ar
Feedback
የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

الذهاب إلى القناة على Telegram

ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።

إظهار المزيد
2 640
المشتركون
+124 ساعات
+87 أيام
+5830 أيام
أرشيف المشاركات
🔴#ስንክሳር መስከረም_24 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም ሃያ አራት ኢትዮጵያዊቷ #ቅድስት_ክርስቶስ_ሠምራ ወደ ደብረ ሊባኖስ የገባችበት፣ ከላይኛው ግብጽ የሆነ ቅዱስ አባት #መነኰስ_ጎርጎርዮስ ያረፈበት እና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመረጣቸው ከሰባ ሁለቱ አርድእት ለአንዱ #ሐዋርያ_አድሊጦስ የምስክርነቱ መታሰቢያ ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅድስት_ክርስቶስ_ሠምራ መስከረም ሃያ አራት ኢትዮጵያዊቷ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ወደ ደብረ ሊባኖስ የገባችበት ነው። ቅድስት እናት ክርስቶስ ሠምራ ቅንነቷ፣ ደግነቷና ቅድስናዋ እጅግ የበዛ ነው። አንድ ቀን ግን ገና በትዳር ውስጥ እያለች ከአገልጋዮቿ አንዷን ትጠራትና ታዛታለች። ያቺ አገልጋይ ግን የታዘዘችውን ጀሮ ዳባ ልበስ ብላ ሳትታዘዛት ትቀራለች። ደጋግማ ብትነግራትም ልትሰማት አልቻለችም። ያን ጊዜ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ልትገስጻት ብላ ጠጠር ብትወረውርባት ያች አገልጋይ ወድቃ ሞተችባት። ቅድስቲቱ እጅግ ደንግጣ አለቀሰች። የምታደርገውንም አጣች። ወዲያው ግን ፈጠን ብላ: ወገቧን ታጥቃ ትጸልይ ጀመረች። "ጌታየ ሆይ! ከሞት አስነሳልኝና ዓለምን ትቼ በቀሪ ዘመኔ አንተን አገልለግልሃለሁ" ብላ ፈጣሪን በብዙ እንባ ተማጸነችው:: ያን ጊዜም አገልጋዩዋ ከሞት ተነሳችላት። ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ጊዜን አላጠፋችም። ልጆቿን በቤት ትታ ሃብትን ብረቷን ንቃ አንድ ልጇን አዝላ ቤቷን እንደ ተከፈተ ትታው ወደ ገዳም ወጣች። በዚህ ዕለትም (መስከረም 24 ቀን) ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም ገባች። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ጎርጎርዮስ_ዘላዕላይ_ግብጽ ዳግመኛም በዚህች ቀን ከላይኛው ግብጽ የሆነ ቅዱስ አባት መነኰስ ጎርጎርዮስ አረፈ ። የዚህም የቅዱስና የተመሰገነ ጎርጎርዮስ ወላጆቹ ደጎች ናቸው በዚህ ዓለም ገንዘብም እጅግ ባለጸጎች ነበሩ ይህን ልጃቸውን ጎርጎርዮስንም በበጎ አስተዳደግ አሳደጉት ። መንፈሳዊ የሆነ የቤተ ክርስቲያን ትምህርትን ሁሉ ሥጋዊም የሆነ ጥበብንና ቋንቋን አስተማሩት ። ከዚህም በኋላ የሀገራቸው ኤጲስቆጶስ ወደ ሆነ ወደ አባ ይስሐቅ ወሰዱት እርሱም እጁን በላዩ ጭኖ አናጒንስጢስነት ሾመው ። ከዚህም በኋላ ወላጆቹ ሊአጋቡት አሰቡ እርሱ ግን ይህን ሥራ አልወደደም ሁለተኛም ወደ ጳጳስ ወስደውት ፍጹም ዲቁናን ተሾመ ወደ አባ ጳኲሚስም አዘውትሮ በመሔድ ከእርሱ የእግዚአብሔርን ሕግ የሚማር ሆነ ከወላጆቹም ብዙ ገንዘብን ወስዶ ወደ አባ ጳኲሚስ አቅርቦ በገዳማቱ ለሚሠሩ ሕንፃዎች ሥራ ያደርግለት ዘንድ ብዙ ልመናን ለመነው እርሱም ተሳትፎ እንዲሆንለት ለሕንፃ ቤተ ክርስቲያንና ለመነኰሳት ቤት መሥሪያ አደረገለት ። ከዚህም በኋላ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዓለምን ትቶ ጥሪቱንና ገንዘቡን ሁሉ ንቆ በመተው ወደ ቅዱስ አባ ጳኲሚስም ሒዶ የምንኲስና ልብስን ለብሶ በጾም በጸሎት በመትጋት በመስገድ ከትሕትና፣ ከቅንነት፣ ከፍቅር ጋር ይጋደል ጀመረ አርአያነቱንና ምሳሌነቱን በአዩ ጊዜ ከእርሱ ፈሪሀ እግዚአብሔርን ተምረው አመንዝራዎች የከፋ ሥራቸውን እስከ ተውና ንስሐም ገብተው ንጹሐንም እስከ ሆኑ ድረስ ተጋደሉ ። ከአባ ጳኲሚስም ዘንድ ዐሥራ ሦስት ዓመት ኖረ ። አባ መቃርስም ወደ አባ ጳኲሚስ በመጣ ጊዜ ሰውነቱን በማድከም ታላቅ ተጋድሎን እየተጋደለ ጥቂት ቀኖች ኖረ ከዚያም በኋላ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሊመለስ ወደደ አባ ጳኲሚስም ከአባ መቃርስ ጋር እንዲሔድ አባ ጎርጎርዮስን አዘዘው እርሱም አብሮ ሔደ በእርሱም ዘንድ ብዙ ዘመናት ኖረ ። ከዚህም በኋላ በዋሻ ብቻውን ይኖር ዘንድ እንዲአሰናብተው የከበረ አባ መቃርስን ለመነው እርሱም እንደ ወደድክ አድርግ አለው ። ያን ጊዜ ወደ ተራራ ሒዶ ታናሽ ዋሻ ቆርቁሮ በውስጧ ሰባት ዓመት ኖረ አባ መቃርስም በየዓመቱ ሁለት ጊዜ መጥቶ ይጎበኘዋል አንደኛ ለከበረ የልደት በዓል ሁለተኛ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተነሣባት በትንሣኤ በዓል ቀን ከርሱ ጋርም ሥጋውንና ደሙን ተቀብሎ ወደ ቦታው ይመለሳል ። አባ መቃርስም ስለ ሥራው ሁሉ ይጠይቀዋል እርሱም የሚያየውንና በእርሱ የሆነውን ሁሉ ይገልጽለታል አባ መቃርስም ሊሠራው የሚገባውን የምንኲስና ሥራን ይሠራ ዘንድ ያዘዋል ። በተጋድሎም ውስጥ ሃያ ሁለት ዓመታት ሲፈጽሙለት ከዚህ የድካም ዓለም ያሳርፈው ዘንድ እግዚአብሔር ፈቅዶ መልአኩን ላከለት እርሱም ከሦስት ቀን በኋላ ከዚህ ከኀላፊው ዓለም ወጥተህ ወደ ዘላለም ሕይወት ትገባለህ አለው ። አባ ጎርጎርዮስም በአስቄጥስ ገዳም ያሉ አረጋውያንን አስጠራቸውና ተሳለማቸው በጸሎታቸውም እንዲአስቡት ለመናቸው እነርሱም ደግሞ በእግዚአብሔር ዘንድ እንዲአስባቸው ለመኑት ከሦስት ቀንም በኋላ አርፎ ወደ ዘላለም ሕይወት ገባ ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ሐዋርያ_አድሊጦስ (ከሰባ ሁለቱ አርድእት) በዚህችም ቀን ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመረጣቸው ከሰባ ሁለቱ አርድእት ለአንዱ ሐዋርያ አድሊጦስ የምስክርነቱ መታሰቢያ ነው ። ይህም ሐዋርያ ትውልዱ ከአቴና አገር ከታላላቆቿና ከምሁራኖቿ ነው እርሱም ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ አገለገለውም ። አጽናኝ የሆነ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ በሃምሳኛው ቀን ከተቀበለ በኋላ ወደ ብዙዎች አገሮች ሒዶ ሕይወት የሆነ ወንጌልን ሰበከ መግኒን ወደሚባልም አገር ደርሶ በውስጧ የከበረ ወንጌልን ሰበከ የብዙዎችንም ልቦና ብሩህ አድርጎላቸው ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ። የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው ሕይወት የሆኑ የወንጌልንም ትእዛዞች አስተምሮ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው ። ከዚህም በኋላ ከእሳቸው ዘንድ ወጥቶ ወደ አቴና አገር ተመለሰ በውስጧም የከበረ ወንጌልን አስተማረ በዚያን ጊዜም በደንጊያ ወገሩት ጽኑዕ የሆነ ሥቃይንም አሠቃዩት ። ከዚህም በኋላ ከእሳት ውስጥ ወረወሩትና በዚያ ተጋድሎውንና ምስክርነቱን ፈጽሞ የሕይወት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን ።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መስከረም_23 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም ሃያ ሦስት በዚህች ዕለት የክርስቶስ ሙሽራው የሆነች #ቅድስት_ቴክላ መታሰቢያ በዓሏ ነው፤ ዳግመኛም #ቅዱሳን_አውናብዮስ_እና_እንድርያስ በሰማዕትነት አረፉ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅድስት_ቴክላ_የክርስቶስ_ሙሽራው መስከረም ሃያ ሦስት በዚህች ዕለት የክርስቶስ ሙሽራው የሆነች ቅድስት ቴክላ የመታሰቢያ በዓሏ ነው፡፡ ይህችውም ቅድስት ለሐዋርያው ለቅዱስ ጳውሎስ ረድእ ሆና ያገለገለች ታላቅ ሐዋርያዊት እናት ናት፡፡ የመቄዶንያ ሀገር ባለጸጎች የነበሩት ወላጆቿ ጣዖት አምላኪ ነበሩና በሕጋቸውና በሥርዓታቸው አሳደጓት፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ወደዚህች ሀገር ገብቶ ቅዱስ ወንጌልን ሰበከ፡፡ ቅድስት ቴክላም ትምህርቱን በሰማች ጊዜ በቤቷ ሆና ሳትበላና ሳትጠጣ 3 ቀን ቆየች፡፡ ከዚህም በኋላ ለሚጠብቃት ዘበኛዋ እንዳይናገርባት በማለት የወርቅ ወለባዋን ሰጠችውና ወደ ቅዱስ ጳውሎስ ሄደች፡፡ እርሱም በደስታ ተቀብሎ የክርስቶስን ሃይማኖት አስተማራት፡፡ በማግሥቱም ቅድስት ቴክላን እናቷ ስትፈልጋት ከቅዱስ ጳውሎስ እግር ሥር አገኘቻት፡፡ ከዚያም ወደ መኰንኑ ዘንድ ሄዳ ልጇ ክርስቲያን መሆኗን በመናገር ከሰሰቻትና ለመኰንኑ አሳልፋ ሰጠቻት፡፡ መኰንኑም ሁለቱን ቅዱስ ጳውሎስንና ቅድስት ቴክላን እንዲያመጧቸው ወታደሮቹን ላከ፡፡ ካመጧቸውም በኋላ መጀመሪያ ቅዱስ ጳውሎስን ወደ እሳት ወረወሩት፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር በተአምራት አዳነው፡፡ ቅድስት ቴክላን ግን ለሀገሩ ልጆች መቀጣጫ ትሆን ዘንድ መኰንኑ ሰውን ሁሉ ከሰበሰበ በኋላ ወደ እሳቱ እንዲወረውሯት አዘዘ፡፡ እርሷ ግን በመስቀል ሦስት ምልክት ካማተበች በኋላ በራሷ ፈቃድ ማንም ሳይነካት ዘላ ከእሳቱ ውስጥ ገባች፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሔር ጥበቃ ልክ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ እርሷም ማንም ሳያያት ከእሳቱ ውስጥ ወጥታ ቅዱስ ጳውሎስ ካለበት ደረሰች፡፡ የራሷንም ጸጉር ቆርጣ በእርሱም ወገቧን ታጥቃ ቅዱስ ጳውሎስን ተከተለችው፡፡ መኰንኑም በሕይወት መኖሯን ሰምቶ ድጋሚ አስፈልጎ አስያዛትና ሃይማኖቷን እንድትለውጥ አስገደዳት፡፡ እሺ እንዳላለችው ባወቀ ጊዜ በተራቡ አንበሶች ጉድጓድ ውስጥ ጨመራት ነገር ግን አንበሶቹ ሰግደው የእግሯን ትቢያ ሲልሱላት ተመለከተ፡፡ መኰንኑም ይህንን በተመለከተ ጊዜ እርሱና ወገኖቹም ሁሉ አምነው ተጠመቁና የክርስቶስ መንጋዎች ሆኑ፡፡ ቅድስት ቴክላም የጌታችንን ወንጌል በማስተማርና ቅዱስ ጳውሎስንም በማገልገል ብዙ ከተጋደለች በኋላ መስከረም 27 ቀን ዐርፋለች፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱሳን_አውናብዮስ_እና_እንድርያስ ዳግመኛም በዚች ቀን ቅዱሳን ጻድቃን መነኰሳት አውናብዮስና እንድርያስ በሰማዕትነት አረፉ። እሊህ ቅዱሳንም ከልዳ ሀገር ከታላላቆቹ ተወላጆች ናቸው ከታናሽነታቸውም በአምላካዊ ምክር ተስማምተው በሶርያ ውስጥ ከሚገኙ ገዳማት ወዳንዱ ገዳም ሒደው መነኰሳት ሆኑ። ከዚህም በኋላ ወደ ከበረ ወደ ተመሰገነ አባ መቃርስ ሔዱ ደቀ መዛሙርቱም ሁነው ታዘዙለት ምክሩንም በመቀበል በጾም በጸሎት በገድል ሁሉ ተጠምደው የሚኖሩ ሆኑ በእንዲህ ያለ ሥራም በዚያ ሦስት ዓመት ኖሩ በጎ የሆነ ተጋድሎአቸውና የአገልግሎታቸው ዜና በተሰማ ጊዜ አውናብዮስን መርጠው ኤጲስቆጶስነት፣ እንድርያስን ቅስና ሾሙአቸው በበጎ አጠባበቅም የክርስቶስን መንጋዎች ጠበቋቸው። ከዚህም በኋላ ሥጋቸውን ፈጽሞ እስከ አደከሙ ድረስ ተጋድሎአቸውንና አገልግሎታቸውን እጅግ አበዙ። ከሀ*ዲ ንጉሥ ዮልዮስም ስለእርሳቸው በሰማ ጊዜ ወታደሮች ልኮ ወደርሱ አስቀርቦ የክብር ባለቤት ክርስቶስን ክደው ወደ ረከሰች አምልኮቱ እንዲገቡ አዘዛቸው ያን ጊዜ እርሱንና የረከሱ ጣዖ*ታቱን ረገሙ እርሱም ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃያቸው ወደ ብዙ ክፍልም ቆራርጦ ከፋፈላቸውና ነፍሳቸውን በእግዚአብሔር እጅ ሰጡ። እያንዳንዳቸውም ሦስት ሦስት አክሊላትን ተቀበሉ አንዱ በገድል ስለ መጸመድና ስለ ምንኲስና ዋጋ፣ ሁለተኛው ስለ ክህነት አገልግሎት፣ ሦስተኛው ደማቸውን ስለ ማፍሰሳቸው ነው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

በአንዲት ዕለትም የጣዖቶቻቸው በዓል በሆነ ጊዜ በሽልማት ሁሉ ሸለሙአቸው በመብራቶችና በሥዕሎችም ዘንባባም አስጌጧቸው በማግሥቱም መጥተው በዓላቸውን ለማክበር በዋዜማው አዘጋጅተው የጣዖታቱን ቤቶች ዘግተው ወደ ቤታቸው ገቡ። ቅዱስ ዮልዮስም ጣዖታቱን ያጠፋቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ለመነ በዚያን ጊዜም ጌታችን መልአኩን ልኮ የጣዖታቱን ራሶቻቸውን ቆረጠ ፊቶቻቸውንም በፍም አጠቆረ ሽልማታቸውንና ዘንባባውን የጣዖቱን ቤት ሥርዓት ሁሉ አቃጥሎ አጠፋ። ማግሥትም በሆነ ጊዜ ለአማልክቶቻቸው እንደ ልማዳቸው በዓልን ሊአከብሩላቸው በከበሩ ልብሶች ተሸልመው ሲመጡ ተጐሳቁለው ጠፍተው አዩአቸው የጣዖቶቻቸውን ድካማቸውን አወቁ። እንዲህም አሉ አማልክቶቻችን ራሳቸውን ማዳን ያልቻሉ እኛን ያድኑ ዘንድ እንዴት ይችላሉ ይህንንም ተናግረው ከአትሪብ መኰንን ጋር በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአንድነት አመኑ። ከዚያም ደግሞ ቅዱስ ዮልዮስ ጡዋ ወደሚባል አገር ሔደ ከርሱም ጋር የገምኑዲ መኰንንና የአትሪብ መኰንን አሉ የጡዋ መኰንን ወደ ሁነ ወደ እስክንድሮስ ቀርቦ በፊቱ ክብር ይግባውና በጌታችን ስም ታመነና እንዲህ አለው ገድሌን ፈጽምልኝ ራሴንም እንዲቆርጡ እዘዝና የምስክርነት አክሊልን ተቀብዬ ወደ ክብር ባለቤት ወደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ እንድሔድ። እስክንድሮስም እኔ አላሠቃይህም በአንተ ላይም ምንም ክፉ ነገር አላደርግም አለው። ቅዱስ ዮልዮስም አምስት መቶ የሚሆኑ አገልጋዮቹን ሰይፎቻቸውን መዝዘው እስክንድሮስን እንዲአስፈሩት አዘዛቸው በዚያንም ጊዜ በእስክንድሮስ ላይ ተነሥተው ለክብር ባለቤት ክርስቶስ ምስክሮቹ እንሆን ዘንድ የሁላችንም ራሶቻችንን እንዲቆርጡ ካላዘዝክ እኛ እንገድልሃለን አሉት። ዳግመኛም ርኵስ መንፈስ እንዲጫንበት ቅዱስ ዮልዮስ አዘዘው ወዲያውኑ በመኰንኑ በእስክንድሮስ ላይ ተጫነበት በዚያንም ጊዜ ራሶቻቸውን ይቆርጧቸው ዘንድ በጽሑፍ አዘዘ ሁሉንም ቅዱሳን ሰማዕታትን ቆረጧቸው። እሊህም ቅዱስ ዮልዮስ፣ ልጁም ቴዎድሮስ፣ የከበረ ወንድሙ ዮንያስ፣ አምስት መቶ አገልጋዮቹ የገምኑዲና የአትሪብ መኰንኖች ብዙዎች ሕዝቦችም የሁሉም ቁጥራቸው አንድ ሺህ አምስት መቶ ነው። በዚያች ቀን ከቅዱስ ዮልዮስ ጋር በሰማዕትነት የሞቱ ናቸው የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። የቅዱስ ዮልዮስን የልጁንና የወንድሙን ሥጋ አንሥተው ወደ እስክንድርያ አገር አደረሱ እርሱ በውስጧ ነዋሪ ሁኖ ነበርና ትውልዱ ግን አቅፋሐስ ከሚባል አገር ነው በአማረ ቦታ ውስጥም አኖሩአቸው። ከዚያም በኋላ ያማረች ቤተ ክርስቲያንን ሠሩላቸው ከእርሳቸው ታላላቅ የሆኑ ድንቆች ተአምራት ተደረጉ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መስከረም_22 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም ሃያ ሁለት በዚህች ቀን የፋርስ ንጉሥ የሳቦር ልጆች #የከበሩ_ኮቶሎስና_እኅቱ_አክሱ፣ #የከበረ_ዮልዮስ በሰማዕትነት ያረፉበት መታሰቢቸው ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ኮቶሎስና_እኅቱ_ቅድስት_አክሱ መስከረም ሃያ ሁለት በዚች ቀን የፋርስ ንጉሥ የሳቦር ልጆች የከበሩ ኮቶሎስና እኅቱ አክሱ በሰማዕትነት አረፉ። ለቅዱስ ኮቶሎስም ጣጦስ የሚባል ክርስቲያን ወዳጅ አለው ይህም ንጉሥ ሳቦር እሳትን የሚያመልክ ነው ብዙዎች ምእመናንን ስለሚያሠቃያቸው ክብር ይግባውና የክርስቶስን ስም ይጠራ ዘንድ በዚያ ወራት የደፈረ የለም። ይህም ጣጦስ በአንዲት አገር ላይ ገዥ ነበር እርሱ ክርስቲያን እንደሆነ በንጉሡ ዘንድ ወነጀሉት። ንጉሡም ስለርሱ የተነገረው እውነት እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ያረጋግጥ ዘንድ ሌላውን መኰንን ወደርሱ ላከ። ሁለተኛም ክርስቲያንን ያገኘ እንደሆነ ጽኑዕ ሥቃይ እንዲያሠቃይ አዘዘው። የንጉሥ ልጅ ኮቶሎስም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ወዳጁ ጣጦስ ወደአለባት ወደዚያች አገር ሔደ ያ መኰንንም በደረሰ ጊዜ ጣጦስን በንጉሥ እንደ ወነጀሉት እንዲሁ ክርስቲያን ሁኖ አገኘው በዚያን ጊዜም የእሳት ማንደጃ ሠርተው ጣጦስን እንዲአቃጥሉት አዘዘ ቅዱስ ጣጦስ ግን በመስቀል ምልክት በእሳቱ ላይ አማተበ እሳቱም የኋሊት ተመልሶ ጠፋ። ኮቶሎስም ይህን ተአምር በአየ ጊዜ እጅግ አድንቆ ጣጦስን ወንድሜ ሆይ ይህን ሥራይ እንዴት ተማርክና አወቅህ አለው። ጣጦስም ይህ ከሥራይ አይደለም ክብር ይግባውና ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት ይህ ድንቅ ተአምር እንጂ ብሎ መለሰለት። ኮቶሎስም እኔ በክርስቶስ የማምን ከሆንኩ እንደዚህ ልሠራ እችላለሁን? አለው ጣጦስም እንዲህ ብሎ መለሰለት በእርሱ ካመንክበት ከዚህ የሚበልጥ ተአምራት ታደርጋለህ። በዚያንም ጊዜ ቅዱስ ኮቶሎስ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ በዚያን ጊዜም ነበልባሉ እጅግ ከፍ ከፍ እስከሚል እሳቱን አነደዱ ቅዱስ ኮቶሎስም ቀረብ ብሎ በእሳቱ ላይ በመስቀል ምልክት አማተበ እሳቱም ወደ ኋላ ዐሥራ ሁለት ክንድ ተመለሰና ጠፋ። ከዚህም በኋላ መኰንኑ ወደ ንጉሥ ሳቦር ከመኰንኑ ከጣጦስና ከልጁ ከኮቶሎስ የሆነውን ሁሉ ጻፈ ንጉሡም ሰምቶ ጭፍራ ልኮ አስቀረባቸው የቅዱስ ጣጦስንም ራሱን በሰይፍ ቆረጠውና የሰማዕትነትን አክሊል ተቀበለ። ልጁን ቅዱስ ኮቶሎስን ግን ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃየውና ደግሞ እንዲአሠቃየው ለሌላ መኰንን ሰጠው እርሱም ብዙ ካሠቃየው በኋላ አሠረው። እኅቱም አክሱ ወደ እሥር ቤት ወደርሱ መጣች ወደ ቀድሞ ሥራው እንዲመለስ ትሸነግለው ዘንድ አባቷ ልኳታልና። እርሱ ግን እኅቱን ገሠጻት መከራት የቀናች ሃይማኖትንም አስተማራት ያን ጊዜም ከስኅተቷ ተመልሳ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነች። ከዚህም በኋላ ወንድሟ ቅዱስ ኮቶሎስ ወደ አንድ ቄስ ላካት እርሱም የክርስትና ጥምቀትን በሥውር አጠመቃት። ወደ አባትዋም ተመልሳ እንዲህ አለችው አባቴ ሆይ ለእኔና ለወንድሜ ለኮቶሎስ የሆነው ላንተ ቢደረግልህ ይሻልሃል ክብር ይግባውና ሰማይና ምድርን በውስጣቸውም ያለውን ሁሉ ከፈጠረ ከጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ የለምና። ይህንንም ነገር አባቷ ከእርሷ በሰማ ጊዜ በእርሷ ላይ እጅግ ተቆጥቶ ነፍሷን በእግዚአብሔር እጅ እስከ ሰጠች ድረስ ጽኑዕ ሥቃይን እንዲአሠቃዩአት አዘዘ በዚህም ምስክርነቷን ፈጽማ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለች። ወንድሟን ቅዱስ ኮቶሎስን ግን በፈረሶች ጅራት ውስጥ አሥረው በተራራዎች ላይ አስሮጧቸው ሥጋውም ተቆራርጦ ተበተነ ነፍሱንም በፈጣሪው እጅ ሰጠ። የቀረ ሥጋውንም ወደ ሦስት ቆራርጠው የሰማይ ወፎች ይበሉት ዘንድ በተራራ ላይ ጣሉት በእንደዚህም ሁኔታ ምስክርነቱን ፈጽሞ የሕይወት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ወታደሮችም ሲመለሱ የሰማዕታትን ሥጋ ይወስዱ ዘንድ በሀገር አቅራቢያ ያሉ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን እግዚአብሔር አዘዛቸው እነርሱም በሌሊት ሔደው የቅዱሳን ሰማዕታትን ሥጋቸውን ወስደው በታላቅ ክብር ገነዙአቸው እንደ በረዶም ነጭ ሁነው አግኝተዋቸዋልና። የመከራው ወራትም እስቲፈጸም ድረስ በመልካም ቦታ አኖሩአቸው። ከዚያም በኋላ ያማረች ቤተ ክርስቲያን ተሠርታላቸው የቅዱሳን ሥጋቸውን በዚያ አኖሩ ከሥጋቸውም ድንቆች ተአምራት ተገለጡ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ዮልዮስ_በሰማዕትነት በዚችም ቀን የከበረ ዮልዮስ በሰማዕትነት ያረፈበት መታሰቢያው ነው። ይህም ቅዱስ አቅፋሐስ ከሚባል አገር ነው ክብር ይግባውና ጌታችንም ስለ ቅዱሳን ሰማዕታት ለሥጋቸው እንዲአስብ ገድላቸውንም እንዲጽፍ ሥጋቸውንም ገንዞ እየአንዳንዱን ወደ ሀገራቸው እንዲልክ ያቆመው ነው። እግዚአብሔርም በመኳንንቱ ልብ መታወርን ስለ አመጣ ለሰማዕታት ይህን ያህል በጎ ሥራ ሲሠራ ምንም ነገር አይናገሩትም ስለ ጣዖት አምልኮም አያስገድዱትም ነበር። ጽሕፈትም የሚያውቁ ሦስት መቶ አገልጋዮች አሉት እነርሱም የሰማዕታትን ገድላቸውን እየተከታተሉ ይጽፋሉ። በመሠቃየትም ሳሉ ሰማዕታትን ያገለግላቸዋል በቊስላቸውም ውስጥ መድኃኒት ያደርግላቸዋል ሰማዕታትም ይመርቁታል እንዲህ ብለውም ትንቢት ይናገሩለት ነበር። አንተም ክብር ይግባውና ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ደምህ ይፈስ ዘንድ አለህ ከቅዱሳን ሰማዕታትም ጋራ ትቈጠራለህ። የከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ የግዛቱ ዘመን በተፈጸመ ጊዜ ዮልዮስን ከቅዱሳን ሰማዕታት ከቁጥራቸው አንድ ሊአደርገው ወዶ ቅዱሳን ሰማዕታትም ትንቢት እንደተናገሩለት በመኰንኑ ፊት ስለ ከበረ ስሙ ይታመን ዘንድ ለግብጽ አገር ደቡብ ወደሆነች ወደ ገምኑዲ ወደ መኰንኑ አርማንዮስ እንዲሔድ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዘዘው። ወዲያውኑ ተነሥቶ ሔደ ከዚያም ደርሶ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ መኰንኑም ታላቅ ሥቃይን ብዙ ጊዜ አሠቃየው እግዚአብሔርም ያለ ጥፋት በጤና ያነሣው ነበር። ከዚህም በኋላ ምድር አፍዋን ከፍታ ጣዖታቱን ትውጣቸው ዘንድ ቅዱስ ዮልዮስ ክብር ይግባውና ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ወዲያውኑ አፍዋን ከፍታ ሰብዓ ጣዖታትን መቶ ሠላሳ የሆኑ ካህናቶቻቸውን ዋጠቻቸው። በዚያንም ጊዜ ቅዱስ ዮልዮስን አምጥተው ለአማልክት በግድ እንዲአሰግዱት መኰንኑ አዘዘ ጣዖታቱን ግን ከካህናቶቻቸው ጋር ጠፍተው አገኙአቸው በዚያ ያሉ ሕዝቦችም ይህን አይተው እጅግ አደነቁ። ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አመኑ መኰንኑ አርማንዮስም ጣዖታቱ ከካህናቶቻቸው ጋር እንደ ጠፉ በአየ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ። ከቅዱስ ዮልዮስም ጋር ወደ አትሪብ ሔደው በመኰንኑ ፊት ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ታመኑ የአትሪብ መኰንን ግን ቅዱስ ዮልዮስን እጅግ ጭንቅ የሆነ ሥቃይን አሠቃየው ክብር ይግባውና ጌታችንም ያለ ጥፋት ያነሣው ነበር።

ቆጵርያኖስም ወደ አንጾኪያ ከተማ በደረሰ ጊዜ ወሬው ተሰማ በአንጾኪያም ከተማ ከሀገር ታላላቆች ተወላጅ የሆነ አንድ ጐልማሳ አለ እርሱም ላህይዋ የሚያምር አንዲቷን ድንግል ብላቴና ተመኛት ወደ ቤተ ክርስቲያን በምትሔድ ጊዜ እያያት በእርሷ ፍቅር ልቡ እንደ እሳት ተቃጠለ በምንም በምን ሊአገኛት አልተቻለውም ገንዘብ በመስጠትም ቢሆን ወይም በማስፈራራት ወይም በሥ*ራይ ሥራ አልሆነለትም። የቆጵርያኖስም ወሬው በተሰማ ጊዜ እርሱ ከሥራ*የኞች ሁሉ እንደሚበልጥ ስለርሱ ተነግሮአልና ያም ድንግል ዮስቴናን የተመኛት ጐልማሳ ወደ ቆጵርያኖስ ሒዶ በልቡ ያለውን ጉዳዩን ድንግሊቱን ዮስቴናን እንደተመኛትና እርሷን ማግኘት እንደተሳነው ነገረው ቆጵርያኖስም እኔ የልብህን ፍላጎት እፈጽምልሃለሁ አትዘን አለው። ከዚያም በኋላ ያን ጊዜ ዮስቴናን ወደርሱ ያመጧት ዘንድ በሥራ*ዩ የአጋንንትን ሠራዊት ወደርሷ ላከ እነዚያም አጋንንት ወደርሷ በቀረቡ ጊዜ እርሷን መውሰድ አልቻሉም ከጸሎቷ የተነሣ ይቃጠላሉና እንዲህም ብዙ ጊዜ ላካቸው ግን ወደርሱ ሊያመጧት አልቻሉም ቆጵርያኖስም ሁሉንም አጋንንት ጠርቶ ድንግል ዮስቴናን ካላመጣችሁልኝ እኔ ከእናንተ ተለይቼ ክርስቲያን እሆናለሁ አላቸው። ከዚህም በኋላ የሰይጣናት አለቃ ሊሸነግለው አሰበ አንዱንም ሰይጣን ከሰይጣናት ውስጥ በዮስቴና አምሳል ተመስሎ ለቆጵርያኖስ እንዲታየው አደረገ። ሰይጣኑም አለቃው እንዳዘዘው እንዲህ አድርጎ ተዘጋጀ እነሆ አሁን የዮስቴናን መምጣት ለቆጵርያኖስ ነገረው እርሱም እውነት መስሎት እጅግ ደስ አለው ሊቀበላትም ተነሣ። በእርሷ አርአያ የተመሰለውንም ምትሐት በአየ ጊዜ የሴቶች እመቤት ዮስቴና መምጣትሽ መልካም ሆነ አለ ይህንንም ስሟን በጠራ ጊዜ ያ በእርሷ አምሳል የተመሰለ ሰይጣን እንደ ጢስ ሁኖ ተበተነ። በዚያንም ጊዜ የሽንገላው ምክንያት ምትሐ*ቱም ከንቱ እንደሆነ ቆጵርያኖስ አወቀ አስተዋለም በልቡም እንዲህ አለ። ስሟን በጠሩበት ቦታ እንደ ጢስ የሚበተኑ ከሆነ በፊቷ ሊቆሙ ሊሸነገሏትስ እንዴት ይቻላቸዋል ይህንንም ብሎ ወዲያውኑ የጥን*ቆላ መጻሕፍቶቹን አቃጠለ። ከዚህም በኋላ ወደ አንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ሒዶ የክርስትና ጥምቀትን ተጠምቆ የምንኲስና ልብስን ለበሰ ከጥቂት ቀኖችም በኋላ ዲቁና ሾመው። ዳግመኛም ቅስና ሾመው በትሩፋት ሥራና በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ከፍ ከፍ ባለ ጊዜ ለሀገሩ ምዕራብ ለሆነች ቅርጣግና ለምትባል አገር ኤጲስቆጶስ ይሆን ዘንድ ተገባው ያን ጊዜም ቅድስት ዮስቴናን ወስዶ ለደናግል ገዳም እመ ምኔት አደረጋት። በቅርጣግናም የቅዱሳን የአንድነት ስብሰባ በሆነ ጊዜ ከጉባኤው አባላት እርሱ አንዱ ነው። ከብዙ ወራት በኋላም ከሀ*ዲው ንጉሥ ዳኬዎስ ስለእነርሱ ሰማ ወደርሱም አስቀረባቸውና የክብር ባለቤት ክርስቶስን ክደው ለጣዖቶቹ እንዲሰግዱ አዘዛቸው። ትእዛዙንም ባልሰሙ ጊዜ ታላቅ ሥቃይን አሠቃያቸው ብዙ ሥቃይንም ከአሠቃያቸው በኋላ የቅዱስ ቆጵርያኖስንና የቅድስት ደንግል ዮስቴናን የሦስት ወንዶችንም ራሳቸውን አስቆረጠ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜንhttps://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መስከረም_21 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም 21 በዚህች ቀን #ብዙኃን_ማርያም (ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሃይማኖታዊ ውሳኔ ለማዘጋጀት ከሩቅም ከቅርብም የተሰባበሰቡት ቀን፤ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ዕፀ መስቀል በግሸን ደብረ ከርቤ የተቀመጠበት ዕለት ነው) እንዲሁም #ቅዱስ_ቆጵርያኖስና #ድንግሊቱ_ዮስቴና በሰማዕትነት ያረፉበትም ቀን ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ብዙኃን_ማርያም በቤተ ክርስቲያናችን ከሚዘከሩ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ክብረ በዓላት መካከል መስከረም ፳፩ ቀን የሚውለው በዓል ‹‹ብዙኃን ማርያም›› በመባል ይታወቃል፡፡ በዓሉ በሁለት ዐበይት ምክንያቶች ይከበራል፤ የመጀመሪያው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሃይማኖታዊ ውሳኔ ለማዘጋጀት ከሩቅም ከቅርብም የተሰባበሰቡት ቀን፤ ሁለተኛው ደግሞ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ዕፀ መስቀል በግሸን ደብረ ከርቤ የተቀመጠበት ዕለት መኾኑ ነው፡፡ ሁለቱንም ታሪኮች ከዚህ ቀጥለን እንመለከታቸዋለን፤ #ጉባዔ_ኒቅያ በ፫፻፳፭ ዓ.ም አር*ዮስ የሚባል መና*ፍቅ የእግዚአብሔር ወልድን የባሕርይ አምላክነት አልቀበልም በሚል ክህ*ደት እርሱ ተሰናክሎ ለሌሎችም መሰናክል ኾነ፡፡ ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት አር*ዮስ ክህ*ደቱን እንዲተው ቢመክሩትም ሊመለስ አልቻለም፡፡ ይህ የአር*ዮስ ክህ*ደትም በሊቃውንቱ መካከል መለያየትን ፈጥሯል፡፡ ጊዜው ታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ‹‹አብያተ ጣዖታት ይትአጸዋ አብያተ ክርስቲያናት ይትረኀዋ፤ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ! አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ!›› የሚል ዐዋጅ የነገረበት ወቅት ነበርና ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ በአር*ዮስ ክህ*ደት ምክንያት በኒቅያ የሃይማኖት ጉባኤ እንዲካሔድ በየአገሩ ላሉ ሊቃውንት መልእክት አስተላለፈ፡፡ በዚህም መሠረት ከሚያዝያ ፳፩ ቀን ጀምሮ እስከ መስከረም ፳፩ ቀን ድረስ ፳፫፻፵፰ (ሁለት ሺሕ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንት) ሊቃውንት በኒቅያ ተሰበሰቡ፡፡ ኒቅያ ለዚህ ጉባኤ የተመረጠችበት ምክንያትም ጳጳሱን ከማኅበረ ካህናቱ፤ ንጉሡን ከሠራዊቱ ጋር አጠቃላ ለመያዝ የምትችል ሰፊና ምቹ ቦታ ከመኾኗ ባሻገር ለኹሉም አማካይ ሥፍራ ስለ ነበረች ነው፡፡ በጉባኤው ከተሰበሰቡ ሊቃውንት መካከልም እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ሙታንን ያስነሡ፣ ለምጽ ያነጹ፣ አንካሳ ያረቱ፣ የዕውራንን ዓይን ያበሩ ድውያንን የፈወሱ፣ ሌላም ልዩ ልዩ ተአምር ያደረጉ፤ እንደዚሁም ስለ ርትዕት ሃይማኖታቸው በመጋደል ዓይናቸው የፈረጠ፣ እጃቸው የተቈረጠ ይገኙበታል፡፡ ሊቃውንቱ ሱባዔ ይዘው በጸሎት ከቆዩ በኋላ ኅዳር ፱ ቀን በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሊቀ መንበርነት፣ በእለእስክንድሮስ አፈ ጉባኤነት ጉባኤው ተጀመረ፡፡ ንጉሡ ሊቃውንቱን "ስማችሁን፣ አገራችሁንና ሃይማኖታችሁን ጽፋችሁ ስጡኝ" ባላቸው ጊዜም ከ፳፫፻፵፰ቱ (2348) መካከል ፫፻፲፰ (318) ሊቃውንት ሃይማኖታቸውን ሲገልጹ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾነው "ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ፤ ወልድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በመለኮት፣ በሥልጣን፣ በፈቃድ፣ በህልውና አንድ ነው" ብለው ጽፈው ሰጡት፡፡ ንጉሡም "ሃይማኖት እንደ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት ይኹን" ብሎ ዐዋጅ አስነግሯል፡፡ እነዚህ ሊቃውንት በኦሪት ዘፍጥረት የተጠቀሱት ፫፻፲፰ቱ የአብርሃም ብላቴኖች ምሳሌዎች ናቸው /ዘፍ.፲፬፥፲፬/፡፡ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት በጉባኤው አርዮ*ስን አው*ግዘው በመለየት "ነአምን በአሐዱ አምላክ፤ በአንድ አምላክ እናምናለን" የሚለውን የሃይማኖት ጸሎት (የሃይማኖት መሠረት) እና ሌሎችንም የሃይማኖት ውሳኔዎችን ደንግገዋል፡፡ ሊቃውንቱ ጉባኤውን ያካሔዱት ኅዳር ፱ ቀን ይኹን እንጂ በአንድነት የተሰባሰቡት መስከረም ፳፩ ቀን ስለ ነበረ ይህ ዕለት "#ብዙኃን_ማርያም" እየተባለ ይጠራል፡፡ ብዙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ለሃይማኖታዊ ጉባኤ የተሳባሰቡበት ዕለት ነውና፡፡ #ዕፀ_መስቀል በሌላ በኩል መስከረም ፳፩ ቀን የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በአምባሰል ተራራ በግሸን ደብረ ከርቤ የገባበትና በዓሉ የከበረበት ዕለት ነው፡፡ ታሪኩም በአጭሩ የሚከተለው ነው፤ ዐፄ ዳዊት መንፈሳዊና ደግ ንጉሥ ነበሩ፡፡ በዘመናቸው በኢትዮጵያ ቸነፈር ተከሥቶ ሕዝቡ ስለ ተሰቃየባቸው እጅግ አዘኑ፤ በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ቢያመለክቱም ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላኩ ባሕታዊ መጥተው "የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል አስመጥተህ በአገርህ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አሠርተህ ብታስቀምጥ ረሃቡ፣ ቸነፈሩ ኹሉ ይታገሥልሃል" አሏቸው፡፡ ዐፄ ዳዊትም ከብዙ ገጸ በረከት (ስጦታ) ጋር "የጌታችንን መስቀል ላኩልኝ" የሚል መልእክት አስይዘው መልእክተኞችን ወደ ኢየሩሳሌም ሰደዱ፡፡ መልእክተኞቹም በታዘዙት መሠረት መስቀሉን ይዘው መምጣታቸውን ዐፄ ዳዊት ሲሰሙ "ክተት ሠራዊት ምታ ነጋሪት" ብለው መስቀሉን ለመቀበል ጉዞ ጀመሩ፡፡ ዐፄ ዳዊት ስናር (ሱዳን) ደርሰው ከመልእክተኞቹ ጋር ተገናኝተው መስቀሉን በክብር አጅበው ወደ መካከል ኢትዮጵያ ለማስገባት ሲነሡም ከበቅሏቸው ወድቀው ጥቅምት ፱ ቀን ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፤ በዚህም ሠራዊታቸው ተደናግጠው የጌታችንን መስቀል እዚያው ትተው የዐፄ ዳዊትን አስከሬን ይዘው ተመለሱ፡፡ መስቀሉ በስናር ከቆየ በኋላ የዐፄ ዳዊት ልጅ ዘርዐ ያዕቆብ ሲነግሡ ወደ መሃል ኢትዮጵያ አምጥተው ቤተ ክርስቲያን አሠርተው ለማስቀመጥ ቢያስቡም ምቹ ቦታ ግን ሊያገኙ አልቻሉም ነበር፡፡ ንጉሡና ሠራዊታቸው ምቹ ቦታ ሲፈልጉ መስቀሉን በኤረር ተራራ፣ በደብረ ብርሃን፣ በመናገሻ ማርያም ዓምባ፣ በእንጦጦ ጋራ ብዙ ጊዜ አስቀምጠውት ቆይተዋል፡፡ መስቀሉ በእንጦጦ ጋራ ሳለ እግዚአብሔር አምላክ "አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል፤ መስቀሌን በመስቀለኛ ተራራ ላይ አስቀምጥ" የሚል ቃል ለንጉሡ በራእይ ነገራቸው፡፡ መስቀሉን ወደ ወሎ ሀገረ ስብከት እንዲወስዱትም አዘዛቸው፡፡ ንጉሡና ሠራዊታቸው በእግዚአብሔር መሪነት መስቀሉን ይዘው ወሎ ሲደርሱም ጌታችን ወደ አምባሰል እያመለከተ "አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል፤ መስቀሌን በመስቀለኛ ተራራ ላይ አስቀምጥ" ይላቸው ነበር፤ ንጉሡ መስቀሉን ይዘው ወደ ቦታው ሲያመሩ መስቀለኛው የግሸን ተራራን አገኙ፤ በዚያም ቤተ ክርስቲያን አሠርተው በ፲፬፻፵፮ (1446) ዓ.ም የጌታችንን መስቀል በክብር አስቀምጠውታል፡፡ ከዚህ በኋላ ንጉሡ ‹‹መካከሏ ገነት፤ ዳሯ እሳት ይኹን! የበረረ ወፍ፣ የሠገረ ቆቅ አይታደንባት! በድንገት ሰው የገደለ፣ ቋንጃ የቈረጠ ወንጀለኛ አይያዝባት!›› ብለው ዐዋጅ ነግረዋል፡፡ የእመቤታችን ጽላትም አብሮ በግሸን ደብረ ከርቤ እንዲቀመጥ አድርገዋል፡፡ ስለዚህም መስከረም ፳፩ ቀን በየዓመቱ በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል፡፡ ኀጢአታቸውን ለካህን ተናዘው፣ ንስሐ ገብተው በዚህ ዕለት ወደ ግሸን ደብረ ከርቤ በመሔድ የሚጸልዩና የሚማጸኑ ምእመናን ኹሉ እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደሚያገኙም ጤፉት በተባለችው መጽሐፍ ተጠቅሷል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ቆጵርያኖስና_ድንግሊቱ_ዮስቴና በዚችም ቀን ቅዱስ ቆጵርያኖስና ድንግሊቱ ዮስቴና በሰማዕትነት አረፉ። ይህም ቅዱስ ቆጵርያኖስ አስቀድሞ ከሀ*ዲና ሥራ*የኛ ነበር እርሱም ለሥራ*የኞች ሁሉ አለቃቸው ነው። በሥራ*ዩም ሥራ ከመመካቱ ብዛት የተነሣ በሥ*ራይ የሚበልጠው ካለ ሊያይና ከዚያ ሊማር ከሌለ ግን በእነርሱ ላይ ሊመካባቸው ወደ አንጾኪያ አገር ሔደ።

🔴#ስንሳር መስከረም_20 #ቅዱስ_አትናቴዎስ_ካልዕ አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም ሃያ በዚች ቀን ለሊቃነ ጳጳሳት ሃያ ስምንተኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባት አትናቴዎስ አረፈ። ይህም አባት አስቀድሞ የእስክንድርያ አገር ቤተክርስቲያን መጋቢ ነበር ከእርሱም በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ ጴጥሮስ በአረፈ ጊዜ ይህን አባት ሊቀ ጵጵስና ይሾሙት ዘንድ ሁሉም ኤጲስቆጶሳት መኳንንቱና ሊቃውንቱ ሕዝቡም በአንድ ምክር ተስማሙ በእግዚአብሔር ሕግ በመጽናት ያደረገው መልካም ተጋድሎውና ቅድስናው ስለርሱ ስለተነገረ መንፈስ ቅዱስም እንደ አደረበት ስለ ተረዱ ያለ ፈቃዱም ወስደው ሊቀ ጵጵስና ሾሙት። ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና የክርስቶስን መንጋዎች በምክሩ፣ በትምህርቱ፣ በጸሎቱ ከዲያብሎስ ተኵ*ላዎች በመልካም አጠባበቅ ጠበቃቸው እሊህም ሃይማኖትን የሚለውጡ መና*ፍቃን ናቸው። በሊቀ ጵጵስናውም ፯ት ዓመት ኖረ እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን ።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መስከረም_19 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም ዐሥራ ዘጠኝ በዚህች ቀን ያለ ደም ማፍሰስ ሰማዕት የሆነ የአርማንያ #ሊቀ_ጳጳሳት_ቅዱስ_ጎርጎርዮስ ከዐዘቅት የወጣበት መታሰቢያው ነው፣ የከበረ #ገዳማዊ_ቂርቆስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው እና የኢትዮጵያ ንጉሥ የናዖድ ልጅ የከበረችና #የተባረከች_ሮማነ_ወርቅ የዕረፍቷ መታሰቢያ ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ጎርጎርዮስ_ዘአርማንያ መስከረም ዐሥራ ዘጠኝ በዚህች ቀን ያለ ደም ማፍሰስ ሰማዕት የሆነ የአርማንያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ ጎርጎርዮስ ከዐዘቅት የወጣበት መታሰቢያው ነው። ይህም በንጉሥ ድርጣድስ ዘመን በአርማንያ አገር ራሱን ባሪያ አድርጎ ይኖር ነበር። ይህም ንጉሥ ከሀዲ ነበርና ዕጣን ሊዐሳርግ ወደ ጣዖቱ ቤት ሲገባ ቅዱስ ጎርጎርዮስን ጠርቶ ለአማልክት ዕጣን እንዲአሳርግ አዘዘው። ቅዱሱ ግን የንጉሡን ትእዛዝ አልሰማም ስለዚህም እጅግ ጽኑዕ የሆነ ሥቃይን አሠቃየው በእሳትም አቃጠለው ከዚህም በኃላ ጥልቅ ከሆነ ጉድጓድ ውስጥ ጣለው በዚያም ዐሥራ አምስት ዓመት ኖረ። በንጉሡ አዳራሽ አቅራቢያም አንዲት አሮጊት ነበረች እርሷም እንጀራ እየጋገርሽ ቅዱስ ጎርጎርዮስ በውስጡ ከአለበት ጉድጓድ ሁል ጊዜ ጣይለት የሚላትን ራእይ አየች። ይችም አሮጊት እንዲህ እያደረገች እንጀራንም እየጣለችለት እስከ ዐሥራ አምስት ዓመት ፍጻሜ ኖረች። በዚያም ወራት ይህ ንጉሥ ድርጣድስ ደናግሎችንና ቅድስት አርሴማን ገድሎ ሥጋቸውም በተራራ ላይ ተጣለ። ሰይጣንም በንጉሥ ድርጣድስ ላይ ተጫነ እግዚአብሔርም የተፈጥሮ መልኩን ለውጦ እንደ እሪያ አደረገው እንዲሁም ከቤተ መንግሥት ሰዎች ብዙዎቹን ሰይጣን ተጫነባቸው በቤተ መንግሥት ውስጥ ታላቅ ኀዘንና ጭንቀት ሆነ። የንጉሡ እኅት ግን በሌሊት ራእይ ጎርጎርዮስን ከጉድጓድ ውስጥ ካላወጣችሁት አለዚያ አትድኑም እንደሚላት ሰውን አየች ለወገኖቿም ነገረቻቸውና እንርሱም ሒደው ቅዱስ ጎርጎርዮስን ከጎድጓድ አወጡት በዚያን ጊዜም ቅዱሳት ደናግልን ሥጋቸውን ገንዞ በመልካም ቦታ አኖራቸው ከዚያም በኃላ ንጉሡንና ቤተሰቦቹን ሁሉንም ረወሳቸው። ዜናውም ሁሉ በዕረፍቱ ታኅሣሥ ዐሥራ አምስት ቀን ተጽፎአል። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ቂርቆስ_ገዳማዊ በዚህችም ቀን በሊቀ ጳጳሳት አባ ብንያሚን ዘመን የሆነ የከበረ ገዳማዊ ቂርቆስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው። ይህም ቅዱስ ሰው ከከሀዲው ንጉሥ ከመርቅያን በሸሸ ጊዜ በከፍተኛ ተራራ ላይ በብቸኛነት ተቀመጠ በውስጡም አራዊት የኖሩበታል ምግቡንም ከእግዚአብሔር ለመነ አጋዘንም በየሦስት ቀን ወደርሱ እንድትመጣ ወተቷንም እንዲጠጣ አዘዘለት በእንዲህ ያለ ሥራም ዐሥር ዓመታት ኖረ። የተረገመ ሰይጣን ግን በተጋድሎው በቀና ጊዜ በየአይነቱ በሆነ ፈተና ሊፈትነው ጀመረ ያስፈራው ዘንድ በጥቁር ባሪያ አምሳል የሚመጣበት ጊዜ አለ ደግሞም በብዙ ሠራዊትና በፈረሰኞች አምሳል ሁነው ይዘው ያሥሩታል በጅራፍም ገርፈው በእግሮቹ ይጎትቱታል ሰይጣናት እንደሆኑ በአወቀ ጊዜ በመስቀል ምልክት በላያቸው ሲአማትብ ያን ጊዜ ሸሹ። በአንዲትም ዕለት በሌሊት ሲሰግድ በታላቅ ከይሱ አምሳል በአንገቱ ላይ ተንጠለጠለና በፊቱ ውስጥ ሊተነፍስበት ፈለገ ያን ጊዜም ከእግዚአብሔር ርዳታን ለመነ መልአኩን ልኮ አዳነው። የዕረፍቱም ጊዜ ሱቀርብ ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ብንያሚን ሒዶ ሥራውን ሁሉ ነገረው ከዚህም በኃላ ወደ በዓቱ ተመለሰ ሊቀ ጳጳሳቱም መገነዣውን እንዲያዘጋጁ ሦስት ኤጲስቆጶሳትን ወደርሱ ላከ ወደ በዓቱም በሔዱ ጊዜ ታሞ አገኙት ነፍሱም ከሥጋው በምትወጣ ጊዜ ለመነገር የማይቻል ታላቅ ክብርን ተመለከቱ በበዓቱም ውስጥ ቀበሩት። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅድስት_ሮማነ_ወርቅ በዚህችም ቀን የከበረችና የተባረከች ሮማነ ወርቅ የዕረፍቷ መታሰቢያ ነው። ይህቺ ቅድስት እናት ኢትዮጵያዊት ናት። የንጉሥ ልጅ ስትሆን አባቷ አፄ ናዖድ እናቷ ደግሞ እሌኒ (ወለተ ማርያም) ይባላሉ። ወንድሟ ደግሞ አፄ ልብነ ድንግል ይባላሉ። በቤተ መንግስት ውስጥ ብታድግም መንፈሳዊነቷ የገዳም ያህል ነበር። መጾምና መጸለይን የምትወድ ድኆችንና ችግረኞችን የምትጐበኝ እና ከተባረከ ትዳሯም ቅዱስ ላዕከ ማርያምን አፍርታለች። አብያተ ክርስቲያናትን ከማነጽ ባለፈ የነዳያን እናትም ነበረች። በክርስትናዋ ፈጣሪዋን ደስ አሰኝታ በዚህ ቀን ዐርፋለች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

እርሱ ግን ብቻውን ወደ ኢያሪኮ ባሕር ዳርቻ ሔደ መርከብንም በአጣ ጊዜ በባሕሩ ሞገድ ላይ ባረከ ገብቶም ወደ ተርሴስ አገር እስከ ገባ ድረስ በባሕሩ ላይ እንደ ደረቅ ምድር ሔደበት ። በሀገሩ ጥጋጥግ አልፎ ሲሔድ በትል የተከበበ ቁስለኛ ሰው አገኘና ሊቅ ያዕቆብ ስምህ ማነው ብሎ ጠየቀው እርሱም ስሜ እንጦኒ ነው አባቴም ለባለ መድኃኒቶች ብዙ ገንዘብ ሰጠልኝ ሊፈውሱኝ አልቻሉም ። መምህር ያዕቆብም ስለ ደዌው ተከዘ ጸሎትንም አድርጎ ሁለመናውን በመዳሰስ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ጤነኛ ሁን አለው ወዲያውኑ ዳነ ደቀ መዝሙሩም ሁኖ ተከተለው ። ከዚህም በኋላ ከረድኡ ጋር ሲጓዝ ሀገረ ዐምድ ደረሱ የንጉሥ አንስጦስን ልጅ እየአበደ ራሱን በደንጊያ ሲደበድብ አገኙት እርሱን መያዝም የሚችል አልነበረም። ሊቅ ያዕቆብም ይዞ ያመጣለት ዘንድ ረድኡን አዘዘው በአቀረበለትም ጊዜ በከበረ መስቀል ምልክት አማተበበትና ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ከሰውዬው ወጥቶ እንዲሔድ ሰይጣንን አዘዘው ። ያን ጊዜም በጥቁር ባርያ አምሳል ወጣ የንጉሡም ልጅ በከበረ ሊቅ ያዕቆብ ጸሎት ዳነ አባቱና ወገኖቹ ሁሉ በታላቅ ደስታ ደስ አላቸው ንጉሡም ለከበረ ሊቅ ያዕቆብ ብዙ ገንዘብ ሊሰጠው ወደደ እርሱ ግን አይሆንም አለ ምንም ምን አልተቀበለም ። ክብር ይግባውና በእግዚአብሔርም ትእዛዝ አብዲን በሚባል አገር የገዳም አበ ምኔት ከሆነ ከአባ በርሳቦ ጋር ተገናኝተው በአንድነት ተጓዙ በጒዞ ላይም እያሉ እንጦኒ በሆድ ተቅማጥ በሽታ ታመመና በሦስተኛው ቀን አረፈ ቀበሩትም። ስሟ አውርሳ ከሚባል አገር በደረሱ ጊዜ የአገረ ገዥውን ልጅ ታሞ አገኙት በሊቅ ያዕቆብም ጸሎት ዳነ መኰንኑም ልጁ እንደ ዳነ አይቶ በታላቅ ደስታ ደስ አለው እስከ ዕለተ ሞቱ ረድዕ ይሆነው ዘንድ ለከበረ ያዕቆብ ልጁን ሰጠው የልጁም ስም ፍቁር ነው ። ወደ ሊቅ በርሳቦ ገዳምም በቀረቡ ጊዜ መነኰሳቱ ተቀበሏቸው በብዙ ምስጋናም እየዘመሩ አስገቧቸው በዚያችም አገር ጎን የታነፀ የጣዖት ቤት አለ ስሙ ሰሚር የሚባል የፋርስ ንጉሥ በየዓመቱ እየመጣ ለጣዖታት በዓልን ያከብራል የከበረ ሊቅ ያዕቆብም መነኰሳቱን እንዲህ አላቸው እነሆ የፋርስ ንጉሥ እንደመጣ ሰምታችኋል የክብር ባለቤት ስለ ሆነ ክርስቶስ ስለ ስሙ ኑ ደማችንን እናፍስስ ። መነኰሳቱም በዚህ ምክር እየተስማሙ ሳሉ የንጉሡ ጭፍሮች ወደዚያ ገዳም ደረሱ መነኰሳቱንም ጥቁር ልብስን ለብሰው አዩአቸውና እናንተ ምንድን ናችሁ ከአምልክትስ ማንን ታመልካለችሁ አሏቸው ። ቅዱሳን መነኰሳትም እንዲህ አሏቸው እኛ ከሰማያት የወረደውን በመንፈስ ቅዱስ ግብር ከቅድስት ድንግል ማርያም ሰው የሆነ የሕያው እግዚአብሔርን ልጅ ክብር ይግባውና ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን እናመልከዋለን ጭፍሮችም ወደ ንጉሥ አቀረቧቸው ። በደረሱም ጊዜ የክብር ባለቤት በሆነ በክርስቶስ ስም በንጉሡ ፊት ታመኑ ንጉሡም ሀገራቸውን መረመረ አባ በርሳቦም የእኔና የወንድሞቼ መነኰሳት አገራችንም ሮም ነው አለ ። አባ ያዕቆብም የእኔ አገር ግብጽ ነው አለ ንጉሡም የአባ ያዕቆብን ቃል ሰምቶ ሊገድለው አልፈለገምና ብቻውን ገለል እንዲያደርጉት አዘዘ ። ከግብጽ ሰዎች ጋር ቃል ኪዳን ስላለው መነኰሳቱን ግን ደማቸው እስቲፈስ ገርፈው ከእሥር ቤት እንዲጥሏቸው አዘዘ የእግዚአብሔርም መልአክ ፈወሳቸው ። በማግሥቱም ጤነኞች ሁነው በአገኛቸው ጊዜ ብዙ ሀብት እንደሚሰጣቸው ተስፋ ሰጣቸው እነርሱ ግን ቃሉን አቃለሉ ። ንጉሡም በወይን መርገጫ ውስጥ በማስረገጥ በግርፋት ጥርሶችን የእጆችንና የእግሮች ጥፍሮችን በማውለቅ ሰባት ቀኖችም ያህል አፍንጫን፣ ከንፈርን፣ ጆሮዎችን በመቆረጥ እንዲአሠቃዩአቸው አዘዘ ። በስምንተኛውም ቀን ራሶቻቸውን ይቆርጧቸው ዘንድ አዘዘ መምህራቸው ሊቅ በርሳቦም እየአንዳንዱን ለሰያፊ ከሰጣቸው በኋላ ዐሥሩ መነኰሳት ተቆረጡ የንጉሡ የፈረሶች ባልደራስ ያን ጊዜ ለቅዱሳኑ የወረዱትን አክሊሎች አየ ትጥቁንም ፈትቶ ጥሎ ክብር ይግባውና በጌታችን ክርስቶስ ታመነ እርሱንም አንገቱን በሰይፍ ቆረጡት መምህር በርሳቦም ልጆቹ ከተቆረጡ በኋላ አንገቱን ዘርግቶ ሰያፊውን የታዘዝከውን ፈጽም አለው ያን ጊዜም ሰያፊው ቆረጠው ምስክርነታቸውንም ነሐሴ ሃያ ስምንት ቀን ፈጸሙ። ንጉሡም ሥጋቸውን በእሳት እንዲአቃጥሉ አዘዘ ምድርም ተከፍታ ሥጋቸውን ሠወረች ንጉሡም አፍሮ ወደ አገሩ ሊሔድ ወደደ ። ያን ጊዜም አባ ያዕቆብ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ከሰማይም ከጠቆረ ደመና ጋርና ከሚከረፋ በረድ ጋር እሳት በንጉሡ ላይ ዘነመ ከሠራዊቱ ሁሉ ጋር ተቃጥሎ ጠፋ ከእነርሱ አንድ እንኳ አልቀረም ። የዚያች አገር ሰዎችም በሰሙ ጊዜ ሁሉም ወጥተው ፈረሶቻቸውንና ዕቃዎቻቸውን ገንዘባቸውንም ወሰዱ ወደ ሊቅ ያዕቆብም አምጥተው እሊህን ገንዘቦች ለምትሻው ሥራ ውሰድ አሉት ። እርሱም አልተቀበላቸውም ግን በሰማዕታት መቃብር ላይ ቤተ ክርስቲያን እንዲሠሩ አዘዛቸው ቤተ ክርስቲያኒቱም እስከ ዛሬ አለች ። ከዘመናትም በአንዲቱ አገር ቸነፈር ሆነ ወደ ሊቅ ያዕቆብ እንዲጸለይላቸው ላኩ እርሱም ሰምቶ እጅግ አዘነ ማዕጠንትም ይዞ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ረጅም ጸሎት ጸለየ ዕጣንንም አሳረገ ። ከዚያም ወጥቶ መልእክተኞችን አትፍሩ አትጨነቁ በሰላም ሒዱ አላቸው ። በደረሱም ጊዜ አገሪቱን ጤነኛ ሁና አገኟት ደስ ብሏቸው የሊቅ ያዕቆብን አምላክ አመሰገኑት ። ዳግመኛም ለከበረ ሊቅ ያዕቆብ ዳንኤል የሚባል ረድእ ነበረው ደግሞ ለቅዱስ ያዕቆብ ወዳጁ የሆነ አገር ገዥ አለ ለአገረ ገዥውም ወደ ቅዱስ ያዕቆብ ከአባቷ ጋር የምትመጣ ብላቴና አለችው ረዱን ዳንኤልን በኃጢአት ልትጥለው ፈለገችው እምቢ ባላትም ጊዜ ከአባቷ አገልጋይ ፀነሰችና በሊቅ ያዕቆብ ረድእ አመካኘችበት አባቷም ሰምቶ መምህር ያዕቆብንና ደቀ መዝሙሩን ሊገድል ሔደ በጒዞ ላይም ሳለ በላዩ ከሰማይ መብረቅ ወርዶ ዐይኖቹን አሳወረው ። የመኰንኑም ልጅ ከወለደች በኋላ ወደ ከበረ መምህር ያዕቆብ በጉባኤ መካከል ሕፃኑን አባትህ ማን እንደሆነ ትናገር ዘንድ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም አዝዝሃለሁ አለው ። ሕፃኑም አባቴ የእናቴ የአባቷ አገልጋይ እገሌ ነው አለ የተሰበሰቡትም ሕዝብ ሰምተው አደነቁ የተመሰገነ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት ። ከዚህም በኋላ ዕረፍቱ ሲቀርብ ደቀ መዝሙሩን እንዲህ ብሎ አዘዘው ከዚህ ዓለም የምለይበት ጊዜ ደርሷል በምሞትም ጊዜ ከአባ በርሳቦና ከልጀቹ ጋራ ቅበረኝ ይህንንም ብሎ በሦስተኛው ቀን አረፈ መላእክትም ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት ነፍሱን በክብር አሳረጉ ።https://t.me/finotebirhan12

ይህ የአቡነ አኖሬዎስ ገዳም ደሴ ዙሪያ በጽጋጋ የሚገኝ ሲሆን ከደሴ ወደ መካነ ሰላም በሚወስደው መንገድ በ12 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ይገኛል፡፡ ገዳሙ የተመሠረተው በ1317 ዓ.ም በንጉሥ ዓምደ ጽዮን ዘመነ መንግሥት ነው፡፡ አቡነ አኖሬዎስ በጽጋጋ ገዳማቸው እያሉ ንጉሥ ዓምደ ጽዮን በክፉዎች ምክር ተታሎ የአባቱን ሚስት በማግባቱ ጻድቁ እንደ ዮሐንስ መጥምቅ ንጉሡን ስለገሠጹት ታስረው ወደ ወለቃ ተጋዙ፡፡ ንጉሡ ሲሞት ሠይፈ አርዕድ ነግሦ የተጋዙት በሙሉ እንዲመለሱ ስላወጀ አቡነ አኖሬዎስም ወደ በዓታቸው ጽጋጋ ተመለሱ፡፡ አቡነ አኖሪዎስ በነገሥታቱ ፊት ቆመው የወንጌልን ሕግ በመመስከራቸው እየታሰሩ ምድረ ጸወን ወደምትባል አገር (ይህውም ደቡብ ወሎ ቦረና የምትገኝ ናት) እንዲሁም ዝዋይ ደሴ ገማስቄ ግድሞ (ባሌ አካባቢ) ወደ ተባለው አገር ተጋዙ፡፡ ለብዙ ዓመታት ገዳም መሥርተው ቆይተው ወደ ጥንት በዓታቸው ተመልሰው ጽጋጋ መጥተው በገዳማቸው ብዙ ተጋድለው በ1471ዓ.ም በዚሁ በጽጋጋ ገዳማቸው ነው ያረፉት፡፡ በኋላም ወደ አሩሲ በመሄድ ኢስላሞችን አስተምረዋል፡፡ ብዙ ተአምራት ያደረጉላቸው ሲሆን መንደራቸውንም ያማረ መንደር ብለው ሰይመውላቸዋል፡፡ የአሩሲ ኢስላሞች እጅግ ያከብሯቸውና ይወዷቸው ነበር። ከአክብሮታቸውም የተነሣ አቡነ አኖሬዎስን ‹‹ኑር ሁሴን›› እያሉ ይጠሯቸው ነበር፡፡ ጻድቁ በአሩሲ ቆመው የጸለዩበት ቦታ ዛሬም ድረስ ተከብሮ ይኖራል፣ ሶፍ ዑመር ዋሻ ተብሎ የሚጠራው ታሪካዊ ዋሻ የአቡነ አኖርዮስ በዓት መሆኑ በታሪክ የሚታወቅ ሐቅ ነው፣ ይህም በገድለ ተክለ ሃይማኖትና በድርሳነ ቅዱስ ዑራኤል ላይ በሰፊው ተጠቅሷል፡፡ ጻድቁ በኢቲሳ 21 ዓመት ቆመው ሲጸልዩ ብርሃን ተተክሎ ይታይ ነበር፡፡ ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ትልቅ ቃልኪዳን ከተቀበሉ በኋላ መስከረም 18 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_መርቆሬዎስ_ካልዕ(ሰማዕት) በዚች ቀን በከሀዲው ዮልያኖስ እጅ ሌላው ቅዱስ መርቆሬዎስ በሰማዕትነት አረፈ እርሱም አስቀድሞ ክርስቲያን የነበረ ነው ። የታላቁ ቈስጠንጢኖስ ልጅ ሁለተኛው ቈስጠንጢኖስ በሞተ ጊዜ የቈስጠንጢኖስ እኅት ልጅ ዩልያኖስ ነገሠ እርሱ ግን ጣዖታትን አመለከ ሰገደላቸውም የክርስቲያን ወገኖችንም አሠቃያቸው ብዙዎችም በእርሱ እጅ በሰማዕትነት አረፉ ። የንጉሡም የልደቱ ቀን በሆነች ጊዜ የሳቅ የሥላቅ የሆኑ ተጫዋቾችን ሰበሰባቸው ይህ ቅዱስ መርቆሬዎስም ቁጥሩ ከእሳቸው ጋር ነበር ካህናት በቤተክርስቲያን እንደሚያደርጉት በክርስትና ሥርዓት እንዲጫወት ይህን መርቆሬዎስን ከሀዲው ንጉሥ አዘዘው እንዳዘዘውም በክርስትና ሥርዓት ሁሉ ተጫወተ ታላቅም ሳቅና ሥላቅ ሆነ። ሁለተኛም በክርስትና ጥምቀት ሥርዓት ሊጫወት ጀመረ በመስቀል ምልክት አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያለ በውኃው ላይ አማተበ ። ያን ጊዜም መለኮታዊ ብርሃን በውኃው ውስጥ ወረደ እግዚአብሔርም የልቡናውን ዐይን ገልጦለት ያንን ብርሃን አየው ልብሱን ጥሎ ራቁቱን ወደ ውኃው ወርዶ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሦስት ጊዜ ብቅ ጥልቅ እያለ ተጠመቀ ። ከዚህም በኋላ ወጥቶ ልብሱን ለበሰ በንጉሡም ፊት ቆሞ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ታመነ ንጉሡም በርሱ ላይ ተቆጣ እንዲህም ብሎ አስፈራራው ለእኔ በመታዘዝ ለአማልክት ዕጣንን ካላሳረግህ ታላቅ ሥቃይን አሠቃይሃለሁ ትእዛዜን ከተቀበልክ ግን እኔ ብዙ ገንዘብ ሰጥቼህ እጅግ አከብርሃለሁ ። ቅዱስ መርቆሬዎስም የዚህን ዓለም ገንዘብ ሁሉና መንግሥትንም ብትሰጠኝ ጌታዬ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስን አልክደውም ብሎ መለሰለት ። ያን ጊዜም ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ ንጉሡ አዘዘና ቆረጡት በሰማያዊት መንግሥትም የማይጠፋ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለ ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ግብጻዊ_ሊቅ_ቅዱስ_ያዕቆብ በዚችም ቀን መስተጋድል የሆነ ግብጻዊ ሊቅ ያዕቆብ አረፈ። ወላጆቹም ደጎች ምእመናን ነበሩ ይህንንም ቅዱስ አገልጋይ ሊሆን ለእግዚአብሔር ሰጡት ። ትምህርቱንም በአደረሰ ጊዜ በእስክንድርያ ወደ አለ ገዳም ወላጆቹ ወሰዱት ለአበ ምኔት አባ ገብርኤልም ሰጡት ። እርሱም ተቀብሎ የዐሥራ ሁለት ዓመት ልጅ ሁኖ ሳለ አመነኰሰው ። ከዚህም በኋላ ሃያ ዓመት ሲሆነው ለተጋድሎ ከመምህሩ ጋር ወደ በረሃ ወጡ ከፍታ ያላት ግንብንም አግኝተው አባ ገብርኤልና አባ ያዕቆብ ከላይዋ ላይ ወጡ ። ከዚያም የውኃ ጉድጓድ አለ ከዚያም ጉድጓድ ውኃ እየቀዱ በገንዳዎች ላይ ያፈሳሉ የዱር እንስሶችም ሁል ጊዜ እየመጡ ከገንዳው ውኃ ይጠጣሉ አባ ያዕቆብም ያልባቸዋል ወተታቸውንም አይብ አድርጎ ከመምህሩ ጋር ይመገባሉ ። አባ ገብርኤልም በአረፈ ጊዜ በእግዚአብሔር ፈቃድ ዐሥራ ሁለት ገዳማውያን መጡ በጾምና በጸሎትም በመትጋት የእንስሶቹን ወተት በመመገብ ከእርሱ ጋር ተቀመጡ ለገዳሙ የሚያስፈልገውን ግን ነጋዴዎች ሥንዴን ከሩቅ ያመጣሉ ። ለዕለታትም በአንዲቱ ዕለት እርስ በርሳቸው እንዲህ ተባባሉ አባ ሙሴ ጸሊምን ብናየው ከእርሱም ብንባረክ እንወድ ነበር። ሰይጣንም በሰማ ጊዜ በመፋቀራቸው ቀንቶ በሙሴ ጸሊም አምሳል በክንፍ እየበረረ መጣ ሽማግሌ ስሆን ከቦታዬ ለምን አናወጻችሁኝ አላቸው ። እነርሱም የሕይወትን ቃል ከአፍህ ልንሰማ ከአንተም በረከትን ልንቀበል እንወዳለን አሉት ደግሞ ኑሮአችሁ እንዴት ነው አላቸው ። እነርሱም ለዱር እንስሶች በገንዳ ላይ ውኃን እንደሚቀዱ ውኃውንም ሊጠጡ ሲመጡ እንደሚአልቧቸውና ሁል ጊዜ በየማታው ከወተታቸው እንደሚመገቡ ነገሩት ። ሰይጣንም እንዲህ አላቸው የአዘዝኳችሁን ትሰማላችሁን አላቸው አዎን እንሰማሃለን አሉት ። ዳግመኛ እንዲህ አላቸው የእንስሶቹን ወተት አትጠጡ እናንተ መነኰሳት ስትሆኑ አታምጡአቸው ጾምን ግን በየአርባ ቀን ጹሙ የዳዊትንም መዝሙር አትጸልዩ እርሱ በዐመፅ የኦርዮን ሚስት ነጥቋልና። እርሱንም ገድሎታልና ጥቅም የሌለው ብዙ ነገርንም መከራቸው እነርሱም እርሱ እንደ አባ ሙሴ መስሏቸው ይመልሱለት ነበር ። ከዚህም በኋላ ሰይጣን እንደሆነ ለሊቅ ያዕቆብ መንፈስ ቅዱስ አስገነዘበው ደቀ መዛሙርቱንም የቁርባን ቅዳሴ እንዲቀድሱ አዘዛቸውና ሥጋውንና ደሙን ከተቀበሉ በኋላ ሰይጣን መሆኑን ለልጆቹ መነኰሳት ነገራቸው ። ሁለተኛም በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አምሳል ወደርሳቸው መጣ ከእርሱም ጋር በኤጲስቆጶሳት አምሳል አሉ ። በደረሰም ጊዜ በላያቸው ተኰሳተረ ከዚህ ልትኖሩ ማን ፈቀደላችሁ ብሎ አወገዛቸው ሊቅ ያዕቆብም አይቶ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር እጆቹን ዘርግቶ ጸሎትን አደረገ ። ወዲያውኑ ሰይጣን ተበተነ ግን መፈታተኑን አሁንም አልተወም በሚአስፈራ ዘንዶ አምሳልም ወደ አባ ያዕቆብ የሚመጣበት ጊዜ አለ ። በንጉሥ አምሳልም ደም ግባታቸው በሚያምር ደናግል አምሳልም በአሞራዎችና በቁራዎች አምሳልም ሁኖ በጥፍሮቻቸው ፊቱን እየነጩ በእንዲህ ያለ ፈተና ሰባት ዓመት ተፈተነ ከዚህም በኋላ ትዕግሥቱንና ድካሙን እግዚአብሔር አይቶ መብረቅን ልኮ ሰይጣንን ቀጥቅጦ በተነው ያዕቆብ ሆይ ከአንተ የተነሣ ወዮልኝ በጸሎትህ አቃጠልከኝ እያለ ሸሸ ። ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና እግዚአብሔር አብዲን ወደሚባል ገዳም እንዲሔድ ሊቅ ያዕቆብን አዘዘው ። እርሱም ለልጆቹ መነኰሳት ይህን ነገራቸው ከዚያም ግንብ ውስጥ እንዲኖሩ አማፀናቸው ።

🔴#ስንክሳር መስከረም_18 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም አስራ ስምንት በዚህች ቀን ታላቁ ኢትዮጵያዊ ጻድቅ #አቡነ_ኤዎስጣቴዎስ ከፋሌ ባሕር፣ የደብረ ጽጋጉ #አቡነ_አኖሬዎስ፣ ሰማዕቱ #ቅዱስ_መርቆሬዎስ_ካልዕ፣ #የአቡነ_ያዕቆብ_ግብፃዊ ዕረፍታቸው ነው። ዳግመኛም ይህች ዕለት ሐዋርያው #ቅዱስ_ቶማስ በሕንድ አገር ድንቅ ተአምር ያደረገባት ዕለት ናት፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ኤዎስጣቴዎስ_ከፋሌ_ባህር መስከረም ዐሥራ ስምንት በዚች ቀን ወንጌልን የሚሰብክ የሃይማኖት መምህር አባታችን ኤዎስጣቴዎስ አረፈ ። የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም ክርስቶስ ሞዓ የእናቱ ስም ስነ ሕይወት ይባላል ሁለቱም ደጋጎች እግዙአብሔርን የሚፈሩና በሕጉ ጸንተው የሚኖሩ ነበሩ። ከዘህም በኋላ በከበረ መልአክ በቅዱስ ገብርኤል አብሣሪነት ይህን ቅዱስ ወለዱት ስሙን የጌታ ጥብቅ ብለው ሰየሙት ። በአደገም ጊዜ የዳዊትን መዝሙርና የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍትን አስተማሩት ። ከዚህም በኋላ የእናቱ ወንድም አባ ዘካርያስ ወደአለበት የመነኰሳት ገዳም ወሰዱት ። አባ ዘካርያስም የእግዚአብሔርን ጸጋ እንዳደረችበት አውቆ የምንኩስናን ሥርዓት አስተምሮ የመላእክትን አስኬማ አለበሰው ። ከገድሉ ጽናት የተነሣ በገዳም ያሉ አረጋውያን እስኪያደንቁ ድረስ በጾም በጸሎት የተጠመደ ሆነ እርሱ በጥበብና በዕውቀት የጸና ነውና ። ከጥቂት ጊዜ በኋላም ዲቁና ተሾመ የዲያቆናት አለቃ እንደሆነ እስጢፋኖስም ለቤተ ክርስቲያን አገለገለ ። ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሚካኤልና ከገብርኤል ጋር ተገለጠለትና ሰላምታ ሰጠው በንፍሐትም መንፈስ ቅዱስን አሳደበረት እንዲህም አለው ወዳጄ ኤዎስጣቴዎስ ሆይ እኔ ከእናትህ ማሕፀን መረጥኩህ ያለ ፍርሀትና ድንጋፄ ወንጌልን ለብዙዎች ሕዝቦች ትሰብክ ዘንድ ከኢትዮጵያ እስከ አርማንያ ድረስ መምህር አደረግሁህ አንተን የሰማ እኔን ሰማ አንተን ያልሰማ እኔን አልሰማም ጌታችንም ይህን ተናግሮ ወደ ሰማይ በክብር ዐረገ ። ቅዱስ ኤዎስጣቴዎስም ወደ ጳጳስ ሒዶ ቅስና ተሾመ የወንጌልንም ሃይማኖት ይሰብክ ዘንድ ጀመረ ብዙ ሰዎች ወደ ርሱ እስቲሰበሰቡ ድረስ በእርሱም እጅ መንኩሰው ደቀ መዛሙርትን ሆኑት ከእርሳቸውም ታላቁ አባ አብሳዲ ነው ። ብዙዎችንም የከፋች ሥራቸውን አስትቶ ከክህደታቸው መለሳቸው ትምህርቱም በሀገሩ ሁሉ ደረሰ በመላ ዘመኑም የሰንበታትና የበዓላት አከባበር የጸና ሁኖ ተሠራ ከሐዋርያትም ሕግና ሥርዓት ወደቀኝም ሆነ ወደ ግራ ሁሉም ፈቀቅ አላሉም ። ወደ ኢየሩሳሌምም ሁለት ጊዜ ሔደ እግዚአብሔርም በእጆቹ የዕውራንን ዐይኖች በማብራት አንካሶችንና ጎባጦችን በማቅናት አጋንንትን በማስወጣት ቁጥር የሌላቸው ተአምራትን አደረገ ። ከዚህም በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም በእግዚአብሔር ፈቃድ ለመሔድ በአሰበ ጊዜ ልጆቹን ሰብስቦ የመነኰሳትን ሥርዓት ይጠብቁ ዘንድ ከመናፍቃንም ጋር እንዳይቀላቀሉ አማፀናቸው ። ልጁ አብሳዲንም በእነርሱ ላይ ሾመውና ወደ ኢየሩሳሌም ሰንበትን እያከበረና የክርስቶስን ሃይማኖት እያስተማረ ሔደ ። ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ብንያሚንም ደርሶ ከእርሱ ቡራኬ ተቀበለ የሃይማኖትንም ነገር ተነጋገሩ ዳግመኛም ከከበሩ ቦታዎች በመሳለም በረከትን ተቀበለ በዮርዳኖስም ተጠመቀ ። ከዚያም ወደ አርማንያ ሔደ ወደ ኢያሪኮ ባሕርም ሲደርስ በመርከባቸው ያሳፍሩት ዘንድ መርከበኞችን ለመናቸው በከለከሉትም ጊዜ ዓጽፉን በባሕሩ ላይ ዘረጋ በቅድስት ሥላሴ ስም በላዩ ባረከ ራሱንም በመስቀል ምልክት አማተበ እንደ መርከብም ሁኖለት በላዩ ተጫነ ሁለት መላእክትም ቀዛፊዎች ጌታችንም እንደ ሊቀ ሐመር ሆኑለት ። ከባሕሩም ግርማ የተነሣ እንዳይፈሩ ልጆቹን አጽናናቸው ። ግን እንዲህ አላቸው ልጆቼ በልባችሁ ቂምንና ሽንገላን እንዳታኖሩ ተጠበቁ ለኔ ግን ከእናንተ አንዱ አንደ ሚጠፋ ይመስለኛል ይህን ሲናገር ልቡ የቂም የበቀል ማከማቻ ስለሆነ ወዲያውኑ አንዱ ከእነርሱ መካከል ሠጠመ ። በእግዚአብሔርም ፈቃድ ባሕሩን ተሻግሮ ወደ አርማንያ ከተማ ደርሶ ከሊቀ ጳጳሳቱ ጋር ተገናኘ ሰገደለትም ከእርሱም ቡራኬን ተቀበለ ሊቀ ጳጳሱም በአየው ጊዜ ታላቅ ደስታን ደስ አለው በፍቅርም ተቀበለው ። አባታችን ኤዎስጣቴዎስም ሁሉም በትመህርቱ አንድ እስከሆኑ ድረስ የአርማንያን ሰዎች ሐዋርያት በሲኖዶሳቸው የሠሩትን ሥርዓት እያስተማራቸው ኖረ ። ከዚህም በኋላ ዕረፍቱ ሲደርስ ክብር ይግባውና ጌታችን ተገለጠለትና ስሙን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ገድሉንም ለሚጽፍ ቃል ኪዳንን ሰጠው ። በአረፈም ጊዜ ጳጳሳትና ካህናት በታላቅ ክብር ገንዘው በሰማዕቱ በቅዱስ መርምህናም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ቀበሩት ። ከሥጋውም ብዙ ተአምራት ተገለጡ ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_አኖሬዎስ_ትልቁ በዚችም ቀን የደብረ ጽጋግ መምህር አባ አኖሬዎስ አረፈ። "አኖሬዎስ ትልቁ" መባላቸው "ትንሹ አኖሬዎስ" በሚል ስያሜ የተጠሩ ሌላ ጻድቅ አሉና ነው፡፡ ይኸውም ታላቁ አቡነ አኖሬዎስ አባታቸው ዘርዐ ሃይማኖት ወይም ዘርዐ አብርሃም እናታቸው ደግሞ ክርስቶስ ዘመዳ ይባላሉ፡፡ አቡነ አኖሬዎስ ታላቁ፣ አቡነ ሳሙኤል ዘወገግ፣ አቡነ ሕፃን ሞዐ፣ አቡነ ተክለ ሃይማኖት፣ አቡነ ዜና ማርቆስና አቡነ ማትያስ ዘፈጠጋር እነዚህ ሁሉም የወንድማማቾች ልጆች ናቸው፡፡ እነኚህ ደጋግ ቅዱሳን በእናትም የእኅትማማቾች ልጆች ናቸው፡፡ ማለትም የአኖሬዎስ ታላቁ እናት ክርስቶስ ዘመዳ፣ የሕፃን ሞዐ እናት ትቤ ጽዮን፣ የንጉሡ የዐፄ ይኮኖ አምላክና የማርያም ዘመዳ እናት እምነ ጽዮን እኅትማማቾች ናቸው፡፡ እነዚህም ሦስቱ እኅትማማቾች (እምነ ጽዮን፣ ትቤ ጽዮንና ክርስቶስ ዘመዳ) መድኃኒነ እግዚእ የሚባል አንድ ወንድም አላቸው፡፡ እርሱም የአቡነ ተክለ ሃይማኖት እናት የቅድስት እግዚእ ኀረያ አባት ነው፡፡ ማርያም ዘመዳም አቡነ ዜና ማርቆስንና ማርያም ክብራን ወልዳለች፡፡ ማርያም ክብራም ትንሹን አኖሬዎስን ወልዳለች፡፡ ታላቁ አቡነ አኖሬዎስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ካረፉ በኋላ ወደ ትግራይ በመሄድ ፀዓዳ ዓንባ ከተባለ ቦታ ገዳም መሥርተዋል፡፡ ግብፃዊው አቡነ ያዕቆብ ከግብፅ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው የደብረ ሊባኖሱን እጨጌ አቡነ ፊልጶስን አስጠርተው ለስብከተ ወንጌል መስፋፋት “ኢትዮጵያ በአንድ ጳጳስ መወሰን የለባትም፡፡ ስለዚህ ዐሥራ ሁለት አበው መርጠን ክርስትና ይስፋፋ” ብለው ባቀረቡት ሐሳብ መሠረት አቡነ ፊልጶስ ዘደብረ ሊባኖስ፣ አቡነ አኖሬዎስ ዘሞረት፣ አቡነ ማትያስ ዘፈጠጋር፣ አቡነ ሳሙኤል ዘወገግ፣ አቡነ አኖሬዎስ ዘወረብ፣ አቡነ ታዴዎስ ዘጽላልሽ፣ አቡነ ገብረ ክርስቶስ ዘግድም፣ አቡነ መርቆሬዎስ ዘመርሐ ቤቴ፣ አቡነ አድኃኒ ዘዳሞት፣ አቡነ ቀውስጦስ ዘመሐግል፣ አቡነ ኢዮስያስ ዘወጅ፣ አቡነ ዮሴፍ ዘእናርያን መርጠው ሀገረ ስብከት ተሰጥቷቸው ለሐዋርያዊ ተልእኮ ተሠማሩ፡፡ እነዚህ ዐሥራ ሁለቱን ንቡራነ ዕድ ለስብከተ ወንጌል በመላዋ አገሪቱ ሲሠማሩ ለአቡነ አኖሬዎስ እንደ ግብጦን የተባለ ቦታ ደረሳቸው፡፡ ይህም ቦታ ከግንደ በረት እስከ ባሌ ያለውን አገር ያካትታል፡፡ እርሳቸውም ሰባት ታቦታት ይዘው በመሄድ አብያተ ክርስቲያናት ተክለው ክርስትናን አስፋፍተዋል፡፡ በአካባቢው ስብከተ ወንጌልን ካስፋፉ በኋላ ባርጋባን የተባለ የአካባቢው ሰው ተአምራታቸውንና ትምህርታቸውን ተመልክቶ በጽጋጋ ገዳም እንዲመሠርቱ ስለነገራቸው አቡነ አኖሬዎስ በጽጋጋ ገዳም መሥርተዋል፡፡

ቅድስት ድንግል ታኦግንስጣም ተጋድሎዋን ከፈጸመች በኋላ እግዚአብሔርንም አገልግላ ደስ አሰኝታ በዚያ ገዳም በደናግሉ መካከል በሰላም በፍቅር አረፈች። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አባት_ዲዮናስዮስ በዚችም ቀን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ዐሥራ አራተኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አባት ዲዮናስዮስ አረፈ። ይህንንም ቅዱስ ንጉሥ ዳኬዎስ ሊገድለው ፈልጎት ነበር ግን እግዚአብሔር ሠወረው ይህም አባት ብልህ አዋቂ ስለነበረ ብዙዎች የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትን ተረጎመ። በዘመኑም በሮም ንጉሥ በከሀዲ ዳኬዎስ እጅ ቅዱስ መርቆሬዎስ በሰማዕትነት አረፈ። ሁለተኛም ሰባቱ ደቂቅ ሦስት መቶ ሰባ ሁለት ዓመት አንቀላፍተው ነቁ እሊህም ለጣዖታት ሊአሰግዳቸው በፈለጋቸው ጊዜ ከዳኬዎስ ፊት የሸሹ ከኤፌሶን አገር ከታላላቆች ተወላጆች ወገን የሆኑ ናቸው። ዳግመኛም በዘመኑ የመነኰሳት አለቃ ገዳማትን የሠራ ግብጻዊው ታላቁ እንጦንዮስ ለመጀመሪያ ጊዜ መነኰስን ሆነ። ይህም ቅዱስ ዲዮናስዮስ በሊቀ ጵጵስናው ሹመት ዐሥራ ሁለት ዓመት ኖረ። መንጋዎቹንም በትክክል በፍቅር አንድነት ጠበቃቸው እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ። በመስቀሉ ላዳነን ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መስከረም_17 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም ዐሥራ ሰባት በዚህች ቀን #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ የተሰቀለበት የከበረ #መስቀል በዓሉ ነው፣ #የቅድስት_ድንግል_ታኦግንስጣ እና የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ_ዲዮናስዮስ እረፍታቸው ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #በዓለ_መስቀል መስከረም ዐሥራ ሰባት በዚች ቀን ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ለከበረ መስቀል በዓሉ ነው። ይህም የጻድቁ ንጉሥ የቈስጠንጢኖስ እናት ንግሥት ዕሌኒ ከተሠወረበት የገለጠችው ነው። የጎልጎታን ኮረብታ በአስጠረገች ጊዜ የከበረ መስቀልን አገኘችው ታላቅ ኮረብታም የሆነበት ምክንያት እንዲህ ነው። ብዙዎች ድንቆች ተአምራት ክብር ይግባውና ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመቃብሩና ከመስቀሉ የሚገለጡ ሁነው ሙታን ይነሡ ነበርና የጎበጡና በሽተኞች ሁሉ ይፈወሱ ነበር። ስለዚህም አይሁድ ተቆጡ እንዲህም ሥርዓትን ሠርተው አዘዙ በይሁዳ አገር ሁሉና በኢየሩሳሌም ቤቱን የሚጠርግ ሁሉ ወይም አፈር ወይም ጉድፍ የሚጠርግ በናዝሬቱ ኢየሱስ መቃብር ላይ ይጥል ዘንድ እንዲህም እያደረጉ ዕሌኒ ንግሥት እስከ መጣች ድረስ ከሦስት መቶ ዓመት በላይ ኖሩ። እርሷም በመጣች ጊዜ ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብርን እስከ አሳዩዋት ድረስ አይሁድን ይዛ አሠቃየቻቸው ያንን ኮረብታም እስከ ጠረጉ ድረስ አስገደደቻቸው የከበረ መስቀሉም ከተቀበረበት ተገልጦ ወጣ። ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያንም ተሠራች በዚች ቀንም አከበሩዋት ለመስቀሉም በዓልን መስከረም ዐሥራ ሰባት ቀን አከበሩለት። የክርስቲያን ወገኖች ሁሉም ከሀገሮቻቸው በመምጣት ክብር ይግባውና ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤውን በዓል እንደሚያከብሩ ለመስቀልም ታላቅ በዓልን የሚያክብሩ ሆኑ። ክርስቲያኖችም በጎዳና እየተጓዙ ሳሉ ስሙ ይስሐቅ የሚባል አንድ ሳምራዊ ሰው ከእርሳቸው ጋር ነበር ከእርሱም ጋር ብዙዎች ሳምራውያን ነበሩ ይህ ይስሐቅም የክርስቲያን ወገኖችን ለምን በከንቱ ትደክማላችሁ ለዕንጨትስ ልትሰግዱ እንዴት ትሔዳላችሁ እያለ ይሣለቅባቸው ነበር። ከክርስቲያን ወገኖችም ስሙ አውዶኪስ የሚባል አንድ ቄስ አለ ሕዝቡም በጎዳና ሲጓዙ የሚጠጡት ውኃ አላገኙም ነበርና ተጠሙ። ወደ አንድ ጉድጓድም ሔዱ በውስጡም መሪር የሆነና የገማ ውኃ አገኙ እጅግም በውኃ ጥማት ተሠቃዩ። ይስሐቅም እጅግ ይሣለቅባቸው ጀመረ የቀናች ሃይማኖት ካለቻችሁ ይህ የገማና የመረረ ውኃ ተለውጦ እስቲ ጣፋጭ ይሁን ይላቸው ነበር። ቀሲስ አውዶኪስም በሰማ ጊዜ መንፈሳዊ ቅናትን ቀንቶ ከዚያ ሳምራዊ ይስሐቅ ጋር ተከራከረ ያ ሳምራዊም በመስቀል ስም የተአምራት ኃይልን ከአየሁ እኔ በክርስቶስ አምናለሁ አለ። ያን ጊዜም ቀሲስ አውዶኪስ በዚያ በገማ ውኃ ላይ ጸለየ ውኃውም ወዲያውኑ ጣፋጭ ሆነ ከእርሱም ሕዝቡ ሁሉ እንስሶቻቸውም ጠጡ። ሳምራዊ ይስሐቅ ግን በተጠማ ጊዜ በረዋት ከያዘው ውኃ ሊጠጣ ፈለገ ግን ገምቶ ተልቶ አገኘውና መሪር ለቅሶን አለቀሰ። ወደ ከበረ ቄስ አውዶኪስም መጥቶ ከእግሩ በታች ሰገደ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አመነ በከበረ ቄስ በአውዶኪስ ጸሎት ጣፋጭ ከሆነው ከዚያ ውኃም ጠጣ። በዚያም ውኃ ውስጥ ታላቅ ኃይል የሚሠራ ሆነ እርሱ ለአማንያን የሚጣፍጥ ሲሆን ለከሀዲያንና ለአረማውያን የሚመር ሆነ በውስጡም የብርሃን መስቀል ታየ በአጠገቡም ውብ የሆነች ያማረች ቤተ ክርስቲያንን ሠሩ። ሳምራዊ ይስሐቅም ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ በደረሰ ጊዜ ወደ ኤጴስቆጶሱ ሒዶ ከቤተሰቡ ጋር የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቀ። የከበረ መስቀልም ዳግመኛ የተገለጠበት መጋቢት ዐሥር ቀን ነው ዜናውንም በዚሁ ቀን ጽፈናል። ምእመናንም በታላቁ ጾም መካከል በዓሉን ማክበር ስለአልተቻላቸው በዓሉን ቤተ ክርስቲያኑ በከበረችበት ቀን አደረጉ ይህም መስከረም ዐሥራ ሰባት ቀን ነው በዚህም ቀን አስቀድሞ ከከበረ መቃብር በንግሥት ዕሌኒ እጅ የተገለጠበት ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅድስት_ታኦግንስጣ በዚችም ቀን የከበረች ሮማዊት ታኦግንስጣ አረፈች ። ይቺም ቅድስት በደጋጎች ነገሥታት በአኖሬዎስና በአርቃዴዎስ ዘመን የነበረች ናት። በዚያም ወራት የህንድ ንጉሥ መልእክተኞች እጅ መንሻ ይዘው ወደ ንጉሥ አኖሬዎስ መጡ በሚመለሱም ጊዜ ይችን ድንግል ታኦግንስጣን አገኟት የምታነበውም መጽሐፍ በእጅዋ ውስጥ ነበር ወደ አገራቸውም ነጥቀው ወሰዷት ለህንድ ንጉሥም ሚስቶቹንና ቤተሰቦቹን የምትጠብቅ ሆነች። በአንዲት ዕለትም የንጉሡ ልጅ አስጨናቂ በሆነ ደዌ ታመመ የከበረች ታኦግንስጣም ወስዳ በብብቷ ታቅፋ በመስቀል ምልክት አማተበችበት በዚያንም ጊዜ ዳነ ከእርሷም ስለ ተደረገው ተአምር የዚች የከበረች ድንግል ታኦግንስጣ ዜናዋ በሀገሩ ሁሉ ተሰማ ከዚያችም ቀን ወዲህ በእነርሱ ዘንድ እንደ እመቤት እንጂ እንደ አገልጋይ አልሆነችም። ከዚህም በኋላ የህንድ ንጉሥ ወደ ጦርነት በሔደ ጊዜ ጉም ጭጋግ ዐውሎ ነፋስና ጨለማ በላዩ መጣ ንጉሡ ግን የከበረች ታኦግንስጣ ስታማትብ ስለአየ በመስቀል ምልክት ማማተብን ያውቅ ነበርና ያን ጊዜ በጭጋጉ በጉሙ በጨለማውና በጥቅሉ ነፋስ ላይ በመስቀል ምልክት አማተበ። ወዲያውኑ ፀሐይ ወጣ ታላቅ ጸጥታም ሆነ ጠላቶቹንም በዚሁ የመስቀል ምልክት ድል አደረጋቸው እጅግም ደስ አለው። ንጉሡም ከጦርነት በተመለሰ ጊዜ ለከበረች ታኦግንስጣ። ከእግርዋ በታች ሰገደ እርሱንና ቤተሰቦቹን ሁሉ የሀገሩንም ሰዎች የከበረች የክርስትና ጥምቀትን ታጠምቀው ዘንድ ለመናት ቅድስት ታኦግንስጣም እንዲህ አለችው ይህን አደርግ ዘንድ ለእኔ አይገባኝም የሚያጠምቃችሁን ካህን ይልክላችሁ ዘንድ ወደ ንጉሥ አኖሬዎስ ላኩ። ያን ጊዜም ከወገኖቹ ጋር የሚያጠምቀውን ካህን እንዲልክለት የህንድ ንጉሥ ወደ ንጉሥ አኖሬዎስ መልእክተኞችን ላከ ንጉሥ አኖሬዎስም ልመናውን ተቀብሎ የሚያጠምቃቸውን ቄስ ላከ ቄሱም አጠመቃቸው መሥዋዕትንም ቀድሶ ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው እግዚአብሔርንም የምትወድ የከበረች ድንግል ታኦግንስጣ እጅግ ደስ አላት ያንንም ቄስ መንፈሳዊ ሰላምታ ሰጠችውና ከእርሱ ቡራኬ ተቀበለች እርሱም ከእርሷ በረከትን ተቀበለ። ከዚህም በኋላ ለራስዋ ገዳም ሠራች ብዙዎች ደናግልም ተሰበሰቡ የምንኩስና ልብስንም በመልበስ እንደርሷ መሆንን ወደዱ እርሷም እመ ምኔት ሆነች። ያም ባሕታዊ ቄስ የክርስትና ጥምቀትን ከአጠመቃቸው በኋላ ወደ ንጉሥ አኖሬዎስ ተመልሶ የህንድን ሰዎች እንዳጠመቃቸውና ክብር ይግባውና ወደ ክርስቶስ ሃይማኖት እንደገቡ ነገረው። ንጉሥ አኖሬዎስም እጅግ ደስ አለው የሮሜ አገር ሊቀ ጳጳሳትንም ይህን ባሕታዊ ኤጲስቆጶስ አድርጎ እንዲሾምላቸው አዘዘው እርሱም ኤጲስቆጶስነት ሹሞ ከህንድ ሰዎች ላከላቸው እጅግም ደስ አላቸው። ከዚህም በኋላ ታላቅ ቤተ ክርስቲያን ሊሠሩ ጀመሩ ምሰሶዎችንም በፈለጉ ጊዜ አላገኙም በዚያም አከባቢ ታላቅ የጣዖት ቤት ነበረ በውስጡም ያማሩ ምሰሶዎች አሉ። ድንግሊቱ ታኦግንስጣም ክብር ይግባውና ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ብዙ በማልቀስ ለመነች ያን ጊዜም እሊያ ምሰሶዎች ከጣዖት ቤት ፈልሰው ሐናፂዎች ከሚሹት ቦታ በቤተ ክርስቲያን መካከል ተተከሉ አማንያን ሁሉ ክብር ይግባውና ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን አመሰገኑት ጣዖትን ሲያመልኩ የነበሩም ጣዖቶቻቸውን ሰብረው ክብር ይግባውና ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት ተመልሰው ገቡ በዚያችም አገር ታላቅ ደስታ ሆነ።

ሁለተኛም የራጉኤልን ልጅ ሣራን ያገባት ዘንድ ተናገረው እግዚአብሔርም ይጠብቀዋልና እንዳይፈራ አጽናናው። ወደራጉኤል ቤትም በደረሱ ጊዜ ሣራ ተቀብላ ደስ አሰኘቻቸው ከዚህም በኋላ ጦቢያ ሣራን ወደዳት። እርሷንም ይሰጠው ዘንድ አባቷን ጠየቀው አባቷም ለሰባት ባሎች አጋብቷት ሰባቱም እንደሞቱ ነገረው ጦብያም የእግዚአብሔር ፈቃድ ይሁን አለ። ወደ ጫጉላ ቤትም በአገቧቸው ጊዜ ሩፋኤል የነገረውን ቃል አስታወሰ የዓሣውንም ጉበትና ልብ ከደቀቀ ዕጣን ጋር አጤሰ ያን ጊዜ አስማንድዮስ የተባለ ጋኔን ሸሸ መልአክ ሩፋኤልም ይዞ ለዘላለሙ አሠረው። ጦቢያም ሚስቱን ሣራን ይዞ ደስ ብሎት ወደ አባቱ ቤት ተመለሰ አባትና እናቱም በደስታ ተቀበሉት የአባቱንም ዐይኖች በኳለ ጊዜ እንደ ጭጋግ ሁኖ ከዐይኖቹ ተገፈፈ ዐይኑን ዐሸ ወዲያውኑ ድኖ ልጁን አየ። ከዚህም በኋላ የከበረ መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል ራሱን ገለጠላቸው ብዙ ነገርንም ነግሮአቸው ወደ ሰማይ ዐረገ። ከዚህም በኋላ ከወገኖቹ ጋር ተድላ ደስታን አደረገ ክብር ይግባውና ስለ ክርስቶስ መከራ እንዲህ ብሎ ትንቢት ተናገረ እርሱ በኃጢአታችን ይገርፈናል ደግሞ እርሱ ይቅር ይለናል ሁለተኛም መከራህን የሚያስቡ የተመሰገኑ ናቸው ። እነርሱ ክብርህን በአዩ ጊዜ በአንተ ደስ ይላቸዋልና አለ። ዳግመኛም ስለ ኢየሩሳሌም መታነፅ እንዲህ ብሎ ትንቢት ተናገረ ኢየሩሳሌም ሰንፔር መረግድ በሚባል በከበረ ዕንቁ ትሠራለች ድልድልዋ፣ ቅጽርዋ፣ አደባባይዋ፣ ደጆቿም በከበረ ዕንቊ በጠራም ወርቅ ይሠራሉ አደባባይዋም ቢረሌ፣ አትራኮስ፣ ሶፎር በሚባል ዕንቁ ይሠራልና በመንገድዋ ሁሉ ሁሉም እግዚአብሔርን አስቀድሞ የነበረ ወደፊትም የሚኖር እያሉ ያመሰግኑታል ደግሞም ከዓለማት ሁሉ ጽዮንን ከፍ ከፍ ያደረጋት እግዚአብሔር ይመስገን ይላሉ። ሁለተኛም የእስራኤል ምርኮኞች ከባቢሎን ወደ ኢየሩሳሌም እንደሚመለሱ ትንቢት ተናገረ ሁለተኛም ደግሞ ዮናስ ከነነዌ እንዲወጣ ልጁን ጦብያን አዘዘው። ዳግመኛም ልጁን እንዲህ አለው ልጄ ሆይ ምጽዋት እንደምታድንና እንደምታጸድቅ ተመልከት ይህን ተናግሮ በዐልጋው ላይ ሳለ በመቶ ኀምሳ ስምንት ዘመኑ አረፈ በክብርም ቀበሩት። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_አጋቶን_ባህታዊ በዚህ ቀን ታላቁ አባት አባ አጋቶን አረፈ፡፡ ይህን ቅዱስ ታላቅ ጻድቅ ገዳማዊና የእግዚአብሔር ሰው ሲሆን አንደበቱን ከክፋት ይከለክል ዘንድ ለ30 ዓመታት ድንጋይ ጐርሶ ኖሯል። ይህንን ቅዱስ ሊቃውንት ሲገልጹት "ክምረ ክምር ጽድቁ እስከ አስተርአየ" ይሉታል። ትእግስቱ ደግነቱ አርምሞው ትሩፋቱ ከመነገር በላይ ነው። በነበረበት በ4ኛው መቶ ክ/ዘመንም እንደ ኮከብ ያበራ ታላቅ አባት ነው። ታላቁ ገዳማዊ አባት አጋቶን የታላቁ መቃርዮስ የመንፈስ ልጅ ነው። ገዳመ አስቄጥስ እልፍ አእላፍ ቅዱሳንን ስታፈራ ይህ አባት ቅድሚያውን ይይዛል። ምንም በብዛት የሚታወቀው በአርምሞው (በዝምታው) ቢሆንም ባለ ብዙ ትሩፋት አባት ነው። የሚገርመው የቀደሙ አባቶቻችን የፈለገውን ያህል መናኝ ቢሆኑም የሰው ጥገኛ መሆንን አይፈልጉም። "ሊሠራ የማይወድ አይብላ" የሚለውን መለኮታዊ ትዕዛዝ መሠረት አድርገው ከተጋድሎ በተረፈቻቸው ሰዓት ሥራ ይሠራሉ። አንዳንዶቹ እንደሚመስላቸው ምናኔ ሥራ መፍታት አይደለምና ሰሌን ዕንቅብ ሠፌድ የመሳሰለውን ይሠፋሉ። ታላቁ አባ አጋቶንም በአንደበቱ ድንጋይ ጐርሶ በእግሮቹ ቀጥ ብሎ ቆሞ እንቅቦችን ይሠፋ ነበር። ቅዱሱ የሰፋውን ወደ ገበያ ይወጣል በጠየቁትም ዋጋ ሽጦት አንዲት ቂጣ ይገዛል። የተረፈውን ገንዘብ ግን እዚያው ለነዳያን አካፍሎት ይመጣል እንጂ ወደ ገዳሙ አይመልሰውም። አንድ ቀን እንደልማዱ የሠፋቸውን እንቅቦች ተሸክሞ ወደ ገበያ ሲሔድ መንገድ ላይ አንድ የኔ ቢጤ ወድቆ ያገኛል። እንደ ደረሰም ስመ እግዚአብሔር ጠርቶ ይለምነዋል። አባ አጋቶን ከእንቅቦቹ ውጪ ምንም ነገር አልነበረውምና "እንቅቡን እንካ" አለው። ነዳዩ ግን ወይ የሚበላ ካልሆነም ገንዘብ እንደሚፈልግ ይነግረዋል። ወዲያው ደግሞ "የምትሠጠኝ ነገር ከሌለህ ለምን ወደ ገበያ ተሸክመህ አትወስደኝም?" አለው። የነዳዩ አካል እጅግ የቆሳሰለ በመሆኑ እንኩዋን ሊሸከሙት ሊያዩትም የሚከብድ ነበር። ጻድቁ ግን ደስ እያለው ያለማመንታት አንስቶ ተሸከመው። ከረጅም መንገድ በኋላ ከገበያ በመድረሳቸው አውርዶ ከጐኑ አስቀመጠው። ያ ነዳይ አላፊ አግዳሚውን ሁሉ ቢለምንም የሚዘከረው አጣ። አባ አጋቶን አንዷን እንቅብ ሲሸጥ "ስጠኝ?" ይለዋል። ጻድቁም ይሠጠዋል። እንዲህ "ስጠኝ" እያለ የእንቅቦችን ዋጋ ያ ነዳይ ወሰደበት። አባ አጋቶን ግን ምንም ቂጣ ባይገዛም በሆነው ነገር አልተከፋምና ሊሔድ ሲነሳ ነዳዩ "ወደ ቦታየ ተሸክመህ መልሰኝ" አለው። አባቶቻችን ትእግስታቸው ጥግ የለውምና ጐንበስ ብሎ በፍቅር አንስቶት አዘሎት ሔደ። ካነሳበት ቦታ ላይ ሲደርሱ ይወርድለት ዘንድ ጻድቁ ቆመ። ነዳዩ ግን አልወርድም አለ። ትንሽ ቆይቶ ግን ለቀቀው ሊያየው ዞር ቢል መሬት ላይ የለም። ቀና ሲል ግን ያየውን ነገር ማመን አልቻለምና ደንግጦ በግንባሩ ተደፋ። ነዳይ መስሎ እንዲያ ሲፈትነው የነበረው ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ነበርና ክንፎቹን ዘርግቶ በብርሃን ተከቦ በግርማ ታየው ከወደቀበትም አነሳው። "ወዳጄ አጋቶን ፍሬህ ትእግስትህ ደግነትህ ግሩም ነውና ዘወትር ካንተ ጋር ነኝ" ብሎት ተሰወረው፤ ጻድቁም በደስታ ወደ በዓቱ ሔደ። አባ አጋቶን ተረፈ ዘመኑን በአርምሞ ኑሮ ዐርፏል። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን ።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መስከረም 16 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም በአስራ ስድስት በዚህች ቀን #ከጌታችን_መቃብር_ላይ_ቤተክርስቲያን_የታነፀችበትና_የተቀደሰችበት ዕለት፣ ከንፍታሌም ነገድ የሆነ የገባኤል ልጅ #ጦቢት_ዕረፍት ነው፣ ተራ ነገርን እንዳይናገር ድንጋይ ጎርሶ የኖረ #አባ_አጋቶን_ባሕታዊ አረፈ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ሕንጸታ_ለኢየሩሳሌም መስከረም ዐሥራ ስድስት በዚች ቀን ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር ላይ ቤተ ክርስቲያን የታነፀችበትና የተቀደሰችበት ነው። ደግሞ በኢየሩሳሌም አገር ንግሥት ዕሌኒ የገለጠቻቸው የከበሩ ቦታዎች ሁሉ የተሠሩበትና የከበሩበት ሆነ። ይህም እንዲህ ነው ልጇ ቁስጠንጢኖስ በነገሠ በሃያ ዓመት ቅዱሳን የሆኑ ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት አባቶችን በኒቅያ ከተማ ከሰበሰበ በኋላ ቅድስት እናቱ ዕሌኒ እንዲህ አለችው ልጄ ሆይ እኔ ወደ ቅድስት አገር ኢየሩሳሌም በመሔድ የክብር ንጉሥ የሆነ የክርስቶስን ዕፀ መስቀል ፈልጌ አወጣ ዘንድ ለእግዚአብሔር ስዕለትን ተስያለሁ። ቁስጠንጢኖስም ሰምቶ በዚህ ነገር ደስ አለው ከብዙ ሠራዊትም ጋር ብዙ ገንዘብ ሰጥቶ ላካት የከበሩ የግምጃ ልብሶችንም ሰጣት እርሷም ወደ ኢየሩሳሌም በደረሰች ጊዜ ከከበሩ ቦታዎች ተባረከች። ከዚህም በኋላ ስለ ከበረና አዳኝ ስለ ሆነ ዕፀ መስቀል መረመረች በታላቅ ድካምና ችግር አገኘችውና ታላቅ ክብርን አከበረችው በታላቅ ምስጋናም አመሰገነችው። ከዚህም በኋላ በጎልጎታ በቤተልሔምም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደበት ዋሻ ደግሞ በጽርሐ ጽዮን የእመቤታችን ማርያም ሥጋዋ በተቀበረበት በጌቴሴማኒ በደብረ ዘይትም በከበሩ ቦታዎች ሁሉ የቤተ መቅደስ መሠዊያ እንዲሠሩ አዘዘች። ዳግመኛም በዕንቁ በወርቅና በብር እንዲአስጌጧቸው አዘዘች። በኢየሩሳሌምም ስሙ መቃርስ የሚባል ኤጲስቆጶስ አለ። እርሱም ንግሥት ዕሌኒን እንዲህ ብሎ መከራት ይህን እንዲህ አትሥሪ ከጥቂት ዘመናት በኋላ በዚህ አገር ሊነግሡ አሕዛብ ይመጣሉ። ሁሉን ይማርካሉ ቦታዎችንም ያፈርሳሉ ወርቁን፣ ብሩን፣ ዕንቁውን ይወስዳሉና ነገር ግን ጠንካራ የሆነ የማይናወጽና የማይፈርስ ጥሩ ሕንፃ ልታሠሪ ይገባል ከዚህ የሚተርፈውንም ለድኆችና ለችግረኞች ስጪአቸው አላት። እርሷም የአባ መቃርስን ምክሩን ተቀብላ መኳንንቱ ሁሉ ለአባ መቃርስ በመታዘዝ በከበሩ ቦታዎች ሁሉ አብያተ ክርስቲያናትን እንዲአንፁ አዘዘቻቸው። ከዚህም በኋላ ንግሥት ዕሌኒ ወደ ልጅዋ ንጉሥ ቁስጠንጢኖስ በተመለሰች ጊዜ በኢየሩሳሌም ያደረገችውን ሁሉ ነገረችው ሰምቶ እጅግ ደስ አለው እንደገና ሌላ ብዙ ገንዘብና ሕንፃውን ተቆጣጥረው የሚያሠሩ ሹሞችን ላከ ለሚገነቡና ለሕንፃው ሥራ ለሚአገለግሉ ሁሉ ደመወዛቸውን ሳያጓድሉ ሁል ጊዜ ወደ ማታ እንዲሰጧቸው ንጉሡ አዘዘ። ስለ ደመወዛቸው እንዳይጮኹና እንዳያዝኑ እግዚአብሔርም ስለ ጩኸታቸው በእርሱ ላይ እንዳይቆጣ ይፈራልና። ጻድቅ ንጉሥ ቁስጠንጢኖስም በነገሠ በ፴ ዓመቱ የከበሩ ቦታዎች ሕንፃቸው በተፈጸመ ጊዜ ንዋየ ቅዱሳትን ዋጋቸው ብዙ ድንቅ የሆነ የከበሩ የግምጃ ልብሶችንም ላከ። ደግሞም ወደ ቁስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳሳት ኤጲስቆጶሳቶቹን በመያዝ እንዲዘጋጅ እንዲሁም ወደ አንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳትና ወደ እስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት ወደ አባ አትናቴዎስ ኤጲስቆጶሳቶቹን በመያዝ ሁሉም ሊቃነ ጳጳሳት ወደ ኢየሩሳሌም ተሰብስበው በከበሩ ቦታዎች ውስጥ የተሠሩትን ወይም የታነፁትን አብያተ ክርስቲያናት እንዲያከብሩ። ንጉሡም እንዳዘዘ ሁሉም ተሰበሰቡ እስከ መስከረም ወር ዐሥራ ስድስት ቀን ኑረው በዚች ቀን ሁሉንም አብያተ ክርስቲያናት መሠዊያቸውንም አከበሩአቸው የቁርባን ቅዳሴንም ቀድሰው ለምእመናን ሥጋውንና ደሙን አቀበሉ በዚችም ቀን ከቶ እንደርሱ ሆኖ የማያውቅ ታላቅ ደስታን ሆነ። የከበረ መስቀልንም በመሸከም በነዚያ በከበሩ ቦታዎች ዞሩ በውስጣቸውም ለእግዚአብሔር ሰገዱ አመሰገኑትም መስቀሉንም አከበሩት ወደ ሀገሮቻቸውም በሰላም በፍቅር ተመልሰው ገቡ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ጦቢት_ነቢይ በዚችም ቀን በፋርስ ንጉሥ አሜኔሶር እጅ ተማርኮ ወደ ነነዌ አገር የተወሰደ ከንፍታሌም ነገድ የገባኤል ልጅ ጦቢት አረፈ። ይህም ጻድቅ ጦቢት በሕይወቱ ዘመን ሁሉ ዕውነትና ቅን በሆነ ሕግ ጸንቶ የሚኖር ነው ከወገኖቹም ጋር ከመማረኩ በፊት ለችግረኞች ብዙ ምጽዋትን ይሰጥ ነበር ብዙ ጊዜም የበጎቹን ጠጉርና ከእህሉ ዐሥራቱን ይዞ ወደ ኢየሩሳሌም ይወጣ ነበር ከገንዘቡም ከሦስት አንዱን ለድኆች የሚሰጥ ነው። በዚያን ጊዜ ሕዝቡ ሁሉም ክደው በዓልና ደማሊ ለሚባሉ ጣዖታት ይሠው ነበር ። ወገኖቹም ወደ ነነዌ በተማረኩ ጊዜ ሁሉም የአሕዛብን እህል በሉ እርሱ ግን ሰውነቱን ይጠብቅ ነበር የአሕዛብን መብል እንዳይበላ እግዚአብሔርን ያስበው ነበርና። በአንዲት ዕለትም በአደባባይ የወደቀ በድን አግኝተው ነገሩት ወዲያውኑ እህል ሳይቀምስ ተነሥቶ ሔደ ፀሐይም እስከሚገባ ወደ አንድ ቤት ውስጥ አስገብቶ አኖረው ፀሐይ ሲገባም ቆፍሮ ቀበረው በዚያች ሌሊትም እንደ ኃጢአተኛ ሁኖ በእድሞ ሥር ተኝቶ አደረ። በእድሞውም ላይ ወፎች መኖራቸውን ስለ አላወቀ ፊቱን ገልጦ ሳለ ኩሳቸውን ከዐይኖቹ ላይ ጣሉበት ዓይኖቹም ተቃጠሉ ከእሳቸውም ጢስ ወጣ ታወሩም ባለመድኃኒትም ሊያድነው አልቻለም። በዚያንም ጊዜ ጦቢት ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ለመነ አቤቱ በቸርነትህ አስበኝ ወደ ችግረኛነቴም ተመልከት ለመማረክና ለመዘረፍ በአደረግኸን በእኔና በአባቶቼ ኃጢአት ተበቅለህ አታጥፋኝ። አሁንም በፊትህ ደስ የሚያሰኝህን ነገር አድርግ ከመኖር ሞት ይሻለኛልና በሞት እሰናበት ዘንድ አፈርም እሆን ዘንድ ነፍሴን የሚቀበል መልአክን እዘዝ። በዚያችም ዕለት የራጉኤል ልጅ ሣራን በጭኗ ያደረ ክፉ አስማንድዮስ የሚባል ጋኔን ለሰባት ባሎች አጋብተዋት ወደርሷ ሲገቡ ሁሉንም ስለገደላቸው ስለዚህ የአባቷ አገልጋዮች ያሽሟጥጧት ነበርና ከሽሙጣቸው ያድናት ዘንድ እያለቀሰች ወደ እግዚአብሔር ትለምን ነበር ጸሎቷና የጦቢት ጸሎትም በልዑል እግዚአብሔር በጌትነቱ ልዕልና ፊት ተሰማ። ጦቢትም በገባኤል ዘንድ አደራ ያስጠበቀውን የብሩን ነገር አሰበ ልጁ ጦብያንም ጠርቶ ሳልሞት በገባኤል ዘንድ አደራ ያስጠበቅሁትን ብር ትቀበል ዘንድ ከአንተ ጋራ የሚሔድ በደመወዝ የሚቀጠር አሽከር ፈልግ አለው። ጦብያም አባቴ ሆይ ያዘዝከኝን ሁሉ አደርጋለሁ አለ ከዚህም በኋላ አሽከር ሊፈልግ ሔደ ቅዱስ ሩፋኤልንም አሽከር በሚሆን ሰው አምሳል አገኘው እርሱም ከጦብያ ጋር መጣ ስሙንም አዛሪያ ነኝ አለ ጦቢትም ላካቸው። ሲሔዱም በመሸ ጊዜ ወደ ጤግሮስ ወንዝ ደረሱ ጦብያም ገላውን ይታጠብ ዘንድ ወረደ። ታላቅ ዓሣም ሊውጠው ተወረወረ ሩፋኤልም ጦብያን ዓሣውን ያዘው አትፍራው እረደውና ጉበቱን፣ ልቡንና፣ አሞቱን ያዝ አለው እርሱም እንዳዘዘው አደረገ። ጦብያም ሩፋኤልን አንተ ወንድሜ አዛርያ ይህ የዓሣ ሐሞት ጉበቱና ልቡ ምን ይደረጋል አለው። አዛርያ የተባለ መልአክም እንዲህ ብሎ መለሰለት ጋኔን ያደረበት ሰው ወንድ ወይም ሴት ጉበቱንና ልቡን ከደቀቀ ዕጣን ጋራ ያጤሱለት እንደሆነ ጋኔን ይሸሻል ሐሞቱም ዐይኖቹ የታወሩ ሰውን ቢኩሉት ይድናል።

111፡33) ብሎ እንደተናገረ እኔ ለፍጥረት ወገን ሁሉ አስባለሁ› አለኝ፡፡ ይህንንም ብሎኝ ሰላሙን ሰጥቶኝ ወደ ሰማያት ዐረገ፡፡››   አቡነ ገብረ ማርያም ያደረጓቸው ተአምራት ተነግረው የሚያልቁ አይደሉም፡፡ በብቸኝነት ሳለ በአንዲት አገር የሚኖር ልጁ የሞተበት ሰው የልጁን አስክሬን ወደ አባታችን አምጥቶ በፊታቸው አስቀመጠውና ‹‹አባታችን ሆይ ልጄ እንደሞተ ተስፋዬ ሁሉ ጠፍቷልና አሁን ብትወድ ከሞት አንሣው ባትወድ ግን እዚሁ ቅበረው›› እያለ አቀሰባቸው፡፡ አባታችንም የሰውየውን ሁኔታውን አይተው ፈጽመው አለቀሱ፡፡ ልቡናቸውም ታወከባቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ይጸልዩ ዘንድ ተነሡና ‹‹…በተቀበረ በ4ኛው ቀን አልዓዘርን ያስነሣኸው አሁንም ይህን ሕፃን አስነሣው…›› ብለው ከጸለዩ በኋላ የልጁን እጅ ይዘው ‹‹በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ተነሥ›› ብለው እፍ አሉበት፡፡ ያንጊዜም ሕፃኑ ከእንቅልፉ እንደሚነቃ አፈፍ ብሎ ተነሣ፡፡ ለአባቱም ‹‹ልጅህን ውሰድ ፈጣሪዬ አስነሣልህ›› ብለው ሰጡት፡፡ ሰውዬውም ከአግራቸው ሥር ሰግዶ የእግራቸውን ትቢያና ሰውነታቸውን ሁሉ ሳመው፡፡ ልጁንም ይዞ ፈጽሞ ደስ እያለው ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ በአንዲት ሀገርም አንድ ልጅ ብቻ ያላት አንዲት ሴት ነበረች፡፡ ልጁም ወደ አባታችን እየመጣ ‹‹አመንኩሱኝ›› እያለ ሁልጊዜ ይጠቃቸው ነበር፡፡ አንድ ቀንም እንዲሁ መጣና ‹‹አባት ሆይ ካላመነኮሱኝ ወደሌላ ሰው ዘንድ ሄጄ እመነኩሳለሁ›› አላቸው፡፡ በዚህም ጊዜ አባታችን ፈቃደ እግዚአብሔርን ጠይቀው የፍላጎቱን ፈጸሙለትና አመነኮሱት፡፡ ወላጅ እናቱም መጥታ ልጇ የምንኩስናን ልብስ እንደለበሰ ባየች ጊዜ እያለቀሰች ሄደችና ራሷን ወደ ገደል ውስጥ ጨመረች፣ ሞችም፡፡ ሰዎችም ተሰብስበው አለቀሱላትና አስክሬኗን ተሸከመው ይቀብሯት ዘንድ ወደ ቤተ ክርስቲያን ወሰዷት፡፡ ሰዎችም ወደ አባታችን መጥተው ‹‹ሴትዮዋ ከመቀበሯ በፊት መጥተው ይዩዋት›› አሏቸው፡፡ አባታችንም ወደ አስክሬኗ አልመለከትም›› አሉ፡፡ እነርሱም በእግዚአብሔር ስም ባማሏቸው ጊዜ አባታችን አስክሬኗ ወዳለበት መጡና አዩዋት፡፡ በማግሥቱም ከገነዟት በኋላ አባታችን ከመዝገበ ጸበላቸው በአፏና በጆሮዎቿ ጸበልን ጨመሩባት፡፡ በፊቷም ‹‹እፍ›› አሉባትና ‹‹በጌታዬ በፈጣሪዬ በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ተነሺ›› አሏት፡፡ ያንጊዜም አፈፍ ብላ ከሞት ተነሣች፡፡ አባታችን ከሞት ያስነሷቸው ሰዎች እንዲሁ በጣም ብዙ ናቸው፡፡ 27 ዓመት ሙሉ ሆዱን የታመመ አንድ ሰው ነበር፡፡ እርሱም ከቤተሰቦቹ ጋር ወደ አቡነ ገብረ ማርያም በመምጣት ጉዳዩን ሳይነግራቸው አንድ ቀን ቆየ፡፡ ከዚህም በኋላ አባታችን የመጣበትን ጉዳዩን በጠየቁት ጊዜ ‹‹አባት ሆይ ሃያ ሰባት ዓመት ሙሉ ታመምኩ፣ እህል አልበላም ውኃም አልጠጣም›› አላቸው፡፡ አባታችንም ሆዱን ይዘው በእጃቸው አሻሹትና ምራቃቸውን ቀቡት፡፡ በዚህም ጊዜ በሆዱ ውስጥ ልዩ ልዩ ዓይነት ድንፆች ተሰሙ፡፡ በውሻ ድንፅ አምሳል፣ በድመት ድንፅ አምሳል፣ በዝንጀሮ ድንፅ አምሳልና በቁራዎቸ ድንፅ አምሳል ጮኸ፡፡ አባታችንም ልጁን ‹‹ልጄ ሆይ እግዚብሔር አድኖሃልና ወደ ቤትህ ተመለስ›› አሉት፡፡ ልጁም ‹‹አባቴ ሆይ ተመልሼ ወደቤቴ አንገባም እስከ ዕለቴ ሞቴ ድረስ አልመለስም ከአንተም አልለይም›› አላቸው፡፡ አባታችንም ‹‹በዚህ መኖር ክፍልህ አይደለምና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለፈወሰህ ወደ ቤትህ ተመለስ›› አሉት፡፡ በደስታም ወደ ቤቱ ሄደና በሌላ ጊዜ ከብዙ ሰዎች ጋር መጥቶ አባታችን  ያደረጉለትን ተአምር ለሕዝቡ ሁሉ መሰከረ፡፡ አቡነ ገብረ ማርያም በእንዲህ ዓይነት አገልግሎት በተአምራታቸው ድውያንን እየፈወሱ ሙታንን እያስነሡ በወንጌል ቃል የነፍስን ቁስል እየፈወሱ የጌታችንንም መከራውን እያሰቡ ራሳቸውን ከመከራው ተሳታፊ በመሆን ብዙ ከደከሙ በኋላ በሥጋ ሞት ከማረፋቸው በፊት ቅዱሳን መላእክት ነጥቀው ገነትንና ሲኦልን አሳይተዋቸዋል፡፡ ጌታችንም በመጨረሻ ተገልጦላቸው ‹‹ወዳጄ ገብረ ማርያም ሆይ ከፍጹም ድካምና መታከት ከኃዘንም ታርፍ ዘንድ ወደ ፍጹም ደስታና ወደ ዘላለማዊ ዕረፍት ወደ እኔ ና›› አላቸው፡፡ እርሳቸውም ‹‹ጌታዬ ሆይ ምን ዋጋ ትሰጠኛለህ?›› ቢሉት ጌታችም ብዙ አስደናቂ ቃልኪዳኖችን ሰጣቸው፡፡ ‹‹እንደፈጠርኩህ አግኝቼሃለሁና ክብርህ እንደ መጥምቀ መለኮት ዮሐንስ ይሁንልህ›› አላቸውና በቅዱሳን እጆቹ ዳስሷቸው ቢስማቸው ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለይታለች፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_ጴጥሮስ_ዘሃገረ_ጠራው በዚችም ቀን ደግሞ ጠራው ከሚባል አገር ለከበረ ጻድቅ አባት አባ ጴጥሮስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ። ይህም ቅዱስ ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮ ለእግዚአብሔር የተሰጠ የስእለት ልጅ ነው። በአደገም ጊዜ ለታላቅ ተጋድሎ ክልቡ በቆራጥነት ተነሣ በቀንና በሌሊትም በጾም በጸሎት ተወስኖ ሁል ጊዜ እግዚአብሔርን የሚያገለግል ሆነ። ሰው የሚመገበውንም ምንም አይመገብም በዱር ያገኘውን ጥቂት ሣርን ይመገባል እንጂ። ደገኛው ምግቡ ግን ክብር ይግባውና የጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ስም ማመስገን ነው። በዚህም ምግባቸው የእግዚአብሔር ምስጋና የሆነ መላእክትን መሰላቸው። አሎን በሚባል የወንዝ ውኃ ላይም ይመላለስ ዘንድ ተገባው እግሮቹም አይርሱም ሥጋ እንደ ሌለው መንፈስ እስከ ሚሆን በሕይወቱ ዘመን ሁሉ ከችግር ብዛትና ከሚለብሰው የብረት ልብስ ክብደት የተነሣ ሥጋው እጅግ ደርቆ የረቀቀም ሁኖ ነበርና በእንዲህ ያለ ተጋድሎም እግዚአብሔርን ከአገለገለው በኋላ ወደርሱ ሔደ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን ።https://t.me/finotebirhan12

በአንደኛውም ቀን ከሰማይ እንዲህ የሚል ቃል ወደ አባታችን መጣ፡- ‹‹ገብረ ማርያም ሆይ በተክለ ሃይማኖት ወንበር ከተሾመ ከመርሐ ክርስቶስ እጅ የመላእክትን አስኬማ ትቀበል ዘንድ ወደ እርሱ ሂድ›› አላቸው፡፡ አባታችንም ወደ ደብረ ሊባኖስ ከመሄዳቸው በፊት አቡነ መርሐ ክርስቶስ በደብረ ሊባኖስ ሆኖ ይህን በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ዐውቆ ለደቀ መዛሙርቱ ‹‹እነሆ ከፀሐይ ይበልጥ የሚያበሩ ሦስት ከዋክብት ቅዱሳን ይመጣሉ›› አላቸው፡፡ አቡነ መርሐ ክርስቶስም እንደተናገረው እነ አቡነ ገብረ ማርያም ደብረ ሊባኖስ ደረሱ፡፡ አቡነ መርሐ ክርስቶስም የምንኩስናን ልብስ አለበሳቸው፡፡ አቡነ ገብረ ማርያም ከመነኮሱ በኋላ ወደ በዓታቸው ተመልሰው ከበፊቱ ይልቅ በጾም በጸሎት ሲተጉ ጌታቸን አሁንም ተገለጠላቸውና ‹‹በጾም በጸሎት ብቻ ተወስነህ አትቀመጥ ሂድና ወንጌልን አስተምር፣ ድውያንን ፈውስ፣ ሙታንን አንሣ…›› ብሎ ነገራቸው፡፡ ዳግመኛም በከበረ እስትንፋሱ እፍ አለባቸውና ‹‹መንፈስ ቅዱስን ተቀበል፤ ይቅር ያልካቸው ኃጢአታቸው ይቀርላቸዋል፣ ይቅር ያላልካቸው ኃጢአታቸው አይቀርላቸውም፡፡ የመንግሥተ ሰማያትን መክፈቻዎች እሰጥሃለሁ በምድር ያሰርከው በሰማያት የታሰረ ነው፤ በምድርም የፈታኸው በሰማያት የተፈታ ይሁን›› አላቸው፡፡ ጌታችን ለአቡነ ተክለ ሃይማኖት ‹‹ካህናት በሊቃነ ጳጳሳት አፍ ይሾማሉ አንተ ግን በመንፈስ ቅዱስ አፍ ተሾምህ›› እንዳላቸውና እንደሾማቸው ሁሉ አሁንም አባታችን አቡነ ገብረ ማርያምን እንዲሁ ብሎ ራሱ ሾማቸው፡፡ አባታችንም እንደታዘዙት ልዩ ልዩ ተአምራትን እያደረጉ ድውያንን እየፈወሱ ሙታንን እያስነሡ ወንጌልን ዞረው አስተማሩ፡፡ ቂሐ ወደምትባል ምድር ገብተው ጎሽ ወደምትባለው ሀገርም ደርሰው ጣዖታትን የሚያመልኩትን የሀገሪቱን ሰዎች አገኟቸው፡፡ ሰዎቹም የሚያመልኩትን ትልቅ ዘንዶ በመስቀሉ ባርኮ ከገደለው በኋላ በውስጧ ወንጌልን እያስተማረ ድውያንን እየፈወሰ ሲቆይ ሰዎቹም አባታችንን ‹‹ቅዳሴ ቀድስልን›› አሉት፡፡ አባታችንም ስለዚህ ነገር ጌታችንን በጸሎት በጠየቁት ሰዓት "ሳትናዘዛቸውና ሳታጠምቃቸው አትቀድስላቸው" የሚል ቃል ከሰማይ ወደ አባታችን መጣ፡፡ ያንጊዜም ሰዎቹን ሁሉ ሰብስቦ በአብ በወልደ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸውና ቅዳሴ ቀድሶ አቆረባቸው፡፡ እመቤታችን ልጇን ይዛ ወደ ግብጽ ከዚያም ወደ አገራችን ኢትዮጵያ ስትሰደድ በእግሯ እየሄደች በሞረት ዋሻ በአቡነ ዜና ማርቆስ ቦታ ግራርያ ከሚባል ቦታ ተቀምጣ እንደነበር የሐምሌው ድርሳነ ቅዱስ ዑራኤል ይናገራል፡፡ በኋላም ተጭነው ከእነ ልጇ በዚህ በአቡነ ገብረ ማርያም ገዳም በሆነ ቦታ ስታልፍ ጌታችን ለቅድስት እናቱ ‹‹ይህች ቦታ ሐንታ ትባላለች፣ በኋለኛው ዘመን በስምሽ የሚጠራ የእኔ ወዳጅና ታዛዥ የሆነ የታላቅ ጻድቅ ቦታ ትሆናለች›› ብሎ ስለነገራት በኋላም ትንቢቱ ደርሶ ጻድቁ ገዳማቸውን በዚሁ ቦታ ስለገደሙት ገዳሙ ‹‹አማን ደብረ ሐንታ›› ይባላል፡፡ ጻድቁ በመንዝና በመርሐ ቤቴ ከ1245-1268 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ ከ19 በላይ የተላያዩ አብያተ ክርስቲያናትን ተክለዋል፡፡ ጾም ጸሎተኛ ባሕታዊ ከመሆናቸው በተጨማሪ የወንጌል ገበሬ፣ ጻድቅና ደራሲም ናቸው፡፡ አቡነ ገብረ ማርያም በጣም ከሚታወቁበት ድርሰታቸው አንዱ የማኅሌተ ጽጌን ድርሰት ከታላቁ ሊቅ ከአባ ጽጌ ድንግል ጋር እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው እመቤታችንንና ፈጣሪ ልጇን በጎ መዓዛ ባላቸው አበባዎችና ፍሬዎች እየመሰለ የሚያመሰግነውን ድርሰቱን በመዝሙረ ዳዊት መጠን 150 አድገው ደርሰዋል፡፡ አቡነ ገብረ ማርያምና አቡነ ጽጌ ድንግል ማኅሌተ ጽጌን በጥምረት ሊደርሱት የቻሉት አቡነ ገብረ ማርያም በወሎ ክፍለ ሀገር በወረኢሉ አውራጃ ልዩ ስሙ ደብረ ሐንታ በሚባለው ገዳም የሕግ መምሕር ሆነው በተሾሙበት ወቅት ነው፡፡ እነዚህም ሁለት ቅዱሳን የዘመነ ጽጌ የማኅሌት አገልግሎትን ሳይለያዩ በሰላምና በፍቅር በአንድነት አግልግለዋል፡፡ ይኸውም የሆነው እንዲህ ነው፡- አንድ ዓመት አቡነ ገብረ ማርያም የክረምት መውጫና የዘመነ ጽጌ ዋዜማ በሆነው መስከረም 25 ቀን ከደብረ ሐንታ መጥቶ ደብረ ብሥራት አቡነ ጽጌ ድንግል ገዳም ገብተው ከመስከረም 25 ቀን እስከ ኅዳር 5 ቀን ያለውን የዘመነ ጽጌ የ40 ቀን አገልግሎት ከአቡነ ጽጌ ድንግል ጋር ፈጽመው ኅዳር 8 ቀን ወደ ደብራቸው ደብረ ሐንታ ይመለሳሉ፡፡ በሚቀጥለው ዓመት ደግሞ አቡነ ጽጌ ድንግል ከገዳማቸው ከደብረ ብሥራት ተነሥተው ወደ ደብረ ሐንታ ሄደው እንዲሁ እንደ አቡነ ገብረ ማርያም 40ውን ቀን አግልግሎ ይመለሳል፡፡ እነዚህ ሁለት ቅዱሳን እንደዚህ እያደረጉ በየተራ አንደኛው ወደ ሌላኛው ገዳም እየሄዱ እስከ ዕለተ ዕረፍታቸው ድረስ በፍጹም ፍቅርና በትሕትና አብረው ሲያገለግሉ ኖረዋል፡፡ ይኸውም በራሳቸው በአቡነ ገብረ ማርያም ገድል ላይ እና በአቡነ ዜና ማርቆስ ገድል ገጽ 72-73 ላይ በሰፊው ተጠቅሶ ይገኛል፡፡ የሁለቱ ድርሰታቸው የሆነው ‹‹ማኅሌተ ጽጌ›› ድርሰት የእመቤታችንንና የልጇን የጌታችንን ሥጋዊ ስደት የሚገልጽ ሲሆን በጨማሪም ስደት የማይገባው አምላካችን ወደ አህጉራችን አፍሪካ ተሰዶ የሠራቸውን ድንቅ ድንቅ ተአምራትና  የእመቤታችንን ንጽሕናዋን ቅድስናዋን አማላጅነቷን የሚያስረዳ ድንቅ መጽሐፍ ነው፡፡ አቡነ ገብረ ማርያም አዲስ አፍልሰው በሠሯት ቤተ ክርስያን ውስጥ ልጆቻቸው ተሰበሰቡና ‹‹አባታችን ሆይ የት እናድራለን? ማረፊያን ያዘጋጅልን ዘንድ እግዚብሔርን ለምነው›› አሉት፡፡ አባታችንም ‹‹ይህ ሥራ ለእኔ አይቻለኝምና እናንተ ለምኑት›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹አባታችን ሆይ አትበትነን›› ብለው ግድ አሉት፡፡ ልጆቹም ግድ ባሉት ጊዜ አባታችን ተነሥቶ ጸለየ፡፡ ስለዚህም ነገር ሲናገር አባታችን እንዲህ አለ፡- ‹‹ከዚህ ነገር አስቀድሞ በቁርባን ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይመጣና ይባርከኝ ነበር፣ እናቱ ድንግል ማርያምም ትባርከኝ ነበር፡፡ ስለዚህ ነገር ግን ጌታችን ተቆጣ፣ እምቢ አለኝ፡፡ ከእኔም ፊቱን መለሰ፡፡ እኔም ብዙ አለቀስኹ የእጁን ቡራኬ አጥቻለሁና፡፡ እናቱ ድንግል ማርያምም ፈጽሜ ሳለቅስ ባየችኝ ጊዜ ‹ወዳጄ ገብረ ማርያም ሆይ ለምን ታለቅሳለህ?› አለችኝ፡፡ እኔም እመቤቴ ሆይ ጌታዬና አምላኬ ፊቱን ከእኔ መልሷልና ስለዚህ አለቅሳለሁ አልኳት፡፡ እመቤታችን ማርያምም የተወደደ ልጇን ‹ልጄ ሆይ ወዳጅህ ገብረ ማርያምን በምን ሥራ አሳዘነህ?› አለችው፡፡ ጌታችንም ለድንግል እናቱ ‹እርሱ አሳዝኖኛል፣ የዮሴፍ ልጅ ያዕቆብ ‹ይህን ዓለም የሚወድ የእግዚአብሔር ጠላት ይሆናል› (ያዕ 4፡4) እንዳለ ከእኔ ፍቅር ይልቅ የዓለምን ፍቅር ወዷልና› አላት፡፡› እናቱ እመቤታችንም የተወደደ ልጇን ‹ልጄ ሆይ ወዳጅህ ገብረ ማርያምን አታሳዝነው ይቅር በለው ባጠባሁህ ጡቶቼ አምልሃለሁ› አለችው፡፡ ጌታችንም ይህን ጊዜ ቅድስት እናቱን ‹የላይኛውን ወይም የታችኛውን ይወድ እንደሆነ ጠይቂው› አላት፡፡ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤልም ከዚያ ቆሞ ነበርና ወደ ለእኔ ‹የላይኛው ያለህ መንግሥተ ሰማያትን ነው፣ የታችኛው ያለህ ይህች ዓለም ናት› አለኝ፡፡ እኔም ያንጊዜ ይህችን ዓለም አልፈልጋትም ነገር ግን ማረፊያ እንዲሰጠን በጸሎቴ የጠየቁት ልጆቼ ከሞቴ በኋላ ተስፋ እንዳይቆርጡ እንዳይበተኑም ብዬ ነው አለኩት፡፡ ጌታችንም ‹‹ገብረ ማርያም ሆይ ለምን ይህንን ታስባለህ? ለልጆችህ እኔ አስብላቸዋለሁና፡፡ ወዳጄ ዳዊት ‹የጻድቃን ልጆች ይባረካሉ፣ ክብርና ባለጠግነት በቤቱ ነው፣ ጽድቁም ለዘለዓለም ይኖራል› (መዝ

🔴#ስንክሳር መስከረም_15 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም ዐሥራ አምስት በዚህች ቀን #የቀዳሜ_ሰማዕት_ቅዱስ_እስጢፋኖስ ፍልሰተ አፅሙ ነው፣ #የአቡነ_ገብረ_ማርያም_ዘሐንታ እና #አቡነ_ጴጥሮስ_ዘሃገረ_ጠራው ዕረፍታቸው ነው፡፡   ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ ቀዳሜ_ሰማዕት_ቅዱስ_እስጢፋኖስ መስከረም ዐሥራ አምስት በዚች ቀን የዲያቆናት አለቃ የሰማዕታት መጀመሪያ ለሆነ ለቅዱስ እስጢፋኖስ የሥጋው ፍልሰት ሆነ። ይህም እንዲህ ነው ከአረፈበት ጊዜ ብዙ ዓመቶች ከአለፉ በኋላ ሦስት መቶ ዓመት ያህል ከዚያም የሚበዛ ጻድቁ ቈስጠንጢኖስ ሲነግሥ የቀናች ሃይማኖትም ተገልጣ የሕያው እግዚአብሔር አምልኮት በሁሉ ሲዘረጋ ያን ጊዜ የቅዱስ እስጢፉኖስ ሥጋ በአለበት አቅራቢያ የገማልያል ቦታ በትምባል በኢየሩሳሌም በአንዲት ቦታ አንድ ሰው ይኖር ነበር። የዚያም ሰው ስም ሉክያኖስ ነው ተጋዳይ የሆነ እስጢፋኖስም ብዙ ጊዜ በሕልም ተገለጠለት እንዲህም ብሎ አስረዳዉ እኔ እስጢፋኖስ ነኝ ሥጋዬ በዚህ ቦታ ተቀብሮ አለ። ያም ሉክያኖስ የሚባል ሰው የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ ወደ ሆነው መጥቶ በራእይ ያየውን ይህን ነገር ነገረው ኤጲስቆጶሱም ሰምቶ እጅግ ደስ አለው ያን ጊዜም ሁለት ኤጲስቆጶሳትን፣ ካህናትንና፣ የቤተ ክርስቲያንን ሰዎች ሁሉ ከእርሱ ጋራ ይዞ ተነሣ የቅዱስ እስጢፋኖስ ሥጋ በውስጡ ወዳለበት ወደዚያ ቦታ ደርሰው ሊቆፍሩ ጀመሩ ታላቅ ንውጽውጽታም ሆነ የቅዱስ እስጢፋኖስ ሥጋ በውስጡ ያለበት ሣጥን ተገለጠ ከእርሱ እጅግ በጎ የሆነው የሽቱ መዓዛ ሸተተ። በሰማያት ለእግዚአብሔር ምስገና ሆነ በምድርም ሰላም ለሰው ነፃነቱ ይሰጠው ዘንድ በጎ ፍቃድ እያሉ ሲያመሰግኑ የመላእክትን ቃሎች ሰሙ። እንዲህም መላልሰው ሦስት ጊዜ አመሰገኑ ኤጲስቆጶሳቱና ካህናቱም የቅዱስ እስጢፋኖስን ሥጋ በያዘ ሣጥን ፊት ለጌታ ሰገዱ ከዚያም በኋላ ወደ ጽርሐ ጽዮን እስኪያደርሱት ብዙ መብራቶችን አብርተው በመያዝ በማኀሌት ምስጋና እየዘመሩ ተሸከሙት። ከዚህም በኋላ እንዲህ ሆነ በኢየሩሳሌም ነዋሪ የሆነ የቊስጥንጥንያ ተወላጅ ስሙ እለእስክንድሮስ የሚባል ሰው ነበር ለቅዱስ እስጢፋኖስም ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያንን ሠርቶለት ሥጋውን አፍልሰው ወደርሷ ወስደው አኖሩት ከአምስት ዓመት በኋላም እለእስክንድሮስ አረፈ ሚስቱም በቅዱስ እስጢፋኖስ አስከሬን ጕን ቀበረችው። ከሌሎች አምስት ዓመቶችም በኋላ የእለእስክንድሮስ ሚስት የቧላን አስከሬን ወደ ቊስጥንጥንያ አገር ይዛ ልትሔድ አሰበች ባሏንም ወደ ቀበረችው እርሱ ባሏ ወደ ሠራት ቤተ ክርስቲያን ሔደች የባሏ ሥጋ ሣጥን ግን የቅዱስ እስጢፋኖስን ሥጋ በያዘ ሣጥን አምሳል ነበር በእግዚአብሔር ፈቃድ የቅዱስ እስጢፋኖስን ሣጥን ወስዳ እስከ አስቃላን ከተማ ተሸከመችው ከዚያም ወደ ቊስጥንጥንያ ልትጓዝ በመርከብ ተሳፈረች። በመርከብ ስትጓዝ ከሣጥኑ ጣዕም ያለው ምስጋናን የምትሰማ ሆነች እጅግም አድንቃ ያን ሣጥን ልታየው ተነሣች በውስጥ የቅዱስ እስጢፋኖስ ሥጋ ያለበት ሣጥን እንደሆነ ተረዳች ይህም የሆነው ክብር ይግባውና በእግዚአብሔር ፈቃድ እንደሆነም አወቀች ወደ ኢየሩሳሌም ትመለስ ዘንድ አልተቻላትም ይህንንም ታላቅ ጸጋ ስለሰጣት ልዑል እግዚአብሔርን አመሰገነች። ወደ ቍስጥንጥንያ አገርም በደረሰች ጊዜ ያቺ ሴት ወደ ንጉሡ ሒዳ የቅዱስ እስጢፋኖስን ዜና ከእርሱ የሆኑትን ተአምራት ወደ ቍስጥንጥንያ አገር ወደብም እንደ ደረሰ ነገረችው ሰምቶም እጅግ ደስ አለው ንጉሡም ከሊቀ ጳጳሳቱና ከካህናቱ ከብዙ ሕዝቦችም ጋር ወጣ ከወደቡም በክብር አንሥተው ወደ መንግሥት አዳራሽ እስከ አስገቡት ድረስ በፍጹም ደስታ እየዘመሩና እያመሰገኑ ተሸክመውት ተጓዙ። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከእርሱ ተአምራትን ገለጠ በሠረገላ ሥጋውን ጭነው በሁለት በቅሎዎች በሚስቡት ጊዜ ቍስጣንጢንዮስ ከሚሉት ቦታም ሲደርሱ የቅዱስ እስጢፋኖስንም ሥጋ በዚያ እንዲያኖሩ ስለ ፈቀደ የሚስቡት በቅሎዎች ቆሙ። አልተንቀሳቀሱም በቅሎዎችንም ይመቷቸው ጀመሩ የቅዱስ እስጡፋኖስን ሥጋ በዚህ ሊያኖሩ ይገባል የሚል ቃል ከአንዱ በቅሎ ሰሙ ይህንንም ያዩና የሰሙ ሁሉም አደነቁ። እግዚአብሔርንም አመሰገኑት የበለዓምንም አህያ ያናገራት እርሱ እነዚህን የቅዱስ እስጢፋኖስን ሥጋ የተሸከሙትን በቅሎዎች ያናገራቸው እርሱ እንደሆነ አወቁ። ንጉሡም በዚያ መልካም የሆነች ቤተ ክርስቲያን ሠርተው ይህን የከበረና ንጹሕ የሆነ ዕንቈ ባሕርይ በውስጧ እንዲያኖሩ አዘዘ። ይኸውም ለተመሰገነና ለተባረከ ሐዋርያ የዲያቆናት አለቃና የሰማዕታት መጀመሪያ ለሆነ እስጢፋኖስ ሥጋው ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_ገብረ_ማርያም_ዘደብረ_ሐንታ ጻድቁ አቡነ ገብረ ማርያም ምግባር ሃይማኖታቸው ከቀና፣ ትሩፋት ተጋድሎአቸው ከሰመረ ደጋግ ወላጆቻቸው ከአባታቸው ኒቆዲሞስ እናታቸው አመተ ማርያም በዐፄ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት ኅዳር 24 ቀን ተወለዱ፡፡ ዕደሜአቸው ለትምህርት ሲደር እነዚህ ደጋግ ወላጆቻቸው ፈሪሃ እግዚአብሔርንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እያስተማሩ አሳደጓቸው፡፡ አባታችን በልጅነታቸው የወላጆቻቸውን ላሞች እየጠበቁ ሳለ ከእለታት አንድ ቀን ጌታችን በወጣት አምሳል ተገለጠላቸውና ‹‹ወዳጄ ገብረ ማርያም ሆይ ለምን እንስሳትን ትጠብቃለህ ደቀ መዝሙሬ ጴጥሮስን ዓሣ ማጥመድን ትተህ ተከተለኝ እንዳልኹት በእንስሳት ፈንታ ሰውን ትጠብቅ ዘንድ …››› አላቸው፡፡ አባታችንም ይህንን በልቡናቸው ሲያወጡ ሲያወርዱ ለ2ኛ ጊዜ ጌታችን በሚያስፈራ ግርማ በእርሻ መካከል ተገለጠላቸው፡፡ ስለዚህም ነገር አባታችን ሲናገሩ ‹‹ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወጣት አምሳል ሁለት ሰዎች ከእኔ ጋር ሳሉ በእርሻ መካከል ወደ እኔ መጣ፤ እነዚያም ከእኔ ጋር የነበሩት ሁለት ሰዎች ባዩት ጊዜ እጅግ ደንግጠው ከግርማው የተነሣ ወዲያና ወዲህ ወደቁ፡፡ በኋላም ተነሥተው ያዩትን መሰከሩ፡፡ ዳግመኛም በሦስተኛ መምጣት ጌታችን እንዲህ አለኝ፡-  ‹ለምን ዘገየህ አብርሃምን ለአባቱ ርስት ለይቼ ያወጣሁት እኔ እንደሆንኹ አላወቅህምን?አለኝ፡፡" ከዚህም በኋላ አባታችን "እናት አባቱን ያልተወ ሊያገለግለኝ አይችልም" (ማቴ 10፥37) የሚለውን የጌታችንን አምላካዊ ቃል ሰምተው ከቤተሰቦቻቸው ተለይተው ወጥተው በመሄድ ቀበት በምትባል ቦታ በዓት ሠርተው በጾም በጸሎት እየታደሉ መኖር ጀመሩ፡፡ በዚህም ጊዜ እግዚአብሔር ያገለግላቸው ዘንድ አንዱን ነብር አዘዘላቸው፡፡ ሰዎችም ከአባታችን በረከትን ለመቀበል ወደ እርሳቸው ይመጡ ነበርና ከዕለታትም በአንደኛው ቀን አንድ ምእመን ወደ አባታችን በመጣ ጊዜ አባታችንን የሚያገለግላቸው ነብር ሰውየውን ዘሎ ያዘው፡፡ ሰውየውም ‹‹አባታችን አድኑኝ›› እያለ ሲጮኽ አቡነ ገብረ ማርያም ከበዓታቸው ወጥተው ነብሩን በመስቀላቸው ቢባርኩት ኃይሉ ደክሞና ለቃላቸው ታዝዞ ሰውየውን ለቀቀው፡፡ አባታችንም ያንን ወጣት ያየውን ነገር ለማንም እንዳይነግር አዘዙት፡፡ አቡነ ገብረ ማርያም እንደ ሊቀ ነቢያት 40 ቀንና 40 ሌሊት እህል ሳይበሉ ውኃ ሳይጠጡ እየጾሙ ወንጌላትን ያነቡ ነበር፡፡ ከመጾማቸውም ብዛት ሰውነታቸው ፍጹም በደከመና አንደበታቸውም መናገር በሳናቸው ሰዓት የብርሃን እናቱ እመቤታችን ተገልጻላቸው ‹‹ወዳጄ ገብረ ማርያም ሆይ ይህን ያህል ገድል የምትጋደል ሰውነትህንስ የምትታስጨንቃት ለምንድነው?›› በማለት አጸናቻቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ረሀብና ጥሙ ጠፋላቸው፡፡

🔴#ስንክሳር መስከረም_13 #ቅዱስ_ባስልዮስ_ዘቂሣርያ አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም ዐሥራ ሦስት በዚህች ቀን ታላቅና ቅዱስ የሆነ የቂሣርያ ሊቀ ጳጳሳት ባስልዮስ ላደረገው ተአምር መታሰቢያ ሆነ። ይህም እንዲህ ነው አንድ ጐልማሳ አገልጋይ የጌታውን ልጅ ስለወደዳት ልቡ እርሷን ወዶ እንደ እሳት እስከ ነደደ ድረስ እርሷንም ከመውደዱ ብዛት የተነሣ ወደ አንድ ከሀዲ ሥራየኛ ሔደ። ሥራየኛውም የክህደት ደብዳቤ ጽፎ ሰጠው። ወደ አረሚ መቃብርም ሒዶ በመንፈቀ ሌሊት ደብዳቤዋን ይዞ ወደላይ እጁን አንሥቶ በዚያ እንዲቆም አዘዘው። ይህም አገልጋይ ይህን ነገር ተቀብሎ ያ መሠርይ እንዳዘዘው አደረገ። በዚያንም ጊዜ ከሰይጣናት አንዱ መጥቶ ወደ አለቃቸው ወስዶ አደረሰው ያቺንም የክህደት ደብዳቤ ከእጁ ወሰደ። እንዲህም ብሎ ጠየቀው "ንጉሥህ ክርስቶስን ትክደ*ዋለህን? ፈቃድህን ከፈጸምኩልህ በኋላ ወደእርሱ አትመለስምን?" ይህም ጐስቋላ ባሪያ "አዎን ጌታዬ ያዘዝከኝን ሁሉ አደርጋለሁ" አለው። መስሐቲ ዲያብሎስም ይህን ልታደርግ በእጅህ ደብዳቤ ጻፍልኝ አለው። እርሱም በከበረ ደሙ የዋጀውን የክብር ባለቤት ክርስቶስን ክዶ በደብዳቤ ውስጥ የክህደቱን ቃል ጻፈለት። በዚያንም ጊዜ ሰይጣን በጌታው ልጅ ልብ ውስጥ የፍትወት እሳትን አነደደ ይህንንም ባሪያ እጅግ ወደደችው ከእርሱም መታገሥ አልተቻላትም። ወደ አባቷ በመጮህ በግልጥ ከዕገሌ ባሪያህ ጋር ካላጋባኸኝ አለዚያ ራሴን እገድላለሁ ትለዋለች እንጂ መታገሥ አልተቻላትም። አባትና እናቷም ፈጽሞ አዘኑ በምንም በምን ሊያስታግሥዋት አልቻሉም። የዚያም አገልጋይ ፍቅሩ በየዕለቱ በልቧ ይጨመር ነበር እንጂ። ስለዚህም ራሷን እንዳትገድል አባቷ ፈራ ለዚያ ባሪያ ሰጠው። እርሱም የጌታውን ልጅ ተቀብሎ ወደቤቱ አስገባት። ከርሷ ጋር ያለውን ፍላጎቱንም ፈጸመ። ከእርሱም ጋር ረጅም ጊዜ ከኖረች በኋላ አባትና እናቷም ይቅር ብሎ ኀዘናቸውን ከላያቸው ያርቅላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ኀዘንንና ልቅሶን አብዝተው ነበር። ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ ጩኸታቸውን ሰማ ልመናቸውንም ተቀብሎ ይህ የወደደችው አገልጋይ ጐልማሳ ክርስቲያን እንዳልሆነ አስገነዘባት ከእርሷ ጋር በነበረበት በዚህ በረጅም ዘመን አንዲት ቀን እንኳ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲሔድ ሥጋውንና ደሙንም ሲቀበል ወይም አዳኝ በሆነ በመስቀል ምልክት ራሱን ሲአማትብ እርሷ አላየችውም። ስለእምነቱም ጠየቀችው ግን አልገለጠላትም እርሷም እንዲህ አለችው "አንተ ክርስቲያን ከሆንክ ና በአንድነት ወደ ቤተ ክርስቲያን እንሒድና በፊቴ ቅዱስ ቊርባንን ተቀበል።" እንዲህም በአስገደደችው ጊዜ ስለርሷ ያደረገውን ሁሉ ወደ ሥራየኛ እንደሔደም በሰይጣንም አምኖ እምነቱንም በክርታስ ጽፎ ያንን ክርታስ ለሰይጣን እንደ ሰጠው ነገራት። ይህንንም ነገር ከእርሱ በሰማች ጊዜ ደነገጠች መሪር ልቅሶንም አለቀሰች ራሷንም በማወዛወዝ እጅግ ተጸጽታ አዘነች። ያን ጊዜም ፈጥና ተነሣች የቤተ ክርስቲያን ምሰሶ ወደሆነው ወደ ሀገርዋ ሊቀ ጳጳሳት ወደ ቅዱስ ባስልዮስ ሔደች ከእግሩ በታችም ወድቃ ሰገደችለት በላይዋ የደረሰውን ሁሉ አስረዳችው ለሰው ልጆች ጠላት ከሆነ ከሠይጣን እጅ ፈጽሞ ያድናት ዘንድ ብዙ በማልቀስ ለመነችው። ቅዱስ ባስልዮስም ባሏ የሆነውን ባርያ ወደርሱ ልኮ አስመጣውና ጠየቀው እርሱም የሠራውን ሁሉ አስረዳው ቅዱስ ባስልዮስም "ተመልሰህ ክርስቲያን ልትሆን ከሰይጣንም እጅ ልትድን ትወዳለህን?" አለው ያም ባርያ "ጌታዬ ይሆንልኛልን?" አለ ይህ ቅዱስ አባትም የፈጣሪህን ስም እየጠራህ ልብህን አጽና አለው። ከዚህም በኋላ ከእርሱ ዘንድ በአንድ ቦታ ዘጋበት በመስቀል ምልከትም አማተበበት እንዲጸልይም አዘዘው ራሱ ቅዱስ ባስልዮስም ስለርሱ ጸለየ። ከሦስት ቀኖች በኋላም ጎበኘው እንዲህም አለው በእሊህ በሦስት ቀኖች የደረሰብህ ምንድን ነው እርሱም በላዩ በመጮህ ሠይጣናት ሲያስፈራሩት ያንንም ደብዳቤ ሲአሳዩትና በእርሱ ላይ ሲቆጡ በመከራ ውስጥ እንደኖረ ነገረው ቅዱስ ባስልዮስም ከእሳቸው ቁጣ የተነሣ አትፍራ እግዚአብሔር ይረዳሃልና አጽንቶም ይጠብቅሃል አለው። ከዚህም በኋላ ጥቂት እንጀራና ውኃ ሰጥቶ ወደ ቦታው መለሰው ቅዱስ ባስልዮስም ስለዚያ አገልጋይ ሒዶ ይጸልይ ጀመረ። ዳግመኛም ከሦስት ቀኖች በኋላ ጐበኘውና በእርሱ ላይ ምን እንደ ደረሰበት ጠየቀው ያ አገልጋይም ጩኸታቸውን እሰማለሁ ግን አላያቸውም ብሎ መለሰለት። እንጀራና ውኃም ሰጠውና መከረው ወደ ቦታውም መለሰውና ስለርሱ ሊጸልይ ቅዱስ ባስልዮስ ሔደ። እስከ አርባ ቀኖች ፍጻሜ ድረስ እንዲህ አደረገ። በአርባውም ቀን ፍጻሜ ከእርሱ ስለ ሆነው ጠየቀው ያ አገልጋይም እንዲህ አለው ቅዱስ አባቴ ሆይ ስለ እኔ ሰይጣንን ስትጣላውና ድል አድርገህ ጥለህ ስትረግጠው በዛሬዋ ሌሊት አየሁ አለው። ቅዱስ ባስልዮስም ይህን ነገር ከእርሱ በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ አለው የገዳማቱን መነኰሳትና ካህናቱንም ጠርቶ ስለዚያ ሰው ያቺን ሌሊት መላዋን እንዲጸልዩባት አዘዛቸ። በነጋ ጊዜም ያንን አገልጋይ ወደ ቤተክርስቲያን እንዲአመጡት የዚያችንም አገር ሕዝብ ሁሉንም ሰብስቦ እጆቻቸውን ወደ ሰማይ አንሥተው አቤቱ ክርስቶስ ማረን ይቅር በለን እያሉ ወደ እግዚአብሔር ፈጽሞ እንዲማልዱ አዘዛቸው እንዳዘዛቸውም አደረጉ። እንዲህም እያሉ ሲማልዱ ያ ሰው ጽፎ ለሰይጣን የሰጠው የክህደት ደብዳቤ ከሰይጣን እጅ በሕዝቡ ሁሉ ፊት ወደቀ ሁሉም ደስ ብሏቸው ምስጉን እግዚአብሔርን አመሰገኑት የከበረ አባት ባስልዮስም ባረካቸው ሥጋውንና ደሙንም አቀብሎ ወደ ቤቶቻቸው በሰላም በፍቅር አሰናበታቸው ። እነርሱም ስለ ኃጢአታቸው ስርየትና ስለ ድኅነታቸው ፈጽሞ ደስ እያላቸው እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ይህንን ቅዱስ አባት ባስልዮስን እያከበሩ ወደ ቤታቸው ገቡ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ አባት ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መስከረም_12 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም ዐሥራ ሁለት መላእክት አለቃ #የቅዱስ_ሚካኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው፣ #ጉባኤ_ኤፌሶን የቅዱሳን የሁለት መቶ ኤጲስቆጶሳት ስብሰባ ሆነ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ሚካኤል_ሊቀ_መላእክት መስከረም ዐሥራ ሁለት በዚች ቀን የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው። በዚችም ቀን ክብር ይግባውና እግዚአብሔር ወደ አሞጽ ልጅ ወደ ነቢይ ኢሳይያስ ላከው ይቅርም ብሎት ወደ ይሁዳ ንጉሥ ወደ ሕዝቅያስ ሒዶ እግዚአብሔር ይቅር እንዳለውና ከደዌው እንዳዳነው በዕድሜውም ላይ ዐሥራ አምስት ዓመት እንደ ጨመረለት ይነግረው ዘንድ አዘዘው። ንጉሱም ሚስት አግብቶ ምናሴን እስከወለደው ድረስ እንዲሁ ሆነ። ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ለንጉሥ ሕዝቅያስ ያደረገለት ተአምር፡- ከጻድቁ ንጉሥ ከቅዱስ ዳዊት በኋላ በእስራኤል እንደ ሕዝቅያስ ያለ ሌላ ጻድቅ ንጉሥ አልተነሣም፡፡ ከሕዝቅያስ በኋላ የተነሡት ሁሉም ጣዖትን አምልከዋል፣ ለጣዖታቱም የሚሆን መሠዊያ ሠርተዋል፡፡ ንጉሡ ሕዝቅያስ በነገሠ ጊዜ ግን ጣዖታትን ሰባብሯቸዋል፣ የእስራኤል ልጆች ያመልኩት የነበረውን የነሐስ እባብ ቆራርጦታል፡፡ እግዚአብሔርንም በማመኑ መንግሥቱ እጅግ ሰምሮለታል፡፡ እግዚአብሔርም ያሳጣው በጎ ነገርም የለም፡፡ ሕዝቅያስ በነገሠ በ14ኛው ዘመን የፋርሱ ነጉሥ ሰናክሬም መጥቶ ኢየሩሳሌምን ከበባት፡፡ ይህም ሰናክሬም በወቅቱ እንደ እርሱ ያለ ኃይለኛ የለም ነበርና ሁሉም የምድር ነገሥታት ይፈሩትና ይገዙለት ነበር፡፡ ሕዝቅያስም ከሰናክሬም ግርማና የጦሩ ብዛት የተነሣ ፈርቶ ኢየሩሳሌምን እንዳያጠፋት ብዙ ወርቅና ብር እጅ መንሻ ቢልክለትም ሰናክሬም ግን እጅ መንሻውን አልቀበልም ብሎ ኢየሩሳሌምን ያጠፋ ዘንድ ተነሣ፡፡ ለሕዝቅያስም ‹‹አምላካችሁ እግዚአብሔር ከእኔ እጅ ሊያደናችሁ ከቶ አይችልም›› የሚል የስድብን ቃል ላከለት፡፡ ሁለተኛም በልዑል እግዚአብሔር ላይ የስድብን ቃል ጽፎ ደብዳቤ ላከለት፡፡ ሕዝቅያስም ይህን ሲሰማ ወደ እግዚአብሔር ቤት ገብቶ አለቀሰ፡፡ ልብሱንም ቀዶ ማቅ በመልበስ የሰናክሬምን ድፍረትና በኢየሩሳሌምና በሕዝቧ ላይ ሊያደርስ ያሰበውንም ጥፋት ወደ እግዚአብሔር አሳሰበ፡፡ ቀጥሎም ሕዝቅያስ ሰናክሬም የተናገረውን ይነግሩት ዘንድ ስለ ሕዝቡም እንዲጸልይ ለነቢዩ ኢሳይያስ መልእክት ላከበት፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስም ወደ እግዚአብሔር አመለከተ፡፡ ከዚህም በኋላ ቅዱስ ሚካኤል ስለ ንጉሡ ለነቢዩ መልእክትን አመጣለት፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስም የመጣለትን መልስ እንዲህ ብሎ ለሕዝቅያስ ላከለት፡- ‹‹ልብህን አጽና፣ አትፍራ፡፡ በዓለሙ ሁሉ እንደ እርሱ ያለ ያልተሰማ ዕፁብ ድንቅ የሆነ ሥራ በሰናክሬም ላይ እግዚአብሔር ይሠራል›› አለው፡፡ ከዚህም በኋላ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ መጥቶ 185,000 (መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ) የፋርስ ሠራዊቶችን በአንድ ሌሊት ገደላቸው፡፡ 2ኛ ነገ 17፣19፡፡ የለኪሶ ሰዎችም ሲነጋ በተነሡ ጊዜ ምድሪቱን በእሬሳ ተሞልታ ስላገኟት በድንጋጤና በፍርሃት ከንጉሣ ጋር ሸሽተው ነነዌ አገር ገቡ፡፡ ንጉሡ ሰናክሬምም ወደ አምላኩ ወደ ጣዖቱ ቤት ገብቶ ሲጸልይ የገዛ ልጆቹ በሰይፍ መትተው ገደሉትና ወደ አራራት ኩበለሉ፡፡2ኛ ነገ ምዕራፍ 19፡፡ ንጉሥ ሕዝቅያስም ከሰናክሬም እጅ ያዳነውን እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡ ከዚህም በኋላ ሕዝቅያስ ታሞ ለሞት በደረሰ ጊዜ ነቢዩ ኢሳይያስ ወደ እርሱ መጥቶ ‹‹እግዚአብሔር ‹ትሞታለህ እንጂ አትድንም› ብሎሃል›› አለው፡፡ ነገር ግን ሕዝቅያስ አሁንም ልብሱንም ቀዶ ማቅ በመልበስ ጸሎቱን ወደ እግዚአብሔር አቀረበ፡፡ በዚህ ጊዜ ነው ቅዱስ ሚካኤል እግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ መጥቶ ነቢዩ ኢሳይያስን ወደ ንጉሡ ሕዝቅያስ ሄዶ በዕድሜው ላይ 15 ዓመት እንደተጨመረለት እንዲነግረው ያዘዘው፡፡ መልአኩ እንዳዘዘው ነቢዩ ኢሳይያስ ንጉሥ ሕዝቅያስን "እግዚአብሔር የአባትህ የዳዊት አምላክ ጸሎትህን ሰማሁ፣ ዕንባህንም አየሁ፣ እነሆ እኔ አድንሃለሁ፡፡ በዘመኖችህም 15 ዓመት ጨምሬልሃለሁ፡፡ ከፋርስ ንጉሥ እጅም አድንሃለሁ፡፡ ይህችን አገር ስለ እኔና ስለ ባለሟሌ ዳዊት አጽንቼ እጠብቃታለሁ›› ብሎሃል ብሎ የተላከውን ነገረው፡፡ ከዚህም በኃላ ንጉሥ ሕዝቅያስ የእግዚአብሔር ኃይል ስላደረበት የምድር ነገሥታት ሁሉ ፈርተውት እየተገዙለት እጅ መንሻን ያገቡለት ጀመር፡፡ ንጉሡም ዕድሜው ከተጨመረለት በኃላ ሚስት አግብቶ ምናሴን እስኪወልድ ድረስ ቆየ፡፡ በመንበረ መንግሥቱም 29 ዓመት ነግሦ ከኖረ በኋላ እግዚአብሔርን አገልግሎ በሰላም ዐረፈ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ጉባኤ_ኤፌሶን በዚችም ቀን ደግሞ በኤፌሶን ከተማ የቅዱሳን የሁለት መቶ ኤጲስቆጶሳት ስብሰባ ሆነ ይህም ለታላላቆች ጉባኤያት ሦስተኛ ነው። ስብሰባቸውም የተደረገው የታላቁ ቴዎዶስዮስ ልጅ አርቃድዮስ የወለደው ታናሹ ቴዎዶስዮስ በነገሠ በሃያ ዓመት ነው። የስብሰባቸውም ምክንያት የቊስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳሳት በሆነ በንስጡር ነው። እርሱ ስቶ እንዲህ ብሏልና እመቤታችን ድንግል ማርያም አምላክን በሥጋ አልወለደችውም እርሷ ዕሩቅ ሰውን ወልዳ ከዚህ በኋላ በውስጡ የእግዚአብሔር ልጅ አደረበት ከሥጋ ጋር በመዋሐድ አንድ አልሆነም በፈቃድ አደረበት እንጂ። ስለዚህም ክርስቶስ ሁለት ጠባይ ሁለት ባህርይ አሉት የተረገመ የከ*ሐዲ ንስጡር የከፋች ሃይማኖቱ ይቺ ናት። ስለ እርሱም የተሰበሰቡ እሊህ አባቶች ከእርሱ ጋር ተከራከሩ ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው አምላክ እንደሆነ ገብርኤል መልአክ በአበሠራት ጊዜ ከተናገረው ቃል ምስክር አመጡ። እንዲህ የሚል እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ነው ከአንቺ የሚወለደውም ጽኑዕ ከሀሊ ነው የልዑል እግዚአብሔር ልጅም ይባላል ። ዳግመኛም እነሆ ድንግል በድንግልና ፀንሳ ወንድ ልጅን ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች ብሎ በትንቢቱ ከተናገረው ከኢሳይያስ ቃል ሁለተኛም ከእሴይ ዘር ይተካል ከእርሱም ለአሕዛብ ተስፋቸው ይሆናል። ዳግመኛም የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ ቄርሎስ ገሠጸው መከረው ስለዚህም እንዲህ ሲል አስረዳው ክብር ይግባውና የክርስቶስ የመለኮቱና የትስብእቱ ባሕርያት በመዋሐድ አንድ ከሆኑ በኋላ አይለያዩም አንድ ባሕርይ በመሆን ጸንተው ይኖራሉ እንዲህም አምነን ሰው የሆነ እግዚአብሔር ቃል አንዲት ባሕርይ ነው እንላለን። ከ*ሀዲ ንስጥሮስ ግን ከክፉ ሐሳቡ አልተመለሰም ከሹመቱም ሽረው እንደሚአሳድዱትም ነገሩት። እርሱ ግን የጉባኤውን አንድነት አልሰማም ስለዚህም ከሹመቱ ሽረው ረግ*መው ከቤተ ክርስቲያን ለይተው አሳደ*ዱት ወደ ላይኛውም ግብጽ ሒዶ በዚያ ምላሱ ተጎልጒሎ እንደ ውሻ እያለከለከ በክፉ አሟሟት ሞተ። እሊህም ሁለት መቶ ኤጲስቆጶሳት አባቶች ሃይማኖትን አጸኑዋት በዚህም ጉባኤ ውስጥ እንዲህ ብለው ጻፉ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከእርሷ ሰው የሆነውን የእግዚአብሔርን አካላዊ ቃል በሥጋ ወለደችው። ከዚህም በኋላ ሥርዓትን ሠርተው ሕግንም አግገው በእጆቻቸው ጽፈው ለምእመናን ሰጡ። እኛም የሕይወትንና የድኅነትን መንገድ ይመራን ዘንድ እግዚአብሔርን እንለምነው። ለእርሱም ክብር ምስጋና ይሁን ለዘላለሙ አሜን። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበረ መልአክ በቅዱስ ሚካኤል እንዲሁም በከበሩ ቅዱሳን አማላጅነት ይማረን ለዘላለሙ አሜን ።https://t.me/finotebirhan12