ እንዳየ ነብር እየተወረወሩ በጦርነቱ መካከል በመግባት የጠላትን ጦር በሰይፍ ይጨፈጭፋት ነበር። መጽሐፍ ሹመትን ሽልማትን ያየ አርበኛ ከጦርነት ከሰልፍ ወደኋላ አያፈገፍግም ብሎ ተናግሯልና፡፡ በዚያም ጊዜ ንጉሡ ሣህለ ማርያም (ምኒልክ) በጦርነቱ መካከል ሳለ ሊቀ ጳጳሱ አባ ማቴዎስ እንዲሁም የአክሱም መነኰሳትና ሌሎቹ ካህናት በሙሉ ታቦተ ጊዮርጊስንና ሥዕለ ማርያምን ይዘው ከንጉሡ በስተኋላ በደጀንነት ቆመው ጸሎተ ምህላ ያደርሱ ነበር። ንግሥቲቱ ወለተ ሚካኤል (እቴጌ፡ጣይቱም) በጸሎት ጊዜ በመዓልትም በሌሊትም ከእነርሱ አትለይም ነበር። የጽዮን አገልጋዮችም በእግዚአብሔር የሕጉ ታቦት ፊት መለከት ይነፉ ነበር።
በዚህም ዕለት ይኸውም የካቲት ሃያ ሦስት ቀን በሮማውያንና በኢትዮጵያውያን መካከል ከፍተኛ ጦርነት ሆነ በዚህም ጊዜ በሰማይ ታላቅ ተአምር ተደረገ። ማለትም የቀስተ ደመና ምልክት ታየ ከዚያም ከቀስተ ደመናው ውስጥ መልኩ አረንጓዴ የመሰለ ጢስ ይወጣ ነበር፡፡ ከዚህም ጢስ ውስጥ እንደ ክረምት ነጐድጓድ ያለ ድምጽ ተሰማ፡፡ ከዚህም የነጐድጓድ ድምጽ የተነሳ በሮማውያን ወታደሮች ዘንድ ከፍተኛ ድንጋጤና ሽብር ሆነ ለመዋጋት አልቻሉም፡፡ ይልቁኑ ኃያሉ ገባሬ ተአምር ማር ቅዱስ ጊዮርጊስ በአምባ ላይ ፈረሱ ተቀምጦ ከነፋስ ሩጫ ይልቅ እየተፋጠነ በአየር ላይ በተገለጸ ጊዜ በግንባራቸው ፍግም እያሉ ወደቁ፡፡ "የኢትዮጵያ ህዝብ አምላካቸው ሊረዳቸው መጣ እንግዲህ ማን ያድኅነናል" አሉ ምድርም ጠበበቻቸው በዚህን ጊዜ የኢትዮጵያ ሠራዊት የሮምን የጦር ሠራዊት ፈጁዋቸው የተረፉትንም ማረኳቸው ፈጽመውም እስኪያጠፏቸው ድረስ በሮማውያን ላይ በእግዚአብሔር ሥልጣን የኢትዮጵያውያን እጅ እየበረታ ሄደ፡፡ ከዚህም በኋላ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ሣህለ ማርያም (ምኒልክ) በእግዚአብሔር ኃይልና በተአምራት አድራጊው በቅዱስ ጊዮርጊስ ተራዳይነት የሮማውያንን የጦር ሠራዊት ድል አድርገው የድል አክሊል ተቀዳጅተው ተመለሱ፡፡
ስለዚህም በዳዊት የምስጋና ቃል የድል ዘውድ ያቀዳጀኝን እግዚአብሔር "ባለ ዘመኔ ሁሉ አመሰግነዋለሁ ለፈጣሪዬ እዘምራለሁ" አለ ሕዝቡም ሁሉ "በክብር ከፍ ከፍ ያለ እግዚአብሔርን በፍጹም ምስጋና እናመስግነውለን የሮማውያንን ኃይል ቀጥቅጦ አጥፍቷልና ሠረገሎቻቸውንም ሠባብሯልና ሠራዊቱንም ሁሉ በምድር ላይ በትኗልና" እያሉ አመሰገኑ። በፈጣሪው በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል በጦርነቱ መካከል የረዳውን ቅዱስ ጊዮርጊስንም በፍጹም ማድነቅ አደነቁ። የሮማም የጦር ሠራዊት በኢትዮጵያውያን ፊት ተዋረዱ ዳግመኛም በኢትዮጵያ ላይ ራሳቸውን ከፍ ከፍ አላደረጉም። በምኒልክም ዘመነ መንግሥት ኢትዮጽያ ከጦርነት ለዓርባ ዓመት ያህል አረፈች።
የኢትዮጵያው ንጉሠ ነገሥት ምኒልክ ከአደዋ ጦርነት ከተመለሱ በኋላ በአዲስ አበባ በምትበል ከተማው መካከል በቅዱስ ጊዮርጊስ ስም ቤተክርስቲያን አሠራ። ስሟንም ገነተ ጽጌ ብለው ሰየሟት። ቅዱስ ጊዮርጊስ በጦርነት ቦታ ሁሉ ይረዳው ነበርና። ልመና ክብሩ በኛ ለዘላለሙ በዕውነት ይደረግል። በረከቱ ከእኛ ጋር ትሁን እኛንም በቅዱስ ጊዮርጊስ አማላጅነት ይማረን ለዘለዓለሙ አሜን!!! (ገድለ ቅዱስ ጊዮርጊስ ተአምር 17)
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን ለእኛም የሰማዕታት ጽናታቸውን አድሎ ከበረከታቸው ይክፈለን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲተት፣ #ገድለ_ቅዱስ_ጊዮርጊስ)
🔴 ስንክሳር #የካቲት_22
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ሃያ ሁለት በዚች ቀን የኤጲስቆጶስ #ቅዱስ_አባ_ማሩና የዕረፍቱ መታሰቢያና #የፋርስ_ሰማዕታት ሥጋቸው የፈለሰበት ነው፣ ታላቅና ክቡር የሆነ መስተጋድል #ቅዱስ_አባ_ቡላ መታሰቢያው ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አባ_ማሩና_ጻድቅ
የካቲት ሃያ ሁለት በዚች ቀን የኤጲስቆጶስ አባ ማሩና የዕረፍቱ መታሰቢያና በከሀዲ በዲዮቅልጥያኖስ ዘመን በፋርስ አገር ለተገደሉ ሰማዕታት ሥጋቸው የፈለሰበት ነው።
ኤጲስቆጶስ ማሩናንም ስለ ድንቆች ተአምራቶቹ ስለ ትሩፋቱና ስለ ጽድቁ የአኖሬዎስና የአርቃዴዎስ አባት ታላቁ ቴዎዶስዮስ ንጉሥ ወደ ፋርስ ንጉሥ ላከው ከእርሱም ጋር እጅ መንሻ በመካከላቸው ስለ አለው ፍቅር ተላከ። ወደ ሳቦር ወደ ፋርስ ንጉሥም በደረሰ ጊዜ ታላቅ ክብርንም አከበረው በቤተ መንግሥቱም እልፍኝ ውስጥ አኖረው። ይህ ቅዱስም የንጉሡ ልጅ ጋኔን አድሮባት እንደታመመች በሰማ ጊዜ የከበረ አባ ማሩና ብላቴናዪቱን ጠርቶ በፊቱ አቁሞ በላይዋ ጸለየ ጋኔኑም ከእርሷ ወጥቶ ዳነች ንጉሡም ልጁ እንደዳነች አይቶ እጅግ ደስ አለው የአባማሩናንም ፍቅርና አክብሮት ጨመረ።
ከዚህም በኋላ አባ ማሩና በፋርስ ሀገር በሰማዕትነት ስለሞቱ የከበሩ ሰማዕታት ሥጋቸውን ስለ መሰብሰብ ከንጉሥ ዘንድ ፈለገ ንጉሡም የሰማዕታትን ሥጋቸውን ይሰበስቡ ዘንድ ቤተ ክርስቲያንም ሠርተው በውስጧ ሥጋቸውን ያኖሩ ዘንድ አዘዘ ያች ቤተ ክርስቲያንም በዚች ዕለት ከበረች።
ዳግመኛም በታላቋ ከተማ ውስጥ በከበረ አባ ማሩና ስም ያማረች ቤተ ክርስቲያንን ሠሩ እርሷም ማረፊያ የተባለች ናት። ከዚህም በኋላ ይህ አባት ወደ ንጉሥ ቴዎዶስዮስ ተመልሶ በሮሜ አገር ሁለት ዓመት ተቀመጠ የእነዚያ ሰማዕታት ቤተ ክርስቲያን በከበረችበት በዚች ዕለት አረፈ ከቤተ ክርስቲያኒቱም ክብር ጋር በዓሉንና መታሰቢያውን የሚያከብሩለት ሆኑ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አባ_ቡላ
ዳግመኛም በዚህች ቀን ታላቅና ክብር የሆነ አቢብ የተባለ መስተጋድል አባ ቡላ መታሰቢያው ነው። የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም አብርሃም የእናቱም ስም ሐሪክ ነው እነርሱም ከሮሜ አገር ሉፊ ከሚባል አውራጃ ናቸው በዘመናቸውም ከሀዲው ንጉሥ መክስምያኖስ በክርስቲያን ወገኖች ላይ መከራ ስለ አመጣ ስደት ሁኖ ነበርና እነርሱም በስደት ብዙ ዘመን ኖሩ።
ልጅንም በአጡ ጊዜ የተባረከ ልጅን ይሰጣቸው ዘንድ በጾም በጸሎት ተወስነው ወደ እግዚአብሔር ለመኑ የእግዚአብሔርም መልአክ በሕልም ተገለጠላቸውና ፍሬ የመላበትን ዘለላ ሰጣቸው።
ይህም ቅዱስ በተፀነሰ ጊዜ በቤታቸው አጠገብ ታላቅ ዛፍ በቀለ በቅጠሉም ላይ በሮማይስጥ ቋንቋ ቡላ የእግዚአብሔር አገልጋይ በጽዮንም አድሮ የሚኖር የያዕቆብ ፈጣሪ ያከበረው የሚል ጽሑፍ ነበረበት።
በተወለደም ጊዜ ክርስትና ሳያስነሡ ዓመት ሙሉ አኖሩት እመቤታችን ማርያምም ለሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ለሰለባስትርዮስ ተገልጣ ወደ አብርሃም ቤት ሒዶ ሕፃኑን እንዲአጠምቀው አዘዘችው እርሱም ሒዶ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው ስሙንም ቡላ ብሎ ሰየመው እናትና አባቱም ሳይነግሩት ቡላ ስለ ሰየመው አደነቁ ዕፁብ ዕፁብ አሉ።
ከዚህም በኋላ ሊቀ ጳጳሳቱ በጸለየ ጊዜ የቊርባን ኅብስትና ወይን የተመላ ጽዋ ከሰማይ ወረደ እርሱም ቀድሶ ሥጋውንና ደሙን ከሕፃኑ ጋር አቀበላቸው በዚያንም ጊዜ ሕፃኑ የአንድ ዓመት ልጅ ሲሆን በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሆነ አብ በግብር በአካል በሰም ልዩ ነው በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሆነ ወልድ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው በባሕርይ በህልውና በመለኮት በአብ ከወልድ ጋር አንድ የሆነ መንፈስ ቅዱስ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው ብሎ ተናገረ።
ከጥቂት ዘመንም በኋላ አባትና እናቱ ኅዳር ሰባት ቀን ሙተው ሕፃኑ ብቻውን ቀረ። ሕፃኑም ዐሥር ዓመት በሆነው ጊዜ ለጣዖት መስገድን የሚያዝ ከሀዲ መኰንን መጣ ቅዱስ ቡላም በሰማ ጊዜ ወደ መኰንኑ ሒዶ የረከሱ አማልክቶቹን ረገመ መኰንኑም በአካል ታናሽነቱን አይቶ እጅግ አደነቀ በዚያንም ጊዜ በችንካር እንዲቸነክሩት ሥጋውንም እንዲሠነጣጥቁት ቆዳውንም ከዐጥንቱ እንዲገፉ እጆቹንና እግሮቹንም በመጋዝ እንዲቆርጡ ጀርባውንም እንዲገርፉ በሾተሎችና በጦሮች መካከል አድርገው ከመንኰርኵር ውስጥ እንዲጨምሩት ዳግመኛም በመንገድ ላይ እንዲጐትቱት አዘዘ የመላእክት አለቃ ሚካኤልም መጥቶ አዳነው ያለ ጉዳትም ጤነኛ አደረገው።
ከዚህም በኋላ ወደ ሌላ መኰንን ሒዶ እርሱንና የረከሱ ጣዖቶቹን ረገመ መኰንኑም ተቆጥቶ በሚያዝያ ወር ዐሥራ ስምንት ቀን ራሱን በሰይፍ ቆረጠው ቅዱስ ሚካኤልም ከሰማይ ወርዶ ከሙታን ለይቶ አስነሣው ወደ አንድ ገዳምም ወስዶ የምንኲስና ልብስንና አስኬማን በመስቀልም ምልክት አለበሰው። እንዲህም አለው ከቅዱሳን ጻድቃን አንድነት ትሆን ዘንድ እግዚአብሔር አዝዞሃል።
ያን ጊዜም ቅዱስ አባ ቡላ ከደረቅ ተራራ ላይ ወጣ ያለ ማቋረጥም በውስጧ እየተጋደለ ኖረ። የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መከራውንና ስቅለቱን በአሰበ ጊዜ ከረጅም ዕንጨት ላይ በመውጣት ራሱን ወደታች ሁል ጊዜ ይወረውር ነበር።
በአንዲትም ቀን ከዛፍ ላይ በተወረወረ ጊዜ ሰይጣን ሊገድለው ስለ በረታበት ሞተ ያን ጊዜም ክብር ይግባውና መድኃኑታችን ከሞት አነሣውና እንዲህ አለው ከእንግዲህ ስምህ ቡላ አይሁን አቢብ ይባል እንጂ የብዙዎች አባት ትሆናለህና።
እርሱም የክርስቶስን ፍቅር እጅግ ጨመረ ፊቱንም እየጸፋ ሥጋውን በየጥቂቱ እየቆረጠ ጀርባውንም ሰባት መቶ ጊዜ እየገረፈ ኖረ ጌታችንም ይፈውሰው ነበር በየእሑድም ቀን ከቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያም እንደተወለደ በሌሎች ቀኖችም እንደተያዘና ከአይሁድ መከራ እንደ ተቀበለ ሁኖ ይገለጽለት ነበር።
ስለዚህም ሳይበላ ሳይጠጣ አርባ ሁለት ዓመት ኖረ ዳግመኛም ናላው ፈስሶ እስቲአልቅ ዐሥራ ሁለት ወር በራሱ ተተክሎ ኖረ። በአንዲትም ቀን የጌታችንን መከራ በአሰበ ጊዜ ሰይፉን በአንጻሩ ተከለ ከዕንጨት ላይም ወጥቶ በላዩ ወድቆ ሞተ ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምም ከአእላፍ መላእክት ጋር መጥታ የእኔና የልጄ ወዳጅ ሰላምታ ይድረስህ አለችው። ከበድኑም ቃል ወጥቶ የሰማይና የምድር ንግሥት እመቤቴ ሰላምታ ይገባሻል አላት እርሷም በከበሩ እጆቿ ዳሥሣ ከሞት አስነሣቸው።
ዕድሜውንም ፈጽሞ ከዚህ ዓለም የሚወጣበት ጊዜ ሲደርስ ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ በእጁ ልዩ የሆኑ አክሊሎችን የሚያበሩ ልብሶችንም ይዞ ተገለጠለት። ወዳጄ አቢብ ሆይ በማያልቅ ተድላ ደስታ ደስ አሰኝህ ዘንድ ወደእኔ ና ስምህን ለሚጠራ መታሰቢያህን ለሚያደርግ እኔ ኃጢአቱን አስተሠርይለት ዘንደ በራሴ ማልኩልህ። ወይም ለተራቆተ የሚያለብሰውን ለተራበም የሚያጠግበውን ለተጠማ የሚያጠጣውን የገድልህን መጽሐፍም የሚጽፈውን ወይም የሚያነበውንና የሚሰማውን በጸሎትህም የሚታመኑትን ሁሉ እስከ ዐሥር ትውልድ እምራቸዋለሁ። ይህንም ብሎ አፉን ሳመው በደረቱም ላይ አድርጎ ወደአየር አወጣው የመላእክትንም ምስጋና በሰማች ጊዜ ነፍሱ ከሥጋው ተለየች ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ገባች። የእረፍቱ ቀንም ጥቅምት ሃያ አምስት ይከበራል፡፡ (የጥቅምት 25 ስንክሳር)
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ለዘለዓለሙ ከእኛ ጋር ትሁን አሜን፡፡
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲተት_እና_ጥቅምት)
https://t.me/finotebirhan12
አዲስ 🛑 ኮሜዲያን እሸቱ መለሰ... ስለ ሰንበት ት/ቤት አገልግሎቱ ተናገረ... ሰብስከራይብና ሼር በማድረግ አገልግሎታችንን ያግዙ Comedian Eshetu
https://www.youtube.com/watch?v=jAPQ0dkCwYQ?sub_confirmation=1
🔴 ስንክሳር #የካቲት_21
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ሃያ አንድ በዚህችም ዕለት የከበረ የሐዋርያው የጳውሎስ ደቀ መዝሙር የሆነ #ቅዱስ_አናሲሞስ በሰማዕትነት አረፈ፣ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት #አባ_ገብርኤል አረፈ፣ የሀገረ ስሐ ኤጲስቆጶስ የከበረ አባት #አባ_ዘካርያስ አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ሰማዕት_አናሲሞስ_ሐዋርያ
የካቲት ሃያ አንድ በዚህችም ዕለት የከበረ የሐዋርያው የጳውሎስ ደቀ መዝሙር የሆነ ቅዱስ አናሲሞስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም ቅዱስ አስቀድሞ ከሮሜ ሰዎች ወገን ለሚሆን ስሙ ፊልሞና ለሚባል ለሮሜ ሰው አገልጋይ ሆኖ ነበር ይህም ፊሊሞና በሮሜ በአስተማረ ጊዜ በቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት በጌታችን አመነ ይህ ፊሊሞናም ከዚያ ከሮሜ አገር ወደ አስባንያ ሔደ።
ይህንንም አገልጋዩን አናሲሞስን ከእርሱ ጋር ወሰደው ሰይጣን ግን አናሲሞስን አሳተው ልቡንም ለወጠውና የጌታውን ገንዘብ ሰረቀ ጌታውም እንደሚቀጣው አውቆ ሸሽቶ ወደ ሮሜ ተመልሶ ሔደና በዚያ ተቀመጠ።
በእግዚአብሔርም ፈቃድ ወደ ከበረ ሐዋርያ ጳውሎስ ሔደ ትምህርቱንም ሰምቶ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ ለቅዱስ ጳውሎስም ደቀ መዝሙሩ ሆነ። ነገር ግን የጌታውን ገንዘብ በመስረቁ በአናሲሞስ ልብ ጽኑ ሀዘን አደረ ለሐዋርያ ጳውሎስም የሠራውን ሁሉ ነገረው ሐዋርያ ጳውሎስም አትፍራ ልብህም አይዘን አለው ወደ ጌታው ወደ ፊልሞናም መልእክትን ጻፈለት ይቺም ስለ አናሲሞስ የጻፋት ከመልእክቶቹ አንዲቱ ናት።
በመልእክቱም እንዲህ አለ እኔ በእሥራቴ ጊዜ ስለወለድኩት ልጄ እማልድሃለሁ ይኸውም አናሲሞስ ነው። የቀድሞው ሥራው አልጠቀመህም ነበር ዛሬ ግን ላንተም ለኔም እጅግ የሚጠቅም ሁኗል አሁንም ወዳንተ ልኬዋለሁና ልጄ እንድመሆንህ ተቀበለው። የበደለህ በደልም ቢኖር ወይም የሚከፍልህ ቢኖር በኔ ላይ አድርገው።
ይህ የከበረ አናሲሞስም ወደ ፊልሞና ወደ ጌታው በደረሰ ጊዜ በማመኑና በመጸጸቱ ደስ አለው ሐዋርያው እንዳዘዘውም አደረገለት እጅግም ወደደው ብዙ ገንዘብም ሰጠው እርሱ ግን ምንም ምን አልወሰደም እኔ በክርስትና ባለጸጋ ሁኜአለሁ አለ እንጂ።
ከዚህም በኋላ ሸኙትና ወደ ሮሜ አገር ተመለሰ በሰማዕትነት እስከ ሚሞትበት ጊዜ ሐዋርያ ጳውሎስን የሚያገለግልው ሆነ። ይህም ቅዱስ ካህን ሆኖ ተሾመ ሐዋርያትም በሥርዓት መጽሐፋቸው በአንቀጽ ሰባ ሰባት ሰማንያ አንድ በኃምሳ ሦስትና በኃምሳ ሰባት በምስጋና አስታውሰውታል እንደ ታማኝ ካህንም ነው አሉ።
ከሐዋርያው ጳውሎስም የምስክርነት ሞት በኋላ የንጉሥ ጭፍራ አለቃ ይህን ቅዱስ ይዞ ወደ አንዲት ደሴት ሰደደው የዚያችን ደሴት ሰዎች ሃይማኖትን እያስተማራቸው ኖረ የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው።
ከብዙ ቀኖችም በኋላ የንጉሥ የጭፍራ አለቃ ወደዚያች ደረሰ የከበረ አናሲሞስንም ሕያው ሁኖ የክብር ባለቤት የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሃይማኖት ለሰዎች ሲያስተምር አገኘው ጽኑ ግርፋትንም ገርፈው ጭኖቹን እንዲሰበሩ አዘዘ ምስክርነቱንም ፈጸመ። የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ለዘለዓለሙ ከእኛ ጋር ትሁን አሜን፡፡
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት)
https://t.me/finotebirhan12
🔴 ስንክሳር #የካቲት_20
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ሃያ በዚህች እለት #አቡነ_ክፍለ_ማርያም_ዘዲባጋ የተሰወሩበት ነው፣ የእስክንድርያ 21ኛ ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_ጴጥሮስ አረፈ፣ አዝማሪው #ቅዱስ_ፊልሞን በሰማዕትነት ሞተ፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_ክፍለ_ማርያም_ዘዲጋባ
የካቲት ሃያ በዚህች እለት አቡነ ክፍለ ማርያም ዘዲባጋ የተሰወረበት ነው፡፡ እኚኽም ቅዱስ ትውልዳቸው እንደርታ ሲሆን በ14 ዓመታቸው መንኩሰው መንነው በቅተው ሲኖሩ በአንድ ወቅት ወደ አክሱም ሄዱና ወላጆቻቸው ካሉበት ደረሱ፡፡ ከቅዳሴ በኋላ መበለት ቆርሰው ሲያድሉ ወላጅ እናታቸው ከስተውና ጠቁረው ስላዩአቸው ለእናታቸው አዳልተው በብዙ ሰጧቸው፡፡ እናትየው ግን ጻድቁ የሠሩትን አያውቁም ነበር፡፡
ጻድቁ ከብቃታቸው የተነሳ መና ከሰማይ እየወረደላቸው ከዓለትም ላይ ውኃ እያፈለቁ ይጠጡ ነበር፡፡ አድሎ ስላደረጉ ግን በዚህ ድርጊታቸው እግዚአብሔር ተቆጥቷቸው የሰጣቸውን ይህን ጸጋቸውን ነሳቸው፡፡ አቡነ ክፍለ ማርያምም ይህን ባወቁ ጊዜ ‹‹ወዮልኝ ወዮታ አለብኝ›› ብለው ከሰው ሳይገናኙ ዋሻ ገብተው ድፍን 11 ዓመት በለቅሶና በዋይታ እግዚአብሔርን ለመኑት፡፡ በኋላም እግዚአብሔር ይቅር እንዳላቸው ነገራቸውና የቀደመ ጸጋቸውና ክብራቸው መለሰላቸው፡፡ ስለ ዘረኝነት አስከፊነትም በብዛት አስተማሩ፡፡
ከዛ በኋላ ውኃ ከደረቅ ጭንጫ ላይ እያፈለቁ አሕዛብን ሁሉ እያስተማሩ ያጠምቁ ጀመር፡፡ ኅብስትም ከሰማይ እየወረደላቸው ሕዝቡን ያቆርቡ ጀመር፡፡ ጻድቁ በመጨረሻ በዚህች ቀን እንደነ ሄኖክና ኤልያስ ዐርገዋል እንጂ በምድር ሞትን አልቀመሱም፡፡ ትልቅና አስደናቂ ገዳማቸው አክሱም ይገኛል፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ሊቀ_ጳጳሳት_ጴጥሮስ
በዚህችም ዕለት የከበረ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ጴጥሮስ አረፈ፡፡ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃያ አንደኛ ነው። ይህንንም ቅዱስ ከሐዋርያዊ አትናቴዎስ በኋላ በሹመቱ ወንበር በተቀመጠ ጊዜ ከንጉሥ ዳርዮስና ከከሀዲ አርዮስ ወገኖች ብዙ መከራ ደርሶበታል።
ሊገድሉትም በፈለጉ ጊዜ ሸሽቶ ሁለት ዓመት ያህል ተሠወረ አርዮሳውያንም ሉቅዮስ የተባለ ከሀዲውን ሰው በእርሱ ፈንታ በወንበሩ ላይ አስቀምጠው ሁለት ዓመት ኖረ።
ከዚህም በኋላ ሃይማኖታቸው የቀና ምእመናን ሁሉም ተነሥተው አርዮሳዊ ሉቅዮስን አሳደዱትና ይህን አባት ጴጥሮስን ወደ መንበረ ሢመቱ መለሱት አርዮሳውያንንም በመጣላት እያወገዛቸውና እያሳደዳቸው ሰባት ዓመት ኖረ። ከዚህም በኋላ ከዚህ ዓለም ድካም አርፎ ወደ ዘላለም ዕረፍት ሔደ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ፊልሞን_መዐንዝር
በዚህችም ዕለት መኰንን አርያኖስን የሚያጫውተው አዝማሪው ፊልሞን በሰማዕትነት ሞተ። በአንዲትም ዕለት አርያኖስ አናጉንስጢስ አስቃሎንን ጠርቶ ለአጵሎን ሠዋ አለው አስቃሎንም ወደ ፊልሞን ሒዶ በእኔ ፈንታ ብትሠዋ አራት የወርቅ ዲናር እሰጥሃለሁ አለው ፊልሞንም ልብስህን ስጠኝና ተሸፋፍኜ በአንተ ፈንታ እሠዋለሁ አለው።
በገባም ጊዜ አውቀውት ምን ሆንክ አሉት ፊልሞንም በክርስቶስ የማምን ክርስቲያን ነኝ አላቸው አርያኖስም በሕይወት እንድትኖር ለአማልክት ሰዋ አለው ፊልሞንም በክርስቶስ ስም ከመሞት በቀር ሕይወት የለም አለው።
አርያኖስም ጥምቀትን ሳታገኝ ፈጥኜ እገድልሃለሁ ተስፋህን ታጣለህ አለው ፊልሞንም ሰምቶ የክርስትና ጥምቀትን ያድለው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ በዚያንም ጊዜ ከሰማይ ብሩህ ደመና መጥቶ አጠመቀው።
አርያኖስም አፍሮ ቢመለስ ብሎ ሦስት ወታደሮች እንዲጸፉት አዘዘ ፊልሞንም የእግዚአብሔር መላእክት ስለ እኔ ደስ ሲላቸው አያለሁና ከዚህ የከፋ ቢጸፉኝም እኔ አላፍርም አለ። አርያኖስም ባላ ባለው ግንድ ላይ ሰቅለው በፍላፃዎች ይነድፉት ዘንድ አዘዘ ግን ምንም የነካው የለም ፍላፃውም እንዳልነካው ለአርያኖስ ነገሩት ዳግመኛም እርሱ እንደ ቆመ ይነድፉት ዘንድ አዘዘ አንዲቱም ፍላፃ ተመልሳ የአርያኖስን ዐይን ነድፋ ዐሳወረችው በዚያንም ጊዜ ከተሰቀለበት አውርደው ከአናጉንስጢስ አስቃሎን ጋር ራሱን እንዲቆርጡ አዘዘ ገድላቸውንም ፈጽመው የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ።
መኰንኑም በፍላፃው ሕመም በተሠቃየ ጊዜ ከቅዱሳን ደም ወስዶ ከዐይኑ ውስጥ እንዲጨምር ሰዎች መከሩት ይህንንም ሲያደርግ ዳነ በክብር ባለቤት በጌታችን ክርስቶስም አመነ እስረኞችንም ሁሉ ፈታቸው እርሱም መጋቢት ስምንት ቀን በዲዮቅልጥያኖስ እጅ በሰማዕትነት ሞተ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ለዘለዓለሙ ከእኛ ጋር ትሁን አሜን፡፡
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት እና #ከገድላት_አንደበት)
https://t.me/finotebirhan12
«ዘወረደ» ይህም በምስጢሩ አምላክ ወልደ አምላክ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቤዛ ዓለም በቅዱስ ፈቃዱ ሰው ሆኖ ከሰማየ ሰማያት ከባሕርይ ልዕልናው በትሕትና ወርዶ ከቅድስት ድንግል ማርያም መወለዱን የሚያመላክት ይህም የሚታወስበት የሚወሳበት የዐቢይ ጾም አንደኛው ሳምንት ነው፡፡ ዮሐ.3፥13
https://t.me/finotebirhan12
የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት #ከፍኖተ_ብርሃን_ሰንበት_ት/ቤት
🔴 ስንክሳር #የካቲት_19
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ዐስራ ዘጠኝ በዚች እለት #የአባ_መርትያኖስ ስጋው የፈለሰበት ሆነ፣ ታላቁ ጻድቅ #አቡነ_አባለ_ክርስቶስም ልደታቸው ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_አባለ_ክርስቶስ
ዳግመኛም በዚህች ቀን ታላቁ ጻድቅ አቡነ አባለ ክርስቶስም ልደታቸው ነው። እርሳቸውም ገና ሲወለዱ ከሰውነታቸው ህቡዕ የሆኑ የእግዚአብሔር የምሥጢር ስሞች በሰውነታቸው ላይ ይዘው (ተጽፎውባቸው) የተወለዱ ናቸው፡፡
አባታቸው ቅዱስ አቃርዮስ እናታቸው ቅድስት ታውክልያ የተባሉ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ደጋግ ቅዱሳን ናቸው፡፡ እነዚህ ቅዱሳን የኢትዮጵያ ነገሥታት መዲና በሆነችው በአክሱም ከተማ በንጉሥ አንበሳ ውድም በ910 ዓ.ም በቤተ ክርስቲያን ሥርዓትና ሕግ በቅዱስ ጋብቻ ተጋቡ፡፡ ንጉሥ አንበሳ ውድም በነገሠ በመጀመሪያ ዓመት እነርሱም በጾም በጸሎት ተወስነው ሲኖሩ እግዚአብሔር የተባረከ ልጅ ቅዱስ አባለ ክርስቶስን ሰጣቸው፡፡ በዚኽም መሠረት አቡነ አባለ ክርስቶስ የካቲት 19 ቀን በአክሱም ከተማ ተወለዱ፡፡ እንደ ነቢዩ ቅዱስ ኤርምያስ በእናታቸው ማሕፀን ሳሉ የተመረጡ ብፁዓት ናቸውና ብፁዕ አባታችን አባለ ክርስቶስ ከሰውነታቸው ህቡዕ የሆኑ የእግዚአብሔር የምሥጢር ስሞች በእብራይስጥ ቋንቋ ‹‹ዲካባ፣ ማርትያስ፣ ክስብኤል›› የተባሉ ህቡዓን የምሥጢር ስሞችን በሰውነታቸው ላይ ይዘው (ተጽፎውባቸው) ተወለዱ፡፡
እናታቸውና አባታቸው ይኽንን ተኣምር በማየት እየተደነቁና እየተገረሙ ትርጉሙ ምን ይሆናል እያሉ ሲደነቁ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል በድንገት መጥቶ ‹‹የእግዚአብሔር አገልጋዮች ጻድቃን ሆይ! ሰላም ለእናንተ ይሁን›› አላቸው፡፡ ዳግመኛም ‹‹እኔ የመጣሁት በእግዚአብሔር ትእዛዝ ነውና እነዚህን የእግዚአብሔር ህቡዓን ስሞች ልተረጉምላችሁ መጥቻለሁ፤ ይህ ታላቅ ስም አባለ ክርስቶስ ተብሎ ይጠራል አላቸው፤ ትርጉሙም አጋንንትን የሚያሥር፣ ጠላትን የሚያርቅ ማለት ነው ›› ብሎ ትርጒሙን ከነገራቸው በኋላ እንዲያጠምቁት አዘዛቸውና ከእነርሱ ተሰወረ፡፡
ከዚኽም በኋላ ወላጆቻቸው ቅዱስ አቃርዮስ እና ቅድስት ታውክልያ በመልአኩ ትእዛዝ መሠረት ወደ አክሱሙ ሊቀ ጳጳስ ወደ አባ ሉቃስ ዘንድ ወሰዷቸው፡፡ ሊቀ ጳጳሱም ሊያጠምቋቸው ሲቀርቡ ህቡዓን የምስጢር ስሞቹ የመለኮት ቃል ስለሆኑ ወዲያውኑ ደንግጠው ወደቁ፡፡ በዚህም ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ በፍጥነት አነሣቸውና ‹‹…በዚህ በምታየው ተኣምር ይህንን ሕፃን አጥምቀው፣ ስሙንም በህቡዓን ስሞች ትርጉም መሠረት አባለ ክርስቶስ ብለህ ጥራው›› በማለት ነገራቸው፡፡ ዳግመኛም መልአኩ ስለ አቡነ አባለ ክርስቶስ ‹‹..እንደ ፋኑኤል መልአክና እንደ አምላኩ መድኀኒዓለም ክርስቶስ የሕሙማን መድኀኒት ይሆናል›› ብሎ ከነገራቸው በኋላ ተሰወረ፡፡
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲትና_ግንቦት_21 #ከገድላት_አንደበት)
https://t.me/finotebirhan12
🛑 ተለቀቀ... ከታች ያለውን በመጫን ሙሉ መንፈሳዊ ድራማን በዩትዩብ ገጻችን ላይ ይመልከቱ ሰብስክራይብና ሼር ያድርጉን
https://youtu.be/E6uh3dn_1Zw?sub_confirmation=1
🔴 መንፈሳዊ ጉዞ በሰንበት ት/ቤታችን የተዘጋጀ
ቀድመው ይመዝገቡ በተጠቀሰው ስልክ አድራሻ
🔴 ስንክሳር #የካቲት_18
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ዐሥራ ስምንት በዚች ቀን ታማኝ የከበረ አባት የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_መላልዮስ አረፈ፣ ከ72ቱ አርድእት አንዱ የሆነ የጌታችን ወንድም የተባለ የአረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍ ልጅ የሐዋርያ #ቅዱስ_ያዕቆብ መታሰቢያው ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አባ_መላልዮስ_ጻድቅ
የካቲት ዐሥራ ስምንት በዚች ቀን ታማኝ የከበረ አባት የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት አባ መላልዮስ አረፈ። ይህም ቅዱስ አዋቂና አስተዋይ ነበረ በታናሹ ቈስጠንጢኖስም ዘመነ መንግሥት በአንጾኪያ ሀገር ሊቀ ጵጵስና ተሾመ።
ከተሾመም እስከ ሠላሳ ቀን ኖረ ከዚህም በኋላ አርዮሳውያንን አወገዛቸው በአንጾኪያም ካለች ቤተ ክርስቲያን ሁሉንም አሳደዳቸው። ንጉሡም በሰማ ጊዜ ከመንበረ ሢመቱ ሊቀ ጳጳሳቱን አሳደደው እርሱ ንጉሡ አርዮሳዊ ነውና።
የአንጾኪያ አገርም ታላላቆችና ኤጲስቆጶሳት ካህናቱም ተሰበሰቡ ስለ ሊቀ ጳጳሳቱ ይመልስላቸው ዘንድ የልመና ደብዳቤ ጽፈው ላኩ ንጉሡም ልመናቸውን ተቀብሎ መለሰላቸው። ይህም አባት በተመለሰ ጊዜ አርዮሳውያንን ወደ ማውገዙ ተመለሰ በቃላቸው የሚያምኑትንም ስሕተታቸውንና ስድባቸውን ግልጽ እያደረገ ወልድ ከአብ ባሕርይ እንደ ተወለደ በመለኮቱም ትክክል እንደሆነ ለሁሉ የሚሰብክ የሚያስተምር ሆነ።
ዳግመኛም አርዮሳውያን ተነሡ የንጉሡን ልብ ወደእሳቸው እስከ መለሱት ድረስ ይህን አባት እየወነጀሉ ወደ ንጉሥ ጻፉ ዳግመኛም ልኮ ከፊተኛው ወደሚርቅ አገር አሳደደው። ወደ ተሰደደበትም አገር በደረሰ ጊዜ መልእክቶቹን ጽፎ በመላክ ከወገኖቹ ጋር እንዳለ ሆነ ከእርሳቸውም ሥውር የሆነውን የመጻሕፍትን ቃል ይተረጉምላቸው ነበር በአንጾኪያ ላሉ መንጋዎቹም ይደርሳቸዋል አዋቂዎች የሆኑ ኤጲስቆጶሳትንና ቀሳውስትን ልዩ በሆነች ሦስትነት ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ አባቶቻችን ያስተማሩዋት የቀናች ሃይማኖትን እንዲአስተምሩ ያዛቸዋል እንዲህም እያደረገ እስከ ዐረፈባት ቀን ድረስ በተሰደደበት ብዙ ዘመናት ኖረ።
ዮሐንስ አፈወርቅም አመስግኖታል የምስጋና ድርሰቶችንም ደረሰለት ስለ ቀናች ሃይማኖትም ብዙ መከራ ስለ ደረሰበት ክብሩና ግርማው ከከበሩ ሐዋርያት ክብር እንደማይጎድል ተናገረ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ሐዋርያው_ቅዱስ_ያዕቆብ
በዚችም ዕለት ከ72ቱ አርድእት አንዱ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ የጌታችን ወንድም የተባለ የአረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍ ልጅ የሐዋርያ ቅዱስ ያዕቆብ መታሰቢያው ነው።
ይህም ቅዱስ የጠራቢው የዮሴፍ ልጅ ነው። እርሱም ከልጆቹ ሁሉ የሚያንስ ነበር። እርሱም ንጹሕ ድንግል ነበር ከጌታችንም ጋራ አደገ ስለዚህም ክብር ይግባውና የጌታችን ወንድም ተባለ። ከጌታችን ዕርገትም በኋላ ሐዋርያት በኢየሩሳሌም ላይ ኤጲስቆጶስ አድርገው ሾሙት። ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አስተምሮ ብዙዎችን ወደ ቀናች ሃይማኖት መለሳቸው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው።
እግዚአብሔርም በእጆቹ ታላላቅ ድንቆችንና ተአምራቶችን አደረገ። በአንዲት ዕለትም በጐዳና ሲጓዝ አንድ ሽማግሌ አገኘ። ቅዱስ ያዕቆብም ሽማግሌ ሆይ በቤትህ ታሳድረኛለህን አለው። አረጋዊውም እሺ እንዳልክ ይሁን አለ በአንድነትም ሲጓዙ ጋኔን ያደረበት ሰው አገኘው በአየውም ጊዜ የክርስቶስ ሐዋርያ ሆይ እኔ ካንተ ጋር ምን አለኝ ልታጠፋኝ መጣህን ብሎ ጮኸ ሐዋርያውም በናዝሬቱ ኢየሱስ ስም ተጠጋ ከሰውዬውም ውጣ አለው። ወዲያውም ያ ጋኔን ከሰውዬው ላይ ወጣ።
ያ ሽማግሌም ይህን ድንቅ ተአምር አይቶ ደነገጠ ከሐዋርያው እግር በታችም ወድቆ እንዲህ አለው። ወደ ቤቴ ልትገባ አይገባኝም ነገር ግን እድን ዘንድ ቤተሰቦቼም ሁሉ ይድኑ ዘንድ ምን ላድርግ አለ ያን ጊዜም ሐዋርያው አቤቱ ጌታዬ ሆይ መንገዴን አሳምረህልኛልና አመሰግንሃለሁ ብሎ ጌታችንን አመሰገነው። ወደ ሽማግሌውም ተመልሶ የድኅነትን ነገር ነገረው ክብር ይግባውና ስለ ጌታችን ሰው መሆን ስለ መከራው ስለ ሞቱና ስለ መነሣቱ አስተማረው።
ከዚህም በኋላ ያ ሽማግሌ ሐዋርያውን ወደ ቤቱ አስገባው ቤተሰቦቹም ሁሉ ወደርሱ ተሰበሰቡ ቅዱስ ያዕቆብም አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው። ሥጋውንና ደሙንም አቀበላቸው።
የከተማው ሰዎችም በሰሙ ጊዜ በሽተኞችን ሁሉ ወደርሱ አመጡ ሁሉንም አዳናቸው ለእነርሱም ሃይማኖትን አስተምሮ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው፡፡ ቀሳውስትንና ዲያቆናትንም ሾመላቸው ያንን ሽማግሌም ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾመው ክብር ይግባውና የጌታችንንም ወንጌል ሰጣቸው ከዚህም በኋላ ያስተምር ዘንድ ወደ ሌሎች አገሮች ወጥቶ ሔደ።
አንዲት መካን ሴት ነበረች እግዚአብሔር ልጅን ይሰጣት ዘንድ ስለርሷ እንዲጸልይላት ቅዱስ ያዕቆብን ለመነችው። እርሱም ጸለየላትና ወንድ ልጅን ወለደች ስሙንም ያዕቆብ ብላ ጠራችው ልጅዋንም ተሸክማ ወደ ሐዋርያው መጥታ ሰላምታ አቀረበችለት ከልጅዋም ጋር ከእርሱ ተባረከች።
ከዚህም በኋላ በአንዲት ቀን ብዙዎች አይሁድ ወደርሱ ተሰበሰቡ ስለ ጌታ ስለ ኢየሱስም የማን ልጅ እንደሆነ ይነግራቸው ዘንድ ጠየቁት እነርሱ እርሱ ጌታን የዮሴፍ ልጅ እንደሆነ እርሱም ወንድሙ እንደሆነ እንደሚነግራቸው አስበው ነበርና።
ቅዱስ ያዕቆብም በሦስተኛ ደርብ ላይ ወጥቶ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነም ከአብ ጋራም ትክክል እንደሆነ ይገልጽላቸው ጀመረ። ይህንንም በሰሙ ጊዜ እጅግ ተቄጡ ከደርቡ ላይ አውርደው የጸና ግርፋትን ገረፉት ከእነርሱም ውስጥ የልብስ ማጠቢያ የዕንጨት ገበታ የያዘ አንድ ሰው መጣ በዚያ ዕንጨትም ቅዱስ ያዕቆብን ራሱ ላይ መታው ያን ጊዜም ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ።
ስለ እርሱም ወይን እንዳልጠጣ፣ ደም ካለው ወገን እንዳልበላ፣ በራሱም ላይ ምላጭ እንዳልወጣ፣ በውሽባ ቤት እንዳልታጠበ፣ ሁለት ልብስንም እንዳልለበሰ፣ ሁልጊዜም እንደሚቆምና እንደሚሰግድ ተጽፎአል። ከመቆም ብዛት የተነሣም እግሮቹ አብጠው ነበር፤ ከዚህም በኋላ አረፈና በቤተ መቅደሱ ጐን ቀበሩት።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት)
🔴 ስንክሳር #የካቲት_17
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
የካቲት ዐስራ ሰባት በዚችም ቀን የእግዚአብሔር ሰው የሆነ የዋህ ቅን ጻድቅ #የሊቀ_ነቢያት_ሙሴ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፣ በዚህች ቀን ከላይኛው ግብጽ ከአክሚም መንደር #መነኰስ_ቅዱስ_ሚናስ በሰማዕትነት ሞተ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ሙሴ_ሊቀ_ነቢያት
የካቲት ዐስራ ሰባት በዚችም ቀን የእግዚአብሔር ሰው የሆነ የዋህ ቅን ጻድቅ የሊቀ ነቢያት ሙሴ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው። ይህ ነቢይ ነፍሱን ስለእሳቸው አሳልፎ እስከ መስጠት ከእግዚአብሔር ወገኖች ጋር የደከመ ነው እርሱም በግብጽ አገር በኤርትራ ባሕርም ድንቆች ተአምራትን ያደረገ ነው።
ይህም ስለ ፈርዖን ትእዛዝ ወላጆቹ በግብጽ ወንዝ ውስጥ በጣሉት ጊዜ አውጥታ ላሳደገችው ለፈርዖን ልጅ ለተርሙት ልጅዋ መባልን አልወደደም። እርሱ ፈርዖን የዕብራውያንን ወንዶች ልጆች ይገድሏቸው ዘንድ አዝዞ ነበርና። በአገኘችውም ጊዜ ለርሷ ልጅ ሊሆናት ወስዳ በመልካም አስተዳደግ አሳደገችው።
አርባ ዓመትም በሆነው ጊዜ አንዱን ዕብራዊ የግብጽ ሰው የሆነ ሲያጠቃው አየ ለዕብራዊውም ተበቅሎ ግብጻዊውን ገደለው። በማግሥቱ ደግሞ ሁለት ዕብራውያን እርስ በርሳቸው ሲጣሉ አያቸው ሊአስታርቃቸውና በመካከላቸው ሰላምን ሊአደርግ ወደደ። አንዱ ዐመፀኛም ትላንት ግብጻዊውን እንደገደልከው ልትገድለኝ ትሻለህን አለው።
ስለዚህም ነገር ሙሴ ፈርቶ ወደ ምድያም አገር ሸሸ በዚያም ሚስት አግብቶ ሁለት ልጆችን ወለደ በዚያም አርባ ዓመት ኖረ በጳጦስ ቍጥቋጦ ውስጥም እሳት እየነደደ ራእይን አየ። አይቶ ሊረዳ በቀረብ ጊዜ ጳጦስ በተባለ ቊጥቋጦ ውስጥ እግዚአብሔር ተናገረው። ወደ ግብጽ አገርም ሒዶ የእስራኤልን ልጆች ከዚያ እንዲአወጣቸው አዘዘው።
ከዚህን በኋላ እግዚአብሔር በሙሴ እጅ በግብጻውያን ላይ ዐሥር መቅሠፍቶችን አመጣ። መጀመሪያው የወንዙን ውኃ ደም ማድረግ የመጨረሻው የግብጻውያንን የበኵር ልጅ መግደል ነው።
ከዚህም በኋላ ሕዝቡን ከግብጽ አገር አወጣቸው የኤርትራንም ባሕር ከፍሎ በውስጡ አሳለፋቸው የባሕሩንም ውኃ በጠላቶቻቸው በፈርዖንና በሠራዊት ላይ ገልብጦ አሠጠማቸው።
ከዚህም በኋላ በምድረ በዳ ውስጥ አርባ ዓመት ሙሉ መና አወረደላቸው ውኃንም ከአለት አፈለቀላቸው ይህን ሁሉ በጎ ሥራ በዚህ በደግ ነቢይ ሙሴ እጅ እግዚአብሔር አደረገላቸው እነርሱ ግን ይዘልፉት ነበር ብዙ ጊዜም በድንጊያ ሊወግሩት ሽተው ነበር።
እርሱ ግን በእነርሱ ላይ ልቡን አስፍቶ በመታገሥ ስለርሳቸው ወደ እግዚአብሔር ይማልዳል። እነርሱንም አብዝቶ ከመውደዱ የተነሣ እግዚአብሔርን አቤቱ የዚህን ሕዝብ በደሉን ይቅር ካላልክ ከሕይወት መጽሐፍህ ሰርዘኝ አለው።
ሰው ከወዳጁ ጋር እንደሚነጋገር አምስት መቶ ሰብዓ ቃላትን ከእግዚአብሔር ጋር እንደተነጋገረ መጽሐፍ ምስክር ሆነ። የእስራኤል ልጆችም በሚያዩት ጊዜ እንዳይሞቱ ፊቱን እስከ ሸፈነ ድረስ በእግዚአብሔር በጌትነቱ ብርሀን ፊቱ በራ።
መቶ ሃያ ዓመት የሆነ ዕድሜውም በተፈጸመለት ጊዜ ለአገልጋዩ ለነዌ ልጅ ለኢያሱ ሕዝቡን እርሱ እንደጠበቃቸው እንዲጠብቃቸው በእጁ ውስጥ እንዲአስረክበው እግዚአብሔር ሙሴን ለኢያሱ አስረክብ ብሎ አዘዘው።
ሙሴም ኢያሱን ጠርቶ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ አዘዘው ሕጉንም እንዲጠብቅ ሕዝቡንም ለኢያሱ በእጁ አስረከባቸው ወደ ምድረ ርስትም እርሱ እንደ ሚአስገባቸው አረጋገጠለት፡፡ ሙሴም እግዚአብሔር እንዳዘዘው በምስክሩ ድንኳን ውስጥ የሚሠራውን ሁሉ ሠርቶ ከአዘጋጀ በኋላ በተራራ ውስጥ አረፈ በዚያም በመላእክት እጅ በሥውር ተቀበረ። የእስራኤል ልጆች ወስደው እንዳያመልኩት እግዚአብሔር የሙሴን ሥጋ ሠወረ።
በእስራኤል ልጆች ውስጥ እንደ ሙሴ ያለ ደግ የዋህ ቅን የሆነ ነቢይ እንደማይነሣ መጽሐፍ ምስክር ሆነ። ሰይጣንም የሙሴን ሥጋ ለእስራኤል ሊገልጥላችው በወደደ ጊዜ ሐዋርያው ይሁዳ በጻፈው መጽሐፉ እንደመሰከረ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ገሠጸው ከዚህም ሥራ ከለከለው የእስራኤል ልጆችም አርባ ቀን አለቀሱለት።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት እና #ስንክሳር_ዘወርኀ_መስከረም_8)
https://t.me/finotebirhan12
现已上线!2025 年 Telegram 研究 — 年度关键洞察 
