ar
Feedback
ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

الذهاب إلى القناة على Telegram

ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።

إظهار المزيد
637
المشتركون
لا توجد بيانات24 ساعات
-37 أيام
-1230 أيام
أرشيف المشاركات
❤ ከዚህም በኋላ ጋውር ከሚባል አገር ዳርቻ ደርሶ በዚያ ተቀመጠ የተመሰገነ የሰማዕታት ፍጻሜ የሆነ የሊቀ ጳጳሳት ጴጥሮስ በዓሉ በደረሰ ጊዜ የቊርባንን ቅዳሴ ሠራ ቅዱስ ጴጥሮስም ተገለጸለትና "ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደርሱ ትመጣ ዘንድ ይጠራሃል" አለው። ከዚችም ቀን ወዲህ የዕረፍቱ ጊዜ እንደ ደረሰ አውቆ ሕዝቡን ጠራቸውና በቀናች ሃይማኖት እንዲጸኑ አዘዛቸው ከዚህም በኋላ እጆቹን ዘርግቶ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ጴጥሮስ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑረሰ ለዘላለሙ አሜን።                               ✝ ✝ ✝ ❤ #አባ_ዮሐንስ፦ ይህም አባት ለእስክድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት ሠለሳኛ ነው። ይህም የከበረ ቀሲስ የሆነ የገምኑደመ ሰው ነው በዘመኑም የቅዱሳን ሰማዕታት የሰርጊስና የባኮስ ቤተ ክርስቲያናቸው ተሠራች ዳግመኛም የአቡቂርና የዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን በምስር መሰብሰቢያ ቅጽር አጠገብ ተሠራች ያነጻቸውሜ ስሙ እንድርያስ የሚባል እግዚአብሔርን የሚፈራ ያዕቆባዊ አንድ የግብጽ ሰው ነው። እርሱም ለመርዋን ልጅ ለገዢው ንጉሥ አብደል ጸሐፊው ነው። ❤ ይህም አባ ዮሐንስ የወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስን ቤተ ክርስቲያን በእስክንድርያ አገር በታወቀ ቃምስ በሚባል ቦታ የሠራ ነው። በዚህ በንጉሥ አብደል ዘመንም ሦስት ዓመት ያህል ጽኑ ረኃብ ሆነ ይህም አባት ለድኆች ለጦም አዳሪዎችና ለችግረኞች የሚያስብ ሆነ በየሳምንቱም አራት ጊዜ ወርቅና ብር እንጀራም ይሰጣቸዋል አብዝቶ የሚራራ መመጽወትን የሚወድ በጎ ሥራዎችን የሚሠራ ነውና። በዘመኑም ንጉሥ ይዜድ ሙቶ በርሱ ፈንታ መርዋን ነገሠ ይህም አባት በቅዱስ ማርቆስ ወንበር ዘጠኝ ዓመት ኖረ በዚች ቀንም በሰላምም ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ዮሐንስ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                              ✝ ✝ ✝ ❤ #አባ_አትናቴዎስ፦ እርሱም ጳውሎስ የተባለ የቂስ መክረም ልጅ የከሊል ልጅ ነው። እርሱም ለእስክንድርያ አገር ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሰባ ስድስተኛ ነው። ምንጭ፦ የታኅሣሥ1 ስንክሳር።                              ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለናቡቴ_በፍቅረ_አሐቲ_ዐፀዱ። ለንጉሥ አክዓብ ሶበ ኢተአዘዘ ለፈቃዱ። እስከ አቅተሎ በግፍዕ እስመ ከመዝ ልማዱ። አጽርዓት ግፍዐ ደሙ በፍትሐ ፈጣሪ አሐዱ። መንግሥተ ምልክና እምኵሉ ትዝምዱ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የታኅሣሥ_1።                               ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "እስመ ቅንዐተ ቤትከ በልዐኒ። ትዕይርቶሙ ለእለ ይትዔየሩከ ወድቀ ላዕሌየ። ወቀጻዕክዎ በጾም ለነፍስየ"። መዝ68፥9-10። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ9፥47-56።                            ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወገሠፀ ነገሥተ በእንቲአሆሙ። ወኢትግሥሡ መሲሐንየ። ወኢትሕስሙ ዲበ ነቢያትየ"። መዝ 104፥14-15። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 11፥1-13፣ ያዕ 5፥16-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 3፥19-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 4፥25-33። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም የነቢዩ የቅዱስ ኤልያስ የልደት በዓልና የጾም ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።                  

❤ "በስመ አብ  ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤ ❤ #የተባረከ_የታኅሣሥ_ወር_የቀኑ_ሰዓት_ዘጠኝ ሲሆን ከእንግዲህም ይጨምራል።             ❤ #ታኅሣሥ ፩ (1) ቀን ❤ እንኳን #ለርእሰ_ባሕታዊ_ለታላቁ_ነቢይ ለቴስብያዊ #ለቅዱስ_ኤልያስ በእስራኤል ፊት ለተገለጠበት ለልደቱ ዓመታዊ በዓል፣ ለእስራኤላዊ #ለቅዱስ_ናቡቴ ለዕረፍት በዓል፣ ለጋዛ አገር ኤጲስቆጶስ ለቅዱስ አባት #ለአባ_ጴጥሮስ_ለዕረፍት_በዓል፣ ለእስክንድርያ አገር ሠላሳኛ ሊቀ ጳጳሳት ለቅዱስ አባት #ለአባ_ዮሐንስና ሰባ ስድስተኛ ሊቀ ጳጳሳት #ለአባ_አትናቴዎስ_ለዕረፍታቸው_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከቅዱሳን_ጴጥሮስ_ከያዕቆብ_ከመነኰስ_ኤልያስ #ከንጉሥ_ሰሎሞን_እናት_ከቤርሳቤህ ከመታሰቢያቸው ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                                                   ✝ ✝ ✝ ❤ #ነቢዩ_ቅዱስ_ኤልያስ፦ ይህ ቀናኢ ኤልያስ ከሌዊ ወገን የሆነ የአባቱ ስም ኢያስኑዩ የእናቱም ስሟ ቶና ነው። ስለርሱም እንዲህ ተነገረ በተወለደ ጊዜ ብርሃንን የለበሱ አራት ሰዎች ሲሰግዱለትና ሕፃናት በሚጠቀለሉበት ጨርቅ ፈንታ በእሳት ሲጠቀለሉበት አባቱ አየ። እርሱም ወደ ኢየሩሳሌም መጥቶ ይህን ለካህናቱ ነገራቸው እነርሱም "ማደሪያው በብርሃን ውስጥ ይሆን በቃሉም የሚቆርጥ ይሆን ወይም እስራኤልን በሰይፍና በእሳት እየቀጣ ይገዛቸው ይሆን" ተባባሉ። ❤ በእስራኤለሰ ንጉሥ በአክዓብና በሚስቱ በኤልዛቤል በልጁም በአካዝያስም ዘመን ያደረገው የተአምራቱ ዜና በመጽሐፈ ነገሥት ተጽፎአል። ወደ ሰማይ ያረገበት ዜናው ግን በጥር ወር በስድስት ቀን ተጽፎአል። በኋላ ጊዜም ስለሚሆነው ሞቱ ራእይን በሕይወቱ ያየ ዮሐንስ ከኄኖክ ጋር እንደሚመጣና ሐሳዊ መሲሕን እንደሚቃወሙት ተአምራትንም እንደሚያደርጉ ተናግአል። "ሁለቱ የዘይት ዕንጨቶች በምድር ላይም የተሾሙ በእግዚአብሔር ፊት የማያበሩ ሁለት መብራቶች ናቸው" አለ። ❤ "ከጠላቶቻቸው ወገን ሊጣላቸው የወደደውን እሳት ከአፋቸው ወጥታ ታጠፋቸውዋለች የሚጣሏቸው እንዲህ ይጠፋሉ። ትንቢት በሚናገሩበት ወራት በምድር ላይ ዝናም እንዳይዘንም ይዘጓት ዘንድ በሰማይ ላይ ሥልጣን አላቸውና ዳግመኛም ደምን ያደርጉት ዘንድ በውኃው ላይ ሥልጣን አላቸው የፈለጉትን ያህል በመቅሠፍቱ ሁሉ ምድርን ያስጨንቋታል። ምስክርነታቸውንና ትንቢታቸውን ከፈጸሙ በኋላ ከባሕር የወጣው አውሬ ከሳቸው ጋር ይጣላል ድል ነስቶም ይገድላቸዋል። አስከሬናቸውም ፍጥሞ በምትባል በታላቂቱ አገር ያስጥለዋል ይችውም በምስጢር ሰዶም ግብጽ የተባለች ጌታቸው የተሰቀለባት ናት። አስከሬናቸውንም ሕዝብና አሕዛብ በአገርም ያሉ ነገዶች ሦስት ቀን ተኩል ያዩታል አስከሬናቸውንም በመቃብር ይቀብሩት ዘንድ አያሰናብቱም። ❤ በምድር ላይ የሚኖሩ ሰዎች በእነርሱ ሞት ደስ ይላቸዋል እርስበርሳቸውም በደስታ እጅ መንሻ ይሰጣጣሉ እሊህ ሁለቱ ነቢያት በምድር በሚኖሩ ሰዎች መከራ አጽንተውባቸዋልና ይላሉ። ከሦስት ቀን ተኩል በኋላ ከእግዚአብሔር ዘንድ የሕይወት መንፈስ መጥታ ታድርባቸዋለች ተነሥተውም በእግራቸው ይቆማሉ በሚያዩዋቸው ላይም ጽኑ ፍርሀት ይሆናል። ከወደ ሰማይ ቃል መጥቶ ወደዚህ ውጡ ይላቸዋል ከዚህ በኋላ ጠላቶቻቸው እያዩአቸው በደመና ያርጋሉ። በዚያችም ሰዓት ጽኑ መነዋወጥ ይሆናል የዚችም አገር ዐሥረኛ እጅዋ ይጠፋል በዚያም መነዋወጥ ሰባት ሽህ ሰዎች ይሞታሉ የቀሩት ግን ደንግጠው የሰማይ አምላክ ፈጽመው ያመሰግናሉ"። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ነቢይ በቅዱስ ኤልያስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                              ✝ ✝ ✝ ❤ #እስራኤላዊው_ቅዱስ_ናቡቴ፦ ይህ ናብቴ በሰማርያው ንጉሥ በክዓብ ቤት አጠገብ የወይን አትክልት ቦታ ነበረው። አክዓብም ናብቴን ለቤቱ ቅርብ ነውና "የተክል ቦታ ይሆነኝ ዘንድ ይህን የወይን ቦታህን ስጠኝ ከሱ የሚሻል ሌላ የወይን ቦታ እሰጥሃለሁ ዋጋውንም ትሻ እንደሆነ የዚህን የወይን ቦታህን ሽያጭ ወርቅ እሰጥሃለሁ የተክል ቦታ ይሁነኝ" አለው። ናብቴም አክዓብን "የአባቶችን ርስት እሰጥህ ዘንድ እንዲህ ያለ ነገር እግዚአብሔር አያምጣብኝ" አለው። ❤ አክዓብም አዝኖ ሔደ ፊቱንም ተከናንቦ በመኝታው ተኛ እህልም አልበላም። ሚስቱ ኤልዛቤልም ወደርሱ ገብታ "እህል የማትበላ ምን ሆንክ የሚያሳዝህስ ምንድን ነው?" አለችው። "የኢይዝራኤል ሰው ናብቴን የወይንህን ቦታ በዋጋ ሽጥልኝ ትወድም እንደሆነ ስለርሱ ፈንታ ሌላ ቦታ እሰጥሃለሁ ብዬ ብናገረው የአባቶቼን ርስት አልሰጥህም ብሎኛልና ስለዚህ ነው ያዘንሁት" አላት። ሚስቱ ኤልዛቤልም "ዛሬ እንዲህ የምታደርግ አንተ የእስራኤል ንጉሣቸው ነህን አሁንም ተነሥተህ እህል ብላ ራስህንም አፅና ልቡናህም ደስ ይበለው የኢይዝራኤል ሰው የናብቴ ቦታ እኔ እሰጥሃለሁ" አለችው። ❤ በአክዓብ ስም ደብዳቤ ጽፋ በማኅተመም አትማ ያቺን ደብዳቤ ከናቡቴ ጋር ወደሚኖሩ ወደዚያ አገር አለቆችና ወደዚያች አገር ሽማግሌዎች ላከቻት። የዚያችም ደብዳቤ ቃል እንዲህ የሚል ነው "ጾምን ጹሙ ናቡቴንም በሕዝቡ ፊት አስቀምጡት የሐሰት ምስክሮችንም ሁለት ሰዎችን አስነሡበት እግዚአብሔርን ሰደብከው ንጉሥንም ረገምከው ብለው ይመስክሩበት ከከተማም ወደ ውጭ አውጥታችሁ በደንጊያ ውገሩትና ይሙት" የሚል ነበር። እንዲህም በግፍ ኤልዛቤል አስገደለችው ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ናቡቴ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                               ✝ ✝ ✝ ❤ #የጋዛ_አገር_ኤጲስቆጶስ_አባ_ጴጥሮስ፦ ይህም ሮሃ ከሚባል አገር ክብር ካላቸው ወገን ነው ይሾመውም ዘንድ ወላጆቹ ለንጉሥ ቴዎዶስዮስ ሰጡት እርሱ ግን ሹመትንና ክብርን ይጠላ ነበር በንጉሡም አዳራሽ ውስጥ በጾም በጸሎት በሰጊድ ተጠምዶ ኖረ ከርሱም ጋር የፋርስ አገር ሰማዕታት ሥጋ አብሮት አለ በዚያም ጊዜ ዕድሜው ሃያ ዓመት ነው። ❤ ከዚህም በኋላ ከገዳማት ወደ አንዱ ገዳም ሔዶ መነኰሰና ጽኑ ተጋድሎንም ተጋደለ የቅድስናውና የተጋድሎው ዜና በተሰማ ጊዜ ያለ ፈቃዱ ወስደው ጋዛ በምትባል አገር በአውራጃዋም ሁሉ ላይ ኤጲስቆጶስነት ሾሙት። ስለርሱም የቊርባንን ቅዳሴ በሚቀድስ ጊዜ ኅብስቱን ሲፈትት ጻሕሉን እስቲመላ ድረስ ብዙ ደም እንደሚፈስ ተነገረ። የቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድን ሥጋ ወደርሱ ወስዶ ከኢየሩሳሌም ገዳማት በአንዱ ገዳም ኖረ በከሀዲው መርቅያን ዘመንም ወደ ግብጽ አገር ሸሸ የቅዱስ ያዕቆብም ሥጋ ከእርሱ ጋር አብሮ ነበር በዚያም ጥቂት ጊዜ ኖረ። ❤ በአንዲትም ዕለት መሥዋዕት አዘጋጅቶ እርሱ ሲቀድስ ቁመው የነበሩ ሕዝብ እርስ በርሳቸው ይነጋገሩ ነበር በቅዳሴ ቊርባን ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስም አልገሠጻቸውም የእግዚአብሔርም መልአክ አይቶ ወደታች ሊወረውረው ወዶ ከመካከላቸው አንሥቶ ያዘው ግን ታግሦ ተወው እርሱ እነርሱን መገሠጽ አፍሮ አክብሮአቸዋልና። ❤ የከሀዲው መርቅያን ዘመን በተፈጸመ ጊዜ ወደ ፍልስጥዔም ምድር ተመልሶ አብያተ ክርስቲያናትን አጠናከረ ከግብጻዊ አባ ኢሳይያስም ጋር ተገናኘ ዜናውም በንጉሥ ዘይኑን ዘንድ በተሰማ ጊዜ ንጉሡም ሊያየው ወደደ እርሱ ግን አልወደደሜ ከዚህ ከኃላፊው ክብር እጅግ ይሸሽ ነበርና።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤             ❤ #ኅዳር ፴ (30) ቀን። ❤ እንኳን #ለቊስጥንጥንያ_ሊቀ_ጳጳሳት ለቅዱስ አባት #ለአባ_አካክዮስ_ለዕረፍት፣ #ለቅዱሳን_ለቆዝሞስና_ለድምያኖስም ቤተ ክርስቲያናቸው ለከበረችበት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በዓል በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከሰማዕት #ከአባ_መርቆሬዎስ ከመታሰቢያ በዓሉ፣ #ከአናንዮስ_ዘዓምድና_ከአባ_ጴጥሮስ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #የቊስጥንጥንያ_አገር ሊቀ_ጳጳሳት_አባ_አካክዮስ፦ ይህም ቅዱስ ቸር የሆነ ምሁር ነው አምላክ ያጻፋቸውንም መጻሕፍት ቃላቸውን አሳምሮ የሚተርጒም አዋቂ ነው በቊስጥንጥንያ ቤተ ክርስቲያንም ቅስና ተሹሞ ነበር በኬልቄዶንም ስብሰባ በሆነ ጊዜ ይህ አባት በጉባኤው ውስጥ በሆነው ሁሉ ደስ አላለውም ስለ እውቀቱም እንዲመጣ በፈለጉት ጊዜ እርሱ አሞኛል ብሎ ስራሱ ምክንያት ሰጠ። ❤ በእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት በቅዱስ ዲዮስቆሮስ ላይ ስለ ደረሰበት ሥቃይ በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ ሃይማኖታቸው የቀና እንደሆነ በሚያውቃቸው ባልንጀሮቹ በሆኑ በወዳጆቹ በወታደር አለቆችና በመኰንኖች ፊት የአንድነት ጉባኤያቸውን ረገመ "ከእሊህም ክፉዎች ከጉባኤያቸው አንድ ያላረገኝ እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ" አለ። የቊስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳሳት እንጣልዮስም በዐረፈ ጊዜ ሃይማኖቱ የቀና እንደ ሆነ ስለ አወቁ የአገሩ ሊቃውንትና መኳንት ይህን አባት አካክዮስን መረጡት። እርሱ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሆነውን መጣላትና መለያየትን ያስወግዳል በማለት ተስፋ አድርገው በቊስጥንጥንያ አገር ላይ ሊቀ ጵጵስና ሾሙት። ❤ በተሾመ ጊዜም ከብቻው እግዚአብሔር በቀር ማንም ሊአስወግደው የማይችል የጥልና የመለያየት የማይድን በሽታ አገኘ በልቡም አስቦ "መጀመሪያ ራሴን አድን ዘንድ አይሻለኝምን" አለ የቅዱሳን አባቶችን የቄርሎስና ዲዮስቆሮስን የቀናች ሃይማኖት የተማረና እርሷ የጸና መሆኑን እየታመነለት ከዚህም በማስከተል በክህነት ሥራ በመሳተፍ ይቀበለው ዘንድ ወደ እስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ወደ ሦስተኛው ጴጥሮስ መልእክት ላከ። አባ ጴጥሮስም መልክቱን በአነበበ ጊዜ ደስ ብሎት ታላቅ ክብርን አከበረው ያቺንም መልክት በጉባኤ ፊት አስነበባት ከዚህም በኋላ አባ ጴጥሮስ ለመልእክቱ መልስ ጽፎ ከሦስት ኤጲስቆጶሳት ጋር ወደ አካክዮስ ላከ እነርሱም ወደ ቊስጥንጥንያ ከአባ አካክዮስ ዘንድ በደረሱ ጊዜ የአባ ጴጥሮስን ደብዳቤ ሰጡት እርሱም ሃይማኖታቸው በቀና በወዳጆቹና በአገሩ መኳንንት ፊት አነበባት። ሁሉም ደስ አላቸው አባ አካክዮስም እሊህን ኤጲስቆጶሳት ታላቅ ክብርን አከበራቸው ወደ አንድ ገዳም ወሰዳቸው መሥዋዕትንም አዘጋጅቶ የቊርባን ቅዳሴ በመቀደስ ከእርሳቸወሰ ጋር አንድ ሆነ ከእሳቸውም ቡራኬ ተቀበለ። ❤ ዳግመኛም ከአባ አትናቴዎስ ከአባ ጢሞቴዎስ ከአባ ቄርሎስ ከአባ ዲዮስቆሮስ ከሃይማኖታቸው የሚተላለፈውን እያወገዘ ጻፈ ያቺንም የመልክት ደብዳቤ ሰጣቸውና በፍቅር በሰላም አሰናበታቸው። ወደ አባ ጴጥሮስም በደረሱ ጊዜ አባ አካክዮስ ያደረገውን ሁሉ ነገሩት የመልእክቱንም ደብዳቤ ሰጡት እርሱም ደስ አለው ስሙንም በማዕጠንትና በቊርባን ጊዜ እንዲጠሩ አዘዘ። ዜናውም በሮሜውያን ኤጲስቆጶሳት ዘንድ በተሰማ ጊዜ አባ አካክዮስን ከቊስጥንጥንያ መንበር አሳደዱት በቀናች ሃይማኖት እንደ ጸና በደሴት ውስጥ ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ አካክዮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘለዓለሙ አሜን። ምንጭ፦ የኅዳር 30 ስንክሳር።                             ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለአካክዮስ_ለእንጣልዮስ_ዋርሱ። ዘዐቢይ ስነ ሞገሱ። ማኅበረ ኬልቄዶን አብዳን አመ ሰደድዎ እምአትሮንሱ። እንበለ ይዕሉ ሃይማኖቶ ወእንበለ ጽድቆ የሐሱ። #በኢየሱስ_ክርስቶስ አዕረፈት ነፍሱ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የኅዳር _30።                           ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ክብር ንጉሥ ፍትሐ ያፈቅር። አንተ አፅናዕካ ለጽድቅ በኃይልከ። ፍትሕ ወጽድቀ ለያዕቆብ አንተ ገበርከ"። መዝ 98፥4-5 ወይም መዝ 25፥5። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ጢሞ 1፥5-15፣ 1ጴጥ 2፥13-21 እና የሐዋ ሥራ 23፥10-32። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ16፥1-8 ወይም ሉቃ 19፥11-28። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም የጻድቁ ንጉሥ የቅዱስ ገብረ መስቀል የዕረፍት በዓልና የነቢያት (የገና) የጾም ጊዜ። ሁላችንም ይሁንልን።          

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤                  ❤ #ኅዳር ፴ (30) ቀን። ❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ለጻድቁ_ንጉሥ_ለዐፄ_ገብረ መስቀል_ለዕረፍት_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #ጻድቁ_ንጉሥ_ዐፄ_ገብረ_መስቀል፦ ይኸውም ንጉሥ ታላቁ ጻድቅ አቡነ አረጋዊ ከሰማይ በወረደላቸው ኅብስት ቀድሰው ያቆረቡትና መንግሥቱን የባረኩለት ነው። ዐፄ ካሌብ የናግራንን ሰማዕታት ደም ተበቅሎ በድል ከተመለሰ በኋላ ከአቡነ ጰንጠሎዎን እጅ መንኰሶ ገዳም ከገባ በኋላ ልጁ ገብረ መስቀል ነገሠ። ዐፄ ገብረ መስቀል በእውነትና በቅንነት ከነገሠ በኋላ አመራሩ ከአህጉሪቷ ጽንፍ እስከ ጽንፍ ደረሰ። በዘመኑም ሁሉ መንግሥቱን የሚቃወም አልተነሣም፤ እርሱም ቤተክርስቲያንን ከመሥራት በቀር ወደ ጦርነት የሄደበት ጊዜ የለም። ❤ መንግሥቱንም ይባረክለት ዘንድ ሠራዊቱን ይዞ ወደ አባታችን ወደ አቡነ አረጋዊ ዘንድ ደብረ ዳሞ ሄደና በፊታቸው ሰግዶ "አባቴ ሆይ! እኔን ባሪያህን፣ መንግሥቴንና ሕዝቤን ሠራዊቴንም ሁሉ ባርክ" እያለ አጥብቆ ማለዳቸው። አባታችን አረጋዊም "የአባቶችህን የዳዊትና የሰሎሞንን መንግሥት የባረከ፣ የአባትህን የካሌብንም መንግሥት የባረከ እግዚአብሔር የአንተንም መንግሥት ይባርክ... "ብለው ባረኩት። ከዚህም በኋላ ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል አቡነ አረጋዊን የት ቦታ ላይ ቤተ ክርስቲያን እንደሚሠራ ጠይቋቸው ካሳዩት በኋላ ሲሠራ ሁለት ዓመት የፈጀበት ግሩም ቤተ ክርስቲያን ሠራላቸውና 12 የወርቅና የብር መስቀሎችን ጨምሮ ብዙ ንዋያተ ቅዱሳቶችንና ሥጦታዎች ሰጣቸው። ጳጳስም አስመጥቶ አስባረካትና ከማኅበረ በኩር ያመጣውን በወርቅ በብር የተለበጠች የእመቤታችንን ታቦት በውስጧ አስገባ። ጳጳሱና ንጉሡ ዐፄ ገብረ መስቀልም አቡነ አረጋዊን "ቀድሰህ አቊርበን" ብለውት ይቀድሱ ዘንድ በገቡ ጊዜ መላእክት ሙቀት ያልተለየው ኅብስትና ወይኑን በጽዋ ለቅዳሴው የሚያስፈልገውንም ሁሉ ከሰማይ አወረዱላቸውና ቀድሰው ሲያበቁ ሁሉንም አቆረባቸው። ❤ ከዚህም በኋላ ንጉሡ ዐፄ ገብረ መስቀል ከተራራው ጫፍ በሚወርዱበት ጊዜ አባታችንን "ይህን የተራራውን መውጫ መሰላል ላፍርሰው ወይስ ልተወው?" አሏቸው። አባታችንም "ለልጅ ልጅ መታሰቢያ እንዲሆን ይህን ድንቅ ሥራ እያየ በፍጥረቱ ሁሉ አንደበት እግዚአብሔር ይመሰገን ዘንድ የደረጃውን መሰላል አፍርሰው፤ ነገር ግን ስለዘንዶው ጅራት ፋንታ ገመድ አብጅ" አለው። ንጉሡም እንደታዘዘው የደረጃውን መሰላል አፈሰውና ወደ ቤተ መንግሥቱ ተመለሰ። ጻድቁ ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል ካበረከተልን ትልቅ ውለታው ውስጥ አንዱ ዛሬ በዩኔስኮ የተመዘገበውን የመስቀል በዓልን በአደባባይ እንዲከበር ያደረገ መሆኑ ነው። በዘመኑም ካህናቱ ሕዝቡ ሁሉ አደይ አበባ ይዘው ወደ አደባባይ በመውጣት በያሬዳዊ ዝማሬ የመስቀልን በዓል ያከብሩ ነበር። ❤ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ብርሃኗ የሆነ ነገር ግን እርሷ እንደሚገባው መጠን ያላከበረችው ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ በዚህ ጻድቅ ንጉሥ በዐፄ ገብረ መስቀል ዘመነ መንግሥት የነበረ ነው። አብረውም ብዙ ታሪኮችን ፈጽመዋል። የተለያዩ ገዳማትን በመዟዟር ቅዱስ ያሬድ ዜማን ሲያስተምር ንጉሡ ደግሞ የቤተ ክርስቲያንን ይዞታ ያስፋፋና ቋሚ መተዳደሪያ ይሰጡ ገዳማቱን ያጠናክሩ ነበር። አቡነ አረጋዊ ደግሞ አብረው ምንኵስናን ያስፋፉ ነበር። ሦስቱም ይህን ተግባራዊ እንዳደረጉ ለማሳያ ይሆን ዘንድ ቅዱስ ያሬድ 3 ዓመት ዝማሬ መዋሥዕት ያስተማረባትና ዛሬም ድረስ ማስመስከሪያ የሆነችውን እጅግ ጥንታዊቷን ዙር አባ ጽርሕ አርያም አቡነ አረጋዊ ገዳምን እንደምሳሌ ማየት እንችላለን። አቡነ አረጋዊና ቅዱስ ያሬድ በቅዱስ ዑራኤል መሪነት በሐረግ ተስበው  ዓምባው ላይ ከወጡ በኋላ ንጉሡ ዐፄ ገብረ መስቀል ደግሞ ተራራውን ባርከው ከፍለው መንገድ አበጅተውላቸው ወደ ዓምባው ወጥተው ሦስቱም በዚያ በጋራ ኖረው ብዙ መንፈሳዊ ሥራን ሠርተዋል። ❤ ጻድቁ ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል ከተሰዓቱ ቅዱሳን ጋር ሆኖ ብዙ መንፈሳዊ ሥራን ሠርቷል።  ዐፄ ገብረ መስቀል በጽድቅ ሕይወት እየተመላለሱ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለአገራችን የዋሉት ውለታ እጅግ ብዙ ነው። ዕረፍታቸውም በዚች ቀን ኅዳር 30 ነው። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳን ከሚለው መጽሐፍ የተወሰደ።                           ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለከ_ንጉሥ_ክቡር። እንተ ትትሜካህ በኃይሉ ለእግዚአብሔር። ገብረ መስቀል መዊዒ ወመግረሬ ፀር። በመዋዕሊከ መዋዕለ ሰላም ወፍቅር። ማኅሌተ ሰማይ መዝሙር ተከስተ በምድር"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የኅዳር_30።                

                            ✝ ✝ ✝ ❤ #ቅዱስ_ቀሌምንጦስ፦ ይህም ቅዱስ ከመንግሥት ልጆች ወገን የሆነ ለሮሜ ንጉሥ የጭፍራ አለቃ ለሆነ ለቀውስጦስ ልጁ ነው ደጎች የሆኑ አባትና እናቱም ቅዱስ ጴጥሮስ የወንጌል ትምህርት በሰበከ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ገንዘባቸውንም ሁሉ ለድኆችና ለችግረኞች ምጽዋት አድርገው ሰጡ። ❤ ከዚህም በኋላ መኰንኑ ቀውስጦስ ወደ ንጉሥ  ሔዶ በዚያው በዘገየ ጊዜ ወንድሙ የመኰንኑን የቀውስጦስን ሚስት ሊአገባት አሰበ እርሷም በአወቀች ጊዜ አባታቸው እስቲመለስ ወደ አቴና ሔዳ ጥበብን ታስተምራቸወሰ ዘንድ ቀሌምንጦስንና ታናሽ ወንድሙን ይዛ በመርከብ ተሳፈረች። በዚያንም ጊዜ ብርቱ ነፋስ በመንፈሱ ማዕበል ተነሥቶ መርከቡ ተሰበረ ቀሌምንጦስም በመርከቡ ስባሪ ተንጠለጠለ የባሕሩም ሞገድ ወደ እስክንድርያ አገር አደረሰውና በዚያ ጥቂት ቀኖች ኖረ። በዚያንም ወቅት የከበረ ሐዋርያ ቅዱስ ጴጥሮስ ቃል ጠራውና ወደ እስክንድርያ አገር እንዲሔድ አዘዘው በሔደም ጊዜ በውስጥዋ የወንጌልን ቃል ሰበከ ከዚህ ከቅዱስ ቀሌምንጦስ በቀር ከአገር ሰው አንድ እንኳን ያመነ የለም እርሱ የቅዱስ ሐዋርያ ጴጥሮስን ትምህርት በሰማ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምኖ የክርስቶስን ጥምቀትን ተጠመቀ። ❤ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስም የጌታችንን የመለኮቱን ምሥጢር ለሚያመልኩትም የሚሰጣቸውን ብልጽግናውንና ክብሩን በስሙም ኃይል ድንቅ ተአምራትም እንደሚደረግ ገለጠለት። ከዚችም ዕለት ጀምሮ ቀሌምንጦስ ቅዱስ ጴጥሮስን ተከተለው ደቀ መዝመሩም ሆነ እርሱም የሐዋርያትን ገድላቸውን ከዐላውያን ነገሥታትና መኳንንት የደረሰባቸውን ሥቃይ ሁሉ ጻፈ። ከዚህም በኋላ በብዙ አገሮች ውስጥ አስተማረ ሐዋርያትም በጉባኤ ተነጋግረው የሠሩአቸውን የሥርዓት መጻሕፍትን ለርሱ ሰጡት። ❤ ከዚህም በኋላ በሮሜ አገር ሊቀ ጵጵስና ተሾመ በትምህርቱም ከሰዎቿ ብዙዎችን እግዚአብሔርን ወደማወቅ መለሳቸው። ስለርሱም ከሀዲ ንጉሥ ጠራብሎስ ሰምቶ ጭፍራ ልኮ ወደርሱ አስመጥቶ "ክርስቶስን ክደህ ለአማልክት ስገድ" አለው ትእዛዙንም ባልሰማ ጊዜ በዚያ ያሠቃዩት ዘንድ ወደ አንዲት አገር ሰደደው እርሱ በላዩ እንዳይነሡበት ከአገር ሰዎችና ከዘመዶቹ የተነሣ ፈርቷልና መኰንኑንም ጽኑዕ ሥቃይን እንዲአሠቃየው አዘዘው። ❤ የዚያችም አገር መኰንን በመርከቦች ውስጥ የሚኖር እግሮች ያሉት ከባድ ብረት በአንገቱ ውስጥ አንጠልጥሎ ከባሕር ውስጥ አሠጠመው ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ ወንጌልን እንደ ሰበኩ ሐዋርያትም በመንግሥተ ሰማያት የምስክርነት አክሊል ተቀበለ። ❤ እንዲህም ሆነ አንዲት ዓመትም ስትፈጸም ባሕሩ ተገልጦ እንደተኛ ሁኖ የቅዱስ ቀሌምንጦስ ሥጋ በጥልቁ ባሕር ውስጥ ታየ። እርሱም ሕይወት ያለው ይመስል ነበር ሰዎችም ገብተው ከእርሱ ተባረኩ የከበረ የደንጊያ ሣጥንም አምጥተው ሥጋውን በውስጡ አድርገው አንሥተው ከባሕር ውስጥ ሊአወጡት ፈለጉ ግን ከቦታው ሊአንቀሳቅሱት አልቻሉም ከባሕር ውስጥ መውጣትን እንዳልፈለገ አወቁ በዚያም ትተውት ወደ ቤቶቻቸው ሔዱ። ከዚህም በኋላ በመታሰቢያው ቀን በየዓመቱ ያቺ ባሕር ከቅዱስ ቀሌምንጦስ ሥጋ ላይ የምትገለጥ ሆነች ምእመናንም ሁሉ ገብተው ከእርሱ ይባረካሉ መታሰቢያውንም በማድረግ በዓሉን ያከብራሉ ከዚያም በኋላ ወጥተው ወደቤታቸው ይገባሉ። ❤ ከአስደናቂዎች ተአምራቶቹም ከተጻፋት ያዩ ይህን ተናገሩ በአንዲት ዓመት ከሥጋው ሊባረኩ በገቡ ጊዜ የቅዱስ ቀሌምንጦስ ሥጋው ካለበት ሣጥን ዘንድ ሲወጡ ታናሽ ሕፃን እንደረሱ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚወዱት ቅዱሳኑ ክብራቸውን ከርሱ የተቀበሉትንም ጸጋ ይገልጥ ዘንድ ወዷልና። ወላጆቹም ከወጡ በኋላ ሕፃኑን ፈለጉት ግን አላገኙትም ባሕሩም በላዩ ተከድኖ ነበር ሙቶ በባሕር ውስጥ ያሉ አራዊት የበሉት መስሏቸው አለቀሱለት እንደ ሥርዓቱም በማዕጠንትና በቊርባን ቅዳሴ መታሰቢያውን አደረጉ። ❤ በዳግመኛውም ዓመት ያቺ ባሕር ተገለጣ እንደ ልማዳቸው ገቡ ሕፃኑንም በሕይወት ሁኖ በቅዱስ ቀሌምንጦስ የሥጋ ሣጥን ዘንድ ቁሞ አገኙት "በዚህ ባሕር ውስጥ አኗኗርህ እንዴት ነበር ምን ትበላ ነበር የባሕር አራዊትስ እንዴት አልበሉህም" ብለው ጠየቁት። እርሱም ቅዱስ ቀሌምንጦስ ያበላኝ ነበር እግዚአብሔርም በባሕር ካሉ አራዊት ይጠብቀኝ ነበር" ብሎ መለሰ ሰምተውም እጅግ አደነቁ በቅዱሳኑና ስለ ከበረ ስሙ ደማቸውን በአፈሰሱ ሰማዕታት የሚመሰገን ምስጉን እግዚአብሔርን አመሰገኑት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ቅዱስ ቀሌምንጦስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የኅዳር 29 ስንክሳር።                          ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለከ_ቀሌምንጦስ_አቡነ። አበ መንፈስነ። ከመ ናጽንዕ ዘልፈ ዘትምህርትከ አሚነ። ጽሒፎሙ ሐዋርያት ኃደጉ ለነ። #ምስለ_ቀሌምንጦስ እንዘ ይብሉ መልእክተ ፈኖነ። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የኅዳር _29።                                                       ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ምስሌከ ቀዳማዊ በዕለተ ኃይል። ወብርሃኖሙ ለቅዱሳን። ወለድኩከ እምከርሥ እምቅድመ ኮከበ ጽባሕ"። መዝ 109፥3። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 2፥1-8።                         ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ኪያየ ይጸንሑ ኃጥአን ይቀትሉኒ። እስከ ስምዐከ ለበውኩ። ለኲሉ ግብር ርኢኩ ማኅለቅቶ"። መዝ 118፥95-96። የሚነበቡት መልዕክታት ፊል 3፥1-15፣ 1ኛ ጴጥ 5፥5-13 እና የሐዋ ሥራ 27፥39-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 10፥1-22። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ባስልዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ቀሌምንጦስ፣ የተፍጻሜተ ሰማዕት የአባ ጴጥሮስ፣ አቡነ ፄዋለ ጽጽቅ የዕረፍታቸው በዓል፣ የአቡነ ዮሐንስ ዘጠገሮ የልደት በዓልና የነቢያት (የገና) የጾም ጊዜ። ሁላችንም ይሁንልን።               

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤           ❤ #ኅዳር ፳፱ (29) ቀን። ❤ እንኳን #ከሰባ_ሁለት_አርድእት አንዱ ለአንዱ ለሆነው #ለሐዋርያው_ቅዱስ_ጴጥሮስ ደቀ መዝሙር #ለቅዱስ_ቀሌምንጦስ_ለዕረፍት_በዓል፣ ለእስክንድር ዐሥራ ሰባተኛ ሊቀ ጳጳሳት #ለተፍጻሜተ_ሰማዕት_ለቅዱስ_ጴጥሮስ_ለዕረፍት_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደአሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከጌታችን_ልደት_ወራዊ መታሰቢያ (በዓለ ወልድ) በዓልና በከሀዲው ንጉሥ በዲዮቅልጥያኖስ ዘመን በሰማዕትነት ከዐረፉ #ከአርባ_ሰባት_አእላፋት ከመታሰቢያቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                         ✝ ✝ ✝ ❤ #ተፍጻሜተ_ሰማዕት_ቅዱስ_ጴጥሮስ፦ የዚህ አባት ወላጅ አባቱ በእስክድርያ አገር ሊቀ ካህናት ስሙ ቴዎድሮስነው እናቱም ስም ሶፍያ እነርሱም እግዚአብሔርን የሚፈሩ ጻድቃን ነበሩ፡፡ ነገር ግን ልጅ ስላልነበራቸው እጅግ ያዝኑ ነበር፡፡ ሶፍያም በአምስተኛኛው ቀን የቅዱሳን ሐዋርያትን የቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስን በዓል ለማክበር ወደ ቤተ ክርስቲያን ስትሄድ ሌሎቹ ሰዎች ከልጃቸው ጋር ለበዓሉ ሲሄዱ አይታ አዘነች፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሄዳ እግዚአብሔርን ልጅ እንዲሰጣት በቅዱሳን ሐዋርያቱ ስም ለመነችው፡፡ በዚያችም ሌሊት የከበሩ ሁለቱ ሐዋርያት ተገለጡላትና "የከበረ ልጅ ትወልጃለሽ ስሙንም ጴጥሮስ በይው" አሏት፡፡ እርሷም ከወለደች በኋላ ስሙን ጴጥሮስ አለችው፡፡ ❤ ሰባት ዓመትም በሆነው ጊዜ የሃይማኖትን ምሥጢር ይማር ዘንድ ወስዳ ለሊቀ ጳጳሳቱ ለአባ ቴዎናስ ሰጠችው፡፡ ሊቀ ጳጳሳቱም በሥርዓት አሳደጉትና ከእርሳቸው ጋር የሚያገለግል ሆነ፡፡ እርሳቸውም ከማረፋቸው በፊት ጴጥሮስ በእሳቸው ቦታ እንዲሾም ተናገሩ፡፡ ካረፉም በኋላ ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ ተሾመና በታላቅ ተጋድሎ እየኖረ አገልግሎቱን በሚገባ አከናወነ፡፡ በእርሱም ዘመን የአንጾኪያዋ ታላቅ ሰማዕት ቅድስት ሣራ ልጆቿን ልታስጠምቅ ወደ እርሱ መጣች፡፡ እርሷም የከሀዲው የዲዮቅልጥያኖስ ባለሟል የሆነ የአንዱ መኳንንት ሚስት ነበረች፡፡ በሏ ንጉሡን በመፍራት ሃይማኖቱን ሲክድ እርሷ ግን በእምነቷ ጸናች፡፡ሁለት ልጆችንም ስትወልድ የክርስትና ጥምቀትን ልታስጠምቃቸው አልቻለችም፡፡ ምክንያቱም በአንጾከያ አብያተ ክርስቲያናት በሙሉ ወድመው ነበር፡፡ ወደ እስክንድርያም ሄዳ በአቡነ ጴጥሮስ እጅ ልታስጠምቃቸው አሽከሮቿን ይዛ ተነሣችና በመርከብ ተሳፈረች፡፡ በመሀልም ኃይለኛ ማዕበል ተነሥቶ መርከቢቱ ልትሰምጥ ሆነ፡፡ ቅድስት ሣራም ልጆቿ ሳይጠመቁ እንዳይሞቱ በማለት ጸሎት ካደረገች በኋላ የቀኙን ጡቷን በምላጭ ቀዳ በደሟ የልጆቿን ግንባር በመስቀል ምልክት አደረገችባቸው፡፡ በጀርባቸውና በደረታቸውም ላይ እንዲሁ አድርጋ በባሕሩ ውስጥ አጠመቀቻቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ታላቅ ፀጥታ ሆነና ማዕበሉ ጠፋ፡፡ ❤ እስክንድርያም ደርሳ ከአባ ጴጥሮስ ዘንድ ልጆቿን ልታስጠምቅ አቀረበቻቸው፡፡ ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስም ብዙ ልጆችን እያጠመቀ በተራ ደግሞ የቅድስት ሣራን ልጆች ሊያጠምቅ ሲል ውኃው እየረጋበት እምቢ አለው፡፡ እስከ ሦስት ጊዜም እንዲሁ ሆነ፡፡ ምን እንደሆነ ቅድስት ሣራን ሲጠይቃት ያደረገችውን ነገረችው፡፡ ይህንንም ሲሰማ እጅግ በመደነቅ "አንዲት ቤተ ክርስቲያን እንዲህ ትላለች እንዲህም ትሠራለች" ብሎ ጌታችንን አመሰገነው፡፡ እርሷም ፈርታ ይቅር በሉኝ ብላ እግሩ ላይ ስትወድቅ እርሱም "አይዞሽ አትፍሪ፣ ሃይማኖትሽ ፍጹም ነው፣ አንቺ ባጠመቅሻቸው ጊዜ በመለኮታዊ እጆቹ ያጠመቃቸው ባለቤቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው" አላት፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ሥጋ ወደሙን ከነልጆቿ አቀብሏትና ወደ አንጾኪያ ተመለሰች፡፡ ❤ ሌላው በቅዱስ ጴጥሮስ ዘመን የተፈጸመው ነገር የአርዮስ መነሳት ነው፡፡ ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና ጌታችንን "ወልድ ፍጡር ነው" ብሎ የተነሣውንና ሰይጣን በልቡ ያደረውን አርዮስን ከስህተቱ ይመለስ ዘንድ ቅዱስ ጴጥሮስ ብዙ መከረው፡፡ ነገር ግን አርዮስ እምቢ ቢለው እረግሞ አውግዞታል፡፡ የንጉሡን አማልክት እንዳያመልኩ በሁሉ ቦታ ቅዱስ ጴጥሮስ እያስተማረ መሆኑን ከሃዲው ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ ሰማ፡፡ ወታደሮቹንም ልኮ አስሮ አስመጣው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ሕዝቡ ስለ እርሱ ሊሞት የተዘጋጀ መሆኑን በተመለከተ ጊዜ ነፍሱን አሳልፎ ሊሰጥ ወደደ፡፡ ሕዝቡንም በቀናች ሃይማኖት እንዲጸኑ ካስተማራቸው በኋላ አጽናንቶ አሰናበታቸው፡፡ አርዮስም ቅዱስ ጴጥሮስ በንጉሡ ትእዛዝ እንደሚሞት ካወቀ በኋላ ከውግዘቱ እንዲፈታው አኪላስንና እለ እስክንድሮስን አማላጅ አድርጎ ላካቸው፡፡ እነርሱም አርዮስን ከውግዘቱ እንዲፈታው ሄደው ቅዱስ ጴጥሮስ ለመኑት ነገር ግን እርሱ ከውግዘቱ ላይ ሌላ ውግዘት ጨመረበት፡፡ ❤ ጌታችንም ልብሱ የተቀደደ ልጅ ሆኖ ተገልጦለት "አርዮስ ልብሴን ቀደደብኝ" ብሎኛል ብሎ ለእነ አኪላስ አስረዳቸው፡፡ ይህም ከባሕርይ አባቴ ለየኝ ማለቱ ነው፡፡ ሁለተኛም "ከአርዮስ ተጠበቁ፣ በክህነት ሥራም አትሳተፉ እርሱ ለክብር ባለቤት ለክርስቶስ ጠላቱ ነውና" አላቸው፡፡ ይህንንም ከነገራቸው በኋላ ሕዝቡ ሳያየው ሊገድለው ካለው ንጉሥ ከዲዮቅልጥያኖስ ጋር ስለሞቱ በስውር ተማከረ፡፡ ይኸውም ሕዝቡ ሳይሰማ እንዴት ይገድሉት ዘንድ ነው፡፡ ንጉሡም አስቀድሞ በእስር ቤት አቆይቶ ልዩ ልዩ በሆኑ ጽኑ ማሠቃያዎች አሠቃይቶት ነበር፡፡ አሁንም ቅዱስ ጴጥሮስ በእስር ቤት ሳለ መስኮቱን ሲያንኳኳላቸው ወታደሮቹ ሰው ሳያይና ሳይሰማ በስውር መጥተው አንገቱን እንዲቆርጡት ተማከረ፡፡ ጌታችንንም በጸሎቱ "የደሜ መፍሰስ ለጣዖታት አምልኮ መጨረሻ ይሁን ከሁሉ ዓለምም ይጥፋ…" ብሎ ለመነው፡፡ ወዲያውም ከሰማይ "አሜን ይሁን ይደረግ" የሚል ድምፅ መጣለት፡፡ ይህንንም ድምፅ በእስር ቤቱ አቅራቢያ የነበረች አንዲት ድንግል ብላቴና ሰምታ ለሕዝቡ ተናግራለች፡፡ ❤ አባ ጴጥሮስም ጸሎቱን ከጨረሰ በኋላ የሚሰይፉትን ወታደሮች ጠርቶ "የታዘዛችሁትን ፈጽሙ" አላቸውና መጥተው ሰየፉት፡፡ በማግስቱም ሕዝቡ ቅዱስ ጴጥሮስ በሰማዕትነት ማረፉን በሰሙ ጊዜ ወደ እስር ቤቱ መጥተው ሥጋውን አንሥተው ወደ ቤተ ክርስቲያን አግብተው በወንበሩ ላይ አስቀመጡት፡፡ ይህም ቅዱስ ጴጥሮስን በሕይወት እያለ ከዚህ በፊት በወንበሩ ላይ ሲቀመጥ ማንም አይቶት አያውቅም ነበርና ነው፡፡ አንድ ቀን "በወንበርህ ላይ የማትቀመጥ ለምድነው?" ብለው ጠይቀውት ነበር፡፡ እርሱም "እኔ እግዚአብሔር በወንበሩ ላይ ተቀምጦ አያለሁና ስለዚህ በዚህ ወንበር ላይ መቀመጥን እፈራለሁ" ብሏቸዋል፡፡ ❤ ግንዘቱንም አከናውነው ከተመረጡ ሊቃነ ጳጳሳት ከሥጋቸው ጋር ሥጋውን አኖሩ እርሱም በወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ ወንበር በሹመት የኖረው ዐሥራ አራት ዓመት ነው የተሾመውም ዲዮቅልጥያኖስ በነገሠ በሃያ ስድስት ዓመት ነው ከሥጋውም ብዙ ድንቅ ተአምራት ተገለጡ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም  በቅዱስ አባት በአባ ጴጥሮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

❤ አባታችን ከሰማይ መስቀል የወረደላቸው ሲሆን ዛሬም በገዳማቸው የሔደ ሰው በወረደው በእጃቸው መስቀል እየተዳበሰ ቆመው በጸለዩበት ባሕር በጠበላቸው ይጠመቃል፡፡ በተጨማሪም ይይዙት በነበረውም  መቋሚያቸው በመዳበስ በረከትን ማግኘት ይቻላል፡፡ ቆመው ከጸለዩበት ባሕር ውስጥ ደረቅ አሸዋ ይወጣል፡፡ አባ ዮሐንስ 500 ዓመት ከኖሩ በኋላ ዕረፍተ ዘመናቸው ሲደርስ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ከ15 ነቢያት፣ ከ12 ሐዋርያት፣ ሄሮድስ ያስፈጃቸው ከመቶ አርባ አራት ሺ ሕፃናት፣ ከአብርሃም ከይስሐቅ፣ ከዕቆብ ጋር ሁሉንም ነገደ መላእክትን፣ ጻድቃን ሰማዕታትን ሁሉ አስከትሎ መጥቶ ታላቅ ቃልኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ "ስምህን የጠራ ገዳምህን የረገጠ፣ መባ የሰጠ፣ ቤተ ክርስትያንህን የሠራ ያሠራ የረዳ፣ ገድልህን የሰማ ያሰማ ያስተረጎመ፣ መታሰቢያን ያደረገ እስከ 10 ትውልድ እምርልሀለው፤ ንስሀ ሳይገባ አይሞትም፣ ልጅ መውለድ ባይችል እኔ ልጅ እሰጠዋለሁ፤ ገድልህን በቤትህ ያስቀመጠ እርኩስ መንፈስ፣ ክፉ አጋንንት ቸነፈር ወባ መልአከ ጽልመት አይነካውም፡፡ በገዳምህ መነኵሴ ቢቀበር በሰማይ ክንፍ አበቅልለታለሁ፤ አይሁድም አረማዊም ያላመነ ያልተጠመቀ በገዳምህ መጥቶ ቢያርፍ ይቅር እልልሃለሁ፣ እንደ መቃብሬ ጉልጎታ እንደተቀበረ አድርጌ እቆጥርልሃለሁ…" የሚል ቃል ኪዳን ከሰጣቸው በኋላ ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ❤ ቅዱስ አባታችንም በ 500 ዓመታቸው ሐምሌ 29 ቀን ዐርፈው በጎንድ ተክለ ሃይማኖት ተቀብረዋል፡፡ በሰሜን ጎንደር የሚገኘውን ይህንን ገዳም ጻድቁ ራሳቸው ናቸው የመሠረቱት፡፡ ነገር ግን የገዳሙን ስያሜ በአባታቸው በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ስም አድርገውታል፡፡ አቡነ ዮሐንስ ካረፉ በኋላ በእርግማናቸው መሠረት በመንዝና በይፋት ብርዱ ድርቁ ስለበዛባቸው አንድ ብቁ ባሕታዊ ከበዓታቸው ወጥተው "በሐሜታችሁ ምክንያት እጨ ዮሐንስ ስለረገማችሁ ነው የእርሱን ዐፅም ካላመጣችሁ ብርዱ ውርጩ ድርቁም አይጠፋላችሁም" አሏቸው፡፡ ሕዝቡም አባታችን በጉንድ አቡነ  ተክለ ሃይማኖት ከተቀበሩ ከ 134 ዓመት በኋላ በቅዱሳን እየተመሩ ሄደው በሌሊት ግማሽ ዐፅማቸውን አምጥተው በሀገራቸው አምጥተው ስላስቀመጡ ብርዱና ውርጩ በመንዝ እየቀነሰላቸው መጥቷል፡፡ ❤ ዛሬም በሀገሩ ብርዱና ውርጭ ሲበዛ የጻድቁን ታቦት ሲያወጡ ውርጩ ይጠፋል፡፡ ጠገሮ በሚባለው ገዳማቸው ውስጥ የሚገኘው ጠበላቸው እጅግ አስደናቂ ነው፡፡ ግማሽ ዐፅማቸውን ከጉንደ ተክለሃይማኖት አምጥተው አርባ ሐራ መድኃኔዓለም አጠገብ በላይ በፍሩክታ ኪዳነምሕረት መጋቢት 18 ፍልሰተ ዐፅማቸው ተከናወነ፡፡ ምድሪቷም ተባረከች፣ የዘሩትንም አበቀለች፣ ውርጩም ብርዱም ቀነሰ፣ ዝናብ አልዘንብ ሲል ወይም ሰብል የሚጨርስ አንበጣ ሲመጣ ታቦታቸው ወጥቶ ምህላ ይያዛል ወድያውም መቅሰፍት ይርቃል፣ ዝናብም ይዘንባል፡፡ ጻድቁ ደመናን፣ ጨረቃንና ፀሐይን በእጃቸው እየያዙ ይጸልዩ ነበር፡፡ በጠገሮ፣ በአዘሎ፣ በፍርኩታና በሌሎቹም ታላላቅ ቦታቦዎች ላይ በእያንዳንዱ ገዳም ሃምሳ ሃምሳ ዓመት በጸሎት ኖረው በአጠቃላይ በ500 ዓመታቸው ነው ያረፉት፡፡ ዐፅማቸው መንዝ ከአርባ ሐራ መድኃኔዓለም አጠገብ ፍርኩታ ኪዳነ ምሕረት ገዳም ውስጥ ይገኛል፡፡ ከአባታች ከእጨጌ አቡነ ዮሐንስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸውም ይማረን። ምንጭ፦ ገድለ እጨጌ (እጨ) አቡነ ዮሐንስ ዘጠገሮና መዝገበ ቅዱሳን መጽሐፍ።

ተአምኆ ቅዱሳን ወግጻዌ (የቅዱሳን ሰላምታ) Teamho Kidusan Wegtsawe (Yekidusa Selamta) Saints Of The Orthodox Tewahedo Church.: ❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤          ❤ #ኅዳር ፳፱ (29) ቀን። ❤ እንኳን #ለኢትዮጵያኑ_ጻድቃን በጸሎታቸው የተከዜን ባሕር ለሁለት ለከፈሉ #ለአቡነ_ገብረ_መስቀል_ዘለጋሶ ለመታሰቢያቸው በዓል፣ የአየር አጋንንት ከእናቱ ጋራ ተገናግቶ የተወለደው መጥቆራ ተብሎ ይጠራ የነበረው #አቡነ_ተክለሃይማኖትና_አቡነ_ዜና_ማርቆስም_በጸሎታቸው ወደ እግዚአብሔር ለምነው በመስቀሉ ኃይል ድል ካደረጉት በኋላ ወደ ሰው አርአያነት እንዲለወጥ አድገውት ሥሙን ለውጠው አመንኵሰው ለታላቅ የቅድስና ደረጃ ለአበቁቱ #ለአቡነ_ፄዋለ_ጽጽቅ ለዕረፍት በዓል፣ ለታላቁ አባት በፀሐይ ላይ 50 ዓመት፣ በጨረቃ ላይ 50 ዓመት፣ በደመና ላይ 50 እንዲሁም ዓለምን በክንፋቸው በመዞር በደመና ላይ 50 ለኖሩ ከሰው ተወልደው ከመላእክት ለተደመሩ ጻድቅ #ለእጨጌ (እጨ) #ለአቡነ_ዮሐንስ_ዘጠገሮ ለልደታቸው በዓል መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                            ✝ ✝ ✝ ❤ #አቡነ_ገብረ_መስቀል_ዘለጋሶ፦ ትውልድ አገራቸው ትግራይ አድዋ ሲሆን የአቡነ ሳሙኤል ዘደብረ ሃሌ ሉያ ልጅ ናቸው። አቡነ ሳሙኤል ዘደብረ ሃሌ ሉያ ያሳደጓቸው የቆብ አባታቸው ሲሆኑ ያመነኰሷቸው ግን አቡነ እንጦንዮስ ዘደብረ ተንኮክ ናቸው። አቡነ ገብረ መስቀል ዘለጋሶ በጸሎታቸው የተከዜን ባሕር በሁለት የከፈሉ ታላቅ አባት ናቸው። በምናኔ ሕይወት 80 ዓመት ሲቆዩ የሴት ፊት ሳያዩና ዓለምን ሳያውቁ ነው የኖሩት። በትግራይ ሽሬ ዘለጋሶ የተባለውን ትልቅ ገዳም ቆርቁረው በዚያው ዐርፈው ተቀብረዋል። ከአቡነ ገብረ መስቀል ዘለጋሶ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳንና ቅዱሳን በዓላት።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #አቡነ_ፄዋለ_ጽድቅ፡- ይኸውም ቅዱስ አባት ቀድሞ መጥቆራ ተብሎ ይጠራ የነበረ አጋንንት የነበረ ነው፡፡ አባቱም "ፈረጎ" የተባለ የአየር አጋንንት ሲሆን እናቱን ደፍሮ ተገናኛትና መጥቆራ ተወለደ፡፡ እርሱም እጅግ ኃይለኛ ነበርና እነ አቡነ ተክለሃይማኖትንና አቡነ ዜና ማርቆስን ሳይቀር በእጅጉ ይፈትናቸውና ይበረታባቸው ነበር፡፡ አቡነ ተክለሃይማኖትና አቡነ ዜና ማርቆስም በጸሎታቸው ወደ እግዚአብሔር ለምነው በመስቀሉ ኃይል ድል ካደረጉት በኋላ ወደ ሰው አርአያነት እንዲለወጥ አድገውት አመንኵሰው ለታላቅ የቅድስና ደረጃ አብቅተውታል፡፡ ስሙንም "አቡነ ፄዋለ ጽድቅ" አሉት፡፡ እርሱም በጾም በጸሎት ተወስኖ በእጅጉ በታላቅ ተጋድሎ ኖሮ ከብቃት ደረጃ ላይ ከደረሰ በኋላ በሞት ሊያርፍ ሲል ጌታችን ተገልጦለት ታላቅ ቃልኪዳን ገብቶለታል፡፡ በሀገራችን በስሙ ቤተ ክርስቲያን ተሠርቶለት ጽላት ተቀርጾለት ይገኛል፡፡ ከአቡነ ፄዋለ ጽድቅ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከቱን ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን። ምንጭ፦ ከገድላት አንደበት።                              ✝ ✝ ✝ ❤ #እጨጌ (እጨ) #አቡነ_ዮሐንስ_ዘጠገሮ፦  ጻድቁ አባታችን የተወለዱት በኢየሩሳሌም አውራጃ ልዩ ስሙ ሳሬራ በሚባል ቦታ ነው፡፡ የካቲት 28 ቀን ተፀንሰው ህዳር 28 ቀን ተወለዱ፡፡ ነገር ግን በዓለ የልደታቸው በዓል የሚከበረው ከወራዊ በዓላቸው ጋራ ኅዳር 29 ቀን ነው።  አባታቸው ድላሶር እናታቸው እምነ ጽዮን ይባላሉ፡፡ ሲወለዱ በወላጆቻቸው ቤት ውስጥ ብርሃን ወርዷል፡፡ ወላጆቻቸውም እግዚአብሔርን የሚፈሩ ደጋግ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ አባታችን ገና በተወለዱ በ5 ዓመታቸው ወላጆቻቸው ወደ እግዚአብሔር ቤት ይዘዋቸው የእመቤታችንን ሥዕል ተመልክተው በደስታ ተመልተው ሳቁ፡፡ አምላክን የወለደች የብርሃን እናቱ እመቤታችንም ከምሥሉ ወጥታ "በምን አውቀኸኝ ነው?" ብላ አቅፋ ሳመችውና "ከእንግዲ ወዲህ የልጄ አገልጋይ ትሆናለህ ኑሮህም እንደ መላእክት ይሆናል በአንተ ምክንያት ብዙ ሰዎች ይድናሉ በምድር ላይም 500 ዓመት ትኖራለህ…" ብላ ባርካው ተሰወረች፡፡ ❤ ከዚያችም ቀን ጀምሮ አባ ዮሐንስ ለክርስቶስ ተላልፎ ተሰጠ፡፡ 50 ዓመትም በበረሃ ሲጋደል ኖሮ ከ50 ዓመት በኋላ በደመና ተጭኖ በመልአኩ በቅዱስ ገብርኤል መሪነት ወደ ቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ መጡ፡፡ ጻድቁ አባታችን በአቡነ ተክለሃይማኖት ዘመን መጨረሻ የመጡ ሲሆን ምንኵስና ከደብረ ሊባኖስ ገዳም ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት ተቀብለው በዚያው በድብረ ሊባኖስ ገዳም ለ50 ዓመት በጾምና በጸሎት በተጋድሎ ኖዋል፡፡ ከዚኽም በኋላ አባ ዮሐንስ ወደ ተዘጋጀላቸው ምድር በቅዱስ ገብርኤል አሳሳቢነት ወደ ጠገሮ መጡ፡፡ ይኽም ጠገሮ ያለው ገዳማቸው በሰሜን ሸዋ በመንዝና ይፋት ክልል መዘዞ በሚባል ቦታ ሲደርሱ በእግር አንድ ሰዓት ከተጓዙ በኃላ ይገኛል፡፡ ❤ ሕዝቡ በተለምዶ እጨ ዮሐንስ እያለ ይጠራቸዋል እንጂ ስማቸው እጨጌ ዮሐንስ ነው፡፡ አቡነ እጨጌ ዮሐንስ መስቀል ከሰማይ የወረደላቸው ታላቅ አባት ናቸው፡፡ መስቀሉም ሁልጊዜ ተአምር ይሠራል፡፡ በልደታቸው ቀን ኅዳር 29 ቀን መስቀሉ ከመቅደሱ ወጥቶ በካህናቱ ታጅቦ ወደ ጸበሉ ሲወርድ ከየት እንደመጣ ሳይታሰብ ደመና መጥቶ ከመስቀሉ ላይ ብቻ እረቦና እንደ ጃንጥላ ተዘርግቶ አብሮ ወደ ጸበሉ ይወርዳል፡፡ እዛው ቆይቶ መስቀሉ ሲመለስም አብሮ አጅቦ ይመለስና መስቀሉ ቤተ መቅደስ ውስጥ ሲገባ ደመናው ወዴት እንደተበተነ ሳይታወቅ ይጠፋል፡፡ ይህ በዘመናችንም ጭምር እየታየ ያለ ታላቅ ተአምር ነው፡፡  ❤ አባታችን በታላቀ ተጋድሎ ሣሉ ሰይጣን የሀገሩን ሰዎች በጠላትነት እንዲነሡባቸው አደረገ፡፡ ሰዎቹም አባታችንን እንዴት እንደሚያጠፏቸው ይማከሩ ጀመር፡፡ ሊገድሏቸው ፈልገው ቅድስናቸው በሁሉ ዘንድ የታወቀ ነውና ፈሩ፡፡ ከዚህም በኋላ "ለምን ከመንደራችን ከወንድ ያረገዘች ሴት ፈልገን እሳቸው አስረገዟት ብለን በሐሰት እንከሳቸው?" ብለው ተማከሩ፡፡ ብዙ ወርቅና ብርም ለአንዲት ሴት ሰጥተው በሐሰት ከእርሱ አርግዣለሁ ብላ እንድትመሰክር አደረጓት፡፡ አባታችንም በሕዝብ ፊት በሐሰት ተከሰሱ፡፡ ጻድቁም "አንቺ ሴት ከእኔ ነው ያረገሽው?" አሏት እርሷም "አዎ ከአንተ ነው ልትክድ ነው እንዴ?" አለቻቸው፡፡ አባታችንም በዚህ አዝነው "በአንቺና በእኔ መካከል እግዚአብሔር ይፍረድ" ሲሉ ያች ሴት ወዲያው ለሁለት ተሰንጥቃ ሞተች፡፡ የአገሩ ሰዎችም እጅግ ፈሩ፡፡ አባታችንም ምድሪቱን እረገሟት፡፡ "የተዘራው ዘር አይብቀልብሽ፣ የተተከለው አይፅደቅ፣ ብርድና ውርጭ ይፈራረቅብሽ" ብለው እረግመዋት በደመና ተጭነው ወደ ሰሜን ጎንደር እስቴ ጉንደ ተክለተሃማኖት ሔዱ፡፡ ❤ አቡነ ዮሐንስ በመላው ኢትዮጵያ ወንጌልን እየተዘዋወሩ ያስተማሩ ሲሆን ከቅድስናቸው የተነሣ በፀሐይ ላይ 50 ዓመት፣ በጨረቃ ላይ 50 ዓመት፣ በደመና ላይ 50 እንዲሁም ዓለምን በክንፋቸው በመዞር በደመና ላይ 50 የኖሩ ከሰው ተወልደው ከመላእክት የተደመሩ ታላቅ ጻድቅ ናቸው፡፡ በይፋት ጠግሮ በዓለወልድ፣ በአፋር አዘሎ፣ በመንዝ ፍርኩታ ኪዳነምሕረት፣ በደብረ ሊባኖስ፣ በጎንድ ተክለ ሃይማኖት በሌሎችም ቦታዎች በመዘዋወር በታላቅ ተጋድሎ ኖረዋል፡፡

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤            ❤ #ኅዳር ፳፰ (28) ቀን። ❤ እንኳን ለአገረ ኒቅዮስ ኤጲስቆጶስ #ለቅዱስ_ሰረባሞን ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላም አደረሰን።                             ✝ ✝ ✝ ❤ #የአገረ_ኒቅዮስ_ኤጲስቆጶስ_ቅዱስ_ሰረባሞን፦ ይህም ቅዱስ በኢየሩሳሌም አገር ከሌዊ ነገድ ለሆነ ለእስጢፋኖስ ከዘመዶቹ ውስጥ ነው። የአባቱም ስም አብርሃም ነው እርሱ የሌዊ ልጅ የዮሴፍ ልጅ ለስምዖን ወንድም ለእስጢፋኖስ እናት ወንድሟ የሆነ ነው። በተወለደም ጊዜ በአባቱ ስም ስምዖን ብለው ጠሩት አባቱም ሲሞት ክርስቲያን ይሆን ዘንድ ወደደ። ከእግዚአብሔርም የታዘዘ መልአክ ተገልጸለትና ወደ ኤጲስቆጶስ አባ ዮሐንስ እንዲሔድ አዘዘወው እንዳዘዘውም ሔደ። እርሱም የመድኃኒታችንን የክርስቶስን ሰው የመሆኑን ምስጢር ገለጠለት ግን ዘመዶቹ የሆኑ አይሁድን ስለፈራ በኢየሩሳሌም አገር የክርስትና ጥምቀት ሊአጠምቀው አልደፈረም። ❤ ኤጲስቆጶሱም ስለርሱ ምን እንደሚያደርግ ሲያስብ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተገልጣለት ወደ እስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ቴዎናስ እንዲልከው አዘዘችው። ሰረባሞንም እየተጓዘ ሳለ እንሆ የእግዚአብሔር መልአክ ቀድም ብሎ በሰው አምሳል ወደ ቴዎናስ ቀርቦ ስለ ቅዱስ ሰረባሞን አስረዳው ሰረባሞንም በደረሰ ጊዜ የእግዚአብሔርን ሕግ አስተምሮ የከበረች የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው። ❤ ከዚህም በኋላ ከእስክንድርያ ከተማ ውጭ በሆነች በአባ ሳዊሮስ ገዳም ውስጥ መነኰሰ አባ ቴዎናስም በዐረፈ ጊዜ በእርሱ ፈንታ አባ ጰጥሮስ ተሾመ። ያን ጊዜም መልክተኞችን ልኮ ይህን አባ ሰረባሞንን ወደርሱ አስመጥቶ በሊቀ ጵጵስናው ሥራ እንዲራዳው አደረገ። ከዚህም በኋላ ኒቅዮስ ለሚባል አገር ኤጲስቆጶስነት ሾመው። ብዙዎች አብያተ ክርስቲያናትም በእርሱ ደስ አላቸው እግዚአብሔርም በእጆቹ ድንቆች ተአምራትን አደረገ በአገሩ አቅራቢያ ሰዎች የሚያመልኳቸው የጣዖት ቤቶች ነበሩ ያጠፋቸውም ዘንድ እግዚአብሔርን ለመነው በዚያንም ጊዜ ምድር አፏን ከፍታ ወጠቻቸውና በቦታው ላይ ባሕር ሁኖ ሸፈናቸው። እግዚአብሔርም በአገረ ስብከቱ ጣዖታትን ደመሰሰ ዳግመኛም አብን ወልድ መንፈስ ቅዱስ አንድ አካል የሚያደርግ የሰባልዮስን ስድብ አስወገደ። ❤ ዲዮቅልጥያኖስም ክዶ ጣዖታትን በአመለከ ጊዜ ቅዱስ ሰረባሞን የአማልክትነሰ አምልኮ እንደሚሽር ነገሩት እርሱም ሰምቶ ተቆጣ ወደርሱም እንዲአመጡት አዘዘ ሲወስዱትም ከንጉሥ መልክተኞች ጋር እስክንድርያ ከተማ ደረሰ ሊቀ ጳጳሳት ጴጥሮስም ወደርሱ መጣ ከእርሱም ጋር ቡዙ ካህናት ነበሩ ሰላምታም ሰጡት ፊቱም እንደ እግዚአብሔር መልአክ ፊት ብሩህ ሁኖ አዩት። ወደ ንጉሡም በደረሰ ጊዜ በተለያዩ በብዙ ዓይነት ሥቃይ አሰቃየው ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ያለ ጥፋት በጤንነት አስነሣው። ይህንም ድንቅ ሥራ አይተው ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብዙዎች አመኑ። ❤ ሕዝቡ ሁሉ በእርሱ ምክንያት በጌታችን እንዳያምኑ ንጉሥ ፈርቶ የእንዴናው ገዥ አርያኖስ ወዳለበት ወደ ላይኛው ግብጽ ሰደደው በዚያ እንዲአሠቃየውና ራሱንም በሰይፍ እንዲቆርጥ በዚያንም ወቅት መኰንኑ አርያኖስ የኒቅዮስ ከተማ ወደብ አቅራቢያ በመርከብ ውስጥ ነበር። መርከቢቱም ቆመች ከቦታዋም ሊአንቀሳቅሱዋት አልተቻላቸውም ቅዱስ ሰረባሞንንም አውጥተው ለአገሩ ደቡብ ወደ ሆነ ቦታ ወስደው በዚያ ራሱን በሰይፍ ቆረጡት ምዕመናንም መጥተው ሥጋውን ወስደው በክብር ገንዙትና በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩት ከሥጋውም ድንቆች ተአምራት ሆኑ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ አባት በቅዱስ ሰረባሞን ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የኅዳር 28 ስንክሳር።                              ✝ ✝ ✝ ❤ "#ሰላም_ለከ_ለቀዳሜ_ሰማዕተ_ዘመዱ። ወፈጻሜ ስምዕ ሱታፌ ክበዱ። #ሰረባሞን ለዕሌከ አመ ዓላውያን ሰደዱ። ሶበ ርእዩ ሥዕለ ፈጣሪ ለስነ ገጹከ በዓውዱ። ታሕተ እገሪከ አናብስት ሰገዱ"። ሊቁ አርከ ሥሉስ (አርኬ) #የኅዳር_28።                                                         ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ "ፍታሕ ፍትሕየ ወባልሐኒ። ወበእንተ ቃልከ አሕይወኒ። ርኁቅ ሕይወት እምኃጥአን። መዝ 118፥154-155። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ13፥10-18።

✨✨✨በዓለ ዕረፍቱ ለአቡነ ሀብተማርያም ✨✨✨
+9
✨✨✨በዓለ ዕረፍቱ ለአቡነ ሀብተማርያም ✨✨✨