Isaiah 48 Apologetics
前往频道在 Telegram
✟ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ✟ "14 The grace of the Lord Jesus Christ, and the love of God, and the communion of the Holy Ghost, be with you all. Amen." (2Corinthians 13:14) 📌 ሌላኛው ቻናላችን:- @ovadiah
显示更多6 368
订阅者
无数据24 小时
+297 天
+18830 天
帖子存档
🚩 እግዚአብሔር ቢፈቅድ እና ብንኖር ዛሬ ማለትም እሁድ 10 ሰዓት ላይ ከአንድ ሙስሊም ወገናችን ጋር ውይይት ይኖረናል
ርዕስ:- ክርስቶስ ተሰቅሏል ወይስ አልተሰቀለም?
♦️ ይህን እውነት በዚያው በኤፌሶን መጽሐፍ ውስጥ እንመለከተዋለን። በኤፌሶን መጽሐፍ ውስጥ አንድ አካል ወይም one body ብሎ የአማኞችን ሲያመለክት ሁሌም የአማኞችን ጉባኤ ወይም ቤተክርስቲያንን ነው፦
"ይህም፥ አሕዛብ አብረው እንዲወርሱ፥ #በአንድ_አካልም (body) አብረው እንዲሆኑ፥ በወንጌልም መስበክ በክርስቶስ ኢየሱስ በሆነ የተስፋ ቃል አብረው እንዲካፈሉ፥ ለቅዱሳን ሐዋርያትና ለነቢያት በመንፈስ አሁን እንደ ተገለጠ በሌሎቹ ትውልዶች ዘንድ ለሰው ልጆች አልታወቀም" (ኤፌ 3:5-6)
በዚህ ቦታ ላይ ሐዋርያው ጳውሎስ አሕዛብ አብረው እንዲወርሱ በአንድ አካልም አብረው እንዲሆኑ በወንጌልም መስበክ በክርስቶስ ኢየሱስ በሆነ የተስፋ ቃል አብረው እንዲካፈሉ ይላል። ይህ ማለት አሕዛብ የክርስቶስ ኢየሱስ ወንጌል ተሰብኮላቸው በጌታ ኢየሱስ ካመኑት አይሁድ ጋር በአንድ አካል ሆነው የተስፋን ቃል እንዲካፈሉ ማለት ነው። ይህ ማለት አሕዛብ ክርስቲያን ሆነው በአካሉ ወይም በቤተክርስቲያን እንዲጨመሩ ማለት ነው። ይህ በኤፌሶን መጽሐፍ ውስጥ ሐዋርያው ጳውሎስ አካል ቤተክርስቲያን ማለቱ እንደሆነ ያሳያል።
"ሁላችን የእግዚአብሔርን ልጅ በማመንና በማወቅ ወደሚገኝ አንድነት፥ ሙሉ ሰውም ወደ መሆን፥ የክርስቶስም ሙላቱ ወደሚሆን ወደ ሙላቱ ልክ እስክንደርስ ድረስ፥ ቅዱሳን አገልግሎትን ለመሥራትና #ለክርስቶስ_አካል (body) ሕንጻ ፍጹማን ይሆኑ ዘንድ" (ኤፌ 4:12-13)
ኤፌ 4:4 ላይ አንድ አካል ካለ በኋላ ወረድ ብሎ እዛው ከቁ.12-13 ላይ የጸጋ ስጦታዎች የተሰጡት የክርስቶስን አካል ወይም ቤተክርስቲያንን ፍጹም ለማድረግ እንደሆነ ሐዋርያው ጳውሎስ ይናገራል። ሁላችንም የእግዚአብሔርን ልጅ በማመንና በማወቅ ወደሚገኝ አንድነት፥ ሙሉ ሰውም ወደ መሆን፥ የክርስቶስም ሙላት ወደሆነ ወደ ሙላቱ እስክንደርስ ድረስ እና ቅዱሳን አገልግሎትን ለመሥራትና ለክርስቶስ አካል ሕንጻ ፍጹማን ይሆኑ ዘንድ በቁ.7 እና በቁ.11 ላይ የተገለጹት የጸጋ ስጦታዎች ተሰጥተዋል። በኤፌ 4:4 አውድ አካል ወይም body ሲል ቤተክርስቲያንን እንደሚያመለክት ያረጋግጣል።
✍️ ስለዚህ በኤፌ 4:4 ላይ በመጠራታችሁ አንድ አካል ሲል ሰዎች ክርስቲያን ሆነው ሊጨመሩባት የሚገባት የክርስቶስ ቤተክርስቲያን ናት። በዚህ ክፍል ላይ አንድ ተስፋ የተባለው የዘላለም ሕይወት ተስፋ ሲሆን (ቲቶ 3:7 ቲቶ 1:2) አንድ አካል የተባለችው ደግሞ የክርስቶስ አካል የሆነችው ቤተክርስቲያን ናት (1ቆሮ 12:12 ኤፌ 3:5-6) አንድ መንፈስ የተባለው መንፈስ ቅዱስ ሲሆን (1ቆሮ 12:13 1ቆሮ 12:11)
አንድ ጌታ የተባለው ደግሞ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው (1ቆሮ 8:6 ሮሜ 10:9-12) አንድ ሃይማኖት የተባለው ለቅዱሳን አንድ ጊዜ የተሰጠው የክርስትና ሃይማኖት ሲሆን (ይሁዳ 1:3 ሐዋ 6:7) አንድ ጥምቀት የተባለው ሰዎች ከክርስቶስ ጋር ለመተባበር የሚጠመቁት የውኃ ጥምቀት ነው (ገላ 3:27 ቆላ 2:12) ከሁሉ በላይ የሆነው በሁሉም የሚሰራው አንድ አምላክ የሁሉም አባት የተባለው ደግሞ የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ አባት እግዚአብሔር አብ ነው (1ቆሮ 12:6 ኤፌ 3:14-15)
✍️ ይህ "አንድ አካል" ሲል መለኮት አንድ ማንነት ብቻ ነው እያለ እንዳልሆነ በግልጽ የሚያሳይ ነው። ምክንያቱም "አንድ አካል" ሲል መለኮት አንድ ማንነት ብቻ ነው እያለ ከሆነ.. አንድ አምላክ፥ አንድ ጌታ፥ አንድ መንፈስ ብሎ አብን ወልድን እና መንፈስ ቅዱስን ባልዘረዘረ ነበር። በግልጽ የማንነት ልዩነትን ባማከለ ሁኔታ ስለ አብ ስለ ወልድ ስለ መንፈስ ቅዱስ መናገሩ "አንድ አካል" ሲል ስለ ቤተክርስቲያን እየተናገረ እንጂ መለኮት አንድ ማንነት ብቻ ነው እያለ እንዳልሆነ ያረጋግጣል።
ጥያቄዎች
1) በኤፌ 4:4 ላይ አንድ አካል የተባለው ማን ነው?
2) በPerson እና በBody መካከል ያለው ልዩነት ምንድነው?
3) አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ሶስት አካል ናቸው ሲባል ሶስት Persons ማለት ሆኖ ሳለ ስለ Body የሚናገርን ክፍል መጥቀስ ስህተት አይሆንምን?
4) በአፌ 4:4 ላይ " #በመጠራታችሁ" ይላል። እነ ማን ናቸው የተጠሩት?
5) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ "መጠራት" የሚለው ሀሳብ ምንን ለማመልከት ጥቅም ላይ ውሏል?
6) "አንድ አካል" የሚለው ሀረግ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ምንን ለማመልከት ጥቅም ላይ ውሏል?
7) አንድ አካል ማለት መለኮት አንድ ማንነት ነው ማለት ከሆነ..አንድ አምላክ የተባለው ማነው? አንድ ጌታ የተባለው ማን ነው? አንድ መንፈስ የተባለው ማን ነው?
▶️ መደምደሚያ
በኤፌ 4:4 ላይ ሐዋርያው ጳውሎስ "አንድ አካል" ሲል መለኮት አንድ ማንነት ወይም Person ብቻ ነው እያለ እንዳልሆነ በበቂ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ ለመመልከት ሞክረናል። በመጀመሪያ ደረጃ ክፍሉ ስለ body እንጂ ስለ Person አይናገርም። ስለዚህ ከመለኮት የአካል/Person ሶስትነትና የባህርይ/Substance አንድነት አይናገርም። ሲቀጥል ክፍሉ ሲጀምር " #በመጠራታችሁ" ብሎ በመጀመሩ እየተናገረ ያለው ከኢ-አማኒነት ወደ ክርስትና ስለመጡት ሰዎች እንደሆነ በመጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃዎች አይተናል።
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ደግሞ የክርስቲያኖች ሕብረት ወይም ቤተክርስቲያን "አንድ አካል" ወይም "One Body" ተብላ እንደምትጠራ በብዙ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃዎች አይተናል። ከዚያም በተጨማሪ በክፍሉ በግልጽ አንድ አምላክ (አብ) አንድ ጌታ ወልድ (ወልድ) አንድ መንፈስ (መንፈስ ቅዱስ) በግልጽ አካላዊ ልዩነትን (Hypostatic Distinction) በማከለ ሁኔታ በመግለጹ "አንድ አካል" ሲል መለኮት አንድ ማንነት ብቻ ነው እያለ እንዳልሆነም ለመመልከት ሞክረናል። የክፍሉ ትክክለኛ አረዳድ ይህ ነው።
ወደዚህ እውነት ያልመጣችሁ ወገኖች ወደ ትክክለኛውን የወንጌል ጥሪ ተቀብላችሁ እውነተኛይቱ የክርስቶስ አካል ውስጥ ትጨመሩ ዘንድ የዘወትር ጸሎታችን ነው
ጌታ ይርዳን!
🚩 አንድ አካል ቤተክርስቲያን ናት
ራሳቸውን "የሐዋርያት ቤተክርስቲያን" ብለው የሚጠሩት ወይም በተለምዶ "Only Jesus" የሚባሉት ወገኖች መለኮት አንድ ማንነት ወይም Person ነው ለማለት እጅግ በተሳሳተ መንገድ ከሚጠቅሷቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች አንዱ ኤፌሶን 4:4 ነው። እነዚህ ወገኖች ይህን ክፍል በመጥቀስ "እግዚአብሔር አንድ አካል ብቻ ነው" ለማለት ይሞክራሉ። ክፍሉ ግን እውን መለኮት አንድ ማንነት/person ብቻ መሆኑን ያሳያልን?
እግዚአብሔር ቢፈቅድ ዛሬ ላይ ይህን ክፍል ለመመልከት የምንሞክር ይሆናል። ክፍሉ እንዲህ ይላል፦
"በመጠራታችሁ በአንድ ተስፋ እንደ ተጠራችሁ #አንድ_አካልና አንድ መንፈስ አለ" (ኤፌ 4:4)
በዚህ ቦታ ላይ ሐዋርያው ጳውሎስ ክርስቲያኖች እንዴት ሕብረት ማድረግ እንዳለባቸው ይናገራል። በቁ.2-3 ላይ በትሕትና ሁሉና በየዋህነት በትዕግሥትም እርስ በእርሳችሁ በፍቅር ታገሱ፥ በሰላም ማሰሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ ካለ በኋላ በቁ.4 ላይ በመጠራታችሁ በአንድ ተስፋ እንደተጠራችሁ አንድ አካልና አንድ መንፈስ አለ ይላል።
እነዚህ ወገኖች ይህን ክፍል በተሳሳተ ሁኔታ ለመረዳታቸው የመጀመሪያው ማሳያ ኤፌ 4:4 "አንድ አካል" ሲል "One Body" እያለ እንጂ "One Person" እያለ አይደለም። ኤፌ 4:4 ላይ "አካል" ተብሎ የተተረጎመው የግሪክ ቃል "σῶμα/ሶማ" የሚለው የግሪክ ቃል ሲሆን በኢንግሊዘኛው "body" ተብሎ ተተርጉሟል፦
"4 There is #one_body, and one Spirit, even as ye are called in one hope of your calling;" (Ephesians 4:4)
ክርስቲያኖች አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ሶስት አካላት ናቸው ስንል ሶስት Persons ናቸው እያልን እንጂ ሶስት bodies ናቸው እያልን አይደለም። ስለዚህ እነዚህ ወገኖች የአማርኛው ቃል በመመሳሰሉ ምክንያት ብቻ ከርዕሰ ጉዳዩ ጋር የማይገናኝን ጥቅስ በመጥቀስ የተሳሳተ እምነት ላይ እንዳሉ ክርስትናንም በተሳሳተ መንገድ እየተቃወሙ እንደሆነ ከዚህ በቀላሉ መረዳት ይቻላል።
✍️ ታዲያ ኤፌ 4:4 በትክክል ምን እያለ ነው?
በአፌ 4:4 ላይ "አንድ አካል" ሲል እያመለከተ ያለው በክርስቶስ ኢየሱስ አምነው የጌታ አካል የሆኑትን የአማኞች ስብስብ ወይንም ቤተክርስቲያንን ነው። ይህንን የምናውቅበት ብዙ መንገድ አለ። ጥቅሱ ሲጀምር የሚጀምረው " #በመጠራታችሁ.." ብሎ ነው። የተጠሩት እነ ማን ናቸው?
ከዓለም ወደ በክርስቶስ ኢየሱስ በማመን ወደ ዘላለምን ሕይወት የተጠሩት አማኞች ናቸው። ይህ ኤፌ 4:4 ላይ "አንድ አካል" ሲል እያመለከተ ያለው እነዚህን የተጠሩትን አማኞች እንደሆነ ያሳያል፦
"ማንም ተገርዞ ሳለ #ተጠርቶ እንደ ሆነ፥ ወደ አለመገረዝ አይመለስ፤ ማንም ሳይገረዝ #ተጠርቶ እንደ ሆነ አይገረዝ" (1ቆሮ 7:18)
በዚህ ቦታ ላይ ሐዋርያው ጳውሎስ ግርዛትን አስመልክቶ ክርስቲያኖችን ሲመክር እንመለከታለን። ማንም ተገርዞ ሳለ ተጠርቶ እንደሆነ ወደ አለመገረዝ አይመለስ ይላል። ይህ ማለት አንድ ሰው ክርስቲያን ከመሆኑ በፊት ተገርዞ ከነበር ክርስቲያን ከሆነ በኋላ ወደ አለመገረዝ መመለስ የለበትም ማለት ነው። ከዚያም ይቀጥልና ማንም ሳይገረዝ ተጠርቶ እንደሆነ አይገረዝ ይላል። ይህ ማለት አንድ ሰው ክርስቲያን ከመሆኑ በፊት ያልተገረዘ ከነበር ክርስቲያን ከሆነ በኋላ መገረዝ የለበትም ማለት ነው። ስለዚህ "መጠራት" ሲል ክርስቲያን መሆን ማለቱ እንደሆነ ከዚህ እንረዳለን።
"ወንድሞች ሆይ፥ እናንተ ለአርነት #ተጠርታችኋልና፤ ብቻ አርነታችሁ ለሥጋ ምክንያትን አይስጥ፥ ነገር ግን በፍቅር እርስ በርሳችሁ እንደ ባሪያዎች ሁኑ" (ገላ 5:13)
በዚህ ቦታ ላይ ሐዋርያው ጳውሎስ የገላትያን ክርስቲያኖች ለአርነት እንደተጠሩ ሲነግራቸው እንመለከታለን። ይህ ማለት ክርስቲያኖች ከመሆናቸው በፊት ከነበሩበት የሕግ ሸክም አሁን ጌታ ኢየሱስን አምነው ክርስቲያኖች በመሆናቸው ምክንያት ከዚያ ሸክም አርነት ወጥተዋል ማለት ነው። በቁ.11 ላይ እስካሁን ስለ መገረዝ ወይም ሕግን ስለመፈጸም እንደማይሰብክ ያስተማረው ለዚያ ነው። ስለዚህ ለአርነት ተጠርታችኋል ሲል ክርስትያን የሆናችሁት ለአርነት ነው ማለቱ ነው። ይህ "መጠራት" የሚለውን ሀሳብ ክርስቲያን መሆንን ለማመልከት እንደሚጠቀመው ከዚህ እንረዳለን።
"በእግዚአብሔር ለተወደዳችሁና ቅዱሳን ልትሆኑ #ለተጠራችሁ በሮሜ ላላችሁት ሁሉ፥ ከእግዚአብሔር ከአባታችን ከጌታም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን" (ሮሜ 1:7)
በዚህ ቦታ ላይ ሐዋርያው ጳውሎስ በእግዚአብሔር ለተወደዳችሁና ቅዱሳን ልትሆኑ ለተጠራችሁ በሮሜ ላላችሁት ሁሉ ከእግዚአብሔር ከአባታችን ከጌታም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን ይላል። ሐዋርያት ጳውሎስ ይህን ሰላምታ እያቀረበ ያለው በሮሜ ላሉት ክርስቲያኖች ሲሆን ቅዱሳን ልትሆኑ የተጠራችሁ ይላቸዋል። ይህ ማለት የተጠሩት ወይም ክርስቲያኖች የሆኑት ቅዱሳን ለመሆን ነው። ክርስቲያኖች በመሆናቸውም ሐዋርያው ጳውሎስ እነርሱን ክርስቲያኖች አድርጎ በመቁጠር መልእክት ጽፎላቸዋል። ስለዚህ "መጠራት" የሚለውን ሀሳብ ክርስቲያን መሆንን ለማመልከት እንደሚጠቀመው ከዚህ እንረዳለን።
▶️ ስለዚህ በአፌ 4:4 ላይ " #በመጠራታችሁ.." ካለ በኋላ "አንድ አካል" ሲል ይህን ከኢ-አማኒነት ወደ ክርስቲያንነት የተሻገሩትን የአማኞች ወይም የክርስቲያኖችን ሕብረት እያመለከተ እንደሆነ ከዚህ እንረዳለን። በዚያው አውድ ላይ "መጠራት" የሚለውን ሀሳብ ለክርስቲያኖች ጥቅም ላይ ያዋለው ለዚያ ነው፦
"እንግዲህ በጌታ እስር የሆንሁ እኔ #በተጠራችሁበት_መጠራታችሁ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እለምናችኋለሁ" (ኤፌ 4:1)
"አንድ አካል" ባለበት በዚያው በኤፌ 4:4 አውድ ላይ "እንግዲህ በጌታ እስር የሆንሁ እኔ በተጠራችሁበት መጠራታችሁ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እለምናችኋለሁ" ይላል። በተጠራችሁበት መጠራታችሁ ሲል ባገኛችሁት የክርስትና ሕይወት እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እለምናችኋለሁ ማለት ነው። ሰዎቹ ከአለማመን ወደ ክርስትና ስለ መጡ ክርስቲያን ሊመላለስ በሚገባው ሕይወት እንዲመላለሱ እየመከራቸው ነው። ይህ "መጠራት" የሚለውን ሀሳብ በዚያው በኤፌ 4:4 ከኢ-አማኒነት ወደ ክርስትና የመጡትን ሰዎች ለማመልከት እንደሚጠቀመው ያሳያል።
✍️ ይህ የክርስቲያኖች ጉባኤ ምን ይባላል?
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ክርስቲያን እንዲሆኑ የተጠሩት የክርስቲያኖች ወይም የአማኞች ሕብረት "አካል" ወይም "body" ተብሎ ተብሏል። ክርስቶስ የቤተክርስቲያን ራስ ነው (ቆላ 1:18) አማኞች ደግሞ የእርሱ አካል ናቸው። ስለዚህ ኤፌ 4:4 ላይ በመጠራታችሁ አንድ አካል ሲል ክርስቲያኖችን ሕብረት እንደሚገልጽ ከዚህ እንረዳለን፦
"እንዲሁ ብዙዎች ስንሆን በክርስቶስ #አንድ_አካል (body) ነን፥ እርስ በርሳችንም እያንዳንዳችን የሌላው ብልቶች ነን" (ሮሜ 12:5)
"እናንተም #የክርስቶስ_አካል (body) ናችሁ እያንዳንዳችሁም ብልቶች ናችሁ" (1ቆሮ 12:27)
" #በአንድ_አካልም (body) የተጠራችሁለት ደግሞ የክርስቶስ ሰላም በልባችሁ ይግዛ። የምታመሰግኑም ሁኑ" (ቆላ 3:15)
"አይሁድ ብንሆን የግሪክ ሰዎችም ብንሆን ባሪያዎችም ብንሆን ጨዋዎችም ብንሆን እኛ ሁላችን በአንድ መንፈስ #አንድ_አካል (body) እንድንሆን ተጠምቀናልና። ሁላችንም አንዱን መንፈስ ጠጥተናል" (1ቆሮ 12:13)
✍️ ስለዚህ በዮሐንስ 5:31-32 ላይ ለጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚመሰክረው ሌላ ምስክር እግዚአብሔር አብ እንጂ ስራ ሊሆን አይችልም። ምክንያቱም ይህ ሌላ ምስክር "እርሱ" ወይም "He" ተብሎ ተጠርቷልና። በተጨማሪም በመላው የመጽሐፍ ቅዱስ አውድና በአቅራቢያው ባለው አውድ "እርሱ" ወይም "He" ተብሎ ለኢየሱስ የሚመሰክረው ምስክር አብ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምራል።
በሚያስገርም ሁኔታ ቅድም ባየነውና በዚያው በዮሐ 5:31-32 አቅራቢያ ባለው አውድ ማለትም በቁ.37 ላይ ለጌታ ኢየሱስ የሚመሰክረው አብ "እርሱ" ወይም "He" ተብሏል፦
"የላከኝ #አብም 👉 #እርሱ 👈 ስለ እኔ #መስክሮአል። ድምፁን ከቶ አልሰማችሁም፥ መልኩንም አላያችሁም" (ዮሐ 5:37)
"37 And #the_Father 👉 #himself 👈 which hath sent me, hath borne #witness of me. Ye have neither heard his voice at any time, nor seen his shape." (John 5:37)
ይህ በማያሻማ ሁኔታ በዮሐ 5:31-32 ላይ ያለው ለጌታ ኢየሱስ የሚመሰክርለት ሌላ ምስክር አብ እንደሆነ ያረጋግጣል። ምክንያቱም በአንድ አውድ ባሉት በሁለቱም ቦታዎች ላይ "እርሱ" ወይም "He" ተብሏልና። ከመስካሪነቱ ባሻገር። ይህ በማያሻማ ሁኔታ ሌላ ምስክር የተባለው አብ እንደሆነ ያረጋግጣል።
♦️ አብ ደግሞ ከኢየሱስ የተለየ ሌላ ምስክር ከሆነ ኢየሱስና አብ አንድ ማንነት ሊሆኑ አይችሉም። ሌላነቱ ወይም the otherness የሚያመለክተው የማንነት ልዩነትን ነው። ጌታ ኢየሱስ " #ለራሴ ብመሰክር ምስክርነቴ እውነት አይደለም" ሲል ራሴ የሚለው የራሱን ማንነት ነው። ከዚያ "ስለ እኔ የሚመሰክረው #ሌላ ነው" ሲል #ሌላ የሚለው ያን #ራሱን ያልሆነውን ሌላን ማንነት ነው። ኢየሱስ አብ ከሆነ አንደኛ ለራሴ አልመሰክርም ብሎ ለራሱ መሰከረ ማለት ይሆናል ሲቀጥል ሌላ ምስክር ማለቱም ትርጉም አይኖረውም። ስለዚህ ይህ ክፍል ኢየሱስ አብ እንዳልሆነ ያረጋግጣል።
ጥያቄዎች
1) በዮሐ 5:31-32 ላይ "እርሱ" ወይም "He" የተባለው ማን ነው?
2) በመላው መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሥራ "እርሱ" ወይም "He" የተባለበት ቦታ አለ?
3) ከላይ ለማየት እንሞከርነው አብ "እርሱ" ወይም "He" ተብሏል። ይህ በዮሐ 5:31-32 ላይ ያለው "እርሱ" ወይም "He" የተባለው ሌላ ምስክር መሆኑን አያሳይም?
4) በዮሐ 5:31-32 አውድ ላይ ባለው ዮሐ 5:37 ላይ ለኢየሱስ የመሰከረው አብ መሆኑ፥ በዮሐ 5:31-32 ላይ ያለው ሌላ ምስክር አብ መሆኑን አያሳይምን?
5) በዮሐ 5:37 ላይ አብ "እርሱ" ወይም "He" መባሉ በዮሐ 5:31-32 ላይ ያለው "እርሱ" ወይም "He" የተባለው ሌላ ምስክር መሆኑን አያሳይም?
6) በዩሐ 5:31-32 ላይ ኢየሱስ ለራሴ ብመሰክር ምስክርነቴ እውነት አይደለም ብሏል። ራሴ ሲል የራሱን ማንነት እያመለከተ አይደለምን?
7) በዩሐ 5:31-32 ላይ ኢየሱስ ለራሴ ብመሰክር ምስክርነቴ እውነት አይደለም ብሏል። ኢየሱስ አብ ከሆነ ለራሱ መሰከረ ማለት አይሆንምን? ታዲያ ምስክርነቱ እንዴት እውነት ይሆናል?
8) በዮሐ 5:31-32 ላይ ኢየሱስ ስለ እርሱ የሚመሰክረው ሌላ ምስክር እንደሆነ ገልጿል። ሌላ ማለት ምን ማለት ነው?
9) በዮሐ 5:31-32 ላይ ኢየሱስ ስለ እርሱ የሚመሰክረው ሌላ ምስክር እንደሆነ ገልጿል። አብ ከኢየሱስ ሌላ ማንነት ካልሆነ #ሌላ መባሉ ትርጉሙ ምንድነው?
▶️ መደምደሚያ
በዮሐንስ 5:31-32 ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱና አባቱ እግዚአብሔር አብ የተለያዩ ማንነት መሆናቸውን ገልጿል። እርሱ ስለ ራሱ ከመሰከረ ምስክርነቱ እውነት እንደማይሆንና ለእርሱ የሚመሰክረው ሌላ ምስክር እንደሆነ ገልጿል። በዚያ ቦታ ላይ ሌላ ምስክር የተባለው ሥራ ሳይሆን አባቱ እግዚአብሔር አብ ነው። በሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች አባቱ እግዚአብሔር እንደመሰከረለት ተገልጿል፥ በአውዱም የመሰከረለት አብ እንደሆነ ተገልጿል።
በተጨማሪም "እርሱ" ወይም "He" በሚለው ማንነትን ወይም Person አመልካች ቃል በመጠቀም የሚመሰክርለት አባቱ እንደሆነ ገልጿል። ስለዚህ እግዚአብሔር አብ ለልጁ ለኢየሱስ የሚመሰክረው ሌላ ምስክር እንጂ ኢየሱስ እንዳልሆነ ከዚህ ክፍል እንረዳለን። አለዚያ "..ለራሴ ብመሰክር ምስክርነቴ እውነት አይሆንም.." ደግሞም "..ሌላ ምስክር.." የሚሉት ቃል ትርጉም አይኖራቸውምና። ይህን እውነት ተረድታችሁ ወደ እውነተኛው አምላክ ወደ እግዚአብሔርና ወደ ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ ያልመጣችሁ ወገኖች ወደ እርሱ ትመጡ ዘንድ የዘወትር ጸሎታችን ነው።
ጌታ ይርዳን!
🚩 ሌላ ምስክር የተባለው አብ ነው
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ እና አባቱ እግዚአብሔር አብ የተለያዩ ማንነቶች መሆናቸውን ከሚያሳዩት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች አንዱ ዮሐንስ 5:31-32 ነው። በዚያ ክፍል ላይ እግዚአብሔር አብ ከጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የተለየ ሌላ ምስክር ተብሏል። እናንብበው፦
"31 እኔ ስለ እኔ ስለ ራሴ ብመሰክር #ምስክሬ እውነት አይደለም 32 #ስለ_እኔ_የሚመሰክር #ሌላ ነው፥ #እርሱም ስለ እኔ የሚመሰክረው ምስክር እውነት እንደ ሆነ አውቃለሁ" (ዮሐ 5:31-32)
በዚህ ቦታ ላይ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እራሱ ቢመስክር ምስክርነቱ እውነት እንዳልሆነ፥ ስለ እርሱ የሚመሰክረው ሌላ ምስክር እንደሆነ እና እርሱም ወይም ሌላኛው ምስክር ስለ እርሱ የሚመሰክረ ምስክርነት እውነት መሆኑን ሲናገር እንመለከታለን። ስለዚህ በዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል መሰረት ከኢየሱስ የተለየ ሌላ ምስክር ለኢየሱስ ይመሰክርለታል ማለት ነው።
እንደ መጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ ለኢየሱስ የሚመሰክርለት ይህ ሌላኛው ምስክር እግዚአብሔር አብ ነው። እግዚአብሔር አብ በደመና ጌታ ኢየሱስ ልጁ መሆኑን መስክሮለታል (ማቴ 3:17) አባት ሆይ ስምህን አክብረው ሲለው "አከበርሁት ደግሞም አክብሬዋለሁ" የሚል ድምፅ በማሰማት በዙሪያው የነበሩ ሰዎች አብ የኢየሱስ አባት፥ ኢየሱስ ደግሞ የአብ ልጅ መሆኑን እንዲያውቁ መስክሮለታል (ዮሐ 12:28-30) በድጋሚም ልጁ መሆኑን ከደመና ድምፅ በማሰማት መስክሮለታል (ማር 9:7) ስለዚህ በዚህ ክፍል ላይ ጌታ "ሌላ ምስክር" ብሎ የሚጠራው አብን ነው ማለት ነው።
ይህንንም እውነት በዚያው በዮሐ 5:31-32 አውድ ላይ እንመለከተዋለን። በዚያ ክፍል ላይ ለክርስቶስ ኢየሱስ የሚመሰክርለት ምስክር አብ እንደሆነ ጌታ ገልጿል፦
"የላከኝ #አብም እርሱ #ስለ_እኔ #መስክሮአል። ድምፁን ከቶ አልሰማችሁም፥ መልኩንም አላያችሁም" (ዮሐ 5:37)
በቁ.31-32 ላይ ስለ እኔ የሚመሰክር ሌላ ምስክር አለ ካለ በኋላ ወረድ ብሎ፥ ጌታ ኢየሱስ በቁ.37 ላይ እርሱን የላከው አብ ስለ እርሱ እንደመሰከረ በመናገር በቁ.31-32 ላይ ሌላ ምስክር ያለው አብን እንደሆነ ገልጿል። ስለዚህ በትክክለኛው አውዳዊ አፈታት (contextual interpretation) በቁ.31-32 ላይ ሌላ ምስክር የተባለው በቁ.37 ላይ ለልጁ ለኢየሱስ የመሰከረው እግዚአብሔር አብ ነው።
✍️ ይህ ቀጥተኛና ግልጽ የሆነው የመጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ ሆኖ ሳለ የOnly Jesus አማኞች በዮሐ 5:31-32 ላይ ሌላ ምስክር የተባለው አብ ሳይሆን ክርስቶስ የሰራው ስራ ነው ይላሉ። ይህ እጅግ በጣም ስህተት የሆነ ኢ-መጽሐፍ ቅዱሳዊ አረዳድ ነው። ምክንያቱም በዮሐ 5:31-32 ላይ የተነገረለት ሌላ ምስክር "እርሱ" ወይም "He" ተብሏል፦
"31 እኔ ስለ እኔ ስለ ራሴ ብመሰክር ምስክሬ እውነት አይደለም 32 ስለ እኔ የሚመሰክር #ሌላ ነው፥ 👉 #እርሱም 👈 ስለ እኔ የሚመሰክረው ምስክር እውነት እንደ ሆነ አውቃለሁ" (ዮሐ 5:31-32)
"31 If I bear witness of myself, my witness is not true. 32 There is #another that beareth witness of me; and I know that the witness which 👉 #he 👈 witnesseth of me is true" (John 5:31-32)
ይህ "እርሱ" ወይም "He" የሚለው ቃል ማንነትን ወይም Person የሚያመለክት ቃል ሲሆን በመላው መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አንድም ጊዜ ለስራ ጥቅም ላይ ውሎ አያውቅም። ስራ "እርሱ" ወይም "He" ተብሎ የተጠራበት አንድም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የለም። ምክንያቱም ስራ ተግባር እንጂ ማንነት አይደለም። ስለዚህ ልክ እንደ ማንነት "እርሱ" ወይም "He" ተብሎ ሊጠራ አይችልም። ስለዚህ በዮሐ 5:31-32 ላይ "እርሱ" ወይም "He" የተባለው ሌላ ምስክር ስራ ሊሆን አይችልም።
▶️ በተቃራኒው ግን እግዚአብሔር አብ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተደጋጋሚ "እርሱ" ወይም "He" ተብሎ ተጠርቷል። ይህ በዮሐ 5:31-32 ላይ የተነገረለት ሌላ ምስክር መሆኑን በሚገባ ያረጋግጣል። ለምሳሌ፦
"እኔ ከራሴ አልተናገርሁምና፤ ነገር ግን #የላከኝ_አብ 👉 #እርሱ 👈 የምለውን የምናገረውንም ትእዛዝ ሰጠኝ" (ዮሐ 12:49)
"49 For I have not spoken of myself; but #the_Father which sent me, 👉 #he 👈 gave me a commandment, what I should say, and what I should speak" (John 12:49)
በዚህ ቦታ ላይ እግዚአብሔር አብ "እርሱ" ወይም "He" ተብሎ ሲጠራ እንመለከታለን። ጌታ ኢየሱስ የሚናገረው ከራሱ እንዳልሆነና የላከው አብ የሚለውን የሚናገረውንም ትዕዛዝ እንደሰጠው ሲገልጽ አብን "እርሱ" ወይም "He" ብሎ ጠርቶታል። ይህ አብ "እርሱ" ወይም "He" ተብሎ እንደሚጠራ ያሳያል።
"ኢየሱስም አላቸው። እግዚአብሔርስ አባታችሁ ከሆነ በወደዳችሁኝ ነበር፤ እኔ #ከእግዚአብሔር ወጥቼ መጥቻለሁና፤ 👉 #እርሱ 👈 ላከኝ እንጂ ከራሴ አልመጣሁምና" (ዮሐ 8:42)
"42 Jesus said unto them, If God were your Father, ye would love me: for I proceeded forth and came from #God; neither came I of myself, but 👉 #he 👈 sent me" (John 8:42)
በዚህ ቦታ ላይም እግዚአብሔር አብ "እርሱ" ወይም "He" ተብሎ ሲጠራ እንመለከታለን። ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ከእግዚአብሔር ዘንድ ወጥቶ መምጣቱንና እርሱ እንደላከው እንጂ ከራሱ እንዳልመጣ ሲናገር እግዚአብሔርን ወይም አብን "እርሱ" ወይም "He" ብሎ ጠርቶታል። ይህ አብ "እርሱ" ወይም "He" ተብሎ እንደሚጠራ ያሳያል።
"እኔም አላውቀውም ነበር፥ ዳሩ ግን በውኃ አጠምቅ ዘንድ #የላከኝ 👉 #እርሱ 👈 መንፈስ ሲወርድበትና ሲኖርበት የምታየው፥ በመንፈስ ቅዱስ የሚያጠምቅ እርሱ ነው አለኝ" (ዮሐ 1:33)
"33 And I knew him not: but 👉 #he 👈 that #sent me to baptize with water, the same said unto me, Upon whom thou shalt see the Spirit descending, and remaining on him, the same is he which baptizeth with the Holy Ghost" (John 1:33)
በዚህ ስፍራ ላይም እግዚአብሔር አብ "እርሱ" ወይም "He" ተብሎ ሲጠራ እንመለከታለን። መጥምቁ ዮሐንስ እግዚአብሔር እንደላከው ሲናገር የላከኝ "እርሱ" ወይም "He" በማለት የላከው እግዚአብሔር አብን "እርሱ" ወይም "He" ብሎ ይጠራዋል። ይህ እግዚአብሔር አብ "እርሱ" ወይም "He" ተብል እንደሚጠራ ያሳያል።
🚩 አርሲ ውስጥ እየፈሰሰ ያለው የኦርቶዶክሳውያን ደም ወደ እግዚአብሔር ይጮሃል!
እግዚአብሔር የነፍሰ ገዳይነትን መንፈስ ይገስጽልን!
🚩 የምንበላው የአብን ሥጋ ነው?
ለኦንሊ ጂሰሱ ቄስ የአጋንንት ትምህርት የተሰጠ ምላሽ
https://vt.tiktok.com/ZSxcouYVQ/
🚩 እግዚአብሔር በሰይጣን ቁጥጥር ገባ ብሎ ለዋሸው ኡስታዝ የተሰጠ ምላሽ!
https://vt.tiktok.com/ZSxsFTgRC/
"12 ያዕቆብ ሆይ፥ የጠራሁህም እስራኤል ሆይ፥ ስማኝ፤ እኔ ነኝ፤ #እኔ_ፊተኛው_ነኝ_እኔም_ኋለኛው_ነኝ 13 #እጄም_ምድርን_መሥርታለች #ቀኜም_ሰማያትን_ዘርግታለች፤ በጠራኋቸው ጊዜ በአንድነት ይቆማሉ" (ኢሳ 48:12-13)
በዚህ ቦታ ላይ እግዚአብሔር አምላክ ዘላለማዊነቱን እና ፈጣሪነቱን በአንድ አውድ ላይ ሲናገር እንመለከታለን። በቁ.12 ላይ "እኔ ፊተኛው ነኝ እኔ ኋለኛው ነኝ" በማለት ዘላለማዊነቱን ይገልጻል። ፊተኛ እና ኋለኛ ማለት ዘላለማዊ ማለት ነውና። ከዚያም በቁ.13 ላይ "እጄም ምድርን መሥርታለት ቀኜም ሰማያትን ዘርግታለች" በማለት ፈጣሪነቱን ይናገራል። እጅና ቀኝ ሃይልን ስለሚያመለክቱ እግዚአብሔር ፍጥረታትን በሃይሉ እንደፈጠረ የሚገልጽ ነው። ስለዚህ በአንድ አውድ ላይ የእግዚአብሔር ዘላለማዊነትና ፈጣሪነት ተገልጿል። ይህ ማለት በዮሐ 1:1-3 ላይ ቃል የተገለጸበት አገላለጽ አምላካችን እግዚአብሔር በኢሳ 48:12-16 የተገለጸበት ራሱ አገላለጽ ነው ማለት ነው። ይህ የቃልን እውነተኛ መለኮትነት በሚገባ ያረጋግጣል።
✍️ ሐዋርያው ዮሐንስ ይህንኑ አይነት አገላለጽ በአዲስ ኪዳንም እግዚአብሔርን ይገልጽበታል። ይህ ሐዋርያው ዮሐንስ እውነተኛ መለኮትን የሚገልጽበት የመግለጫ መንገድ እንደሆነ በሚገባ ያሳያል፦
"9 እንስሶቹም በዙፋን ላይ ለተቀመጠው #ከዘላለምም_እስከ_ዘላለም_በሕይወት_ለሚኖረው ለእርሱ ክብርና ውዳሴ ምስጋናም በሰጡት ጊዜ፥ 10-11 ሀያ አራቱ ሽማግሌዎች በዙፋን ላይ በተቀመጠው ፊት ወድቀው፥ #ከዘላለም_እስከ_ዘላለም_በሕይወት_ለሚኖረው እየሰገዱ። ጌታችንና #አምላካችን ሆይ፥ አንተ #ሁሉን_ፈጥረሃልና #ስለ_ፈቃድህም_ሆነዋልና #ተፈጥረውማልና ክብር ውዳሴ ኃይልም ልትቀበል ይገባሃል እያሉ በዙፋኑ ፊት አክሊላቸውን ያኖራሉ" (ራዕ 4:9-11)
በዚህ ቦታ ላይ የእግዚአብሔር ዘላለማዊነት፥ አምላክነትና ፈጣሪነት በአንድ አውድ ተገልጾ እንመለከታለን። ሐዋርያው ዮሐንስ ከጌታ ዘንድ ተቀብሎ የሚያየውን ራዕይ እንመለከታለን (ራዕ 1:1) በቁ.9 ላይ እንስሳቱ ወይም አራቱ ኪሩቤል ከዘላለም እስከ ዘላለም በሕይወት ለሚኖረው ለእርሱ ክብርና ውዳሴ ምስጋናም ሰጡት ይላል። "ከዘላለም እስከ ዘላለም በሕይወት የሚኖረው" መባሉ የእግዚአብሔርን ዘላለማዊነት የሚገልጽ ነው። ይህን እውነት በቁ.10-11 ላይ ተደግሟል። ሀያ አራቱ ሽማግሌዎች "ከዘላለም እስከ ዘላለም በሕይወት ለሚኖረው" እየሰገዱ ይላል። ይህ የእግዚአብሔርን ዘላለማዊነት የሚያመለክት ነው።
ከዚያም ይቀጥልና ሀያ አራቱ ሽማግሌዎች ከዘላለም እስከ ዘላለም በሕይወት ለሚኖረው እየሰገዱ "ጌታችንና አምላካችን ሆይ" ይላሉ። "አምላካችን" ሆይ መባሉ የእግዚአብሔርን አምላክነት የሚያሳይ ነው። ከዚያም ይህን ካለ በኋላ በዚያው ቁጥር ላይ "አንተ ሁሉን ፈጥረሃል ስለ ፈቃድህም ሆነዋልና ተፈጥረዋልና" ማለታቸውን ይዘግብልናል። ይህ የእግዚአብሔርን ፈጣሪነት ያሳያል። ስለዚህ በአንድ አውድ ላይ የእግዚአብሔር ዘላለማዊነት፥ አምላክነትና ፈጣሪነት ተገልጿል። ይህ ማለት ዮሐ 1:1-3 ላይ ቃል የተገለጸበት አገላለጽ እግዚአብሔር አምላክ በራዕ 4:9-11 ላይ የተገለጸበት ያው አገላለጽ ነው። ይህ የቃልን እውነተኛ መለኮትነት ያረጋግጣል።
" #ሰማይንና_በእርሱም_ያሉትን_ምድርንና_በእርስዋም_ያሉትን_ባሕርንና_በእርሱም_ያሉትን_በፈጠረው፥ #ከዘላለምም_እስከ_ዘላለም_ድረስ_ሕያው_ሆኖ_በሚኖረው ምሎ" (ራዕ 10:6)
በዚህ ቦታ ላይ የአምላካችን የእግዚአብሔር ፈጣሪነት እና ዘላለማዊነት በአንድ አውድ ላይ ሲነገር እንመለከታለን። ሐዋርያው ዮሐንስ አንድ ደመናን የተጎናጸፈ ብርቱ መልአክ ከሰማይ ሲወርድ በራዕይ ያያል (ራዕ 10:1) ይህም መልአክ ወደ ምድር ከወረደ በኋላ "ሰማይንና በእርሱም ያሉትን ምድርንና በእርሷም ያሉትን ባህርንና በእርሷም ያሉትን በፈጠረው" እንደ ማለ ይናገራል። ይህ የእግዚአብሔርን ፈጣሪነት የሚያሳይ ነው። ነገር ግን መልአኩ በእግዚአብሔር ሲምል ፈጣሪነቱን ብቻ ሳይሆን ያመለከው ዘላለማዊነቱንም ነው። "ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ሕያው ሆኖ በሚኖረው" ምሎ ይላል። ይህ የእግዚአብሔርን ዘላለማዊነት ያመለክታል። ስለዚህ በአንድ አውድ ላይ የአምላካችን የእግዚአብሔር ፈጣሪነትና ዘላለማዊነት ተገልጿል። ይህ ማለት ዮሐ 1:1-3 ላይ ቃል የተገለጸበት አገላለጽ እግዚአብሔር አምላክ በራዕ 10:6 ላይ የተገለጸበት ያው አገላለጽ ነው። ይህ የቃልን እውነተኛ መለኮትነት ያረጋግጣል።
♦️ አስተውሉ! የዮሐንስ ራዕይንም የዮሐንስ ወንጌልንም የጻፈው ሐዋርያው ዮሐንስ ነው። በራዕዩ ላይ እግዚአብሔር አምላክን በገለጸበት በዚያው የአምላክነት፥ የፈጣሪነትና የዘላለማዊነት አገላለጽ ወንጌሉ ላይ ቃልን ወይም ልጁ ኢየሱስን መግለጹ በማያሻማ ሁኔታ የእግዚአብሔር ልጅ ጌታ ኢየሱስ መለኮት መሆኑን ያረጋግጣል። ሐዋርያው ዮሐንስ በመንፈስ ቅዱስ ጥንሳሴ የጻፈው መለኮታዊ መገለጥ እርሱ ነውና።
▶️ ድምዳሜ
በሁለት ተከታታይ ክፍሎች በዮሐንስ 1:1 ላይ ያለው ቃል ወይም ልጁ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማን እና ምን እንደሆነ በብዙ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃዎች ለመመልከት ሞክረናል። ቃል ወይል ወልድ አባቱ እግዚአብሔር አብ ዘላለማዊ፥ አምላክ፥ ፈጣሪ መሆኑ በተነገረለት በዚያው መንገድ ዘላለማዊነቱ፥ አምላክነቱና ፈጣሪነቱ የተነገረለት፥ ደግሞም በብሉይ ኪዳንና በአዲስ ኪዳን እግዚአብሔር አብ በተገለጸበት አገላለጽ (portrayal) የተገለጸ ነው። ይህ ያለ ምንም ጥርጥር እውነተኛ መለኮት መሆኑን ያሳያል። ይህን ጌታ አውቃችሁ የዘላለም ሕይወት ያላገኛችሁ ሰዎች አውቃችሁት ትድኑ ዘንድ የዘወትር ጸሎታችን ነው!
ጌታ ይርዳን!
🚩 ዮሐንስ 1:1 እና የቃል ማንነት (ክፍል 2)
ባለፈው ክፍል ላይ ሐዋርያው ዮሐንስ በመንፈስ ቅዱስ ጠንሳሽነት በዮሐንስ 1:1 ላይ የቃል ወይም የእግዚአብሔርን ልጅ የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን ማንነት እንዴት እንደተናገረ ለማየት ሞክረን ነበር። የቃልን ዘላለማዊነት፥ የቃልን ከእግዚአብሔር ጋር የነበረ መሆን፥ የቃልን በምንነት ደረጃ እግዚአብሔር መሆን፥ የቃልን ፈጣሪነት እንዴት እንደገለጸ ለመመልከት ሞክረን ነበር። በሰዋሰውም በጽንሰ ሀሳብም ሐዋርያው ዮሐንስ ስለ ቃል የተናገረው ነገር ቃል ወይም ጌታ ኢየሱስ ከአብ ጋር የነበረው፥ ከዘላለም ጀምሮ የነበረው የሁሉ ፈጣሪ የሆነው እግዚአብሔር መሆኑን ያረጋግጣል።
▶️ ዛሬ እግዚአብሔር ቢፈቅድ በዚህ ክፍል ላይ ይህንኑ እውነት በተጨማሪ ማስረጃዎች መመልከቱን እንቀጥላለን
"1 #በመጀመሪያው_ቃል_ነበረ፥ #ቃልም_በእግዚአብሔር_ዘንድ_ነበረ፥ #ቃልም_እግዚአብሔር_ነበረ 2 ይህ በመጀመሪያው በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ 3 #ሁሉ_በእርሱ_ሆነ፥ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም" (ዮሐ 1:1-3)
ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርነው ሐዋርያው ዮሐንስ ቃል ዘላለማዊ፥ ከእግዚአብሔር ጋር የነበረ፥ እግዚአብሔር እና ፈጣሪ መሆኑን በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ገልጿል። የቃልን ዘላለማዊነት የገለጸው በኢሳ 43:13 ላይ እግዚአብሔር አምላክ የራሱ ዘላለማዊነት በገለጸበት መንገድ ሲሆን የቃልን እግዚአብሔርነት የገለፀው ደግሞ በመዝ 118:27 ላይ የእግዚአብሔር አምላክነት በተገለጸበት በዚያው መንገድ ነው። የቃልን ፈጣሪነት የገለጸው ደግሞ ሮሜ 11:36 ላይ የእግዚአብሔር ፈጣሪነት በተገለጸበት በዚያው መንገድ ነው።
በብሉይ ኪዳን አስተምህሮ በአንድ አውድ ላይ ዘላለማዊነቱ፥ አምላክነቱና ፈጣሪነቱ የተነገረለት እግዚአብሔር አምላክ ብቻ ነው። ሐዋርያው ዮሐንስ በብሉይ ኪዳን ውስጥ እግዚአብሔር በተገለጸበት በዚህ አይነት ገለጻ (portrayal) ቃልን መግለጹ ቃል እውነተኛ መለኮት መሆኑን በማያወላዳ ሁኔታ ያረጋግጣል። ማስረጃ፦
"አላወቅህምን? አልሰማህምን? እግዚአብሔር #የዘላለም_አምላክ፥ #የምድርም_ዳርቻ_ፈጣሪ_ነው፤ አይደክምም፥ አይታክትም፥ ማስተዋሉም አይመረመርም" (ኢሳ 40:28)
በዚህ ቦታ ላይ አምላካችን እግዚአብሔር የዘላለም አምላክና የምድር ዳርቻ ፈጣሪ መሆኑ ተነግሮ እንመለከታለን። "የዘላለም" መባሉ አምላካችን እግዚአብሔር ዘላለማዊ መሆኑን የሚያሳይ ሲሆን "አምላክ" መባሉ ደግሞ አምላክነቱን የሚገልጽ ነው። "የምድር ዳርቻ ፈጣሪ" መባሉ ደግሞ ፈጣሪነቱን የሚያመለክት ነው። ስለዚህ በአንድ አውድ ላይ የእግዚአብሔር ዘላለማዊነት፥ አምላክነትና ፈጣሪነት ተገልጿል። ይህ ማለት ዮሐ 1:1-3 ላይ ቃል የተገለጸበት ይህ አገላለጽ ኢሳ 40:28 ላይ እግዚአብሔር አምላክ የተገለጸበት ያው አገላለጽ ነው ማለት ነው። ይህ የቃልን እውነተኛ መለኮትነት በማያሻማ ሁኔታ ያረጋግጣል።
"24 እኔም እንዲህ አልሁ፤ #አምላኬ ሆይ፤ በዘመኔ እኵሌታ አትውሰደኝ፤ #ዘመናትህ_ከትውልድ_እስከ_ትውልድ ይኖራሉ። 25 #አንተ_ከጥንት_ምድርን_መሠረትህ፤ #ሰማያትም_የእጆችህ_ሥራ_ናቸው። 26 እነርሱ ይጠፋሉ፤ #አንተ_ግን_ጸንተህ_ትኖራለህ፤ ሁላቸው እንደ ልብስ ያረጃሉ፤ እንደ መጐናጸፊያም ትለውጣቸዋለህ፤ እነርሱም ወዲያ ይጣላሉ። 27 #አንተ_ግን_ያው_አንተ_ነህ፤ #ዓመቶችህም_ከቶ_አያልቁም" (መዝ 102:24-27)
በዚህ ቦታ ላይ የጌታ እግዚአብሔር አምላክነት፥ ፈጣሪነትና ዘላለማዊነት በአንድ አውድ ተገልጾ እንመለከታለን። በቁ.24 ላይ ጸሐፊው እግዚአብሔርን "አምላኬ" በማለት የእግዚአብሔርን አምላክነት ይናገራል። ከዚያም በቁ.25 ላይ "አንተ ከጥንት ምድርን መሠረትህ ሰማያትም የእጆችህ ስራ ናቸው" በማለት እግዚአብሔር አምላክ ፈጣሪ መሆኑን ይገልጻል። ከዚያም በቁ.26-27 ላይ ሰማይና ምድር ቢጠፉም እግዚአብሔር ግን እግዚአብሔር እንደሆነና ዓመታቱም ከቶ እንደማያልቁ በመናገር የእግዚአብሔርን ዘላለማዊነት ይናገራል።
ይህንኑ ሀሳብ በቁ.24 ላይ "ዘመናትህ ከትውልድ እስከ ትውልድ ይኖራሉ" በማለት የእግዚአብሔርን ዘላለማዊነት በድጋሚ ይገልጻል። በቁ.26 ላይም "አንተ ግን ጸንተህ ትኖራለህ" በማለት የእግዚአብሔርን ዘላለማዊ ሕልውና ይገልጻል። ስለዚህ በአንድ አውድ ላይ አምላክነቱ፥ ፈጣሪነቱና ዘላለማዊነቱ የተነገረለት እግዚአብሔር ነው ማለት ነው። ስለዚህ በዮሐ 1:1-3 ላይ ቃል የተገለጸበት አገላለጽ በመዝ 102:24-27 ላይ እግዚአብሔር የተገለጸበት አገላለጽ መሆኑን ከዚህ እንረዳለን። ይህ በማያሻማ ሁኔታ የቃልን እውነተኛ መለኮትነት ያረጋግጣል።
"10 እግዚአብሔር ግን #እውነተኛ_አምላክ ነው፤ እርሱም ሕያው አምላክና #የዘላለም_ንጉሥ_ነው፤ ከቍጣው የተነሣ ምድር ትንቀጠቀጣለች፤ አሕዛብም መዓቱን አይችሉም 11 እናንተም። ሰማይንና ምድርን ያልፈጠሩ እነዚህ አማልክት ከምድር ላይ ከሰማይም በታች ይጠፋሉ ትሉአቸዋላችሁ 12 #ምድርን_በኃይሉ_የፈጠረ፥ #ዓለሙን_በጥበቡ_የመሠረተ #ሰማያትንም_በማስተዋሉ_የዘረጋ እርሱ ነው" (ኤር 10:10-12)
በዚህ ቦታ ላይ ነቢዩ ኤርምያስ የእግዚአብሔርን አምላክነት፥ ዘላለማዊነትና ፈጣሪነት በአንድ አውድ ላይ ሲናገር እንመለከታለን። በቁ.10 ላይ እግዚአብሔር "እውነተኛ አምላክ ነው" በማለት የእግዚአብሔርን እውነተኛ አምላክነት ይናገራል። ከዚያ በዚያው ቁጥር ላይ "የዘላለም ንጉሥ ነው" በማለት ዘላለማዊነቱን ይገልጻል። ከዚያም ቁ.12 ላይ ወረድ ብሎ "ምድርን በኃይሉ የፈጠረ፥ ዓለሙን በጥበቡ የመሠረተ፥ ሰማያትንም በማስተዋሉ የዘረጋ" በማለት የእግዚአብሔርን ፈጣሪነት ይናገራል። ስለዚህ በአንድ አውድ የእግዚአብሔር አምላክነት፥ ዘላለማዊነትና ፈጣሪነት ተገልጿል። ይህ ማለት ዮሐ 1:1-3 ላይ ቃል የተገለጸበት አገላለጽ ኤር 10:10-12 ላይ እግዚአብሔር አምላክ የተገለጸበት ራሱ አገላለጽ ነው ማለት ነው። ይህ የቃልን እውነተኛ መለኮትነት በሚገባ ያሳያል።
"6 የእስራኤል ንጉሥ እግዚአብሔር፥ የሚቤዥም የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። #እኔ_ፊተኛ_ነኝ_እኔም_ኋለኛ_ነኝ፥ #ከእኔ_ሌላም_አምላክ_የለም 7 እንደ እኔ ያለ ማን ነው? ይነሣና ይጥራ ይናገርም፤ #ከጥንት_የፈጠርሁትን_ሕዝብ ያዘጋጅልኝ፥ የሚመጣውም ነገር ሳይደርስ ይንገሩኝ" (ኢሳ 44:6-7)
በዚህ ቦታ ላይ አምላካችን እግዚአብሔር በአንድ አውድ ላይ ዘላለማዊነቱን፥ አምላክነቱንና ፈጣሪነቱን ሲገልጽ እንመለከታለን። በቁ.6 ላይ "እኔ ፊተኛ ነኝ እኔም ኋለኛ ነኝ" በማለት ዘላለማዊነቱን ይገልጻል። ከዚያም በዚያው ቁጥር ላይ "ከእኔ ሌላም አምላክ የለም" በማለት አምላክነቱን ይናገራል። ከዚያም በቁ. 7 ላይ "ከጥንት የፈጠርሁትን ሕዝብ" በማለት ፈጣሪነቱን ይናገራል። ስለዚህ በአንድ አውድ ላይ ዘላለማዊነቱም፥ አምላክነቱም ፈጣሪነቱም ተገልጿል። ይህ ማለት በዮሐ 1:1-3 ላይ ቃል የተገለጸበት አገላለጽ አምላካችን እግዚአብሔር በኢሳ 44:6-7 የተገለጸበት ራሱ አገላለጽ ነው ማለት ነው። ይህ የቃልን እውነተኛ መለኮትነት በሚገባ ያረጋግጣል።
ምክንያቱም በብሉይ ኪዳን የሰብዓ ሊቃናቱ ትርጉም ላይ የእግዚአብሔር አምላክነት የተገለጸው በዚሁ መንገድ ነው፦
" #እግዚአብሔር_አምላክ_ነው፥ ለእኛም በራልን፤ እስከ መሠዊያው ቀንዶች ድረስ የበዓሉን መሥዋዕት በገመድ እሰሩት" (መዝ 118:27)
በዚህ መዝሙር ላይ እግዚአብሔር አምላክ እንደሆነ ተገልጾ እንመለከታለን። እግዚአብሔር አምላክ ነው ማለት በምንነት ደረጃ ወይም በባህርይው እግዚአብሔር ምንድነው የሚለውን ጥያቄ የሚመልስ ነው። እግዚአብሔር በባህርይው አምላክ ነው። በዚህ ቦታ ላይ "እግዚአብሔር" ተብሎ የተተረጎመው የዕብራይስጥ ቃል "יְהוָה/ያሕዌ" ሲሆን ጥቅም ላይ የዋለው ሳቢ (subject) ሆኖ ነው። ስም ስለሆነ (ዘጽ 15:3) ሳቢ ነው። "አምላክ" ተብሎ የተተረጎመው ቃል ደግሞ "אֵל/ኤል" ሲሆን ጥቅም ላይ የዋለው ገላጭ (predicate) ሆኖ ነው። የእግዚአብሔር ባህርይ ምን እንደሆነ ያመለክታል።
ይህ ራሱ ቃል በሰብዓ ሊቃናቱ ትርጉም ላይ እንዲሁ ይነበባል፦
" #θεὸς_κύριος καὶ ἐπέφανεν ἡμῖν συστήσασθε ἑορτὴν ἐν τοῖς πυκάζουσιν ἕως τῶν κεράτων τοῦ θυσιαστηρίου" (Psalms 118:27 LXX)
በሰብዓ ሊቃናቱ የግሪክ ትርጉም ላይ "እግዚአብሔር" ተብሎ የተተረጎመው የግሪክ ቃል "κύριος/ኪሪዮስ" ሲሆን ጥቅም ላይ የዋለው ሳቢ (subject) ሆኖ ነው። ስም ስለሆነ ውስን መስተጻምር ቢኖረውም ባይኖረውም ውስን መስተጻምር እንዳለው ወይም definite እንደሆነ ይቆጠራል። "አምላክ" ተብሎ የተተረጎመው የግሪክ ቃል ደግሞ "θεὸς/ቴኦስ" የሚለው ቃል ሲሆን ልክ እንደ ዮሐ 1:1 ጥቅም ላይ የዋለው ገላጭ (predicate) ሆኖ ሲሆን ውስን መስተጻምር (definite article) የለውም፥ የገባበትም case የnominative case ነው። እግዚአብሔር አምላክ መሆኑ የተገለጸው በዚህ የግሪክ ሰዋሰው አወቃቀር ነው።
✍️ ይህ ማለት ዮሐንስ 1:1 ላይ የቃል እግዚአብሔር መሆን የተገለጸው በመዝ 118:27 ላይ የራሱ የእግዚአብሔር አምላክነት በተገለጸበት በዚያው መንገድ ነው። የሁለቱም ክፍሎች ሰዋሰዋዊ አወቃቀር አንድ አይነት ነው። ይህ በማያሻማ ሁኔታ ቃል ወይም የእግዚአብሔር ልጅ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛው አምላክ መሆኑን ያረጋግጣል።
4) ሁሉ በእርሱ ሆነ
" #ሁሉ_በእርሱ_ሆነ፥ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም" (ዮሐ 1:3)
" #πάντα_δι_αὐτοῦ_ἐγένετο καὶ χωρὶς αὐτοῦ ἐγένετο οὐδὲ ἕν ὃ γέγονεν" (John 1:3 Greek)
ሐዋርያው ዮሐንስ በመንፈስ ቅዱስ ጥንሳሴ ቃል በመጀመሪያ እንደነበር፥ ከእግዚአብሔር ጋር እንደነበር ደግሞም በባህርይው እግዚአብሔር እንደነበር ከገለጸ በኋላ ሁሉ በእርሱ እንደሆነ ከሆነውም አንዳች ያለ እርሱ እንዳልሆነ ይናገራል። እንደ መጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ ሁሉን የፈጠረው እውነተኛው አምላክ ሲሆን (ኤር 10:16 ኤፌ 3:8-9) ቃል የሁሉ ፈጣሪ መባሉ እውነተኛው አምላክ መሆኑን ያሳያል። ከእግዚአብሔር በቀር ማንም ፍጥረትን አልፈጠረምና (ኤር 10:11) የቃል/ወልድ ፈጣሪነት በሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም የተረጋገጠ እውነት ነው (ዕብ 1:2 ዕብ 1:8-12 ቆላ 1:13-17 1ቆሮ 8:6)
በዮሐ 1:3 ላይ "በእርሱ" ተብሎ የተተረጎመው የግሪክ ቃል "δι αὐτοῦ/ዲ አውቱ" ሲሆን "ሆነ" ተብሎ የተተረጎመው የግሪክ ቃል ደግሞ "ἐγένετο/ኤጌኔቶ" የሚለው ቃል ነው። "ሁሉ" ተብሎ የተተረጎመው የግሪክ ቃል ደግሞ "πάντα/ፓንታ" የሚለው የግሪክ ቃል ነው። ይህ የቃልን ፈጣሪነት ለመግለጽ ጥቅም ላይ የዋለው የግሪክ ሰዋሰዋዊ አወቃቀር በሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች የአምላካችን እግዚአብሔርን ፈጣሪነት ለመግለጽ ጥቅም ላይ ውሏል፦
" #ሁሉ ከእርሱና #በእርሱ ለእርሱም #ነውና፤ ለእርሱ ለዘላለም ክብር ይሁን፤ አሜን" (ሮሜ 11:36)
"ὅτι ἐξ αὐτοῦ καὶ #δι_αὐτοῦ καὶ εἰς αὐτὸν #τὰ_πάντα· αὐτῷ ἡ δόξα εἰς τοὺς αἰῶνας ἀμήν" (Romans 11:36 Greek)
በዚህ ቦታ ላይ ሐዋርያው ጳውሎስ እግዚአብሔር አምላክ የሁሉ ፈጣሪ መሆኑን ሲገልጽ እንመለከታለን። እግዚአብሔር አማካሪ እንደማያስፈልገው በቁ.35 ላይ ከገለጸ በኋላ ሁሉ ከእርሱና በእርሱ ለእርሱም እንደሆነ በቁ.36 ላይ ይናገራል። ይህ ማለት የተፈጠረው ፍጥረት ሁሉ የተፈጠረው በእግዚአብሔር ነው ማለት ነው። "በእርሱ" የሚለው የግሪክ ሀረግ "δι αὐτοῦ/ዲ አውቱ" የሚለው ሀረግ ሲሆን "ሁሉ" ተብሎ የተተረጎመው የግሪክ ሀረግ ደግሞ "τὰ πάντα" የሚለው ሀረግ ነው። እነዚህ የእግዚአብሔርን ፈጣሪነት ለመግለጽ ጥቅም ላይ የዋሉት የግሪክ ሀረጋት ዮሐ 1:3 ላይ የቃልን ፈጣሪነት ለመግለጽ ጥቅም ላይ የዋሉ ሀረጋት ናቸው።
✍️ ይህ ማለት በዮሐ 1:3 ላይ የቃል ፈጣሪነት የተገለጸው ሮሜ 11:36 ላይ የራሱ የእግዚአብሔር ፈጣሪነት በተገለጸበት በዚያው ሰዋሰዋዊ አወቃቀር ነው። ይህ በማያሻማ ሁኔታ ቃል ወይም የአብ ልጅ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የፍጥረታት ሁሉ ፈጣሪ መሆኑን ያረጋግጣል። ከመለኮት በቀር ሌላ ፈጣሪ ካለመኖሩ ባሻገር የራሱ የአብ ፈጣሪነት በተገለጸበት አገላለጽ የልጁ ፈጣሪነት መገለጹ የሚያሳየው ይህንን ነውና።
▶️ ይቀጥላል
🚩 ዮሐንስ 1:1 እና የቃል ማንነት (ክፍል 1)
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት ማስረጃ ከሆኑት ክፍሎች እጅግ ታዋቂውና እጅግ ግልፅ የሆነው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ዮሐንስ 1:1 ነው። ይህ ክፍል የጌታ ኢየሱስን ዘላለማዊነት፥ ከአብ ጋር የነበረ መሆኑን፥ እግዚአብሔር መሆኑን ደግሞም የሁሉ ፈጣሪ መሆኑን በቀጥታ ይናገራል። ይህ እውነተኛ አምላክ መሆኑን በማያሻማ ሁኔታ ያረጋግጣል። በዚህም ምክንያት እጅግ ጥንታዊ ከሆኑት የቤተክርስቲያን አባቶች አንስቶ እስከ አሁኑ ዘመን በደረሰችው ቤተክርስቲያን ለክርስቶስ ኢየሱስ አምላክነት ተጠቅሷል።
ዛሬ እግዚአብሔር ቢፈቅድ ይህ ክፍል የጌታ ኢየሱስን አምላክነት እንዴት እንደሚያሳይ በይበልጥ ለመመልከት እንሞክራለን። ክፍሉ እነሆ፦
"በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ" (ዮሐ 1:1)
1) በመጀመሪያ ቃል ነበር
" #በመጀመሪያው_ቃል_ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ" (ዮሐ 1:1)
" #Ἐν_ἀρχῇ_ἦν_ὁ_λόγος καὶ ὁ λόγος ἦν πρὸς τὸν θεόν καὶ θεὸς ἦν ὁ λόγος" (John 1:1 Greek)
ሐዋርያው ዮሐንስ መልእክቱን የጀመረው "በመጀመሪያ ቃል ነበር" በማለት ነው። ስለዚህ በዚህ ክፍል መሰረት ቃል የነበረ እንጂ የሆነ አይደለም። በዚያው አውድ ላይ የተፈጠሩ ፍጡራንን የሆኑ ብሎ ሲገልጻቸው (ዮሐ 1:3) ቃልን ግን የነበረ እንደሆነ ገልጿል። ይህ ቃል ከፍጡራን ጋር እንደማይመደብ ያሳያል። ሐዋርያው ዮሐንስ ቃል በመጀመሪያ የነበረ መሆኑን የተናገረው ዘላለማዊ መሆኑን ለመግለጽ ነው። በዚህ ክፍል ላይ "መጀመሪያ" ተብሎ የተተረጎመው የግሪክ ቃል "ἀρχῇ/አርኼ" ሲሆን በብሉይ ኪዳን የራሱን የእግዚአብሔርን ዘላለማዊነትን ለማመልከት ጥቅም ላይ የዋለ ቃል ነው፦
" #ከጥንት_ጀምሮ_እኔ_ነኝ ከእጄም የሚያመልጥ የለም፤ እሠራለሁ፥ የሚከለክልስ ማን ነው?" (ኢሳ 43:13)
በዚህ ቦታ ላይ እግዚአብሔር አምላክ ስለ ራሱ ሕልውና ሲናገር "..ከጥንት ጀምሮ እኔ ነኝ" በማለት ይናገራል። እንደሚታወቀው እግዚአብሔር የዘላለም አምላክ ነው፥ ሕልውናውም ዘላለማዊ ነው (ዘዳ 33:27 መዝ 90:2 93:2) ስለዚህ "..ከጥንት ጀምሮ እኔ ነኝ" ሲል ዘላለማዊነቱን እየተናገረ እንደሆነ ግልጽ ነው። ይህ እጅግ ወሳኝ ነጥብ ነው። ምክንያቱም በኢሳ 43:13 ሰብዓ ሊቃናት ትርጉም ላይ "ከጥንት ጀምሮ" ተብሎ የተተረጎመው የግሪክ ቃል ዮሐ 1:1 ላይ "መጀመሪያ" ተብሎ የተተረጎመው "ἀρχῇ/አርኼ" የሚለው ራሱ ቃል ነው፦
"ἔτι ἀπ᾽ #ἀρχῆς καὶ οὐκ ἔστιν ὁ ἐκ τῶν χειρῶν μου ἐξαιρούμενος ποιήσω καὶ τίς ἀποστρέψει αὐτό" (Isaiah 43:13 LXX)
✍️ ይህ ማለት በዮሐንስ 1:1 ላይ ሐዋርያው ዮሐንስ በመንፈስ ቅዱስ ጥንሳሴ የቃልን ዘላለማዊ ሕልውና የገለጸው እግዚአብሔር አምላክ በብሉይ ኪዳን የራሱን ዘላለማዊ ሕልውና በገለጸበት በዚያው መንገድ ነው። ይህ ቃል ወይም የእግዚአብሔር ልጅ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘላለማዊ ሕልውና እንዳለው በማያሻማ ሁኔታ ያረጋግጣል።
2) ቃልም እግዚአብሔር ነበር
"በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ #ቃልም_በእግዚአብሔር_ዘንድ_ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ" (ዮሐ 1:1)
"Ἐν ἀρχῇ ἦν ὁ λόγος καὶ #ὁ_λόγος_ἦν_πρὸς_τὸν_θεόν καὶ θεὸς ἦν ὁ λόγος" (John 1:1 Greek)
በመንፈስ ቅዱስ ጥንሳሴ የቃልን ዘላለማዊ ሕልውና ከገለጸ በኋላ ሐዋርያው ዮሐንስ ቃል ከእግዚአብሔር ጋር እንደነበር ይናገራል። ይህ ማለት ቃል/ወልድ ከእግዚአብሔር/ከአብ ጋር ነበር ማለት ነው። ይህ እውነት በወንጌል ላይ በራሱ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የተገለጸ ሲሆን (ዮሐ 17:5) በእርሱና በአባቱ መካከል የነበረውን ዘላለማዊ አብሮነት ያመለክታል። እንደሚታወቀው መለኮት መንፈስ ነው (ዮሐ 4:23-24 1ቆሮ 15:45) በቦታ አይወሰንም (ኤር 23:23-24 መዝ 139:8) ስለዚህ ቃል/ጌታ ኢየሱስ ከእግዚአብሔር ጋር ነበር ሲባል በቦታ ባልተገደበ፥ መንፈስ በሆነ አኳሃን ነው ማለት ነው። ከዚህም ባሻገር ግን ቃል ከእግዚአብሔር ጋር መሆኑ መለኮት መሆኑን ያረጋግጣል።
ምክንያቱም እግዚአብሔር ዘላለማዊ ነው (ዕን 1:12) ስለዚህ ቃል ከእግዚአብሔር ጋር ነበር ማለት ከእርሱ ጋር የነበረው ለዘላለም ነው ማለት ነው። ፍጡራን ግን ከእግዚአብሔር ጋር አልነበሩም፦
"ከማኅፀን የሠራህ፥ የሚቤዥህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። ሁሉን የፈጠርሁ፥ ሰማያትን ለብቻዬ የዘረጋሁ ምድርንም ያጸናሁ እግዚአብሔር እኔ ነኝ፤ #ከእኔ_ጋር_ማን_ነበረ?" (ኢሳ 44:24)
በዚህ ቦታ ላይ እግዚአብሔር አምላክ ሰማይና ምድርን ሲፈጥር ከእርሱ ጋር ማንም እንዳልነበር ሲናገር እንመለከታለን። እግዚአብሔር በአውዱ እየተናገረ የነበረው ስለ ሀሰተኛ አማልክት ነው (ኢሳ 44:9-23) ስለዚህ ከእውነተኛው አምላክ ውጪ ያሉ የትኛውም ፍጡራን (ጣዖታትን ጨምሮ) ከእግዚአብሔር ጋር አልነበሩም። ይህ ፍጡራን ከዘላለም ጀምሮ ከእግዚአብሔር ጋር እንዳልነበሩ ያሳያል።
"ምድርን በመሠረትሁ ጊዜ #አንተ_ወዴት_ነበርህ? ታስተውል እንደ ሆንህ ተናገር" (ኢዮ 38:4)
በዚህ ቦታ ላይ እግዚአብሔር አምላክ ኢዮብን ሲጠይቀው እንመለከታለን። ምድርን በመሠረትሁ ጊዜ አንተ ወዴት ነበርህ ይለዋል። ይህ ማለት ኢዮብ እግዚአብሔር አምላክ ምድርን ሲመሠርት አብሮት አልነበረም ማለት ነው። ኢዮብ ፍጡር ስለነበር እግዚአብሔር ፍጥረታትን ሲፈጥር ከእርሱ ጋር አብሮ አልነበረም። ይህ ፍጡራን ከእግዚአብሔር ጋር ከዘላለም ጀምሮ እንዳልነበሩ ያሳያል።
✍️ በዮሐንስ 1:1 ላይ ግን ቃል ከዘላለማዊው እግዚአብሔር ጋር ነበር ተብሎለታል። ይህ ማለት ቃል እንደ ፍጡራን ከእግዚአብሔር ጋር ያልነበረ አይደለም ማለት ነው። ከእግዚአብሔር ጋር የነበረ ነው። ስለዚህ ይህ ክፍል ከአባቱ ከእግዚአብሔር ጋር በባህርይ አንድነት (ፊል 2:6 ዘጽ 23:21) ከዘላለም ጀምሮ የነበረው ዘላለማዊው መለኮት መሆኑን ያረጋግጣል። ዘላለማዊ የሆነው መለኮት ነውና።
3) ቃልም እግዚአብሔር ነበር
"በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ #ቃልም_እግዚአብሔር_ነበረ" (ዮሐ 1:1)
"Ἐν ἀρχῇ ἦν ὁ λόγος καὶ ὁ λόγος ἦν πρὸς τὸν θεόν #καὶ_θεὸς_ἦν_ὁ_λόγος" (John 1:1 Greek)
ሐዋርያው ዮሐንስ ቃል በመጀመሪያ እንደነበር፥ ከእግዚአብሔር ወይም ከአብ ጋር እንደነበር ከገለጸ በኋላ ቃል ራሱ እግዚአብሔር እንደነበር በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ይናገራል። ቃልም እግዚአብሔር ነበር ማለት ቃል በምንነት ደረጃ መለኮት፥ አምላክ፥ እግዚአብሔር እንደሆነ የሚያመለክት ነው። ቃል ምንድነው የሚለውን ጥያቄ የሚመልስ ነው። ቃል በባህርይው እግዚአብሔር ነበር። በዚህ ቦታ ላይ "እግዚአብሔር" ወይም "θεὸς/ቴኦስ" የሚለው የግሪክ ቃል ገላጭ (predicate) ሆኖ ሲሆን የገባው ውስን መስተጻምር (definite article) የለውም። የገባውም በnominative case ነው። ይህ እጅግ ወሳኝ ነጥብ ነው።
🚩 የሰው ልጅ እንደ አብ?
ለኦንሊ ጂሰሱ ቄስ የሀሰት ትምህርት የተሰጠ ምላሽ
https://vt.tiktok.com/ZSxSYY9pT/
🚩 1ጢሞ 3:15-16 ስለ ማን ነው?
ለኦንሊ ጂሰሱ ቄስ የሀሰት ትምህርት የተሰጠ ምላሽ
https://vt.tiktok.com/ZSxNt7rg1/
🚩 የእግዚአብሔር ልጅ በስጋ መጥቷል!
ለኦንሊ ጂሰሱ ቄስ የሀሰት ትምህርት የተሰጠ ምላሽ
https://vt.tiktok.com/ZS9EpK9jD/
ሐ) ምስጋና
"አቤቱ አምላኬ #ለዘላለም_አመሰግንሃለሁ" (መዝ 30:12)
"ሁልጊዜ በእግዚአብሔር እንከብራለን፥ ስምህንም #ለዘላለም_እናመሰግናለን" (መዝ 44:8)
"በቤትህ የሚኖሩ ሁሉ የተመሰገኑ ናቸው፤ #ለዓለምና_ለዘላለምም_ያመሰግኑሃል" (መዝ 84:4)
"ብቻውን አምላክ ለሚሆን ለማይጠፋው ለማይታየውም ለዘመናት ንጉሥ #ምስጋናና ክብር እስከ #ዘላለም ድረስ #ይሁን፤ አሜን" (1ጢሞ 1:17)
መ) ኃይል
"ብቻውን ለሆነ አምላክና መድኃኒታችን ከዘመን ሁሉ በፊት አሁንም #እስከ_ዘላለምም ድረስ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ክብርና ግርማ #ኃይልም ሥልጣንም ይሁን፤ አሜን" (ይሁዳ 1:25)
"አሜን፥ በረከትና ክብር ጥበብም ምስጋናም ውዳሴም #ኃይልም ብርታትም #ከዘላለም_እስከ_ዘላለም ድረስ ለአምላካችን ይሁን፤ አሜን አሉ" (ራዕ 7:12)
▶️ የትኛውም ፍጡር ዘላለማዊ የሆነ በረከት፥ ክብር፥ ምስጋናና ኃይል attribute አልተደረገለትም። ዘላለማዊ በሆነ አኳሃን ማለትም ፍጻሜ በሌለው መንገድ እነዚህ ነገሮች የሚባሉት ለእግዚአብሔር ብቻ ነው። በራዕይ 5:13 ለእግዚአብሔርና ለልጁ ለኢየሱስ የቀረበው doxology በሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ለእግዚአብሔር የቀረበ አምልኮ በመሆኑ፥ አምልኮ መሆኑን እንረዳለን።
3) በራዕይ 5:13 የቀረበው doxology "ላትሬኦ/λατρεύω" ተብሏል
በራዕይ መጽሐፍ ውስጥ ራዕይ 5:13 ላይ ካለው doxology ጋር አንድ አይነት የሆነ ሌላ doxology እንመለከታለን፦
"9፤ ከዚህ በኋላ አየሁ፥ እነሆም፥ አንድ እንኳ ሊቆጥራቸው የማይችል ከሕዝብና ከነገድ ከወገንም ከቋንቋም ሁሉ እጅግ ብዙ ሰዎች ነበሩ፤ #ነጭ_ልብስም_ለብሰው የዘንባባንም ዝንጣፊዎች በእጆቻቸው ይዘው በዙፋኑና በበጉ ፊት ቆሙ፤ 10፤ በታላቅም ድምፅ እየጮሁ። በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለአምላካችንና ለበጉ ማዳን ነው አሉ። 11፤ መላእክቱም ሁሉ በዙፋኑና በሽማግሌዎቹ በአራቱም እንስሶቹ ዙሪያ ቆመው ነበር፤ በዙፋኑም ፊት በግምባራቸው ተደፉ፥ ለእግዚአብሔርም እየሰገዱ። 12፤ አሜን #በረከትና_ክብር_ጥበብም_ምስጋናም_ውዳሴም_ኃይልም ብርታትም #ከዘላለም_እስከ_ዘላለም ድረስ ለአምላካችን ይሁን፤ አሜን አሉ" (ራዕ 7:9-12)
✍️ በዚህ ስፍራ ሐዋርያው ዮሐንስ በራዕዩ ማንም ሊቆጥራቸው የማይችልን ነጭ ልብስ የለሰቡ ሰዎችን ያያል። እነዚህም ሰዎች ለእግዚአብሔር እየሰገዱ "በረከትና ክብር ጥበብም ምስጋናም ውዳሴም ኃይልም ብርታትም ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ አምላካችን ይሁን አሜን" በማለት እግዚአብሔርን ያመልካሉ።
በራዕይ 7:12 ላይ እነዚህ የተዋጁ ነፍሳት እያቀረቡ ያሉት doxology በራዕይ 5:13 ፍጥረት ሁሉ ለአብና ለወልድ ካቀረቡት doxology ጋር አንድ አይነት ነው። አወቃቀሩ፥ ጥቅም ላይ የዋሉት ቃላት፥ መልእክቱና አላማው ሁሉ አንድ አይነት ነው።
♦️ በጣም በሚያስገርም ሁኔታ በራዕይ 7:12 ላይ ያለው doxology አምልኮ ወይንም "ላትሬኦ/λατρεύω" ተብሏል!
በራዕይ 7:9-12 ላይ የምንመለከታቸው፥ ነጭ የለበሱና ማንም ሊቆጥራቸው የማይችል ሰዎች ያቀረቡት doxology አምልኮ ተብሏል፦
"13 ከሽማግሌዎቹም አንዱ ተመልሶ። እነዚህ #ነጩን_ልብስ_የለበሱ እነማን ናቸው? ከወዴትስ መጡ? አለኝ። 14 እኔም። ጌታ ሆይ፥ አንተ ታውቃለህ አልሁት። አለኝም። እነዚህ ከታላቁ መከራ የመጡ ናቸው፥ ልብሳቸውንም አጥበው በበጉ ደም አነጹ። 15 ስለዚህ በእግዚአብሔር ዙፋን ፊት አሉ፥ ሌሊትና ቀንም በመቅደሱ #ያመልኩታል፥ በዙፋኑም ላይ የተቀመጠው በእነርሱ ላይ ያድርባቸዋል" (ራዕ 7:13-15)
▶️ ሐዋርያው ዮሐንስ ነጭ የለበሱት የተዋጁ ሰዎች ለእግዚአብሔር doxology ሲያቀርቡ ካየ በኋላ ከሀያ አራቱ ሽማግሌዎች አንዱ ነጭ የለበሱት እንደማን እንደሆኑ ይጠይቀዋል። ዮሐንስም እንደማያውቅ ይነግረዋል። ከዚያም ሽማግሌው እነዚህ ሰዎች ከታላቁ መከራ እንደመጡ፥ ልብሳቸውን በበጉ እንዳነጹ፥ በእግዚአብሔር ዙፋን ፊት እንዳሉና ሌሊትና ቀንም በመቅደሱ እንደሚያመልኩት ይነግረዋል።
👉 ስለዚህ እነዚህ ሰዎች እግዚአብሔርን የሚያመልኩ ሰዎች ናቸው ማለት ነው። አምልኳቸው ምን አይነት ነው?
የእነዚህ ሰዎች አምልኮ በራዕ 7:12 ላይ የምንመለከተው doxology ነው! በዚያ ክፍል ላይ ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት እየሰገዱ ያቀረቡት doxology ነው በራዕ 7:15 ላይ አምልኮ የተባለው። በቁ.9 ላይ ነጭ ልብስ እንደለበሱ የተነገረላቸው ሰዎች ራሳቸው ሰዎች እንደሆኑ "ነጭ ልብስ የለበሱ እነማን ናቸው" በማለት በቁ.13 ላይ ተረጋግጧል፥ ከዚያ ባሻገርም እነርሱ ራሳቸው ሰዎች እግዚአብሔርን እንደሚያመልኩ በቁ.15 ላይ ተገልጿል። ስለዚህ ይህ አምልኳቸው ምንድነው ከተባለ በቁ.12 ላይ ያቀረቡት doxology ነው።
ያመልኩታል ሲባል ከዘላለም እስከ ዘላለም በረከትና ክብር ጥበብም ምስጋናም ውዳሴም ኃይልም ብርታትም ለእግዚአብሔር ይሁን በማለት እነዚህን ነገሮች ለእግዚአብሔር attribute ያደርጋሉ ማለት ነው። ወይም እነዚህ ባህርያት የእግዚአብሔር መሆናቸውን ይናገራሉ።
✏️ እንደ መጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ አምልኮ attribution ነው። መለኮታዊ ባህርያትን መስጠት፥ ወይም አንድ አካል እነዚያ መለኮታዊ ባህርያት እንዳሉት መናገር ነው። ለምሳሌ፦
"3 የእግዚአብሔርን ስም እጠራለሁና፤ #ለአምላካችን ታላቅነትን #ስጡ" (ዘዳ 32:3)
ለእግዚአብሔር ታላቅነትን ስጡ ማለት ይህን መለኮታዊ ባህርይ ለእርሱ attribute አድርጉ፥ ይህ ባህርይ የእርሱ እንደሆነ ተናገሩ ማለት ነው። ታላቅነት የእግዚአብሔር ባህርይ መሆኑ በተደጋጋሚ ተነግሯል (ዘዳ 11:2 ዘዳ 3:24 ዘዳ 5:24) ስለዚህ ታላቅነትን ስጡ ማለት ይህን ባህርይ ለእርሱ ascribe አድርጉ ማለት ነው።
"3 Because I will publish the name of the LORD: #ascribe ye greatness unto our #God." (Deut 32:3)
ስለዚህ በራዕይ 7:9-15 የምናያቸው ሰዎች ከላይ የተዘረዘሩትን ባህርያት ለእግዚአብሔር attribute ሲያደርጉ እያመለኩ ነው። የአምልኮ ትርጉም ይህ ነውና። በራዕይ 7:15 ቃል በቃል ይህ ራሱ ተግባር "ያመልካሉ" በመባል "አምልኮ" ተብሎ የተጠራው ለዚያ ነው። በራዕ 7:15 ላይ "ያመልካሉ" የሚለው የግሪክ ቃል "ላትሬኦ/λατρεύω" የሚለው ቃል ሲሆን ይህ ቃል የራሱ የእግዚአብሔርን አምልኮ ያመለክታል (ማቴ 4:10)
♦️ ነገር ግን በራዕይ 7:15 "አምልኮ" ተብሎ የተጠራው የራዕይ 7:12 doxology በራዕይ 5:13 ከሚገኘው doxology ጋር ፍጹም አንድ አይነት ነው!
በራዕይ 5:13 እና በራዕይ 7:12 በሚገኙት doxologies መካከል የአወቃቀር፥ የቃላት፥ የመልእክት የአላማ ልዩነት የለም። ፍጹም አንድ አይነት ናቸው። ስለዚህ ልክ እንደ ራዕይ 7:12 doxology የራዕይ 5:13 doxologyም አምልኮ ወይም "ላትሬኦ/λατρεύω" ነው ማለት ነው። "ላትሬኦ/λατρεύω" ከተባለው የራዕይ 7:12 doxology ጋር ፍጹም አንድ አይነት ነውና። ይህ ከምንም በላይ በራዕይ 5:13 ክርስቶስ ከአባቱ ጋር በአንድነት "ላትሬኦ/λατρεύω" ወይንም አምልኮ እንደተቀበለ የሚያረጋግጥ ተጨባጭ ማስረጃ ነው። ስለዚህ ጌታ ኢየሱስ በፍጥረት ሁሉ ለዘላለም የሚመለከው አምላክ ነው! ይህን መለኮት የሆነውን ጌታ ያላወቃችሁ ታውቁት ዘንድ ጸሎታችን ነው!
ጌታ ይርዳን!
🚩 ጌታ ኢየሱስ፦ በፍጥረት ሁሉ ለዘለዓለም የሚመለከው አምላክ
መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምልኮ የሚገባው መለኮት መሆኑን በስፋት ያስተምራል። የእግዚአብሔር ቃል አስተምህሮ ወልድ አምላክ እንደሆነ (ዕብ 1:8 ዮሐ 1:1 1ዮሐ 5:20) ከአባቱ ከእግዚአብሔር አብ ጋር በመለኮታዊ ባህርይ አንድ እንደሆነ (ዮሐ 10:27-30 ፊል 2:6 ዕብ 1:3) ዓለም ሳይፈጠር እንደነበር (ዮሐ 17:5 ዕብ 1:2) ዘላለማዊ እንደሆነ (ራዕ 1:17-18 ራዕ 22:13-16) የሁሉ ፈጣሪ እንደሆነ (ዮሐ 1:3 ቆላ 1:13-17 1ቆሮ 8:6 ዕብ 1:8-12 ዕብ 1:2) በሁሉ ስፍራ እንደሚገኝ (ማቴ 18:19-20 ዮሐ 3:13 ኤፌ 4:10 ራዕ 1:13/20) መንፈስ እንደሆነ (1ቆሮ 15:45 2ቆሮ 3:14-18) በኋላም ጊዜው በደረሰ ጊዜ ሰው ሆኖ እንደመጣ (ዮሐ 1:14 ሮሜ 8:3 ዕብ 2:11-14) ያስተምራል።
ይህ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ እውነተኛ መለኮት መሆኑን በሚገባ ያሳያል። እንደ መጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ ክርስቶስ ኢየሱስ እውነተኛ መለኮት ከሆነ አምልኮ ይገባዋል ማለት ነው። ስለዚህ በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ ጌታ ኢየሱስ ሲመለክ ማየት አለብን ማለት ነው። ለእውነተኛ አምላክ አምልኮ ስለሚቀርብ ማለት ነው። ዛሬ እግዚአብሔር ቢፈቅድ የእግዚአብሔር ልጅ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በፍጥረት ሁሉ የተመለከበትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ለመመልከት የምንሞክር ይሆናል።
ክፍሉ እነሆ፦
" #በሰማይና_በምድርም_ከምድርም_በታች_በባሕርም ላይ ያለ #ፍጥረት_ሁሉ #በእነርሱም_ውስጥ_ያለ_ሁሉ። #በረከትና_ክብር_ምስጋናም_ኃይልም_ከዘላለም_እስከ_ዘላለም #በዙፋኑ_ላይ_ለተቀመጠው፥ #ለበጉም ይሁን ሲሉ ሰማሁ" (ራዕይ 5:13)
በዚህ ቦታ ላይ ሐዋርያው ዮሐንስ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበለውን ራዕይ (ራዕ 1:1) ማየቱን እናነባለን። በዚህ ራዕይ በጉ ማኅተሙን በዙፋኑ ላይ ከተቀመጠው እጅ ከተቀበለ በኋላ (ራዕ 5:7) አራቱ እንስሳት፥ ሀያ አራቱ ሽማግሌዎችና መላእክት ታርዶ ሰዎችን በመዋጀቱ ምክንያት ሲያመሰግኑት (ራዕ 5:8-12) ከሰማ በኋላ በሰማይም በምድርም ከምድርም በታች በባህርም ውስጥ ያለ ፍጥረት ሁሉ በእነርሱም ውስጥ ያለ ፍጥረት ሁሉ በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለበጉም በረከትና ክብር ምስጋናም ኃይልም ከዘላለም እስከ ዘላለም ይሁን ሲሉ በቁ.13 ላይ ይሰማል።
በዙፋኑ ላይ የተቀመጠው የጌታ ኢየሱስ አባት እግዚአብሔር አብ ሲሆን (ማቴ 23:22 መዝ 103:19) በጉ የተባለው ደግሞ የእግዚአብሔር ልጅ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው (ዮሐ 1:29) ቀጥለን በማስረጃ እንደምንመለከተው በራዕይ 5:13 ላይ ለእግዚአብሔርና ለልጁ ለኢየሱስ የቀረበው ይህ doxology አምላክ ላልሆነ አካል ፈጽሞ ሊቀርብ የማይችል ለመለኮት ብቻ ሊቀርብ የሚችል እውነተኛ አምልኮ ነው። ነጥብ በነጥብ እንመልከተው፦
1) ከፍጥረት ሁሉ የቀረበ doxology ነው
በራዕይ 5:13 ላይ እንደምናነበው ለእግዚአብሔርና ለልጁ ለክርስቶስ ኢየሱስ "በረከት፥ ክብር፥ ምስጋናም ኃይልም ከዘላለም እስከ ዘላለም ይሁን" ያለው ፍጥረት ሁሉ ነው። ሐዋርያው ዮሐንስ ይህን ያለው ፍጥረት ሁሉ መሆኑን ምንም በማያሻማ ሁኔታ ለማመልከት " #በሰማይና_በምድር_ከምድርም_በታች_በባሕርም_ላይ_ያለ_ፍጥረት_ሁሉ_በእነርሱም_ውስጥ_ያለ_ሁሉ" ብሏል። ይህ ማለት የቀረ ፍጥረት የለም ማለት ነው። በሁሉፍ ስፍራ ያለ ፍጥረት ሁሉ ነው ለእግዚአብሔርና ለልጁ ይህን doxology ያቀረበው
✍️ እንደ መጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ በፍጥረት ሁሉ የሚመሰገነው ማነው?
እንደ መጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ በፍጥረት ሁሉ የሚመሰገነው እግዚአብሔር ብቻ ነው። ፍጡር በፍጥረት ሁሉ የተመሰገነበት አንድም አጋጣሚ የለም፦
" #ሰማይና_ምድር_ባሕርም #በእርስዋም_የሚንቀሳቀስ_ሁሉ #ያመሰግኑታል" (መዝ 69:34)
" #ፍጥረቶቹ_ሁሉ በግዛቱ ስፍራ ሁሉ፥ #እግዚአብሔርን_ባርኩ። ነፍሴ ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኪ" (መዝ 103:22)
"አቤቱ፥ #ሥራህ_ሁሉ_ያመሰግኑሃል፥ ቅዱሳንህም ይባርኩሃል" (መዝ 145:10)
" #እስትንፋስ ያለው #ሁሉ እግዚአብሔርን #ያመስግን። ሃሌ ሉያ" (መዝ 150:6)
▶️ ከዚህ በተጨማሪም #በመዝሙር_148 ላይም በመላው ፍጥረት የሚመሰገነው እግዚአብሔር መሆኑ ተገልጿል።
በመላእክት ሰራዊት ሁሉ (መዝ 148:2) በጸሐይና ጨረቃ በኳክብትና ብርሃን (መዝ 148:3) በሰማየ ሰማያት፥ ከሰማያት በላይ ባለው ውኃ (መዝ 148:4) በእባቦችና ጥልቆች (መዝ 148:7) በእሳትና በረዶ በአመዳይና ውርጭ ቃሉን በሚያደርግ ዓውሎ ንፋስ (መዝ 148:8) በተራሮችና ኮረብቶች ሁሉ በሚያፈራም ዛፍ ዝግባም ሁሉ (መዝ 148:9) በአራዊትና በእንስሳትም ሁሉ በተንቀሳቃሾችም በሚበርሩ ወፎችም ሁሉ (መዝ 148:10) በምድር ነገሥታት አሕዛብም ሁሉ በአለቆችና በምድር ፈራጆች ሁሉ (መዝ 148:11) በጎልማሶችና ቆነጃጅቶች በሽማግሌዎችና በልጆች (መዝ 148:12) የሚመሰገነው እግዚአብሔር ነው። ምስጋናውም በሰማይና በምድር የሞላው እርሱ ነው (መዝ 148:13) ይህ መዝሙር አንድ ያልጠቀሰው የፍጥረት ወገን የለም
👉 ስለዚህ በተፈጠረው ፍጥረት ሁሉ የሚመሰገነው እግዚአብሔር ብቻ ነው ማለት ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ #አንድም ፍጡር በፍጥረት ሁሉ የተመሰገነ የለም። ከተፈጠረው ፍጥረት ሁሉ የሚቀርብ ምስጋና አምልኮ መሆኑን ከዚህ እንረዳለን። ስለዚህ በራዕይ 5:13 ለእግዚአብሔርና ለልጁ የቀረበው አምልኮ መሆኑን ከዚህ እንረዳለን። በፍጥረት ሁሉ የቀረበ ነውና
2) ዘላለማዊ doxology ነው
በራዕይ 5:13 ለእግዚአብሔርና ለልጁ ለኢየሱስ ክርስቶስ በአንድነት የቀረበው doxology አምልኮ እንደሆነ የምንረዳበት ሌላው መንገድ የተባሉት ነገሮች በሙሉ ዘላለማዊ መሆናቸው ነው። ሐዋርያው ዮሐንስ ሰምቶ እንደዘገበው ፍጥረት ሁሉ "በረከት፥ ክብር፥ ምስጋናም ኃይልም #ከዘላለም_እስከ_ዘላለም_ይሁን" ነበር ያለው።
✍️ ዘላለማዊ በረከት፥ ክብር፥ ምስጋናና ኃይል የማን ነው?
እንደ መጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ ለዘላለም በረከት፥ ክብር፥ ምስጋናና ኃይል የእግዚአብሔር ብቻ ነው። ዘላለማዊ በረከት፥ ክብር፥ ምስጋናና ኃይል ለፍጡር የተሰጠበት አንድም አጋጣሚ የለም፦
ሀ) በረከት
" #ከዘላለም_እስከ_ዘላለም የእስራኤል አምላክ እግዚአሔር #ይባረክ። አሜን አሜን" (መዝ 41:13)
"እግዚአብሔር #ለዘላለም_ይባረክ። ይሁን ይሁን" (መዝ 89:52)
" #ከዘላለም_እስከ_ዘላለም የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር #ይባረክ ሕዝብም ሁሉ አሜን ይበል። ሃሌ ሉያ" (መዝ 106:48)
"ይህም የእግዚአብሔርን እውነት በውሸት ስለ ለወጡ በፈጣሪም ፈንታ የተፈጠረውን ስላመለኩና ስላገለገሉ ነው፤ እርሱም #ለዘላለም_የተባረከ ነው፤ አሜን" (ሮሜ 1:25)
ለ) ክብር
"ሁሉ ከእርሱና በእርሱ ለእርሱም ነውና፤ ለእርሱ #ለዘላለም_ክብር ይሁን፤ አሜን" (ሮሜ 11:36)
"ለአብ #ከዘላለም_እስከ_ዘላለም #ክብር ይሁን፤ አሜን" (ገላ 1:5)
"ለእርሱ በቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ ኢየሱስ እስከ ትውልዶች ሁሉ #ከዘላለም_እስከ_ዘላለም #ክብር ይሁን፤ አሜን" (ኤፌ 3:21)
"ለአምላካችንና ለአባታችንም #እስከ_ዘላለም ድረስ #ክብር ይሁን፤ አሜን" (ፊል 4:20)
🚩 በዮሐንስ 1:1 የግሪክ አተረጓጎም ላይ ለዋሸው ኡስታዝ የተሰጠ መልስ (ክፍል 3)
https://vt.tiktok.com/ZS9bm1Fuc/
现已上线!2025 年 Telegram 研究 — 年度关键洞察 
